Administrator

Administrator

የሰዓሊ ግዛቸው ከበደ 20 የሚደርሱ የስዕል ሥራዎች ለዕይታ የሚቀርቡበት ኤግዚቢሽን በትላንትናው ዕለት ምሽት ከገርጂ መብራት ኃይል ወደ ሳሊተ ምህረት በሚወስደው መንገድ፣ ከሮቤራ ካፌ ጀርባ፣ በማላንጋ የስዕል ጋለሪ ተከፈተ፡፡ ኤግዚቢሽኑ ለተመልካች ክፍት የሚሆነው ዘወትር ቅዳሜና እሁድ፣ ለአራት ተከታታይ ሳምንታት ነው ተብሏል፡፡ ሰዓሊው የአሁኑን ጨምሮ በ50 የስዕል ኤግዚቢሽኖች ላይ (በግልና በቡድን) ሥራዎቹን እንዳቀረበ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ሰዓሊና ቀራጺ ግዛቸው ከበደ፤ ከዚህ ቀደም ዘመን ባንክ በር ላይ የቆመውንና በአሜሪካ የስቶክ ገበያ ተምሳሌት የሆነውን  የበሬ ኮርማ (bull) ፣ከፊትለፊቱ  በኦዳ ታወር ላይ ያለውን ሞሳይክ መስራቱ የሚታወቅ ሲሆን ስቴዲየም በሚገኘው የኦሮምያ ባህል ማዕከል ባለ ሁለት አውታረ መጠን ቅርጾችንም ሰርቷል፡፡   

 የዶ/ር ሙሉዓለም ተገኘወርቅ  የግጥም ሥራዎች በሙዚቃ ተቀናብረው የቀረቡበት  “የአመጻ ገጾች” የተሰኘ የግጥም ሲዲ የፊታችን አርብ በዋቢሸበሌ ሆቴል ትልቁ አዳራሽ ከምሽቱ 11፡30 ጀምሮ እንደሚመረቅ ተገለጸ፡፡
ዶ/ር ሙሉዓለም ተገኘወርቅ የህክምና ባለሙያ ሲሆኑ ከአ.አ  ዩኒቨርሲቲ በቲያትር ጥበባት ት/ቤት በ Visual and Performing Art  በእጅግ   ከፍተኛ ማዕረግ ተጨማሪ ድግሪያቸውን ሠርተዋል፡፡ በአሁኑ  ወቅት የኢትዮጵያ የጥርስ ህክምና ባለሙያዎች ማህበርን በፕሬዝዳንትነት እያገለገሉ ይገኛሉ ፡፡
ዶ/ር ሙሉዓለም ከዚህ ቀደም በ2001 ዓ.ም “‹‹ኡ…..ኡ››” የሚል የግጥም መድበል ያሳተሙ ሲሆን የተለያዩ የመድረክ ትያትሮችን በመፃፍ፣ በመተወን እንዲሁም በማስታወቂያና ድራማዎች ላይ በመስራት ላይ  እንደሚገኙ ለማወቅ ተችሏል፡፡  

   ባለፈው ረቡዕ “ያልታየው ተውኔት” የተሰኘ የግጥም ሲዲውን በሒልተን ሆቴል ያስመረቀው ገጣሚ ደምሰው  መርሻ፤ የግጥም ባለውለታ ያላቸውን ሁለት ተቋማትና አራት ግለሰቦች የክብር ዋንጫ በመሸለም ምስጋናውን አቀረበ፡፡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሥነጽሁፍ መምህሩ ዶ/ር ፈቃደ አዘዘና ገጣሚና ጸሃፌ-ተውኔት አያልነህ ሙላቱ ምስጋናው ከቀረበላቸው መካከል ይጠቀሳሉ፡፡
የግጥም ሲዲውን መርቀው የከፈቱት የቀድሞ ኢምፔሪያል ሆቴል ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ አቶ ጸጋዬ፤ ለግጥምና ሥነጽሁፍ ፕሮግራሞች ለረዥም ጊዜያት አዳራሽ በነጻ በመፍቀድ ላደረጉት በጎ አስተዋጽኦ የምስጋና ዋንጫ የተበረከተላቸው ሲሆን ሸበሌ ሆቴል ግጥም በጃዝ ሲጀመር አዳራሹን ለመስጠት ሳይሳሳ ለጥበብ ላሳየው ቸርነት፣ አዲስ አድማስ ጋዜጣ ደግሞ ለግጥም ዕድገት በተለያዩ መንገዶች ለተጫወተው ሚና  የምስጋና ዋንጫ ተሸልመዋል፡፡
ገጣሚና ጸሃፌ-ተውኔት አያልነህ ሙላቱ፤ ለወጣት ገጣሚያን የፑሽኪን አዳራሽን በመፍቀድ ተሰጥኦዋቸውን የሚያወጡበት ዕድል በመስጠታቸው፣ ዶ/ር ፈቃደ አዘዘ እንዲሁ ለጀማሪ ገጣሚያን መንገድና አቅጣጫ በማመላከት ላበረከቱት ጉልህ ድርሻ የምስጋና ዋንጫው የተበረከተላቸው ሲሆን እስክንድር ሃይሉም ለገጣሚያን የመድረክ ንባብ ክፍያ ባልተለመደበት ጊዜ ገንዘብ በመክፈል ለጥበቡ ክብር ሰጥቷል በሚል ከገጣሚው የምስጋና ሽልማቱን አግኝቷል፡፡
ገጣሚ ደምሰው መርሻ ምስጋናውን ለማቅረብ ምን እንዳነሳሳው ለአዲስ አድማስ ሲገልጽ፤ “ለእኔ የግጥም ህይወት እዚህ መድረስ የየራሳቸውን ድርሻ አበርክተዋል የምላቸውንና ለግጥሙም ክብርና ማዕረግ መቀዳጀት ተግተዋል ብዬ ያሰብኳቸውን ለማመስገን በማሰብና ዕውቅና ሊሰጣቸው ይገባል በሚል ግላዊ እምነቴ ነው” ብሏል፡፡ ምስጋናውና ዕውቅናው ከተበረከተላቸው ግለሰቦች መካከል አንዳንዶቹ በሰጡት አስተያየት፤ በገጣሚው አርአያነት ያለው ተግባር መደመማቸውን ገልጸው ምስጋና እና ዕውቅና ለሚገባው ሁሉ መስጠት ሊዳብር የሚገባው ባህል ነው ብለዋል፡፡  

