Administrator

Administrator

ቡድኑ በቀጣዩ ኦሎምፒክ ማጣሪያም አይሳተፍም

    የኢትዮጵያ ሴቶች እግር ኳስ ብሔራዊ ቡድን ሉሲ፣ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ለሚመለከተው አካል መላክ የነበረበትን የተሳትፎ ማረጋገጫ ደብዳቤ ባለመላኩ በሰራው ጥፋት ሳቢያ፣ በካሜሩን አስተናጋጅነት ከሚካሄደው የ2016 የአፍሪካ ዋንጫ ቅድመ ማጣሪያ ውድድር ውጭ ሆኗል፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን፣ የውድድር ተሳትፎ ማረጋገጫ ደብዳቤውን ባለመላኩ ሳቢያ ብሄራዊ ቡድኑ
ከቅድመ ማጣሪያ የምድብ ድልድል ውጭ መደረጉን የተነገረ ሲሆን፣ ከዚህ በተጨማሪም ቡድኑ በዚሁ የፌዴሬሽኑ ጥፋት ምክንያት ከ2016ቱ የሪዮ ዴ ጄኔሮ ኦሎምፒክ ማጣሪያ ውጭ መሆኑንም ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡
ባለፈው ማክሰኞ ካይሮ በሚገኘው የካፍ ዋና ጽህፈት ቤት በተከናወነው የቅድመ ማጣሪያ ውድድር የምድብ ድልድል እጣ አወጣጥ ስነስርዓት ውስጥ ሉሲዎቹ አለመካተታቸውን ያስታወሱት ምንጮች፣ ፌዴሬሽኑ ከሚመለከተው አካል ጋር ተጻጽፎ ቡድኑን ወደ ውድድር ለመመለስ ማቀዱንና የፌዴሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ ትናንት ወደ ግብፅ በማቅናት፣ በበጀት ምክንያት በውድድሩ
በማይሳተፉ አገራት ቡድኖች ምትክ ብሄራዊ ቡድኑ መሳተፍ የሚችልበትን ዕድል ለማመቻቸት እንዳሰቡም ጠቁመዋል፡፡ፌዴሬሽኑ ባለፈው የአለም ዋንጫ ማጣሪያ ውድድር ተሳትፎ በነበረው የወንዶች ብሄራዊ ቡድን መመዝገብ የነበረበትን የምንያህል ተሾመ ቢጫ ካርዶች ችላ በማለቱ ሳቢያ በተፈጠረ ችግር ከፍተኛ የህዝብ ተቃውሞ ገጥሞት እንደነበር ይታወሳል፡፡

ከእንግሊዝ በተለይ ለአዲስ አድማስ)

“‘የሚያቅትህ ነገር የለም!...‘ እየተባልኩ ነው ያደግሁት...” - ደራሲ ስዩም ገ/ ህይወት


ከ12 አመታት በፊት ለንባብ የበቃው “ሚክሎል - የመቻል ሚዛን” በበርካታ አንባብያን ዘንድ ከፍተኛ አድናቆት የተቸረው የረጅም ልቦለድ
መጽሃፍ ነው፡፡ የመጽሃፉ ደራሲ ስዩም ገብረ ህይወት፣ በዚሁ መጽሃፍ ላይ ቀጣዩን “ሚክሎል - የማቃት አንጀት” ለንባብ እንደሚያበቃ ቢገልጽም፣
መጽሐፉ ለረጅም አመታት ለህትመት ሳይበቃ መቆየቱ፣ በርካታ አንባቢያን ዘንድ መልስ ያልተገኘለት ጥያቄ ሆኖ ቆይቷል፡፡ደራሲ ስዩም ገ/ ህይወት
ከአስር አመታት በላይ ድምጹን አጥፍቶ መቆየቱ ያሳሰባቸው አድናቂዎቹ፣ በቅርቡ በማህበራዊ ድረ ገጾች በኩል ደራሲውን የማፈላለግ ዘመቻ
መጀመራቸው ይታወቃል፡፡ ጋዜጠኛ አንተነህ ይግዛው፤ለደራሲ ስዩም ገብረ ህይወት በግል ህይወቱ፣ በመጀመሪያው ልብወለድ መጽሐፉና ተያያዥ
ጉዳዮች ዙሪያ፣ በኢሜይል ላቀረበለት ጥያቄዎች፣ የሰጣቸውን ምላሾች የመጀመሪያ ክፍል እንዲህ አጠናቅረነዋል፡፡

