Administrator

Administrator

በ800 ሜትር ሳይሸነፍ 15 ወራት አልፈዋል
ዘንድሮ ለዳይመንድ ሊግ ድል ለሃትሪክ ተጠብቋል
አዲስ የዓለም ሪከርድ እንደሚያስመዘግብ ግምት ተሰጥቶታል

አትሌት መሃመድ አማን ባለፉት 15 ወራት በሮጠባቸው የ800 ውድድሮች አልተሸነፈም፡፡ ኢትዮጵያ በዓለም የአትሌቲክስ ስፖርት ላለፉት 30 ዓመታት በረጅም ርቀት ከፍተኛ ስኬት ያስመዘገቡ አትሌቶችን በማፍራት ትታወቅ ነበር፡፡ ባለፉት 5 ዓመታት ግን በ20 ዓመቱ የዓለማችን የመካከለኛ ርቀት ምርጥ ሯጭ  ኮርታለች፡፡ አትሌት መሃመድ የኢትዮጵያን የአትሌቲክስ ዝና በአዲስ ምዕራፍ ቀይሶታል፡፡
ዘንድሮ በዳይመንድ ሊግ ውድድሮች ላይ ምርጥ ብቃት ያሳያሉ ተብለው ከተጠበቁ ምርጥ አትሌቶች አንዱ የሆነው መሃመድ በዚህ የውድድር ዘመን የ800 ሜትር የዓለም ሪከርድን ሊሰብር እንደሚችል በመገመትም ላይ ነው፡፡  በእርግጥም በርቀት አይነቱ  የዓለም ንጉስ ለመባል የሚቀረው ሪከርዱን መስበር ብቻ ነው፡፡ አንዳንድ የአትሌቲክስ ባለሙያዎች አትሌቱ አሁን በያዘው ብቃት ከቀጠለ ዘንድሮ ባይሳካለት እንኳን በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት በዓለም አቀፍ ውድድሮች የሚኖሩት ልምዶች የዓለም ሪከርድን የሚያሻሽልበት ብቃት ላይ እንደሚያደርሱት እየመሰከሩ ናቸው፡፡ ከሁለት ሳምንት በፊት የ2014  የዳይመንድ ሊግ ውድድር በኳታር ዶሃ ሲጀመር አንፀባራቂ ከነበሩ አትሌቶች ዋናው የነበረው አትሌት መሃመድ አማን፤ በወቅቱ በ800 ሜትር ውድድር ሲያሸንፍ ያሳየው አስደናቂ የአጨራረስ ብቃት ከፍተኛ አድናቆት አጉርፎለታል፡፡ እንደውም አንዳንድ ዘገባዎች ‹‹ሱፕር አትሌት›› ብለው አግንነውታል፡፡ ይሁንና አትሌቱ ከ2013 አጋማሽ ጀምሮ በተሳተፈባቸው የ800 ሜትር ውድድሮች ሳይሸነፍ ለመቆየቱ በቂ ምክንያት በማቅረብ የሚከራከሩ አልጠፉም፡፡ በእነዚህ ተከራካሪዎች መሃመድ አማን የሚቀናቀነው የጠፋው በተለይ የርቀቱ ሁለት ምርጥ አትሌቶች ጋር ባለመገናኘቱ ነው የሚል ማስረጃ ይቀርባል፡፡ በ2012 እኤአ ላይ ለንደን ኦሎምፒክ ላይ የዓለምን ሪከርድ ያስመዘገበው የ25 ዓመቱ ኬንያዊው ዴቪድ ሩዲሻ በጉዳት ከውድድር ከራቀ ሁለት ዓመት አልፎታል፡፡ ሌላው ምርጥ አትሌት እና በእድሜው እኩያው የሆነው ደግሞ የቦትስዋናው ኒጄል አሞስ ሲሆን እሱም በጉዳት ከውድድር እንደራቀ ነው፡፡
በዓለም አትሌቲክስ ዘንድሮ በከፍተኛ ጉጉት ከሚጠበቁ ትንቅንቆች ዋንኛው መሃመድ አማን ፤ ኒጄል አሞስ እና ዴቪድ ሩዲሻ የሚገናኙበት የ800 ሜትር  ፍጥጫ እንደሆነ ይገለፃል፡፡ ሶስቱ አትሌቶች በዳይመንድ ሊግ መገናኘታቸው እየተጠበቀ ሲሆን በተለይ ከሳምንት በኋላ በአሜሪካዋ ከተማ ዩጂን፤ የሚደረገው የፕሮፎንታይኔ ክላሲክስ ላይ ከተገናኙ አስገራሚ ፉክክር እንደሚኖራቸው   ተገምቷል፡፡ የ800 ሜትር የዓለም ሪከርድ በዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር በኦፊሴላዊ ደረጃ መመዝገብ የተጀመረው በ1952 እኤአ ነው፡፡ የመጀመርያው ሪከርድ በአሜሪካዊው አትሌት ቴድ ሜሪንዴዝ በ1.51 ደቂቃዎች የተመዘገበ ሲሆን ከዚሁ ሪኮርድ በኋላ 24 ጊዜ ሰዓቱ ሲሻሻል በርካታ እንግሊዛዊያንና አሜካዊያን አስተዋኝኦ ነበራቸው፡፡ ከ2008 ጀምሮ የተመዘገቡ ሦስት ሪኮርዶችን ማስመዝገብ የቻለው ኬንያዊው ዴቪድ ሩዲሻ ሲሆን የወቅቱ ሪከርድ ከ2 ዓመት በፊት በለንደን ኦሎምፒክ  በ1 ደቂቃ ከ41.54 ሰኮንዶች ያስመዘገበው ነው፡፡ አትሌት መሃመድ አማን ዘንድሮ በርቀቱ ሪከርድ ለመስበር  ፍላጐት እንዳለው በይፋ የተናገረው ነገር ባይኖርም የራሱን ምርጥ ሰዓት ወይንም የኢትዮጵያን ሪከርድ ለ7ኛ ጊዜ ለማሻሻል ያስባል፡፡ 800 ሜትርን ከ1.40 ደቂቃ በታች እንደሚገባም ያምናል፡፡

