Administrator

Administrator

ባለፈው ቅዳሜ ማለዳ...
ምዕራብ አፍሪካዊቷ ጋና፣ ለሳምንታት ደፋ ቀና ያለቺበትን የአዲሱ መሪዋ በዓለ ሲመት በድምቀት አከበረች፡፡ አዲሱ የጋና ፕሬዚዳንት ናና አኩፎ አዶ፣ ከመዲናዋ አክራ ለሚወዱት ህዝባቸው በስሜት የታጀበና ልብ የሚነካ ንግግር አደረጉ፡፡ ህዝባቸውም የታላቁን ናና አኩፎ አዶን አነቃቂ ንግግር በጥሞና እያዳመጠ፣ ባለ ራዕይ መሪነታቸውንና አንደበተ ርቱዕነታቸውን ሲያደንቅ ዋለ፡፡
የዋሁ የጋና ህዝብ የአዲሱን መሪውን የንግግር ችሎታ እያደነቀ ባለበት ቅጽበት ግን፣ ጉድ መጎልጎል የሚወደው የፌስቡክ ሰራዊት፣ አዲሱን መሪውን ትዝብት ላይ የሚጥል ዘመቻ ከፈተ፡፡
“ፕሬዚዳንቱ በበዓለ ሲመታቸው ላይ ባደረጉት ንግግር፣ ከሁለት የቀድሞ የአሜሪካ ፕሬዚዳንቶች ንግግር፣ የተመነተፏቸውን አንቀጾች ተጠቅመዋል” የሚለው ያልተረጋገጠ ውንጀላና ሃሜት፣ቅዳሜን ሙሉ በፌስቡክ ሲሰራጭ ዋለ፡፡
በነጋታው...
ነገርዬው ካልተረጋገጠ ውንጀላና ሃሜትነት፣ በማስረጃ ወደተደገፈ አነጋጋሪ ዜናነት ተቀየረ፡፡ የናና አኩፎ አዶ ንግግር፣ የበርካታ የዓለማችን መገናኛ ብዙሃን ትኩስ ዜና ብቻ ሳይሆን የአዲሱ የጋና መንግስት የሃፍረትና የይቅርታ አጀንዳ ሆነ፡፡
ቢቢሲ እንደዘገበው፣ የጋናው ፕሬዚዳንት በበዓለ ሲመታቸው ላይ ባደረጉት ንግግር፣ የቢል ክሊንተንን እና የጆርጅ ደብሊው ቡሽን ንግግሮች መንትፈው፣ የራሳቸው በማስመሰል ማቅረባቸው ተረጋግጧል፡፡ የአዲሱ ፕሬዚዳንት ጽህፈት ቤትም፣ አዲሱ ፕሬዚዳንት የተባለውን ነገር መፈጸማቸውን በማመን፣ እሁድ ማለዳ የይቅርታ መግለጫ አውጥቷል፡፡
የጋናው ፕሬዚዳንት በዕለቱ ባደረጉት ንግግር፣ የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ቢል ክሊንተን ከ20 አመታት በፊት በበዓለ ሲመታቸው ላይ ካደረጉት ንግግር የወሰዱትን አንድ ማራኪ አንቀጽ የራሳቸው አስመስለው አቅርበዋል፡፡ ይሄም ብቻ አይደለም። ጆርጅ ደብሊው ቡሽ በ2001 ካደረጉት ንግግር፣ የወሰዱትን ሌላ ማራኪ አንቀጽም፣ ምንጩን ሳይጠቅሱ አነብንበዋል፡፡
ከሌላ ሰው የመነተፉትን ልብ አማላይና ማራኪ አንቀጽ የራሳቸው አስመስለው በማቅረብ፣ የጋናው ፕሬዚዳንት የመጀመሪያው የአገር መሪና ገናና ፖለቲከኛ አይደሉም የሚለው ቢቢሲ፤ ወደ ኋላ መለስ ብሎ ተጨማሪ ክስተቶችን ያስታውሳል፡፡
የትራምፕ ሚስት
የተመራጩ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የዶናልድ ትራምፕ ባለቤት፣ ሚላንያ ትራምፕ በሃምሌ ወር ላይ ባደረጉት ንግግር፣ ቀዳማዊት እመቤት ሚሼል ኦባማ በ2008 ካደረጉት ንግግር የመነተፏቸውን አንቀጾች የራሳቸው አስመስለው አቅርበዋል፣ በሚል የትችት ናዳ ሲወርድባቸው መሰንበቱን የቢቢሲ ዘገባ አስታውሷል፡፡
የማዳጋስካር መሪ
የማዳጋስካር ፕሬዚዳንት በበኩላቸው፤በጥር ወር 2014 በተካሄደው በዓለ ሲመታቸው ላይ ባደረጉት ንግግር፣ ተመሳሳይ ምንተፋ መፈጸማቸው ተነግሯል፡፡ ፕሬዚዳንቱ በወቅቱ ባደረጉት ንግግር ውስጥ፣ የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ከአስር አመታት በፊት ካደረጉት ንግግር የተወሰደና አንዳች እንኳን ለውጥ ያልተደረገበት አንቀጽ ተገኝቷል፡፡
የፕሬዚዳንቱ ተወካይ ግን፣ እንደ ጋናው አቻቸው ይቅርታ አልጠየቁም፡፡
“ከሌሎች ሰዎች ንግግር የተመረጠ አንቀጽ ወስዶ መጠቀም ምን ነውር አለው?!...” ብለው ድርቅ አሉ እንጂ፡፡
የናይጀሪያው መሪ
የናይጀሪያው ፕሬዚዳንት ሙሃመድ ቡሃሪ፤ በመስከረም ባደረጉት ንግግር፣ ባራክ ኦባማ በ2008 ካደረጉት ንግግር የወሰዱትን አንቀጽ ተጠቅመዋል፡፡
የአየርላንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር
የአየርላንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ኤንዳ ኬኒ፤ ምንተፋ ግን ለየት ያለ ነው፡፡
እሳቸው በ2011 ደብሊን ውስጥ ባራክ ኦባማን ለህዝብ ሲያስተዋውቁ ባደረጉት ንግግር የተጠቀሙትን አንድ አንቀጽ የመነተፉት፣ ከራሳቸው ከባራክ ኦባማ መሆኑ ተነግሯል፡፡
ኦባማ ራሳቸው
ከንግግሮቻቸው በርካታ አንቀጾችን በሌሎች ሰዎች የተመነተፉት ኦባማ ራሳቸውም፣ ከሌሎች ሰዎች ተመሳሳይ ምንተፋ መፈጸማቸውን የቢቢሲ ዘገባ ያስረዳል፡፡
ዘገባው እንዳለው፣ ኦባማ በ2008 ባደረጉት ንግግር፣ የቀድሞው የማሳቹሴትስ ገዢ ዴቫል ፓትሪክ፤ ከአስር አመታት በፊት ካደረጉት ንግግር የወሰዱትን አንቀጽ የራሳቸው አስመስለው አቅርበዋል፡፡
ኦባማ ይህን በማድረጋቸው ለቀረበባቸው ወቀሳ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ “ይህን አንቀጽ በንግግሬ ውስጥ እንድጠቀም ምክር የሰጡኝ ራሳቸው ዴቫል ፓትሪክ ናቸው፤ ይሄም ሆኖ አንቀጹ የእሳቸው መሆኑን አለመጥቀሴና እውቅና አለመስጠቴ ስህተት መሆኑን አምናለሁ” በማለት፡፡
የቀድሞው የካናዳ ጠቅላይ ሚኒስትር
የቀድሞው የካናዳ ጠቅላይ ሚኒስትር ስቴፈን ሃርፐርም በ2003 ባደረጉት ንግግር ተመሳሳይ ድርጊት ፈጽመዋል፡፡
ሰውዬው በወቅቱ ባደረጉት ንግግር ውስጥ የተጠቀሙት አንድ አንቀጽ፣ የያኔው የአውስትራሊያ ጠቅላይ ሚኒስትር ጆን ሃዋርድ፤ ከቀናት በፊት ካደረጉት ንግግር የተመነተፈ እንደሆነ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡ ይህ የአንቀጽ ምንተፋ፣ እንደ ዋዛ ታልፎ አልቀረም፡፡ ድርጊቱ ከተፈጸመ ከአምስት አመታት በኋላ፣ ሌላ መዘዝ ይዞ መጥቷል፡፡ በወቅቱ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግሩን የጻፈላቸው ሰው፣ ያንን አንቀጽ ከሌላ ሰው መመንተፉ በመረጋገጡና ድርጊቱ ስቴፈን ሃርፐርንና ፓርቲያቸውን ሃሜትና ስላቅ ላይ በመጣሉ፣ ስራውን እንዲለቅ ተደርጓል፡፡