ውልደትና እድገት
ድርና ማጌ ወሎ ነው። “ሃድራው የሚደምቀው ተደራርበው ሲተኙ” እየተባለ የተዘፈነለት ባቲ ገንደድዩ፣ የአባቴ አገር ነው። “እኒህ አምባሰሎች አበላል ያውቃሉ በጤፍ እንጀራ ላይ ሳማ አርጉ ይላሉ” የተባለለት አምባሰል ደሞ የእናቴ አገር ነው። እኔ ግን ባቲ ተወልጄ፣ ያኔ የቃሉ ወረዳዋና ከተማ በነበረችው ሐርቡ ነው ያደግሁት። አስታውሳለሁ ገና የስምንት ዓመት ልጅ እያለሁ፣ ከቤታችን በር አጠገብ ባለው ወደ ሰሜን በሚሄደው ጎዳና ዳር ቆሜ፣ ወደማታ ላይ የሚያልፉትን አውቶቡሶች ማየት ደስ ይለኝ ነበር። አንዳንዶቹ አሥመራ፣ አንዳንዶቹ መቀሌ የሚል የተለጠፈባቸው ነበሩ። “እኔ ግን ሳድግ የምኖረው መቀሌ ነው” እል ነበር፤ ሁልጊዜ። ምን ታይቶኝ ነበር ማለት ነው? መቀሌን ማየት ይቅርና ስለሱ ሲወራ እንኳን ሰምቼ አላቅም።
 የትምህርት ሂደት
የአንደኛ ደረጃ ትምህርቴን ሐርቡና ቢስቲማ በምትባለው አምባሰል ባለች ትንሽ ከተማ ነው የተማርኩት። ሰባተኛ ክፍል ብቻ ባቲ ተማርኩ እንጂ የቀረው የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን የጨረስኩት የቃሉ አውራጃ ዋና ከተማ በሆነችው ኮምበልቻ ነው። ከዛ እድሜዬ በኋላ ከወሎ ጋር እንደተለያየን ቀረን። መጀመሪያ አዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ተመድቤ ከሄድኩበት ጊዜ አንስቶ በቋሚነት ለመኖር ተመልሼ አላውቅም። የሐርቡ ልጅነት መንፈሴ ግን የትም ልሂድ የትም፣ ቋሚ መኖሪያው እስካሁን ሐርቡ ነው። ከአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ላይብራሪ ሳይንስ በሚባል ሙያ በዲፕሎማ እንደተመረቅሁ፣የተመደብኩበት መስሪያ ቤት አንድ ስህተት ሰራ። አሁን ሳስበው ለካ ስህተትም ትክክል የሚሆንበት ጊዜ አለ እላለሁ። ያ መስሪያ ቤት  ስሜን ብቻ በማየት የሰሜን ተወላጅ ነው ብሎ በማመኑ፣ መቀሌ መድቦ ላከኝ። ለካ የራሴ ቃል ጥሪ ነው መስሪያ ቤቱን ያሳሳተው። ምን ይሄ ብቻ -  ያን ስህተት ትክክል የሚያደርገው ጉድ መች ታየና።
መፈጸም የነበረበት ስህተት ---  
አሁን ባለትዳርና የአራት ልጆች አባት ነኝ። የመሆኔ ብርታት፣የነፍሴ ብርሃን፣ የራዕየ ምርኩዝ የሆነችው ውዷ ባለቤቴ ባትኖር ኖሮ የኔ ማንነት ባዶ ነበር። ሚክሎልን ያነበበ ሁሉ በስም ያውቃታል። ሚክሎል የተወለደው ከኔ የሁነት አብራክ ብቻ ሳይሆን ከሷምዝንታለም የማይላላ፣ የማያረገርግ የድጋፍ ምሶሶ ነው። ያለ ምሶሶ ጎጆ ሊቆም ይችላል? በብርቱ ሴት ጠጣር መንፈስያልተደገፈ የወንድ ህይውት፣ በሸንበቆ ተራዳ የቆመ ጊዜያዊ ድንኳን ነው።
ትዳር ሳልይዝ፣ሶስት ዓመት ኖሬ መቀሌን ለቅቄ ሄድኩ። ሁለት ዓመት አዲስ አበባ ከኖርኩ በኋላ እንደገና ዩንቨርስቲ ገባሁ። ከዱሮው ሞያዬ ላይ የኢንፎርሜሽንና ኮምፒውተር ሳይንስ ተጨምሮበት በዲግሪ ተመረቅሁ። በጣም የሚገርመው ነገር ግን የመቀሌ አዙሪትሊለቀኝ አልቻለም። በከፍተኛ ትምህርት ኮሚሽን ተወዳድሬ አለፍኩና አሁንም ዳግመኛ መቀሌ ተላኩ። የመቀሌ ዩንቨርስቲን ለማቋቋም ከየትምህርት ተቋሙ ተመርጠው ከተመደቡት በጣት የሚቆጠሩት የአካዳሚክ ሰራተኞች አንዱ ሆንኩ። እንግዲህ የመሆኔ መረብ ሊይዝ የሚፈልገው ዓሳ፣ እዛው መቀሌ ስለነበር ይሆናል፡፡
በመቀሌ ዩንቨርስቲ የመጀመሪያውን ላይብረሪና የኮምፒውተር ማዕከል አቋቋምኩ። የመጀመሪያውም የኮምፒዩተር ስልጠና አደራጅና አስተማሪም እኔው ነበርኩ።መቀሌ ዩንቨርስቲ ሥራ እንደጀመርን ብዙም አልቆየንም። ከሁለት ጓደኞቼ ጋር እየተጨዋወትን፣ በግቢው ውስጥ እንንጎራደዳለን። ፀሃፊዎች ለመቅጠር ማስታወቂያ ወጥቶ ነበርና ማመልከቻ ለማስገባት የሚጎርፈው ግቢውን እጥለቅልቆታል። ከፊት ለፊታችን ከሚመጡትሶስት ወጣት ሴቶች መሃለኛዋ ላይ ዓይኔ ድንገት አረፈ። በህይወቴ ተሰምቶኝ የማያውቅ ልዩ ንዝረት ሁለንተናዬን ናጠው። ልቤ አምልጦ አለት ላይ እንደወደቀ እንቁላል ጧ ብሎ የፈረጠ መሰለኝ። ልጅቷ እስከመቼውም የማይጠፋ የሚመስል እሳተጎመራ አስነስታ፣ሄደች። ደግሜ ላያትም አልቻልኩም። ተፈልጋ የምትገኝበትም መንገድ የለም።  ህመሜን ተሸክሜ ቀረሁ። እንደ ካሜራ፣ ያ ድንገት ከፊቴ ላይ ፏ ብሎ የጠፋው ብርሃን፣ አሁንም እሁንም እየተመላለሰ ይጎበኘኝ ነበር። እሸሸዋለሁ ይከተለኛል። እንዲሁ ሲያንገላታኝ አንድሁለት ሰሞን እንዳለፈ፣ አንድ ቀን ድንገት ወደ ቢሮዬ ስልክ ተደወለ። ከአስተዳደር ነበር። ከሚቀጠሩት ሶስት ፀሃፊዎች አንዷ፣ ለኔ የሥራ ክፍል መሆኑን አውቅ ነበር። አስተዳዳሪው ሦስቱ መመረጣቸውን ገልጾልኝ፣ ለኔ የተቀጠረችውን እገሌ ትባላለች ብሎ ስሟን ነገረኝ። ስሟን በልቤ እየደጋገምኩ  ወደ አስተዳደር መሄድ ጀመርኩ። ልቤ ግን ስሟን መሸከም የከበደው ይመስል ምቱ ጨመረ። “ደሞ ይሄ ምን እሚሉት በሽታ ነው ለማያውቁት ሰው። ኧረ ተው! ኧረ ተው! አንተ ልብ አበዛኸው!” አልኩት።
ሦስቱ የተመረጡት ፀሃፊዎች ያሉበት ክፍል ደርሼ፣ ዓይኔን ወደ ውስጥ ወርወር ሳደርግ፣ ልቤም ተፈትልኮ ተወረወረና በእርግጡን እንቦጭ ብሎ ፈረጠ። እንዴት አድርጎ መልሶ እቦታው እንደተመለሰ አላውቅም። ከሶስቱ አንዷ ያቺው ልጅ እራሷ ነበረች። ጉልበቴእየተብረከረከና ከንፈሮቼ እየተንቀጠቀጡ፣ “መብራት አበራ የምትባለው የትዋ ነች?” አልኩኝ፤ ዓይኖቼን ከዓይኗ ላይ ሳልነቅል። ይባስ ብሎ ይቺው ልጅ እራሷ “እኔ ነኝ” እለችኝ። እርፍ! እሞት እንደሁ ጉዱን አየዋለሁ። ለካ ያቺ ልጅ የሁነቴ አሻራ መረብ አጥምዷትየነበረችው መብራት አበራ ነበረች።
ያቺ የነፍሴ ብርሃን መብራት አበራ (እኔ መብርህቴ እያልኩ ነው የምጠራት) ወደውጭ ለመሄድ እያደረገችው የነበረውን ዝግጅት ሰርዛ፣ መቀሌን ለቀን አዲስ አበባ በመግባት በሠርግ ተጋባን። የመሆኔ ብርታት፣ የራዕዬ ምርኩዝ ሆና፣ ሚክሎል መፅሐፍን አብረን ወለድን። ሦስት ወንድ ልጆችም ወለደችልኝ።
“የፍቅር መታሰቢያችን - ታይታኒክ” - በመቀሌ ዩኒቨርሲቲ
በጣም የሚገርመው ከ22 ዓመታት በኋላ ሦስቱን ልጆቻችንን ይዘን (ሚክሎል፣ ኖባ እና ካሌብን) መቀሌ ቤተሰብ ለመጠየቅ ከእንግሊዝ አገር እንደሄድን፣ ያኔ የቅርብ ጓደኛችን የነበረው የዩንቨርስቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር ክንደያ ገ/ሕይወት ዩንቨርስቲውን እንድንጎበኝጋበዘን። ያኔ ሲጀምር 42 ተማሪ ብቻ እንዳልተቀበለ ሁሉ ዛሬ ከ30 ሺ ተማሪ በላይ የሚያስተናግድበት አቅም ላይ ደርሷል። ደስ አለን። ግና በጣም ደስ የሚያሰኝም ያሳቀንም፣ ልጆቻችንንም እጅግ በጣም አድርጎ ያስገረመው ነገር የመጣው በኋላ ነበር።
ዶ/ር ክንደያ፤ ግቢውን እያስጎበኘን እያለ፣ ቀጥ አድርጎ ወደ አንድ ልዩ ቦታ ወሰደን። ያቺ ልዩ ቦታ መብርህቴን ለመጀመሪያጊዜ ያየሁባት፣ ከመጀመሪያው ያስተዳደር ህንፃ ፊት ለፊት የነበረች ነጥብ ናት። ሌላው እጅግ በጣም ጉድ የሚያሰኘውን ነገር የተናገረው ወዲያውኑ ነበር። እሱና የሥራ ባልደረቦቹ እየሳቁ፤ “ይቺን ሃውልት ያሰራነው ለናንተ ፍቅር መታሰቢያ ነው” አሉን። እኛም እጃቸው የሚጠቁመውን ስንከተል፣ በመርከብ ቅርፅ በኮንክሪት የተሰራች ትንሽ ጀልባ የምትመስል ሃውልት ዓየን። እኛም ልጆቻችንም ፍንድቅ ብለን የሳቅነውግን “ታይታኒክ” ተብላ ተሰይማለች ሲሉን ነበር። አይገርምም!
የድሮው ቢሯችን የነበረበት ህንፃም እስካሁን ድረስ አለ። “የኔ ቢሮ እዚህ፣ የናታችሁ ቢሮ ደሞ እዚህ ነበር” ብዬ ለልጆቼ ቢሮዎቹን እያሳየኋቸው ሳለ፣ ቀልደኛው ትንሹ ካሌብ ስዩም ፈገግ አለና በእንግሊዘኛ “ስለዚህ እናቴ ገና እዚህ መስራት እንደጀመረች ያለ ምክንያት ወደቢሮዋ መመላለስ ጀምረህ ነበር ማለት ነው!” ብሎ ሁላችንንም አሳቀን። ከዩንቨርስቲው ባልደረቦች አንዱ እየሳቀ፤ “ያኔ ያለምክንያት ቢሆንም አሁን ሲታይ ግን ለካ ለጥሩ ምክንያት ነበር የሚመላለሰው ያስብላል” አለ።
 ልምድ ያካበትኩበት ብሪትሽ  ካውንስል