 ገንዘቤ ዲባባ
በ1500፤ በ3ሺ እና በ5ሺ ሜትር የዓለም የቤት ውስጥ ውድድሮች ሶስት ሪከርዶች ይዛለች፡፡
በ5ሺ ሜትር በኦልአትሌቲክስ የውጤት ደረጃ በ1365 ነጥብ አንደኛ ናት፡፡
2015 ከገባ በአሜሪካ የ5ኪሜ የጎዳና ላይ ሩጫ፤ በ5ሺ ሜትር የቤት ውስጥ ውድድር ስቶክሆልም ላይ እንዲሁም በ5ሺ ሜትር በዩጂን የዳይመንድ ሊግ ውድድር አሸንፋለች፡፡

                   ዮሚፍ ቀጀልቻ
17 ዓመቱ  ነው፡፡
በ5ሺ ሜትር 12.58 39 ፈጣን የግሉን ሰዓት አስመዝግቧል፡፡
በ2013 በዓለም ወጣቶች ሻምፒዮና በ3ሺ ወርቅ፤ በ2014 በቻይና የኒንግ በተካሄደው የወጣቶች ኦሎምፒክ በ3ሺ ወርቅ እንዲሁም በ2015 በአፍሪካ የአትሌቲክስ ሻምፒዮና በአዲስ አበባ በ5ሺ የወርቅ ሜዳልያ አግኝቷል፡፡ በ1317 ነጥብ 2ኛ ነው፡
በ2015 በ3ሺ ሜትር በኳታር ዶሃ እንዲሁም በ5ሺ በጣልያን ሮም ሁለት የዳይመንድ ሊግ ውድድሮች አሸንፏል፡፡

                    ሙክታር ኢድሪስ
በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና በወጣቶች ውድድር የቡድን የብር ሜዳልያ በ2011 እኤአ ላ ካገኘ በኋላ በተመሳሳይ ዓመት በአፍሪካ ወጣቶች አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ10ሺ ሜትር አራተኛ ደረጃ ነበረው፡፡ በ2012 እኤአ ላይ ደግሞ በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና በወጣቶች ውድድር የወርቅ ሜዳልያ ያገኘ ሲሆን በዓለም ወጣቶች አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ በ5ሺ ሜትር የወርቅ ሜዳልያም ተጎናፅፏል፡፡
በኦልአትሌቲክስ የአትሌቶች የውጤት ደረጃ በ5ሺ ሜትር 1315 ነጥብ በማስመዝገብ 3ኛ ደረጃ ላይ ነው፡፡

                     ገለቴ ቡርቃ
በዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ1500 ሜትር በ2008 እኤአ ላይ በሻሌንሽያ የወርቅአንዲሁም በ2010 በኳታር ዶሃ የነሐስ ሜዳልያ ያገኘች ሲሆን በ2012 እኤአ ላይ ኢስታንቡል ላይ በ3ሺ ሜትር የነሐስ ሜዳልያ ተጎናፅፋለች፡፡ ለሁለት ጊዜያት በዓለም አትሌቲክስ ውድድሮች ፍፃሜ የብር ሜዳልያ፤ በኦል አፍሪካን ጌምስ እና በአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ሁለት የወርቅ ሜዳልያዎች በ1500 አግኝታለች፡፡
በኦልአትሌቲክስ የውድድር ውጤት ደረጃ በ10ሺ ሜትር በ1210 ነጥብ ከዓለም ሁለተኛ ደረጃ ላይ ናት፡፡

                       አልማዝ አያና
ከሁለት አመት  በፊት  በ14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ5ሺ የነሐስ ሜዳልያ፤ በ2014 ደግሞ በማራኬሽ በርቀቱ የአፍሪካ ሻምፒዮን በመሆን የወርቅ ሜዳልያ ተጎናፅፋለች፡፡
በ5ሺ ሜትር በኦልአትሌቲክስ የውጤት ደረጃ በ1323  ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ አላት
በ2015 በሻንጋይ ዳይመንድ ሊግ ስታሸንፍ፤ ከሳምንት በፊት በሞሮኮ በ3ሺ ሜትርም አንደኛ ሆናለች፡፡