Saturday, 14 January 2017 15:40

የዘላለም ጥግ

(ታላላቅ ሰዎች በመሞቻቸው ሰዓት)

“ይቅርታ አድርግልኝ ጌታዬ፤ ሆን ብዬ
ያደረግሁት አይደለም”
ንግስት ሜሪ አንቶይኔቴ
(የሰቃይዋን እግር በስህተት ረግጣ የተናገረችው)
· “እኖራለሁ!”
የሮማ ንጉስ
(በራሱ ወታደሮች ከመገደሉ በፊት)
· “ህመም ይሰማኛል፡፡ ሀኪሞቹን ጥሯቸው”
ማኦ ዜዶንግ
(የቻይና ኮሙኒስት ፓርቲ መሪ)
· “የተጎዳ ሰው አለ?”
ሮበርት ኤፍ.ኬኔዲ (የአሜሪካ ፕሬዚዳንት)
(በጥይት ከተመቱ በኋላ ኮማ ውስጥ ከመግባታቸው
ጥቂት ሰኮንዶች በፊት ሚስታቸውን የጠየቁት)
· “አትጨነቅ፤ ዘና በል!”
ራጂቭ ጋንዲ (የህንድ ጠ/ሚኒስትር)
(በአጥፍቶ ጠፊ ከመገደላቸው ጥቂት ደቂዎች
በፊት ለፀጥታ ሰራተኛቸው ያሉት)
· “ኢየሱስ፤ እወድሀለሁ! ኢየሱስ፤ እወድሃለሁ!”
ማዘር ቴሬሳ
(ህንዳዊ መነኩሲት፣ በጎ አድራጊ)
· “በደንብ አውቅሻለሁ እንጂ! ፍቅሬ ነሽ፡፡
እወድሻለሁ”
ጆን ዋይኔ
(ለሚስቱ የተናገረው)
· “ኦህ ዋው! ኦህ ዋው! ኦህ ዋው!”
ስቲቭ ጆብስ
(የአፕል ኮምፒዩተር መሥራች)
· “እማማ፤ እቃዎቼን እሸክፍና ከዚህ ቤት
እወጣለሁ፡፡ አባባ ጠልቶኛል፤ ስለዚህ
ተመልሼ አልመጣም”
ማርቪን ጌይ
(በአባቱ ከመገደሉ ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት ያለው)
· “የፍሎሪዳ ውሃዬን”
(የምትፈልገው ነገር ካለ ተጠይቃ የመለሰችው)
ሉሲሌ ቦል
· “ለምን ታለቅሳላችሁ? ለዝንተ ዓለም የምኖር
መስሏችሁ ነበር?”
ሉዊስ 14ኛ
(የፈረንሳይ ንጉስ)
· “መሞቴ ነው ወይስ ልደቴ ነው?”
ናንሲ አስቶር
(ስትነቃ በቤተሰቦቿ መከበቧን አይታ የተናገረችው)
· “ኦህ … አታልቅሱ - ጥሩ ልጆች ሁኑ፤ እናም
ሁላችንም በገነት እንገናኛለን፡፡”
አንድሪው ጃክሰን
(የአሜሪካ 7ኛው ፕሬዚዳንት)

የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ፤”የሰላም እና የእርቅ ሀገራዊ የምክክር መድረክ”፤ በአፍሪካ የኢኮኖሚ ኮሚሽን አዳራሽ፣ ባለፈው ማክሰኞና ረቡዕ
ተካሂዷል፡፡ በዚህ መድረክ ላይ የተለያዩ የሃይማኖት መሪዎች፣ባለፈው ዓመት የተቀሰቀሰውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ፣የተከሰተውን የዜጎች ህልፈትና
የንብረት ውድመት እንዲሁም በህዝቦች መካከል የተፈጠረውን መቃቃር በማስታወስ፣አገራዊ አንድነቱንም ሆነ ህዝባዊ ትስስሩን ወደቀድሞው ቦታው
ለመመለስ እርቀ ሰላም ማውረድ ወሳኝ መሆኑን በስፋት አንጸባርቀዋል፡፡
የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፣በምክክር መድረኩ ላይ ተገኝቶ የሃይማኖት መሪዎቹን የእርቀ ሰላም ሃሳብና ጥሪ እንደሚከተለው አጠናቅሮታል፡፡
ለፖለቲካዊ ችግሮች መፍትሄው ፖለቲካዊ ውይይት ነው፡፡

“ጠባሳው እንዲድን የእርቀ ሰላም ስራዎች
መስራት ይገባል”

ፓትርያርክ አባ ማትያስ (የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ፓትርያርክ)

ጌታችን በትምህርቱ፤”አስታራቂ ሰዎችን ብፁአን ናቸው” ብሎ ከማወደሱም በላይ “የእግዚአብሔር ልጆች ይግባቡ” በማለት የመጨረሻውን አምላካዊ ክብር እንደሚሰጣቸው አረጋግጦአል፡፡ ከዚህ አኳያ የዕርቀ ሰላም ተግባር ምን ያህል ታላቅ እንደሆነ መገንዘቡ የሚከብድ አይሆንም፡፡ በዓለም ዙሪያ ሁሉ እንደሚታየው፣ ጥንትም ሆነ ዛሬ፣ በአማንያንም ሆነ በኢ-አማንያን፣ የችግሮች ሁሉ መቋጫና አስተማማኝ መፍትሄ፣ እርቀ ሰላም ብቻ እንደሆነ ጥያቄ የለውም፡፡ ከአምላካዊ መርህ በመነሳት ስለ እርቀ ሰላም አስፈላጊነት ስናሰላስል፣ ነገሩ ግልፅ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ እግዚአብሔር ሁሉን ማድረግ የሚችልና ምንም የሚሳነው የሌለ ኃያል አምላክ ሲሆን ደካማ ከሆነው ፍጡር ጋር መታረቅ ለምን መረጠ? ብንል፣ እግዚአብሔር ባህርዩ ዕርቀ ሰላምን የሚወድ፣ ጥላቻን የሚጠላ በመሆኑ ብቻ እንደሆነ ቅዱስ መፅሐፍ ይነግረናል፡፡
ምንጊዜም ከሃይማኖት ቅኝት ርቆ የማያውቀው የሀገራችን ብሂለ አበው፤ “እርቅ ደም ያደርቅ” እያለ ከእግዚአብሔር ቃል ጋር በመተባበር፣ የዕርቀ ሰላም ሰዎች እንድንሆን ያስተምረናል፡፡ ባለፈው የክረምት ወራት በአንዳንድ የሃገራችን አካባቢዎች ያለአስፈላጊ አለመግባባቶች ተከስተው፣ በንፁሃን ወገኖች ላይ የህይወትና የንብረት ጉዳት ከማድረሳቸውም ሌላ በህዝቦች መካከል የመቃቃር ጠባሳ ፈጥረው አልፈዋል፡፡ ይሁንና ይህ መጥፎ ጠባሳ ብዙ እድሜ ሊሰጠው ስለማይገባ፣ ጠባሳው ሙሉ በሙሉ ድኖ፣ በፊት እንደነበረው ጤናማ እንዲሆን፣ተከታታይነት ያላቸው የዕርቀ ሰላም ስራዎች መስራት ይገባናል፡፡
መንግስት ባስቀመጠው ህጋዊ አሰራር ነገሩ ለጊዜው ሰከን ያለ ቢመስልም አበው፤ ‹‹መተው ነገሬን ከተተው›› እንደሚሉት፣ ሁሉም ቅሬታውን በመተው፣ ወደ ፍፁም መግባባት ይደርስ ዘንድ ባለድርሻ ወገኖች ነገሩን በሰከነ መንፈስ ተወያይተውበት፤ እንዲህ ያለ የሃገርን አንድነት የሚፈታተን ጎጂ ድርጊት እንዳይደገም፣የእርማት ስራ ሰርተውበት፣ በሃገራዊና ወንድማዊ መንፈስ ተማምነው፣ በዕርቀ ሰላም ማህተም የሚያትሙበት፣ ለወደፊትም መሰል ችግር ተነስቶ ዜጎች እንዳይጎዱ የሚያስችል አመለካከትና አስተሳሰብ የሚያሳድጉበት የዕርቀ ሰላም ስራ መሰራት አለበት፡፡ ይኸም ተልዕኮ በዋናነት የሃይማኖት አባቶች ኃላፊነትና ግዴታ መሆኑ ስለሚታወቅ፣ እኛ የሃይማኖት መሪዎች፣ ህዝቡን አስተምረን አሳምነንና አስታርቀን፣ ወደ ቀድሞው ሁናቴ ለመመለስ የአንበሳውን ድርሻ ወስደን፣ በሠፊው ለመስራት መትጋት ይኖርብናል፡፡
እኛ ኢትዮጵያውያን፤ ትናንትም ዛሬም ነገም አንድ ነን፡፡ መቼም ቢሆን አንለያይም፡፡ ይህንንም የምናረጋግጠው፣ በህዝቦቻችን መካከል ብቅ ማለት የጀመሩትን ብዥታዎች፣ ስሜታዊ እንቅስቃሴዎች በዕርቀ ሰላም እንዲስተካከሉና፣ በይቅርታ መንፈስ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ፋይላቸው እንዲዘጋ በማድረግ ነው፡፡

