Administrator

Administrator

- እስካሁን 6 ክብረ ወሰኖችን አስመዝግቧል
- ከወራት በፊት የአመቱ ምርጥ አትሌት ተብሏል

በአሜሪካ የ3ኛ ክፍል ተማሪ የሆነውና የ8 አመት ዕድሜ ያለው ትውልደ ኢትዮጵያዊው ታዳጊ ታም ጋቬናስ፤ ባለፈው ሳምንት በኒውዮርክ በተካሄደው የኬንዝ ዶላን መታሰቢያ የ5 ሺህ ሜትር የሩጫ ውድድር አዲስ የአለም ክብረወሰን ማስመዝገቡን ያሁ ኒውስ ዘግቧል፡፡
ታዳጊው የ5ሺህ ሜትር ሩጫውን በ18 ደቂቃ በማጠናቀቅ፣በዚህ ዕድሜ ርቀቱን ፈጥኖ የጨረሰ የዓለማችን ባለተስፋ ታዳጊ አትሌት ተብሏል ያለው ዘገባው፤ታዳጊው ከሶስት አመታት በፊትም በዚያው በአሜሪካ በተካሄደ የ5 አመት ዕድሜ ያላቸው ታዳጊዎች የሩጫ ውድድር ላይ በ800 ሜትርና በ1ሺህ 500 ሜትር አዲስ የዓለም ክብረወሰን ማስመዝገቡን አስታውሶ፣ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ በርካታ ሽልማቶችን ማግኘቱንና መነጋገሪያ መሆኑን አስታውቋል፡፡  
ባለፈው አመት በ800 ሜትር፣ በ1ሺህ 500 ሜትርና በ400 ሜትር ውድድሮች አዳዲስ ብሄራዊ ክብረ ወሰኖችን ያስመዘገበው ታዳጊው፤ከወራት በፊትም በአሜሪካ በተካሄደው ዩኤስኤቲኤፍ አመታዊ የታዳጊ አትሌቶች ሽልማት፣የአመቱ ምርጥ አትሌት ተብሎ መሸለሙም ታውቋል፡፡  
ታም ጋቬናስ በኢትዮጵያ እንደተወለደና ዕድሜው ሶስት አመት ሳይሞላው፣ ሜሪ ሊዛ ጋቬናስ በተባለቺው አሜሪካዊት አማካይነት በጉዲፈቻ ወደ አሜሪካ መወሰዱን ያስታወሰው ያሁ ኒውስ፣ አሳዳጊው የተፈጥሮ ክህሎቱን በማጤን ለስኬት እንዲታትር ታበረታታው እንደነበር ጠቁሟል፡፡

     በባንግላዴሽ ባለፈው ሳምንት የታጠቁ ሃይሎች በፈጸሙት ተከታታይነት ያለው ጥቃት፣ በበርካታ ዜጎች ላይ አሰቃቂ ግድያዎች መፈጸማቸውን ተከትሎ የጽንፈኛ ቡድኖችን እንቅስቃሴ ለመግታት የተጠናከረ እርምጃ መውሰድ የጀመረው የአገሪቱ መንግስት፤ ከ11 ሺህ በላይ ተጠርጣሪዎችን ማሰሩን ሲኤንኤን ዘገበ፡፡
የአገሪቱ መንግስት ሰሞኑን በርካታ ዜጎችን በመግደል ከፍተኛ ጥፋት ካደረሱ ጽንፈኛ ቡድኖች ጋር ግንኙነት አላቸው ያላቸውን 150 ታጣቂዎችና በአገሪቱ በተከሰቱ ብጥብጦች በተለያዩ ወንጀሎች ተሳትፈዋል በሚል የጠረጠራቸውን ከ11 ሺህ በላይ ግለሰቦች ማሰሩን ዘገባው ገልጧል፡፡
የአገሪቱ ፖሊስ አብዛኞቹ በቁጥጥር ስር የዋሉ ግለሰቦች ጃማቱል ሙጅሃዲን የተባለው አክራሪ ቡድን አባላትና ለጥፋት ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ናቸው ቢልም፣ ባንግላዴሽ ናሽናሊስት ፓርቲ የተባለው የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲ ግን፣ የመንግስት እስር በአባላቶቼ ላይ ያነጣጠረ ነው፤ 2 ሺህ 100 አባላቶቼና ደጋፊዎቼ ታስረውብኛል ማለቱ ተዘግቧል፡፡
በባንግላዴሽ ባለፈው አንድ አመት ብቻ 35 ያህል ተመሳሳይ የሽብር ጥቃቶችና ግድያዎች መፈጸማቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ በአገሪቱ በህቡዕ የሚንቀሳቀስ አንድ አክራሪ ጽንፈኛ ቡድንም ከእነዚህ ጥቃቶች መካከል ሃያ ሶስቱን ለመፈጸሙ ሃላፊነት መውሰዱን ገልጧል፡፡

    የዚህ ዓምድ ትኩረት ሥነ-ጥበብ፤ በዋነኝነትም የኢትዮጵያ ሥነ-ጥበብ ነው። በተለይም ዘመንኛው (Contemporary) የኢትዮጵያ ሥነ-ጥበብ ላይ አጽንኦት በመስጠት ወቅታዊና በመታየት ላይ ያሉ ትርዒቶችን ይዳስሳል፡ ገለጻ ያቀርባል፡ ያትታል፡ ይመረምራል፡ ሂስ ያቀ ርባል። ግለሰቡን
ሳይሆን ስራውን በመተቸት የሂስ ባሕልን ለማዳበር ይጥራል፡፡ የዓምደኛውን እይታ መሬት በያዙና ሚዛን በሚደፉ አመክንዮች በማስደገፍ ግለሰብ አንባቢ ስለ ሥነ-ጥበብና ስለ ኢትዮጵያ ሥነ-ጥበብ ግንዛቤ እንዲጨብጥ፣ የዕይታ ባሕሉ (Visual Culture) እንዲዳብር፡ የሥነ-ጥበብ አድናቆቱ
ከፍ እንዲል፡ ሥነ-ጥበብን የሕይወት ዘዬው (Life Style) አድርጎ እንዲወስደው መንገድ ለመክፈት ይጥራል። በማኅበረሰብና በሃገር ደረጃም ልክ እንደ ኤኮኖሚያዊ፡ ፖለቲካዊ፡ ማኅበራዊ፡ ባሕላዊና ትውፊታዊ እንዲሁም ታሪካዊ እንቅስቃሴዎች ሁሉ ሥነ-ጥበብን የሰፊው የሕይወት መር (Mainstream) አካል እንዲሆን ይተጋል።

የትርዒቱ ርዕስ፡ የውስጥ ዳና ሠዓሊ፡ ሙሉጌታ ታፈሰ (ዶ/ር) የትርዒቱ አይነት፡ የግል፤ የቀለም ቅብ ስራዎች ብዛት፡ 41 የቀለም ቅብ፤ 11 የፓስቴል ኪነ- ንድፍ(Pastel Drawing)፤ 1 የቅይጥ (Mixed
Media) ስራዎች የቀረበበት ቦታ፡ ሌላ ጋለሪ(ጦር ኃይሎች፣ ቻይና ኤምባሲ አካባቢ፣ ለመጎብኘት ከረቡዕ-እሁድ ከጠዋቱ 4:00-ምሽቱ 12:00 ሠዓት ለአቅጣጫ+251911300756)፡ አዲስ አበባ
ጊዜ፡ ሰኔ 04-ሰኔ 20: 2008 ዓ.ም ዳሰሳ አቅራቢ፡ ሚፍታ ዘለቀ (የሥነ-ጥበብ አጋፋሪ)       

ጥቆማ-ልብ የሚል ልብ ላለው!