ምርጥ ሰዓቶቹ- በ800 ሜትር 1፡42.37 ቤልጅዬም ብራሰልስ  በ2013 እኤአ የተመዘገበ ሰዓት ሲሆን የኢትዮጵያ ሪከርድ ነው፡፡ በ800 ሜትር የኢትዮጵያ ሪከርድን ለስድስት ጊዜያት አሻሽሏል፡፡ በ1500 ሜትር 3፡43.52 ምርጥ ሰዓት ያስመዘገበ ሲሆን በ1 ማይል ያለው ምርጥ ሰዓት ደግሞ 3፡57.14 ነው፡፡
ወቅታዊ ደረጃው- በኦልአትሌቲትክስ ድረገፅ ዘንድሮ በ800 ሜትር በ1405 ነጥብ የዓለም አንደኛ አትሌት ሲሆን በሁሉም የአትሌቲክስ የውድድር መደቦች በተመሳሳይ ነጥብ ከዓለም 8ኛ ነው፡፡ በዓለም የ800 ሜትር የምንግዜም ፈጣን ሰዓቶች ደረጃ 9ኛ ነው፡፡
ማኔጅመንት እና ስፖንሰር -የትጥቅ ስፖንሰሩ ናይኪ ሲሆን፤ ከ2009 እኤአ ጀምሮ ኤሊት ስፖርትስ ማኔጅመንት ኢንተርናሽናል ESMI በመታቀፍ እየሰራ ነው፡፡
አስደናቂ ድሎቹ- አሁን በጉዳት ላይ የሚገኘው የኬንያው አትሌት ዴቪድ ሩዲሻ የ800 ሜትር የዓለም ሪከርድን ለስድስት ጊዜያት አሻሽሏል፡፡ ግዙፉ አትሌት በሩጫ ዘመኑ ካደረጋቸው 47 ውድድሮች 45ቱን አሸንፏል፡፡ የተሸነፈባቸው ሁለት ውድድሮች የመሃመድ አማን ሁለት አስደናቂ ድሎች ናቸው፡፡ የመጀመርያው በ2011 እኤአ ላይ በጣሊያኗ ከተማ ሬቲ ያሸነፈበት ሲሆን በወቅቱ ዴቪድ ሩዲሻ ለመጀመርያ ጊዜ የተሸነፈው ከ34 ተከታታይ ድሎች በኋላ ነበር፡፡ ሁለተኛው ደግሞ በ2012 እኤአ ላይ በዙሪክ የተካሄደ የዳይመንድ ሊግ ውድድር ሲሆን በዚህ ወሳኝ ትንቅንቅ ለመጀመርያ ጊዜ የዳይመንድ ሊግ ዋንጫን ያሸነፈበት ነበር፡፡

ባርሴሎና ለሊዮኔል ሜሲ ሰሞኑን በሰጠው አዲስ የኮንትራት ውል  ተጨዋቹን የዓለማችን ውዱ  ተከፋይ አድርጎታል፡፡ እስከ 2018 በኑካምፕ ለማቆየት በፈጸመው ስምምነት በየዓመቱ 16.3 ሚሊዮን ፓውንድ ይከፍለዋል፡፡ 20 ሚሊዮን ዩሮ ወይም 27 ሚሊዮን ዶላር ወይም 580 ሚሊዮን ብር  ማለት ነው፡፡ በዓለም ዋንጫ ሰሞን 27 ዓመቱን የሚደፍነው ሜሲ ባለፉት 11 ዓመታት ከባርሴሎና ጋር ለ8ኛ ጊዜ የኮንትራት ውል እና ማራዘሚያዎች መፈራረሙ ነው፡፡
የባርሴሎና የምንግዜም ከፍተኛ አግቢ ሲሆን በ425 ጨዋታዎች 354 ጎሎችን አግብቷል፡፡ 6 የላሊጋ፤ 3 የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ፤ 2 የኮፓ ዴላሬይ እና ሌሎች በድምሩ 21 ዋንጫዎችን አግኝቷል፡፡
በአጠቃላይ ዓመታዊ ገቢ  እስከ 73 ሚሊዮን ዶላር የሚያገኘው  ክርስትያኖ ሮናልዶ ይበልጠዋል፡፡ የሜሲ 65 ሚሊዮን ዶላር ነው፡፡
 ለሊዮኔል ሜሲ እስከ 250 ሚሊዮን ፓውንድ የዝውውር ሂሳብ ይጠራል፡፡

በእግር ኳስ ዓመታዊ ትርፍ 2.8 ቢሊዮን ዶላር የአዲዳስ 1.9 ቢሊዮን ዶላር የናይኪ
አዲዳስና ናይኪ ዓለም ዋንጫው ገና ወራት ሲቀሩት በገበያ ዘመቻቸው ከባድ ትንቅንቅ ውስጥ ገብተዋል፡፡ ሁለቱ ኩባንያዎች በእግር ኳሱ የማልያ ትጥቅ አቅራቢነት ከ5 ቢሊዮን ዶላር በላይ በየዓመቱ ያንቀሳቅሳሉ፡፡ በከፍተኛ የቴክኖሎጂ እገዛ የተመረጡ ታኬታዎችና ማልያዎችን በማቅረብ ፉክክራቸውን ያጧጡፋሉ፡፡