      ከ2 ወራት በኋላ በቻይናዋ ቤጂንግ ከተማ በሚካሄደው 15ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ  አዳዲስ ክዋክብት ልትጠብቅ ነው፡፡ ከ7 ዓመታት በፊት ኦሎምፒክን ባስተናግደውና እስከ 54ሺ ተመልካች  በሚይዘው የቤጂንጉ ምርጥ ስታድዬም bird nest  የወፍ ጎጆ በሚካሄደው ሻምፒዮና፤ ከ203 የዓለም አቀፉ አትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር አባል አገራት በመወከል 2567 አትሌቶች እንደሚገኙበት መገለፁ በውድድሩ ታሪክ በሪከርድነት የሚመዘገብ የተሳትፎ ብዛት ይሆናል፡፡   
በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች ከፍተኛ ውጤት ያላቸው ትልልቅ የኢትዮጵያ አትሌቶች በተለያዩ ምክንያቶች ላይገኙበት ይችላሉ፡፡ በውድድር ዘመኑ የልጆች እናት የሆኑት በ10ሺ ሜትር የወቅቱ  ሻምፒዮን ጥሩነሽ ዲባባና  በ5ሺ ሜትር የወቅቱ ሻምፒዮን መሰረት ደፋር ከአራስነት ተነስተው ለሻምፒዮናው የሚደርሱበት ሁኔታ የለም፡፡ ከ2 አመት በፊት  በ14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ሞስኮ ላይ ሁለቱ አትሌቶች በ10ሺ እና በ5ሺ ሜትር ያስመዘገቡትን ክብር የሚያስጠብቁላቸው አዳዲስ ክዋክብቱ ናቸው። በ10ሺ ወንዶች ከ2 አመት በፊት የተነጠቀውን ክብር ለማስመለስም ቀነኒሳ በቀለ፤ ስለሺ ስህንና እና ሌሎችም ልምድ ካላቸው አትሌቶች በዓለም ሻምፒዮናው አይሰለፉም፡፡
በ15ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ኢትዮጵያ ልምድ ባላቸው አትሌቶች የምትወከለው ምናልባት በማራቶን ውድድሮች ላይ ይሆናል፡፡ በተጨማሪ  በ800 ሜትር የወቅቱ የዓለም ሻምፒዮን መሃመድ አማን ብቻ ክብሩን ለማስጠበቅ ተሳታፊ ይሆናል፡፡ በኦልአትሌቲክስ የአትሌቶች ውጤት ደረጃ  በ800 ሜ በ1334 ነጥብ 2ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው መሐመድ፤ 2015 ከገባ በኋላ በፈረንሳይ በልዩ 1ሺ ሜትር ሩጫ ከማሸነፉም በላይ  በሮም በተካሄደ  የዳይመንድ ሊግ ውድድር በ800 ሜትር አሸንፏል፡፡
በሻምፒዮናው አዳዲስ ክዋክብት እንደሚሆኑ ከሚጠበቁት መካከል በዳይመንድ ሊግ በ5ሺ ሜትር አስደናቂ ውጤት ላይ የሚገኙት ገንዘቤ ዲባባና አልማዝ አያና እንዲሁም በ1500 የትራክ ውድድር ከፍተኛ ልምድ ያላትና በ10ሺ ሜትር የምትገባው ገለቴ ቡርቃ በሴቶች በኩል ይጠቀሳሉ፡፡ በወንዶች ደግሞ ሐጎስ ገብረህይወት፤ ዮሚፍ ቀጀልቻ እና ሙክታር ኢድሪስ ናቸው፡፡
አይ.ኤ.ኤ.ኤፍ ለዓለም ሻምፒዮናው ሚኒማ ለማምጣት የሰጠው ጊዜ አምስት ሳምንታት ይቀሩታል። ከሁለት ዓመት በፊት ተደርጎ በነበረው በየውድድር መደቡ ሻምፒዮን የሆኑት፤ የ2014 የዳይመንድ ሊግ ያሸነፉት በቀጥታ ያለ ሚኒማ ተሳትፎ ማግኘት ይችላሉ፡፡ያለፈው የዓለም ሻምፒዮኖች እና የዳይመንድ ሊግ አሸናፊ አትሌቶች ያሏቸው አገራት ከዋናው የ3 አትሌት ኮታ በተጨማሪ በየውድድር መደቡ አራት አትሌቶች በዓለም ሻምፒዮናው እንዲያሳትፉ ፈቃድ አግኝተዋል፡፡
የተቀዛቀዘው 44ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና
44ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና  ከሰኔ 3 እስከ ሰኔ 7 ቀን በአዲስ አበባ ስታድዬም የተካሄደ ሲሆን ከ37 ክለቦች፣ ከሁለት ከተማ መስተዳድሮችና ከ7 ክልሎች የተውጣጡ 1 ሺህ 282 አትሌቶች ተሳትፈውበታል፡፡ በሻምፒዮናው የመከላከያ ክለብ በ460 ነጥብ አንደኛ ሆኖ አጠናቅቋል፡፡ የኦሮምያ ክልል በ316 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ሲወስድ የባንክ ክለብ በ135 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ በማግኘት ጨርሷል፡፡ ዘንድሮ ሻምፒዮናውን  የሚደግፉ ስፖንሰሮች አለመኖር ትልቅ ፈተናና ክፍተት እንደፈጠረበት ያሳወቀው ፌደሬሽኑ፤ ትልልቅ አትሌቶችን በተለያዩ ምክንያቶች እንዳያሳትፍ መገደዱ መጠነኛ መቀዛቀዝ  እንደተፈጠረበት አመልክቷል፡፡ ባለፉት ዓመታት ሻምፒዮናዎች በቁሳቁስና በገንዘብ ደረጃ ለተወዳዳሪዎች ድጋፍ ሲያቀርብ የቆየው አገር በቀሉ ኩባንያ ጋራድ ሲሆን  ኩባንያው የዘንድሮውን ሻምፒዮና ስፖንሰር እንደማያደርግ ከገለፀ በኋላ ፌደሬሽኑ ሌላ ስፖንሰር ማግኘት አልቻለም። በሌላ በኩል ታዋቂ አትሌቶች በዓለም ዓቀፍ  የዲያመንድ ሊግ፣ የማራቶን ውድድሮች ላይ ለመካፈል ወደ ተለያዩ አገራት በመሄዳቸው ያልተሳተፉበት ሲሆን ሁኔታው የሻምፒዮናውን የፉክክር ደረጃ እንደቀነሰውና  የተመልካቹን ድባብ መቀዛቀዝ እንዳመጣ ተገልጿል፡፡
በሻምፒዮናው በ400፤ 800፤ 1500 ሜትር የመካከለኛ ርቀት ውድድሮች የኢትዮጵያ ተስፋ ሊሆኑ የሚችሉ በርካታ ወጣት አትሌቶች ታይተዋል፡፡  አትሌቶቹ በመስከረም ወር በዲሪ ኮንጎ በሚዘጋጀው የመላው አፍሪካ ጨዋታዎች ተሳታፊ የሚሆነው የኢትዮጵያ ቡድን አካል ይሆናሉ፡፡ ፌደሬሽኑ በሻምፒዮናው  ለ2008 የውድድር ዓመት ብሔራዊ አትሌቶችን ለመምረጥ ታሳቢ ያደረገ ቢሆንም ሌሎች ዘርፈ ብዙ ውጤቶችን ያገኘበት ሆናል፡፡ በአትሌቲክስ ሻምፒዮናው በክልሎች፣ በከተማ አስተዳድሮች፣ በክለቦችና በማሠልጠኛ ማዕከላት ለሚገኙ አትሌቶች የውድድር ዕድል ለመፍጠር፤ ተተኪ አትሌቶችን ለማፍራት፤ ለብሔራዊ አትሌቲክስ ስልጠና አትሌቶችን ለመምረጥ፤ አመቺ መድረክ ሆኖለታል። በዘንድሮው የ44ኛው አትሌቲክስ ሻምፒዮና አስር ያህል አዲስ ክብረወሰኖች ሲመዘገቡ ጉኑ ሲሆን ብዙዎቹ ክብረወሰኖች በሜዳ ላይ ስፖርቶች የተገኙ ናቸው ተብሏል፡፡ በውርወራ ስፖርት በአሎሎ፣ በዲስከስና መዶሻ፣ በከፍታ ዝላይ፣ በዱላ ቅብብል  እንዲሁም በአጭር ርቀት የመሰናክል ሩጫ የተሻሻሉ ክብረወሰኖች ወደፊት አገሪቱ በአህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ የውድድር መድረኮች ከረጅም ርቀት እና ከመካከለኛ ርቀት ባሻገር ሊኖራት የሚችለውን ተሳትፎ የሚያነቃቃ ሆኗል፡፡
ለ10ሺ ሚኒማ በሄንግሎ
በ15ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ10 ሺህ ሜትር ኢትዮጵያን በመወከል የሚሳተፉ አትሌቶችን ለመለየት የማጣርያ ውድድር የተደረገው ባለፈው ሐሙስ በሆላንዷ ከተማ ሄንግሎ ነበር፡፡ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኑ ሄንግሎ ላይ ለ10ሺ ሜትር ሚኒማ ማግኛ የማጣርያ ውድድር  ለአትሌቶች ሲያዘጋጅ የዘንድሮው ለሶስትኛ ጊዜ ነው፡፡ 28 ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በሁለቱም ጾታዎች የማጣሪያ ውድድሩን ሲሳተፉበት አትሌቲክስ ፌደሬሽኑ በውድድሩ ከአንድ እስከ ሶስተኛ የወጡ አትሌቶች በዓለም ሻምፒዮና በዚሁ ርቀት እንዲሳተፉ ከመወሰኑም በላይ ከአራተኛ እስከ ስድስተኛ የወጡ አትሌቶች ደግሞ በኮንጎ ብራዛቪል በሚካሄደው የመላው አፍሪካ ጨዋታዎች ላይ እንዲሳተፉ ያደርጋል፡፡
በሄንግሎው የዓለም ሻምፒዮና የ10ሺ ሜትር ሚኒማ ለማምጣት በተደረገው የማጣርያ ውድድር በሴቶች ምድብ የመካከለኛ ርቀት ሯጯ ገለቴ ቡርቃ የዓመቱን ፈጣን ሰዓት በ30 ደቂቃዎች ከ53.69 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ አስመዝግባ አሸንፋለች፡፡ በመካከለኛ ርቀት ከፍተኛ ልምድ ያላት ገለቴ ቡርቃ በርቀቱ ገና ለሁለተኛ ጊዜ መወዳደሯ ነበር፡፡  በ2012 እኤአ በለንደን ኦሎምፒክ ላይ በ5ሺ ሜትር ተሳትፋ የነበረችው ገለቴ ቡርቃ አምስተኛ ደረጃ ነበር ያገኘችው፡፡ በተለያዩ ዓለም አቀፍ ውድድሮች በ1500 እና በ3000 ሜትር እና በአገር አቋራጭ ሻምፒዮና ላይ ከፍተኛ ልምድ ያላት ቢሆንም ኢትዮጵያን በመወከል በ10ሺ ሜትር በዓለም ሻምፒዮና ስትሳተፍ ለመጀመርያ ጊዜ ይሆንላታል፡፡ በሄንግሎ የ10ሺ ማጣርያ ለመጀመርያ ጊዜ ርቀቱን በትራክ ላይ የሮጠችው አለሚቱ ሃሮዬ በ30 ደቂቃዎች ከ50.83 ሰከንዶች ሁለተኛ እንዲሁም በርቀቱ ከ2 ዓመት በፊት የነሐስ ሜዳልያ ያገኘችው በላይነሽ ኦልጅራ በ30 ደቂቃዎች ከ53.69 ሰከንዶች በማስመዝገብ የቤጂንግ ቲኬታቸውን ቆርጠዋል፡፡
በወንዶች ደግሞ በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና የነሐስ ሜዳልያ ተሸላሚ የነበረው ሙክታር ኢድሪስ በሩጫ ዘመኑ ለሁለተኛ ጊዜ በሮጠው የ10ሺ ሜትር ውድድር የግሉን ፈጣን ሰዓት በ27 ደቂቃዎች ከ17.18 ሰከንዶች በማስመዝገብ ሊያሸንፍ በቅቷል፡፡ በ2011 እኤአ ላይ በርቀቱ የዓለም ሻምፒዮን የነበረውና ከ2 ዓመት በፊት ሞስኮ ላይ በርቀቱ የብር ሜዳልያ አግኝቶ የነበረው ኢብራሂም ጄይላን ውድድሩን አቋርጦ ወጥቷል፡፡ ባለፉት ሶስት የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች ኢትዮጵያን ወክሎ የተሳተፈው እና በ2011 እኤአ ላይ የብር ሜዳልያ የወሰደው ኢማና መርጋ በ27 ደቂቃዎች ከ17.63 ሰከንዶች እንዲሁም ሞሰነት ገረመው በ27 ደቂቃዎች ከ18.86 ሰከንዶች በማስመዝገብ በሁለተኛ እና በሶስተኛ ደረጃ የዓለም ሻምፒዮና ትኬታቸውን ቆርጠዋል፡፡
ለማራቶን  ጊዜያዊ ቡድን በማራቶን
የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን በቤጂንጉ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ በማራቶን ውድድር የሚሳተፉ አትሌቶችን ከሁለት ወር በፊት በመምረጥ ጊዜያዊ ዝርዝሩን ይፋ አድርጓል፡፡ የማራቶን ቡድኑ በሁለቱም ፆታዎች 9 አትሌቶችን የያዘ ሲሆን የቦስተን ማራቶን አሸናፊው እና ከሁለት ዓመት በፊት በዓለም ሻምፒዮና የብር ሜዳልያ የወሰደው ሌሊሳ ዴሲሳ እና የለንደን ማራቶን አሸናፊዋ ትዕግስት ቱፋ ይገኙበታል፡፡ በወንዶች ሌሎቹ አትሌቶች የማነ አዳነ፤ እንደሻው ንጉሴ፤ ጥላሁን ረጋሳ እና ለሚ ብርሃኑ ሲሆኑ በሴቶች ደግሞ ማሬ ዲባባ፤ ትርፌ ፀጋዬ፤ ትግስት ቱፋ እና ብርሃኔ ዲባባ ናቸው፡፡