ሰፊው የማኅበረሰብ ክፍል ኑሮን ለማሸነፍ ደፋ ቀና በሚልባት፤ ሃብታሙ ሺዎችን ሚሊዮን፡ ሚሊዮኖችን ለማብዛትና ቢሊዮኖችን ለማካበት ነብሱን በሳተባት፤ ምሁሩም የጋን ውስጥ መብራቱን በታቀፈባትና መንግስትም ከልማት አቅጣጫ ብቻ ልጓሙን ባጠበቀባት አዲስ አበባችን ሠዓልያንና ለሥነ-ጥበብ ሕልውና የሚተጉ ተቋማት ለዘመንኛ ኑሮአችን የሰላ አተያይ እንዲኖረን የሚያግዙና ወሳኝ ሚና የሚጫወቱ ትርዒቶችን በማቅረብ ላይ ይገኛሉ፡፡ በቀጣይ ሳምንታት የተወሰኑት ላይ ዳሰሳ የማቀርብ ሲሆን ከዚህ ጥድፊያና ግርግር ከተሞላበት የኑሮ እሽክርክሪት ጥቂት ጊዜ ቆርሳችሁ፣ ትርዒቶቹን ቀድማችሁ ብትመለከቷቸው ዳሰሳዎቼን ለመረዳትም ሆነ ሥነ-ጥበብን የሕይወታችሁ ዘዬ(Life Style) አድርጋችሁ ለመውሰድ ማለፊያ ልምምድ ይሆናችኋልና የትርዒቶቹን ቦታዎች ልጠቋቅማችሁ፡፡ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዝየም፡ ጊዜያዊ የሥዕል ማሳያ አዳራሽ- በሠዓሊ ፍቅሩ ገብረማሪያም-እስከ ሐምሌ 07 የሚቆይ የግል ትርዒት፤ በአልያንስ ኢትዮ-ፍራንሴስ-በሠዓልያን አዲስ ገዛኧኝ፡ ደረጀ ደምሴ፡ ሱራፌል አማረና ታምራት ገዛኧኝ-እስከ ሰኔ 19 የሚቆይ የቡድን ትርዒት፤ በጉራምዓይኔ የሥነ-ጥበብ ማዕከል-በሠዓሊ ደረጀ ደምሴ-እስከ ሰኔ 30 የሚቆይ የግል ትርዒት፤ በጋለሪያ ቶሞካ-በሠዓሊ ተስፋ ሰለሞን-እስከ ነሐሴ 05 የሚቆይ የግል ትርዒት፤ በላፍቶ አርት ጋለሪ እስከ ሐምሌ 17 የሚቆይ የግል ትርዒት ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ ቦታዎቹን ለማታውቁ በ+251911702953 መረጃ ታገኛላችሁ፡፡ ታዲያ ይህ ጥቆማ ልብ የሚል ልብ ላለው! ብቻ ሳይሆን ለሥነ-ጥበብ ፋይዳ ቦታ የሌላቸውንና ነብሳቸውን እንዲያው በቅብዝብዝ ለሚያባዝኗት ሰዎች መረጃውን ለማቀበል ድልድይ ለመሆን ልብ ላለው ጎበዝ ሁሉ ይሁን! ወደ ዛሬው ዳሰሳ እንለፍ?
ሠዓሊ ዶ/ር ሙሉጌታ ታፈሰ ማነው?
ልከኛ ሰው ነው፡፡ ዶ/ር ሙሉጌታ ታፈሰ ጉምቱ ሠዓሊ ነው፤ የሥነ-ጥበብ ሃያሲና የሥነ-ጥበብ ቲዎረቲሽያን፡ ፈላስፋና ተመራማሪ ነው፡፡ በ1953 ዓ.ም አዲስ አበባ እስጢፋኖስ ቤ/ክ አካባቢ ተወለደ፡፡ በ1972 ዓ.ም በያኔ ስያሜው አዲስ አበባ ሥነ-ጥበብ ት/ቤት በአሁኑ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲው አለ የሥነ-ጥበብና ዲዛይን ት/ቤት ተመርቆ፣ በት/ቤቱ፣ ለቀጣይ ሁለት አመታት አስተምሯል፡፡ ቡልጋሪያ ሶፊያ ከተማ ከሚገኘው Higher Institute of Fine Arts (1983 ዓ.ም) እንዲሁም ቤልጅየም፡ አንትወርፕ ከተማ ከሚገኘው National Higher Institute for Fine Arts (1989 ዓ.ም) የማስተርስ ዲግሪዎቹን፣ በ(2004 ዓ.ም) ደግሞ ከስፔኑ La laguna University የፍልስፍና ዶክትሬት ዲግሪውን በከፍተኛ ማዕረግና ክብር ተቀብሏል። በውጪ ሃገራት ትምህርቱን ሲከታተልና ኑሮውን ሲመራ በቆየባቸው በእነዚህ ሰላሳ አመታት ውስጥ በተደጋጋሚ ወደ ሃገሩ እየተመላለሰ፣ ለአዲስ አበባችን የሥነ-ጥበብ እድገት የበኩሉን ለማበርከት ትምህርታዊ ገለጻዎችንና ውይይቶችን ሲያቀርብ ቆይቷል፡፡ ታዲያ በነዚህ ኃላፊነቶችና መሰጠቶች ታጅቦ፣ ሁሉ ለአፍታ ቸል የማይለው ጉዳይ ቢኖር የስቱዲዮ ሠዓሊነት ጥማቱና ይህን ለማሟላት ከቶም እማይቦዝነው ሙያዊ ስነ-ስርዓቱ ነው፡፡ ከ1987 ዓ.ም ጀምሮ ነዋሪነቱን የቤልጅየሟ አንትወርፕ ከተማ ያደረገው ሠዓሊ ሙሉጌታ ታፈሰ፤ ከአክሪሊክና ዘይት ቀለም እስከ ሕትመትና ድብልቅ ቁስ ጥበባት የሚጠቀምና ስራዎቹ በከፍተኛ ባለሙያዎች ተመዝነው ሚዛን በመድፋት በዓለም-አቀፍ ደረጃም ክብርና እውቅናን ያገኘ ሠዓሊ ነው፡፡ በሃገር ውስጥና በዓለም-አቀፍ መድረኮች አያሌ የቡድንና የግል ትርዒቶች ስራውን ያቀረበ ሲሆን በግለሰብና በሕዝባዊ፡ ሃገራዊና፡ የባሕል ተቋማት ስርም ስራዎቹ ተሰብስበው ይገኛሉ፡፡ በቤልጅየም የሚገኘው የWARP Contemporary Art Platform ዳይሬክተር የሆነውና የሥነ-ጥበብ አጋፋሪው ስቲፍ ቫን በሊንገን፤ ‘ከበርካታ ሰበዞችና ሁኔታዎች ሃሳብ እየመዘዘ እንካችሁ የሚል ዘላን አእምሮ ያለው ነው’ ሲል ይገልፀዋል፡፡
“ስራዎቹ ልዕለ-ዓለማዊ (universal) በመሆናቸው ሁላችንም ወደምናውቀው ግን ደግሞ ሌላ ወደ ሆነ ዓለም  እንድናተኩር በር ከፋች ናቸው፡፡ የማስመሰል ቅመሞች ሳይነሰነሱ፤ ስራዎቹ የሰው ልጅምን ሆነ የሌሎች ነገሮችን ወካይ ቅርፆችን በተለየ መንገድ እንድንመለከት ዳግም ይፈጥራቸዋል፡፡ ተፈጥሯዊነትን ባይከተልም፣ ሰራዎቹ ዋቢ የሚያደርጉት የሰው ልጅን ቅርፅ ነው፡፡ የሚፈጥራቸው ቅርፆች ድብቅ እምቢተኝነት እንዲያመላክቱ፣ ለተለምዷዊ የእውቀትና የመረዳት ልምዶች በእጄ እንዳይሉ በማድረግ ነው የሚያስቀምጣቸው፡፡ ድብቅ በሆነው የሥራዎቹ ህልውናዎች ውስጥም አንድ ልብ ብሎ የሚያስተውል ሰው፣ የተብላላ ሀሳብ እንደሚያገኘው ሁላ በሂደቶች መሐል ለሚስተዋሉ እውነቶች ከፍ ያለ ትኩረት ይሰጣል፡፡ የሚያስቀምጣቸው ጉልህ ምስሎች ወደ አንድ ራሱን ወደቻለና በእይታ ለምንዳስሰው ዓለም ትኩረት እንድንሰጥ የሚያደርጉ ናቸው፡፡ እያንዳንዱ ስራዎቹ ብጥስጣሽ ስሜትና ሀሳቦችን ሹክ የሚሉ ቢሆንም ተመላልሰን ስንመለከታቸው ግን አንደኛው ከሌላኛው ጋር የሚዛመድበትን የአንድነት ክር መምዘዝ ያስችለናል። በአጭር የሚቀርና አንድና አንድ ነገር ብቻ አመላክቶ የማለፍ የሥነ-ጥበብ ቀቢፃዊነትን በስራዎቹ አናይም፡፡ ይልቅስ፤ የሚያነሳት አንዷ ሀሳብ ሌላ፣ ሌላኛዋ ደግሞ ሌላኛውን እየነካችና እየቀሰቀሰች በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ በጋራ የምናጋራቸውን ሀሳቦች፣  ስሜቶችንና እውነቶችን ማእቀፍ ውስጥ የሚከቱ ስራዎችን ነው የሚሰራው” ይላል - በቢልገን፡፡
