Administrator

Administrator

  በተጠናቀቀው የፈረንጆች አመት 2016፣ በአለማችን የተለያዩ አገራት ከ100 በላይ ጋዜጠኞች መገደላቸውን ያስታወቀው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፤ በአመቱ በአማካይ በየአራት ቀኑ አንድ ጋዜጠኛ መገደሉን ገለጸ፡፡
በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ተቋም( ዩኔስኮ) በአለማቀፍ ደረጃ የተሰራን የጥናት ውጤት ጠቅሶ እንዳለው፣ በአመቱ በርካታ ጋዜጠኞች የተገደሉት በመካከለኛው ምስራቅ በሚገኙ የአረብ አገራት ሲሆን በርካታ ግድያዎች የተፈጸሙት በሶርያ፣ ኢራቅና የመን ነው፡፡ ምንም እንኳን የጋዜጠኞች ግድያ ካለፈው አመት ጋር ሲነጻጸር ዘንድሮ ቢቀንስም፣ በጋዜጠኞች ላይ የሚደረገው የመብት ጥሰትና ግድያ በአለማቀፍ ደረጃ እየተባባሰ ነው ያለው ተቋሙ፤ መንግስታት የጋዜጠኞችን ግድያዎች እንዲያጣሩ ጥሪ አቅርቧል፡፡
በፈረንጆች አመት 2015 በአለማችን የተለያዩ አገራት ስራቸውን በማከናወን ላይ ሳሉ የተገደሉ ጋዜጠኞች ቁጥር 115 እንደነበርም ተቋሙ አስታውሷል፡፡

  መኪናዋ ያለ አሽከርካሪ ራሷን ችላ የምትንቀሳቀስ ናት

      ታዋቂው የአውሮፕላን አምራች ኩባንያ ኤርባስ ግሩፕ፣ የተራቀቀ ቴክኖሎጂ ውጤት የሆነቺና ያለ አሽከርካሪ ራሷን ችላ የምትንቀሳቀስ በራሪ መኪና እየሰራ መሆኑን አስታውቆ፣ እስከ 2017 መጨረሻ የሙከራ በረራ ለማድረግ ማቀዱን ጠቁሟል፡፡
ኩባንያው ቫሃና የሚል ስያሜ የሰጣትንና አንድ ሰው ብቻ የማሳፈር አቅም እንዳላት የተነገረላትን በራሪ መኪና፣ እስከ አዲሱ የፈረንጆች አመት 2017 መጨረሻ ሰርቶ በማጠናቀቅ፣ የበረራ ሙከራ እንደሚያካሂድ ማስታወቁን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
ኤርባስ በአስር አመታት ጊዜ ውስጥም መሰል መኪናዎችን በብዛት በማምረት ለአለም ገበያ የማቅረብ እቅድ እንዳለው ማስታወቁን የጠቆመው ዘገባው፣ እንዲህ ያሉ በራሪ መኪኖች የትራፊክ መጨናነቅን እንደሚያቃልሉና ለመንገድና ለድልድዮች ግንባታ የሚውለውን በቢሊዮኖች ዶላር የሚቆጠር ገንዘብ እንደሚያድኑ መግለጹን አስረድቷል፡፡

