Administrator
የነጭ ሽንኩርትን መጥፎ ጠረን መከላከል ይቻላል
የነጭ ሽንኩርት ጠረን የሚፈጠረው ሰልፈር የተባለውን ማዕድን ከያዙ አራት ዋና ዋና ውህዶች ነው፡፡ እነዚህ ውህዶች ሲበሉ ደም ዝውውር ውስጥ ይገቡና በሳምባና በላብ ዕጢዎች ይወጣሉ፡፡ ይህ ሂደት ግን መጥፎ ጠረናቸው እንዲቀንስ አያደርግም። በኦሃዮ ስቴት ዩኒቨርሲቲ ያሉ የምግብ ሳይንቲስቶች፣ የነጭ ሽንኩርትን ጠረን ማጥፋት ባይችሉም፣ ሽንኩርት ከተበላ በኋላ የትኞቹ ምግቦችና መጠጦች ቢወሰዱ ጠረኑን ሊያለዝቡ (ሊቀንሱ) ይችላሉ በማለት ጥናት ያደረጉባቸውን ምግቦችና መጠጦች ባለፈው ኤፕሪል አንድ የጥናት ወረቀት አሳትመዋል፡፡ መረጃውን ያቀረበው ፖፑላር ሳይንስ፣ የተባሉትን ምግቦችና መጠጦች ሞክሮ መደምደሚያ ላይ መድረሱንም አውስቷል፡፡
ፖም (አፕል) ይብሉ፡- ለአየር ሲጋለጡ ወደ ቡናማ ቀለም የሚቀየሩ አትክልቶች የፕሮቲን መጠን የሚቆጣጠር ኢንዛይም (Oxidating enzyme) ይኖራቸዋል፡፡ የኦክሲጅንና ኢንዛይሙ ኮምፓዎንድ (ውህድ) የነጭ ሽንኩርቱን መጥፎ ሽታ የሚያጠፋ (የሚቀንስ) የኬሚካል ሰንሰለት ይፈጥራል፡፡ ስለዚህ ነጭ ሽንኩርት ከተመገቡ በኋላ ፖምን መብላት መጥፎ ሽታውን ይቀንሳል ብለዋል ሳይንቲስቶቹች፡፡
አረንጓዴ ሻይ ይጠጡ፡- ይህ ሻይ ፖሊፌኖልስ (Polyphenols) በተባለ የአትክልት ኬሚካል የተሞላ ነው፡፡ ኬሚካሉ ደግሞ በተመሳሳይ መንገድ አራቱንም የሰልፈር ውህዶች የሚፈጥረውን መጥፎ ሽታ ያጠፋል ወይም ይቀንሳል፡፡ ስለዚህ ነጭ ሽንኩርት ከበሉ በኋላ አረንጓዴ ሻይ ፉት ይበሉበት።
ትንሽ የሎሚ ጭማቂ ይጠጡ፡- የአሲድ መጠናቸው፣ ከ3.6 የዘ (የዘ የአሲድ መለኪያ ሲሆን የውሃ የአሲድ መጠን 7 ነው) በታች የሆኑ መጠጦች ነጭ ሽንኩርት ሲበላ ተነቃቅቶ የሰልፈር ሽታ እንዲፈጠር የሚያደርገውን alliinase የተባለ ኢንዛይም ያጠፋል፡፡ ስለዚህ ነጭ ሽንኩርት ከበሉ በኋላ ሎሚ መምጠጥ፣ ሌላ የሽታው መከላከያ አማራጭ ነው፡፡
የውርስ ነገር!...
“ልጆቼ ሆይ!... ከ182 ሚ. ፓውንድ ሃብቴ ሽራፊ ሳንቲም አላወርሳችሁም!” - ታዋቂው ሙዚቀኛ ስቲንግ
“በፍጹም!” አለ ስቲንግ፡፡
“በፍጹም አላደርገውም!... ይሄን ሁሉ ሃብትና ንብረቴን አውርሼ፣ በልጆቼ ላይ እንደመርግ የከበደ ጫና አላስቀምጥም!” በማለት እቅጩን ለጋዜጠኞች ተናገረ፡፡ ይህን የሰሙ የዓለማችን ታዋቂ ጋዜጦችና ድረ-ገጾችም፣ ያሳለፍነውን ሳምንት ነገሩን እየተቀባበሉ አሰራጩት። ስቲንግ እንዲህ አለ የሚሉ ዘገባዎች በስፋት ተነበቡ፡፡
ስቲንግ ማን ነው?
በቅጽል ስሙ ስቲንግ እየተባለ የሚጠራው ጎርደን ሰምነር፣ በሰሜናዊ ቲንሳይድ ዋልሴንድ የተባለች ከተማ ውስጥ የተወለደ እንግሊዛዊ ነው፡፡ አራት ልጆች ለነበሯቸው ወላጆቹ የበኩር ልጅ የሆነው ስቲንግ፣ እናቱ ጸጉር ሰሪ አባቱ መሃንዲስ ነበሩ፡፡ አባትዬው ከስራቸው ጎን ለጎንም ከብት ያልቡ ነበርና፣ ስቲንግም ልጅነቱን የገፋው አባቱ የሚያልቡትን ወተት በየሰፈሩ እየዞረ በማደል ነበር፡፡
ገና በልጅነቱ የሙዚቃ ስሜት በውስጡ ያደረበት ስቲንግ፤ የ10 አመት ልጅ ሳለ ጀምሮ ነበር የአባቱን ጓደኛ ጊታር አንስቶ ክሮቹን መነካካት የጀመረው። ሙዚቃ እንጀራው እስክትሆን ድረስ፣ ሌላ የእንጀራ መብያ ስራ መስራት ነበረበትና፣ ሳያማርጥ ስራዎችን ሰርቷል፡፡ በህንጻ ግንባታዎች የቀን ሰራተኛ ሆኖ አሸዋና ጠጠር አመላልሷል፡፡ የቀረጥ ሰብሳቢ ድርጅት ሰራተኛ ሆኖ ሌት ተቀን በትጋት ሰርቷል፡፡ ጎን ለጎን ትምህርቱን በመከታተልም፣ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን አጠናቆ ኖርዘርን ካውንቲስ ኮሌጅ በመግባት በመምህርነት ተመርቋል፤ ለሁለት አመታትም አስተምሯል፡፡
ስቲንግ ከአባቱ የከብቶች በረት ራሱን አውጥቶ፣ ህይወቱን ወደተሻለ አቅጣጫ ለማምራት ከልጅነት እስከ እውቀት ታትሯል፡፡ ኑሮውን ለማሸነፍ ደፋ ቀና ሲል ኖሯል፡፡ ከልጅነቱ አንስቶ በውስጡ የነበረው የሙዚቃ ፍቅር ግን፣ ወደኋላ ላይ ራሱን ከፍ ወዳለ ደረጃ የምታወጣው መክሊቱ ሆነች፡፡