ከላይ የተገለፀውን ሀሳብ በዝርዝር ከማየታችን በፊት ከሰዓሊው መደንግግ የተወሰኑ ሃሳቦችን በአጭሩ እንመልከት፡
“የምሰራቸው ምስሎች የሚወለዱት ሊገለፅ ከማይቻለው የህይወት ትንቅንቅ ነው፡፡ አሻራቸውም በሞገዳዊ እንቅስቃሴአቸው ይገለፃል”
“ስራዎቼ ቅፅበታትን ይወክላሉ፡፡ የሰው ልጅ እንቅስቃሴዎች ላይ ትኩረት ያደርጋሉ”
“በመገለጥ ወይም በብርሃን የተሞላ አካባቢና ህይወት የመፍጠር ፍላጎት ሁሌም በውስጣችን ይኖራል፤ ስሜት የማይሰጥ ቢሆንም እንኳን ሥዕል መስራት አስፈላጊ ነው”
“ስራዬን ፎቶ ግራፍን በምናይበት አይን ስንመለከተው፣ የዕውነታን እቅጩን ሳይሆን ትንሽ ለወጥ አድርጌ ወይም የእቅጩነት ደረጃውን ቀንሼ እቀዳለሁ/አስመስላለሁ፡፡ እውነታዊነት ያቀፋቸው ሰፊ አማራጮች ረጋ ባለ ሆኔታ ያስፈነድቁኛል፡፡ እነሱኑ ነው በስራዎቼ ልዘግብ ወይም ልገልጥ የምሞክረው፡፡”
 እውነታዊነት፡-
በብዙኃን የሀገራችን የሥነ-ጥበብ አድናቂዎችና በጥራዝ ነጠቆች ጭምር Realism እና Realistic በተወዘጋገቡ መረዳቶች አሉ፡፡ በመሰረቱ Realistic ወይም እውነታዊ ማለት በእውነታ ያሉ ነገሮችንና በተፈጥሮ የሚገኙትን መድገም ወይም አስመስሎ መስራት ሲሆን የማስመሰሉ ደረጃ ወደ ውሸትና ማታለል ያዘነበለ፣ ‘እዚያ ሲደርሱ እዚያ ብሎ ነገር የሌለበት’ የሌለውን አለ በማለት የሚሰራ የአሳሳል ፍልስፍና ነው። Realism ወይም እውነታዊነት ደግሞ ከነባራዊው ዓለም ፣ ከእለት ተዕለት ኑሮ እና እውነታ በመነሳት የሚሳል፣ የሚፃፍና የሚመረመር ፍልስፍና ነው፡፡ እነዚህ ሁለት ተጓዳኝ ፍልስፍናዎች በኢትዮጵያ ሥነ-ጥበብና ዕድገቱ ላይ አሉታዊም ሆነ አወንታዊ ተፅዕኖ ያሳደሩ በመሆናቸው፣ ሌላኛው ሥነ-ጥበባችን ላይ ወለፈንዲ ተፅዕኖ ፈጣሪ ከሆነው ኢ-ምስላዊ ወይም አብስትራክት አርት ጋር በማያያዝ ሰፋ ያለ ሀተታ ለማቅረብ ጊዜና ሁኔታዎች እስኪፈቅዱ በይደር እናቆየውና ወደ እውነታዊነት እንመለስ፡፡
አዎ … እውነታዊነት የሰው ልጆችን የህይወት አቅጣጫ ለመቀየስ፣ ለማስመልከት፣ ለማስጤንና ለማስገንዘብ ሲሞክር የቆየ ፍልስፍና ነው፡፡ በተለይ በሥነ-ጥበቡ ዓለም፤ ለምንኖረው ሕይወት ጥራትና ደረጃ የበኩሉን ለማድረግ የሚታገል ትልቅ ፍልስፍናዊ መሰረት ያለው አሳሳል ነው፡፡ ሠዓሊ ዶ/ር ሙሉጌታ ታፈሰ፤ ለዘመናት ምናልባትም ሥነ-ጥበባዊ አቅጣጫውን በንቁ ንቃተ ህሊናው መግራት ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ እስካሁኑ ጊዜ ድረስ ለእውነታዊነት ሲያቀነቅን መኖሩ የፍልስፍናውን ጥልቀት ከመረዳት የመነጨ ይመስለኛል። ‘እኔ ሥነ-ጥበብን እንድከውን የሚያደርገኝ ኃይል፣ አካባቢዬ ላይ ያሉ ችግሮችን ለመፍታት ሥራዎቼ የበኩሌን ጥረት ለማድረግ የሚያስችሉኝ እንደሆኑ ስለማምንበት ነው’ የሚለው አስተያየቱ ‘እውነታዊነት ምሴ ነው’ ከማለት የተለየ አይመስለኝም፡፡ ሥዕል የሚሰራው ድንቅ ስሜቶችን ከመፍጠር ወይም ከWOW!!! የዘለለ ፋይዳ በሥነ-ጥበብ ማዕቀፍ ውስጥ የተቋጠረ ቃልኪዳን መኖሩን በመረዳቱ ለመሆኑና እውነታዊነት ለዚህ መረዳቱ አይነተኛ ቋንቋ እንደሆነው የሚያስረዱ አተያዮቹንና ሥራዎችን እንደ ምሳሌ እያነሳን እንቀጥል፡፡
የድምፅ ምናብ፡ የድምፅ ጎርፍ = ሰብዓዊነት  
በዚህ ትርዒት ከቀረቡት ሥራዎች መሀል ስምንቱ ድምፅ፣ ድምፃዊያንና ሙዚቃ ላይ ያተኩራሉ፡፡ ሠዓሊ ዶ/ር ሙሉጌታ ታፈሰ፤ እውነታዊነትን ለዚህ ትኩረቱ መግሪያ ካደረገበት አመክንዮ እንነሳ፡፡ የሰው ልጅ በዓለም ላይ ሲኖር መደሰት ይገባዋል ፡ ትንሿ መብቱም ነች፤ ደስታ። ጉልበታቸውን ለክፉ በማዋል ደስታን ነጣቂዎችም በዓለም ላይ ሞልተዋል፡፡፡ ኧረ እንደውም ዓለም እራሷ በእነዚህ ነጣቂዎች እየተነዳች ያለች ነው የምትመስለው። ሙዚቃ ደስታን ትቸራለች፡፡ ለተነጠቀብን ደስታም እንደ ሙዚቃ ያለ መፅናኛ የለም፡፡ ከተቀማ ደስታ የተወለደውን ብሉዝ  ማንሳት ይቻላል፡፡ አዎ… የብሉዝ ሙዚቃ የጥቁርነትና የነጭነት፤ በግፍ የመግዛትና በግፍ አልገዛም ባይነትና እምቢተኝነት ትንቅንቅ የተፈጠረ ነው፡፡ ይህ የመብት ጥያቄ የእውነታዊነት ፍልስፍና ከሚሞግተውና ከሚቆምለት እውነታ መሀከል አንዱ ነው፡፡ ሠዓሊ ዶ/ር ሙሉጌታ ታፈሰ ይህን ሙግት ወደ ሥዕል ያመጣው የጣፈጠና ከላይ ኩሬተር ወይም አጋፋሪ ስቲፍ እንዳለው፤ “የሚፈጥራቸው ቅርፆች ድብቅ እምቢተኝነትን እንዲያመለክቱ…” በማድረግ ነው። በትርዒቱ ውብ የሥዕሎች አሰቃቀል (Display) ግዘፍ እንዲነሱ ሆነው የተሰቀሉት አምስት ስዕሎችን ማንሳት ይቻላል፡፡ የብሉዝ የሙዚቃ ስልት ንጉስ ማይልስ ዴቪስን የሳለበትንና ከማይልስ ዴቪስ ስዕል በስተቀኝ የተሰቀሉት አነስተኛ መጠን ግን ደግሞ ልብ የሚደልቅ ግዝፈት ያላቸውን የሌሎች ጥቁር ሙዚቀኞችን ሥዕሎች ስንመለከት፣ ድብቅ እምቢተኝነትን የማመላከቻው ማጣቀሻ ይሆናሉ፡፡ አምስቱም ሙዚቀኞች በየበኩላቸው፤ በዘመናቸው ለተፈጠሩ አካባቢያዊና የአካባቢው የዘረኝነት ችግሮች ቀጥተኛ መፍትሔ ባይሆኑም መፅናኛ ብቻ ተደርገው ቢወሰዱ፤ የሙዚቃቸውን ዋጋ ሊያሳንስ የሚችሉ..... ከዚህ ሁሉ  አልፎ ተርፎም እስከዛሬ ድረስ እያዳመጥናቸው ለነፍሳችን ምግብ የሚሆኑ ሙዚቃዎችን ትተውልናል፡፡ ሙዚቃቸውም፣ ከሙዚቃቸው የሚወጣውና የሚያወጡት ድምፅ፣ በሙዚቃቸው ድርሳን የሚያቀነቅኑት ሀሳብ፣ በዜማቸው የሚቃኘው ተመስጦ ሁሉ የድምፅን ምናብ እንድናስብ የሚያስገድድ ኃይል አላቸው፡፡ እንደ ሠዓሊ ዶ/ር ሙሉጌታ ታፈሰ  አተያይ ድምፅ፤ ‘የስልጣኔ አንዱ የደም ስር ነው’ የደም ስርነቱና የመዘወርነቱ ኃይልና መነሻ ስልጣኔ ነው፡፡ ለምሳሌ ብሉዝን ብንወስድ የሰው ልጅ ስልጣኔ ካመጣው አንድ ጣጣ ማለትም አንዱ ሌላኛውን በመጨቆን፣ ለመክበር የሚደረገውን ጭቆና ከመቃወምና ከመቋቋም የተወለደ ሙዚቃ ነው፡፡ በዚህም ብሉዝ የተራማጁ ስልጣኔ የፈጠረው ነው ማለት ይቻላል። ድምፅ ሰውን ስሜታዊ ያደርጋል፡፡ የሰውን ሀሳብ ከመረዳት የሚመነጭና መልሶም ሰውን የመርዳት አቅም ያለው ነው፡፡ በተለይም በብሉዝ የሚፈጠረው ድምፅ ምናብን ይፈጥራል፡፡ ያልሸነፍ ባይነት  ምናብ በድምፅ ይፈጠራል። ይህ ሲጠራቀም ደግሞ የድምፅ ጎርፍ ፈጥሮ በጊዜው በተለመደውና ነጮች ጥቁሮችን ይጨቁኑበት ለነበረው የመረዳት ልምድ፣ እምቢ ባይነትን በማነሳሳት፣ጥቁሮች ለመብታቸው እንዲነሱ ረድቷል። ከዚህ አኳያ ሠዓሊ ዶ/ር ሙሉጌታ ታፈሰ፤ ይህንን የድምፅ ምናብ ፈጥረውና የድምፅ ጎርፍ ከስተው፣ በወቅቱ የነበረውን የጥቁር ሰው የህይወት አቅጣጫ ለመቀየስ፣ በሙዚቃቸው የበኩላቸውን ለሞከሩት ሙዚቀኞች ታላቅ ኃላፊነት በተሞላበት ሁኔታ ሰብዓዊ ክብር ሰጥቷል  ባይ ነኝ። የጥቁሮች መብት ታጋይ የነበረው ማልኮም ኤክስንም ከድምፅ ማጉያ ጋር አድርጎ፣ የጎላ የታጋይ ሰብዕናውን በሌላ ሥዕሉ ያሳየናል፡፡
የሰብዓዊነት መገለጫ፡ ሰዎች ለሰዎች መስጠት ካለባቸው ክብር ባሻገር የሰሩት ስራ አክብሮት ለሰው ልጆች ህይወት እሴት መጨመሩን ማስመልከትና አክብሮቱን የሚሰጥበትንም ፍልስፍናዊ መሰረት ጠንቅቆ ማወቅ ነው። ይህን በማድረግ ሰዓሊው የእውነታዊነት አሳሳልን ብቻ ሳይሆን ፍልስፍናውንም በጥልቀት የሚመረመር መሆኑን መረዳት እንችላለን፡፡ ይህ እንዴት ቢባል፣ አንድም ይሄን ሁሉ ላደረጉ ሙዚቀኞች ሊሰጥ የሚገባውን ክብር በማስታወሱ፣ በሌላ በኩልም ሥዕሎችን ከመሳል ባለፈ የእውነታዊነት ፍልስፍናን መሬት በረገጡ እሳቤያዊ መሰረት ማስደገፍ መቻሉ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ከሀገራችን ባሻገር በዓለም ላይ ላሉ ቁጥራቸው በጣም አነስተኛ ለሆኑ ብቁ ሰዓሊያን ብቻ የሚቻል የጥበብና የፍልስፍና አቋቋም በመሆኑ፣ ለሠዓሊ ዶ/ር ሙሉጌታ ታፈሰ ላቅ ያለ ክብር እንድንሰጠው ያስገድደናል፡፡  
ትንሽዬ ምርቃት፡     ምርቃቷ ራሷ ምርቃት የምትመስለዋን BH የተሰኘች ሁለት መዳፍ ተጋጥመው የማትሞላ ስራን ይመለከታል፡፡ ስራዋ በአንዷ ገፅ የተከፈተና ውስጧ በዘመናዊ የጆሮ ኩክ መጥረጊያ ጥጥ የተደፈነች ሳጥን ነች፡፡ በቅርበት በግልፅ ባይታይም ራቅ ስንል ግን የአድማጮችን ጆሮ የምትኮረኩረውና ከመንፈስ ዘልቃ የብሶት ኩክ ጠራርጋ የምታወጣዋ የብሉዝ አቀንቃኟ ቢሊ ሆሊደይን ምስል ያሳያል፡፡ በዚህ ስራ ሶስት ነገሮችን ልብ ይበሉ፡፡ ሙዚቃ፣ የጆሮ መጥረጊያ ኩክ፣ ከዚያ ስዕል፡፡ ለእኔ ይህ ሥዕል የConceptual Art ልከኛ አብነት ነው፡፡
መድብላዊነት (Pluralism)
የአንድ ሰው አፈጣጠርና አኗኗር ራሱን ሆኖ እንዲኖር “እጣ ፋንታ”ውን ወይም “አካሄድ”ን ያካትታል። እኛነታችን አንድም ከራሳችን ጋር አብሮ ይወለዳል፤ አንድም ከአካባቢያችንም ሆነ ከአኗኗራችን እኛነታችንን እናገኛለን፡፡ በአንድ እኛነታችን ብዙ መድብሎች ነን። ውስጣዊ ማንነታችን ከውጫዊ አለም እየተላተመ፣ በማያቋርጥ ሂደት እኛነታችንን እንገነባለን፡፡ እናፈርሳለን። በዚህ ትርዒት የቀረቡት የተወሰኑት ስራዎች እዚህ ሀሳብ ላይ ያተኩራሉ፡፡ አንድ ምስል ከሌላኛው ጋር የሚስተጋበርበት (Converse የሚያደርግበት )፣ ራሳችን ከራሳችን የምንሟገትበት መድብላዊነትን ከሰው ልጅ አፈጣጠርና ኑሮ አንፃር ያስቃኘናል፡፡ ውስጣዊውና የውጭ መስመርን (Inside Track) በዚህ ልብ ብለን ማየት እንችላለን፡፡
በስሜት የተሞሉ እንቅስቃሴዎች ወይም አኳኋኖች
አብዛኞቹ የሠዓሊ ዶ/ር ሙሉጌታ ታፈሰ ስራዎች፣ አንቅስቃሴ በተለይም በሰው ልጅ እንቅስቃሴ ላይ ያተኩራሉ፡፡ ሰዓሊው ከእንቅስቃሴ ባሻገር አኳኋኖችን እንዴት ለስሜትና ለሀሳብ ቅርብ አድርጎ እንደሚያስቀምጥ ከእውነታዊነት ጋር አያይዘን በአንድ ስራው ውስጥ እንመልከት፡፡ ይህ ስራ “የተንበረከከ” የሚሰኝ ሲሆን እጅግ ህመም በተሞላበት ስሜት መሸነፍን፣ እጅ መስጠትን የሚያሳይ ነው፡፡ የሰው ልጅ ህይወት ከአለፍ ባገደም በዝቅጠት የተሞላ ነው፡፡ በዘመንኛ አኗኗራችን ይህ እውነታ በአያሌው ይስተዋላል፡፡ ሆኖም ይህንን ዝቅጠታችንን በተለያዩ መንገዶች ለመሸፋፈን እየሞከርን፣ ቀጥ ብለን የቆምን እንደሆንን ሁሉ በEGO ወይም በእኔነት መንፈስ ተወጥረን እንገዳደራለን፡፡ ይሁን… መቼስ፤ ሰው ያለ EGO አይኖር፡፡ ሆኖም አኗኗራችን አደጋ ላይ ሲወድቅ፣ የስሜትና የሀሳብ ውዥንብር ሲከሰትብን እጅ እንድንሰጥ፣ እንድንሸነፍ ሲያስገድደን ምናለ በ’ጄ ብንል? በ’ጄ ማለትና መሸነፍ አንድም ትልቅነት አለያም መማርና ማነስ ሲሆን፤እንዲህ መሆን የሚችል ሰው ወደ ውስጡ የመስመጥ፣ ውስጡን የመመልከት አቅም ያለው እንደሆነም ልብ ይሏል፡፡ እውነታን መቀበልና መማር ለሌላ እድልና ትምህርት ዝግጁ መሆን የሚያስችል ጥበብ እንደሆነም መገንዘብ ይቻላል። ሠዓሊ ዶ/ር ሙሉጌታ ታፈሰ፤ እውነታዊነትን እየሰበከ እንደሆነ ለማሳያ ልዩ ቦታ ያላት ስራ ናት፡፡
ጭምብል-Mask
ሁለት ጭንብል ተኮር ስራዎች በዚህ ትርዒት ተካተዋል። ብላክ ማስክ እና ዋይት ማስክ የተሰኙ። ጭንብል ስሜትና ሀሳብን ለመግለፅም ሆነ ለመደበቅ ይውላል፡፡ ይህ በመላው ዓለም ያለ ታሪክ፣ ባህልና እውነት ነው፡፡ የጥቁርና የነጭ ጭንብሎች፣አያሌ የገሀዱ ዓለም ነፀብራቆችን ይወክላሉ፡፡ ነጮች ጥቁሮችን ለመበዝበዝ ጥቁር ጭንብል ለብሰዋል፡፡ እስካሁንም ይህንኑ ያደርጉታል፡፡ ጥቁሮችም ከነጮች ለመቃረም ነጭ ጭንብል በመልበስ ወስክ ወስክ ይላሉ፡፡ (ጥቁሮች ስል ኢትዮጵያውያንንም መሆኑን ልብ ይሏል)፡፡ ይህንኑ እውነት ፍርጥርጥ አድርጎ ነው ሠዓሊ ዶ/ር ሙሉጌታ ታፈሰ  በጭንብል ስራዎቹ የሚያስገነዝበን። ይመችህ!
