Administrator

Administrator

Saturday, 16 January 2016 10:09

የዘላለም ጥግ

(ስለ ደስታ)

- ደስታን በራስ ውስጥ ማግኘት ቀላል
አይደለም፤ ሌላ ቦታ ማግኘት ደግሞ
አይቻልም፡፡
አግኔስ ሪፕልየር
- ደስታ ልክ እንደ ደመና ነው፤ ለረዥም ሰዓት
ትክ ብለህ ካየኸው ይተናል፡፡
ሳራ ማክላችላን
- ደስታ የሚገኘው በመስጠትና ሌሎችን
በማገልገል ነው፡፡
ሔነሪ ድራሞንድ
- ደስታ በአካል አለመታመም ወይም በአዕምሮ
አለመረበሽ ነው፡፡
ቶማስ ጄፈርሰን
- የተካፈሉት ደስታ ይጨምራል፡፡
ጆስያህ ጊልበርት ሆላንድ
- ራስን መርሳት ደስተኛ መሆን ነው፡፡
ሮበርት ሉዊስ ስቲቨንሰን
- ደስታን መግዛት ነፍስን መሸጥ ነው፡፡
ዳግላስ ሆርቶን
- ፈገግታ አፍንጫህ ስር የምታገኘው ደስታ
ነው፡፡
ቶም ዊልሰን
- ነፃነት ደስታ ነው፡፡
ሱዛን ቢ.አንቶኒ
- ደስተኛ ለመሆን የሚያስፈልግህ ጥሩ
ጠብመንጃ፣ ጥሩ ፈረስና ጥሩ ሚስት ብቻ
ናቸው፡፡
ዳንኤል ቡኔ
- ደስታ ለሰውነት ጠቃሚ ነው፤ የአዕምሮን
ኃይል የሚያጐለብተው ግን ሀዘን ነው፡፡
ማርሴል ፕሮስት
- የደስታ ሁሉ መሰረቱ ጤና ነው፡፡
ሌይግ ሃንት
- በመከራ ወቅት የደስታ ጊዜን ከማስታወስ
በላይ ከፍተኛ ሃዘን የለም፡፡
ዳንቴ አሊግሂሪ

Saturday, 16 January 2016 10:07

የዝነኞች ጥግ

(ስለ ሞዴሊንግ)
- ሞዴል አይደለሁም፡፡ ሞዴል የእውነተኛው
ነገር ቅጂ ነው፡፡
ማ ዌስት
- በቀን ከ10 ሺ ዶላር በታች ለሆነ ክፍያ
ከእንቅልፌ አልነሳም፡፡
ሊንዳ ኢቫንጄሊስታ
- መቀመጫዬ ፎቶግራፍ ለማንሳት ትልቅ
ካልሆነባቸው፣ ለእኔ ትልቅ ሊሆንብኝ
የሚገባ አይመስለኝም፡፡
ክርስቲ ቱርሊንግተን
- ለ20 ዓመታት በየቀኑ መስተዋት
ተመልክቼአለሁ፡፡ ፊቴ ያው ነው፡፡
ክላውዲያ ሺፈር
- አንዳንዴ ብቸኝነት ይሰማኛል፤ ነገር ግን
ብቸኛ መሆን ግሩም ነው፡፡
ታትጃና ፓቲትዝ
- ሜክአፕ የሚያጐናፅፈኝን በራስ መተማመን
እወደዋለሁ፡፡
ቲራ ባንክስ
- ጋዜጣ ከማንበብ ይልቅ የአካል እንቅስቃሴ
ማድረግ እመርጣለሁ፡፡
ኪም አሌክሲስ
- መቀመጫዬ ወደ ጎን ባያዘነብል እመኛለሁ፤
ነገር ግን ያንን መጋፈጥ ያለብኝ ይመስለኛል፡፡
ክሪስቲ ብሪንክሌይ
- የፕላስቲክ ቀዶ ህክምና ለማግኘት ሁሉም
ሰው በቂ ገንዘብ ሊኖረው ይገባል፡፡
ቢቨርሊ ጆንሰን
- ሽቶ የማትቀባ ሴት ወደፊት ተስፋ የላትም፡፡
ኮኮ ቻኔል
- ሰውነቴን እወደዋለሁ፡፡ እግዚአብሔር
የሰጠኝ ነው፡፡
ኬት አፕቶን
- ሞዴሎች ብዙ ጊዜ በእኔ ጥያቄዎች ይደነቃሉ፡
፡ ሃሳባቸውን፣ ተስፋቸውን፣ ህልማቸውን …
ማወቅ እፈልጋለሁ፡፡
ሃርሌይ ብራውን
- ልዕለ ሞዴል ለመሆን ለራሴ የአንድ ዓመት
ጊዜ ሰጠሁት፤ እናም “ካልተሳካ ወደ ት/ቤት
እመለሳለሁ” አልኩኝ፡፡
ቲራ ባንክስ
- እውነተኛ ውበት፤ ለራስ ታማኝ መሆን ነው፡፡
ያ ነው ጥሩ ስሜት እንዲሰማኝ የሚያደርገኝ፡፡
ላቲቲያ ካስታ

ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ለአቅመ ሄዋን የደረሰች ቆንጂት ልትዳር ሽማግሌዎች መጥተው ልጅዎን ለልጃችን ብለው ይጠይቁና እሺ ተብለው፤ ቀን ተቆርጧል፡፡ የሠርጉ ዝግጅትም ተጠናቋል፡፡ ተደገሠ፡፡ ተበላ፡፡ ተጠጣ፡፡
“ሙሽሪት ልመጅ
ሙሽሪት ልመጅ
እሰው ሀገር ሄዶ የለም የእናት ልጅ
እንዝርቱን ልመጅ
ደጋኑን ልመጅ
ምጣዱን ልመጅ
ሰፌዱን ልመጅ
እሰው ሀገር ሄዶ የለም የእናት ልጅ!” ተባለላትና ተሸኘች፡፡
ለመደች ለመደችና እናት አባቷን ለመጠየቅ መጣች፡፡
እናቷ ከአባቷ ይልቅ በሴትነት ለመወያየት ይቀርባሉና፤
“እንዴት ከረምሽ ልጄ?” አሏት፡፡
ልጅ፤
“ደህና ከርሜያለሁ እማዬ”
እናት፤
“ሳይሽ ወፈርፈር ብለሻል፤ እንዲያው ለመሆኑ ፀንሰሽ ይሆን እንዴ? አርግዘሽ ከሆነ የገንፎ እህልም፣ ሌላም አስፈላጊ ነገር እንዳዘጋጅልሽ ቀኑን ንገሪኝ፡፡ ለመሆኑ ያረገዝሽበትን ጊዜ ታውቂዋለሽ?”
ልጅ፤
“አይ እማዬ፤ ቀኑን እንዴት አውቀዋለሁ፡፡ እሱ በላይ በላዩ ይጨምርበታል!!”
*          *         *
በላይ በላዩ የምንጨምርበት ነገር በበረከተ ቁጥር ችግራችን ቅጥ - እያጣ፣ ህይወታችን ቅጥ - እያጣ፣ በመጨረሻም አገራችን ዕቅድ - አልባ ወደመሆን እያመራች ትሄዳለች፡፡ ቅጥ - አልባ መሆን ለሀገር ትልቅ አደጋ ነው፡፡ ታቀደ የተባለው ሁሉ ዕልባት ሳያገኝ በላይ በላዩ ዕቅድ ካወጣንበት ሩጫችን ፍሬ-አልባ ነው የሚሆነው። ኑሯችንን እናጣጥም፡፡ ኢኮኖሚአችንን እናጣጥም፡፡ ፖለቲካችንን እናጣጥም፡፡ ዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ያልነውን እናጣጥም፡፡ “ሲሮጡ የታጠቁት ሲሮጡ ይፈታል” የሚለውን ተረት እናጣጥም፡፡ ማንኛውም አዲስ መንግስት በመጣ ቁጥር ያለፈውን ሥርዓት መኮነኑ የተለመደና ምናልባትም ግድ ሊሆን ይችላል፡፡ የተለመደነቱ አዲሱ አሮጌውን መጣሉ አይቀሬ (Invincible) ስለሆነ ነው ይባላል፡፡ ግድነቱ ግን ከአሮጌው የተሻለ ነገር ሰርቶ ማሳየት ስላለበት ነው፡፡ ኩነና (condemnation) ብቻውን አቅም አይሆነንም፡፡ የኩነናችንን ምክን ከህልውናችን ምክን (raison d’être) ጋር ማያያዝ አለብን እንጂ ባዶ ኩነና (Vacant condemnation እንዲሉ) ምንም አይፈይደንም፡፡ ሁለተኛው ችግራችን ፍረጃ ነው (branding) ለየችግሩ ሁሉ እነእገሌ ናቸው ተጠያቂ ማለት፡፡ እነ እገሌ ደግሞ ይህን የሚያደርጉት እንትን ስለሆኑ ነው ብሎ ቦቃ ማበጀት፡፡ ፈርጅ መፍጠር፡፡ እንዲህ ያለው አካሄድ ከዋናው ችግር ስለሚያራርቀን መፍትሄውም የዚያኑ ያህል ይርቅብናል፡፡ ችግሮቻችን የሚደራረቡት በቅጥ በቅጥ እየፈታናቸው ስለማንሄድ ነው፡፡ የፖለቲካውን ለፖለቲካ፣ የኢኮኖሚውን ለኢኮኖሚው ማድረግ ይጠበቅብናል፡፡ “የቄሣርን ለቄሣር” እንዲል መጽሐፍ፡፡ ሁሉን ችግር ፖለቲካዊ ፍረጃና መፍትሄ እንስጠው ካልን አገርን የፖለቲከኞች እንጂ የአገሬው አናደርጋትም፡፡ ዜጎቿን የማታከብር አገር ደግሞ አገር አትሆንም፡፡ ደካማ ትምህርት ያላት አገር ዕውቀት እንጂ ፖለቲካ አያሻትም፡፡ ደካማ ጤና ያላት አገር የጤና ባለሙያ እንጂ ፖለቲከኛ አያስፈልጋትም፡፡ ደካማ ኬላ ያላት አገር ሀቀኛ ተቆጣጣሪ እንጂ ፖለቲከኛ የግድ አያሻትም፡፡ መልካም ልማት የራባት አገር የልማት ባለሙያ እንጂ ፖለቲከኛ ገምጋሚ ባለውለታ አይሆናትም፡፡
አሁንም “የየሱስን ለየሱስ፤ የቄሣርን ለቄሣር እንስጥ!” ፍትህ የሚሻን ነገር ሌላ ሰበብ አንፈልግለት፡፡ ፍትሕ እንስጠው፡፡ ለምሳሌ በየኬላው የሚካሄዱ ፍተሻዎች ሚዛናዊ አይደሉም ከተባሉ ፈታሾቹን ፈትሾ ፍትሕ መስጠት ነው፡፡ ምሬቶችን አለማጠራቀም ለአገር ሰላም ይበጃል፡፡ ትናንሽ ጅረቶች ተጠራቅመው ወንዝ እንደሚሆኑ አለመርሳት ወሳኝ ብልሃት ነው፡፡ የቢሮክራሲው ቀይ ጥብጣብ (አሻጥር/bureaucratic red-tape እንቅፋት እንደማለት) አሁንም አልተበጠሰም፡፡ እንዲያወም ተተብትቧል ቢባል ይሻላል፡፡ ይህንንም መታገል ከልማት ጋር ቀጥተኛ ተያያዥነትና ተቀጣጣይነት ያለው ነው! በቅርብ እናስብብት!
እስከዛሬ አገራችን ተሰርቶላታል የምንለውን ነገር፤ ካልተሰራላት ጋር አነፃፅረን፤ የበላችውን ከተራበችው ጋር አወዳድረን፤ ከግብርናዋ ኢንዱስትሪዋን፣ ከኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪዋ ያልተሰራውን ቤትና ያልገባላትን መንገድ አጢነን፤ ገና የሚቀረንን ጉዞ ማየት እንጂ በላይ በላይዋ ውዳሴ ብናበዛባት የአገራዊውን አባባል “የበላችው ያቅራታል፤ በላይ በላዩ ያጎርሷታል” የሚለውን መዘንጋት ይሆንብናል፡፡ ከዚህ ይሰውረን!