በተውሶ ጊታር ጣቶቹን ማፍታታት የጀመረው ብላቴና፤ ቀስ በቀስ ራሱን አሰልጥኖ፣ በተለያዩ የምሽት ክለቦች ሙዚቃዎቹን ማቅረብ ቀጠለ፡፡ እንዲህ እንዲህ እያለም በአገረ እንግሊዝ ስማቸው ጎልቶ ከሚጠቀስ አርቲስቶች ጎራ ተቀላቀለ፡፡ በሂደትም በጃዝ፣ ሮክ፣ ሂፕ ሆፕና በተለያዩ ስልቶች የተቀነቀኑ ከ17 በላይ የቡድንና የነጠላ የሙዚቃ አልበሞችን ለአድማጭ አበረከተ፡፡ አለማቀፍ ኮንሰርቶችን በግሉና በቡድን በማቅረብ ዝናው ናኘ፡፡ በበርካታ ፊልሞችና የቴሌቪዥን ድራማዎች ላይ በተዋናይነት ተሳትፎ የጥበብ ክህሎቱን አስመሰከረ፡፡
በህይወቱና በስራዎቹ ዙሪያ የሚያጠነጥኑ 6 መጽሃፍት የተጻፉለት የ62 ዓመቱ ዝነኛ እንግሊዛዊ ድምጻዊ፣ የፊልም ተዋናይና ፕሮዲዩሰር ጎርደን ሰምነር (ስቲንግ) 16 የግራሚ ሽልማቶችን ተቀብሏል፤ የብሪት፣ ጎልደን ግሎብ፣ ኤሚ ተሸላሚ ሆኗል፤ የኦስካር ዕጩም ለመሆን በቅቷል፡፡
ሰውዬው በረጅሙ የሙያ ጉዞው ከፍተኛ ዝናን ብቻም አይደለም የተጎናጸፈው፣ ከባለጠጎች ተርታ የሚያስመድበውን ሃብት ጭምር እንጂ፡፡ የሙዚቃ ስራዎቹ በመቶ ሚሊዮን ኮፒ በአለም ዙሪያ ተቸብችበዋል፡፡ ወተት ሲያመላልስ ያደገው ድሃ አደግ ብላቴና፣ አሁን 182 ሚሊዮን ፓውንድ የሚገመት ሃብት ያፈራ ባለጸጋ ነው፡፡ “ሰንደይ ታይምስ” የአመቱ የእንግሊዝ 100 ቀዳሚ ባለጸጎች ብሎ ከመረጣቸው ሰዎች ተርታ ያሰለፈው፣ ከሶስት አመታት በፊት ነበር፡፡ በወቅቱ በእንግሊዝ የሙዚቃ ኢንዱስትሪ ውስጥ ከፍተኛ ሃብት ካፈሩ አስር ዝነኛ አርቲስቶች አንዱ ስቲንግ ስለመሆኑ ተመስክሮለታል፡፡ ስለዝናውም ስለ ሃብቱም ብዙ ተዘግቦለታል፡፡
ከሰሞኑ ደግሞ መገናኛ ብዙሃን ስለዚሁ ባለጸጋ አርቲስት ሌላ ዘገባ አሰራጭተዋል - “ስቲንግ ሃብቴን ለልጆቼ አላወርስም አለ” የሚል፡፡ የ182 ሚሊዮን ፓውንድ ባለጸጋው ስቲንግ፣ ባሳለፍነው እሁድ ከታዋቂው “ዘ ደይሊ ሜይል” ጋዜጣ ጋር ባደረገው ቃለ ምልልስ ነበር፣ ልጆቹ የሃብት ንብረቱ ወራሾች እንደማይሆኑ በግልጽ የተናገረው፡፡
“ይሄን ሁሉ ገንዘብ ለልጆቼ ማውረስ፣ መጥቀም ሳይሆን መጉዳት ነው!... ሰርተው ያላገኙትን የውርስ ገንዘብ ለልጆቼ መስጠት፣ ሊሸከሙት የማይችሉትንና የሚያጠፋቸውን ከባድ ጫና በአንገታቸው ላይ እንደማሰር ነው የምቆጥረው፡፡” ብሏል ስቲንግ ለጋዜጠኞች፡፡
ይሄን የሰሙ ሌሎች መገናኛ ብዙሃንም ነገሩን እየተቀባበሉ አስተጋቡት፡፡ የሚያወርሱት የተትረፈረፈ ሃብት ይዞ፣ ለልጆች ላለማውረስ መወሰን ለእኛ እንጂ ለውጪው አለም አዲስ ባይሆንም፣ የስቲንግ ውሳኔ ግን የመገናኛ ብዙሃን ቀዳሚ ወሬ መሆኑ አልቀረም፡፡
ስቲንግ ውሳኔውን ያሳለፈው ለልጆቹ የማያስብ ጨካኝ አባት ሆኖ አይደለም፡፡ ሃብቱን ሳይሆን ትጋቱን ቢወርሱ እንደሚበጃቸው ስለተሰማው እንጂ። የራሳቸውን ህልም አልመው ቢነሱ የተሻለ ውጤታማ እንደሚሆኑ በማመኑ እንጂ፡፡ ይህን እምነት ደግሞ ከራሱ የህይወት ተመክሮ ነው የቀዳው፡፡
ልጆቹ አባታቸው ባፈራው የውርስ ሃብት ሳይሆን፣ የራሳቸውን መንገድ ተከትለው ተግተው በመስራት ውጤታማ መሆን አለባቸው ብሎ የሚያምነው ስቲንግ፤ እሱም በዚህ መንገድ ራሱን ወደ ስኬት ማድረሱን ያስታውሳል፡፡ እሱ የሚወረስ ሃብት ያፈራ አባት ያሳደገው ልጅ አይደለም፡፡ አባቱ የሚያልበውን ወተት በየቤቱ ሲያመላልስ፣ በቀን ሰራተኛነት የራሱን ጥሩ ቀን ለመፍጠር ሲባዝን ነው ያደገው፡፡ በአባቱ ውርስ ሳይሆን በራሱ ህልም ራሱን ሰው ለማድረግ ቃል ገብቶ ነው ረጅሙን ጉዞ የጀመረው፡፡
ትዝ ይለዋል፡፡ ልጅ እያለ አንድ ዕለት አንዲት የተከበሩ እንግዳ ወደሚኖርበት አካባቢ ለጉብኝት መምጣታቸውን ሰማ፡፡ ማናት ሴትዮዋ ሲል ጠየቀ፡፡ የእንግሊዟ ንግስት መሆናቸው ተነገረው፡፡ ብላቴናው ስቲንግ ወደጉብኝቱ ስፍራ አመራ፡፡ በግርግሩ ውስጥ ተሽሎክሉኮም አይኖቹን አሻግሮ ላከ፡፡
ንግስቲቱ በርቀት ታዩት፡፡ አሻግሮ እያያቸው ድምጹን ዝቅ አድርጎ የህይወቱን ግብ የተለመባትን ነገር ለራሱ ተናገረ - “ሃብታም፣ ታዋቂና ስኬታማ ሰው እሆናለሁ!... እኔም እንደ ንግስቲቷ ዘመናዊ ሮልስ ሮይስ መኪና እነዳለሁ!” በማለት፡፡
ስቲንግ እሆናለሁ ያለውን ሆነ፡፡ አሻግሮ ያማተራትን ስኬት ተግቶ ደረሰባት፡፡ ብዙ ዝና፣ ብዙ ክብር፣ ብዙ ሃብት አካበተ፡፡ ስቲንግ እዚህ የደረሰው በራሱ ጥረት እንደሆነ ያምናል፡፡ ይሄን ሁሉ ሃብት ያፈራው፣ በላቡ መሆኑን ያውቃል፡፡ ይሄን ስለሚያውቅና እንዲህ ስለሚያምን ነው፣ በእጆቹ የያዘውን ሃብት ለልጆቹ ላለማውረስ የወሰነው፡፡