እኔ ብዙውን የሥራ ዘመኔን ለብሪትሽ ካውንስል ኢትዮጵያ ነው የሠራሁት። አራት ዓመት ሙሉ የፕሮጄክት ማኔጀር ሆኜ ስሰራ፣ መላኢትዮጵያን ልቅም አድርጌ ለማየት ዕድል አግኝቻለሁ። ከዚያም ቀጥሎ የብሪቲሽ ካውንስል ኢትዮጵያ ቤተመጻህፍትናኢንፎርሜሽን አገልግሎት ዋና ሥራ አስኪያጅ ሆኜ አገልግያልሁ። በስሬ እስከ 25 ፕሮፌሽናል ሠራተኞች ነበሩ። በዚህ የሰባት ዓመት የሥራ ዘመን፣ እጅግ በርካታ የማኔጅመንትና ፕሮጄክት ማኔጅመንት ሥልጠናዎችን በአውሮፓ፣በአፍሪካና በኤስያ እየተዘዋወርኩ ወስጃለሁ፡፡ እጅግ በጣም በርካታ ፕሮጀክቶችን ነድፌአለሁም ፣ የሥራ ፕሮግራማቸውንም መርቻለሁ።በብሪትሽ ካውንስል ቆይታዬ ከሠራኋቸው ብዙ ነገሮች አንድ ሁለቱን ልጥቀስ። በኢትዮጵያ የመጀመሪያዎቹን ቴሌሴንተሮች (ኢንተርኔት ካፌና ኮምፒውተር ማዕከል) ያቋቋመው ፕሮጄክት ሃሳብ፣ንድፍና ትግበራም የኔው የአእምሮ ውጤት ነው። እኒህ የመጀመሪያዎቹማዕከሎች የተቋቋሙት በወሊሶ፣ በደብረብርሃን፣በጎንደርና በአክሱም ከተሞች ነበር። በኢትዮጵያ ውስጥ ያኔ የነበሩትን ሁሉንም ዩንቨርስቲዎች፣ ኮሌጆች፣ መምህራን ማሰልጠኛ ተቋማት፣ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች፣ ሆስፒታሎችና ጤና ጣቢያዎችን በኢንፎርሜሽን ቁሳቁስ፣መጽሐፍትና ሥልጠና ይረዳ የነበረውን እጅግ በጣም ሰፊ ፕሮጀክት በሃላፊነት መርቻለሁ። የኢንፎርሜሽን ማኔጅመንትና ፕሮጀክት ማኔጅመንት ኮርሶችን በማዘጋጀትና በማስተማርም አገልግያለሁ።
የሥራ ልምዴ በእንግሊዝ -----
በፊት የነበረኝን የማኔጅመንትና የፕሮጄክት ማኔጅመንት ዕውቀትና ልምድ በመጠቀም፣ እዚህ እንግሊዝ አገር ባለሁበት ክፍለ ሀገር (ዮርክሻየር) ለክፍለ ሃገሩ ስደተኞች ጉዳይ አስተዳደር መ/ቤት የፖሊሲና ሕዝብ ግንኙነት ሃላፊ በመሆን አገልግያለሁ።  ዋና ስራዬ ግን፣ በእንግሊዝኛ የሚታተም ወርሃዊ ጋዜጣ ማዘጋጀት፣ የማኔጅመንት ኮርሶችን ማዘጋጀትና መምራት፣ ዌብ ሳይት ማኔጅ ማድረግ፣ ኢንፎርሜሽን ማሰራጨት፣ ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ ጥናትና ምርምር ማካሄድን ይጨምር ነበር።
ጉግሳና ስዩም ምንና ምን ናቸው?
የሚክሎልጉግሳ ሙሉ በሙሉ ሃሳብ ወለድ ገጸባህሪይ ነው። እኔንም ሆነ ሌላ ማንንም ሰው አይወክልም። መጀመሪያ ስዩም ና ጉግሳ የማይመሳሰሉበትን ብናነሳ አይሻልም? አንባቢዎቼም ይሄንን ልብ ብለው እንዲረዱልኝ እፈልጋለሁ። ካልሆነማ እኔም በየአእምሮአቸው ጓዳሲንጀላጀል የሚኖር ዘባተሎው ጉግሳ ቀዌ ሆኜ መቅረቴ ነው።
ጉግሳኮ በየስብሰባው “ያዝ እንግዲህ” እያለ ታዳሚን ሲያሰለች ነው የሚውለው። እኔ ግን እሱ በተገኘበት ስብሰባ ሁሉ እግሬ የረገጠ ቢሆንም አንድ ቀን እንኳን ትንፍሽ ብዬ አላውቅም። ሲነሳ ሲወድቅ የነበረውን የዩኒቨርስቲ ተማሪ ስሜት ማዕበል ልብ ዬ መታዘብነበር ስራዬ። በልቤ ጓዳ ውስጥ ግን ልብ ያላልኩት የጉግሳ ሽል እየተፈራገጠ ሊሆን ይችላል። የማቀው ነገር የለኝም።ጉግሳ ሁሌ አለባበሱ የተንጀላጀለ፣ ያን ድንኳን የሚያህል ጃኬቱን እያንጓፈፈ ባለፈ ቁጥር በአካባቢው የነበረ ሁሉ “ይሄ ጅልአንፎ ቀውስ መጣ እንግዲህ” እያለ እሚጠቋቆምበት ነበር። ስዩም ግን ከረባት ከአንገቱ፣ ሱፍ ከትከሻው ወርዶ የማያውቅ፣ ዘወትር ሽክ እንዳለየሚታይ የዘመናዊ (አውሮፓዊ) ቢሮ ፕሮፌሽናል ማኔጀር ነበር።ጉግሳኮ ሴቶች ሲፈልጉት አይገባውም። መቼስ ጉዳዩ ነበረና ለሴት። እነ ፀደኒያና እነ ሶስና እንዴት ነበር በድንዝዝነቱ ልባቸው እርር ይል የነበረው። ስዩምም ለሴቶች እንደጉግሳ ነበር ብል እውነት አሁን የሚያውቁኝ ሁሉ ልባቸው ፍርስ እስኪል አይስቁም ትላላችሁ።
ጉግሳ የሐርቡ ልጅ ሆኖ ሲያድግ እንጂ አዲስ አበባ ከገባ በኋላ የነበረው ሁሉ ትምህርቱም፣ ድርጊቱም፣ ውሎውም የራሱ ብቻ ነው፡፡ ከስዩምጋር ምንም ግንኙነት የለውም። ስዩምኮ ሥነ-ጽሁፍ የሚባል ነገር ተምሮ አያውቅም።እሺ አሁን ደሞ ጉግሳና ስዩምን የሚያመሳስላቸው ምንድነው የሚለውን እንይ። የጉግሳ አስተዳደግና የጉግሳ አባት ባህሪና ታሪክ የራሱ የስዩም አባት ባህሪና ታሪክ ቀጥተኛ ነፀብራቅ ነው። ጉግሳ  የስዩምን ማንነት ኮርጆ ተወለደ እንጂ ስዩም የጉግሳን ማንነት ኮርጆ አልተወለደም። ለካ መኮረጅ የምጠላው ገና ከመወለዴ በፊት ነበር።
እንግዲህ ልብወለድ ያልሆነውን ፤ እውነቱን (ያልተኮረጀውን) ስዩም፣ የሐርቡን ልጅ አስተዳደግ እንዲህ እንዲህ አድርገን ዳሰስ ልናደርገው እንችላለን።
አባቴ “ትንሽ ነገር አታስብ” እያሉ ነው ያሳደጉኝ  
በአብዛኛው የባላንባራስ ልጅ እየተባልኩ ነበር የምታወቀው፤ በዛችው በሐርቡ ከተማ ሳድግ። አባቴ ባላንባራስ ገ/ሕይወት ሽማግሌ ከሆኑ በኋላ ነበር የወለዱኝ። ባላንባራስ ገ/ሕይወት ገና በጉርምስናቸው ነበር ከወላጆቻቸው ጋር ከሚኖሩበት ባቲ አካባቢ ካለ ገጠርመንደር በመጥፋት ወደ አስመራ የተሰደዱት። ከጣሊያን ወረራ በፊት ገና ዱሮ ነው ይባላል ይሄ የሆነው። ባላንባራስ ገብረሕይወት በጉርምስናቸው አገር ቤት እያሉ  ሰፈር ከሰፈር በሚደረገው ውጊያ የወንድ አውራ ነበሩ። በዛም የተነሳ ዑመር አባስበር የሚል ስምወጥቶላቸው ነበር። ይህን ያልወደዱላቸውና ስሞታው ያሰለቻቸው አባታቸው ሸህ አሊ ያሲን፤ እረግምሃለሁ እያሉ ስላስቸገሯቸው ነው ጥሎ ለመጥፋት ወስነው የተሰደዱት።
አስመራ ከተማ የትሪቦሊ (ትሪፖሊ) ዘማች ወታደር ሲመለምል ለነበረው ጣሊያንም ያን መለሎ፣ዠርጋዳ፣ወጠምሻ ዑመር አሊ ማግኘት ትልቅ ሲሳይ ነበር። ወጣቱ ዑመር አባስበር ዘወትር የሚናፍቀውን የወንድ ቦታ አግኝቶ፣ “ሸጋው ትርቡሊ” እየተባለ የሚዘፈንለትንሠራዊት ተቀላቀለ። ቦርድ ወጥቶ ወደ ጣሊያን እስኪመለስም ድረስ ወደ ስምንት አመት በየአረብ በረሃው ሲዋጋ ቆየ። ከዛም በኋላ ለዚያኑ ያህልጊዜ በጣሊያን አገር የዘመናዊ እርሻና አትክልት አዘማመር ሙያ ሲማርና ሲሰራ ቆይቷል። ወደ ኢትዮጵያ ተመልሶ፣ በአሥመራናመቀሌ ከተሞች ለብዙ ጊዜ እንደኖረ ይናገራል።
ገና ወዲያው መቀሌ እንደደረሰም ነው ያኔ የትግራይ ንጉስ ከነበሩት ከራስ ስዩም መንገሻ (የአፄ ዮሐንስ የልጅ ልጅ) ጋር የተዋወቀው። አብሮአቸው እንዲሰራም ሲጋብዙት ተስማምቶ በአስተርጉዋሚነት ከቤተመንግስታቸው መስራት ገና ከመጀመሩ ነበር ክርስትና ያነሱት።ዑመር አሊ ቀረና ገ/ሕይወት ካሳ የሚል አዲስ ስም አወጡለት። ‘ባላንባራስ’ የሚል ማዕረግም ሰጡት።
ባላንባራስ ገ/ሕይወት እድሜያቸው ገፋ ካለ በኋላ ነበር ወደ ትውልድ አገራቸው ባቲ ተመልሰው ሚስት አግብተው ልጅ መውለድ የጀመሩት። እስከዛ ድረስ መሃን ነኝ ብለው ይገምቱ የነበሩት ሰውዬ፣ አከታትለው ሦስት ልጅ ወለዱ። ሶስተኛ የተወለደውን ወንድ ልጅ በራስ ስዩም ስም ጠሩት። የስዩም ገ/ሕይወት ነፍስ፣ የህልውና ፊደሏን መቁጠር ጀመረች። አድጋም ከመብራት ህልውና ጋር ተሳሰረች። መብራት የማን ልጅ እንደሆነች ታቃላችሁ? የመብራት አባት አስር አለቃ አበራ ወልዱ የራሳቸው የራስ ስዩም ልጅ የሆኑት የራስ መንገሻ ስዩም ዋና አጃቢ ነበሩ። ታዲያ ይሄን ምን ትሉታላችሁ? ባላንባራስና ስዩምን ወደ መቀሌ ምን ጎተታቸው? አጋጣሚ ወይስ የህልውና አብሮነት አሻራ አዙሪት?
ስዩም ገ/ሕይወት ከእናቱ ተለይቶ ማደግ የጀመረው ገና የስምንት ወር ልጅ እያለ ነበር (በህመም ምክንያት) ። ባላንባራስም በአንቀልባ እያዘሉ፣ ወደ ስራቸው ቦታ ይዘውት ይሄዱና የፍየል ወተት የተሞላ ጡጦውን እያስታቀፉ ከዛፍ ጥላ ስር ደልድለው ያስተኙት ነበር። እዛበርሃ መሃል። ባላንባራስ ያኔ  ዱብቲ ተንድሆ አዋሽ ወንዝ ዳር የጥጥ እርሻ መሬት በማልማት ሥራ ላይ ተሰማርተው ነበር።
አባትም እናትም ሆነው ያሳደጉኝ ባላንባራስ ገ/ሕይወት፤ ገና ሦስት ዓመት ሳልሞላ የፍየል ሃሞት ያጠጡኝ እንደነበረ በደንብ አስታውሳለሁ። ፍየል ባረዱ ቁጥር የሃሞቱን ከረጢት ከሆድቃው መዝው ያወጡና “ናልኝ እስቲ ወዲህ የኔ አንበሳ... አንተነህ የወንዶች ወንድጀግና.... በል ያዝና ግጥም አድርጋት” እያሉ ይሰጡኝ ነበር። ታላቄ የነበሩት ወንድሜና እህቴ ከጎን ቆመው ያዩኛል። “እዩት እዩት የኔን ልጅ ፊቱ ትንሽ እንኳን ጨምደድ አይልም” ይላሉ ባላንባራስ። እኔም አንድ ጊዜ ጀግና የወንዶች ወንድ ተብሎ የተሰጠኝን ስም ላለመነጠቅ፣ ፊቴ ዘና እንዳለ ጭልጥ አደርጋታለሁ። በወንድነት ኩራትም እህትና ወንድሜን ጀነን ፈጠጥ ብዬ አያቸዋለሁ።
“ትንሽ ነገር አታስቡ” እያሉ ነው ያሳደጉኝ ባላንባራስ። “ትንሽ ነገር ማሰብ ትንሽ ያደርጋል። የኔልጅ ትልቅ ነህ። የሚያቅትህ ነገር የለም!!” ይሉኝ ነበር በየአጋጣሚው።ባላንባራስ የሚዝረከረክ ሰው አይወዱም። “ሰው ማለት ሁሉ ነገሩ ስትር ያለ ነው። ይሄ ልብሱን እንኳን በአግባቡ መሰተር ያቃተው ሰው፣ ምን የተሰተረ ህይወት ሊኖረው ይችላል።” ሲሉ እየሰማሁ ነው ያደግኩት።