ናይኪ ለዓለም ዋንጫው ያቀረበው ታኬታ የቅርጫት ኳስና የሩጫ ጫማዎች የተሰሩባቸውን ቴክኖሎጂ አጣምሮ የያዘው “ማጂስታ” ነው፡፡ ኢኒዬስታና ማርዮ ጎትዜ በዚህ ታኬታ አሠራር ላይ የሃሳብ ተሳታፊ ነበሩ፡፡ የናይኪ “ማጂስታ” ታኬታ ዋጋ 275 ዶላር ነው፡፡ አዲዳስም “አዲዜሮ ኤፍ50” በሚል ስያሜ በሊዮኔል ሜሲ የሚተዋወቁትን የታኬታ ምርቶች ለዓለም ዋንጫው ይዞ ቀርቧል፡፡ የገበያ ዋጋቸው 270 ዶላር አካባቢ ነው፡፡የዓለም ዋንጫዋን ኳስ “ብራዙካ” ያቀረበውም አዲዳስ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት የዓለማችን ግዙፉ የስፖርት ትጥቅ አምራች ኩባንያ በዓለም ገበያ 17% ድርሻ የያዘውና 25 ቢሊዮን ዶላር ዓመታዊ ገቢ ያስመዘገበው የአሜሪካው ናይኪ ነው፡፡ የጀርመኑ ኩባንያ አዲዳስ በ12% የገበያ ድርሻ እና በ20 ቢሊዮን ዶላር ዓመታዊ ገቢ ይከተለዋል፡፡
አዲዳስ  ከዓለም ዋንጫ ውድድሮች እና በአጠቃላይ በእግር ኳስ ስፖርት የቅርብ አጋር ሆኖ ሲሰራ ከ66 ዓመታት በላይ አስቆጥሯል፡፡ በአንፃሩ ናይኪ ከዓለም ዋንጫ እና ከእግር ኳስ ስፖርት ጋር መንቀሳቀስ ከጀመረ ገና 20 ዓመቱ ነው፡፡
በ20ኛው ዓለም ዋንጫ ላይ ናይኪ የ10 ብሔራዊ ቡድኖችን ትጥቅ ሲያቀርብ የአዲዳስ 9 ናቸው፡፡ ፑማ ለ8 ብሔራዊ ቡድኖች ትጥቅ በማቅረብ 3ኛ ደረጃ አለው፡፡  
የዓለም ኮከብ ተጨዋች ክርስቲያኖ ሮናልዶ የናይኪ ታኬታዎች ዋና አምባሣደር ሲሆን የብራዚልና የፖርቱጋል ብሄራዊ ቡድኖች ሙሉ ትጥቅ ከሚወስዱት ይጠቀሳሉ፡፡  የስፔንና የጀርመን ብሔራዊ ቡድኖች ደግሞ የአዲዳስ ዋና ደንበኞች ሆነው ሲጠቀሱ በፊፋ የዓለም ኮከብ ተጨዋች ተብሎ ለ4 ጊዜያት የተመረጠው ሊዩኔል ሜሲ የአዲዳስ ትጥቆች ዋና አምባሳደር ነው፡፡ ፡፡
በኢንተርኔት የማህበረሰብ ድረገፆች በቀጠለው የሁለቱ ኩባንያዎች ዘመቻ ናይኪ ብልጫ ሲኖረው 36 ሚሊዮን የፌስ ቡክ ወዳጆች፣ እንዲሁም 8.8 ቢሊዮን የትዊተር ተከታታዮች በማስመዝገቡ ነው፡፡ አዲዳስ 17 ሚሊዮን የፌስ ቡክ ወዳጆች እና 9.4 ሚሊዮን የትዊተር ተከታታዮች አሉት፡፡

የዓለማችን የረጅም ርቀት ምርጥ አትሌቶች የሆኑት  ቀነኒሣ በቀለ እና ጥሩነሽ ዲባባ በጐዳና ላይ ሩጫዎች ስኬታማ እየሆኑ ናቸው፡፡  ባለፈው ሳምንት  በእንግሊዝ በተካሄደው የቡፓ ግሬት ማንቸስተር ራን በ10 ኪ.ሜ የጐዳና ላይ ሩጫ በሁለቱም ፆታዎች አሸናፊ ሆነዋል፡፡
አትሌት ቀነኒሣ በቀለ በወንዶች ምድብ ያሸነፈው ርቀቱን በ28.23 ደቂቃዎች በመሸፈን ነበር፡፡ የዓለም ማራቶን ሪኮርድ ባለቤቱን ኬንያዊው ዊልሰን ኪፕሳንግ በ5 ሰኮንዶች በመቅደም አስከትሎት ገብቷል፡፡ ይህ ውጤት  ሁለቱ አትሌቶች ለመጀመርያ  በማራቶን የሚገናኙበትን ሁኔታ አጓጊነት ጨምሮታል፡፡ ዊልሰን ኪንሳንግ በ2013 አጋማሽ ላይ በበርሊን ማራቶን 2 ሰዓት ከ03 ደቂቃ ከ23 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ  የዓለም ሪከርድን ያስመዘገበ ነው፡፡ ከወር በፊት ቀነኒሳ የመጀመርያ ማራቶኑን በፓሪስ ሮጦ የቦታውን ሪከርድ አስመዝግቦ ሲያሸንፍ በዚያው ሰሞን ዊልሰን ኪፕሳንግም በለንደን ማራቶን በተመሳሳይ የቦታውን ሪከርድ አስመዝግቦ ማሸነፉ ይታወሳል፡፡ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ በቀጣዩ የውድድር ዘመን ከዊልሰን ኪፕሳንግ ጋር በማራቶን መሮጥ ፍላጎት እንዳለውም የሰጠው፡፡ ከቡፓ ግሬት ማንችስተር ራን በኋላ ቀነኒሳ በሰጠው አስተያየት አሁን ትኩረቱ ወደ ትራክ ውድድሮች መመለስ እንደሆነ ገልፆ፤ በተለይ በ10ሺ ሜትር አንድ ውድድር ማድረግ እንደሚፈልግ አስታውቋል፡፡ በሌላ በኩል በሴቶች ምድብ ደግሞ አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ ርቀቱን በ32 ደቂቃ ከ20 ሰኮንዶች በመሸፈን አሸንፋለች፡፡ ጥሩነሽ  በቡፓ ግሬት ማንችስተር ራን ዘንድሮ ያሸነፈችው ለሁለተኛ ግዜ  ሲሆን አምና ውድድሩን ስታሸንፍ በ30.49 ደቂቃዎች በሆነ ጊዜ የቦታውን ሪከርድ አስመዝግባ ነበር ፡፡