ሶስት ወንድ እና ሶስት ሴት ልጆቹ እንደ እሱ ስኬታማ እንዲሆኑ፣ የእሱን መንገድ መከተል እንጂ የእሱን ሃብት መጠበቅ እንደሌለባቸው ነግሯቸዋል፡፡ ከአባታቸው ጥረትን እንጂ ጥሪትን እንዳይወርሱ አበክሮ መክሯቸዋል፡፡ በጥንታዊ አሰራር የተሰራው የእንግሊዙ ማራኪ ቤቱም ዊልትሻየር ውስጥ የሚገኘውን ዘመናዊ ቪላውን፣ በገጠራማዋ የእንግሊዝ የሃይቆች አውራጃ የሚገኘው የተንጣለለ ቤቱን፣ የኒውዮርኩን ዘመናዊ ቤቱንም ሆነ የጣሊያኑን የሪል ስቴት መኖሪያውን… ሁሉንም እንወርሳለን ብለው እንዳያስቡ ከአሁኑ እቅጩን ነግሯቸዋል፡፡“ልጆቼ ተግተው መስራት እንዳለባቸው ነው የማምነው፡፡ ይህንንም ስለሚያውቁ፣ ሁሉም ልጆቼ አልፎ አልፎ ካልሆነ በቀር ምንም አይነት ድጋፍ አጠይቁኝም። ይህ ደግሞ ይበል የሚያሰኝ ነገር ነው፡፡ ችግር ውስጥ ካልሆኑ በቀር፣ የገንዘብ ድጋፍ አድርጌላቸው አላውቅም። በራሳቸው ተሰጥኦና ችሎታ ተጠቅመው ስኬታማ የመሆን ፍላጎት የሚያሳድርባቸውን ይሄን አካሄድ ነው የሚከተሉት፡፡” ብሏል ስቲንግ፤ ስለልጆቹ ሲናገር፡፡
“ይሄን ሁሉ ገንዘብ ለልጆቼ ማውረስ፣ ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ ያመዝናል፡፡ በራሳቸው አቅም ሃብት መፍጠር እንዲችሉ ማገዝ እንጂ፣ የኔን ሃብት በማውረስ ልጆቼን ማኮላሸት አልፈልግም፡፡ ሰርተው ያላገኙትን በመቶ ሚሊዮኖች ፓውንድ የውርስ ገንዘብ ለልጆቼ መስጠት፣ ሊሸከሙት የማይችሉትንና የሚያጠፋቸውን ከባድ ጫና በላያቸው ላይ መጫን ነው፡፡” ብሏል፤ ሃብቱን ከልጆቹ ይልቅ ለበጎ አድራጎት ስራ ለመስጠት የወሰነው ስቲንግ ለጋዜጠኞች፡፡
እንዲህ እንደ ስቲንግ ሃብታቸውን ለልጆቻቸው ላለማውረስ የወሰኑ በርካታ የዓለማችን ባለጸጎች አሉ። ከእነዚህ አንዱ የአለማችን ባለጸጎች ፊታውራሪ የማክሮሶፍት ኩባንያ መስራች ቢል ጌትስ ነው። ቢል ጌትስ ከ76 ቢሊዮን ዶላር በላይ ሃብቱን ለልጆቹ እንደማያወርስና እነሱም እንወርሳለን ብለው እንደማይጠብቁ ተናግረዋል፡፡225 ሚሊዮን ዶላር ሃብት ያፈራው ዝነኛው የሙዚቃ ተሰጥኦ ውድድር ዳኛ ሲሞን ኮዌልም፣ በዚህ አመት መጀመሪያ ለወለደው ልጁ ለኤሪክ ሳይሆን፣ ለበጎ አድራጎት እንደሚያውለው ተናግሯል - “ሀብትን ዘር ቆጥሮ ከትውልድ ወደ ትውልድ በውርስ መልክ በማስተላለፍ አላምንም” በማለት፡፡
ቦዲ ሾፕ የተባለው ታዋቂ ኩባንያ መስራች የሆነችው አኒታ ሮዲክም ብትሆን፣ ጥሪት ሳልተውላቸው ብሞት ምን ይውጣቸው ይሆን ብላ ሳትሰጋ 51 ሚሊዮን ዶላር የሚገመት ሃብቷን ሙሉ ለሙሉ ለበጎ አድራጎት ስራ ሰጥታለች፡፡
ለዚህች ሴት፣ ሃብት ንብረትን ለልጅ ወይም ለሌላ የቤተሰብ አባላት ማውረስ፣ አሳፋሪና ነውር ድርጊት ነው፡፡ኤኦ ዶት ኮም የተባለውን ትርፋማ ኩባንያ በዋና ስራ አስፈጻሚነት የሚመራው ጆን ሮበርትስም፣ 500 ሚሊዮን ዶላር ሃብቱን የአብራኩ ክፋይ ለሆኑት ልጆቹ እንደማያወርስ አፍ አውጥቶ ከተናገረ ቆይቷል፡፡ ሰውዬው ይሄን ውሳኔ ያስተላለፈው፣ በልጆቹ የሚጨክን ክፉ አባት ስለሆነ አይደለም፡፡ ስለልጆቹ የሚጨነቅ አርቆ አሳቢ በመሆኑ እንጂ፡፡ ሃብቱን ለልጆቹ የማያወርሰው የወደፊት ህይወታቸው ሰላማዊ እንዲሆንና የስኬታማነት ስሜት እንዲፈጠር በማሰብ መሆኑን ነው ሮበርትስ የተናገረው፡፡
ህፃናት ለእግዚአብሔር የፃፏቸው ደብዳቤዎች
ውድ እግዚአብሔር፡-
ትልቋ እማማ ወደ ቤቷ ስትሄድ ከእኛ ጋር የምትሆን ሌላ እማማ ልትልክልኝ ትችላለህ?
ሶፊ - የ4 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
አባቢ ዶክተር እንድሆን ይፈልጋል፡፡ እኔ ደሞ አልፈልግም፡፡ አንተ ግን ሳይንቲስት እንድሆን ትፈቅድልኝ የለ?
ብሩክ - የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ዳዲን ካየሁት ብዙ ጊዜ ሆኖኛል፡፡ ማሚን ስጠይቃት የሄደበትን አታውቀውም፡፡ አንተ ጋ መጥቷል እንዴ?
ጆሲ - የ5 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
በዚህ ዓመት ከክፍላችን አንደኛ የሚወጣው ማነው? ለእኔ ብቻ በጆሮዬ ንገረኝ፡፡
ሄለን - የ5 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ታላቅ እህቴ፤ ማሚ ያስቀመጠችውን ቸኮላት ሰርቃ ስትበላ አየኋት፡፡ ለማሚ ልንገርባት ወይስ አንተ ትቆጣታለህ?
ዴቭ - የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
አንተ ጋ ትምህርት ቤት የለም አይደል! አለ እንዴ?