ገና የአስራ ስድስት ዓመት ልጅ ሳለሁ ነው የሐርቡ ከተማ ወጣቶች ሊቀመንበር ሆኜ የተመረጥኩት። እንዴት እሳት የላሰ ምላስ እንደነበረኝ አስታውሳለሁ። ያኔ ነበር ሸዋየ እብዲቱ ‘የልጅ ሹም’ ትለኝ የነበረው። “አይ የልጅ ሹም..... የልጅ ሹምና የህዳር ጉም አንድ ነው”ትለኝ ነበር ባየችኝ ቁጥር። አስታውሳለሁ-- ጓደኞቼ ሁሉ የመንግስት ሠራተኞች ነበሩ፤ ካድሬ፣የግብርና ሚ/ር ሠራተኞች፣ አስተማሪዎች።
ከጥበብ ጋር ትውውቅ
በዛው እድሜዬ በወረዳው የታውቅሁ ሰዓሊ ነበርኩ። የመስከረም ሁለት ዓመታዊ በዓል ሲመጣ፣ አንደኛ ሆኖ የሚመረጠው አብዮታዊ ግጥም የኔ ነበር። ሰው ጢም አለበት አደባባይ ወደ መድረክ ወጥቼ አሸናፊ ግጥሜን ሳነብ ኩራቴ ወደር የለውም ነበር። የባላንባራስማ ኩራት ምኑ ተወርቶ። “ እንዴት ያለ ልጅ ነው ያለዎት አቦ አላህ ያሳድግልዎት” እያለ ሰው አድናቆቱን ሲገልፅላቸው፣ “ድሮስ የኔ ልጅ ምን ያቅተውና” ይሉ ነበር በኩራት ጀነን ብለው። በተመሳሳይ ጊዜ ነው በሐርቡ ከተማ የመጀመሪያውን ቤተመጽሐፍት ያቋቋምኩትና እዛው የመጀመሪያው አስነባቢ ላይብረሪያን ሆኜ መስራት የጀመርኩት። ትዝ ይለኛል እነዚያን ትርጉም የሩስያ ልብወለድ መጻሕፍት እንዴት አድርጌ እየተንሰፈሰፍኩ አነባቸው እንደነበረ።
እሚገርም እኮ ነው።  በጣም ከመጓጓቴ የተነሳ የነቻርልስ ዲክንስና ዶስቶይቪስኪ ትልልቅ የእንግሊዘኛ ልብወለድ መፃሕፍት ለመረዳት እታገል ነበር። ከእንግሊዘኛ ጋር የነበረን ፍጥጫ ትዝ ይለኛል። “እኔ ደግሞ ትሞታታለህ እንጂ አልገባህ” ይለኝ ነበር አያ እንግሊዘኛ።
እረስቼው....... ለካ በኪነትም ሃርሞኒካ ተጫዋቹ እኔው ነበርኩ።
እና ይሄውላችሁ ጉግሳ እንዳለ የኮረጀው  የሐርቡው ልጅ ስዩም፣ ልብወለድ ያልሆነው ታሪክ ይህን ይመስላል።
 “የቃሉ ሰው ቃል ማንጠር ይወዳል”
የቃሉ ሰው ከሆንክ ከቃሉ ጋር የሚኖርህ ፍቅር በእንዶድ ቢያጥቡት የሚለቅ አይደለም።የቃሉ ሰው ቃል ማንጠር ይወዳል። ተራው ሰው እንደ ዋዛ ጣል እሚያደርገው ነገር አባባል ሆኖ ይቀራል። ስነፅሁፍ ተፃፈም አልተፃፈም ያው ቃል ማንጠር ከሆነ ስነጽሁፍ የጀመረኝ ገና እኔ አድጌ ሳልጀምረው ነበር። ገና ብዕር ይዤ ልጻፍህ ሳልለው በፊት ነበር፣በልጅነቴ ቃል በገፍ የሚነጠርበትን ገበያ ሁሉ ማዘውተር የጀመርኩት። ከነ ሰይድዋ ሙሄ መች መለየት እወድ ነበር፡፡ እኔም ጅና የጠገበ ሸመሌን ይዤ በየለፍጀሌው (የሠርግ ዋዜማ ዘፈን ምሽት)፣ በየሠርጉ ሆታ፣ በአረፋው ጭፈራ እየታደምኩ፣ ያን የቃሉ ቃል እሸትእየዠመገግኩ ስቅመው፣ ያቺ ትንሽ ነፍሴ እንዴት ውስጧ ጥግብ እያለ ትመለስ እንደነበር ትዝ ይለኛል። የነ ሸህ ሁሴን ማሃዲ፣ የነሸህ ሙሃመድ አወልን መንዙማ ስሰማማ እንኳን ያኔ አሁንም ቢሆን ቀልቤን ይዞት ጥፍት ይላል። የነፍሴን ክሮች ልብን በሰመመን ጣቶችደበስበስ እያደረገ በሚያስተኛ የንዝረት ቅኝት ያርገበግባቸዋል። የእናቶቻችን ቡና እየጠጡ የሚፈለፍሉት የወግ እሸትስ የት ይረሳል።ቃልን በጽሁፍ የማንጠሩንም ስራ የጀመርኩት በዛውን ዘመን ነው። ለአብዮት በዓሉ፣ ለኪነቱ ማድመቂያ የሚሆኑ ግጥሞች እሞነጫጭር ነበር። አዎ እንዲያውም አንድ ነገር ትዝ አለኝ። እሱ ተጣፈው የሴትን ልጅ ልብ በአንድ ጊዜ ትኩስ ምጣድ ላይ እንዳረፈ ቅቤ ቅልጥነው የሚያደርገው ይባልለት የነበረ የፍቅር ደብዳቤም እፅፍ ነበር፤ለራሴ ሳይሆን ለሌሎች ጓደኞቼ። እኔማ አይናፋር ነበርኩ። አስታውሳለሁ አንድ ቀን ለጓደኛዬ የፃፍኩለት የፍቅር ደብዳቤ አምጥቶብኝ የነበረው መዘዝ። ደብዳቤው የተፃፈላት ልጅ ልክደብዳቤውን እንዳነበበች፣ እሱን ትታ ለምን እኔኑ ወዳ እርፍ አትልም መሰላችሁ። ጓደኛዬ መቼም ምን ቢማር ቢራቀቅ እንዲህ ያለ ደብዳቤ በህልሙም ሆነ በእውኑ ሊጥፍ እንደማይችል ለካ ልቧ ነግሯት ነበር።ሕይወት’ኮ ቅኔ ነች፤ ወርቁን ሳይሆን ሰሙን ብቻ እየኖርነው ሆኖ እንጂ።
 ቃሉና ቃሉ (አገሩ) እንዲህ በማይላቀቅ የፍቅር ቃልኪዳን ተሳስረው መኖራቸውን ሳስበው ግርም ይለኛል!
ሚክሎል -  ከጽንሱ እስከ ውልደቱ
ሚክሎል የተፀነሰው የሁነቴ አሻራ አካል ሆኖ ነው፣ እኔ ልብ ባልለውም።
መጀመሪያውኑ ከዘሩ ውስጥ ያልነበረ ነገር በኋላ የዛፍ ቅጠል፣ አበባና ፍሬ ሆኖ ሊታይ አይችልም። ቃለሚክሎል ከልቤ ውስጥ ሆኖ ኩኩሉሉ ሲል መሰማት የጀመረው ግን በኋላ ጊዜ የዩንቨርስቲ ተማሪ እያለሁ ተነስቶ የነበረውን የፖለቲካ ነውጥ ካሸተተ በኋላ ነበር።የዛን ጊዜ የዩኒቨርስቲ ተማሪ ትርምስን አባዜ በልቤ ውስጥ፣  የብላቴ ወታደር ማሠልጠኛ ጣቢያ ህይወቱን በፅሁፍ ልቅም እያደረግኩ እዘግብ ነበር - አንድ ቀን ወደ መፅሐፍ እቀይረዋለሁ በሚል ምኞት።ከዚህ ሁሉ በጣም ጠንካራ የሚመስሉኝ ግን እነዚህ ሁለት ምክንያቶች ናቸው። አንደኛው ከእውነት ስሪት ምንነት ጥያቄ ጋር ሁልጊዜ እንደተፋጠጠ የሚኖረው አእምሮዬ ነው። ገና ከልጅነቴ ጀምሮ እውነት እንደቡና ቁርስ ቂጣ ተቆራርሳ ልትኖር አይገባትም ይልየነበረው ልቤ ቂም አግቷል። “አንድ ፈጣሪ ከሆነ ያለው ለምን ብዙ እውነት ይኖራል። ብዙ እምነት ማለት’ኮ ብዙ እውነት ማለት ነው። እውነትማ አንድ ብቻ ትንፋሽ ነው እንጂ መሆን ያለበት። ፖለቲካ እንጂ እውነት እንዴት በጎራ ተከፋፍሎ ያዙኝ ልቀቁኝ እያለ፣በበላይነት ነግሶ ለመውጣት ይፋለማል። እውነትማ ገለልተኛ ገላጋይ ዳኛ እንጂ ጎራ የለየ አዋጊ ሊሆን አይገባውም። እውነት የጥያቄና መልስ አንድነቱን ጨርሶ፣ ሙሉነቱን ያለ የነበረ አንድ ትንፋሽ ካልሆነማ፣ መጀመሪያውኑስ እንዴት ሊፈጥረን ቻለ። የጥያቄና መልስእድሜውን ጨርሶ እንደ አለቀ እውነት ያልተቋጠረ፣ እስቲ የትኛው ትንተና፣ የትኛው ንድፈ-ሃሳብ ነው ወደ ድርጊት ተቀይሮ መፍጠር የቻለ።” ከዚህ ጥያቄጋ ግብግብ የሚገጥም መጽሐፍ የመጻፍ ህልሜ፣ ዘወር በል ብለውም ዘወር የማይል የመንፈሴ አውራጅና ማገር ሆኖይኖር ነበር።እውነቴን አይደለምን’ዴ? እውነት ያልሆነችውን ስንሆን እንከፋፈላለን፣ እርስ-በርስ እንገዳደላለን፣እውነት የሆነችውን ስንሆን ግን አንድ እንሆናለን፣እንፋቀራለን፤
ከራስም ከማህበረሰብም ጋር። ታዲያ መሆን ማለት ሌላ ምን ትርጉም አለው? የእራስን እውነትእንደ አንድ ያለቀ የህልውና ትርጉም ፈልጎ ከማግኘት ውጭ!ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ የሚገርም ነው። አንድም ቀን ባነበብኩት መጽሐፍ  እርካታ የማታውቀው ውስጠ ነፍሴ፣ ‘አንተ ልታነብ የምትፈልገውን ዓይነት መጽሐፍ መጻፍ አለብህ’ እያለች ሁልጊዜ ትሞግተኝ ነበር። አሁንም አልረካችም። ‘ሚክሎል፤የመቻል ሚዛን’ መጀመሪያህ፣እንጂ መጨረሻህ አይደለም ትለኛለች፤ እስካሁን።
ሚክሎል እና አንባቢው
ሚክሎል የመቻል ሚዛን በመጀመሪያ ህትመቱ አንባቢዎችን የመድረስ ችግር ነበረበት። የታተመው ቅጂ ብዛት ውስን፣ የስርጭቱ አያያዝ በአግባቡ ያልተደረገ ነበር። ምንም የማስተዋወቅም ሥራ አልተሰራለትም ነበር። እንደምንም ከብዙ ጊዜ በኋላም ቢሆን እጃቸውከገባው አንባቢዎችውስጥ፤ ‘ይሄ ሁልጊዜ ላነበው እፈልገው የነበረ፣ ሁሉን ነገር በአንድ ላይ አሰናድቶ የያዘ፣ መቼም ተሰርቶ የማያውቅ ሥራ ነው’ እያሉ እስካሁን አድናቆትና ከበሬታቸውን የሚገልፁልኝ ብዙ ናቸው። “ይሄ በጣም ከባድ መጽሐፍ ስለሆነ እኔ የምወደው ዓይነትአይደለም” የሚሉም አይብዙ እንጂ አሉ።
 ሚክሎል ላይ ያበቃል --?
ሚክሎል የመቻል ሚዛንን ያሳተምኩት በራሴ ገንዘብ ነበር። ከላይ እንደገለፅኩት፣ ስርጭቱ በጣም ብዙ ችግር ስለነበረበት የወጣውን ወጪ እንኳን መመለስ አልቻለም። ‘የማቃት አንጀት’ አብዛኛው ሥራው አልቆ የነበረ ቢሆንም እንደገና መጽሐፍ ማሳተም፣የሚታሰብ አልነበረም። ምንም እንኳን ምናቤ እጅግ በጣም ከፍ ያለ ቢሆንም በአጠቃላይ በሃገራችን ከነበረው ተጨባጭ እውነታ አንፃር፣ መጽሐፍ ተጽፎ ሊኖር እንደማይቻል ስረዳ፣ ብዕሬ፤”ምነው ገና ብዙ ለመውለድ ዱብ ዱብ ከማለቴ ወደ ኪስህ ከተትከኝ”  ስትለኝ  ሰምቼ፣እንዳልሰማሁ ዘጋኋት፤ ተውኳት። ‘ምናልባት አንድ ቀን ይሆናል..... አሁን ግን አልሆነም’ እያልኩ በልቤ የማቃት አንጀትን ረቂቅ ይዤ፣ ከነቤተሰቤ አገር ለቅቄ ወጣሁ። አሁን አስራ አራት ዓመት አልፎ፣ ከስንት ፍለጋ በኋላ አድነው የያዙኝ አድናቂዎቼ ጩኸት ቀሰቀሰኝ።ጠፍቷል ተብሎ ተስፋ የተቆረጠበት፣ሁለተኛውክፍል ‘የማቃት አንጀት’ ረቂቅም ከጓሮ አሮጌ ዕቃ ማጠራቀሚያ ጋራዥ ውስጥ አቧራ ለብሶ ተገኘ።