ከወር በፊት በፓሪስ እና ለንደን በተካሄዱ የማራቶን ውድድሮች የመጀመርያ ማራቶናቸውን የሮጡት ቀነኒሳ በቀለ እና ጥሩነሽ ዲባባ አጀማመራቸው ስኬታማ እነደሆነ ያመለከቱ መረጃዎች፤ በሚቀጥሉት ዓመታት በሁለቱም ፆታዎች የተያዙ የዓለም ማራቶን ሪከርዶችን ለመስበር ግንባር ቀደም እጩዎች ስለመሆናቸውም ግምት ሰጥተዋል፡፡ የመጀመርያ ማራቶኑን በፓሪስ የሮጠው አትሌት ቀነኒሳ በቀለ የቦታውን ሪከርድ ካሸነፈ በኋላ ያሳየው ብቃት በሚቀጥሉት 5 ዓመታት የዓለም ማራቶን ሪከርድን ሊሰብር እንደሚችል ያመለክታል በሚል በርካታ ዘገባዎች አውስተውለታል፡፡ አትሌት ቀነኒሳ የፓሪስ ማራቶንን ሲያሸንፍ ርቀቱን የሸፈነበት 2 ሰአት ከ05 ደቂቃ ከ4 ሰኮንዶች ነበር፡፡ በረጅም ርቀት 5 የዓለም ሻምፒዮና እንዲሁም 3 የኦሎምፒክ የወርቅ ሜዳልያዎች ያሏት ጥሩነሽ ዲባባ ደግሞ ከወር በፊት በለንደን የመጀመርያ ማራቶን ውድድሯን  በሁለት ሰዓት ከ20 ደቂቃ ከ54 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ በሶስተኛ ደረጃ ጨርሳለች፡፡ ይሄው የጥሩነሽ ሰዓት በማራቶን የመጀመርያ ሩጫ ከተመዘገቡ ፈጣን ሰዓቶች በሶስተኛ ደረጃ ተመዝግቧል፡፡

ሚድሮክ ኢትዮጵያ የአትሌቲክስ ክለብ ይመሠረታል
ሚድሮክ ኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ ግሩፕ በሚቀጥለው ዓመት የአትሌቲክስ ስፖርት ክለብ እንደሚመሰርት አስታወቀ፡፡  በሚድሮክ ኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ስር ባሉ ኩባንያዎች መካከል ዘንድሮ ለ11ኛ ጊዜ የተካሄደው ዓመታዊ የስፖርት ውድድር ሰሞኑን ተጠናቅቋል፡፡ በዚሁ ዓመታዊ የስፖርት ውድድር መዝጊያ ስነስርዓት ላይ ንግግር ያደረጉት ዋና ስራ አስፈፃሚው ዶ/ር አረጋ ይርዳው የሚድሮክ ኢትዮጵያ የአትሌቲክስ ክለብ ለመመስረት የተወሰነው በስፖርቱ እድገት ላይ ተገቢውን  ድርሻ ለማበርከት ታቅዶ ነው ብለዋል፡፡ የመቻሬ የእግር ኳስ ክለብ ወደ ብሔራዊ ሊግ ደረጃ ለማድረስ ከፍተኛ ጥረት እንደሚያደርግም ዋና ስራ አስፈፃሚው ተናግረዋል።

       ዛሬ በፖርቱጋል ዋና ከተማ ሊዝበን በሚገኘው  ኢስታድዮ ዳ ሉዝ ስታድዬም ለ59ኛው የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ  ዋንጫ  ሁለቱ የማድሪድ ከተማ ክለቦች ሪያልና አትሌቲኮ ማድሪድ  ይፋጠጣሉ፡፡ በሻምፒዮንስ ሊግ ታሪክ ለፍፃሜ ጨዋታ የአንድ ከተማ ክለቦች ሲገናኙ  ለመጀመርያ ጊዜ  ነው፡፡ የዋንጫ ጨዋታው በ200 አገራት የቀጥታ ቴሌቭዢን ስርጭት ሲኖረው እስከ 1 ቢሊዮን ተመልካች እንደሚያገኝ ተገምቷል፡፡ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ዋንጫውን ለሚያሸንፈው ክለብ 10.5 ሚሊዮን ዩሮ እንዲሁም ለሁለተኛው ክለብ ደግሞ 6.5 ሚሊዮን ዩሮ ያበረክታል፡፡ በአጠቃላይ ሁለቱ የማድሪድ ክለቦች እስከ ፍፃሜው በነበራቸው ግስጋሴ ከቴሌቭዥን ስርጭት መብት፤ ከሜዳ ገቢ እና ከተለያዩ ንግዶች በነፍስ ወከፍ እስከ 55 ሚሊዮን ዩሮ ድርሻ ይኖራቸዋል፡፡ በሻምፒዮንስ ሊጉ ከዋንጫው ጨዋታ በፊት በተደረጉት 124 ጨዋታዎች 357 ጎሎች ሲመዘገቡ፤ ኮከብ ግብ አግቢነቱን የሪያል ማድሪዱ ክርስትያኖ ሮናልዶ በ16 ጎሎች እየመራው ነው፡፡