ለቤት ፈላጊዎች በአክሰስ ሪል ስቴት ስር ያሉ መሬቶች ይከፋፈላሉ

   የአክሰስ ሪል ስቴት መስራችና ዳይሬክተር አቶ ኤርሚያስ አመልጋ፤ ከቤት ገዥዎች 1.4 ቢ. ብር ከሰበሰቡ በኋላ የገቡትን ውል ሳይፈጽሙ ባልታወቀ ምክንያት ከአገር መሰወራቸው ይታወሳል፡፡ መንግስት የቤት ፈላጊዎችን ተደጋጋሚ ክስና ቅሬታ መነሻ በማድረግም አቶ ኤርሚያስ ከአንድ ዓመት በፊት ያቀረቡት ዕቅድ ተቀባይነት አግኝቶ ወደ አገር ቤት መመለሳቸው ይታወቃል፡፡ ባቀረቡት እቅድና በተሰጣቸው ጊዜ አንድም ነገር አላከናወኑም በሚል ሰሞኑን በቁጥጥር ስር ውለው ምርመራ እየካሄደባቸው ተጠቁሟል፡፡ ከዚህ በኋላ የቤት ፈላጊው ዕጣፈንታ ምን ይሆናል? የገባበት ያልታወቀው የ1.4 ቢ. ብር ጉዳይስ? አቶ ኤርሚያስ የታሰሩት ያቀዱት ባለመሳካቱ ነው ወይስ በሌላ? በሚሉና በተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ ችግሩን ለመፍታት በመንግስት የተቋቋመው ኮሚቴ ሰብሳቢ ከአቶ ኑረዲን አህመድ ጋር አጭር ቆይታ አድርጋለች፡፡  
አቶ ኤርሚያስን በዋናነት ለእስር የዳረጋቸው ጉዳይ ምንድነው? የተሰጣቸው የጊዜ ገደብ አልቆ ነው ወይስ…?
የጊዜ ገደብ አልቆ አይደለም የታሰሩት፡፡ ሆኖም በንግግራቸው መሰረት አልፈፀሙም፡፡ ከውጭም ሆነው የላኩትና እዚህም መጥተው ያቀረቡት የስድስት ወር እቅድ ነበረ፡፡ ይህ እቅድ በስድስት ወራት ውስጥ ሶስት ነገሮችን መፈፀምና አክሲዮን ማህበሩን ስራ ማስጀመር ነው፡፡
እነዚህ ሶስት ጉዳዮች ምንድን ናቸው?
የመጀመሪያው ቅድሚያ የተሰጣቸውን ሳይቶች ማስነሳት፣ ሁለተኛው እቅድ የብድርና የእዳ ጉዳይ ያለባቸውንና የሶስተኛ ወገኖችን ጉዳይ መጨረስ፣ ሶስተኛው ደግሞ ሶስተኛ ወገን ጋ የሚገኘውን ብር መሰብሰብ ነበር፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ይሄ ተከናወነ የምንለው አንድም ነገር አላገኘንም፡፡ ይሄ ማለት አንዳቸውም ሳይቶች አልተነሱም፣ ምክንያቱም ሳይት ለማስነሳት ገንዘብ መገኘት አለበት፡፡ ገንዘብ አመጣለሁ ያሉት ደግሞ አብሬያቸው የምሰራው የውጭ ኮንትራክተር ኩባንያዎች አግኝቻለሁ ብለው ነበር፡፡ ነገር ግን አንዳቸውም መጥተው እንሰራለን ያሉ ወይም በተግባር ስራ የጀመሩ ኩባንያዎች የሉም፡፡ ሌላው ከሶስተኛ ወገኖች ጋር ያሉ ጉዳዮችን በድርድር እጨርሳለሁ አንድም በድርድር ያለቀ ጉዳይ የለም፡፡ ሶስተኛው 300 ሚሊዮን ብር አሰባስባለሁ ብለው ነበር፡፡ እንኳን ይሄን ገንዘብ አንድም ብር ወደ አክሲዮን ማህበሩ አካውንት አልገባም፡፡ ይህ የስድስት ወር እቅድ መጋቢት 14 ቀን 2007 ዓ.ም ነው የቀረበው፡፡ አብይ ኮሚቴውም ያፀደቀው ያን ጊዜ ነው፡፡ እስከ መስከረም 30 ቀን 2008 መከናወን ነበረበት፤ ምንም የተጀመረ ነገር ግን የለም፡፡ እንደገና ጥቅምት 18 ቀን 2008 ዓ.ም በመንግስት የተዋቀረው ኮሚቴ ሌላ አቅጣጫ ዘረጋ።
ምን አይነት አቅጣጫ?
ሌላው ወዲያ ወዲህ ይቅርና ቢያንስ ከአክሲዮን ማህበሩ የዳይሬክተሮች ቦርድ ጋር ተስማምታችሁና ተግባብታችሁ መስራት መቻላችሁን እንድናረጋግጥ፣ በተለምዶ ኒያላ ሞተርስ የተባለውን ሳይት ለማስጀመር ቅድመ ሁኔታዎችን ጨርሳችሁ አምጡልን አልናቸው፡፡ ሆኖም እስከ ህዳር አጋማሽና ከዚያ በኋላም ምንም እንቅስቃሴ አልጀመሩም፡፡ ይህን ሁሉ እድል ሰጥተን ታግሰንም የእኛ ሪፖርት፤ ካቀረቡት እቅድ ውስጥ አንዱንም እንዳልሰሩ ያረጋግጣል፡፡
እሺ አቶ ኤርሚያስ በቁጥጥር ስር ዋሉ፡፡ ከዚህ በኋላ ቤት ለማግኘት ጓጉቶ የሚጠብቀው ቤት ፈላጊ እጣ ፋንታ ምን ይሆናል ይላሉ?
የአቶ ኤርሚያስ መታሰር የህግ አግባብ ጥያቄ ነው፡፡ መጀመሪያም ከውጭ ሲመጡ የህግ ከለላ ተሰጥቷቸው ሳይሆን ያሉት በርካታ ክሶች ባሉበት ተቋርጠው የመፍትሔው አካል እንዲሆኑ ነው እንጂ ከህግ ተጠያቂነት ነፃ ሆነው አይደለም፡፡ ይህንን ስምምነት ማሳየት ይቻላል፡፡ በወንጀለኛ መቅጫ ስነስርዓት አንቀጽ መሰረት፣ የተመሰረቱባቸው ክሶች ባሉበት ተቋርጠው የመፍትሔው አካል ይሆናሉ ተብሎ ነው የመጡት፡፡ ነገር ግን እርሳቸው ባቀረቡት እቅድና በተሰጣቸው እድል መሰረት መፍትሔ ማምጣት ስላልቻሉ ቀደም ብለው የተቋረጡት ክሶች እንደገና ተንቀሳቀሱት ማለት ነው፡፡ ስለዚህ የህግ ጥያቄ እንጂ ከቤት ፈላጊዎቹና ከአክሲዮን ማህበሩ ጉዳይ ጋር የተገናኘ አይደለም፡፡
የህዝቡን ጥያቄ በተመለከተስ?
ቤት ፈላጊ ህዝቡን በተመለከተ አክሲዮን ማህበሩ 1.4 ቢሊዮን ብሩን ከበላና ያ የተበላው ብር መሬት ላይ ነው የዋለው ከተባለ የአክሲዮን ማህበሩ የዳይሬክተሮች ቦርድ ጠቅላላ ጉባኤ ጠርቶ ያ ብር በምንና እንዴት ያሉ ጉዳዮች ላይ እንደዋለ እንዲያሳይ ነው የሚደረገው፡፡ ቤት ፈላጊዎቹ በኮሚቴ ተደራጅተዋል፡፡ ቤት የሚሰሩ ሰዎች የሚደራጁበት አካሄድና የህግ አግባብ አለ፡፡ በዚያ መልኩ ህጋዊ ቁመና ፈጥረው፣ አክሰስ ያለው መሬት ወደ እነሱ የሚዞርበትን መንገድ እያመቻቸን ነው ያለነው፡፡ የተባለውን ብር በተመለከተ ከአክሲዮን ማህበሩ ጋር እየተደራደሩ በህግ እየተከታተሉ ይቆያሉ፡፡ የመሬት ጉዳይ ግን በህገ-ወጥ መንገድ የተያዙና በህጋዊ መንገድም የአክሰስ ሪል ስቴት የሆኑ መሬቶች አሉ፡፡ እነሱን ካሰባሰብን በኋላ ለቤት ፈላጊዎቹ እናደላድላለን፡፡
ቤት ፈላጊዎቹ መሬት ቢያገኙም የመስሪያውን ገንዘብ ከማውጣት አይድኑም ማለት ነው?
1.4 ቢሊዮን ብሩን በህግ ሂደት የሚያገኙበት መንገድ እንደተጠበቀ ሆኖ ነገር ግን መንግስት የቤት ፈላጊዎቹን ችግር ለማቃለል ቢያንስ መሬቱን እንዲያገኙ ያመቻችላቸዋል፤ ስለዚህ በራሳቸው ገንዘብ ይሰራሉ ማለት ነው፡፡

• ከዩኒቨርስቲው ጋር የተፈራረሙት የደብረ ሊባኖስ ገዳም አስተዳዳሪ ከሥራቸው ታግደው ነበር
• ሐዋርድ ያዘጋጀው ውል የባለቤትነት መብትን ይነፍጋል
• ቤተ ክርስቲያኒቱ የምትቀበለው ውል እንዲዘጋጅ ትዕዛዝ ተሰጥቷል