“እኔ በቁሜ ብሸለምም ሽልማቱ ለሌሉት ባልደረቦቼም ነው” (አርቲስት ዙፋን)

“ቆንጆ ቆንጆ ሴቶች ፈልጉ” ተብሎ ነው፤ተመርጬ የተቀጠርኩት
· ተወዛዋዥነት ለዘመናት ተንቆ የኖረ ሙያ ነው ትላለች

  የ50 ዓመት የኪነ ጥበብ ጉዞሽ እንደሚዘከር ቀደም ብሎ መረጃ ነበረሽ? በሰማሽ ወቅት ምን አልሽ? የአንጋፋ አርቲስቶችን የረዥም ዘመን የኪነጥበብ አገልግሎት መዘከር የተለመደ ይመስላል፡፡ ትክክል ነኝ?
የተሰማኝን ነገር እንኳን ልነግርሽ አልችልም፡፡ እግዚአብሄር እራሱ ሲፈቅድ ነው ሁሉም የሚሆነው፡፡ እኔ በቁሜ እያለሁ ይሄ በመደረጉ ከምነግርሽ በላይ ደስ ብሎኛል (በስሜት  እያለቀሰች) ምክንያቱም የውዝዋዜ ሙያ እንደ ሙያ፣ ሙያተኛውም እንደ ሙያተኛ ሳይቆጠር ዘመናት አልፈዋል፡፡ መጀመሪያ የ50ኛ ዓመት በዓሉ ሊከበር የነበረው መስከረም 27 ነበር፡፡ በመንግስት ስብሰባዎች ምክንያት ወደ ጥቅምት ሁለት ተዛወረ፤ ከዛ በኋላ እንደገና ወደ ጥቅምት 11 ተዛውሮ፣ እናትና ልጁ ሲፈቅዱ (ክርስቶስንና ማሪያምን ማለቷ ነው) ያው በዚህ ቀን በልዩ ሁኔታ ተከበረ፡፡ በዚህ አጋጣሚ ባህልና ቱሪዝምን ላመሰግን እወዳለሁ፡፡ የብሔራዊ ቴአትር የባህል ማዕከል ሰራተኛ የሆነችውን ወ/ሮ ብርሃንንም አመሰግናታለሁ፤ ብዙ ደክማለች ለዚህ በዓል፡፡ ድካምና መሰላቸት ሳይሰማት ለዚህ ክብር አብቅታኛለች፡፡ ለዚህ ክብረ - በዓል ብዙ የለፉትን ሌሎችንም ሁሉ በጣም አመሰግናለሁ፡፡
የውዝዋዜ ሙያና ሙያተኛው በተለየ ሁኔታ የማይከበሩበት ምክንያት ምን ነበር ?…
እኔ እንግዲህ መንታ አርግዤ እንደተገላገልኩ የምቆጥርባቸው ሁለት ነገሮች አሉኝ፡፡ ሙያውና ሙያተኛው እንደሙያተኛ አለመቆጠራቸውና ክብር አለማግኘታቸው አንዱ ያረገዝኩት ሃሳብ የነበረ ሲሆን ሁለተኛው የምንሰራው ብሔራዊ ቴአትር ይሁን እንጂ እኛ ተወዛዋዦች  የመንግስት አልነበርንም፡፡ ስለዚህ የጡረታ መብት አልነበረንም፡፡ ከዚያ ሰላማዊ ሰልፍ ወጥተን፣ የማዘጋጃ ቤት አንድ አርቲስት ህይወቱ አልፎ፣ ስንቱ በሳንጃ ተወግቶ ነው ጡረታችንን ያስከበርነው፡፡ ለ4 ወር ታስረን ሁሉ ነበር፡፡ በደምና በህይወት የተገነባ መብት ነው፡፡ የተወዛዋዡን ጉዳይ በተመለከተ ምንም ክብር አልነበረም፡፡ ቴአትር የሰራ፣ ዘፈን የዘፈነ፣ አሁን ዘመን ያመጣውን ፊልም የሰራ ጭምር ሲሸለም ታያለሽ፡፡ የኛን ሙያ ስታይና ስታስቢው ያሳለፍነው መከራ ይከብዳል፡፡ ከእኛ በፊት የነበሩ የዘርፉ ባለሙያዎች፤ በትንሽ ብር ደሞዝ ሀብት ንብረት ሳያምራቸው፣ ለሙያው ፍቅር ሲሰሩና መስዋዕትነት ሲከፍሉ ኖረዋል፡፡ ቀጣዮቹ እኛ ነን፤ ከኛም በኋላ የመጡ አሉ፡፡ ስለዚህ በተሰጠሽ ሙያ ተተኪን ታስተምሪያለሽ፤ ታሰለጥኛለሽ፤ ራስሽም ታገለግያለሽ፡፡ ለምን ብትይ… ያለፉት ለእኛ አስተምረዋል አገልግለዋል፡፡ በሌላ በኩል ተወዛዋዥ የሚሰራው ውዝዋዜ ብቻ አይደለም፡፡ ሁለገብ ነው፤ ቴአትርም ዘመናዊና ባህላዊ ውዝዋዜም… ብቻ ብዙ ነገር ይሰራል፡፡ ይህን ሁሉ የሚሰራው ሙያተኛ ግን አንድም ቀን ስሙ ሲጠራና ሲወደስ አትሰሚም፤ ሲሸለምም አታይም፡፡ ውዝዋዜ የዕድሜ፣ የጉልበትና የወጣትነት ስራ ነው፡፡ ለምን ስሙ አይነሳም? ለምን አይሸለምም? የሙዚቃ ማህበራት፣ የቲያትር ማህበራት፣ የፊልም ሰሪዎች ማህበራት አሉ፤ የውዝዋዜ ግን የለውም፡፡
እነዚህ ሁሉ ነገሮች ይቆጩሽ ነበር?
በጣም ይቆጨኝ ነበር… በጣም! እኔ እንደሚታወቀው፤ ለሚዲያም ቅርብ አይደለሁም፤ ግን አንድ ቀን እድል ገጥሞኝ ይህን ቁጭት እንደምናገረው እርግጠኛ ነበርኩ፡፡ ይሄው እግዚአብሔር ፈቅዶ፣ 50ኛ ዓመት ክብረ በዓሉ ሲከበር በደንብ ተናገርኩት፡፡ አንደኛ በእንዲህ መልኩ በውዝዋዜ ጥበብ 50 ዓመት ሰርታለች ተብዬ፣ ክብረ በዓሉ መዘጋጀቱ አንዱን አረገዝኩ ያልኩሽን ሃሳብ እንደመገላገል ነው፡፡ ሽልማቱ፣ ክብረ በዓሉና ዝግጅቱ የእኔ ብቻ ሳይሆን ከዚህ በፊት በዘርፉ ብዙ ሰርተው፣ ምንም ክብርና ሞገስ ሳያገኙ ላለፉት ሁሉ ነው፡፡ አንድ ሰው ግጥም ይጽፋል፣ ሌላው ዜማ ሊደርስ ይችላል፡፡ አቀናባሪው ሙዚቃውን ያቀናብራል፡፡ ከዚያ በኋላ ተወዛዋዡ መድረክ ላይ ይውረገረግበታል፡፡ እነዚህ ሁሉ ተቀናጅተው ነው አድማጭ ተመልካችን በቁጥጥር ስር የሚያውሉት፡፡ እንደ ጆሮ ሁሉ አይንም እኮ ሙዚቃን ማየት ይፈልጋል፡፡ ቪሲዲ የሚሰራው ለዚህ አይደለም እንዴ? ውዝዋዜ ለሙዚቃ የጀርባ አጥንት እኮ ነው፡፡
ከዚህ በፊት የተሸለሙ ተወዛዋዦች የሉም?
እርግጥ ባህልና ቱሪዝም እንዲሁም የኢትዮጵያ የባህል ማዕከል ይህን ሲያደርጉ የመጀመሪያቸው አይደለም፡፡ ለአርቲስት መርአዊ ስጦት፣ ለአርቲስት ደስታ ገብሬም ሲዘጋጅላቸው ነበርኩኝ፡፡ ነገር ግን ደስታ ገብሬ ማለት የኢትዮጵያን ብሔር ብሔረሰቦች ባህልና ውዝዋዜ በአሜሪካ፣ አውሮፓ፣ በአፍሪካና በክልል ስታስተዋውቅ ዘመኗን የጨረሰች ናት፡፡ ወዲህ ደግሞ ስትጨፍር አይን የምታፈዝ፣ አጥንት አላት የላትም እየተባለ የምታከራክር ትልቅ ባለሙያ፡፡ ከዚህ አንጻር አንደኛ በህይወት እያለች ባለመሸለሟ፣ ሁለተኛ ደግሞ በዝግጅቱ ቀን ብዙ ሰው ባለመምጣቱ በጣም ቅር ተሰኝቼ ነበር፡፡ አንድ ሰው ከሞተ በኋላ አበባ ማስቀመጥ፤ ወዲህ ወዲያ ማለት ጥቅም የለውም፡፡ እንደኔ በቁሙ ያለ ሰው፤ እንዲህ አይነት ክብር ሲደረግለት ግን እጅግ ያስደስታል፡፡
ያንቺ የ50ኛ ዓመት ክብረ በዓል ምን ይመስል ነበር? …
ከጅምሩ ልጆቼና የልጆቼ ጓደኞች ቀኑ ደርሶ ዝግጅቱ ሲጧጧፍ፣ እኔ በሌሊት ፀጉር ቤት ሄጄ ፀጉሬን ተሰርቼ ስመጣ፣ በራሴ መኪና እንደምሄድ ነበር የማውቀው፡፡ ልጆቼም የራሳቸው መኪና አላቸው፡፡ እናም በእናንተ ታጅቤ ስለምሄድ፣ መኪናችሁን አዘጋጁ፤ አገር ልብስም አዘጋጁና ልበሱ ብያቸው ነበር፡፡ ከፀጉር ቤት እንደመጣሁ ትንሿ ልጄ፤ “ማሚዬ፤ ዛሬ እኔ ነኝ ፕሮቶኮል፤ ተረጋጊ” አለችኝ፡፡  
ወደ ብሔራዊ የመጣሽው ግን በራስሽ መኪና ሳይሆን በሽንጠ ረጅም ሊሞዚን ነበር-----
ልክ ነው ልነግርሽ ነው፡፡ ከዚያ በቃ ገባሁ፤ ለበስኩና “በሉ እንዳናረፍድ እንውጣ” ስላቸው፣ “ቆይ ማሚ ትንሽ እንቆይ፤ ከዝግጅቱም ቦታ እየደወሉ ነው፤ እኛም በስልክ እየተገናኘን ነው” ይሉኛል፡፡ ልክ ወደ ውጭ ስወጣ፣ የ “ዋዜማ” ድራማ ካሜራ ማንን አየሁት፡፡ እንዴ እዚህ ምን ይሰራል ብዬ ገረመኝ፡፡ “ለምን እዚህ መጣህ ሳሚ?” አልኩት “ማሚዬ፤ ካንቺ ጋር ከቤትሽ ጀምሮ አብሬ መሄድ ፈልጌ ነው” አለኝ፡፡ እኔ አዳራሽ እንዲመጣ ነበር የጠራሁት፡፡ ለካ ከልጄ ጋር ተነጋግረው ኖሯል፡፡ ስወጣ ፎቶ እንዲያነሳኝ ተጠርቶ ነው፡፡ ከዚያ ለባብሼ ጨርሼ ስወጣ፣ ያን ሊሞዚን ተገትሮ አየሁት እልሻለሁ፡፡ ልጆቼና ቤተሰቦቼ ናቸው ሰርፕራይዝ ያደረጉኝ፡፡ ልጆቼ፣ ቤተሰቤና የልጆቼ ጓደኞች፤ በአበባ የታጀበውን ሊሞዚን ከበው እልልል ይባላል፡፡ በጣም ነው ያለቀስኩት! (አሁንም እያለቀሰች)
በደስታ ስሜት ----?
አዎ! አንደኛ ይህን ሁሉ ሳያዩ ያለፉ ተወዛዋዥ አስተማሪዎቼን አስቤ አለቀስኩ፡፡ እኔ የደረስኩበት አልደረሱም፤ ቢያንስ በህይወት ቢኖሩ ጡረታ ይወጡ ነበር፡፡ ለሙያው እየተሰጠ ያለውን ክብር ያዩ ነበር፡፡ በእነዚህ ምክንያቶች እንዲሁም ቤተሰቤና ልጆቼ ባደረጉት ነገርም በጣም ተደሰትኩኝ፡፡ ከዚያ እንባዬን መቆጣጠር አልቻልኩም፡፡ ማልቀስ ሲያንሰኝ ነው፡፡ በብሔራዊ ቴአትር፣ የአገር ፍቅር--- የባንዲራ ፍቅር------ የብሔር ብሔረሰብ ፍቅር… ያስተማሩን፣ ከአገራችን ወጥተን በዚያው እንዳንቀር፣ አገራችንን እንድንወድ ያደረጉን አንጋፋዎቹ አልፈዋል፤ ይህንን አላዩትም (አሁንም ለቅሶ…) እኔ በህይወት ቆሜ ብሸለምም ሽልማቱ የእነሱም ነው፡፡ በህይወት እያሉ በየጓዳው ተረስተው የቀሩ፣ በውጭም በስደት ህይወታቸውን የሚገፉ፣ ለሙያው መስዋዕትነት የከፈሉ ብዙ አሉ፤ ሽልማቱ የእነሱም ጭምር ነው፡፡
ሽልማትሽ ምን ነበር?
ብዙ ነገር ተሸልሜያለሁ፤ ወርቅ፣ ብርና የተለያዩ ነገሮችን ተሸልሜያለሁ፡፡ ከ “ዋዜማ” ድራማ አዘጋጆችና ተዋንያን፣ እንደ አዋርድ የሚሰጥ ሽልማት ተበርክቶልኛል፡፡ ከተለያዩ አርቲስቶችም በርካታ ሽልማት አግኝቻለሁ፡፡ ከሽልማቱ ይበልጥ የሚያኮራው ደግሞ እያንዳንዱ ሰው፤ ስለኔ የሚያወራውና የሚሰጠው ምስክርነት ነበር፡፡ “አልጋነሽ ማለት ይህቺ ናት፤ እሷ ማለት እንዲህ ናት---” ተብሎ በቁምሽ ስትሰሚ፤ከዚህ በላይ ደስታ የለም፡፡ ይህ ክብረ በዓል ተከታዮቻችንን ያበረታታል፤ ለሙያቸው ፍቅር እንዲኖራቸው ያደርጋል፡፡
ከብሔራዊ ቴአትር ጡረታ የወጣሽው መቼ ነው?
ጡረታ የወጣሁት 2001 ዓ.ም አካባቢ ነው፡፡ አሁን በግሌ ብዙ ስራዎችን በመስራት ላይ እገኛለሁ፡፡
በመሃል ግን ውጭ ቆይተሽ መጥተሻል፡፡ የሄድሽው ለስራ ነበር ወይስ ለእረፍት?
ጡረታ እንደወጣሁ አሜሪካ ሄጄ፣ ሁለት ዓመት ቆይቼ ነው የተመለስኩት፡፡ እንደተመለስኩም፤ በየሻሽ ወርቅ በየነ የተዘጋጀ “ደመነፍስ” የሚባል ቴአትር አስተባብር ነበር፡፡ እስከ ዛሬዋ ቀን ድረስ እየሰራሁ ነው ያለሁት፤እግዚብሔር ይመስገን፡፡
በአሁኑ ወቅት “ቃቄ ወርዲዮት”፣ “ዋዜማ” ---- ላይ እሰራለሁ፡፡ ይኼው ለብሔራዊ ቴአትር 60ኛ ዓመት ክብረ በዓል ዝግጅትም እየሰራን ነው፡፡ እኔ ጡረታ ብወጣም ከቤቱ አልወጣሁም፡፡ ብሔራዊ ቴአትር፤ ለእኔ አባቴም እናቴም፣ለእዚህ ሁሉ ያበቃኝ ስለሆነ ከዚህ መራቅ አልፈልግም፡፡ ከታላቆቼም ከታናሾቼም… በቤቱ ካሉ የአስተዳደር ሰራተኞችም ጋር ተዋድጄ ነው የምኖረው፡፡
እስኪ ወደ ኋላ ልመልስሽ ----- ትውልድና እድገትሽ የት ነው?
ተወልጄ ያደግሁት ጎጃም ውስጥ ነው፡፡ በጣም ትንሽ ሆኜ ነው አዲስ አበባ የመጣሁት፡፡ እዚሁ ነው ያደግኩት፡፡ የጎጃም ተወላጅ ሆኖ አዲስ አበባ የሚኖር ሰው አግብቶ በልጅነቴ ይዞኝ መጣ፡፡ ያው እንደሚታወቀው፣ በዛን ዘመን ልጅ ሆነሽ ትዳሪያለሽ፤ ለአቅመ ሄዋን እስክትደርሺ ባልሽ ጋ ታድጊያለሽ፤ እኔም በዚህ መልኩ አግብቼ ሊያስተምረኝ አመጣኝ፤ አልተመቸኝም፤ ወደ አገሬ ተመለስኩኝ፡፡ ከዚያ ብዙ ሳልቆይ አክስቴ አዲስ አበባ አመጣችኝ ግን የሚያስተምረኝ አልተገኘም፡፡ ከዚያ ወደ ብሄራዊ ቴአትር መጣሁና ተቀጠርኩኝ፡፡ ዋናው ነገር በአሁኑ ሰዓት ደስ የሚለኝ፤ እኔ ያላገኘሁትንና የተቆጨሁበትን ትምህርት፤ በወንድሞቼ፣ በልጆቼ፣ በዘመዶቼ ተወጥቼዋለሁ፡፡ አሁን ያስተማርኳቸው ፕሮፌሰር፣ ዶክተር ወንድሞች አሉኝ፡፡ ልጆቼንም አስተምሬያለሁ፤ ሁሉም በጥሩ ሁኔታ ላይ ነው የሚገኙት፡፡
ብሔራዊ ቴአትር እንዴት ተቀጠርሽ?
ያን ጊዜ የባህልም የዘመናዊም ተወዛዋዥ እንዲኖራቸው አርቲስት አውላቸው ደጀኔ ጥያቄ አቀረቡ፡፡ በባህሉ በኩል የራሳቸው ተወዛዋዦች እንዲኖራቸው ሲፈቀድላቸውም “ቆንጆ ቆንጆ ሴቶች ፈልጉ” ተብሎ፤ተፈልጌ ነው ተመርጬ የተቀጠርኩት፡፡
ያው መልክሽም ቁመትሽም የሰጠ ሆኖ ተገኘሽ?    እንዴታ! መልክና ቁመና፣ ቅጥነት ጭምር መስፈርት ነበር፡፡ በወቅቱ ስንፈተን ደግሞ ዝም ብሎ ፈተና እንዳይመስልሽ፡፡ እስከ ላይ እስከ ጭንሽ ድረስ ልብስሽን ገልበሽ፣ አንዲት ጠባሳ በሰውነትሽ ላይ ካለ፣ አታልፊም፡፡ ፈታኙ በወቅቱ አርቲስት ጌታቸው ደባልቄ ነበር፡፡ ጠባሳው ብቻ ሳይሆን አቋቋምሽም ይታያል፤እግርሽ ቀጥ ያለ መሆን አለበት፤ወልገድ ሸፈፍ ካልሽ አለቀልሽ፡፡
 የበረራ አስተናጋጆች  እንደሚመለመሉት ማለት ነው?
እንደዚያ ነው! ከባድ ነበር ፈተናው፡፡ ከዚያ ስድስት ልጆች ተመረጥን፡፡ የሚገርምሽ ስድስታችንም በህይወት አለን፡፡
እስኪ እነማን እንደነበራችሁ ----- የሌሎቹን ስም ንገሪኝ?
አልማዝ ሀይሌ (ማሚ)፣ አሰለፈች በቀለ፣ ወይንሸት በላቸው፣ አበበች ገ/ሚካኤል፣ አሰለፈች  ገሰሰ፣ አልጋነሽ ታሪኩ ነን፡፡ ፍቅርተ ጌታሁን ሰባተኛ ናት፡፡ አሰለፈች ገሰሰና አሰለፈች በቀለ ውጭ ነው የሚኖሩት፤ ሌሎቻችን እዚሁ አለን፡፡ አሁን ለብሔራዊ ቴአትር 60ኛ ዓመት፣ ወገባችንን ስናውረገርግ ለማየት ያብቃሽ እንግዲህ፡፡
ብሔራዊ ቴአትር በስንት ዓመትሽ ነበር የተቀጠርሽው?
ምናልባት 16 ዓመት ቢሆነኝ ነው፤ በጣም ልጅ ነበርኩኝ፡፡
ውዝዋዜ ያቆምሽው መቼ ነው?
ለ24 ዓመት በውዝዋዜ ከሰራሁ በኋላ ነው ያቆምኩት፡፡ ለምን አቆምሽ ብትይ…በድሮ ጠቅላይ ግዛት፣ በአሁኑ ክ/ሀገር ስትሄጂ፣ ውዝዋዜም ቴአትርም ይዘሽ ሄደሽ ነው የምትሰሪው፡፡ ስለዚህ ባህል ትሰሪያለሽ፤ መሀል ላይ ቴአትር ትሰሪና ከዚያ በባህል ትዘጊያለሽ፡፡ ወይም ባህልና ዘመናዊ፣ ከቴአትር ጋር ይዘሽ ትሄጂና በዘመናዊ ዳንስ ትዘጊያለሽ… እንዲህ ነበር የሚሰራው፡፡ ከኢትዮጵያ ውጭ የብሄር ብሄረሰቦችን ስራ እንሰራለን፤ ፈረንጅ ቋንቋችንን ስለማያውቀው፣ማይም የሚሰራበትም ጊዜ አለ፡፡
በዚህን ወቅት መጀመሪያ የውብሸት ወርቃለማሁ ድርሰት የሆነውን “አንድ ለሶስት” ድራማ ሰርቻለሁ፤ “ሀሁ በስድስት ወር” ላይ የለማኝ ገፀ ባህሪ፣ “እናታለም ጠኑ” የጉሊት ሽንኩርት ነጋዴ፣ “ሀኒባል” ላይ ወታደር፣ “ቴዎድሮስ” ላይ የንግስቲቱ ገረድ ሆኜ ------ ተጫውቻለሁ፡፡ ከዚህ በኋላ በመዋቅር ዝውውር ወደ ቴአትር ክበብ ገባሁ፡፡
በማስተባበር ደረጃ እነ “ደመነፍስ”ን አስተባብሬያለሁ፡፡ በ “ገመና” አንድ ላይም የቃልኪዳን አክስት ሆኜ ሰርቻለሁ፡፡ አሁን “ዋዜማ” ድራማ ላይ ታማሚዋ ጥሩዬን ሆኜ እየሰራሁ ነው፡፡ ገና ያልታየ “የኔ ዘመን” ፊልም ላይ እየተወንኩ ነው፤ በቅርቡ ተጠናቅቆ ይመረቃል፡፡ “ይግባኝ” ላይም ዳኛ ሆኜ ሰርቻለሁ፡፡
እኔ የምለው ----“ይግባኝ”፣ “የባላገር ፍቅር”፣ “በእንቅልፍ ልብ“፣ “ዋናው ተቆጣጣሪ”፣ የተሰኙት ቴአትሮች ላይ የተወንሽው ወደ ቴአትር ክፍል ከተዛወርሽ በኋላ ነው?
ልክ ነው ግን አሁን ጠፋብኝ እንጂ በማስተባበርም በመተወንም ብዙ ሰርቻለሁ፡፡ “ስሌት” ፊልም ላይም ተውኛለሁ፡፡
ብሔራዊ ቴአትር ውስጥ መኪና የገዛሽ የመጀመሪያዋ አርቲስት አንቺ ነሽ ይባላል፡፡ ይሄ እውነት ነው?
ልክ ነው፤ በ1966 መስከረም 19 ቀን ነው መኪናዬ ከሞኤንኮ የወጣው፤አዝዤ ነው ያስመጣሁት፡፡ በደርግ ጊዜ እሱ መኪና ነዳጅ ይበላል ተብሎ እንዲገባ አይፈቀድም ነበር፤ ላለፉት 40 ዓመታት ነድቼዋለሁ፡፡ አሁን 41ኛ ዓመቱን ይዟል፤እሱ ቀለም እንዲቀባ ጋራዥ ገብቷል፡፡ አሁን ልጆቹ ለልደቴ ኮሮላ መኪና ገዝተውልኝ ነው የምነዳው፡፡ ከብሔራዊ ቴአትር የመጀመሪያ መኪና ገዢ ብሆንም ከሃገር ፍቅር አሰለፈች አሽኔና ዘነበች ታደሰ (ጭራ ቀረሽ) ቀድመውኝ ገዝተው ነበር፡፡
ስንት ልጆች አሉሽ?
ሶስት ሴቶች ልጆች አሉኝ፡፡ በጥሩ ሁኔታ ነው ያሳደግኋቸው፡፡ አንዷ ዲፕሎማና ዲግሪዋን ይዛ የራሷን ስራ ትሰራለች፡፡ አንዷ አግብታ፣ አንድ ልጅ ወልዳለች፤ ሆስተስ ናት፡፡ አንዷም አግብታ አሜሪካ ነው የምትኖረው፡፡ በዚህ ሁኔታ ላይ ይገኛሉ፡፡



    ከ2000 በላይ የጠቅላላ እውቀት ጥያቄና መልሶችን የያዘውና በድጋሚ ተሻሽሎ የታተመው “ምን ያህል ያውቃሉ” የተሰኘ መፅሐፍ ለ6ኛ ጊዜ ታትሞ ለንባብ በቃ፡፡ በቁምነገር መፅሔት ባለቤትና ስራ አስኪያጅ በጋዜጠኛ ታምራት ኃይሉ የተሰናዳው የጠቅላላ እውቀት መፅሀፍ፤ በቴክኖሎጂ፣ በኢኮኖሚ፣ በስነ-ፅሁፍ፣ በህክምና፣ በህግ፣ በታሪክ፣ በጠፈር፣ በቱሪዝም፣ በስፖርትና በሌሎች በርካታ ጉዳዮች ላይ እንደሚያተኩር ለማወቅ ተችሏል፡፡
 መፅሀፉ ለታዳጊም ሆነ ለአዋቂዎች እድሜ ሳይገድብ እውቀትን ለማስፋፋት ይረዳል የተባለ ሲሆን በየጊዜው እየተሻሻለና አዳዲስ ነገሮችን እያካተተ እንደሚሄድ ታውቋል፡፡መፅሀፉ በ193 ገፆች ተቀንብቦ፣ በ48 ብር ከ65 ሳንቲም ለገበያ ቀርቧል፡፡  