ቅርበትና ርቀት-Perspective
የሠዓሊ ዶ/ር ሙሉጌታ ታፈሰ  ሥነ-ጥበባዊ ሰዋሰው ከሚያዘነብልባቸው አናስራት (elements) መሃከል ቅርበትና ርቀት አንዱ ነው፡፡ ሁሌም በነገሮች መሀል ነው የምንገኘው፡፡ ወደ እኛ የሚቀርቡም ሆነ ከኛ የሚርቁ ነገሮች መሃል ነው የምንኖረው፡፡ ታዲያ የቀረበውም ቅርብ፣ የራቀውም ሩቅ የሚሆነው እኛ ከቆምንበት አንፃር ስንለካው ነው፡፡ ቻይናዊው ሠዓሊ አይ ዌይ ዌይ፤ከቆመበት ሆኖ የመሃል ጣቱን ሲያሳየን፣ ጣቱ ግዙፍ ሆኖ በአንፃሩ ደግሞ ከርቀት የሚታየው የቤጂንግ ቤተ-መንግስትን አሳንሶ ያሳየናል፡፡ የአይ ዌይ ዌይን ስሳቅ ትተን ወደ ውስጣዊውና የውጭ መስመርን (Inside Track)  ስንመጣ፣ ከቅርበትና ርቀት አንፃር ስንመለከተው፣አሁንም ወደ እውነታ የሚቀርቡ እሳቤዎችን ነው የምናገኘው። የሰው ልጅ ቦታን ይፈጥራል፡፡ ከፈጠራቸውና ከሚኖርባቸው ቦታዎች ጋር ያለው ግንኙነት ከቦታዎቹ ጋር ያለውን ስሜታዊና ሀሳባዊ ተዛምዶም ጠቋሚ ነው። ሠዓሊ ዶ/ር ሙሉጌታ ታፈሰ፤  scenery ወይም ከባቢን በቅርበትና ርቀት ሲሰራ፣ በነፃነት የሚጨፍርና  የሚቦርቅ ነፃነቱን እንዲሁም የቅርቡን ይበልጥ እያቀረበና ሩቁንም እያራቀ፣ ስለ ቦታ ያለንን ስሜት፣ግንዛቤና ሃሳብ ጥልቅ ወደ ሆነ መረዳት ያሻግርልናል፡፡ ስለዚህ ትርዒት ብዙ ብዙ ማለት ይቻላል፡፡ እስከዚህም ላነበባችሁኝ ምስጋና ይገባችኋል፡፡ ምናልባት የመጨረሻ ነጥብ፡፡ እሱም የሠዓሊ ዶ/ር ሙሉጌታ ታፈሰን ጥበባዊ ጉዞ ጠያቂ ነው፡፡ ለመዳሰስ እንደሞከርኩት፤ሠዓሊ ዶ/ር ሙሉጌታ ታፈሰ ብዙ ሰው ነው፡፡ የአዕምሮውንም ዘላንነት እናያለን፡፡ ታዲያ ይህ ዘላን አእምሮው መቼ ነው ኢትዮጵያ ላይ የሚያርፈው? ኢትዮጵያን ፈፅሞ መተው የማይችለው ሠዓሊ ዶ/ር ሙሉጌታ ታፈሰ፤ ኑሮው ኢትዮጵያ ውስጥ ባለመሆኑ የሥራዎቹ ትኩረት ይበልጡን ዓለም አቀፋዊ ይዘትና ሰብዓዊነት ላይ እንዲሆን ያስገደደው ይመስላል። የኢትዮጵያ አፈር፣  የኢትዮጵያ  ሰማይ፣  የኢትዮጵያ ኑሮ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለ ህይወት በስራዎቹ በቂ ትኩረት አለማግኘታቸው ስለ ሠዓሊው ሳስብ የሚከነክነኝ ብቸኛው ጉዳይ ነው፡፡ ለነገሩ በብዙ አቅጣጫዎች ስንመለከተው፣ለእሱ አይነት የአኗኗር ዘይቤና ሰብዕና (በነገራችን ላይ በጣም ጭምትና ትሁት ሰብዕና ያለው ሰው ነው)ምቹ ያልሆነ ማህበረሰባዊ፣ ኢኮኖሚያዊ… ወዘተ ንቅዘት በሞላበትና የሥነ-ጥበባችን ማዕቀፍ ጤነኛ አካሄዶችን በማይከተልበት ሀገር መጥተህ ኑርና፣ ኢትዮጵያን የተመለከቱ ሥራዎች እየሰራህ ለሀገራችንም ቤዛ ሁን የሚል ሃሳብ ማንሳት ጭራሹንም የያዘውን ለማስጠፋት የሚደረግ ሙከራ ሊመስልብኝ ይችላል፡፡ ግን እንደው... ዝም ብሎ ቅር የሚል ነገር አለ አይደል? ለዚያ ነው ያነሳሁት፡፡ ስለ ሠዓሊ ዶ/ር ሙሉጌታ ታፈሰ በይበልጥ ለማወቅ www.mulugetatafesse.com’ን ይጎብኙ ፡፡ ቸር እንሰንብት!   

13 የአገሪቱ ታዋቂ ሳይንቲስቶች በአባልነቷ መቀጠሏን ደግፈዋል
የእንግሊዝን የአውሮፓ ህብረት አባልነት ቀጣይ ዕጣ ፋንታ የሚወስነው ህዝበ ውሳኔ በመጪው ሳምንት የሚካሄድ ሲሆን፣ ከአባልነቷ ትውጣ የሚለው አብላጫ ድምጽ የሚያገኝና ውሳኔው ተግባራዊ የሚደረግ ከሆነ፣ 800 ሺህ ያህል እንግሊዛውያን ከስራ ገበታቸው ሊፈናቀሉ እንደሚችሉ ተዘገበ፡፡
ሴንተር ፎር ኢኮኖሚክስ ኤንድ ቢዝነስ ሪሰርች የተባለው የአገሪቱ የጥናት ተቋም ያወጣውን የጥናት ውጤት ጠቅሶ ዘ ቴሌግራፍ እንደዘገበው፣ በአገሪቱ ህዝቦች ቀጣይ ዕጣ ፋንታ ላይ ትልቅ ተጽዕኖ የሚፈጥር ነው የተባለው ይህ ህዝበ ውሳኔ፣ እንግሊዝን ከህብረቱ አባልነት ውጭ ካደረገ፣ በተለያዩ የስራ መስኮች ላይ ተሰማርተው ህይወታቸውን ይመሩ የነበሩ 800 ሺህ ያህል ዜጎች ስራ አጥ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡
በአለማቀፍ ደረጃ ታዋቂ የሆኑ 13 እንግሊዛውያን ሳይንቲስቶችም፣ እንግሊዝ በህብረቱ አባልነቷ ትቀጥል የሚለውን የውሳኔ ሃሳብ እንደሚቀበሉት ለቴሌግራፍ ጋዜጣ በላኩት ይፋ የአቋም መግለጫ ደብዳቤ አስታውቀዋል፡፡
በቀጣዩ ህዝበ ውሳኔ ላይ በህብረቱ አባልነቷ ትቀጥል ብለው ድምጻቸውን እንደሚሰጡ ያስታወቁት ሳይንቲስቶቹ፣ አገሪቱ ከህብረቱ አባልነቷ መውጣቷ ሳይንሳዊ ምርምሮችንና ጥናቶችን የሚያደናቅፍ መሆኑን ገልጸው፣ ህብረቱ ተመራማሪዎችና ሳይንቲስቶች በትብብር እንዲሰሩ ዕድሎችን በመፍጠር ረገድ ላቅ ያለ ሚና ሲጫወት እንደቆየ አስታውሰዋል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አህያና አንድ ለማዳ ውሻ በአንድ ጌታ ቤት ይኖሩ ነበረ፡፡
አህያው ከጋጣ ውስጥ ብዙ አጃና ገብስ እንዲሁም ሳር ተደርጎለት እስኪጠግብ እየበላ ይተኛል፡፡ ትንሹ ቡችላ ውሻ ደግሞ ሳሎን ውስጥ ለእሱ በተዘጋጀለት ሶፋ ላይ ይቀመጣል፡፡ አንዳንዴ ደግሞ በጌታው ጭን ላይ ቂብ ይላል፡፡ ጌትዬው ምግብ የሚበላ ከሆነ ለውሻው ይቀነስና ይሰጠዋል፡፡ ወደ ውጪ ለራት የወጣ እንደሆነም በከረጢት ለውሻው ያመጣለታል፡፡ ውሻውም ጭራውን እየቆላ ይሮጥና ገና ከደጅ ይቀበለዋል፡፡
አህያው በጣም ብዙ ሥራ አለበት፡፡ ወፍጮ ቤት የሚፈጭ እህል ተሸክሞ ይሄዳል፡፡ ከተፈጨ በኋላም ተሸክሞ ይመለሳል፡፡ ወደ እርሻ ቦታም እየሄደ.፣ የተከመረ እህል በኩንታል እየተሞላ ይጫንበትና ወደ ቤት ይመጣል፡፡ ለአህያው፤ ሸክም የዕድሜ ልክ ሥራው ነው፡፡
አህያው በለማዳ ውሻው ምቾትና የቅንጦት ኑሮ በጣም ቅናት ገባውና፤
“እስከ መቼ ድረስ ነው፤ እኔ እዚህ ጋጣ ውስጥ ተቀርቅሬ የምኖረው? እስከ መቼሽ ነው እኔ እንደዚህ ውሻ ሳልንደላቀቅና ኑሮ ሳይደላኝ፣ አንድም ቀን ሳሎን ሳልገባ የምቀመጠው?” ሲል አሰበ፡፡
በመጨረሻም አንድ ቀን ተነስቶ፣ ጋጣውን ሰባብሮ ወጥቶ ወደ ጌታው ቤት አመራ፡፡ ጌትዬው እራት ሊበላ እንደተቀመጠ፣ አህያ ሆዬ ሳሎን ገባ፡፡ እንደ ውሻው ጭራውን እየቆላ፣ እንደ ውሻ “ው ው ው!” እያለ ይጮህ ጀመር፡፡ ይጎማለልና በማላገጥ መልክ ውሻው የሚያደርገውን በመኮረጅ፣ ለጌታው እንደ ቲያትር ያሳይ ገባ፡፡ ጠረጴዛውን በእርግጫ አለው፡፡ የጠረጴዛ ልብሱንም ገፈፈው፡፡ በዚህ ብቻ ባለመርካቱ፣ እንደ ውሻው ጌታው ጭን ላይ ለመቀመጥ ሁሉ ሞከረ፡፡ “የጌታዬ ጭን፤
ለውሻ ተፈቅዶ፣ እኔ ለምን እከለከላለሁ?” እያለ ጮኸ!