  “እውነት እና አገልግሎት” ተቋማዊ ብሂሉና መፈክሩ ነው፡፡ በተለይ፣ ለጥቁሮች በሚሰጠው የከፍተኛ ትምህርት ዕድልና አስተምሮ በሚያወጣቸው ጥቁር ምሁራን ብዛት ይታወቃል - የአሜሪካው ሐዋርድ ዩኒቨርስቲ፡፡
የዘርና የቀለም ልዩነቶች፣ ፖሊቲካዊና ኢኮኖሚያዊ በደሎች ያስከተሏቸውን መድልዎች፤ ለማኅበራዊ ፍትሕ በቆሙና ለሰብአዊ ነፃነት በሚሟገቱ ምሁራን ማስወገድ ዓላማው ያደረገው ዩኒቨርስቲው፤ በአፍሪካ፣ በአሜሪካና በሌላውም ዓለም የተበተኑ ጥቁሮችን የታሪክና የባህል ቅርሶች ያካበተበት የምርምር ማዕከሉም ከዓለም በቀዳሚነት ከሚጠቀሱት መካከል ያደርገዋል፡፡
በየአጋጣሚው ያሰባሰባቸውን ቅርሶችና ውርሶች፣ ወደ ጥንት ቦታቸውና ትክክለኛ ባለቤቶቻቸው በሕጋዊ መንገድ መመለስ፣ “ታሪካዊና ባህላዊ ሀብቶቹን ማክበር ነው፤” ይላሉ፣ የዩኒቨርስቲው የሥነ መለኰት ት/ቤት የአካዳሚያዊ ጉዳዮች ተባባሪ ዲን ዶ/ር ጌይ ባይረን፡፡ በተለይም ኢትዮጵያዊ ቅርሶችን ለኢትዮጵያ የመመለስ ጉዳይ፣ የት/ቤቱ የቆየ ፍላጎት እንደነበርና ይህም በአሜሪካም ሆነ በሌላው ዓለም ቅርሶቹን በግልና በተቋም ለያዙ ግለሰቦች፣ ሙዝየሞችና ተቋማት አርኣያነት እንዳለውና ተነሣሽነትንም እንደሚፈጥር ዶ/ር ባይረን ያስረዳሉ፡፡
በት/ቤቱ ማኅደረ ቅርስ ከተከማቹት ኢትዮጵያዊ የብራና ሥነ ጽሑፍ ሀብቶች መካከል፣ ገድለ ቅዱስ ሰራባሞንና ገድለ ቅዱስ ጳውሎስ አንዱ ነው፡፡ የብራና መጽሐፉ፣ በ1993 ዓ.ም. ዶ/ር አንድሬ ቲውድ ከተባሉ የዩኒቨርስቲው የቀድሞው ተማሪ በስጦታ የተበረከተ ሲሆን የ4ኛው መ/ክ/ዘመኑን ሰማዕት ቅዱስ ሰራባሞንና የሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስን ገድል በአንድ ጥራዝ የያዘ ነው፡፡ ከግብጽ ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ ከዐረብኛ ወደ ግእዝ የተተረጎመው በዘጠነኛው የደብረ ሊባኖስ ዕጨጌ አባ መርሐ ክርስቶስ አስተዳደር(ከ1456-1490 ዓ.ም.) ነበር፡፡
የጥንተ ክርስትና እና የሐዲስ ኪዳን ምሁር የሆኑት ዶ/ር ባይረን፣ የብራና መጽሐፉን ወደ ዲጅታል በመለወጥ፣ የትመጣውን ለማወቅ ጥናት ካደረጉት የሥነ መለኰት ት/ቤቱ ምሁራን አንዱ እንደነበሩ፣ የዩኒቨርስቲው ድረ ገጽ ዘግቧል፤ የገድሉ ጥንተ ባለቤት የደብረ ሊባኖስ ገዳም መሆኑ የታወቀውና ወደ ጥንት ቦታው ለመመለስ የተወሰነውም በጥናቱ ሒደት እንደነበር በዘገባው ተገልጧል፡፡ ከገድሉ ይዞታ ጋር በተያያዘ አስተዳደራዊና ሕጋዊ አካሔዶችን ጨምሮ የተለያዩ ዕንቅፋቶች ዩኒቨርስቲውን እንዳጋጠሙት፣ ድረ ገጹ በጥናቱ የተሳተፉ ምሁራንን ጠቅሶ ዘግቧል፡፡
ዩኒቨርስቲው ገድሉን ወደ ጥንት ቦታው በሕጋዊ መንገድ ለመመለስ በማሰብ፣ በሕግ አማካሪው አርቃቂነት “የስጦታ ውል” የተሰኘና በስምንት ነጥቦች የተዘረዘረ የስምምነት ሰነድ አዘጋጅቷል፡፡ ውሉ በሐዋርድ ዩኒቨርስቲና በደብረ ሊባኖስ ገዳም መካከል የተፈፀመ መሆኑን የሚገልፀው ዘገባው፤ በሥነ መለኰት ት/ቤቱ ዋና ዲን ዶ/ር አልቶን ፖላርድና በገዳሙ ፀባቴ (አስተዳዳሪ) አባ ወልደ ማርያም አድማሱ እንደተፈረመበትም ጠቁሟል፡፡ ይሁንና የውሉ ይዘት  ከባለቤትነት መብትና ከቅርሱ አመላለስ ጋር የተያያዙ ጥያቄዎችን የሚያስነሳ ሆኖ ተገኝቷል ይላሉ ምንጮች፡፡
ዩኒቨርስቲው÷ “ከማናቸውም ግዴታ ነፃ የሆነ የባለቤትነት መብት በብራና መጽሐፉ ላይ አለው” የሚለው የውሉ መግቢያ፣ ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሚመልሰውም “በስጦታ ለመስጠት በመፈለጉ” እንደኾነ ይገልፃል፡፡ የብራና መጽሐፉን ለገዳሙ በስጦታ የሚሰጥበት የባለቤትነት መብት እንዳለው ገዳሙ መስማማቱን የሚገልፀው ውሉ፤ ገዳሙም የብራና መጽሐፉን ሲቀበል፣ ዩኒቨርስቲው ሙሉ በሙሉ የሚያስተላልፈው፣ “አካላዊ የባለቤትነት መብት”ን እንደሆነ አስፍሯል፡፡ ገዳሙን በመወከል የፈረሙት ሓላፊም፤ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የውል ስምምነቱን እንድታከብር የሚያደርግ ዋስትና የመስጠት ሥልጣን እንዳላቸው በውል ሰነዱ ላይ ተመልክቷል፡፡
ባለፈው ሰኞ፣ የዩኒቨርስቲው ሓላፊዎችና ምሁራን በፓትርያርኩ ጽ/ቤት ተገኝተው ገድለ ቅዱስ ሰራባሞን ወጳውሎስን ለገዳሙ ባስረከቡበት ወቅት፣ በግልጽ የተነሡት ተቃውሞዎችና ስጋቶች፣ አስተዳዳሪው ከዩኒቨርስቲው ጋር የተፈራረሙት ሰነድ፣ የገድሉን ባለቤትነት ለገዳሙ ሳይሆን ለዩኒቨርስቲው መስጠቱን አረጋግጧል፡፡
ዩኒቨርስቲው ገድሉን ወደ ጥንት ቦታው መመለሱን ቤተ ክርስቲያኒቱ በከፍተኛ አድናቆት እንደምትመለከተውና እንደሚያስደስታት ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ተናግረዋል፡፡ “ጥንታዊው ብራና ቅርሳችን በመሆኑ ብንቀበለውም ስምምነቱ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን ሕጋዊ የባለቤትነት መብት የሚጎዳ፣ በትውልዱም ዘንድ የሚያስነቅፍ በመሆኑ ተቀባይነት የለውም፤” ሲሉ ተቃውመዋል፡፡
የውል ሰነዱም፣ በልዩ ጽ/ቤታቸው፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የውጭ ግንኙነት መምሪያ፣ በሕግ አገልግሎቱና በቅርሳቅርስ ጥበቃ መምሪያ በጋራ እንዲታይና እንዲመረመርም ፓትርያርኩ መመሪያ ሰጥተዋል፡፡
የደብረ ሊባኖስ ገዳም የሚገኝበትን የሰሜን ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት በሊቀ ጳጳስነት የሚመሩት አቡነ ቀውስጦስ በበኩላቸው፣ የቅርሱ መመለስ የሁላችን ደስታ ቢሆንም የተመለሰበት ሒደት ግን የቤተ ክርስቲያኗን ሥርዓትና መዋቅር እንዲሁም የገዳሙን ክብር እንዳልጠበቀ ገልጸዋል፡፡ ሦስተኛ ወገን በማስገባት በአስተዳዳሪውና በዩኒቨርስቲው የተፈረመውን ስምምነት÷ የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት፣ ሊቀ ጳጳሱ፣ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ፣ ቅዱስ ፓትርያርኩና ቅዱስ ሲኖዶሱ ሳያውቁትና ሳይመረምሩት ሕጋዊ የባለቤትነት መብትን በሚያሳጣ መልኩ መፈጸሙን ብፁዕነታቸው አስረድተዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱን ቀኖናና መዋቅር በመጣስ “ለመታየት እና ለመግነን” ሲባል የተፈጸመው ድርጊት አግባብ ያለመሆኑን ሊቀ ጳጳሱ በርክክቡ ወቅት በመናገራቸውም፣ “እዚያች ገዳም ትኖራታለህ፤ እንተያያለን፤ የፈለከውን ሹምበት” በሚል በገዳሙ አስተዳዳሪ መዘለፋቸው ተጠቅሷል፡፡
ከዚሁ ጋር በተያያዘ የገዳሙ አስተዳዳሪ ባለፈው ረቡዕ በሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት በተጻፈ ደብዳቤ÷ ከሥራ፣ ከደመወዝና ከአገልግሎት ታግደው እንደነበር ታውቋል፡፡ ከትላንት በስቲያ የገዳሙን መነኰሳት አስከትለው በመምጣት በፓትርያርኩ ፊት ሊቀ ጳጳሱን ይቅርታ በመጠየቃቸው በመካከላቸው  ዕርቀ ሰላም ወርዷል፤ ተብሏል፡፡  ይኹንና አስተዳዳሪው “ተጠሪነቴ ለቅዱስ ፓትርያርኩ ነው” በሚል ያለሥልጣናቸው ከዩኒቨርስቲው ጋር ፈጽመውታል የተባለው ስምምነት ያስነሣቸው ስጋቶችና ተቃውሞዎች ግን መቋጫ አላገኙም፡፡
ቤተ ክርስቲያኒቱ የባለቤትነት መብቷን አሳልፋ ሰጥታ መልሳ በስጦታ መልክ የምትቀበልበት አንዳችም ምክንያት እንደሌለና የዩኒቨርስቲውም ፍላጐት እንዳልሆነ ሒደቱን በቅርበት የሚከታተሉ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡  የስጦታ ውሉ ባስነሳው ውዝግብ ሳቢያ ዩኒቨርስቲው የሕግ አማካሪውን ሳያሰናብት እንዳልቀረም እኒሁ ምንጮች ይናገራሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቷ በበኩሏ፤ “የስጦታ ውል” ሰነዱን እንደምትቃወመው ለዩኒቨርስቲው በይፋ በማሳወቅ፣ ተቀባይነት ያለው ስምምነት እንዲዘጋጅ ጥያቄ ማቅረብ እንዳለበት ተወስኗል፡፡ አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች ቤ/ክርስቲያኗ የአሜሪካንና የአውሮፓን ዩኒቨርሲቲዎች፣ ቤተ መጻሕፍትና ቤተ መዛግብት ባደመቁት  ሌሎች ቅርሶቿ አመላለስ ላይ የራሱ አዎንታዊ ተፅዕኖ ያሳድራል ብለዋል፡፡