 ኢትዮጵያ ከኬኒያ ወደ 4ኛውን የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ (ቻን) ለማለፍ በመጀመርያ ዙር ማጣሪያ ጨዋታ በባህርዳር ስታዲየም ይገናኛሉ፡፡ ቻን የአፍሪካ ክለቦች የሊግ ውድድሮች የሚፈተሹበት፤ ከአገራቸው ወጥተው ለመጫወት ያልቻሉ እና የፕሮፌሽናል ተስፋ ያላቸው የሚታዩበት፤ የውድድሩ አዘጋጅ ለአፍሪካ ዋንጫ መስተንግዶ ያለውን ብቃት የሚለካበት አህጉራዊ ሻምፒዮና ነው፡፡ በመጀመርያ ዙር ማጣርያው ከኢትዮጵያ እና ኬንያ ጥሎ የሚያልፈው ከጅቡቲ እና ብሩንዲ አሸናፊ ጋር ለመጨረሻው ማጣርያ ይገናኛል፡፡
በአትሌቲክሱ ዓለም የቅርብ ተቃናቃኞች የሆኑት ኢትዮጵያ እና ኬንያ በእግር ኳስም የረጅም ጊዜ ተፎካካሪዎች ናቸው፡፡ ነገ ባህርዳር ላይ በአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ የመጀመርያ ዙር ማጣርያ የሚገናኙት ለ35ኛ ጊዜ ይሆናል፡፡ ሁለቱ  ቡድኖች በታሪክ በሁሉም አህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ ግጥሚያዎች በድምሩ 34 ጊዜ ተገናኝተዋል፡፡ ኢትዮጵያ 14 ስታሸንፍ፤ ኬንያ 12 አሸንፋ በስምንት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል፡፡  
ባለፈው ሳምንት በተጀመረው የ31ኛው አፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣርያ የመጀመርያ ጨዋታቸው ኢትዮጵያ በሜዳዋ 2ለ1 በሆነ ውጤት ሌሶቶን አሸንፋለች፡፡ ኬንያ ደግሞ ከሜዳዋ ውጭ ከኮንጎ  ጋር አንድ እኩል አቻ ተለያይታለች፡፡
በመጀመርያ የነጥብ ጨዋታቸው ድል የቀናቸው አሰልጣኝ ዮሃንስ ሳህሌ  ስለቡድናቸው በሰጡት አስተያየት ‹‹በጣም ጥሩ አጀማመር ነው፡፡ ወደ ጋቦን ለምናደርገው ጉዞ በሩን ከፍተናል ማለት ይቻላል፡፡ ከኋላ ተነስተው ማሸነፋቸው ልጆቼ ከፍተኛ የማሸነፍ ስነልቦና እና ቁርጠኝነት እንዳላቸው አረጋግጦልኛል›› ብለዋል። በአፍሪካ ዋንጫው የምድብ 10 ሌላ ጨዋታ አልጄርያ ሲሸልስን 4ለ0 አሸንፋለች፡፡ ምድቡን አልጄርያ በ3 ነጥብ እና በአራት ግብ ክፍያ ስትመራ ኢትዮጵያ በእኩል 3 ነጥብ እና 1 የግብ ክፍያ ሁለተኛ ሆና ጀምራለች፡፡ ሌሴቶ በባዶ ነጥብ እና 1 የግብ እዳ ሶስተኛ እንዲሁም ሲሸልስ በ4 የግብ እዳ 3ኛ እና 4ኛ ደረጃ ላይ ናቸው፡፡
ከኢትዮጵያ ጋር ለሚደረገው ጨዋታ 20 ምርጥ የኬንያ ፕሪሚዬር ሊግ ተጨዋቾችን 2 ቀን ሰርተው  ትናንት ገብተዋል፡፡ ከተጨዋቾች ስብስቡ በአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያው ከኮንጎ ጋር 1ለ1 ከተለያየው ቡድን 10 ይገኙበታል ከኤፍሲ ሊዮፓርድስ  ከማታሬ ዩናይትድ ከታስከር ኤፊሲ ክለቦችም ተካትተዋል፡፡ በተለይ ለጎሮማሃያ ክለብ የሚጫወተው ግብ ጠባቂው ቦኒፌስ ኦሉዉች እና በአጥቂ መስመር የሚጫወተው እና በኬንያ ፕሪሚዬር ሊግ ኮከብ ግብ አግቢነት ተፎካካሪ በሆነው አሊ አቦንዶ ብዙ እንደሚጠበቅ ዘገባዎች ጠቁመዋል፡፡
የኬንያ ቡድን የቀድሞ አሰልጣኞች የሃራምቤ ኮከቦች ለአፍሪካ ዋንጨጫ እና ለቻን ውድድር በሚያልፉበት ብቃት ፍፁም እምነታቸውን አየገለፁ ናቸው፡፡ ስኮትላንዳዊው ቦቢ ዊልያምሰን፤ በአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያው ከኮንጎ ጋር ባደረጉት ጨዋታ አቻ መለያየታቸውን አድንቀው በምናደርጋቸው የማጣርያ ውድድሮች በተለይ በሜዳችን በጭራሽ መሸነፍ የለብንም ብለዋል፡፡  አሰልጣኝ ቦቢ  ኬንያ ጎረቤቷን ኢትዮጵያ ጥላ በማለፍ ለቻን ውድድር እንደምታልፍ ከፍተኛ እምነት እንዳላቸው በተደጋጋሚ ተናግረዋል፡፡ የኬንያ ፕሪሚዬር ሊግ በዞኑ እና በአፍሪካ ደረጃ ምርጥ መሆኑን ማስመስከር የሚችለው ከኢትዮጵያ ጋር የሚያደርገው ጥሎ ማለፍ በድል በመወጣት ነው ብለው ኢትዮጵያዎች ኳስን ተቆጣጥሮ የመጫወት ብቃት አላቸው ስለዚህም ከሜዳችን ውጭ ስንገጥማቸው ኳስ እንዳይዙ ማድረግ ስትራቴጂን እንከተላለን ሲሉ ተናግረዋል፡፡