  የ92 አመቱ የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጆርጅ ኤች ደብሊው ቡሽ ባጋጠማቸው የጤና እክል የህክምና እርዳታ ለማግኘት ካለፈው ሳምንት ቅዳሜ ጀምሮ ሂዩስተን በሚገኝ ሆስፒታል ውስጥ እንደሚገኙ ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
ቡሽ ከዚህ ቀደምም ለሁለት ጊዚያት ወደዚህ ሆስፒታል ገብተው የመተንፈሻ አካላት ህክምና እንደተደረገላቸው ያስታወሰው ዘገባው፣ በደህና ሁኔታ ላይ እንደሚገኙና ከቀናት በኋላ ህክምናቸውን ጨርሰው ይወጣሉ ተብሎ ከመጠበቁ ውጪ ወደ ሆስፒታል ያስገባቸው በሽታ ምን እንደሆነ አለመገለጹን አስረድቷል፡፡
አሜሪካን እ.ኤአ. ከ1989 እስከ 1993 ያስተዳደሩት 41ኛው የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ጆርጅ ኤች ደብሊው ቡሽ፣ በፓርኪንሰንስ ህመም ሳቢያ ራሳቸውን ችለው መንቀሳቀስ አቅቷቸው፣ በሰው ድጋፍና በተሽከርካሪ ወንበር ታግዘው መንቀሳቀስ ከጀመሩ አመታት እንዳለፏቸውም ዘገባው አብራርቷል፡፡
ቡሽ ትናንት በተካሄደው የዶናልድ ትራምፕ በዓለ ሲመት ላይ ለመገኘት ቀጠሮ ቢይዙም ሆስፒታል በመግባታቸው ሳቢያ በዝግጅቱ ላይ ሳይገኙ መቅረታቸው ተነግሯል፡፡

   20 በመቶ ጃፓናውያን ሰራተኞች ለሞት የሚያሰጋ ስራ ይሰራሉ

       የጃፓን መንግስት ዜጎቹ ከሚገባው በላይ ስራ በመስራት ለአደጋ እንዳይጋለጡ ለማድረግ በማሰብ፣ የትርፍ ስራ ሰዓት ገደብ የሚጥል ህግ ሊያወጣ ማቀዱን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
በርካታ የአገሪቱ ዜጎች ተጨማሪ ገቢ ለማግኘት በማሰብ፣ ከመደበኛው የስራ ሰዓታቸው በተጨማሪ የትርፍ ጊዜ ስራ በመስራት ብዙ ሰዓት ተጠምደው እንደሚውሉና እንደሚያድሩ የጠቆመው ዘገባው፤ከዚህ ጋር በተያያዘ ብዙዎች ለጤና ችግር ብሎም ለሞት እየተዳረጉ መሆኑ መንግስትን እንዳሳሰበው ገልጧል፡፡
20 በመቶ የሚሆነው የአገሪቱ ሰራተኛ ህዝብ ከሚገባው በላይ ስራ በመስራት ለሞት የመጋለጥ አደጋ አንዣቦበታል ያለው ዘገባው፤ አብዛኞቹም በወር ከ80 ሰዓታት በላይ የትርፍ ጊዜ ስራ እንደሚሰሩ ገልጧል፡፡ ይህንን ችግር ለመፍታት በሚልም የአገሪቱ መንግስት ከመጪው ወር ጀምሮ ተግባራዊ የሚደረግ የትርፍ ሰዓት የስራ ገደብ የሚያስቀምጥ ህግ ለማውጣት መወሰኑን ዘገባው አስረድቷል፡፡