ሳሚ - የ7 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ከክፍላችን ልጆች ሁሉ ቀድሜ መሮጥ እንድችል ታደርገኛለህ? እርግጠኛ ነኝ ትችላለህ፡፡
ፊሊፕ - የ5 ዓመት ህፃን
የፍቅር ጥግ
የሴትን ልብ ለማግኘት እርግጠኛው መንገድ ተንበርክኮ ማለም ነው፡፡
ዳግላስ ጄሮልድ
(እንግሊዛዊ ፀሃፌ ተውኔት)
ማናቸውንም የፍቅር ጉዳዮች አላስታውስም። ሰው የፍቅር ጉዳዮችን በምስጢር ነው መያዝ ያለበት፡፡
ዋሊስ ሲምፕሰን
(ትውልደ-አሜሪካ እንግሊዛዊ መኳንንት)
መጀመሪያ ማፍቀር እንጂ መኖር አልፈልግም፡፡ መኖር የምሻው እግረመንገዴን ነው፡፡
ዜልዳ ፊትዝጌራልድ
(አሜሪካዊ ፀሃፊ)
ከሁሉም ዓይነት ሴቶች ጋር ፍቅር ይዞኛል። ወደፊትም ሙሉ በሙሉ በዚሁ ለመቀጠል አቅጃለሁ፡፡
ቻርልስ
(የዌልስ ልኡል)
በፀደይ ወራት የጎረምሳ ህልም በስሱ ወደ ፍቅር ሃሳብ ይገባል፡፡
አልፍሬድ ቴኒሰን
(እንግሊዛዊ ገጣሚ)
ፍቅር እንደ ሲጋራ ነው፤ ከጠፋብህ እንደገና ትለኩሰዋለህ፡፡ ነገር ግን ፈፅሞ እንደ መጀመሪያው አይጥምም፡፡
አርኪባልድ ፐርሲቫል ዋቬል
(እንግሊዛዊ ወታደር)
ጓደኝነት ክንፍ አልባ ፍቅር ነው፡፡
ሎርድ ባይረን
(እንግሊዛዊ ገጣሚ)
ከማፈቅረው ሰው ጋ መሄድ ፍላጎቴ ነው፡፡ ወጪውን ማስላት አልፈልግም፡፡ ጥሩ ይሁን መጥፎ ማሰብ አልሻም፡፡ ያፍቅረኝ አያፍቅረኝ ማወቅ አልፈልግም፡፡ ከማፈቅረው ጋ መሄድ ፍላጎቴ ነው፡፡
ቤርትሎት ብረሽት
(ጀርመናዊ ፀሐፌ ተውኔትና ገጣሚ)
ፍቅር ከድህነትና ከጥርስ ህመም በቀር ሁሉንም ነገሮች ያሸንፋል፡፡
ማ ዌስት
(አሜሪካዊ ተዋናይና ኮሜዲያን)
ፍቅር ደስታ መሆኑ የቀረው ምስጢር መሆኑ የቀረ ጊዜ ነው፡፡
አፍራ ቤኸን
(እንግሊዛዊ ደራሲና ድራማ ፀሃፊ)
የአልማዝ ስጦታውን እስከ መመለስ የሚያደርስ ጥላቻ ለወንድ ኖሮኝ አያውቅም፡፡
Zsa Zsa Gabor
(ትውልደ - ሃንጋሪያዊ አሜሪካዊ ፊልም ሰሪ)
የፖለቲካ ጥግ
(ስለ ጠላት)
ጠላቶችህን ሁልጊዜ ይቅር በላቸው፣ ስማቸው ግን ፈፅሞ አትርሳ፡፡
ሮበርት ኬኔዲ
(አሜሪካዊ ፖለቲከኛ)
ጠላቶቼን ይቅር ማለት አይጠበቅብኝም፤ ሁሉንም ገድያቸዋለሁ፡፡
ራሞን ማርያ ናርቫዝ
(ስፔናዊ ጄነራልና ፖለቲከኛ)
ጠላቶቼ እውነት እንዳላቸው መቀበል አልወድም።
ሳልማን ሩሽዲ
(ትውልደ - ህንድ እንግሊዛዊ ደራሲ)
ጠላትህን በስትራቲጂ መናቅ፣ በታክቲክ ግን ማክበር አለብህ፡፡
ማኦ ዜዶንግ
(ቻይናዊ ፖለቲከኛ)
በወዳጆችህ ትከበራለህ… በጠላቶችህ ትታወቃለህ። እኔ በእጅጉ የታወቅሁ ነበርኩ፡፡
ጄ. ኤድጋር ሁቨር
(አሜሪካዊ የወንጀል ጥናት ባለሙያና የመንግስት ባለስልጣን)
ዝናና እውቅና ለጠላቶች ያጋልጣል፡፡
ሲ.ኤል.አር.ጀምስ
(የትሪኒዳድ ፀሃፊ፣ የፖለቲካ ንድፈ ሃሳብ ቀማሪ)
ከአስተዋይነት የበለጠ ጠቃሚ መሳሪያ፣ ከድንቁርና የከፋ ጎጂ ጠላት የለም፡፡
አቡ አብደላህ መሃመድ
አል-ሃሪቲ-አል-ባግዳድ-አል-ሙፊድ
(ኢራቃዊ ምሁርና የህግ ባለሙያ፤ በ10ኛው ክ/ዘመን የኖረ)
ገንዘብ ወዳጆችን መግዛት አይችልም፡፡ ነገር ግን የተሻለ የጠላት መደብ ሊያስገኝልህ ይችላል፡፡
ስፓይክ ሚሊጋን
(ትውልደ-ህንድ እንግሊዛዊ ፀሃፊ፣ ተዋናይና ተረበኛ)
ሰላም የሚፈጠረው ከትላንት ጠላቶች ጋር ነው፡፡ ሌላ ምን አማራጭ አለ?
ሺሞን ፔሬስ
(የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር)
አይዟችሁ፤ “ስንዴው ከሳምንት በኋላ ጂቡቲ ይደርሳል”
መንግስት፣ በየጊዜው “የምስራች” እያለ የሚነግረንን ወሬ ማመን ቢቀርብን ይሻላል። ግን፣ መስማትና ማመን ለምዶብናል፡፡ መልካም ነገር ስለምንመኝ ይሆን፤ “ለማመን” የምንቸኩለው? መንግስት አዲስ ወሬ ሲያበስረን እንሰማዋለን፤ “የዛሬውስ እውነት ሊሆን ይችላል” ብለን እናምነዋለን፡፡ ሌላው ይቅርና፤ “ኢትዮጵያ በእህል ምርት ራሷን ችላለች” ሲለን እንኳ አምነነዋል። በየጎዳናው የምናየው ድህነትና በየጓዳው የሚያጋጥመን የኑሮ ችግር በጣም ከባድና አሳዛኝ እንደሆነ ብናውቅም፤ የምስራች ሲበሰር ቶሎ ለማመን ዝግጁ ነን።
ምን ዋጋ አለው? ዳቦ ቤቶች በስንዴ እጥረት እንደ ዘንድሮ ተቸግረው አያውቁም፡፡ ባለፈው ጥቅምት ወር ገደማ ነው ነገሩ የተጀመረው። “አዝመራው ጥሩ ምርት ይዟል” ተባለ በደፈናው፡፡ ግን በዚሁ ተደፋፍኖ አልቀረም፡፡ በእህል አይነት እየተዘረዘረ፤ ከነመጠኑ በኩንታል እየተጠቀሰ “ከፍተኛ የእህል ምርት ይሰበሰባል” የሚል የማዕከላዊ ስታትስቲክስ ባለስልጣን ሪፖርት ወጣ። ይህን ሪፖርት ተከትሎ፤ የእህል ንግድ ድርጅት መግለጫ ለመስጠት ቀናት አልፈጀበትም። ስንዴ ከውጭ ለመግዛት ነው ወራት የሚፈጅበት፡፡
የእህል ገበያ ድርጅት ሃላፊዎች፤ የእህል ምርት በብዛት እንደሚሰበሰብ በመጥቀስ ታህሳስ ወር ላይ በሰጡት መግለጫ፤ የእህል ዋጋ አሽቆልቁሎ ገበሬዎች ተጎጂ እንዳይሆኑ እንሰጋለን በማለት ጭንቀታቸውን አስረድተዋል።
እንዲያውም፣ የእህል ዋጋ ገና ካሁኑ የመቀነስ አዝማሚያ ጀማምሮታል በማለት የተናገሩት የድርጅቱ ሃላፊዎች፣ ለምሳሌ የጤፍ ዋጋ በኩንታል 20 ብር ቀንሷል በማለት ማስረጃ አቅርበዋል፡፡ የአንድ ኪሎ የጤፍ ዋጋ ላይ የሃያ ሳንቲም ቅናሽ መታየቱ እንደ ትልቅ ነገር መወራቱ አያስገርምም? ይሄም ብቻ አይደለም፡፡ በየአመቱ ከታህሳስና ከጥር ወር በኋላ የእህል ዋጋ እንደሚጨምር እንዴት ይዘነጉታል? ለዚያውም “የእህል ንግድ” ላይ የተሰማሩ ሃላፊዎች ናቸው!