የሙከራ ስርጭቱን በናይል ሳት 11595 ጀምሯል
   መቀመጫውን በኬንያ ያደረገውና በኢትዮጵያውያን ባለሃብቶች የተቋቋመው “ናሁ ቲቪ” የተሰኘ የሳተላይት ቴሌቪዥን ጣቢያ በመጪው የካቲት ወር መደበኛ የ24 ሰዓት ስርጭቱን እንደሚጀምር አስታወቀ፡፡
ከትላንት በስቲያ ቦሌ በሚገኘው ጎልደን ቱሊፕ ሆቴል በተከናወነው የጣቢያው ይፋ የምረቃ ስነስርዓትና ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ የቴሌቪዥን ጣቢያው ባለቤትና ፕሬዚዳንት አቶ ወንድ ወሰን ካሴ እንደተናገሩት፤ በናይል ሳት 11595 ቨርቲካል (V) ላይ የሙከራ ስርጭቱን ቀደም ብሎ የጀመረው “ናሁ ቲቪ” በየካቲት ወር መደበኛ የ24 ሰዓት ስርጭቱን የሚጀምር ሲሆን፣ ከዚህ በተጨማሪም በኢቴል ሳት 70 ዲግሪ ዌስት 70w እና IP ቲቪ በኩል ስርጭቱን ለመላው አለም ለማዳረስ አቅዷል፡፡
የቴሌቪዥን ጣቢያው በመላው አለም ለሚገኙ ኢትዮጵያውያን ተደራሽነቱን ለማስፋትና ጥሩ የመረጃ አማራጭ ለመሆን በማሰብ፣ በሰሜን አሜሪካና አውሮፓ የዜና ወኪል ለመክፈት በዝግጅት ላይ እንደሚገኝም የ “ናሁ ቲቪ” ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ቅዱስ ዳኛቸው ተናግረዋል፡፡
“ናሁ” የሚለው ቃል የግዕዝ ቃል መሆኑንና “አሁን” የሚል ትርጉም እንዳለው የተናገሩት አቶ ቅዱስ፤ “ጊዜው አሁን ነው” ወይም “Now is the time” የሚል መርህ ያነገበው ጣቢያው፤ ከሚያቀርባቸው ፕሮግራሞች 75 በመቶው በሪያሊቲ ሾው ፎርማት፣ 25 በመቶው ደግሞ በቶክ ሾው አቀራረብ እንደሚዘጋጁም ገልጸዋል፡፡
በጣቢያው የሚተላለፉት ፕሮግራሞች ሙያዊ የጥራት ደረጃቸውን የጠበቁ እንደሚሆኑ የተገለጸ ሲሆን፣ የቴሌቪዥን ጣቢያው ሙያ ነክ ጋዜጠኝነት ላይ እንደሚያተኩርና በተለያዩ የሙያ መስኮች የሰለጠኑና የሚሰሩበትን ጉዳይ በጥልቀት የሚያውቁ ባለሙያዎች በአዘጋጅነት እንደሚሳተፉበትም ተገልጿል፡፡
እያዝናና መረጃ በመስጠት ላይ ትኩረቱን ባደረገው “ናሁ ቲቪ”፣ በርካታ ታዋቂ ግለሰቦችና ባለሙያዎች በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ የሚያጠነጥኑ አዝናኝና አስተማሪ ፕሮግራሞችን ለማቅረብ ዝግጅታቸውን ማጠናቀቃቸውን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለስልጣን በያዝነው ዓመት መጀመሪያ ላይ አካባቢያዊ አቀፍ (Local frequency) የቴሌቪዥን ጣቢያ ለመክፈት ለሚፈልጉ ኢትዮጵያዊያን ባስተላለፈው ጥሪ መሰረት ተገቢውን መስፈርት አሟልቶ የተመሰረተው ቱባ ሚዲያ፣ መቀመጫውን በኬንያ ካደረገው ናሁ ጋር በመቀናጀት ጣቢያውን መክፈቱ ታውቋል፡፡