ይሄኔ አሽከሮቹ ጌታቸው አደጋ ላይ መሆኑን በመገንዘብ፣ በዱላ፣ በፍልጥና በጅራፍ ቀጥቅጠው ቀጥቅጠው፣ እንዳይሞት እንዳይድን አድርገው፣ አቁስለው፤ ወደ ጋጣው እየነዱ አስገቡት፡፡
አያ አህያ ቆሳስሎ፤ ተሰባብሮ፣ ጋጣው ውስጥ ተኝቶ እያቃሰተ፤
“አዬ! ምነው አርፌ ብቀመጥ? ምነው በተፈጥሮ የተሰጠኝን ማንነቴን አክብሩ ብኖር? በገዛ እጄ፣ ያለ ተፈጥሮዬ፣ ውሻን አክል፣ ውሻን እሆን ብዬ፣ ራሴ ላይ መዘዝ አመጣሁ!” አለ
*          *         *
ያልሆንነውን እንሁን ብለን የሌሎችን ህይወት ለመቀዳጀት መሞከር ቀቢፀ - ተስፋ ነው! ተፈጥሮአችን የማይፈቅደውን ነገር ለመሆን መዳከር ክፉ አባዜ ነው፡፡ በክህሎት የሌላውን ተፈጥሮ “ውስጤ ነው” ማለት ከንቱ ድካም ነው፡፡ ክህሎት ወይም ብቃት የራስን ትጋት የሚጠይቅ ቢሆንም ሰብዕናን፣ ሥነ ምግባርንና ተፈጥሮአዊ ማንነትን ማማከሉን መገንዘብ ያባት ነው፡፡ ማንም የማንንም ቦታ ለመተካት በቅንዓት፣ በምቀኝነትና “በምን - ይጎለኛል?” ሊያደርገው አይችልም፡፡
በሀገራችን ግን፤ ቅንዓትን ከመልካም አስተዳደር፣ ዕድልን ከጥሮ - ግሮ ማግኘት፣ እያምታታን ዘራፍ ማለት እየተለመደ መሆኑን ልብ እንበል፡፡ ሌላውን ቦታ ከመመኘት ይልቅ ኃላፊነትን መወጣት ነው ዋናው ጉዳይ! በውስጥና በውጪ ኦዲተር የሚመጣብንን ሪፖርት በተግባር ምን ይሁን? ምን እርምጃ እንውሰድ ማለት ተገቢ ነገር ነው! ችግሮቻችን ብዙ ናቸው፡፡ የማስተር ፕላን ጣጣ፡፡ ያላግባብ መሬት መያዝ፡፡ በተሰጠን ቦታ ላይ ግንባታ አለማካሄድ፣ ለባለስልጣናት የሚሰጠውን ጥቅማ ጥቅም “እኔ ታክስ ከፋይ ነኝ” (I am a tax - payer) ከሚለው ህዝባዊ አስተያየት ጋር አለማዋሃድ፡፡ ፍትሕ ተዛባ፣ ህጋዊነት ጠፋ … የሚልና ጩኸት የሚሰማ ጆሮ መጥፋት፡፡ የዲሞክራሲ በወገናዊነት እንደ አሸቦ ተሸብቦ መቅረት፡፡ የመልካም አስተዳደር ሽባ ሆኖ በከዘራ መሄድ፡፡ ምኑ ቅጡ፡፡ ዛሬ ደግሞ የኢትዮ - ኤርትራ ጦርነት ማገርሸት! የጎረቤት አገርን እብሪት ለመግታት በማቴሪያል፣ በሰው ኃይል፣ በፋይናንስ የምናወጣው ወጪ ጎጂነት የትየለሌ ነው፡፡ ሲሆን ሰላምን የማስፈን የሞራል ዋጋ በከፈልን ደግ ነበር፡፡ “ተመጣጣኝና አስተማሪ ቅጣት መስጠት” ካልንም፣ ትንኮሳው ከባላንጣችን መምጣቱን አመላካች ነውና ሁሉን በወጉ መያዝ ይጠበቅብናል፡፡ ዞሮ ዞሮ የሉዓላዊነት ጥያቄ ነው!
አንድ አዛውንት ከዓመታት በፊት፣ በመጀመሪያው ኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት፤ የትግራይ ሰው ሆነው በኤርትራዊ ድምፃዊ ዘፈን ሲደንሱ ታዩ፡፡
“እንዴት ጦርነቱ ሊጀመር አንድ ሃሙስ ሲቀረው፣ በኤርትራዊ ዘፋኝ እስክስታ ይወርዳሉ?” ቢባሉ፤
“አይምሰላችሁ፡፡ እዚህ ድንበር ላይ የጀርመን ግንብ እንኳ ቢገነባ፣ የሙዚቃ ካሴት መቀባበያ ትንሽ መስኮት ትኖራለች” አሉ ይባላል፡፡
የሁለቱ ህዝቦች ባህላዊ ትሥሥር ምንጊዜም ይኖራል ማለታቸው ነው፡፡ ይህን ዕውነታ ማንም አይክደውም፡፡ የጎረቤት አገር አምባገነን መሪ ምንም አቋም ይውሰድ ምንም፣ “ወረራ ውስጤ ነው፡፡ ማስወረርም ውስጤ ነው!” ቢልም እንኳን፤ የሁለቱ አገር ህዝቦችን ትሥሥር መናቁ ነውና፣ አስተሳሰቡ በማናቸውም መንገድ መሻር አለበት፡፡ ስለሆነም፤ “ከርከሮ አንዲት ፀጉር አለችው፡፡ እሷኑ ለማጥፋት ይተሻሻል” የሚለው ተረት የእሱ ይሆናል!