አንዳንድ ዕውነተኛ ክስተቶች ሲቆዩ ተረት ይመስላሉ፡፡ የሚከተለው እንደዚያ ዓይነቱ ነው፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን፣ ከዓመታት በፊት፣ እዚሁ እኛ አገር የቀበሌና የከፍተኛ የሶስት ወር የሂሳብ ሪፖርት፣ ይሰማ ነበር ይባላል፡፡ በዚህ ስብሰባ ምክንያት የታሠሩ አንድ ሰው ለእሥር መዝጋቢው የነገሩት ነው፡፡ እንዲህ አሉ፤ “ሪፖርቱን ይሰማ ዘንድ የቀበሌው ነዋሪ ግዴታ አለበት፡፡”
በዚሁ መሰረት የዚያን ዕለት የቀበሌው ህዝብ ግልብጥ ብሎ ወደቀበሌው አዳራሽ መጥቷል፡፡
ሰብሳቢው -
“እንደለመደው የቀበሌያችንን የፋይናንስ ሪፖርት እናዳምጣለን” አሉ፡፡
ይሄኔ እኔ፤
“ከዚያ በፊት እኔ አንድ አስተያየት አለኝ” አልኩ፡፡
ዕድል ተሰጠኝ፡፡
(በዚያን ዘመን ገዢ የነበረው መንግሥት - “የጊዜያዊ ወታደራዊ አስተዳደር ደርግ” ነበር የሚባለው፡፡ የሽማግሌው አስተያየት ይህን ስም በተመለከተ ነበር)
“በተሰጠኝ ዕድል በመጠቀም የመንግሥታችን ስም “ጊዜያዊ” የሚለው ልክ አይደለም፡፡ ይሄን ሁሉ ዓመት አስተዳድሮን ዘላቂ የማይሆንበት ምክንያት አይታየኝም፡፡ ስለዚህ ከዛሬ ጀምሮ “ጊዜያዊ” የሚለውን እንሰርዝና ዘላቂ እናድርገው” አልኩ፡፡
ህዝቡ በሁለት ተከፍሎ ሙግት ገጠመ፡፡ የጠዋቱ ስብሰባ እስከ ከሰዓት ዘለቀ፡፡ ሰብሳቢው ተናደዱና፤
“ስብሰባው ለሌላ ቀን ተዛውሯል” አሉና በተኑት፡፡
ከዚያ እኔም እንደሌላው ሰው ወደ ቤቴ እየሄድኩ ሳለሁ
“ትፈለጋለህ” ብለው ወደ እሥር ቤት አመጡኝ፡፡ ምን አጠፋሁ? ብል፤ “የፋይናንስ ስብሰባ አደናቅፈሃል!” አሉኝ… ካሉ በኋላ ወደ መዝጋቢው ፍርጥም ብለው ዞረው፤ “ይሄውልህ ወዳጄ፤ ይሄ መንግሥት ለምን ዕድሜ ጨመርክልኝ ብሎ አሠረኝ፡፡ ባጭሩ መቀጨት ነው እንዴ የሚፈልገው?” አሉ፡፡
***
ብዙ መንግሥታት የሚበጃቸውን አያውቁም፡፡ የሚጠቅማቸውን ሲመከሩ፣ በግድ ምክሩ ከራሴ ወገን ካልመጣ በሚል ይመስላል፤ አሻፈረኝ፣ አልሰማም ይላሉ፡፡ አንድ የትምህርት ሚኒስቴር ሹም እንዳሉት ነው፡፡ አንድ ጊዜ አንድ ወጣት የዩኒቨርሲቲ ምሩቅ ኃላፊው አልሰማ እያሉ ሲያስቸግሩት፤
“ይሆናል ሲሉዎት አይሆንም
አይሆንም ሲሉዎት ይሆናል፤
የርሶ ነገር ምን ይሻላል?”
ሲል ፃፈላቸው፡፡
ኃላፊው የመለሱለት፤
“ተጣጥሮ መሾም ነው!” የሚል ነበር፡፡
ይህ ዕውነታ ዛሬም የሚከሰት ነው፡፡ ልዩነቱ ዛሬ በግልፅ ሹሞቹ እንቢታቸውን አለመግለፃቸው ነው፡፡ አለመሰማማት ክፉ አባዜ ነው፡፡
የምክሩን ምንነት እንጂ የመካሪውን ማንነት ብቻ ማየት ከጥንት ጀምሮ ጐጂ ባህል ነው፡፡ ምክሩን አውቆና መርምሮ፣ ጠቃሚውንና ጐጂውን መለየትም ያባት ነው፡፡ ሁሉም ነገር ሂደት መሆኑን አለመርሳት ብልህነት ነው፡፡
አዲስ ሃሳብን እንደጠላት ማየት የዋህነት ነው፡፡ ሁሌ በአንድ ሀዲድ ላይ መሄድ ለውጥን ያርቃል እንጂ አያቀርብም፡፡ ፕሮጄክቶች ሥራ ከመጀመራቸው በፊት፣ ዕቅዶች ከመተግበራቸው በፊት፣ የሚቀርቡ የሥጋት አስተያየቶችን ለእንቅፋትነት የተሰነዘሩ አድርጐ ማየት በተለይ ከተለመደ፤ አደገኛ ነው፡፡ የሚያመላክተውም የአሉታዊነት ኃይልን (Negative Energy) ነው፡፡
አለመቀበልን “እኔ ያልኩት ብቻ ነው ልክ” ማለትን፣ አልፎ ተርፎም ፍርደ ገምድልነትን ነው የሚያመጣው፡፡ ያ ደሞ ፀረ - ዲሞክራሲ ነው፡፡ ሥራዎች ከተሠሩ በኋላ “ይፍረሱ”፣ “እንደገና ይስተካከሉ”፣ “መጀመሪያም ፕላኑ ችግር ነበረበት” ማለት ጊዜን፣ የሰው ኃይልን፣ ገንዘብና ንብረትን ማባከን መሆኑን መቼም ማንም ጅል አይስተውም፡፡  ብዙ ተብሏል፡፡ አልተሰማም፡፡ ሆኖም መንግሥት ባይሰማስ እኛ ምን እናድርግ? ብሎ ማሰብም ደግ ነው፡፡ ሁሌ መንግሥትን በመጠበቅ ህዝብ ተባብሮ መሥራት የሚችለውን ተሳትፏዊ ተግባር አለመፈፀምም ደካማነት ነው፡፡ ለምሳሌ በ1966 ዓ.ም ድርቅ ወቅት የዩኒቨርሲቲ መምህራንና ተማሪዎች፤ ወሎና ትግራይ ድረስ በራሳቸው ወጪ ሄደው ህዝቡን ለመታደግ ጥረዋል፡፡ ዛሬም እንደዚያ ማሰብ ጠቃሚ ነው፡፡ ህዝብ በረሃብ ሲጐዳ እጅን አጣምሮ መቀመጥ፤ “ያንተ ቤት ሲንኳኳ ይሰማል እኔ ቤት” የሚለውን መዘንጋት ነው፡፡ ችግሩ ያገር ነውና አገር መረባረብ አለበት፡፡ ህዝብ የሚቻለውን ማድረግ አለበት፡፡ አለበለዚያ “ሁሉ ፈረስ ላይ ከወጣ ማን መንገድ ያሳያል” ይሆናል፡፡

     በኢንተርኔት ነጻነት ከ12 የአፍሪካ አገራት የመጨረሻውን ደረጃ ይዛለች ቻይና የኢንተርኔት ነጻነት በመገደብ 1ኛ ናት
    የኢንተርኔት ነጻነት በአለማቀፍ ደረጃ ለአምስት ተከታታይ አመታት እያሽቆለቆለ እንደሚገኝና ኢትዮጵያም የኢንተርኔት ነጻነት ከሌለባቸው የአለማችን አገራት አንዷ መሆኗን “ፍሪደም ሃውስ” የተባለው አለማቀፍ ተቋም ሰሞኑን ባወጣው አመታዊ ሪፖርት አስታወቀ፡፡ተቋሙ በ65 የአለማችን አገራት ላይ ያካሄደው የ2015 የኢንተርኔት ነጻነት ጥናት ሪፖርት፣ ከአለማችን አገራት የከፋ የኢንተርኔት ነጻነት የተንሰራፋባት ቻይና መሆኗን ጠቁሞ፣ ጥናቱ ካካተታቸው 12 የአፍሪካ አገራት መካከልም ኢትዮጵያ በኢንተርኔት ነጻነት የመጨረሻውን ደረጃ ትይዛለች ብሏል፡፡
2.9 በመቶ የኢንተርኔት አገልግሎት ሽፋን ባለባት ኢትዮጵያ፣ የማህበራዊ ድረ ገጾችና የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ አፕሊኬሽኖች እንዲሁም ፖለቲካዊና ማህበራዊ ይዘት ያላቸው ጽሁፎች ይታገዳሉ፣ ጦማርያንና የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ተጠቃሚዎችም ይታሰራሉ፣ ፕሬሱም ነጻ አይደለም ብሏል፡፡
በአገሪቱ የኢንተርኔት አቅርቦትና ተደራሽነት ችግሮች እንዳሉ የጠቆመው ሪፖርቱ፣ የአገልግሎት መቆራረጥና አዝጋሚነት በስፋት እንደሚያጋጥምና በአይሲቲው ዘርፍ ለሚሰማሩ ገለልተኛ ተቋማትና ስራ ፈጣሪዎች የሚሰጠው ዕድልም እጅግ ውስን ነው ብሏል፡፡የ2007 አገራዊ ምርጫ መቃረቡን ተከትሎ በርካታ ተጽዕኖ ፈጣሪ ዜናዎች እንዳይሰራጩ ታግደዋል፣ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ድረገጾችም አገልግሎት እንዳይሰጡ ተደርገዋል ያለው ሪፖርቱ፤ ከ100 በላይ ድረገጾችም አሁንም ድረስ ታግደዋል፤ መንግስት በኢንተርኔትና በሞባይል በሚደረጉ ግንኙነቶች ላይ የሚያደርገውን ክትትልና ስለላ አጠናክሮ ቀጥሏል ብሏል፡፡
መንግሥት በበኩሉ ከተቃዋሚ ፓርቲዎች የሚሰነዘሩ ተመሳሳይ ትችቶችን ማስተባበሉ ይታወቃል፡፡ የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለስልጣን በቅርቡ እንደገለፀው፤ የኢንተርኔት ስርጭትና አጠቃቀምን ለመቆጣጠር የሚያስችል ህግ ይፀድቃል፡፡
ኢትዮጵያ በርካታ ጋዜጠኞችን በማሰር ቀዳሚ ከሆኑት የአለማችን አምስት አገራት አንዷ ናት ያለው ሪፖርቱ፣ ከ2014 እስከ 2015 ባለው ጊዜም፣ መንግስት ሃሳባቸውን በገለጹ ጦማርያንና በድረገጽ ጋዜጠኞች ላይ የሚያደርሰውን እንግልትና እስራት አጠናክሮ ቀጥሏል ሲል ገልጿል፡፡የ2015 የኢንተርኔት ነጻነት ሪፖርት እንደሚለው፤ ጥናት ከተደረገባቸው 65 የአለማችን አገራት መካከል ነጻ የተባሉት 18 ሲሆኑ፣ 28 አገራት የተወሰነ የኢንተርኔት ነጻነት እንዳለባቸው፣ 19 አገራት ደግሞ  የኢንተርኔት ነጻነት እንደሌለባቸው ተረጋግጧል፡፡