ሁለቱ የማድሪድ ከተማ ክለቦች እርስ በራስ የሚገናኙበት ጨዋታ “ኤል ደርቢ ማድሪሊያኖ” በሚል መጠሪያ ሲታወቅ ከዛሬው የዋንጫ ጨዋታ በፊት  264 ጨዋታዎች ተደርገውበታል፡፡  በ143 ሪያል ማድሪድ ሲያሸንፍ በ64  ጨዋታዎች ያሸነፈው  አትሌቲኮ ማድሪድ ነው፡፡ በ57 ጨዋታዎች ደግሞ አቻ ተለያይተዋል፡፡ ኤልደርቢ ማድሪሊያኖ አንድ ክፍል ዘመን ያስቆጠረ የእግር ኳስ ትንቅንቅ ነው፡፡  ባለፉት አስር ዓመታት ይህን ታላቅ ደርቢ ሪያል ማድሪድና ባርሴሎና የሚገናኙበት ኤልክላሲኮ ሸፍኖት  ቆይቷል፡፡
 የዓለም ሃብታሙ ክለብ ሪያል ማድሪድ ዛሬ ዋንጫውን ካነሳ በውድድሩ ታሪክ ለ10ኛ ጊዜ ይሆናል፡፡ ከዚህ ቀደም 13 ጊዜ ለፍፃሜ ቀርቦ 9 ዋንጫዎችን ወስዷል፡፡ የመጨረሻው ድሉ ከ12 ዓመት በፊት ነው፡፡ በአንፃሩ አትሌቲኮ የሚያገኘው ድል በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ  ነው፡፡ ከ40 ዓመት በፊት ብቸኛውን የፍፃሜ ጨዋታ አድርጎ  በባየር ሙኒክ 5ለ0 ተሸንፎ ዋንጫውን አልምጦታል፡፡ ሪያል ማድሪድ ኮፓ ዴ ላሬይን ቢያሸንፍም የውድድር ዘመኑን ውጤታማ ለማለት የግድ የሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫ ያስፈልገዋል፡፡ ባለፈው ሳምንት   ከ18 ዓመት በኋላ  የላሊጋ ዋንጫን ላገኘው አትሌቲኮ የማድሪድ ከተማ በ200ሺ ደጋፊዎች ተጥለቅልቃ ነበር ፡፡ የአውሮፓን ክብር ደርቦ ካሸነፈ  ደግሞ በከተማዋ የሚኖረው ፌሽታ ሚሊዮኖችን ያሳትፋል ተብሏል፡፡
ሪያል ማድሪድ በአገር ውስጥ ውድድሮች ከ60 በላይ፤ በአውሮፓ ደረጃ ከ11 በላይ ዋንጫዎችን የሰበሰበ ሲሆን አትሌቲኮ  በአገር ውስጥ ውድድሮች 24 በአውሮፓ ደረጃ ደግሞ 5 ዋንጫዎች አሉት፡፡
በስፔን ፕሪሚዬራ ሊጋ ሪያል ማድሪድ  32 ጊዜ ሻምፒዮን ሲሆን አትሌቲኮ ዘንድሮ 10ኛውን የሻምፒዮናነት ክብር አግኝቷል፡፡ በኮፓ ዴላሬይ ሪያል ማድሪድ 19 ዋንጫ ሲወስድ አትሌቲኮ ማድሪድ 10 አለው፡፡ሪያል ማድሪድ ለውድድር ዘመኑ የነበረው በጀት 515 ሚሊዮን ዩሮ ሲሆን በ4 እጥፍ የሚያንሰው የአትሌቲኮ በጀት 120 ሚሊዮን ዩሮ ነው፡፡
ሪያል ማድሪድ ማልያውን ከፍተኛ ስፖንሰርሺፕ ሲያገኝበት አትሌቲኮ ማድሪድ ለ2 የውድድር ዘመን ስፖንሰር አጥቶ የአዘርባጃን መፈክር ላንድ ኦፍ ፋየርን ለጥፎ ቅናሽ ገቢ አለው፡፡
ሪያል ማድሪድ  የተመሰረተው ከ112 ዓመታት በፊት ሲሆን በዘንድሮ አጠቃላይ የተጨዋቾች ስብስቡ በትራንስፈር ማርኬት 505 ሚሊዮን ዩሮ የዋጋ ተመን ሲኖረው  ከተመሰረተ ከ111 ዓመታት የሚሆነው የአትሌቲኮ ማድሪድ የተጨዋቾች ስብስብ ተመኑ 282 ሚሊዮን ዩሮ ነው፡፡

የኢትዮጵያ ሴቶች ብሔራዊ ቡድን (ሉሲዎቹ) በኢኳቶሪያል ጊኒ አስተናጋጅነት በ2007 ዓ.ም. ለሚከናወነው 9ኛው የአፍሪካ ዋንጫ  ለማለፍ  ጥቋቁሮቹን ንግስቶች ከተባሉት የጋና አቻቸው  በደርሶ መልስ ይፋለማሉ፡፡ የመጀመርያው ጨዋታ ነገ በአዲስ አበባ ስታድዬም የሚደረገው ነው፡፡ ሉሲዎቹ በዚሁ ፍልሚያ በሰፊ የግብ ልዩነት ማሸነፍ ከቻሉ የማለፍ እድላቸውን ያጠናክራሉ፡፡ ሁለት የወዳጅነት ጨዋታዎችን ከካሜሮንና ከናሚቢያ ብሔራዊ ቡድኖች ጋር የኢትዮጵያ ሴቶች ብሔራዊ ቡድን በሜዳቸው እና ከሜዳ ውጭ አድርገዋል፡፡ በጥሩ ደረጃ አቋማቸውን በመፈተሽም አስተማማኝ ብቃት ላይ ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ሴቶች ብሄራዊ ቡድን ከፕሪምየር ሊግ 12 ክለቦች የተወጣጡና 16 አዳዲስ ተጨዋቾች በሚገኙበት ቡድን በአጠቃላይ 37 ተጨዋቾች አሰባስቦ ቢያንስ ለወር ያህል ጠንካራ ዝግጅት ሲያደርግ ቆይቷል፡፡