===========================================

“የሰላም ዋጋ የሚታወቀው ሰላም የጠፋ ጊዜ ነው”

ሼህ ሙሃመድ አሚን ጀማል ኡመር (የኢ/እስ/ጉ/ጠ/ም/ቤት ፕሬዚዳንት)

    እርቅና ሰላም፤ ጥልቅ ትርጉም ያላቸው፣ በሁሉም ሃይማኖቶች የሚፈለጉና የሚወደዱ ሀሳቦች ናቸው፡፡ የምክክር መድረኩም በእርቅና በሰላም ላይ በማተኮር መዘጋጀቱ፣ በሀገራችን ዘላቂ ሰላም እንዲረጋገጥ፣ የሀይማኖት ተቋማት የድርሻችንን ለማበርከት እድል ይሰጠናል፡፡ በተለይም ከሀገራችን ወቅታዊ የሰላም ሁኔታ አንፃር ሲታይ፣መድረኩ ወቅታዊና የጎላ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ጠቅላይ ምክር ቤታችን ይገነዘባል፡፡
ከጥቂት ወራት በፊት በሀገራችን አንዳንድ አካባቢዎች የታየው አለመረጋጋትና የተፈጠረው ግጭት፣ይህንንም ተከትሎ የደረሰው የህይወትና የንብረት ውድመት ሲታይ፣ ሰላም በምንም የማይተመን ዋጋ እንዳለው ያስገነዝበናል፡፡ የሰላም ዋጋ የሚታወቀው ሰላም የጠፋ ጊዜ ነው፣ የሚለውን አባባል በተግባር አይተናል፡፡ ሁላችንም እንደምናውቀው፣ በሀገራችን ባሳለፍናቸው ሁለት አስርት አመታት፣ አንፃራዊ ሰላም በመኖሩ በርካታ ለውጦችን ተመልክተናል፡፡ መልካምና ተስፋ ሰጭ የእድገትና የልማት ጅማሮዎች ታይተዋል፡፡ ይህም አንዱ የሀገራችን ተጨባጭ እውነታ ነው፡፡ በአንፃሩ ከእድገታችንና ከለውጣችን ጋር አብሮ መጓዝ ያልቻለ የኋላቀርነት አመለካከት፣ ድህነት፣ ብልሹ አስተዳደርና አመራር፣ ሙስና እና መሰል ሁኔታዎች በተቃራኒው የእኛ መገለጫዎች ናቸው፡፡
ይህ አይነቱ የተደበላለቀ ሁኔታም፣ አንዱ በሌላው ላይ የበላይነት ለመያዝ በሚደረግ ፍትግያ፣ በሀገራችን በአንፃራዊነት ሰፍኖ የነበረው ሰላማዊ ሁኔታ፣ በአንዳንድ አካባቢዎች ለመታወክና ለግጭት መፈጠር ምክንያት ሆኗል፡፡ በውጤቱም ሁሉንም ወገን ያሳዘነ ክስተት ተፈጥሮ አልፏል፡፡ ይህ አይነቱ ሁኔታ ዳግም እንዳያገረሽና እንዳይከሰት፣ በየደረጃው ያለን የሀይማኖት መሪዎች፣ ምዕመናንን የማስተማር ኃላፊነታችንን ልንወጣ ይገባል፡፡
በሰዎች ማህበራዊ ግንኙነት ውስጥ የሀሳብ ልዩነትና የሀሳብ ግጭት መኖሩ የሚጠበቅና ተፈጥሯዊ ነው፡፡ ይሁንና ዋናው ጉዳያችን መሆን ያለበት፣ ልዩነቱና ግጭቱ ለምን ተፈጠረ የሚለው ሳይሆን፣ ግጭቱ እንዴት እንደሚፈታ ማወቁ ላይ ነው፡፡ ከዚህ አንፃር የሀሳብ ልዩነቶች ላይ ተመስርቶ የሚፈጠር ግጭትና አለመግባባት፣ በሰከነ መንገድ በውይይት፣ በጥበብና በብልሃት መፈታት አለበት፡፡ ይህ ግጭትን በሰላማዊና በሰለጠነ መንገድ የመፍታት፣ የይቅርታና የእርቅ መንገድም በሀይማኖቶች የሚደገፍ ቅዱስ ስራ ነው፡፡ በመካከላችን እርቅና ሰላም እንዲሰፍንም፣ ፍትህ እንዳይጓደል መጠበቅና ፍትሃዊ መሆን ይገባል፡፡ ሁሉም ሃይማኖቶች ፍትህን በመጠበቅ፣ ግጭትንና ጥላቻን በይቅርታ ልብ ማከም እንደሚገባ ያስተምራሉ፡፡ እስልምናም ከዚህ አስተሳሰብ ጋር በእጅጉ ይስማማል፡፡ በብዙ የቁርአን አንቀፆችም ፍትህን፣ ይቅርታን፣ እርቅንና ሰላምን የተመለከቱ ግልፅ መመሪያዎች ሰፍረዋል፡፡

==================================

‹‹ልዩነቶችን በመነጋገር መፍታት የስልጣኔ ም ልክት ነው››

ካርዲናል ብርሃነየሱስ ሱራፌል (የኢ/ካ/ቤ/ክ ሊቀጳጳስ)

በሃገራችን በተለያዩ የታሪክ ምዕራፎች ውስጥ መጠነ ሰፊ የሆኑ የውጭና የውስጥ ግጭቶችን ያስተናገድን ህዝቦች ብንሆንም የውጭውን ግጭቶች፣ ሃገራዊ ፍቅርን መሰረት ባደረገ፣ ጥበብ በተሞላበት ስልት በመከላከል፣ በአለም መድረኮች እስከ ዛሬ ስማችንን የሚያስጠራ ታሪክ ተመዝግቦ ይገኛል፡፡ በሌላ በኩል በሃገር ውስጥ የሚነሱ ሃይማኖታዊም ሆነ ፖለቲካዊ ግጭቶች በተለያዩ ደረጃና ሁኔታዎች መፍትሄ እየተበጀላቸው ካለንበት ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡ የሃገራችን ህዝቦች ዘመናት ተሻግሮ እስከ ዛሬ ድረስ ህያው የሆነ ዘላቂ ሰላም ይገኝ ዘንድ የእርቅ ሂደቶች፣ ግጭቶችን የመፍታት ጥበብና ክህሎቶች ጠብቀው በማቆየት አስተላልፈውልናል፡፡ ይህ ጥልቅ የሆነ ሀይማኖትን መሠረት አድርጎ፣ ህዝቦችንና የሃገራችንን ሀብቶች ማክበር፣ የእለት ተእለት ኑሮአችን መርሆ ማድረግ ያለብን መልካም እሴት ነው፡፡
በሃገራችን ካለፈው አመት ጀምሮ የሰላም መደፍረስ አጋጥሞ እንደነበር ይታወሳል፡፡ ሰላም ያልሰፈነበት ህብረተሰብ፤ ስለ ሁለንተናዊ የሰው ልጅ ብልፅግና፣ ግብረ-ገብነትና መልካም አስተሳሰብ በፅናት የመቆም አቅሙ ይዳከማል። ተያያዥ ውጤቱም ምድራዊና ሰማያዊ ድህነት ይሆናል፡፡
በሃገራችን ህዝቦቿ ምንም አይነት ልዩነት ሳይገድባቸው በጋራ ለሰው ልጆች ክብር፣ ለፍትህ፣ ለእውነት፣ ለነፃነትና ለፍቅር የቆሙ እንዲሆኑ አደራ እንላለን፡፡ በሃገራችን በተከሰተው ሁከትና ጠብ ሰለባ ሆነው ላለፉት ወገኖቻችን ከልብ እናዝናለን፡፡ የጠፋውም የአገር ሃብት የሚያስቆጭና የሚያሳዝን ነው። ለዚሁ ጥፋት ምክንያት የሆኑ ተግባራት ሁሉ ሊወገዙና ሊታረሙ ይገባል፡፡ ለወደፊት ተመሳሳይ ፈተናዎች ቢያጋጥሙን እንኳን ሰላማዊ በሆነ መንገድ፣ በውይይት የመፍታት ልምድ እንድናዳብር ከወዲሁ መሰራት እንዳለበት በታላቅ አፅንኦት አደራ እንላለን፡፡
ልዩነቶችን በሠላማዊ መንገድ በመነጋገር መፍታትም የስልጣኔ ምልክት ነው፡፡ ይህን የሚቃወም ወይም የሚያግድ አካልም መኖር የለበትም፡፡ ልዩነቶች በሰላማዊ መንገድ የማስተናገድ ልምድ እንዲኖረን፣ በት/ቤቶች የግብረገብና ስነምግባር ትምህርት ከመዋዕለ ህፃናት ጀምሮ መሰጠት እንዳለበት እምነታችን ነው፡፡