“የእህል ምርት፣ ከአምና የበለጠ እንጂ ያነሰ አይሆንም”…ግብርና ሚኒስቴር “እንደ ኢትዮጵያ በድርቅ የተጐዳ የለም፤ 15 ሚሊዮን ሰው ሊራብ ይችላል”…ለጋሾችየዝናቡ መጠን ካለፈው ዓመት በ40 በመቶ ቀንሷል

ባለፉት 30 ዓመታት ባልታየ ከፍተኛ ድርቅ ሳቢያ፣ የተረጂዎች ቁጥር 15 ሚሊዮን ሊደርስ ደሚችል የተገለፀ ሲሆን ግብርና ሚኒስቴር በበኩሉ፤ የዘንድሮ የእህል ምርት ከአምናው የበለጠ ይሆናል አለ፡፡ በኤሊኖ ምክንያት፣ እንደ ኢትዮጵያ በድርቅ የተጐዳ አገር ካለመኖሩም በተጨማሪ፣ ካለፈው አመት ጋር ሲነፃፀር የተረጂዎች ቁጥር ከ3 ሚሊዮን ወደ 8 ሚሊዮን እንደጨመረ መንግስትና ለጋሾች በጋራ ገልፀዋል፡፡ ከጥቂት ወራት በኋላም የተረጂዎች ቁጥር 15 ሚ. ሊደርስ ይችላል ብለዋል - ለጋሾች፡፡ ግብርና ሚኒስቴር በበኩሉ፣ ትናንት በሰጠው መግለጫ፣ ድርቁ ከባድ ቢሆንም፣ ከፍተኛ የእህል አምራች አካባቢዎች ላይ ብዙ ጉዳት አልደረሰም ብሏል፡፡ ዘንድሮ ምን ያህል እህል እንደሚሰበስብ፣ በስታትስቲክስ ኤጀንሲ ጥናት ይካሄዳል ያሉት የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ፤ ጥቅል የሀገሪቱ የእህል ምርት እንደማይቀንስ ግን በጥቅል ዳሰሳ

ለሳተላይት ሥርጭቱ ከ12ሚ. ብር በላይ ዓመታዊ በጀት ጸድቋል

    የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ በሀገር ውስጥና በዓለም ዙሪያ ለሚገኙ፣ ምእመና ድምፅዋን የምታሰማበትና መረጃ የምትሰጥበት የ24 ሰዓት የቴሌቪዥን አገልግሎት እንድትጀምር ቅዱስ ሲኖዶስ ወሰነ፡፡
ከጥቅምት 12 ጀምሮ የዓመቱን የመጀመሪያ የምልአተ ጉባኤ መደበኛ ስብሰባ በማካሔድ ላይ የሚገኘው ቅዱስ ሲኖዶስ፣ የቴሌቪዥን አገልግሎቱን ለማስጀመር ከ12 ሚሊዮን ብር በላይ ዓመታዊ በጀት ከትላንት በስቲያ ማጽደቁ ታውቋል፡፡
በጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የብዙኃን መገናኛ ድርጅት በሚል ተዋቅሮ ሥራ አስኪያጅ በመሠየምና እስከ 22 ሠራተኞችን በመቅጠር የሚጀምረው አገልግሎቱ፤ ዝግጅቱንና ቀረጻውን በሀገር ውስጥ በማከናወን በሳተላይት እንደሚሠራጭ ተገልጿል፡፡
 በስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያ ተልእኮ መምሪያ የበላይ ሓላፊ ሊቀ ጳጳስ የሚመራውና ዘጠኝ አባላት ያሉት የብዙኃን መገናኛ ቦርድ፣ የሳተላይት ሥርጭት አገልግሎቱን የሚሰጠው የኮሚዩኒኬሽን ኩባንያ በመምረጥ ሥራውን ለመጀመር እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ ተጠቅሷል፡
በሚዲያ ጥቅም፣ አሠራርና የወደፊት አቅጣጫ ለምልአተ ጉባኤው አባላት ማብራሪያ የሰጡት የቦርዱ አመራሮች፤ የሳተላይት ሥርጭቱ መካከለኛው ምሥራቅን፣ ደቡብ አውሮፓን፣ ሰሜንና ምሥራቅ አፍሪቃን እንደሚያካልልና ለተቀረው ዓለም ዝግጅቱን በኢንተርኔት በመጫን እንደሚያስተላልፍ አስረድተዋል፡፡
 በሀገር ውስጥና በዓለም ዙሪያ ከ50 ሚሊዮን ያላነሱ አገልጋዮችና ምእመናን ያሏት ቤተ ክርስቲያኒቱ፣ ተከታዮቿን ለማስተማርና ለመጠበቅ የምትችልበት ተጨማሪ ሚዲያ ካላመቻቸች በተለይም ተረካቢውን ወጣት ትውልድ ለመድረስ እንደሚያስቸግራት፣ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል ተናግረዋል፡፡
 የሚዲያ ጥናት እና የገቢ አሰባሳቢ ኮሚቴውን በማስተባበርና የውጭ ተሞክሮዎችን በመዳሰስ ጥረት ሲያደርጉ የቆዩት አቡነ ሳሙኤል፣ የቴሌቪዥን አገልግሎቱ ቤተ ክርስቲያኒቱ መሠረተ እምነቷን፣ ሥርዐቷን፣ ትውፊቷንና ታሪኳን ለማስተማር፤ ቅዱሳት መካናቷንና ቅርሶቿን ለማስተዋወቅ፤ ለጥናትና ምርምር ለማነሣሣት፤ በየአህጉረ ስብከቱ የተሠሩ መልካም ሥራዎችን በማቅረብ የምእመኑን ድጋፍ ለማግኘት እንደሚረዳት “ሚዲያ እና ዓለምአቀፋዊ አስተሳሰብ” በሚል ርእስ ባቀረቡት ጽሑፍ አስረድተዋል፡፡

የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ዘንድሮና ቢያንስ በ7 በመቶ ያድጋል ተብሏል

     አለማቀፉ የገንዘብ ተቋም አይ ኤም ኤፍ፤ ከሰሃራ በታች የሚገኙ የአፍሪካ አገራት የ2015 የኢኮኖሚ ዕድገት በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚቀንስና ባለፉት ስድስት አመታት ከተመዘገቡት የአካባቢው
የኢኮኖሚ ዕድገቶች ዝቅተኛው እንደሚሆን መተንበዩን ቢቢሲ ዘገበ፡፡ተቋሙ ባለፈው ማክሰኞ ይፋ ባደረገው የአካባቢው የግማሽ አመት የኢኮኖሚ ዕድገት ትንበያ እንዳለው፣ አምና 5 በመቶ የነበረው የኢኮኖሚ ዕድገት ዘንድሮ ወደ 3.75 በመቶ ዝቅ እንደሚል የሚጠበቅ ሲሆን፣ ለኢኮኖሚ ዕድገቱ መቀነስ በምክንያትነት ከተጠቀሱት ዋና ዋና ጉዳዮች መካከልም የነዳጅና የሸቀጦች ዋጋ መቀነስ እንዲሁም በቻይና ኢኮኖሚ ላይ የታየው መቀዛቀዝ ይገኙበታል፡፡ከሰሃራ በታች ያሉ የአፍሪካ አገራት የዘንድሮ የኢኮኖሚ ዕድገት ከአገር አገር የተለያየ እንደሚሆን የጠቆመው ተቋሙ፤ ኮትዲቯር፣ ኢትዮጵያና ታንዛኒያን የመሳሰሉ አገራት ዘንድሮና በቀጣዩ አመት የ7 በመቶ እና ከዚያ በላይ ዕድገት እንደሚኖራቸው ይጠበቃል ብሏል፡፡የነዳጅ ዋጋ ከ2014 አጋማሽ ጀምሮ ከግማሽ በላይ መቀነሱ፣ ናይጀሪያ እና አንጎላን የመሳሰሉ የነዳጅ ላኪ አገራትን በተለየ ሁኔታ ተጎጂ አድርጓል ያለው ተቋሙ፤ ዛምቢያ፣ ጋና እና ደቡብ አፍሪካን የመሳሰሉ የሚኒኔራል ላኪ አገራትም በሸቀጦች ዋጋ ቅናሽ ክፉኛ እንደተጎዱ ገልጧል፡፡ከቅርብ አመታት ወዲህ በአለማችን ፈጣን ዕድገት ከሚያስመዘግቡ አካባቢዎች ተርታ መሰለፍ የቻለው ከሰሃራ በታች የሚገኙ የአፍሪካ አገራት መንግስታት፣ የኢኮኖሚ ዕድገት ቅናሹ የሚያስከትላቸውን አሉታዊ ተጽዕኖዎች ለመቋቋም የሚያስችሉ የፖሊሲ ማሻሻያዎችን እንዲያደርጉም አይ ኤም ኤፍ አሳስቧል፡፡

       የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ልዩ ጸሃፊ አህመድ ሻሂድ ሰሞኑን ባወጡት ሪፖርት፣ የኢራን መንግስት በዚህ አመት ብቻ ከ1ሺህ በላይ ሰዎችን በስቅላት ለመግደል አቅዷል ማለታቸውን ፎክስ ኒውስ ዘግቧል፡፡
የኢራን መንግስት በተለያዩ ምክንያቶች በስቅላት የሚገድላቸው ሰዎች ቁጥር ባለፈው አመት በከፍተኛ ሁኔታ ጨምሯል ያሉት ሻሂድ፣ የአገሪቱ መንግስት ካለፈው ጥር ወር አንስቶ 700 ያህል ሰዎችን በስቅላት መግደሉን ተናግረዋል፡፡ባለፉት ሁለት ሳምንታት ብቻ አለማቀፍ ህጎችን በመጣስ፣ ሁለት ወጣት ጥፋተኞችን በስቅላት የገደለው የኢራን መንግስት፤ በሌሎች  ወጣቶች ላይም ተመሳሳይ ድርጊት ለመፈጸም እየተዘጋጀ መሆኑን የጠቆሙት ሻሂድ፣ ስቅላት የተፈረደባቸው አብዛኞቹ ወጣቶች በሰው ላይ ያደረሱት ጉዳት የለም፤ አደንዛዥ ዕጽ በመጠቀም ስለተወነጀሉ ብቻ ነው ቅጣቱ የተጣለባቸው ብለዋል፡፡የሰብአዊ መብቶች ተሟጋቾች፤ ኢራን አለማቀፍ ህጎችን በመጣስ የራሷንና የውጭ አገራትን
ጋዜጠኞች ታንገላታለች በሚል በተደጋጋሚ ሲተቹ መቆየታቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ ሻሂድም
ብዙ ጋዜጠኞች አመለካከታቸውን በማንጸባረቃቸውና ዘገባ በመስራታቸው ብቻ በአገሪቱ መንግስት
የከፋ ቅጣት እየተጣለባቸው መሆኑን ገልፀዋል፡፡
በማህበራዊ ድረገጾች፤ ዜናዎችንና የተለያዩ ጽሁፎቻቸውን በማሰራጨታቸው ብቻ የሞት ቅጣት የተጣለባቸው ጋዜጠኞችም እንዳሉ ሻሂድ ገልጸዋል፡፡ ተቀማጭነቱን በኒውዮርክ ያደረገው የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ሲፒጄም፤ ባለፈው የፈረንጆች አመት መጨረሻ ከ30 በላይ ጋዜጠኞች
በኢራን እስር ቤቶች ውስጥ እንደሚገኙ ማስታወቁን ዘገባው አክሎ ገልጿል፡፡