የተራ ሞባይሎች ተፈላጊነት እየቀነሰ፤ “የስማርት ፎን” ሽያጭ ባለፈው አመት አንድ ቢሊዮን ያህል የደረሰ ሲሆን፤ የምርጦች ምርጥ ሆነው የገነኑት የአፕል አይፎን እና የሳምሰንግ ጋላክሲ ሞባይሎች ላይ ፉክክሩ አይሏል - በየገበያው እና በየፍርድ ቤቱ።
አፕል እስካሁን፣ ግማሽ ቢሊዮን አይፎኖችን ሸጧል። ቆየት ብሎ ወደ “ስማርትፎን” ገበያ የገባው ሳምሰንግ፣ ምርቶቹን በፍጥነት በማስፋፋት ከ200 ሚሊዮን በላይ ጋላክሲ ሞባይሎችን ለመሸጥ ችሏል።
አፕል ባለፈው መስከረም ወር ለገበያ ያቀረበው አይፎን 5፤ በመጀመሪያዎቹ ሶስት ቀናት 9 ሚሊዮን ያህል ተሽጦለታል። ከጊዜ ወደ ጊዜ ሽያጩ እየጨመረ፣ ባለፉት አስራ ሁለት ወራት ብቻ፤ 160 ሚሊዮን የተለያዩ የአይፎን ሞባይሎችን ለመሸጥ ችሏል። ነገር ግን፤ የሳምሰንግ ጋላክሲ ብርቱ ተፎካካሪ ሆነውበታል።
ከአይፎን በሶስት አመት ዘግይቶ የመጣው የሳምሰንግ ጋላክሲ፤ በፍጥነት እየተሻሻለ ከጋላክሲ ኤስ1 ዘንድሮ ጋላክሲ ኤስ5 ደርሷል። ባለፈው ወር  ለገበያ የቀረበው ጋላክሲ ኤስ5፤ ከአይፎን 5 ያልተናነሰ ገዢ እያገኘ እንደሆነ ተዘግቧል።



በሃይማኖት አክራሪነቱ ምክንያት ተቃውሞ የገጠመውን “የሙስሊም ብራዘርሁድ መንግስት” በመገልበጥ ስልጣን የያዙት ጄ/ል አልሲሲ፣ በግብፅ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ያለ ብዙ ፉክክር በሰፊ ልዩነት ያሸንፋሉ ተብሏል።
በእርግጥ ምርጫው የሚጀመረው  ሰኞ ነው። ነገር ግን፤ በውጭ የሚኖሩ ግብፃዊያን ከወዲሁ ድምፅ ሰጥተው ቆጠራ ተካሂዷል። በዚሁ ቆጠራ፤ ጄ/ል አልሲሲ፣ 94.5% ድምፅ ሲያገኙ፣ ወደ ሶሻሊዝም የሚያዘነብሉ ተቀናቃኛቸው 5.5% ድምፅ ማግኘታቸውን ዎልስትሪት ጆርናል ዘግቧል።
ሰኞ በሚጀመረው የአገር ውስጥ ምርጫም አልሲሲ አብዛኛውን ድምፅ እንደሚያገኙ ከመራጮች የተሰበሰበሰ አስተያየት ይጠቁማል። በእርግጥ፤ በጭራሽ ድምፅ ላለመስጠትና ላለመምረጥ የወሰኑ ግብፃዊያን ብዙ ናቸው። ከፊሎቹ ጄነራሉን በጠላትነት የሚቃወሙ የሙስሊም ብራዘርሁድ ደጋፊዎች ናቸው። ከፊሎቹ ደግሞ፤ የተሻለ አማራጭ የያዘ ደህና ፓርቲና ደህና ፖለቲከኛ በማጣት ከምርጫው ራሳቸውን አግልለዋል። ከእነዚህ ውጭ የሆነው አብዛኛው ግብፃዊ መራጭ፤ ለጊዜው ለአገሪቱ የሚበጃት ጄነራል አልሲሲን የመሰለ ጨከን ያለ መሪ ነው ብለው ያምናሉ።
በሌላ በኩል፤ በመፈንቅለ መንግስት ስልጣን ይዘው ከሰላሳ አመት በላይ ግብፅን የገዟት ሆስኒ ሙባረክ፣ 3 ሚሊዮን ዶላር ገደማ የመንግስት ገንዘብ አጭበርብረዋል በሚል ሰሞኑን የሶስት አመት እስር ተፈርዶባቸዋል። ልጃቸው ደግሞ የአራት አመት እስር። ከዚሁም ጋር የ14 ሚሊዮን ዶላር ቅጣት ተወስኖባቸዋል።

         ጡረተኛው ጄነራል ካሊፋ ሂፍጠር ከሁለት ወር በፊት አስቀድመው ተናግረዋል። “የሊቢያ መንግስት የሃይማኖት አክራሪዎችንና አሸባሪዎችን መቆጣጠር ካልቻለ፤ የራሴን እርምጃ እወስዳለሁ” በማለት በይፋ የተናገሩት በየካቲት ወር ነው። አንዳንድ ሊቢያውያን፤ “ምነው እንደአፋቸው ባደረጉት!” በማለት ተመኝተዋል። አንዳንዶች ደግሞ፤ “ጦር ሰራዊት የሌለው የጦር ጄነራል!” በማለት ተሳልቀዋል። ከአርባ አመት በላይ ሊቢያን አንቀጥቅጠው የገዟት ሶሻሊስቱ ሙዐመር ጋዳፊ በአመፅ ከስልጣን ወርደው ከተገደሉ በኋላ ለጥቂት ወራት የተስፋ ጭላንጭል ቢታይም፤ ብዙም ሳይቆይ አገሪቱ ወደ ግጭትና ትርምስ ተንሸራትታለች።