=================================

‹‹ሰላም የሁላችንንም ስምምነት ትፈልጋለች››

ፓስተር ፃድቁ አብዶ (የኢት/ወ/አ/ክ/ህ/ፕሬዚዳንት)

የሰላም ሕልውና በተለያዩ ምክንያቶች አደጋ ውስጥ ሊወድቅ ይችላል፡፡ በእግዚአብሔር አምሳል በተፈጠሩ ሰዎች መካከል የሚደረግ አድልዎ፣ ወገንተኝነትና ብሔርተኝነት፣ የመልካም አስተዳደር እጦት እንዲሁም የተለያዩ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ መድልዎች የሰላምን እስትንፋስ በአጭሩ ሊቀጩት ይችላሉ፡፡ እንዲህ ዓይነቱ አደጋ በትውልድ ላይ እንዳይወድቅ፣ የአገር መሠረት ከሆነው ቤተሰብ ጀምሮ ሰላምን በማስፈን፣ እውነቶች ላይ መነጋገርና ወደ ማኅበረሰብ ማዝለቅ ከእያንዳንዳችን ይጠበቃል፡፡
እርስ በርስ መከባበርን፣ መደማመጥንና ለሌላው የሚጠቅመውን ማሰብን፤ ይህንንም መልካም እሴት ኅብረተሰቡ በሃይማኖታዊ ግንኙነት፣ በማኅበራዊ ተራክቦውና በፖለቲካ አስተሳሰቡ ተግባራዊ እንዲያደርገው ማስተማርና ደጋግሞ ማስገንዘብ በብርቱ ይጠበቃል፡፡ በተለይ በአሁኑ ወቅት፣ የዓለማችን ሰላም በተለያዩ ምክንያቶች በመደፍረሱ፣ የሰው ልጆች ሕይወት ከመቼውም ጊዜ ይልቅ ስጋት ላይ ወድቋል፡፡ ተፈጥሮ በምታስከትለው ቀውስና የሰው ልጆች በሚፈጥሩት ፀረ ሰላም ድርጊቶች፣ ሕዝቦች ሰላማቸውንና ነፃነታቸውን ተነጥቀው፣ ተንከራታችና ምውት ሆነው መመለከት ሲበዛ ኀዘን ላይ ይጥላል፤ ልብንም ይሰብራል፡፡
መቼም ጦርነትን ለመቀስቀስ ብዙ ልፋት አያስፈልግም፡፡ ጥቂት አሉታዊ ቃል መሰንዘር ይበቃል፡፡ ሰላምን ለማስፈን ግን እንደዚያ አይደለም፤ ብዙ ውይይት፣ ብዙ ትጋትና ብዙ መሥዋዕትነትን የሚጠይቅ ሂደት ነው፡፡ ከዚህም የተነሳ፣ ሰላም በአንድ ወገን መልካም ፈቃድ ብቻ የምትገነባ ሳይሆን የሁላችንንም ስምምነት የምትፈልግ ናት፡፡ ስለሆነም ማናችንም አስቀድመን በሰላም አስፈላጊነት ልናምን፣ አስከትሎም እውነተኛ በሆነ የአመለካከትና የሕይወት ለውጥ እምነታችንን ልንተረጉም ያስፈልጋል፡፡
ሰላም በሰው ልጅ ሕይወት ውስጥ መሠረታዊ ጉዳይ በመሆኑ፣ ክርስቶስ ኢየሱስ ወደ ምድር የመምጣቱ ብሥራት በተነገረ ጊዜ፣ ከመላዕክቱ የምሥጋና ቃል ጋር የተላለፈውና፣ ‹‹ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን፣ ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ›› የተሰኘው መልዕክት፣ በዓለማችን ላይ የሰላም አስፈላጊነት የቱን ያህል ዋጋ እንዳለው ያመላክተናል፡፡ ስለሆነም የሰላም መልዕክተኞች ተብለን የምንጠራ የሃይማኖት አባቶች፣ በዚህ ዐቢይና ዋነኛ ጉዳይ ላይ አብዝተን እንድንሠራ የሰላም አለቃ ከሆነው ከእግዚአብሔር የተሰጠን ሃላፊነት በመሆኑ፣ ለሰላም መስፈን እንቅፋት የሆነውን ጉድፍ ነቅሰን በማውጣት፣ በሕዝባችን መካከል ፍፁም ሰላም የሚሰፍንበትን ጎዳና ልንተልም፣ ሰላምና እድገት በምድራችን ይሠፍን ዘንድም በተግባርና በጸሎት ሃላፊነታችንን ልንወጣ፣ አብዝተን ሰላምን እንደምንሻ ሁሉ የመጠበቅንም ትጋት አጥብቀን ልንፈልግ የእያንዳንዳችን ሃላፊነት መሆኑን ልንገነዘብ ያስፈልጋል፡፡

=================================

“ዘላቂ ሰላም የሚኖረው ሁሉም ለሰላም ሲሰራ ነው”
ፓስተር ተመስገን ቡልቲ (በሰባተኛው ቀን አድቬንቲስት
ቤ/ክ የኢትዮጵያ ዩኒየን ሚሽን ፕሬዚዳንት)

ፈጣሪ አምላካችን የሰላም አምላክ ነው፡፡ እንደዚሁም የፍትህ አምላክ ነው፡፡ ሰላምና ፍትህ ለአንድ ሀገር እድገትና ልማት ወሳኝ መሆናቸው አያጠያይቅም፡፡ በቅርቡ በሀገራችን ተከስቶ የነበረው የሰላም መደፍረስ አስከትሎት የነበረው አለመረጋጋት፣ የሰላም ዋጋ ምን ያህል ውድ እንደሆነ እንደገና እንድናስታውስ አድርጎናል፡፡ ሰላም ለሁሉም አስፈላጊና ጠቃሚ ቢሆንም ዘላቂ ሰላም ሊኖር የሚችለው፣ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በአንድነት ለሰላም ሲሰሩ ብቻ ነው። ሰላም አንድ አካል ብቻ በተናጠል ሊያስጠብቀው የሚችለው እሴት አይደለም። ይልቁንም ሁሉም አካላት የሚጠበቅባቸውን ድርሻ በትጋት፣ በቅንነትና ሌላውን በመረዳት ሲያበረክቱ ዘላቂ ሰላም ይሰፍናል። ስለዚህ የሀገራችንን ሰላም ዘላቂ በሆነ መልኩ ለማስፈን፣ መንግስትም ሆነ ሌሎች የፖለቲካ ፓርቲዎች እንደዚሁም መላው የሀገራችን ህዝቦች፣ በፍቅርና በመቻቻል፣ ይቅር ተባብለው፣ ወደ ሰላም መድረክ ለመምጣት ዝግጁ መሆናቸው ወሳኝ ነው፡፡
ሰላም የሚወርደው “እኔ ያልኩት ብቻ ይሁን” በማለት እንዳልሆነ፣ ያለፈው ታሪካችን በግልፅ ያሳያል። መቻቻል፣ ተጨማሪ ምዕራፍ መሄድ፣ የመሸነፍ ሳይሆን የበሳልነት፣ የአመራር ብቃት ምልክቶች ናቸው፡፡ ስለዚህ ከመንግስትም ሆነ ከሌሎች የፖለቲካ ፓርቲዎች እንደዚሁም ከመላው የሀገራችን ህዝቦች፣ ይሄ ከመቼውም ጊዜ ይልቅ በአሁኑ ወቅት ይጠበቃል። የአመለካከት ልዩነቶች እንደተጠበቁ ሆነው፣ የጋራ ሀገራችንን ለማሳደግና ለማልማት፣ ሁሉን አቀፍ የሆነ ዲሞክራሲን ለማስፈን፣ በመቀራረብ፣ በልበ ሰፊነትና በይቅርታ መንፈስ፣ ሁሉም ወገኖች ለእርቅና ለሰላም እንዲሰሩ ጥሪ እናቀርባለን፡፡    