ለማንኛውም የእነሱ ጭንቀት፣ የእህል ምርት “ተትረፍርፎ” ገበያ ላይ ዋጋው እንዳይወድቅ ነው። ደግነቱ፤ ችግር የለም፡፡ ችግር አይፈጠርም። የእህል ንግድ ድርጅት አለልን፡፡ ሃላፊዎቹ፤ እህል በመግዛትና በመሰብሰብ በገበያ ላይ ዋጋው እንዳያሽቆለቁል ለማድረግ እንደተዘጋጁ ገልፀዋል - በታህሳስ ወር።
በእርግጥ እንደዚህ ቢያስቡ አይገርምም። የማዕከላዊ ስታትስቲክስ ባለስልጣን መረጃዎች ሲታዩ፤ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚመረተው ስንዴ በተለይ ባለፉት ስድስት አመታት በእጅጉ ጨምሯል። በ2001 ዓ.ም የስንዴ ምርት 25 ሚሊዮን ኩንታል፤ በ2004 ዓ.ም ደግሞ 29 ሚሊዮን ኩንታል እንደነበር ይገልፃል የባለስልጣኑ መረጃ። አምና በከፍተኛ የምርት እድገት 34 ሚሊዮን ኩንታል ስንዴ እንደተሰበሰበ አመታዊው የባለስልጣኑ ሪፖርት ያመለክታል። ዘንድሮ ደግሞ አርባ ሚሊዮን ኩንታል።
ሪፖርቶቹ እውነተኛ ከሆኑ፣ የስንዴ ምርት በሁለት አመታት ውስጥ በ11 ሚሊዮን ኩንታል ጨምሯል ማለት ነው። የ45% እድገት ቀላል አይደለም፡፡ አስደናቂ ነው፡፡ “ምርት ተትረፈረፈ” ያስብላል፡፡
ግንቦት 20 በሚከበርበት እለት ደግሞ ተጨማሪ ትልቅ ስኬት ተበሰረ፡፡ ለተከታታይ አመታት በተመዘገበው የግብርና እድገት ዘንድሮ ኢትዮጵያ በእህል ምርት ራሷን ችላለች በማለት ጠ/ሚ ሃይለማርያም ደሳለኝ ተናግረዋል፡፡ ድንቅ ነው፡፡
የእህል ምርት እየጨመረ መምጣቱ አይካድም፡፡ ጥሩ ነው፡፡ “ኢትዮጵያ በእህል ምርት ራሷን ችላለች” ብሎ መናገር ግን ሌላ ነገር ነው፡፡ ያለ መንግስት ድጐማ ኑሯቸውን መቀጠል የማይችሉ 6.5 ሚሊዮን ችግረኛ የገጠር ነዋሪዎች አሉ፡፡ ያለ ውጭ እርዳታ በህይወት መቆየት የማይችሉ 6.5 ሚሊዮን ረሃብተኞች መኖራቸውን ደግሞ ዩኤን ገልጿል፡፡ በድምሩ 13 ሚሊዮን
ተረጂዎች ያሉባት አገር “በእህል ምርት ራሷን ችላለች” ሲባል ምን ትርጉም አለው?
የመንግስት ብስራት ግን በዚህ አላቆመም፡፡ የስንዴ ምርት በእጅጉ እያደገ መሆኑን በመጥቀስ፤ “ኤክስፖርት ይደረጋል” በማለት የመንግስት ባለስልጣናት ሲናገሩ ከርመዋል፡፡ የሆይ ሆይታው ተከፋይ የሆኑት የእህል ንግድ ድርጅት የስራ ሃላፊዎች፤ ከዚህ “ብስራት እና “ስኬት” የተለየ ነገር አልተናገሩም፡፡ እንዲያውም የተወሰነ ያህል ቁጥብነት አሳይተዋል፡፡ ባለፈው አመት ምን እንደሰሩና ለዘንድሮ ምን እንዳቀዱ የድርጅቱ የስራ ሃላፊዎች ሲዘረዝሩ እንመልከት፡፡
በ2005 ዓ.ም ወደ አምስት ሚሊዮን ኩንታል ገደማ ስንዴ በ4.5 ቢሊዮን ብር ከውጭ ሀገር በመግዛት ገበያውን ለማረጋጋት እንደተቻለ ለዋልታ የገለፁት ዋና ስራ አስኪያጁ አቶ ብርሃኑ ሃይሉ፤ ዘንድሮ በቂ ስንዴ ስለተመረተ ከውጭ አገር ገዝተን አናስመጣም አላሉም፡፡ ግን እንደሌላው ጊዜ በፍጥነት ስንዴ ለመግዛትም ውሳኔ አላስተላለፉም።
ከ2005 ዓ.ም ጋር ሲነፃፀር በ2006 ዓ.ም የሚሰበሰበው የስንዴ ምርት በ4 ሚሊዮን ኩንታል እንደሚበልጥ የተናገሩት የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ፤ የስንዴ እጥረትንና የዋጋ ንረትን ለማቃለል ታስቦ ከውጭ እየተገዛ የሚመጣው ስንዴ ዘንድሮ በግማሽ እንደሚቀንስ ገልፀዋል፡፡ አምና ከውጭ ተገዝቶ የመጣው ስንዴ ከ5 ኩንታል በላይ ስለሆነ ዘንድሮ 2.5 ሚሊዮን ኩንታል ብቻ ይሆናል ማለት ነው፡፡
“ዘንድሮ ከውጭ ገበያ የሚገዛው ስንዴ በግማሽ እንደሚቀነስ ነው ዋና ስራ አስኪያጁ ያመላከቱት” ብሏል ፋናቢሲ በታህሳስ 28 ቀን ዘገባው።
የማዕከላዊ ስታትስቲክስ ባለስልጣን መረጃ፣ የመንግስት ባለስልጣናት ሆይሆይታ እና የእህል ንግድ ድርጅት ሃላፊዎች ውሳኔ ውሎ አድሮ መጨረሻው አላማረም፡፡
ገና የካቲት ወር ላይ ነው በስንዴ እጥረት የአገሪቱ ዳቦ ቤቶች መቸገር የጀመሩት፡፡ እንደታሰበው በ2.5 ሚሊዮን ኩንታል ግዢ ብቻ የስንዴ እጥረትን ማቃለል እንደማይቻል በግልጽ እየታየ የመጣው፤ ስራ ፈትተው በራቸውን የሚዘጉ ዳቦ ቦቶቹ ሲበራከቱ ነው፡፡
ለዚህም ነው የኋላ ኋላ አራት ሚሊዮን ኩንታል ለመግዛት የተወሰነው፡፡ ለነገሩ ቀደም ሲል የታሰበው 2.5 ሚ ኩንታል ስንዴ፤ ቶሎ ተገዝቶ አልመጣም። ለጊዜው በቂ ስንዴ ተመርቷል ስለተባለ ከውጭ አገር ገዝቶ ማስመጣት የሚያስቸኩል ጉዳይ አልሆነባቸውም፡፡
አሁን እንደምታዩት፤ የስንዴ እጥረት አፍጥጦ ወጥቷል፡፡ የመንግስት እና የእህል ንግድ ድርጅት ሆይሆይታ በመጨረሻ “ዳቦ አልቋል” ወደሚል ችግር አደረሰን፡፡ ነገር ግን የመንግስት ባለስልጣናትም ሆኑ የድርጅቱ ሃላፊዎች በተሳሳተ ግምት የስንዴ እጥረት እንደፈጠሩና ጥፋት እንደሰሩ አምነው አይቀበሉም፡፡
“የስንዴ እጥረት ተፈጠረ፤ ዱቄት ጠፋ፣ ዳቦ አለቀ” የሚል ቅሬታ ሲቀርብባቸው፤ “የአቅርቦት እጥረት የለም፤ ችግሩ የስርጭት ነው” የምትል የተለመደች ምላሽ ይሰጣሉ፡፡
የስርጭት ችግርምኮ የነሱ ጥፋት ነው፡፡ ግን ይሄንን ለማሰብ ጊዜ የላቸውም። በወሬ ብቻ የስንዴ እጥረትን የሚያስወግዱ ስለሚመስላቸው፤ ሌላ ነገር አይታያቸውም፡፡ “የአቅርቦት እጥረት የለም” የሚል ወሬ አላዋጣ ሲል ነው፤ የተስፋ ቃል መናገር የሚጀምሩት፡፡ “አይዟችሁ፡፡ ከሳምንት በኋላ ስንዴው ጅቡቲ ይደርሳል” በማለት በተስፋ እንድንጠብቅ ሰሞኑን ነግረውናል፡፡
ለመብላት የጠፋ ቅቤ ስሞት በአፍንጫዬ ይፈስሳል፤ አለ ዶሮ
(በቁም ያልረዳ ዘመድ ሲሞቱ አርባ ይደግሳል)
ከዕለታት አንድ ቀን ሶስት ሰዎች አንድ ጫካ እያቋረጡ ሳሉ፣ አንዲት የወፍ ጫጩት ከዛፍ ላይ ጎጆዋ ወድቃ መሬት ላይ ያገኙዋታል፡፡
አንደኛው - “ቤቴ ወስጄ እንደ ዶሮ ጫጩት አሳድጋታለሁ” አለ፡፡
ሁለተኛው - “ለጥናትና ምርምር ትጠቅማለች፡፡ ወደ ላቦራቶሪ ወስደን ለባለሙያ እንስጣት” አለ፡፡
ሶስተኛው - “የለም ጎበዝ፤ ወደገበያ ወስደን እንሽጣት” አለ፡፡
በዚህ ክርክር ብዙ ከተሟገቱ በኋላ በዚያው አካባቢ የሚኖር አንድ ፈላስፋ አዋቂ ስላለ ወደሱ ዘንድ ሄደው ዳኝነት ሊጠይቁ ተስማሙ፡፡ ወፊቱን ይዘው አዋቂው ቤት ሄዱ፡፡
“ምን ልርዳችሁ ምን ላግዛችሁ?” አለና ጠየቃቸው፡፡ ተወካያቸው እንዲህ ሲል አስረዳ፡-
“ከዛፍ ጎጆዋ የወደቀች ወፍ አግኝተናል፡፡ አንዱ ቤቴ ወስጄ ላሳድጋት አለ፡፡ አንዳችን ለቤተ-ምርምር እንስጣት አልን፡፡ አንዳችን ገበያ ተወስዳ ትሸጥ አልን፡፡ ማንኛችን ነን ትክክል?”