በመገበያያ ገንዘቧ ዶላር ላይ የታዋቂ መሪዎቿን ምስል የምታወጣው አሜሪካ፣ በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ የሴት ምስል ለማውጣት መወሰኗን ዘ ቴሌግራፍ ከትናንት በስቲያ ዘገበ፡፡ የአሜሪካ የገንዘብ ተቋም እንዳስታወቀው፣ በአገሪቱ የ10 ዶላር ኖት ላይ የአንዲትን ታላቅ አሜሪካዊት ሴት ምስል ለማውጣት ውሳኔ ላይ የተደረሰ ቢሆንም፣ በዶላሩ ላይ የምትወጣዋ ሴት ማን ናት የሚለው ግን ገና አልታወቀም፡፡
ከዚህ በፊት በአሜሪካ የ10 ዶላር ኖት ላይ የነበረው ምስል የአሌክሳንደር ሃሚልተን እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ የአገሪቱ የትሬዠሪ ጸሃፊ ጃክ ሊው በጉዳዩ ዙሪያ ከህዝብ ጋር ከመከሩና በድረገጽ አማካይነት የሚሰጠውን ጥቆማ ከገመገሙ በኋላ በኖቱ ላይ ምስሏ የሚወጣላትን ሴት እንደሚመርጡ አስታውቋል፡፡
አዲሱ ዶላር ከአምስት አመታት በኋላ በሚከናወነውና የአገሪቱ ሴቶች የመምረጥ መብታቸውን የተጎናጸፉበትን 100ኛ አመት ለመዘከር በሚዘጋጅ ስነስርዓት ላይ ይፋ እንደሚሆንም ይጠበቃል፡፡
በአገሪቱ የመገበያያ ገንዘብ ላይ ምስሏ የሚወጣላትን ሴት በተመለከተ ዘገባው ባስቀመጠው ግምት፣ ሴቶችን ከባርነት በማውጣት ታሪክ የሰራችው ሃሬት ቱብማን፣ የቀድሞው ፕሬዚዳንት ፍራንክሊን ሩዝቬልት ባለቤት ኤሊኖር ሩዝቬልት፣ የጥቁሮች መብት ተሟጋቿ ሮዛ ፓርክስ፣ ቼሮኬን ለ10 አመታት ያህል ያስተዳደሩት ዊልማ ማኒከርን ጠቅሷል፡፡