===============================


‹‹የችግሮቻችን መፍቻ ያለው በእኛው እጅ ነው››
ቄስ ዋቅስዮም ኢዶሣ (ዶ/ር) (የኢ/ወ/ቤ/ክርስቲያን መካነኢየሱስ ፕሬዚዳንት)


የሰው ልጅ ለዕለት ተእለት ኑሮውና ተግባሩ፣ ለእድገቱና ለደህንነቱ አስተማማኝ ሠላም መኖሩ እጅግ አስፈላጊ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ለግለሰብ፣ ለቤተሰብ፣ ለማህበረሰብ፣ በአጠቃላይ ለህብረተሰብ እንዲሁም ለሃገር እድገትና ብልፅግና ሰላም የሁሉም ነገር መሠረት ነው፡፡ በምንኖርባት ምድር ላይ ለሰላምና ስለ ሰላም ሲባል ትልቅ ዋጋ የሚከፈለው፣ የሰላም መደፍረስ ወይም እጦት የሚፈጥረው ቁስል ጥሎ የሚያልፈው የማይሽር ጠባሳን ለማስቀረት ነው፡፡
ባለፉት ጥቂት ወራት ህዝባችን ለመንግስት ሲያቀርብ ከነበረው የመልካም አስተዳደር ችግር ጋር ተያይዞ በሃገራችን የተለያዩ ቦታዎች የተከሰተው ግጭትና ሁከት ያስከተለው የሰው ልጅ ህይወት ማለፍና የንብረት ጥፋት፣ ምን ያህል የዜጎችን ልብ እንዳሳዘነና እንዳቆሰለ እንዲሁም ምን ያህል የሃገርን ሰላም እንዳወከ በቅርብ የምናስታውሰው ነው፡፡ ሃገራችን ኢትዮጵያ በብዙ አባቶችና እናቶች ያልተቋረጠ ትግልና መስዋዕትነት፣ ሰላሟ ተጠብቆ፣ ከዚህ የደረሰች አኩሪ የሰላም እሴት ያላት ሃገር ነች፡፡ ከእነዚያ አባቶችና እናቶች ጥንካሬና እግዚአብሄርም ከሰጣቸው ስኬት የተነሳ የተረከብናትን ይህቺን ሃገር፣ ለመጭው ትውልድ የማስረከብ ኃላፊነት የተጣለው አሁን ባለን ኢትዮጵያውያን ሁሉ ላይ እንደሆነ ግልፅ ነው፡፡ ይህንን ብርቱ ኃላፊነት ለመወጣት ዛሬም ተቀራርቦ መመካከርና ለጋራ ችግሮቻችን የጋራ መፍትሄ ማፈላለጉ ጊዜ የምንሰጠው ጉዳይ አይደለም፡፡ ሃገሪቱ የእኛ፣ እኛም የእኛ ስለሆንን፣ የራሳችንን ችግር ለመፍታት ከእኛ የተሻለ የምንጠብቀው ሌላ አካል የለም፡፡ የችግሮቻችን መፍቻ ያለው በእኛው በኢትዮጵያውያን እጅ ነው። በተለይም የሃይማኖት መሪዎችም ሆነ ተቋማት ግንባር ቀደም ተግባር ለእርቅና ለሰላም ግንባታ መስራት መሆን ይኖርበታል፡፡
በሁለት ወይም ከዚያ በላይ በሆኑ ግለሰቦች፣ ቤተሰቦች፣ ህዝብና መንግስት መካከል የሃሳብ ልዩነቶች መከሰታቸው የማይቀር ሃቅ ነው። እነዚህን ልዩነቶች የምናስተናግድበትም ሆነ የምንይዝበት መንገድ ግን ሊጠቅመን ወይም ሊጎዳን ይችላል፡፡ ስለዚህ የሃሳብ ልዩነቶችን ይዘን፣ በረጋ መንፈስና በማስተዋል መፍትሄ ካበጀንላቸው፣ ለአብሮነታችን፣ ለሰላማችንና ለእድገታችን መፋጠን ያላቸው ጠቀሜታ ከፍተኛ እንደሚሆን መገመት አያዳግትም።
ለዚህም ስራ ውጤታማነት የሁላችን የሆነችውን የሃገራችንን ሰላም፣ የህዝቦቿን አንድነት ለመጠበቅ፣ አባቶቻችን የተጠቀሙባቸውን የሽምግልና ዘዴዎች መዳሰስና መከተሉ ጠቃሚ ይመስለኛል፡፡ ያለፉ መልካም ምሳሌነት ያላቸው ልምዶቻችን፣ ወደፊት ለምንሰራቸው ስራዎች ኃይል ሆነውን አዲስ ታሪክን ለመስራት የሚቀሰቅሱን መሆን አለባቸው። ስለዚህ አኩሪ ታሪክን ከቀደምት ኢትዮጵያውያን እንደተረከብን ሁሉ፣ የእኛም ልጆች የሚኮሩበትና የሚጠቅሱት መልካም ታሪክ ለመስራት ጊዜው አሁን እንደሆነ አልጠራጠርም፡፡ እኛ በመልካም ነገር ስንነሳ፣ ፍቅር የተሞላው አምላካችን እግዚአብሔር፣ እንደሚረዳንና ስራችንን እንደሚባርክ እርግጠኛ ነኝ።

በሀገራዊ ምርጫ ውጤት የክልልና የፌደራል መንግስታት ስልጣን በተለያዩ የፖለቲካ ሃይሎች ቢያዝ፣ በሁለቱ መንግስታት መካከል የሚኖረውን ግንኙነት የሚደነግግ የህግና ፖሊሲ ማዕቀፍ መዘጋጀቱ ተገለፀ፡፡
የህግ ማዕቀፍ ዝግጅቱ 4 አመታትን መፍጀቱ የተገለፀ ሲሆን ሀሳቡ በፌደራልና አርብቶ አደር ጉዳዮች ሚ/ር እና በፌዴሬሽን ም/ቤት ፈልቆ የተዘጋጀ ነው ተብሏል የፖሊሲ የህግ ማዕቀፉ ከዚህ ቀደም በፌደራል መንግስቱና በክልል መንግስታት መካከል የነበረውን ተለምዷዊ የመንግስታት ግንኙነት በህግ የሚያጠናክር ይሆናል ተብሏል፡፡
እስካሁን የነበረው የፌደራልና የክልል መንግስታት ግንኑነት፤ መደበኛ ያልነበረ ሲሆን አሁን የሚዘጋጀው የፖሊሲ የህግ ማዕቀፍ፣ ህገ መንግስቱን መሰረት አድርጎ በህግና በፖሊሲ የተደገፈ ዘላቂነት ያለው መደበኛ ግንኙነት እንዲኖር የሚያደርግ መሆኑን በፌዴሬሽን ም/ቤት የዲሞክራሲያዊ አንድነት የመንግስታት እርስ በእርስ ግንኙነት ማጠናከሪያ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ አስቻለው ተክሌ ለአዲስ አድማስ አብራርተዋል፡፡
በህገ መንግስቱ አንቀፅ 51፤ የፌደራል መንግስቱ የሃገሪቱን የኢኮኖሚ ማህበራዊና ልማት ስትራቴጂ የማውጣትና የማስፈፀም ስልጣን እንዳለው የሚደነግግ ሲሆን አንቀፅ 52 ደግሞ የክልል መንግስት የራሳቸውን የኢኮኖሚ፣ማህበራዊና የልማት እቅድ የማውጣት ስልጣን እንዳላቸው ይደነግጋል፡፡
እነዚህን ተግባራት እስካሁን የፌደራልና የክልል መንግስታት ተለምዶአዊ በሆነ መንገድ በምክክር ሲሰሩ ቢቆዩም ህገ መንግስታዊ ድንጋጌያቸውን በዝርዝር የሚያብራራ የህግ ማዕቀፍ በማስፈለጉ ላለፉት አራት አመታት ይኸው ጥናትና ዝግጅት ሲካሄድ መቆየቱ ተገልጿል፡፡
በህንድ ለረዥም አመታት ኮንሰርቫቲቭ ፓርቲ የፌደራሉንም የክልል መንግስቱንም ስልጣን በብቸኝነት ተቆጣጥሮ መቀጠሉንና ኋላ ላይ በክልል ያለው ስልጣኑ በተቃዋሚዎች እየተሸረሸረ መጥቶ የፌደራል መንግስትነት ቦታውንም ማጣቱን በተሞክሮነት የጠቀሱት አቶ አስቻለው፡፡ በኛም ሀገር የምርጫ 97 አጋጣሚ ማሳያ በመሆኑ፣ ለወደፊት የተለያዩ ፓርቲዎች ወደ ስልጣን ቢመጡ ሀገሪቱ ጤናማ በሆነ መልኩ እንድትቀጥል አርቆ በማሰብ የተዘጋጀ የፖሊሲ የህግ ማዕቀፍ መሆኑን ለአዲስ አድማስ አብራርተዋል፡፡ እንደየዘመኑ አዳዲስ ጉዳዮች ሲፈጠሩ የሚስተናገዱበትን መንገድም የፖሊሲ ህግ ማዕቀፉ አስቀምጧል ብለዋል አቶ አስቻለው፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን የዱር አራዊቶች ሁሉ በአንድነት ተሰብስበው አውጫጪኝ ያደርጋሉ፡፡ የጫካው ንጉስ አያ አንበሦ ናቸው ሰብሳቢው፡፡
የስብሰባውን አላማ እንዲህ ሲሉ ገለፁ፡-
“የስብሰባችን አላማ በየጊዜው በአደን የመጣ ንብረት ይጠፋል፡፡ ዋሻ፣ ቁጥቋጦ፣ ዛፍና የመሳሰሉት ማደሪያና መኖሪያዎቻችን የአንዱን አንዱ