Saturday, 18 June 2016 12:47

የዘላለም ጥግ

ስለ ጦርነት
• ሁለቱ እጅግ ኃያል ጦረኞች፡- ትዕግስትና ጊዜ
ናቸው፡፡
ሊዮ ቶልስቶይ
• ከአንድ ጠላት ጋር በተደጋጋሚ መዋጋት
የለብህም፤ አለበለዚያ የውጊያ ጥበብህን
በሙሉ ታስተምረዋለህ፡፡
ናፖሊዮን ቦናፓርቴ
• በጦርነት የሚገደሉት በህይወት ያሉት ብቻ
አይደሉም፡፡
አይሳክ አሲሞቭ
• ጦርነት የውድመት ሳይንስ ነው፡፡
ጆን አቦት
• ሽማግሌዎቹ ጦርነት ያውጃሉ፡፡ የሚዋጉትና
የሚሞቱት ግን ወጣቶቹ ናቸው፡፡
ኸርበርት ሁቨር
• ጦርነትን የሚጀምሩት ወታደሮች አይደሉም፤
ፖለቲከኞች ናቸው፡፡
ዊሊያም ዌስትሞርላንድ
• ጦርነትን ካላጠፋን፣ ጦርነት ያጠፋናል፡፡
ኤች.ጂ.ዌልስ
• ጦርነት ሌቦችን ይፈጥራል፤ ሰላም
ትሰቅላቸዋለች፡፡
ጆርጅ ኸርበት
• ጦርነት ለሰው ልጅ ሽንፈት ነው፡፡
ዳግማዊ ፓፕጆን ፖል
• ጦርነትን መከላከያው እርግጠኛ መንገድ
አለመፍራት ነው፡፡
ጆን ራንዶልፍ
• ግን መቼ ነው መሪዎቻችን የሚማሩት -
መልሱ ጦርነት አይደለም፡፡
ሔለን ቶማስ
• ከሌሎች ጋር በጦርነት ውስጥ ያሉ ሰዎች
ከራሳቸው ጋር ሰላም አይደሉም፡፡
ዊሊያም ሃዝሊታ

    በአቶ ሐይሉ ገ/ሕይወትና በሼል ኢትዮጵያ ወይም ኦይል ሊቢያ መካከል ስለነበረው ሁኔታ አቶ አብዱልመሊክ ሁሴን በተባሉ ሰው ወይም ስም የተፃፈውን አቤቱታ ተመልክተነዋል፡፡ የአቶ አብዱልመሊክ ሁሴን አቤቱታ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ “በግልፅ ደብዳቤ” የተፃፈ ሲሆን ዋናው ዓላማው አቶ ሐይሉ ገ/ሕይወት በሼል ኢትዮጵያ ወይም ኦይል ሊቢያ “የተነጠቁትን ቦታ” ማስመለስ ነው፡፡ አቶ አብዱልመሊክ፤የአቶ ሐይሉ የሕግ አማካሪ ወይም ጠበቃ ወይም ጋዜጠኛ ይሁኑ በግልፅ ባናውቅም ከእነዚህ ውስጥ አንዱን ቢሆኑ እንኳን ማንሳት የሚገባቸውን ቁልፍ ጥያቄ ሳያነሱ አገር ምድሩን ወንጅለዋል፡፡ ለነገሩ ቁልፉ ጥያቄ ከተነሳ አቤቱታው አያስፈልግም ወይም እዚያው መልስ ያገኛል፡፡ ስለዚህ አማራጭ ሆኖ ያገኙት ዙሪያውን መወንጀል ነውና ይህንኑ አድርገዋል፡፡
ለመሆኑ አቶ ሐይሉ ተወሰደባቸው የተባለው ቦታ የተጠቃሚነት መብት ቀድሞ የነበረው ማነው? ሼል ኢትዮጵያ ለዓመታት ሲገለገልበት በነበረው ቦታ ላይ የሼልን መሠረተ - ልማት ተጠቅመው ነዳጅ ማከፋፈል ጠይቀውና ተፈቅዶላቸው የመጡ ሰው ናቸው፡፡ በአጭር አገላለፅ አቶ ሐይሉ የነዳጅ ወኪል ለመሆን ጠይቀው በተፈቀደላቸው መሠረት ነው ከሼልም ከቦታውም ጋር ግንኙነት የፈጠሩት፡፡ ከዚያ ቀድሞ ለዓመታት ሼል ኢትዮጵያ በቦታው ላይ ማደያ ገንብቶ ሲሰራ ነበር፡፡ አሁንም ሼል ኢትዮጵያን የገዛው ኦይል ሊቢያ እየሰራ ይገኛል፡፡ ይህን ጥሬ ሀቅ ደብቀው ነው አቶ አብዱልመሊክ ያለ ይሉኝታና ያለ ሀፍረት የስንቱን ስም ያጠፉትና የወነጀሉት፡፡ የሕግ ተጠያቂነቱ እንዳለ ሆኖ፣ ሌሎች ተጨማሪ ሀቆችን ለግልፅነት እናንሳ፡፡
የዚህ የማደያ ቦታ ባለቤት አቶ አሰፋ መንገሻ ይባላሉ፡፡ በንጉሱ ዘመን መሬት የግል ሃብት የነበረበት ጊዜ ስለሆነ ሼል ኢትዮጵያ ከአቶ አሰፋ መንገሻ ባዶ መሬት በመከራየትና ማደያ በመገንባት ስራውን ማካሄድ ጀመረ፡፡ በመካከል ደርግ ወደ ስልጣን መጣ፡፡ እናም የከተማ ቦታና ትርፍ ቤትን የመንግስት ያደረገውን አዋጅ ቁጥር 47/1967 አወጀ፡፡ መሬቱንም ወረሰ፡፡
የነዳጅ ማደያ ስራን ያለ ቦታ ማከናወን ስለማይቻል፣ ይህንኑ በመረዳት ነዳጅ ማደያዎችን ብቻ የተመለከተው መመሪያ በደርግ መንግስት አማካይነት ወጣ፡፡ በዚሁ መሠረት ሼል ኢትዮጵያ በቦታው ላይ የመስራት ህጋዊ መብት እንደማንኛውም የውጭ ኩባንያ አገኘ፡፡ እናም ስራውን ቀጠለ፡፡ አቶ ሐይሉ ወደ ሼል የመጡት ከዚህ በኋላ ነው፡፡ እንደ ማንኛውም ደምበኛ በማደያው ነዳጅ የማከፋፈሉን ስራ ከሼል ጠይቀው፣ በ1971 ዓ.ም ከተፈቀደላቸው በኋላ የሽያጭ ወኪልነት ውላቸው እየታደሰ ንግድ ፈቃድ አውጥተው በወኪልነት ሲሰሩ፣ማደያውን በህገ ወጥ መንገድ የተቆጣጠሩ መስሏቸው፣ በገዛ ፍቃዳቸውን ውሉን በ2001 ዓ.ም እስኪያቋርጡ ድረስ ሰርተዋል፡፡ በእነዚህ አመታት እንደ ሌሎቹ ማናቸውም የቆዩ ወኪሎች ኩባንያውን ወክለው ከሦስተኛ ወገን ጋር ግንኙነት ያደርጉ ነበር፡፡ በዚህ አጋጣሚ ነው እንግዲህ አቶ ሐይሉ የቦታው ሕጋዊ ባለቤት ነኝ በማለት ስውር ደባ የጀመሩት፡፡ ዝርዝሩን እዚህ መግለፅ የማንፈልገውን የተለያየ መንገድ በመሄድ፣የቦታው ባለቤትነትን ለማረጋገጥ ጥረት አድርገዋል፡፡ ሁሉም ግን ሕገወጥ ነው፡፡ በዚህ አጋጣሚ አቶ ሐይሉ ከወረዳ አስፈፃሚዎችና ፈፃሚዎች ጋር በመመሳጠር፣ ኩባንያው ሳያውቅ ውዝፍ ግብር በፍርድ ቤት ተገደው እንዲከፍሉ የተደረገበትን ድራማ ሌላ ጊዜ በስፋት ማቅረብ የምንችል መሆኑን ለአንባብያን እንገልፃለን፡፡
ሊቢያ ኦይል ኢትዮጵያ ሊሚትድ፤ ይህ ድርጊት ህገወጥ እንደሆነና ከድርጊታቸውም ተቆጥበው ከኩባንያው ጋር እንደ ከዚህ በፊቱ በሰላም እንዲሰሩ በተደጋጋሚ ቢጠይቅም፣ ይባስ በለው ኩባንያው መሳሪያዎቹን በአጭር ጊዜ ውስጥ ካላነሳ፣ተጠያቂ እንደማይሆኑ ማስጠንቀቂያ ላኩ፡፡ ይህን ጊዜ ነው እንግዲህ ኩባንያው ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት ለመውሰድ የተገደደው፡፡
ቀደም ሲል እንደተገለፀው፣ከአቶ አሰፋ መንገሻ በደርግ ከተወረሰ በኋላ ቦታው የመንግስት ነው፡፡ ሼል ኢትዮጵያ ድሮም የእሱ አልነበረም፡፡ ቀጥሎም የእሱ አልነበረም፡፡ መሬት፣ የመንግስት ነውና፡፡ የመገልገል መብቱ ግን ያኔም የተረጋገጠ ነው፡፡ አሁንም በእጁ ያለ ነው፡፡ አቶ ሐይሉ በውክልና ከተጠጉ በኋላ ስር ለስር በሰሩት ስራ አጽመ-ርስታቸው ሊያደርጉት አሰቡ፡፡ አልተሳካም፣ ሊሳካም አይችልም፡፡ ሕግና ስርዓት ያለበት ሀገር ነው፡፡ ይህ ጉዳይ የቀረበላቸው ፍርድ ቤቶች (በሁሉም ደረጃ የሚገኙት) የአቶ ሐይሉን ጥያቄ ውድቅ በማድረግ የኦይል ሊቢያን የተገልጋይነት ባለመብትነት በፍርዳቸው አረጋግጠዋል፡፡ ሰበር ሰሚ ችሎትም ውሳኔዎቹ የሕግ ስህተት እንደሌለባቸው አረጋግጧል፡፡
እውነታው ይህ ሆኖ ሳለ አቶ አብዱልመሊክ፤ጥቂት ማጣራት ሳያደርጉ ሌላ ሕገወጥ ተግባራትን ፈጽመዋል፡፡ አቶ አብዱመሊክ፤ ለስግብግብና ሕገወጥ ፍላጐት መሟላት ሲሉና ምንም ሳያፍሩ በኢትዮጵያ የተሰማሩ የውጭ ሀገር ኢንቨስተሮች ሁሉ በወንጀል ተግባር ላይ ተሰማርተዋል የሚል የክስ ማዳበሪያ ይዘወ ቀርበዋል፡፡ ሀገሪቱ እጆቿን ዘርግታ የጋበዘቻቸውን የውጭ ኢንቨስተሮች፤ ሽፍታና ወራሪ አድርገው ለማቅረብ ሞክረዋል፡፡ የሀገሪቱ ፍርድ ቤቶች ሁሉ በማይመለከታቸው ጉዳይ ጣልቃ እየገቡ፣ስራ አላሰራ ብለዋል ለማለትም በቁ፡፡ በሚያሳፍር ሁኔታ የሊቢያ ሕዝብ ተባብሮ ያስወገዳቸውን አምባገነኑን መሀመድ ጋዳፊን ዋቢ በማድረግ ኦይል ሊቢያን በጋዳፊ ስም እስከ መወንጀልም ደርሰዋል፡፡ የሚገርመው ነገር አቶ አብዱልመሊክ ስለ ምርመራ ጋዜጠኝነትም አንስተዋል፡፡
መርምሮ ደባቂ ነው ወይስ መርምሮ አጋላጭ ነው? እንዴትስ ነው አንድ መርማሪ ጋዜጠኛ ኦይል ሊቢያ፣ የሊቢያ ኩባንያ ስለሆነና ሊቢያን ያስተዳድሩ የነበሩት ጋዳፊ ስለነበሩ፣ ሼልን መግዛቱ አግባብ አይደለም ብሎ የሚነሳው? እውነቱን ለመናገር ለጋዳፊ የሚቀርበው የትኛው አስተሳሰብና ተግባር ነው?