ፓርላማው፤ በአክራሪዎች እና አክራሪነትን በሚቃወሙ በርካታ ፓርቲዎች ለሁለት ተከፍሏል። አክራሪዎቹ እርስበርስ ይቀናቀናሉ - በጭካኔ ብዛት ይፎካከራሉ። አክራሪነትን የሚቃወሙት ፓርቲዎችም ቢሆኑ፤ በጎሳ እየተቧደኑ ይሻኮታሉ። ፉክክሩና ሽኩቻው፣ በንግግርና በፅሁፍ ብቻ አይደለም። ዘ ጋርድያን እንደዘገበው፤ እያንዳንዱ ፓርቲና ቡድን፤ የየራሱ ጦርና ታጣቂ ቡድን አለው። አንዳንዶቹ በታንክና በከባድ መሳሪያ የተደራጁ፤ በሺ የሚቆጠሩ ታጣቂዎችን ያሰለፉ ናቸው። የታጣቂ ቡድኖቹ ብዛት በመቶ ይቆጠራል። በሊቢያ የጦር መሳሪያ እጥረት የለም። አንዳንዶቹ  እንደአቅሚቲ በወረዳ፣ ከዚያም አልፎ በመንደርና በሰፈር ግዛታቸውን ለማስፋፋት የታጣቂ ቡድን ያንቀሳቅሳሉ። ገሚሶቹ ግን ወደቦችንና የነዳጅ ማውጫ ቦታዎችን ለመቆጣጠር ይዘምታሉ። ሌት ተቀን፣ ግድያ፣ ተኩስ፣ ፍንዳታ፣ ውጊያ ነው። የሊቢያ የነዳጅ ምርት፣ በቀን 1.4 ሚሊዮን በርሜል እንደነበረ የገለፀው ዎልስትሪት ጆርናል፤ አሁን በታጣቂዎች ግጭት የተነሳ የአገሪቱ የነዳጅ ምርት ወደ 200ሺ እንደወረደ ዘግቧል።
ባለፈው የካቲት ወር በትሪፖሊ በርካታ ነዋሪዎች በታጣቂዎች ከተገደሉ በኋላ ከፍተኛ ተቃውሞ በመነሳቱ፤ ዋና ከተማዋን ተቀራምተው የነበሩ ታጣቂ ቡድኖች ከተማዋን ለቀው እንዲወጡ ተደርገዋል። ግን ብዙም አልራቁም። ዙሪያውን በተለያዩ ከተሞች ካምፕ ሰርተው ተከማችተዋል። ትሪፖሊ የተወሰነ እፎይታ ብታገኝም፤ እንደ ቤንጋዚና ሚዝራታ የመሳሰሉ ከተሞች ግን የታጣቂ ቡድኖች መፈንጫ ሆነዋል። በየሳምንቱ፤ በደርዘን የሚቆጠሩ ፖሊሶች፣ ምልምል ወታደሮችና ዳኞች በተለያዩ ታጣቂ ቡድኖች ይገደላሉ - በተለይ ደግሞ ከአልቃይዳ በማይተናነሱ አክራሪ ቡድኖች። አነስተኛ ከተሞችና የገጠር መንደሮች ደግሞ፣ በጎሳ በተቧደኑ ታጣቂዎች ይታመሳሉ።
በጎሰኝነት እና በሃይማኖት አክራሪነት የተቃወሱ አገሮች ውስጥ፤ እንደ ሞሶሎኒና ሂትለር፤ ወይም እንደ ግብፁ ጄነራል አልሲሲ፤ “እናት አገር” ወይም “አባት አገር” የሚል መፈክር ይዞ የሚመጣ ብሔረተኛ መች ይጠፋል? በሊቢያ ደግሞ ጄነራል ካሊፋ ሂፍጠር።
ከአርባ አመት በፊት የጋዳፊ ወዳጅ የነበሩት ጄ/ል ሂፍጠር፤ ጎረቤት አገር ላይ የወረራ ዘመቻ እንዲመሩ ተመድበው ስላልተሳካላቸው ነው የጋዳፊ ጥርስ ውስጥ የገቡት። እንደምንም አምልጠው በስደት ወደ አሜሪካ የገቡት ጄ/ል ሂፍጠር፤ ተቃዋሚዎችን ለማደራጀት ለበርካታ አመታት ቢጣጣሩም የጋዳፊን መንግስት ሊያነቃንቁት አልቻሉም። የዛሬ 3 አመት በአረብ አገራት ሰፊ የተቃውሞ አመፅ የተቀሰቀሰ ጊዜ ነው፤ ወደ ሊቢያ ተመልሰው የወታደራዊ አመፅ መሪ የሆኑት። ከድል በኋላ የመከላከያ ሃይል ዋና አዛዥ የመሆን እድል አላገኙም። ምክትል ዋና አዛዥ ሆነው ትንሽ ከቆዩ በኋላ፤ ያንኑም ትተው የወጡት ጄ/ል ሂፍጠር፤ ለሁለት አመታት ያህል ድምፃቸው አልተሰማም። ድምፃቸውን ሊያሰሙ ቢሞክሩም፤ ያን ያህልም ሰሚ አልነበራቸው። ከጊዜ ወደ ጊዜ በጎሳ የተቧደኑ ታጣቂዎች እና በተለይም የሃይማኖት አክራሪ ቡድኖች የሚፈፅሙት ግድያ፣ ግጭትና ፍንዳታ እየተባባሰ፣ በሰላም ወጥቶ መመለስ እየጠፋ ሲመጣ አብዛኛው ሊቢያዊም ሲማረር ግን ሰሚ ተገኘ።