“በማህበራዊ ድረ ገፅ ፅሁፍ ሰበብ ብንባረርም ጉዳዩ ሌላ ነው

    የሰማያዊ ፓርቲ ስነ-ስርዓት ኮሚቴ ሰሞኑን ባደረገው ስብሰባ፤ ከፍተኛ የስነ - ስርዓት ጥሰት ፈፅመዋል ያላቸውን አራት የብሔራዊ ምክር ቤት አባላት ከፓርቲው አባረረ፡፡
የተባረሩት የብሔራዊ ም/ቤት አባላት፣ በእስር ላይ የሚገኙት የፓርቲው የቀድሞው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ዮናታን ተስፋዬ፣ አቶ ኢያስጴድ ተስፋዬ፣ አቶ ጋሻዬነህ ላቀና አቶ ዮናስ ከድር ናቸው ተብሏል፡፡
ፓርቲው በተባበሩት አባላት የስንብት ደብዳቤ ላይ የተባረሩበትን ምክንያት የጠቀሰ ሲሆን የቀድሞ አባላት የታሪክና የጎሳ ጥላቻ የሚቀሰቅስ የኢትዮጵያን ህዝብና የተለያዩ የሀገራችንን መንግስታት ታሪኮች የሚያጐድፍ፣ ለጥላቻ የሚያነሳሳና በህዝብ መካከል የባህል መከባበር እንዳይኖር የሚያደርግ… ፅሁፎችን በማህበራዊ ድረገፅ ላይ በማሰራጨታቸው ክስ ተመስርቶባቸው መባረራቸውን ያስረዳል፡፡ በተጨማሪም ተሰናባቾቹ የሰማያዊ ፓርቲን ደንብና ፕሮግራም በመጣስ፣ ስለፓርቲው ከማስረዳት ይልቅ ሌላ ቀደምት የፖለቲካ ተቋማትን ፕሮግራምና ደንብ በመደገፍ እንደሚያብራሩ ጠቅሶ፣ በአጠቃላይ ከፋፋይነት ያላቸውን ፅሁፎች አሰራጭተዋል ብሏል፡፡
ከፓርቲው ከተባረሩት መካከል አቶ ዮናስ ከድር፤ በማህበራዊ ድረ - ገፅ ላይ የአቶ ኢያስጴድንና አቶ ዮናስን ሀሳብ የሚደግፉ ጽሑፎች በመለጠፍ በተለይም በኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ ላይ መሳለቃቸውንና፣ በባንዲራ ዙሪያ ከፋፋይ ፅሁፎችን ማውጣታቸው ተጠቁሟል፡፡ ተሰናባቾች በበኩላቸው፤ ምንም እንኳን የተከሰሱትና የተሰናበቱት ማህበራዊ ድረ - ገፅ ላይ ተሰራጨ በተባለ ፅሁፍ ቢሆንም ይህ ሽፋን እንጂ የተከሰሱበት ትክክለኛ ምክንያት እንዳልሆነ ጠቁመው፤ የፓርቲውን ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃልን ከቦታው ማስነሳት የሚፈልጉ አካላት እርሱን ስለደገፍንና አካሄዳቸውን ስለተቃወምን የሸረቡብን ሴራ ነው ሲሉ ቅሬታቸውን ሰንዝረዋል፡፡
አቶ ኢያስጴድ በሰጡት አስተያየት፤ “ጉዳዩ ወደ ዲሲፒሊን ኮሚቴ የተመራው የማይመለከታቸው ግለሰብ በሰጡት ድምፅ በተፈጠረ ብልጫ ነው” ብለዋል፡፡ የፓርቲው የኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን ሰብሳቢ አቶ አበራ ገብሩ በበኩላቸው፤ ድምፅ መስጠት አይገባውም የተባለው ግለሰብ ድምፅ ባይቆጠርም አቶ ኢያስጴድን ወደ ዲሲፒሊን ኮሚቴ ለማቅረብ በቂ ድምፅ ተገኝቶ እንደነበር ገልፀዋል፡፡
ከፓርቲው አባልነት የተሰናበቱት ግለሰቦች በ15 ቀናት ውስጥ ይግባኝ የመጠየቅ መብት እንዳላቸው ታውቋል፡፡