አምና የተመዘገበው ዝናብ በ30 አመታት ዝቅተኛው ነው
   ሰሜን ኮርያ ባለፉት መቶ አመታት ገጥሟት በማያውቅና የከፋ የምግብ እጥረቷን በከፍተኛ ሁኔታ በማማባስ ወደ ቀውስ ያስገባታል ተብሎ በተሰጋለት ድርቅ መመታቷን ስካይ ኒውስ ዘገበ፡፡ የአገሪቱን የዜና ወኪል ኬሲኤንኤን ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፤ ህዋንጌና ፓዮንጋን የተባሉትን ዋነኞቹ የሰሜን ኮርያ ሩዝ አብቃይ ግዛቶች ጨምሮ በመላ አገሪቱ የሚገኙ የሩዝ ሰብሎች በዝናብ እጥረት ሳቢያ በቡቃያው አርረዋል፡፡ አገሪቱ በክፍለ ዘመኑ የከፋ ባለችው ድርቅ መመታቷንና በግብርና እንቅስቃሴዋ ላይ ከፍተኛ ጥፋት መድረሱን ያስታወቀች ሲሆን፣ ድርቁ ተመድ ከአምስት አመት ዕድሜ በታች ከሚገኙ ሶስት ህጻናት አንዱ በተመጣጠነ ምግብ እጥረት ሳቢያ የመቀጨጭ ችግር ተጠቂ እንደሆነ ባረጋገጠባት ሰሜን ኮርያ ላይ የከፋ ጥፋት ያስከትላል ተብሎ እንደሚሰጋ ጠቁሟል፡፡  
ባለፉት 30 አመታት የአገሪቱ ታሪክ ዝቅተኛ የተባለው የዝናብ መጠን ባለፈው አመት መመዝገቡ፣ ለድርቁ መከሰት በምክንያትነት የተጠቀሰ ሲሆን፣ ሩዝ በቂ ውሃ ካላገኘ በአግባቡ ማደግ አለመቻሉና የዝናብ እጥረቱ መቀጠሉ አደጋውን የከፋ እንደሚያደርገው ይጠበቃል ተብሏል፡፡ የአገሪቱ አርሶ አደሮች የውሃ ፓምፖችን በመጠቀም ሰብሎቻቸውን ውሃ እንዲያጠጡና ከጥፋት እንዲታደጉ የሚያበረታታ አገር አቀፍ ዘመቻ መጀመሩም ታውቋል፡፡