እየወሰደ፣ ጉልበተኛው ደካማውን እየቀማ ስላስቸገረ፤ እነዚህን ለማስተካከል ነው” አሉና “የተወሰደ ንብረት በሙሉ ለባለቤቶቹ ይመለሳል”

ሲሉ ደመደሙ።
በዚህ መካከል ጦጢት እጇን አውጥታ፤ “እኔ ከጫካው ውስጥ ማደሪያዬ የሆነው ዛፍ ጠፍቶብኛልና ሊመለስልኝ ይገባል” አለች፡፡
ይሄኔ ዝንጀሮ እጁን አወጣና፤
“እኔ ጦጢትን እቃወማለሁ፡፡ ተቃውሞዬም ጦጢት በየጊዜው ከአንድ ዛፍ አንድ ዛፍ ስለምትዘል የተወሰነ ዛፍ የላትም” አለ፡፡
ጦጢት መልሳ ዝንጀሮን ተቃወመች፤
“አያ አንበሶ፣ የእኔ ዛፍ የተለየ ነው፡፡ ምክንያቱም ቅርንጫፎቹን ማር ቀብቻቸዋለሁ፡፡”
አያ ነብሮ እዚህ ላይ ጣልቃ ገባና፤
“ጦጢት ማሩን ከየት እንዳመጣች እንድትጠየቅልኝ እፈልጋለሁ!” አለ፡፡
ጦጢትም፤
“እጫካ ውስጥ የተሰቀለ ቀፎ አግኝቼ፤ ከዚያ ቆርጬ ነው!” አለች፡፡
ጦጢት ይሄን እያስረዳች ሳለች እነ ቀበሮ፣ እነ ተኩላ፣ እነ ዝንጀሮ የጦጢትን ማር ሊልሱ፣ ከምኔው ሄዱ ሳይባል ወደ ዛፉ ሄደዋል፡፡
ይሄኔ ጦጢት፤
“በቃ በቃ ዛፉ የት እንዳለ አውቄያለሁ” አለች፡፡
“እንዴት አወቅሽ?” አለ አያ አንበሶ፤ ለምን በስብሰባችን ትቀልጃለሽ በሚል የቁጣ ስሜት፡፡
“አያ አንበሶ፤ እነ ዝንጀሮ ወዴት እንደሄዱ ይጣራልኝ፡፡ አሁን እዚህ የነበሩት የት ተወሰሩ?”
ዕውነትም አያ አንበሶና አያ ነብሮ ዞር ብለው ቢያዩ፤ እነ ዝንጀሮ የሉም፡፡ ስለዚህ ነብር ወደ ጫካ ተላከ፡፡ ጦጢት ተከትላ ካልሄድኩ አለችና

አስቸገረች፡፡
አያ አንበሶ፤
“ያንቺን ጉዳይ እያጣራን አንቺ ወዴት ትሄጃለሽ?” አላት፡፡
ጦጢትም፤
“በእነ ዝንጀሮ ጅልነት ልስቅባቸው ነው የምሄደው”
“እንዴት?”
‹‹እኔ የዛፉን ቅርንጫፎች ምንም ማር አልቀባሁም፡፡ እነሱም ግን ዛፉን ስለሚያውቁት ወደዚያው ሂደዋል፡፡ ማሩ የለም! አሁን ማ ሌባ እንደሆነ

አወቅን … አያ አንበሶ!” አለች እየሳቀች፡፡
*   *   *
ማር መላስ የማይፈልግ የለም፡፡ ያም ሆኖ ግን አንዱ አንዱን እየጠለፈ፣ አንዱ የአንዱን እየዘረፈ ወይም ከመንግስት እየመዘበረ፣ የሚኖርበትን

ሥርዓት ማስወገድ ተገቢ ነው፡፡ እጅግ የተወሳሰበና የተቆላለፈው የሙስና መረብ፣ በተለይ ከፖለቲካው ጋር ሲተበተብ ለያዥ ለገራዥ

ማስቸገሩን እያየነው ነው!! የሙስናን አሻጥር ለመረዳት በተለይ ዛሬ ዓይንን ማሸት አይፈልግም፡፡ ምን ያህል የሀገርና የህዝብ ገንዘብ ለግል ጥቅም

እየዋለ መሆኑን፣ የተጠረጠሩ የሙስና ባለ እጆችን ማስተዋል ብቻ በቂ ነው፡፡ ሆን ተብሎም ሆነ ለጥንቃቄ ተብሎ አሊያም በስህተት የሙስና

ክስ ዘግይቷል ብንል ማጋነን አይሆንም፡፡ አሁንም መፍጠን አለበት፡፡ የሙስና ዘዴው በአብዛኛው የሚታወቅ ነው፡፡ በዘመኑ ቋንቋ የተበላ ዕቁብ

ነው
‹‹እኔም ሌባ፣ አንተም ሌባ
ምን ያጣላናል፤ በሰው ገለባ!››
የሚባልበት ያፈጠጠ፣ ያገጠጠ ጊዜ ነው፡፡ አለቃና ምንዝር ሳንለይ የሚሠርቁ እጆች መያዝ አለባቸው፡፡ ቁጥጥሩ መጥበቅ አለበት፡፡ ፎቆቹ

በአደባባይ ይናገራሉ፡፡ ቤቶቹ በይፋ ያሳብቃሉ፡፡ መሬቶቹ ሊያሸሿቸው የማይችሉ የምዝበራው አካል ናቸው፡፡ ከየት እንደመጣ ማብራሪያ

የማይሰጥበት ሀብት የፊት ለፊት ማስረጃ ነው!! ለባንክ ዕዳ መክፈያ ለሀራጅ የሚቀርቡት ንብረቶች፣ በማያወላውል መልክ በመሞዳሞድ የታጀሉ

ብዝበዛዎችን ያጋልጣሉ!!
‹‹አንድ አንኳር ጨው ውቂያኖስን አያሰማ›› የሚለውን ተረት በጥሞና እያስተዋልን፣ እርምጃው ለጥቂት ጊዜ ብቻ ዘምቶ የሚቆም መሆን

እንደሌለበት መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡ ለዚህ ምክንያቱ፤ አንድም ሙስናው ውቂያኖስ አከል በመሆኑ፣ አንድም ሙስና የቀጣይነት ባህሪው

ሥር-ሰደድ በመሆኑ ነው፡፡ ለዚህ የሙስና ሂደት አስተዋፅኦ የሚያደርጉ የመንግሥት አባላት፣ የፓርቲ አባላት፣ ነጋዴዎች፣ ደላሎችና ዐይን

ያወጡ ኤጀንሲዎች ወዘተ … የቢሮክራሲያዊ ካፒታሊዝሙ ፓኮ ውስጥ ያሉ ናቸው። እንዲህ በአገር ደረጃ ኢኮኖሚያዊ ምዝበራን እንዲያጥጥና