Wednesday, 25 January 2017 07:22

የቢዝነስ ጥግ

 - ሁላችንም በአንድ ላይ ነው የምንሰራው፤ ያ ነው ምስጢሩ፡፡
      ሳም ዋልትን (የዎልማርት መስራች)
- ስኬቴ የሚመነጨው በየቀኑ በእጄ ያለውን ስራ ተግቼ ከመስራት ነው፡፡
     ጆኒ ካርሰን
- ለሰዎች የሚጠቅም ከሆነ፣ ለቢዝነስ ይጠቅማል፡፡
    ሊዎ ቡርኔ
- ሰዎች ሲወዱህ የምትለውን ይሰሙሃል፤ ሲያምኑህ ግን አብረውህ ቢዝነስ ይሰራሉ፡፡
    ዚግ ዚግላር
- ታላላቅ ኩባንያዎች የተገነቡት በታላላቅ ምርቶች ላይ ነው፡፡
    ኢሎን ሙስክ
- ስህተት የማይሰሩት የሚተኙ ሰዎች ብቻ ናቸው፡፡
   ኢንግቫር ካምፓርድ (የIKEA መስራች)
- ስሜ በሌለበት ህንፃ ውስጥ ፈፅሞ ኖሬ አላውቅም፡፡
    ኢቫንካ ትራምፕ
- ከሥራዬ በተባረርኩ በነጋታው አዲስ ኩባንያ ጀመርኩ፡፡
     ማይክል ብሉምበርግ
- ለቢዝነስህ ፍቅር ከሌለህ ልትሸጠው፣ ለሰው ልትሰጠው አሊያም ልትለውጠው ይገባል
- በማትወደው ቢዝነስ ውስጥ መዳከር የለብህም፡፡
      ቶኒ ሮቢንስ
- ራስህን ፈፅሞ እንደ አማካይ ሰው አትቁጠር።
     ጆርጅ ሉካስ
- ቢዝነስ አትገነባም፤ የምትገነባው ሰዎችን ነው፤ ከዚያም ሰዎች ቢዝነሱን ይገነባሉ፡፡
     ዶናልድ ትራምፕ (ቢሊዬነርና የአሜሪካ ፕሬዚዳንት)
- ተግቶ መስራት በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ በእጅጉ ተግተህ ካልሰራህ የትም አትደርስም
     ጆኢል ስፖልስኪ
- የምትሸጠው የማይጠቅመኝ ከሆነ፣ ለምን በሬን ትቆረቁራለህ፡፡
    ጆርጅ ሉካስ
- ቢዝነስ አትገነባም፤ የምትገነባው ሰዎችን ነው፤ ከዚያም ሰዎች ቢዝነሱን ይገነባሉ፡፡
     ዚግ ዚግላር
- ምርታችንን ሳናሻሽል የምናሳልፈው እያንዳንዱ ቀን የባከነ ቀን ነው፡፡
     ጆኢል ስፖልስኪ
- የምትሸጠው የማይጠቅመኝ ከሆነ፣ ለምን በሬን ትቆረቁራለህ፡፡
    ክሪስ ሙሬይ

Sunday, 22 January 2017 00:00

የፖለቲካ ጥግ

- ሰላም መፍጠር የምትሻ ከሆነ፣ ከወዳጆችህ ጋር ሳይሆን ከጠላቶችህ ጋር ትወያያለህ፡፡
    ሞሼ ዳያን
- እኔ መናገር ስፈልግ ማንም አይሰማኝም፤ እነሱ እንድናገር ሲሹ እኔ የምለው የለኝም፡፡
   ዊንስተን ቸርቺል
- የፖለቲካ ልዩነት ሁልጊዜ ጤናማ ውይይት ይፈጥራል፡፡ ከጊዜ በኋላ ግን ውይይቱ ይበልጥ በጥላቻ የተሞላና አልፎ አልፎም ሁከት ፈጣሪ ይሆናል፡፡
    ማርክ ዩዳል
- ምንም የምትለው ነገር ከሌለህ፣ ዝም በል፡፡
   ማርክ ትዌይን
- እንደ ብልህ አስብ፤ነገር ግን በህዝብ ቋንቋ ተግባባ፡፡
   ዊሊያም በትለር ይትስ
- ዲሞክራሲ ማለት በውይይት የሚመራ መንግስት ነው፡፡ ውጤታማ የሚሆነው ግን ሰዎችን ከንግግር መግታት ከቻልክ ነው፡፡
   ክሌሜንት አትሊ
- ፖለቲካዊ ትክክለኛነት ውይይትን ይገድለዋል፡፡
   ላርስ ቮን ትሪዬር
- ውይይት የዕውቀት ልውውጥ ሲሆን ክርክር የድንቁርና ልውውጥ ነው፡፡
    ሮበርት ኪውይሌ
- በውይይት ላይ የሳይንቲስቱ ዓላማ ማግባባት አይደለም፤ ማብራራት እንጂ፡፡
    ሊዎ ስዚላርድ