  በድረ-ገጾች ላይ የሚጫነው መረጃ መጠን ከሶስት አመታት በፊት ከነበረው በእጥፍ ያህል መጨመሩን ተከትሎ፣ የድረ-ገጾች ፍጥነት በአለማቀፍ ደረጃ መቀነሱንና ድረ-ገጾችን ለመክፈት የሚፈጀው አማካይ ጊዜ መጨመሩን ሲኤን ኤን ዘገበ፡፡
በአሁኑ ወቅት አንድ ድረ-ገጽ ሳይት የሚይዘው አማካይ የመረጃ መጠን 2.1 ሜጋ ባይት ደርሷል ያለው ኤችቲቲፒ፣ ለድረ-ገጾች ፍጥነት መቀነስ በምክንያትነት ከተጠቀሱት መካከል ቪዲዮዎች፣ ስዕሎችና ድህንነትን ለማስጠበቅ በሚል የሚጫኑ ሌሎች መረጃዎች መብዛታቸውና የመረጃ ዝውውሮች መጨናነቃቸው ይገኙበታል፡፡
ስማርት ፎኖችና ታብሌቶች በስፋት ለኢንተርኔት አገልግሎት መዋላቸውም ለድረ-ገጾች ፍጥነት መቀነስ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ዘገባው ጠቁሞ፣ ምንም እንኳን ፍጥነቱ የቀነሰው በሰከንዶች እድሜ ቢሆንም፣ እያንዳንዷ ማይክሮ ሰከንድ ትልቅ ዋጋ በያዘችበት በዚህ የመረጃና የፈጣን የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ዘመን ጉዳዩ አሳሳቢ ነው የሚል አስተያየት መሰጠቱን አስታውቋል፡፡
የኢንተርኔት ተጠቃሚነት በአለማቀፍ ደረጃ እያደገ መምጣቱን ተከትሎ የኔትወርክ መጨናነቅ መፈጠሩ፣ የብራውዘሮች አይነትና አቅም መለያየትም ለችግሩ መከሰት በምክንያትነት ተጠቅሰዋል፡፡

- በቀን ከ42 ሺህ በላይ ሰዎች ይሰደዳሉ
- ባለፈው አመት 60 ሚ. ያህል ሰዎች ተሰደዋል፤ ግማሽ ያህሉ ህጻናት ናቸው
- በግጭት ሳቢያ የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር በ350 በመቶ አድጓል
- አይስላንድ የአለማችን ሰላማዊ አገር ናት

       ባለፈው የፈረንጆች አመት 2014 ብቻ በዓለማችን የተለያዩ አገራት ለተደረጉ ጦርነቶችና የእርስ በርስ ግጭቶች ከ14 ትሪሊዮን ዶላር በላይ ወጪ መደረጉን ዘ ቴሌግራፍ ዘገበ፡፡
ኢንስቲትዩት ፎር ኢኮኖሚክስ ኤንድ ፒስ የተባለው አለማቀፍ ተቋም ያወጣውን ሪፖርት ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ባለፈው አመት ለጦርነትና ለእርስ በርስ ግጭት የወጣው አጠቃላይ ወጪ፣ ከዓለማችን አጠቃላይ የአገር ውስጥ ምርት 13 በመቶ እንደሚሆንና የእንግሊዝ፣ የፈረንሳይ፣ የጀርመን፣ የካናዳ፣ የስፔንና የብራዚል ኢኮኖሚ በአንድ ላይ ተደምሮ አይደርስበትም፡፡
አለማችን ግጭትን በ10 በመቶ መቀነስ ከቻለች ለጦርነትና ለእርስ በርስ ግጭት ከሚወጣው ገንዘብ 1.43 ትሪሊዮን  ዶላር ማዳን ትችላለች ብለዋል የኢንስቲትዩቱ ዋና ስራ አስፈጻሚ ስቲቭ ኪሌላ፡፡ ሰሞኑን ይፋ የተደረገው አለማቀፍ የሰላም ሁኔታ አመልካች ሪፖርት በበኩሉ፣ በ2015 የግጭት መናኸሪያ በመሆንና በአደገኛ ሁኔታ ውስጥ በመገኘት ረገድ የአለማችን ግንባር ቀደም አገር ሶሪያ መሆኗንና ኢራቅና አፍጋኒስታን እንደሚከተሏት አስታውቋል፡፡
በአመቱ የሰላም ሁኔታዋ በከፍተኛ ሁኔታ የቀነሰባት አገር ሊቢያ ናት ያለው ሪፖርቱ፣ የእርስበርስ ግጭት ከተነሳበት ጊዜ አንስቶ 6ሺ ያህል ዜጎች የሞቱባትንና 1 ሚሊዮን ህዝብ የተፈናቀለባትን ዩክሬን በሁለተኛነት አስቀምጧታል፡፡ በአለማችን በግጭቶች ሳቢያ ለህልፈተ ህይወት የሚዳረጉ ሰዎች ቁጥር ባለፉት አራት አመታት ከ350 በመቶ በላይ አድጓል ያለው ሪፖርቱ፣  በ2010 ብቻ 49 ሺህ ሰዎች መሞታቸውንና ይህ ቁጥር በ2014 ወደ 180 ሺህ ከፍ ማለቱን ጠቁሟል፡፡ ይህም ሊሆን የቻለው በ2013 ከሽብርተኝነት ጋር በተያያዘ ለሞት የሚዳረጉ ሰዎች ቁጥር 61 በመቶ በማደጉ ነው ያለው ሪፖርቱ፤ በአመቱ ከሽብርተኝነት ጋር በተያያዘ የሞቱ ሰዎች ቁጥር 18ሺህ እንደነበርና አብዛኞቹ ሟቾችም በአፍጋኒስታን፣ ኢራቅ፣ ናይጀሪያ፣ ፓኪስታንና ሶሪያ የተገደሉ እንደሆኑ አስታውቋል፡፡
በአንጻሩ ደግሞ ሰላማዊ ሆና በመዝለቅ ቀዳሚዋ አህጉር ናት በተባለችው አውሮፓ የሚገኙት አይስላንድ እና ዴንማርክ የዓለማችን ሰላማዊ አገራት ተብለዋል በሪፖርቱ፡፡ ቢቢሲ በበኩሉ፤ የተባበሩት መንግስታት ድርጅትን መረጃ ጠቅሶ ከትናንት በስቲያ እንደዘገበው፣ በጦርነትና በእርስ በእርስ ግጭት  ሳቢያ የሚሰደዱ ሰዎች ቁጥር ታይቶ በማይታወቅበት ደረጃ ከፍ በማለት በ2014 60 ሚሊዮን ያህል ደርሷል፡፡ በየዕለቱ አገራቸውን ጥለው የሚሰደዱ ዜጎች ቁጥርም 42 ሺህ 500 ደርሷል፡፡
የተመድ የስደተኞች ኮሚሽን ያወጣው ሪፖርት እንደሚለው፣ የስደተኞች ቁጥር በ2013 ከነበረበት በ8.3 ሚሊዮን ያደገ ሲሆን ለስደተተኞች ቁጥር መጨመር ዋነኛ ምክንያት የተደረገውም ተባብሶ የቀጠለው የሶርያ ግጭት እንደሆነ ተረጋግጧል፡፡ ባለፉት አምስት አመታት 15 ያህል ግጭቶች መከሰታቸውን ወይም እንደገና ማገርሸታቸውን የጠቆመው ሪፖርቱ፣ ከእነዚህ መካከልም ስምንቱ በአፍሪካ፣ ሶስቱ ደግሞ በመካከለኛው ምስራቅ አገራት የተከሰቱ እንደሆኑ በመግለጽ፣ በዚህም እስከ 2014 መጨረሻ 59.5 ሚሊዮን ሰዎች ከመኖሪያቸው ተፈናቅለው ለስደት መዳረጋቸውንና ከእነዚህም ግማሽ ያህሉ ህጸናት መሆናቸውን አስታውቋል፡፡
ስደተኞቹ የአንድ ሃገር ህዝብ ቢሆኑ፣ አገሪቷ በአለማችን በህዝብ ቁጥር ብዛት 24ኛ ደረጃ ልትይዝ እንደምትችል አስታውቆ፤ 19.5 ሚሊዮን የሚሆኑ የተለያዩ አገራት ዜጎችም በስደተኞች መጠለያ ጣቢያዎች አስከፊ ኑሮ እንደሚገፉም አክሎ ገልጧል፡፡
በርካታ ዜጎች ከሚሰደዱባቸው የዓለማችን አገራት መካከል ቀዳሚዋ 4 ሚሊዮን ሰዎች የተሰደዱባት ሶርያ ስትሆን. አፍጋኒስታን በ3 ሚሊዮን፣ ሶማሊያ በሁለት ሚሊዮን ይከተላሉ፡፡ በሜዲትራንያን ባህር በኩል ወደተለያዩ የአውሮፓ አገራት የገቡ 1.8 ሚሊዮን ስደተኞች ጥገኝነት ለማግኘት ያቀረቡትን ጥያቄ ምላሽ እየተጠባበቁ እንደሚገኙና፣ ከእነዚህም መካከል ብዙዎቹ በጀርመንና በስዊድን እንደሚገኙም ሪፖርቱ ጠቁሟል፡