እንዲናኝ የሆነው መዝባሪዎቹ ማንን ተማምነው ነው? የሚለውን ጥያቄ ማቅረብ የአባት ነው፡፡ ምነው ቢሉ፤ ‹‹ጌታዋን የተማመነች በግ ላቷን

ውጪ ታሳድራለች›› የሚለው ተረት ፊታችን ድቅን ይላልና! አሁንም ውስጣችንን እንመርምር፡፡ ጥልቅ ተሐድሶ የዕውነት ጥልቅ መሆኑን

በተግባር እናረጋግጥ! ልባዊ እንጂ አፍአዊ አለመሆኑን እናጣራ!
‹‹ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮህንም›› አስብ! ‹‹ባለቤቱን ካልናቁ፣ አጥሩን አይነቀንቁን›› አንርሳ!
“ያሳር እሳት የሚጫረው”
ጥንትም በእፍኝ ጭራሮ ነው!
የሚለውን በመሰረቱ እንገንዘብ፡፡
በሼክስፒር ብዕርና በፀጋዬ ገ/መድህን አንደበት፤
“ነበርን ማለት ግን ከንቱ ነው፣
ተው ነው መጀነኑ በቅቶን፤
ጉራ መንዛት መዘባነን፣
የሚያዛልቅ ዘዴ ባይሆን!”
የሚለውን በጭራሽ አንዘንጋ፡፡
መልካም የጥምቀት በዓል
ክርስትና ዕምነት ተከታዮች!!

በበዓሉ ላይ የምታቀነቅነው የ16 አመቷ ድምጻዊት፣ በአልበም ሽያጭ ቀዳሚ ሆናለች

        ተሸናፊዋን የዲሞክራት ዕጩ ሂላሪ ክሊንተንን ጨምሮ ሶስት የአሜሪካ የቀድሞ ፕሬዚዳንቶች ከሁለት ሳምንት በኋላ በዋሽንግተን ዲሲ በሚከናወነው የዶናልድ ትራምፕ በዓለ ሲመት ላይ እንደሚገኙ ማረጋገጫ መስጠታቸውን ሲቢኤስ ኒውስ ዘግቧል፡፡
ሂላሪ ክሊንተንና ባለቤታቸው የቀድሞው ፕሬዚዳንት ቢል ክሊንተን ባለፈው ማክሰኞ በትራምፕ በዓለ ሲመት ላይ እንደሚገኙ ያስታወቁ ሲሆን፣ ጂሚ ካርተርና ሌላኛው የቀድሞ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጆርጅ ደብሊው ቡሽም የበዓሉ ታዳሚዎች እንደሚሆኑ ማረጋገጫ መስጠታቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡ በህይወት ከሚገኙት የቀድሞ የአሜሪካ ፕሬዚዳንቶች በትራምፕ በዓለ ሲመት ላይ የማይገኙት ብቸኛ ሰው ትልቁ ቡሽ መሆናቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ የ92 አመቱ ቡሽ በትራምፕ በዓለ ሲመት ላይ የማይገኙት በእርጅና እና በጤማ ማጣት ሳቢያ እንደሆነ ማስታወቃቸውንም አስረድቷል። በተያያዘ ዜናም በበዓለ ሲመቱ ላይ የሙዚቃ ስራዎቿን እንድታቀርብ ከአዘጋጅ ኮሚቴው ጥያቄ የቀረበላት ድምጻዊቷ ሬቢካ ፈርጉሰን፣  ግብዣውን ተቀብላ ለመዝፈን ፈቃደኛ የምትሆነው “ስትሬንጅ ፍሩት” የተሰኘውንና በአሜሪካ የሚታየውን ዘረኝነት የሚያወግዘውን የሙዚቃ ስራዋን ለማቅረብ ከተፈቀደላት ብቻ እንደሆነ አስታውቃለች፡፡
የ16 አመቷ አሜሪካዊ ድምጻዊት ጃኪ ኢቫንቾ፤በትራምፕ በዓለ ሲመት ላይ የአሜሪካን ብሄራዊ መዝሙር እንደምታቀርብ መነገሩን ተከትሎም፣ የሙዚቃ አልበም ሽያጭዋ በከፍተኛ ደረጃ ተመንድጎ፣ በአንደኝነት ደረጃ ላይ መቀመጡ ተዘግቧል፡፡ ድምጻዊቷ የትራምፕ በዓለ ሲመት ተሳታፊ መሆኗ በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን በስፋት የተዘገበ ሲሆን ይህን ተከትሎም፣ “ድሪም ዊዝ ሚ” እና “ኦ ሆሊ ናይት” የተሰኙት የድምጻዊቷ አልበሞች፣ በቢልቦርድ የደረጃ ሰንጠረዥ በሁለተኛ ደረጃ መቀመጣቸውንም ዘገባዎች ጠቁመዋል፡፡

 ከተማዋ በአመቱ በ21.5 ሚ. ሰዎች ተጎብኝታለች
      የታይላንድ ርዕሰ መዲና ባንኮክ፣ በተጠናቀቀው የፈረንጆች አመት 2016፣ በርካታ ቁጥር ባላቸው ሰዎች በመጎብኘት ከአለማችን ከተሞች የአንደኛነት ደረጃ መያዟን ፎርብስ መጽሄት ዘግቧል፡፡
በአመቱ ባንኮክን የጎበኙ ሰዎች ቁጥር 21.5 ሚሊዮን እንደደረሰ ማስተርካርድ የተባለው ተቋም ያወጣው አመታዊ ዓለማቀፍ የመዳረሻ ከተሞች ሪፖርት ማስታወቁን የጠቆመው ዘገባው፤ በሁለተኛ ደረጃ የተቀመጠቺው ደግሞ በ19.9 ሚሊዮን ሰዎች የተጎበኘቺው ለንደን መሆኗን አስታውቋል። የፈረንሳዩዋ መዲና ፓሪስ በአመቱ በ18 ሚሊዮን ሰዎች በመጎብኘት ከአለማችን ከተሞች የሶስተኛነት ደረጃን የያዘች ሲሆን ዱባይ በ15.27 ሚሊዮን፣ ኒውዮርክ በ12.75 ሚሊዮን፣ ሲንጋፖር በ12.11 ሚሊዮን፣ ኳላላምፑር በ12.02 ሚሊዮን፣ ኢስታምቡል በ11.95 ሚሊዮን፣ ቶክዮ በ11.70 ሚሊዮን፣ ሴኡል በ10.2 ሚሊዮን እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል፡፡
በአመቱ በ3.6 ሚሊዮን ሰዎች የተጎበኘቺው የደቡብ አፍሪካዋ ጁሃንስበርግ፣ ከአፍሪካ ከተሞች በአመቱ በበርካታ ሰዎች በመጎብኘት ቀዳሚነቱን ስትይዝ፣ ካይሮ በ1.55 ሚሊዮን፣ ኬፕታውን በ1.37 ሚሊዮን ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃ መያዛቸውን ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

ባለፈው ሃምሌ የተቃጣውን የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ተከትሎ ተግባራዊ ያደረገውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከአንድ ወር በፊት (በጥቅምት) ለ3 ወራት ያራዘመው የቱርክ ፓርላማ፤ባለፈው ማክሰኞ ባሳለፈው ውሳኔ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን እንደገና ለ3 ወራት ማራዘሙን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
ፓርላማው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ደጋግሞ ማራዘሙ፣ የአገሪቱ መንግስት ያለ ከልካይ የዜጎችን መብቶች የሚገድቡ ወይም ሙሉ ለሙሉ የሚያሳጡ አዳዲስ ህጎችን ለማውጣትና ተግባራዊ ለማድረግ አስችሎታል ያለው ዘገባው፣ የአገሪቱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ግን፣ አዋጁን ዳግም ማራዘም ያስፈለገው የሽብርተኞች እንቅስቃሴ መቀጠሉን በማጤን ነው ብለዋል፡፡
 ከቀናት በፊት በተከበረው የፈረንጆች አዲስ ዓመት ዕለት የተከሰተው የሽብር ጥቃት 39 ያህል ቱርካውያንን ለሞት መዳረጉን ተከትሎ በአገሪቱ ከፍተኛ ውጥረትና ስጋት የተፈጠረ ሲሆን ፓርላማው በጠራው ስብሰባ፣ አዋጁን እንደገና ለማራዘም መወሰኑን ዘገባው ገልጧል፡፡
የቱርክ መንግስት በሃምሌ ወር ከተቃጣበት መፈንቅለ መንግስት ሙከራ ጋር ንክኪ አላቸው በሚል ከ40 ሺህ በላይ ሰዎችን ማሰሩንና 100 ሺህ ያህል የመንግስት ሰራተኞችን ከስራ ገበታቸው ማባረሩን ያስታወሰው ዘገባው፤ የአውሮፓ ህብረት የቱርክ መንግስት ያወጣውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በተደጋጋሚ ሲተቸው እንደነበርም አክሎ ገልጧል፡፡