ታዋቂዋ የሆሊውድ የፊልም ተዋናይት አንጀሊና ጁሊ በ2007 ከኢትዮጵያ በጉዲፈቻ የወሰደቻት ዘሃራ ወላጅ እናት፤ ‹‹በህይወት አለሁ፤አንጀሊና ከልጄ ጋር እንድገናኝ  ትፍቀድልኝ›› በማለት መማፀኗ ተዘግቧል፡፡
አሁን የ12 ዓመት ታዳጊ የሆነችው ዘሃራ ወላጅ እናት፣ ወ/ት ምንትዋብ ዳዊት ሌቢሶ፤ ‹‹እባክሽን አንጀሊና፤ ልጄን እንዳነጋግራት ብቻ ፍቀጅልኝ›› ስትል በተማፅኖ መጠየቋን የእንግሊዙ “ዴይሊ ሜል ኦንላይን” ዘግቧል፡፡
በደቡብ ክልል ሾኔ ከተማ ከወላጅ እናቷ ጋር በዝቅተኛ ኑሮ ላይ የምትገኘው ወ/ት ምንትዋብ፤  ዘሃራን በ19 ዓመቷ በማታውቀው ሰው ተደፍራ መውለዷን፣ ጠቁማ፤ ከወሊድ በኋላ ለረዥም ጊዜ በመታመሟ በቤተሰቧ ግፊት ልጇን ለአሳዳጊ ድርጅት ለመስጠት መገደዷን ተናግራለች፡፡
‹‹ልጄን ላለፉት 12 አመታት በቀንም በሌት ሆነ ሳስባት የቀረሁበት ጊዜ የለም›› ያለችው ወላጅ እናቷ፤ ‹‹አሁን ግን የልጄን ናፍቆት መቋቋም አልቻልኩም፤ ልጄ ልክ እንደ አሳዳጊዋ  የምትወዳትና የምትሳሳለት ወላጅ እናት እንዳላት እንድታውቅ እፈልጋለሁ›› ብላለች ከዴይሊ ሜል ጋር ባደረገችው ቃለ ምልልስ፡፡
አንጀሊና ልጄን በማደጎነት ከወሰደቻት በኋላ ባሉት ጊዜያት ምንም ዓይነት ደብዳቤም ይሁን  መልዕክት አሊያም ገንዘብ ደርሶኝ አያውቅም›› ብላለች፤ የ31 ዓመቷ የዘሀራ ወላጅ እናት
‹‹እንዲያም ሆኖም ዘሃራ ወላጅ እናት እንዳላት እንድታውቅና እንድትጠይቀኝ ብቻ እንጂ ልጅቷን ከአንጀሊና ላይ የመውሰድ ፍላጎት የለኝም›› በማለት አስረድታለች፡፡
እውቋ የሆሊውድ ተዋናይት አንጀሊና ጁሊ፤ በ1997 ዓ.ም ዘሃራን ከኢትዮጵያ በጉዲፈቻ ለማሳደግ ስትወስዳት፣ ወላጆቿን በኤችአይቪ ያጣች ህፃን መሆኗ ተነግሯት እንደነበር ያስታወሰው ዴይሊ ሜል፤ ከ2 ዓመት በኋላ ግን ወላጅ እንዳላት መስማቷን ጠቁሟል፡፡

  የአልበሙ ሽያጭ ሙሉ ለሙሉ ለፌስቱላ ህሙማን ይውላል
    በሰርከስ ትግራይ ውስጥ ያደገው የወጣቱ ኢሳቅ ኪ/ማሪያም “ፍናን” የትግርኛ አልበም የፊታችን ሐሙስ ድምፃዊው ላለፉት ሰባት አመታት እየሰራበት ባለው ‹‹ክለብ ፍሪደም›› ይመረቃል፡፡ በቅርቡ ለገበያ የቀረበው አልበሙ 400 ሺህ ብር እንደወጣበት የገለፀው ድምፃዊ ኢሳቅ፤ የአልበሙ ሽያጭ ሙሉ ለሙሉ ለፌስቱላ ህሙማን እንደሚውል ለአዲስ አድማስ ተናግሯል፡፡ 12 የትግርኛ ዘፈኖችን ያካተተው ‹‹ፍናን›› 16 የሙዚቃ ባለሙያዎች የተሳተፉበት ሲሆን አልበሙን ሰርቶ ለማጠናቀቅ በርካታ አመታት ፈጅቷል ተብሏል፡፡ በቀጣይ በመቀሌና በአውሮፓ እንደሚመረቅ አስተባባሪው አቶ ተስፋዬ ገ/ዮሀንስ ገልጸዋል፡፡ የአልበሙ ስያሜ “ፍናን” የግዕዝ ቃል ሲሆን ሞራል (ወኔ) የሚል ፍቺ እንዳለው ተጠቁሟል፡፡