ፈላስፋውም ጥቂት ካሰበ በኋላ፤
“ወዳጆቼ ሆይ! ለዶሮ ጫጩት የሚሆነው ኑሮ ለወፍ ጫጩትም ይሆናል ብሎ ያሰበ ተሳስቷል፡፡ ሁሉም የየራሱ ኑሮ ነው ያለው፡፡ አሳድጎስ ምን ሊያደርጋት ነው? ዓላማ ቢስ ይሆናል! ቤተ-ምርምር እንውሰዳት ያለውም ተሳስቷል፡፡” ለወፊቱ የሚጠቅማት ነገር የለምና፡፡ ወደገበያ ወስደን እንሽጣት ያለውም ከዚች ጫጩት ሽያጭ ማንኛችሁ ምን ያህል ልትጠቀሙ ነው? የማያዋጣ ጥቅም ከመፈለግ አለማድረጉ ይመረጣል” አላቸው፡፡
“እንግዲያስ ምን አድርጉ ትለናለህ?” አሉና ጠየቁት፡፡
ፈላስፋውም፤
“ከሁሉም የሚሻለው ወፊቱን ወደ ጎጆዋ መመለስ ነው፡፡ ኑሮዋን መልሱላት፡፡ ሰላሟን ስጧት፡፡ የተፈናቀለን ሰው እንደምታቋቁሙ ሁሉ ለወፊቱም እንደዚያ አስቡላት” ብሎ አሰናበታቸው፡፡
* * *
ያለዓላማ ጉዞ ከንቱ ነው፡፡ ያለቅርስና ያለበቂ መሰረታዊ ጥቅም ነፃ-ገበያን መመኘት የጫጩት አትራፊነት ምኞት ነው፡፡ ያለብስለት ጥናትና ምርምር፣ ያለብቁ ባለሙያ ዕድገት ዘበት ነው፡፡ ኑሮው ካልተመለሰለት፣ ደሀ ጎጆው ካልተመለሰ፣ ልማቱ ከደረቀ፣ እሳቱ ካልሞቀ ተስፋው ይሞትበታል፡፡ ኑሮው መለወጥ አለበት፡፡ መታገዝ አለበት፡፡ ገቢና ወጪው መመጣጠን መቻል አለበት፡፡ ውሎ አድሮ ገቢው ይጨምር ዘንድ መንገዱ ሊጠረግለት ይገባል፡፡
ዛሬ እንደፋሽን የተያዘው ህገ-ወጥ ብልፅግና ነው፡፡ ሀገራዊ ስሜት ያለጥርጥር እየቀጨጨ ነው፡፡ ደምብና ሥርዓትን መጣስ እንደፋሽን ተይዟል፡፡ ድህነትን መቀነስ እንደአፍ አመል ሆኖ ይነገራል እንጂ በበሰለ መልኩ ህዝብ ውስጥ አልሰረፀም፡፡ ግማሽ ጎፈሬ፣ ግማሽ ልጩ የሆነ ካፒታሊዝም ከፋይዳው ማነስ ግራ ማጋባቱ ይብሳል፡፡ የምሁሮቻችን የድህነትን አሽክላ ለማስወገድ ዝግጁ አለመሆን፣ ከስራ አጥነት መዘዝ ጋር ተዳምሮ፣ ከአረንቋው እንዳንወጣ እያደረገን ነው፡፡ አዙሪቱ እጅግ ጥምዝምዝና ተደጋጋሚ ነው፡፡ “ከእለት እንጀራና ከትክክለኛ ምርጫ የትኛው ይሻላል?” ዓይነት አጣብቂኝ የድህነት የቤት ጣጣ ነው፡፡ ሀብት እኩል ባልተከፋፈለበት አገር ምርጫ 100% ተሳካ ሲባል አይገርምም ይላሉ ለበጠኛ አበው - ባለሙያዎች እንዲህ ግራ-ገብ ነገር ሲበዛባቸው፡፡ ከሁሉም ይሰውረን ማለት ትልቅ ፀሎት ነው፡፡
የዲሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ኢ-አድሎአዊነትና ቀናነትን ይጠይቃል፡፡ የብዙሃን ፓርቲ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት መመስረት አስፈላጊነት አጠያያቂ ያለመሆኑን ያህል፤ ሁሉም ፓርቲዎች እኩል መሆናቸውን፣ በታሪክ የብቻውን ካሳ የሚያገኝ አንድም ፓርቲ መኖር እንደማይገባ፣ እርስ በእርስ መወዳደራቸው የዕድገት ማሺን መሆኑ እጅግ ግልፅ ሊሆን ይገባል፡፡ ሁሉም ፓርቲዎች ያለጭቦ መሳተፋቸውና መወከላቸው፣ የሲቪል ቡድኖችም ሊሳተፉበት ማስፈለጉ ገሀድ ጉዳይ ነው፡፡ በማግለል እንጂ በማሳተፍ የምናወጣው ነገር እንደሌለ ልብ ማለት ተገቢ ነው፡፡
ኑሮ ዛሬ ነው፡፡ ነገ ምኞት ነው፡፡ ህይወት በእጅ ባለበት ሰዓት የሚኖር እንጂ በምኞት የሚታቀድ አይደለም፡፡ ዛሬ መኖር መቻል አለበት፡፡ መሰረታዊ የፍጆታ ዕቃዎች በቀላሉ መገብየት አለባቸው፡፡ ቀን በቀን እየናረ የሚሄደውን የኑሮ ውድነት ሳንገታ ዕድገትን ብናልም ምኞት ብቻ ነው፡፡ ለመብላት የጠፋ ቅቤ ስሞት በአፍንጫዬ ይፈስሳል፤ አለ ዶሮ የሚበላው ለዚህ ነው፡፡
ኢትዮጵያና ግብጽ በ7 ነጥቦች ላይ ተስማሙ
ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝና የግብጹ ፕሬዚዳንት አብደል ፋታህ አልሲሲ ከትናንት በስቲያ በኢኳቶሪያል ጊኒ ማላቦ ከተማ ተገናኝተው አዲስ ስምምነት ላይ መድረሳቸው የተዘገበ ሲሆን፤ የጋራ ጥቅምን ባስጠበቀ መልኩ ለመስራትና ከወዲሁ አስፈላጊ ዝግጅቶችን በመጀመር በሶስት ወራት ውስጥ የጋራ ስብሰባ ለማድረግ መስማማታቸውን የግብጽ መንግስት ገለፀ፡፡
የሁለቱ አገራት መሪዎች ውይይት ስኬታማ እንደሆነ በመጥቀስ፣ የኢትዮጵያና የግብጽ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች በሰጡት የጋራ መግለጫ፤ የአባይ ወንዝን በሚመለከት የግብጽ ህልውናና የኢትዮጵያ የልማት ፍላጎትን መሰረት በማድረግ ለመስራት ተስማምተናል ብለዋል፡፡ በአባይ ወንዝ እና በህዳሴ ግድብ ዙሪያ መሪዎቹ ተወያይተው በ7 ነጥቦች እንደተስማሙ ሚኒስትሮቹ ገልፀው፤ ለሁለቱ አገራት ጥቅም የሚበጀውን የውይይትና የትብብር መርህ እናከብራለን የሚል ነጥብ በቀዳሚነት ጠቅሰዋል፡፡