የሽበት ማጥፊያ ቀለሞችን አዘውትሮ መጠቀም ለካንሰር ያጋልጣል

ቀለም ተቀባ ወይ ወንዱ ሁሉ ዘንድሮ
ሽማግሌ ጠፋ ሽበት እንደ ድሮ ….
                           (ድምፃዊት በዛወርቅ አስፋው)
ዛሬ ዛሬ የሽምግልና ፀጋ የሆነው ሽበት በራስ ቅላቸው ላይ ሳይታይ የሚያረጁ ወንዶችና ሴቶች እየተበራከቱ መጥተዋል፡፡ ሽበት የብስለትና የአዋቂነት ምልክት መሆኑ እየቀረ የመጣ ይመስላል፡፡ አብዛኛው ሰው ነጭ ፀጉር ሳይታይበት ወደማይቀረው እርጅና መጓዝን መርጧል፡፡ በዚህም የተነሳ ሽበትን የሚያጠፉ የፀጉር ቀለሞች ተጠቃሚዎች በርክተዋል፡፡
በአገራችን በዚህ ዙሪያ የተደረገ ጥናት መኖሩን እንደማያውቁ የሚናገሩት የሥነ ውበት ባለሙያዋ ወ/ሮ ትርሀስ ሰለሞን፤ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን የፀረ-ሽበት ቀለም ተጠቃሚው ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ እየጨመረ መምጣቱን ይገልፃሉ፡፡ በቦሌ መድኀኒዓለም፣ በሣር ቤትና በሳሚት አካባቢ የሴቶችና የወንዶች የውበት ሳሎኖች ከፍተው አገልግሎት የሚሰጡት ባለሙያዋ፤ ከደንበኞቻቸው መካከል ከ80 በመቶ በላይ የሚሆኑት የፀረ-ሽበት ቀለሞች ተጠቃሚ መሆናቸውን ይናገራሉ። የፀረ-ሽበት ቀለሞች ተጠቃሚ ደንበኞቻቸው በአማካይ በወር ሁለት ጊዜ ለዚሁ አገልግሎት ወደ ማዕከሉ እንደሚመጡ የጠቆሙት ወ/ሮ ትርሀስ፤ ቀለሙን ደጋግሞ የመቀባት ጉዳይ ደንበኞቻቸው እንደሚጠቀሙት የፀረ-ሽበት ቀለም አይነት እንደሚለያይ ገልፀዋል፡፡
ፀጉር ተፈጥሮአዊ ቀለሙን የሚይዘው በሰውነታችን ውስጥ በሚገኘው “ሜላሚን” የተሰኘ ኬሚካል ሳቢያ ሲሆን የኬሚካል መጠኑ መጨመርም ሆነ መቀነስ በፀጉራችን ተፈጥሮአዊ መልክ ላይ ተፅዕኖ ያሳድራል፡፡ ዕድሜያችን እየጨመረ ሲሄድ የኬሚካል መጠኑ እየቀነሰ የሚመጣ ሲሆን በዚህም ምክንያት አዲስ የሚበቅለው ፀጉራችን ቀለም አልባ ሆኖ እንዲያድግ ያደርገዋል፡፡ ይህን ጊዜም ሽበት ይበቅላል፡፡ የፀጉር ቀለም አልባ ሆኖ ማደግ አንዳንድ ጊዜ በህመምና በዘር አማካኝነት ሊከሰት እንደሚችል ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡ አንዳንድ ሰዎች በወጣትነት ዕድሜ ላይ ሆነው ፀጉራቸው የሚሸብተውም በዚህ የተነሳ ነው፡፡
በዕድሜ መሸምገል የተነሳ የሚመጣውን የፀጉር መሸበት ለማጥፋት በተለይ የከተማ ነዋሪዎች የፀጉር ቀለም ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸው ይነገራል። እንደ ሥነ-ውበት ባለሙያዋ ወ/ሮ ትርሀስ አይነት ሥራቸው በቀጥታ ከፀጉር ጋር የሚያገናኛቸው ሰዎች ደግሞ፤ የዚሁ የፀረ-ሽበት ትግል አጋርና ምስክሮች ናቸው፡፡ በአገራችን በጉዳዩ ላይ የተደረጉ ጥናቶች ባይኖሩም፣ በአሜሪካ ኒውዮርክ ዩኒቨርሲቲ የተደረገ ጥናት፤ 68% የሚሆኑት ሴት አሜሪካውያን የፀረ-ሽበት ቀለም ተጠቃሚዎች መሆናቸውን አረጋግጧል፡፡ ታይም መፅሄት ያወጣው አንድ ዘገባም፤ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማን ጨምሮ ታዋቂ ፖለቲከኞች፣ የፊልምና የሙዚቃ ባለሙያዎች እንዲሁም ሌሎች ዝነኞች የፀረ-ሽበት ቀለም ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቁሟል፡፡
Boomgril.com የተሰኘው በሴቶች ጤናና ውበት አጠባበቅ ላይ አተኩሮ የሚሰራው ድረ ገፅ ያወጣው መረጃ እንደሚያሳየው፤ በአሜሪካ የሴኔት አባላት ከሆኑና ዕድሜያቸው ከ46-74 ዓመት ከሆናቸው ሴቶች መካከል የፀረ ሽበት ቀለም ተጠቃሚ ያልሆነ አንድም ሰው አልተገኘም። በፀረ ሽበት ቀለሞች አጠቃቀም ላይ ሴቶች ከፍተኛ ድርሻ ቢኖራቸውም እጅግ በርካታ ቁጥር ያላቸው ወንዶችም የፀረ ሽበት ቀለሙ ተጠቃሚ መሆናቸውንና የተጠቃሚው ቁጥርም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱን ድረ ገፁ አመልክቷል፡፡ የፀረ ሽበት ቀለም መቀባት ማራኪነትና ተወዳጅነት ይጨምራል የሚል እምነት በተጠቃሚዎች ዘንድ እንዳለም ተጠቁሟል፡፡ የፀረ ሽበት ቀለም ተጠቃሚዎች ለውበታቸው የሚጨነቁትን ያህል ለጤናቸውም ማሰብ እንዳለባቸው ያሳሰበው ድረ ገፁ፤ ቀለሙን አዘውትሮ መጠቀም ለተለያዩ የጤና ችግሮች እንደሚያጋልጥ ባለሙያዎችን ጠቅሶ ዘግቧል፡፡
የሥነ ውበት ባለሙያዋ ወ/ሮ ትርሀስ በአሁኑ ወቅት ለደንበኞቻቸው የተለያየ ዓይነት ደረጃ ያላቸውን የፀረ ሽበት ቀለሞች እንደሚጠቀሙ ያስረዳሉ፡፡ እንደ ደንበኛው ፍላጎትና ጥያቄም ቀለሞቹን በውበት ማዕከሎቻቸው ውስጥ በማቅረብ አገልግሎቱን ይሰጣሉ፡፡ በወ/ሮ ትርሀስ የውበት ማዕከል ውስጥ ለጥቂት ቀናት የሚያገለግሉ፤ በውሃና በዝናብ በቀላሉ የሚለቁ ዋጋቸው ርካሽ የሆኑ የፀረ-ሽበት ቀለሞች ይገኛሉ፡፡ ከተቀቡት በኋላ ለሳምንታት የማይለቁ፣ ወደ ፀጉር ውስጠኛው ክፍል በተወሰነ ደረጃ የሚዘልቅ በዝናብም በቀላሉ የማይለቁ፣ በዋጋ ወደድ ያሉ ቀለሞችም እንዳሏቸው የሚናገሩት ወ/ሮ ትርሀስ፤ እኒህ አይነቶቹ ፀረ ሽበት የፀጉር ቀለሞች በርካታ ተጠቃሚዎች እንዳሏቸውና በውበት ሳሎኖቻቸው ውስጥ በስፋት ጥቅም ላይ እንደሚውሉ ይናገራሉ፡፡
በውስጠኛው የፀጉራችን ክፍል አልፎ ወደ ማዕከላዊው የፀጉራችን ክፍል የሚገባና በቀላሉ የማይለቅ፣ ለወራት እንደጠቆረ አሊያም እንደቀላ የሚዘልቅ የፀረ ሽበት ቀለም እንዳለ የሚገልፁት የሥነ ውበት ባለሙያዋ፤ ይህ አይነቱ ቀለም በዋጋው እጅግ ውድ በመሆኑ በአገራችን ገበያ ውስጥ እምብዛም እንደማይገኝ ይናገራሉ፡፡ አገልግሎቱን ፈልጎ ለሚመጣና የመክፈል አቅም ላለው ደንበኛ ግን የፀረ ሽበት ቀለሙን ከውጭ በማስመጣት ጥቅም ላይ እንደሚያውሉ ይገልፃሉ፡፡
የፀረ ሽበት ቀለም ተጠቃሚው ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መሄዱ ጥሩ ምልክት አይደለም የሚሉት የቆዳና የአባላዘር ስፔሻሊስቱ ዶ/ር አብርሃም ተከተል፤ ለፀረ ሽበትም ሆነ ለፀጉር ማቅለሚያነት ታስበው የሚሰሩ የፀጉር ቀለሞች በውስጣቸው ካንሰር አምጪ ኬሚካሎችን መያዛቸውንና የእነዚህ ኬሚካሎች ተደጋግሞ ጥቅም ላይ መዋል በካንሰር የመያዝ ዕድልን እንደሚጨምር አመልክተዋል። ቀደም ሲል በጥቅም ላይ ይውሉ የነበሩት የፀጉር ቀለሞች ከሰልና ታር የተባሉ ኬሚካሎችን የያዙ እንደነበሩ የሚናገሩት ዶክተር አብርሀም፤ በአሁኑ ወቅት የሚፈበረኩትና ጥቅም ላይ የሚውሉት በአብዛኛው ከፔትሮሊየም የሚሰሩና ሜቲክሲና ዲያሚይን የተባሉ ካንሰር አምጪ ኬሚካሎችን በውስጣቸው የያዙ ቀለሞች ናቸው ብለዋል። ምንም እንኳን እነዚህን ቀለማት አምራች የሆኑ አገራት ካንሰር አምጪ ኬሚካሎችን ለቀለም ምርቱ ግብአትነት ከማዋል መቆጠባቸውን የሚገልፁ ቢሆንም ምርቶቹ ሙሉ በሙሉ ከካንሰር አምጪ ኬሚካሎች የፀዱ ለመሆናቸው ማረጋገጫ መስጠት አለመቻላቸውንም ዶክተሩ ገልፀዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት የፀረ ሽበት ቀለሞች ተጠቃሚው ቁጥር በአገራችን እየጨመረ መምጣቱ ጉዳዩን የበለጠ አሳሳቢ ያደርገዋል ያሉት የህክምና ባለሙያው፤ እነዚህ ሰዎች ቀለማቱን በሚጠቀሙ ጊዜ ከፍተኛ ጥንቃቄ ሊያደርጉ እንደሚገባና አዘውትሮ ቀለሞቹን ከመጠቀም መቆጠብ እንደሚገባቸው ይመክራሉ። የፀረ ሽበት ቀለሞች ተጠቃሚዎች እጅግ ለከፋው የቆዳ ካንሰርና ለሌሎች የጤና ችግሮች ከመጋለጣቸው በፊት ከድርጊታቸው መቆጠብና እርጅና ተፈጥሮአዊ መሆኑን በመገንዘብ፣ ለውጦቹን በአግባቡ መቀበልና እንደ አመጣጣቸው ማስተናገድ እንደሚገባቸውም ዶ/ር አብርሃም ያስረዳሉ፡፡  