 ደራሲና ጋዜጠኛ ዩሱፍ ያሲን የፃፈውና በማንነት ጥያቄዎች ዙሪያ ያሉትን ውስብስብ ክርክሮች አሰባስቦ በመያዝ፣ መፍትሄዎችን ያመላክታል የተባለው ‹‹ኢትዮጵያዊነት፣ አሰባሳቢ ማንነት በአንድ አገር ልጅነት›› የተሰኘ መፅሃፍ ለንባብ በቃ፡፡ መፅሀፉ በተለይም የዛሬይቱ ኢትዮጵያ ከተጋረጠባት ውስብስብ የማንነት ጥያቄ አንፃር የሚያስጨንቁና መፍትሄ የሚሹ ጉዳዮች በጥልቀት የተተነተኑበት ነው ተብሏል፡፡ የመጽሀፉ የመጀመሪያ ዕትም በውጭ አገር ለገበያ የቀረበ አንደነበር የተገለፀ ሲሆን የያዘው ቁም ነገር በውጭ አገር ተገድቦ እንዳይቀርና ኢትዮጵያዊያን በስፋት እንዲያወያዩበት ታስቦ፣ ሁለተኛው እትም አገር ቤት መሰራጨቱም ታውቋል፡፡ በበርካታ ምዕራፎችና ንዑስ ምዕራፎች ተከፋፍሎ በ437 ገፆች የተቀነበበው፤ መፅሁፉ በ131 ብር ከ60 ሳንቲም ለገበያ ቀርቧል፡፡

 በክንፈ ባንቡ ተፅፎ የተዘጋጀውና የፍቅር ዘውግ ያለው ‹‹ፍሬ›› ፊልም ለዘንድሮው የታላቁ አፍሪካ ፊልም ፌስቲቫል (ፌስፓኮ) መታጨቱ ተገለፀ፡፡ አንጋፋዎቹ አርቲስት ፈለቀ የማር ውሃ አበበ፣ ራሄል ግርማና ኤማ ብዙነህ በመሪ ተዋናይነት የተሳተፉበት ይህ ፊልም፤ በፊስቲቫሉ እጩ በመሆኑ መደሰቱን ደራሲና ዳይሬክተሩ ገልጿል፡፡ በዘንድሮው የፌስፓኮ ፊልም ፌስቲቫል ላይ ከአንድ ሺህ በላይ ፊልሞች ለውድድር የቀረቡ ሲሆን ኢትዮጵያዊው ‹‹ፍሬ›› ፊልም ለፍጻሜ ከቀረቡት 20 ፊልሞች አንድ መሆኑ ታውቋል፡፡ በዚህ ፌስቲቫል ላይ የፕሮፌሰር ሃይሌ ገሪማ ‹‹ጤዛ›› ፊልም ከዚህ ቀደም እጩ እንደነበር የገለፀው ክንፈ ባንቡ፤ ‹‹ፍሬ›› ሁለተኛው ኢትዮጵያዊ የዘርፉ እጩ ፊልም መሆኑን ጠቁሟል፡፡
ከፌቡራሪ 25 እስከ ማርች 4, 2017 በሚካሄደው በዚህ ፌስቲቫል ላይ ለመሳተፍ የፊልሙ አዘጋጆችና ተዋንያን ወደ ቡኪናፋሶ እንደሚጓዙ ታውቋል፡፡