Saturday, 20 June 2015 11:11

የፀሐፍት ጥግ

ስለትወና)
ትወና፤ የሌሎችን ሰብዕና የመውሰድና የራስህን ጥቂት ተመክሮ የማከል ጉዳይ ነው።
ዣን ፖል ሳርተር
ተዋናይ ለመሆን ህንፃ መሆን አለብህ፡፡
ፖል ኒውማን
ትወና ስሜታዊነት አይደለም፤ ስሜትን በተሟላ መንገድ መግለፅ መቻል እንጂ፡፡
ቶማስ ሬይድ
ሥነ ጥበብ እጃችን፣ ጭንቅላታችንና ልባችን እንደ አንድ ሆነው የሚጣመሩበት ነው፡፡
ጆን ሩስኪን
ትወና ደስ የሚል ስቃይ ነው፡፡
ዣን ፖል ሳርተር
ትወና ከሞላ ጎደል ከጨዋታ በላይ አይደለም። ሃሳቡም ህይወትን ሰዋዊ ማድረግ ነው፡፡
ጄፍ ጎድልብሊም
የትወና ጥበብ ሰዎች እንዳያስሉ ማድረግንም ይጨምራል፡፡
ራልፍ ሪቻርድሰን
ትወና እወዳለሁ፤ ምክንያቱም ህልም እውን የሚሆንበት፣ ቅዠት ህይወት የሚዘራበትና የሚቻለው ነገር ሁሉ ገደብ የሌለበት በመሆኑ ነው፡፡
ጄሲካ አልባ
ራሴን ለፍቅረኛ እንደምሰጠው ነው ለገፀባህርያቶቼ የምሰጠው፡፡
ቫኔሳ ሬድግሬቭ
ተዋናይ ህይወትን መተርጎም አለበት፤ ያንን ለማድረግ ደግሞ ህይወት የምትሰጠውን ተመክሮ ሁሉ በፀጋ ለመቀበል ፈቃደኛ መሆን ይኖርበታል፡፡
ማርሎን ብራንዶ
ተዋናዮች ከህይወት በላይ መግዘፍ አለባቸው። በዕለት ተዕለት ህይወት ከብዙ ተራና እዚህ ግቡ የማይባሉ ሰዎች ጋር ትገናኛላችሁ፡፡ በመድረክም ላይ ከእነሱ ጋር የምትጋፉበት ምክንያት አይታየኝም፡፡
ኒኖን ዲ ሌንክሎስ
የታላቅ ተዋናይ መሰረታዊ ጉዳይ በትወና ውስጥ ራሱን መውደዱ ነው፡፡
ቻርሊ ቻፕሊን