 በወርቅ በተለበጠ የሰርግ ካርድ፣ 50 ሺህ ሰዎች ተጠርተዋል
      በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ህንዳውያን በገንዘብ እጥረት ቀውስ በሚሰቃዩበት በዚህ አስቸጋሪ ወቅት፣ የቀድሞው የህንድ ሚኒስትር ዲኤታ ጋሊ ጃናርዳና ሬዲ፤ 74 ሚሊዮን ዶላር በማውጣት ድል ባለ ድግስ ልጃቸውን መዳራቸው፣በአገሪቱ ዜጎች ዘንድ ከፍተኛ ተቃውሞ እንደገጠመው ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የቀድሞው የቱሪዝም ሚኒስትር ዲኤታ ሴት ልጃቸውን የዳሩበት ይህ ሰርግ፣ በአገረ ህንድ ታሪክ እጅግ ከፍተኛ ገንዘብ ወጪ ከተደረገባቸው የቅንጦት ሰርጎች አንዱ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፤ የሰርጉ መጥሪያ ካርድ በወርቅ የተለበጠ፣ ለሰርጉ የተጋበዙ እንግዶች ቁጥርም 50 ሺህ መሆኑን አመልክቷል፡፡
የቅንጦት ሰርጉ በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ተቃውሞ መቀስቀሱን ተከትሎ፣ የአካባቢው የግብርና መስሪያ ቤት ባለስልጣናት የግለሰቡን የንግድ ድርጅቶች መዝጋታቸውንና ስለ ሰርጉ ወጪ ማብራሪያ እንዲሰጡ ማድረጉ ተነግሯል፡፡ ሰውዬው ለባለስልጣናቱ በሰጡት ምላሽ፣ በሲንጋፖርና በሌሎች አካባቢዎች ከሚያከናውኑት የቢዝነስ ስራ ባገኙት ገንዘብ፣ የሰርጉን ወጪ መሸፈናቸውንና ለመንግስትም ተገቢውን ግብር በወቅቱ መክፈላቸውን እንደገለጹ ዘገባው አስረድቷል፡፡
ሚኒስትሩ በሙስና ክስ ተመስርቶባቸው ለሶስት አመታት በእስር ላይ ከቆዩ በኋላ፣ ባለፈው አመት በዋስ መፈታታቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ ከእስር ከወጡ በኋላም”ክዛር” የተባለውን የማዕድን አውጭ ኩባንያ ማስተዳደር መቀጠላቸውን ጠቁሞ፣ በርካታ ህንጻዎችና ሌሎች የንግድ ኩባንያዎችመም እንዳሏቸው አስታውቋል፡፡

 የአገር መሪዎች ወደ ሥልጣን ከመምጣታቸው በፊት ምን ይሰሩ እንደነበር ወይም በምን ሙያ ላይ ተሰማርተው እንደቆዩ አስባችሁት ታውቃላችሁ? እኔ ትዝ ብሎኝም አያውቅም፡፡ ግን እኒህ ሰዎች ሲወለዱ ፕሬዚዳንት ወይም ጠ/ሚኒስትር ሆነው አለመወለዳቸውን ያለ ጥርጥር እናውቃለን፡፡ (የንጉሳውያን ቤተሰብ ካልሆኑ በቀር) ይሄ ማለት ደግሞ ወደ ሥልጣን እስኪመጡ ድረስ ባለው ዕድሜያቸው ሲተዳደሩ የቆዩበት ሙያ እንደሚኖራቸው ይጠቁማል፡፡ አንዳንዴ ታዲያ ተሰማርተው የነበሩበት ሙያ ወይም የሥራ ዘርፍ ከፖለቲካና ከአገር መሪነት ጋር ባለው ከፍተኛ ርቀት የተነሳ መገረምና መደነቅ ሊፈጥርብን ይችላል፡፡ የሚከተሉት መሪዎች ማለፊያ ምሳሌዎች ይመስሉኛል፡፡
                                  
     ሙዚቃ ቀማሪው ፕሬዚዳንት
 -   የክሮኤሽያው ፕሬዚዳንት ኢቮ ጆሲፖቪክ፤ወደ ፖለቲካ  ከመግባታቸው በፊት የክላሲካል ሙዚቃ ቀማሪ ነበሩ፡፡ በደርዘን የሚቆጠሩ ክላሲካል ሙዚቃዎችን የደረሱ ሲሆን የክሮኤሽያን ዋነኛ የሙዚቃ ፌስቲቫል መርተዋል፡፡  
•   ጆሲፖቪክ በፕሬዚዳንትነት የተመረጡት እ.ኤ.አ በ2010 ሲሆን በወቅቱ የሙዚቃ ሙያቸውን እንደማያቆሙ ቃል ገብተው ነበር። በኋላ ላይ ግን የፕሬዚዳንትነት ስራቸው ፋታ የማይሰጥ በመሆኑ ቃላቸውን መፈፀም እንዳልቻሉ አምነዋል፡፡ እንዲያም ሆኖ ግን አንድ ፒያኖ  ወደ ፕሬዚዳንታዊ ቢሮአቸው ለማስገባት አልሰነፉም፡፡ ኢቮ ጆሲፖቪክ፤ በቅድመ ምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ኪ-ቦርድ መጫወታቸው ተዘግቧል፡፡
    ሰዓሊው ጠ/ሚኒስትር
 -   የአልባኒያው ጠ/ሚኒስትር ኢዲ ራማ ወደ አገር መሪነት ሥልጣን ከመምጣታቸው በፊት ሰዓሊ ነበሩ፡፡ በፓሪስ የሥነ  ጥበብ ት/ቤት ስዕል ያጠኑት ራማ፤ እ.ኤ.አ በ1998 ወደ አልባኒያ ሲመለሱ የባህል ሚኒስትር ሆነው ተመደቡ። ከዚያም የአልባኒያ ከተማ- ቲራና፣ ከንቲባ ሆነው ተሾሙ፡፡ ይሄም ለሥነ ጥበባዊ ውበት ያላቸውን ስሜት ለመወጣት ዕድል የሰጣቸው ሲሆን በሲሚንቶ የተገነቡ የኮሙኒስት ዘመን ግራጫ ህንፃዎች፤ በሮዝ፣ በብጫ፣ በአረንጓዴና ሀምራዊ ቀለማት እንዲዋቡ አስደርገዋል፡፡
•   የቀድሞ የቅርጫት ኳስ ተጫዋችም የነበሩት ራማ፤ እ.ኤ.አ በ2004 ለቢቢሲ በሰጡት  ቃለ መጠይቅ፤ “በእርግጠኝነት ፖለቲከኛ ነኝ ለማለት አልችልም፡፡ እኔ አሁንም ሰዓሊ ነኝ ነው የምለው፤ ፖለቲካን ለለውጥ በመሳሪያነት ለመጠቀም እየሞከርኩ ነው” ብለው ነበር፡፡
•   በ2012 የTED ቶክ ላይ ለመሪዎች ባስተላለፉት ጥሪ፡- “ከተማችሁን በቀለም መልሳችሁ ፍጠሩ” ብለዋል፡፡  
   ገጣሚው ፕሬዚዳንት
 -   የአየርላንድ ፕሬዚዳንት ማይክል ዲ.ሂጌንስ፣ የሥልጣን መንበር ከመቆናጠጣቸው በፊት ገጣሚ ነበሩ፡፡ አራት የግጥም ጥራዞችን (volumes) ለህትመት ያበቁ ሲሆን የአየርላንድ የመጀመሪያው የሥነ ጥበብ ሚኒስትርም ነበሩ። ማይክል ዲ. በሚል ቁልምጫ የሚታወቁት ታጋይ-ገጣሚ ፕሬዚዳንቱ፤ አየርላንድ “የፈጠራ ሪፑብሊክ” እንድትሆን ጠይቀዋል፡፡  
•    የራሳቸው የግጥም ስራዎች ግን ከሃያስያን የሰላ ትችት አላመለጡም፡፡ አንዱ ሃያሲ እንደውም፤ “ፕሬዚዳንቱ በሥነ ፅሁፍ ላይ ለፈፀሙት ወንጀል ክስ ሊመሰረትባቸው ይችላል” ማለቱ ተዘግቧል፡፡