ለጄነራሉ ጆሯቸውን ለመስጠት ቀዳሚ ከሆኑት መካከል፣ ፖሊሶችና ወታደሮች ናቸው። የታጣቂ ቡድኖች የግድያ ዘመቻ፤ በፖሊሶችና ወታደሮች ላይ ይበረታልና። በጎሳ የተቧደኑ አንዳንድ ታጣቂዎችንም ለማግባባት ሞክረዋል ጄ/ል ሂፍጠር። እንዲህ አይነት ዝግጅቶችን ለሁለት ወራት እንዳካሄዱ የሚገልፁት ጄ/ል ሂፍጠር፤ ባለፈው ሳምንት በቤንጋዚና በትሪፖሊ ከተሞች ወታደሮችን በማሰማራት ወደ ጥቃት ዘመቻ እንደተሸጋገሩ አውጀዋል። ያሰባሰቡትን ወታደራዊ ሃይል፤ “የሊቢያ ብሔራዊ ጦር” ሲሉ ሰይመውታል። “አባት አገር ተደፍሯል” የሚሉት ጄ/ል ሂፍጠር፤ የዘመቻው መጠሪያ ስም፤ “የሊቢያን ክብር የማስመለስ ዘመቻ” የሚል እንደሆነ ተናግረዋል። ቤንጋዚ ከተማ ውስጥ፤ ባለፈው አርብ ሶስት አክራሪ ቡድኖች ላይ ጥቃት ከፈፀሙ በኋላ፤ እሁድ እለት በትሪፖሊ ፓርላማ ላይ ታጣቂዎችን አዝምተዋል።
የፓርላማው የስልጣን ዘመን ካበቃ ሁለት ወር ስላለፈው ህጋዊ ስልጣን የለውም የሚሉት ጄ/ል ሂፍጠር፤ “አክራሪዎች ፓርላማውን ተቆጣጥረውታል፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአክራሪ ቡድን ተወካይ ናቸው፤ ብሔራዊ ጦርና ብሔራዊ ፖሊስን ከማደራጀት ይልቅ አክራሪ ታጣቂ ቡድኖችን በመደገፍ ያጠናክራሉ” በማለት ፓርላማ ላይ የፈፀሙት ጥቃት ተገቢ እንደሆነ ይናገራሉ። አክራሪ ቡድኖችና ታጣቂዎች በድርድርና በውይይት አያምኑም፤ ስለዚህ እስክናጠፋቸው ድረስ እንዋጋለን ብለዋል ጄነራሉ።
የጄነራሉን ድርጊት ለማውገዝ እንደማይፈልጉ የገለፁ አንዳንድ ሚኒስትሮችና የፓርላማ አባላት፤ አክራሪ ቡድኖችን መቃወም ተገቢ ነው ብለዋል። የተወሰኑ ሚኒስትሮች ደግሞ፤ የጄነራሉ ጥቃት አደገኛ ነው፤ በቋፍ ያለችውን አገር ወደ ለየለት ጦርነት ሊያስገባት ይችላል ብለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩና በርካታ ባለስልጣናት ግን፤ የጄነራሉ ዘመቻ ከመፈንቅለ መንግስት ተለይቶ አይታይም ሲሉ አስጠንቅቀዋል። በትሪፖሊ ዙሪያ የሰፈሩ ታጣቂ ቡድኖች ወደ ዋና ከተማዋ በመግባት የጄነራሉን ጥቃት እንዲከላከሉ ጥሪ ያስተላለፉት ጠቅላይ ሚኒስትር፤ የቤንጋዚ አየር ማረፊያ አገልግሎት እንዳይሰጥ ትዕዛዝ አስተላልፈዋል። የአገሪቱ መከላከያ ሃይል፤ በጡረተኛው ጄነራል ላይ እርምጃ እንዲወስድም በይፋ አዘዋል - ጠቅላይ ሚኒስትሩ። ነገር ግን ትዕዛዛቸው አልሰራም። በሁለት ከተሞች የሚገኙ የአየር ሃይል ካምፖች በጡረተኛው ጄነራል ስር ለመመራት በመወሰናቸው፤ ሄሌኮፕተሮችና የጦር አውሮፕላኖች በቤንጋዚ ዘመቻ ላይ ተካፍለዋል። የመከላከያ ሃይል ወታደራዊ ፖሊስ አዛዥ በበኩላቸው፤ በጄነራል ሂፍጠር መሪነት የአገሪቱ መንግስት ከስልጣን መታገዱን በማወጅ፤ ጊዜያዊ መንግስት እንደሚመሰረት ገልፀዋል።
ለሁለት አመት ተረስተው የነበሩት ጡረተኛ ጄነራል፤ አሁን ወታደራዊ ልብስ ከነማዕረጋቸው ለብሰው በሳምንት ውስጥ ገናና ለመሆን ቢችሉም፤ የመንግስት ስልጣን ለመቆጣጠር አቅም ይኑራቸው አይኑራቸው ገና አልታወቀም። ለእርስ በርስ ጦርነት የሚሆን አቅም እንዳላቸው ግን አያጠራጥርም። ለዚህም ይመስላል፤ የአልጄሪያ መንግስት ልዩ ወታደራዊ ሃይል በመላክ ዲፕሎማቶቹንና ዜጎቹን ከሊቢያ ሲያስወጣ የሰነበተው። የሞሮኮ መንግስትም አምስት ሺ ወታደሮችን ወደ ድንበር አሰማርቷል። የአውሮፓ አገራትና አሜሪካ፤ ዜጎቻቸውን በአፋጣኝ ለማስወጣት መጣደፍ ጀምረዋል። በአጠቃላይ በግጭት የምትታመሰው ሊቢያ፤ አሁን እንደገና መጨረሻው በማይታወቅ የጦርነት ውጥረት ውስጥ ገብታለች።