“ፀሐይ መማር ትወዳለች” በተሰኘው የፓፔት ትርኢት የሚታወቀው ዊዝኪድስ ወርክሾፕ፤ በጤናና በጤና ዙሪያ የሚያጠነጥኑ 39 ፊልሞችንና 12 መፃህፍትን አዘጋጅቶ ሊያስመርቅ መሆኑ ተገለፀ።
በህፃናት ጤና ዙሪያ ግንዛቤ ለማስጨበጥና የባህርይ ለውጥ ለማምጣት ያስችላል ተብሎ ከዩኤስኤይድ በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ የተሰሩት የህፃናት ፊልምና መፃህፍት፣ በመጪው ጥር 26 በኦሮሞ ባህል ማዕከል እንደሚመረቁ የዊዝኪድስ ወርክሾፕ መስራችና ሥራ አስኪያጅ ወ/ሮ ብሩክታዊት ጥጋቡ ተናግረዋል፡፡
ድርጅቱ፤ “ፀሐይ መማር ትወዳለች” የተሰኘውን የፓፔት ትርኢት በመጠቀም በአራት ዋና ዋና ርዕሰ ጉዳዮች ማለትም ተላላፊ የሆኑ በሽታዎች፣ የተመጣጠነ ምግብ፣ ራስን ከአደጋ ስለመከላከልና ስለንፅህና አጠባበቅ ለህፃናት የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎችን ለመስራት ከፍተኛ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ መሆኑንም ሥራ አስኪያጇ ገልፀዋል፡፡
በኢትዮጵያ ውስጥ በየዓመቱ 350ሺህ ህፃናት እንደሚሞቱ ጥናቶች ያሳያሉ፡፡ ከእነዚህ ህፃናት መካከልም 90 በመቶ የሚሆኑት የሚሞቱት በቀላሉ አስቀድሞ መከላከልና ህክምና ማግኘት በሚችሉ የሳንባ ምች፣ ተቅማጥ፣ ወባ፣ የተመጣጠነ ምግብ እጥረትና ኤችአይቪ ኤድስን የመሳሰሉ በሽታዎች መሆኑን የጠቆሙት ስራ አስኪያጇ፤ የህፃናቱን ግንዛቤ በማሳደግ እነዚህን ሞቶች ለመቀነስ ብሎም ለማስቀረት ይቻላል ብለዋል፡፡ በቅርቡ የሚመረቁት ፊልሞችና መፃህፍት አካል ጉዳተኛ ህፃናትንም ከግምት ውስጥ ያስገቡ ሲሆን የምልክት ቋንቋን እንዳካተቱም እንደሆነም ተገልጿል፡፡

    ቶታል ኢትዮጵያ “Startupper of the year by total” በሚል ርዕስ ባዘጋጀው የመነሻ ካፒታል ሽልማት ውድድር ላይ ዕጩዎች እንዲወዳደሩ ጋብዟል፡፡
ከ1-3 ለሚወጡ አሸናፊዎች ከ350ሺ ብር እስከ 150ሺ ብር ይሸልማል ተብሏል፡፡
ውድድሩ ማንኛውም ዕድሜው 35 ዓመት ወይም ከዚያ በታች ለሆነ ኢትዮጵያዊ ነፃና ክፍት ሲሆን ተወዳዳሪዎች ፕሮጀክታቸውን በኢንተርኔት (ኦንላይን) ማቅረብ ይችላሉ ተብሏል፡፡ ለውድድር የሚቀርቡት ፕሮጀክቶች አዲስ ፈጠራ፣ ፈር ቀዳጅ፣ ሊያድጉ የሚችሉና የሰዎችን ኑሮ የሚያሻሽሉ መሆን እንዳለባቸው ተጠቁሟል፡፡  
እጩ ተወዳዳሪዎች ፕሮጀክታቸውን እስከ ጥር 22 ቀን 2008 ዓ.ም ድረስ ማቅረብ ይኖርባቸዋል፡፡ 10 ፕሮጀክቶች በመስፈርቶች መሰረት በዳኞች ከተመረጡ በኋላ የስም ዝርዝር ከየካቲት 20 በፊት በዌብ ሳይት እንደሚገለጽ፣ ድርጅቱ ለተመረጡ ተወዳዳሪዎች የተለያዩ ድጋፎችን እንደሚያደርግ ተመልክቷል፡፡
ተወዳዳሪዎች ከመጋቢት 6 በፊት የመጨረሻ ፉክክር (ፕሬዘንቴሽን) ካደረጉ በኋላ በዳኞች የተመረጡ ፕሮጀክቶች የሚሸለሙ ሲሆን 1ኛ የወጣው ፕሮጀክት 350 ሺህ ብር፣ 2ኛው  200 ሺህ ብር፣ 3ኛው 150ሺህ ብር እንደሚሸለሙ ታውቋል፡፡