እያደገ የመጣውን የውሃ ፍላጎት ለማሟላትና የውሃ እጥረትን ለመቋቋም የሚያስችል የገንዘብ አቅም የሚያስገኙ ክፍለ አህጉራዊ ፕሮጀክቶችን ለመዘርጋት ቅድሚያ እንሰጣለን ብለው እንደተስማሙም ሚኒስትሮቹ ተናግረዋል፡፡
ሶስተኛው የስምምነት ነጥብ፣ የአለም አቀፍ ህግ መርሆዎችን እናስከብራለን የሚል ነው፡፡ ይሁን እንጂ፤ ሁለቱ አገራት “የአለም አቀፍ ህግ መርህ” በሚለው ጉዳይ ላይ የተለያየ ትርጓሜ በመስጠት እንደሚወዛገቡ የሚታወቅ ሲሆን፤ ለዚህ አወዛጋቢ ጉዳይ እልባት የሚሰጥ አዲስ ሃሳብ አልመጣም፡፡ በግብጽ በኩል፤ ከ90 አመት በፊት ግብጽና እንግሊዝ እንዲሁም ከ50 ዓመታት በፊት ሱዳንና ግብጽ የተፈራረሟቸው ስምምነቶች መከበር አለባቸው የሚል መከራከሪያ ይቀርባል፡፡ በኢትዮጵያ በኩል ደግሞ ብዙዎቹ የአባይ ተፋሰስ አገራትን ያላሳተፉ የድሮ ስምምነቶች ተቀባይነት የላቸውም፤ የአባይ ተፋሰስ አገራት የፈረሙበት አዲስ ውል ሊከበር ይገባል የሚል መከራከሪያ ይቀርባል፡፡
ጠ/ሚ ሃይለማርያም እና ፕ/ት አልሲሲ የተስማሙበት አራተኛው ነጥብ፤ ሱዳንን ጨምሮ በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዙሪያ ኢትዮጵያ፣ ግብጽ እና ሱዳን የተቋቋሙት የሶስትዮሽ ኮሚቴን የሚመለከት ነው፡፡ በግብጽ ተቃውሞ ሳቢያ ኮሚቴው ስራ እንደቆመ የሚታወቅ ሲሆን፤ አሁን የኮሚቴውን ስራ በአፋጣኝ መልሶ ለማስጀመር ተስማምተናል ሲሉ ሁለቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ተናግረዋል፡፡ አለማቀፍ የባለሙያዎች ኮሚቴ ያቀረባቸውን የመፍትሄ ሃሳቦች ለማስተግበር እንዲሁም በቀጣይ የግድቡ ግንባታ ሂደት ላይ በሚካሄድ ጥናት የሚገኙ ውጤቶችን በጸጋ ለመቀበል መስማማታቸውም ተገልጿል፡፡
አምስተኛው ነጥብ በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ሃላፊነትን የሚጥል ሲሆን፤ የግድቡ ግንባታ በግብጽ የውሃ አጠቃቀም ላይ ማናቸውም ችግር እንዳይፈጠር በፅናት እጥራለሁ ይላል፡፡ የግብጽ መንግስት ላይ ሃላፊነትን የሚጥለው 6ኛ ነጥብ ደግሞ የኢትዮጵያን የልማት ፍላጎት ከግምት ውስጥ ከሚያስገባ ገንቢ ውይይት ላለማፈንገጥ ቃል እገባለሁ የሚል ነው፡፡
ሱዳንን በሚጨምረው የሦስትዮሽ ኮሚቴ ስር በቅንነት ለመስራትም ሁለቱ መሪዎች ተስማምተዋል፤ በ7ኛው ነጥብ፡፡
የሁለቱ መሪዎች ውይይት ግልጽነት የተመላበት ነበር ያሉት የግብጹ የውጭ ጉዳይ ሚንስትር ሳሜህ ሾክሪ፤ ውይይቱና ስምምነቱ ለሁለቱ አገራት ግንኙነት ትልቅ ስፍራ አለው፤ በመተማመንና በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ አዲስ የግንኙነት ምዕራፍ ከፍተናል ብለዋል፡፡
የህዳሴ ግድብ በግብጽ የውሃ አጠቃቀም ላይ ችግር እንዳይፈጥር ኢትዮጵያ ምን ማድረግ ትችላለች ተብለው የተጠየቁት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም፣ የግድቡ ዲዛይን የተሰራው ምንም አይነት ችግር ሊያስከትል በማይችል መልኩ ነው፤ ከዚህም በተጨማሪ አገራቱ በተስማሙት መሰረት በጉዳዮቹ ዙሪያ በጋራ መወያየትና መፍትሄ ማበጀት ይችላሉ ብለዋል፡፡
ለአልሸባብ ወደ አክራሪነት መለወጥ ኢትዮጵያ ተጠያቂ ናት መባሉን መንግስት አጣጣለ
አልሸባብ ፅንፈኛ ድርጅት የሆነው ኢትዮጵያ ወደ ሶማሊያ ጦር ሰራዊት በማዝመቷ ነው በማለት ኒው አፍሪካን መጽሔት የዘገበ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በበኩሉ የአልሸባብ ታጣቂዎች አፍጋኒስታን ሄደው ስልጠና የወሰዱት ገና ድሮ ነው በማለት ዘገባውን አጣጣለ፡፡
አልሸባብ በዩጋንዳ እና በኬኒያ በፈፀማቸው ጥቃቶች ሳቢያ የምስራቅ አፍሪካ አገራት ውስጥ ስጋት መፍጠሩን በመጥቀስ ነው መጽሔቱ አልሸባብን የሚመለከት ሰፊ ዘገባ ያቀረበው፡፡
ዜጐች በሄዱበት ሁሉ በፍተሻ መከራቸውን እያዩ እንደሆነ መጽሔቱ ገልፆ፤ በኬኒያ እና በዛንዚባር የቱሪዝም ገቢ ክፉኛ አሽቆልቁሏል፤ የኬኒያ መንግስት የመከላከያ በጀቱን ለመጨመር ተገዷል፡፡
አልሸባብ ወደ አክራሪነት የተለወጠው፤ በ2006 የኢትዮጵያ መከላከያ ሀይል በአሜሪካ ድጋፍ ወደ ሶማሊያ በመዝመቱ ነው ሲልም መጽሔቱ ኢትዮጵያን ተጠያቂ አድርጓል፡፡ በመጽሔቱ የቀረበው ውንጀላ መሰረተ ቢስ ነው ሲል ያጣጣለው የኢትዮጵያ የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር በበኩሉ፤ ኢትዮጵያ አልሸባብን አዳከመች እንጂ ወደ አክራሪነት እንዲለወጥ አላደረገችም በማለት ሰፊ ምላሽ ሰጥቷል፡፡ እንዲህ አይነቱ ውንጀላ በተደጋጋሚ የሚሰነዘር መሆኑን ሚኒስቴሩ ጠቅሶ፤ ነገር ግን ምንም አይነት ማስረጃ የማይቀርብበት መሰረተ ቢስ ውንጀላ ነው ብሏል፡፡
በሶማሊያ እየገነነ የነበረው የእስልምና ፍርድ ቤቶች ምክር ቤት በኢትዮጵያ ጦር በመመታቱ አይደለም አልሸባብ ያቆጠቆጠው፡፡ እንዲያውም የፍርድ ቤቶች ምክር ቤት ሶማሊያ ውስጥ እየተንቀሳቀሰ በነበረበት ወቅትና ከዚያ በፊት ወደ አፍጋኒስታን ለስልጠና ተልከው በነበሩ ቡድኖች ናቸው አልሸባብን የመሰረቱት ብሏል ሚኒስቴሩ፡፡
የእስልምና ፍርድ ቤቶች ህብረት ኢትዮጵያ ላይ ጦርነት አውጆ እንደነበር ሚኒስቴሩ አስታውሶ፤ ያንን ጥቃት ለመከላከል የተወሰደው ወታደራዊ እርምጃ ተገቢ ነበር ብሏል፡፡
ወታደራዊ እርምጃ የወሰድነውም፤ አለም አቀፍ ህጐችን በማይጥስ መንገድና ከሶማሊያ የሽግግር መንግስት በተደረገልን ግብዣ ነው ብሏል - ሚኒስቴሩ፡፡ የኢትዮጵያ ጦር ሶስት አመት ሶማሊያ ውስጥ በቆየበት ወቅት ምንም አይነት ድጋፍ ከአሜሪካን እንዳልተሰጠውም ጠቅሷል፡፡
የሸራተን ሰራተኛ ማህበርና ማኔጅመንቱ እንዲደራደሩ ተወሰነ
የሸራተን ሠራተኛ ማህበርና ማኔጅመንቱ ለድርድር እንዲቀርቡ በሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የአሰሪና ሰራተኛ ወሳኝ ቦርድ ባለፈው ማክሰኞ የወሰነ ሲሆን፤ የአዲስ አበባ ሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ፣ አደራዳሪ እንዲመደብ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
የሸራተን ሆቴል ጠበቃ አቶ ተካ አስፋው፤ ክሱ እንዲሰረዝና ያለ አደራዳሪ ራሳቸው እንዲደራደሩ ያቀረቡት ጥያቄ ተቀባይነት ሳያገኝ ቀርቷል፡፡
ላለፉት 6 ወራት የሸራተን ሰራተኛ ማህበር ማኔጅመንቱ በህብረት ስምምነቱ ላይ እንዲደራደር ጥያቄ ሲያቀርብ ቢቆይም ማኔጅመንቱ ለድርድር ፈቃደኛ ባለመሆኑ፣ ለኢንዱስትሪ ፌዴሬሽን የእገዛ ጥያቄ ማቅረቡን እንዲሁም ጉዳዩ ከፌዴሬሽኑ አቅም በላይ በመሆኑ ለኢሰማኮ ደብዳቤ መፃፉንና ኢሰማኮ ለማኔጅመንቱ የአምስት ቀን ጊዜ መስጠቱን መዘገባችን ይታወሳል፡፡ ማኔጅመንቱ የተሰጠውን የአምስት ቀን የጊዜ ገደብ ከጨረሰ በኋላ የኢንዱስትሪ ፌዴሬሽኑ ለአሰሪና ሰራተኛ ወሳኝ ቦርድ ክስ መስርቶ፣ ባለፈው ማክሰኞ የፌዴሬሽኑ ጠበቃ አቶ ሰኢድ ይመርና የማኔጅመንቱ ጠበቃ የቀድሞው የስፖርት ፌዴሬሽን ም/ፕሬዚዳንት አቶ ተካ አስፋው በተገኙበት ውሳኔ ተሰጥቷል፡፡
ቦርዱ፤ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ፤ አደራዳሪ እንዲመድብ ትዕዛዝ እንደሚያስተላልፍ ገልጿል፡፡
በጉዳዩ ላይ ፌዴሬሽኑ በአደራዳሪነት እንዲገባ የኢንዱስትሪ ፌዴሬሽኑ ጠበቃ አቶ ሰኢድ ይመር የጠየቁ ሲሆን የሸራተን ሆቴል ጠበቃ አቶ ተካ አስፋው ጥያቄውን ተቃውመውታል፡፡ “በጭራሽ መደረግ የለበትም፤ ፌዴሬሽኑ በአደራዳሪነት ገባ ማለት በእሳት ላይ ቤንዚን እንደማርከፍከፍ ይቆጠራል” ብለዋል - አቶ ተካ፡፡ የፌዴሬሽኑ ጠበቃ አቶ ሰኢድ በበኩላቸው፤ “በህግ አምላክ! ህጋዊ ሰውነት ያለውን ድርጅት በዚህ መልኩ መዝለፍ በህግ ያስቀጣዎታል” ሲሉ ምላሽ የሰጡ ሲሆን ቦርዱ አቶ ተካ ከንግግራቸውን እንዲታቀቡ አድርጓል፡፡
የሠራተኛ ማህበሩና ማኔጅመንቱ ለድርድር ቀርበው እስከ ሀምሌ 1 ቀን 2006 ዓ.ም የደረሱበትን ሁኔታ ለቦርዱ ሪፖርት እንዲያደርጉ ትዕዛዝ ተሰጥቷል፡፡
በእለቱ ጉዳዩን ለመከታተል ከመጡት በርካታ የሸራተን ሰራተኞች መካከል አብዛኞቹ እንደገለፁልን፤ ሰራተኞች ችግራቸውን በሚዲያ ከገለፁ በኋላ፣ ሥራ አድረው ጠዋት ወደ ቤት ለሚሄዱ ሰራተኞች የሚቀርበው ሰርቪስ (የትራንስፖርት አገልግሎት) የቆመ ሲሆን በህመም፣ በጋብቻና በዘመድ ሞት ምክንያት አስፈቅዶ የቀረ ሰው ሰርቪስ ቻርጅ አይከፈለውም ተብሎ በድርጅቱ ሰሌዳ ላይ እንደተለጠፈም ጠቁመዋል፡፡
“የኪችን ሰራተኛ 350 ብር፣ የላውንደሪ ሰራተኛ፣ 400 ብር፣ የጥበቃ ሰራተኛ 450 ብር፣ እንግዳ ተቀባይ 700 ብር፣ አስተናጋጅ 450 ብር ደሞዝ እያገኘ በችግር ምክንያት የቀረን ሰው ሰርቪስ ቻርጅ አንከፍልም ማለት አሳፋሪ ነው” ብለዋል ሰራተኞቹ፡፡ የኢንዱስትሪ ፌዴሬሽኑ ጠበቃ አቶ ሰኢድ ይመር በበኩላቸው፤ በሰራተኞቹ ላይ እየተወሰደ ያለው እርምጃ አግባብ ባለመሆኑ ድርጅቱ ከዚህ ድርጊቱ እንዲታቀብ ለቦርዱ አቤቱታ አቅርበዋል፡፡
ሰራተኞቹም የተወሰደው እርምጃ በህብረት ስምምነቱ የሌለና አዲስ የመጣ በመሆኑ ድርጅቱ የወሰደውን እርምጃ በአሰሪና ሰራተኛ አዋጁ መሰረት እንዲያነሳ ጠይቀዋል፡፡
ስለቀጣዩ የማህበሩና ማኔጅመንቱ ድርድር የጠየቅናቸው የሰራተኛ ማህበሩ ፕሬዚዳንት አቶ ዳዊት ሳሙኤል፤ ጉዳዩ በፍ/ቤት የተያዘ መሆኑን ጠቅሰው፤ አስተያየት ከመስጠት ተቆጥበዋል፡፡