አቶ አብዱልመሊክ ስለ ኪራይ ሰብሳቢነትም አንስተዋል፡፡ ትክክለኛው ኪራይ ሰብሳቢነት የተፈፀመበትን ጉዳይ ደብቀው፣ ሌሎችን ለመወንጀል ሲጣጣሩ፣ የኪራይ ሰብሳቢዎች የዘመኑ ፋሽን መሆኑን በሚገባ አረጋግጠውልናል፡፡ የማይመለከታቸውን፣ የእርሳቸው ያልሆነውን ቦታ በአቋራጭ ለመንጠቅና ለመክበር ከተደረገው የአቶ ሐይሉ እንቅስቃሴ በላይ ምን ኪራይ ሰብሳቢነት አለ? ከአባት ያልወረሱትን፣ ከሌላ ሰው ያልገዙትን፣ በስጦታ ያላገኙትን የመንግስት ቦታ፤ሼልን ተጠግተው በውክልነት ሲገለገሉ፣ የከፈሉትን ግብር ብቻ መነሻ አድርገው ቦታውን ጠቅልዬ ልውሰድ የሚሉትን ሰው አቤቱታና ክስ፣ በየደረጃው ውድቅ ያደረጉት የሀገሪቱ ፍርድ ቤቶች ሁሉ፣ በአቶ አብዱልመሊክ ኪራይ ሰብሳቢ ተብለዋል፡፡
ስለዚህ እንዲህ ያለውን ሁኔታ ፀሐፊው፤ ሼል ኩባንያ በአስተዳደር በኩል መሄድ ሲያቅተው ፍርድ ቤትን አቋራጭ መንገድ አድርጐ የፈለገውን ማስፈፀም እንደቻለ ማቅረቡ የፍርድ ቤቶችን ክብር፣ ህልውና፣ ሥራ እጅጉን ይነካል፡፡ ፍርድ ቤቶች በማንም የሚመሩ፣ የማንንም ጉዳይ አስፈፃሚ ናቸው ማለቱ ነው? ስለሆነም ፍትህ በኢትዮጵያ የለም እያለ ነው? ደግሞስ የወረዳና የክፍለ ከተማ አስፈፃሚዎች ውሣኔ፣ የመጨረሻ ውሳኔ ይሁን እያለ ነው?
ጋዜጣውስ ምን እያደረገ ነው? ያስተናገደው ፅሁፍ ነፃ አስተያየት ነው? የመርማሪ ጋዜጠኛ ሪፖርት ነው? የጠበቃ አቤቱታ ነው? ምንድነው? ሦስተኛ ወገንን በቀጥታ የሚወነጅል ሀሰተኛ መረጃ ሲቀርብ ማጣራት የለበትም? ፍሬ ጉዳዩ፣ ሂደቱ፣ ውሳኔው በማይታወቅ መደምደሚያ፡-
የውጭ ሀገር ኩባንያዎች ሀገር እያጠፉ፣ የዜጐችን መሬት እየቀሙ ነው፤
ፍርድ ቤቶች በማያገባቸው ጉዳይ እየገቡ፣ የዜጐችን ባለመብትነትና መንግስትን ስራ እያወኩ ነው
ሼል ኢትዮጵያ አለማቀፍ አጭበርባሪ ነው፣
ኦይል ሊቢያ ከጋዳፊ ሀገር ስለመጣ፣ሼልን እንዲገዛ ሊፈቀድለት አይገባም ነበር----
የመሳሰሉ አሳፋሪና ሕገወጥ ማጠቃለያዎች፣እንዴት ጉዳይ ሆነው በጋዜጣው ላይ ወጡ? ኦይል ሊቢያ ሕግና ስርዓት ባለበት ሀገር እየሰራ ይገኛል፡፡ ሕግና ስርአትንም አክብሮ ይሰራል፡፡ መብቱንም እንደዚሁ በሕግና ስርአት ያስከብራል፡፡

• ልብ አንጠልጣይ ታሪክንና ትልልቅ ሃሳቦችን ያስታረቀች ደራሲ
• ለዘመናችን ቀውሶች ሁነኛ መፍትሔዎችን አቅርባለች

“እስቲ በአንድ ሺ ኮፒ አትመን እንሞክረው” ተብሎ የተጀመረው የሃሪ ፖተር ታሪክ፣ በህትመትና በሽያጭ ብዛት... አቻ ያልተገኘለት ዝነኛ ታሪክ ሆኗል፡፡ ግማሽ ቢሊዮን ኮፒ ሊደርስ ምን ቀረው! “ለማንኛውም፣ የቀን ስራ ብታፈላልጊ ይሻላል” የተባለችው ደራሲ፤ በአለም የመጀመሪያዋ ቢሊዬነር ደራሲ ሆናለች - ጄኬ ሮውሊን።
በድርሰቶቿ ውስጥም፣ የ“ተዓምረኛ ሰዎችን” ታሪክ ነው የምታስነብበን። እምቅ የተፈጥሮ አቅማቸውን ካዳበሩ፣ ትንግርተኛ ብቃት ሊቀዳጁ የሚችሉ፣ የአስር ዓመት ልጆች... ናቸው ዋናዎቹ ባለታሪኮች። በምናብ በማሰብ ብቻ አገር ምድሩን የሚያንቀጠቅጡ ፣ ጥቂት ቃላትን በማነብነብ አዳራሹን በጣፋጭ ምግብ የሚሞሉ፣ ስንዝር የምታክል ብትር በማወዛወዝ ብቻ መብረቅ የሚያወርዱና እንደ ንስር የሚበርሩ፣ ብርጭቆ እግር አውጥቶ እንዲራመድ ነፍስ የሚዘሩ፣  ቅጠል ስራስር፣ ጨውና ምናምን አዋህደው በአንድ ጠብታ በሽታን የሚፈውሱ ወይም አገርን የሚያቃጥሉ... እንዲህ አይነት ብቃት፣ በእርግጥም ትንግርት ነው፡፡ ግን ምሳሌያዊ ትርጉሙንም ስንመለከትስ?
አለምን የሚቀይሩ ትልልቆቹ የለውጥ ማዕበሎች፣ ከጥቂት ሰዎች ምናብ ውስጥ የተፈለፈሉ የተሳሳቱ አስተሳሰቦች ወይም ከጥቂት ብሩህ አእምሮዎች የፈለቁ ትክክለኛ አስተሳሰቦች ናቸው፡፡ በመፃሕፍት ውስጥ የሰፈሩ፣ በንግግር የሚደመጡ ቃላት፣…እውቀትን ወይም ጭፍንነትን በማስፋፋት አለምን የሚያስደንቅ አዲስ ታሪክ ይፈጥራሉ - ለክፉም በደግም፡፡
መቶ ሺ ኩንታል ጭነት፣ ውቅያኖሶችንና በረሃዎችን አቋርጦ የሚጓዘው… በመርከብና በባቡር ሹፌሮች ጥቂት የእጅ እንቅስቃሴ አማካኝነት ነው፡፡ ጣታችንን ሞባይል ላይ በማንሸራተት ስንት ተዓምር መስራት እንችል የለ? እንዲያውም፣ ስንለምዳቸው፣ ተራ ነገር ይመስሉናል እንጂ፣ የሰው ልጅ፣ አጀብ የሚያሰኙ ብቃቶች አሉት፡፡ እነዚህን ብቃቶች ነው በሀሪ ፖተር ታሪኮች ውስጥ በምሳሌያዊ አገላለጽ የምናገኛቸው፡፡
ግን፣ በዋዛ አይደለም፣ እንዲህ አይነት ብቃት ላይ የሚደረሰው። አእምሮን ተጠቅሞ መማር፣ ማጥናት፣ መመርመርና ማወቅ ያስፈልጋል። ሳይታክቱ መሞከር፣ መለማመድ፣ መስራት....
ግን፣ ይህ ብቻውን በቂ አይደለም። በእርግጥ፣ ከአላዋቂነትና ከጭፍንነት ይልቅ፣ አስተዋይነትንና ለመቀዳጀት መትጋት፣ አዋቂነትን... ከስንፍናና ከገልቱነት ይልቅ... ችሎታንና ሙያን ለማዳበር መጣጣር፣ አንድ ቁም ነገር ነው። ነገር ግን፣ በእውቀቱና በችሎታው አማካኝነት፣ ዋጋ ያለው ጠቃሚ ነገር ለመስራትና ስኬት ላይ ለመድረስ የማይጣጣር ከሆነ፣ ከንቱ ሆኖ ይቀራል። ጭራሽ፣ ለመጥፎ አላማም ሊያውለው ይችላል - ሰዎችን ለማታለል፣  የስራ ውጤታቸውን ለመዝረፍ፣ ህይወታቸውን ለማጥፋት ወዘተ፡፡ በስኬት መንገድ መጓዝ፣  አልያም ስኬትን በሰበብ አስባቡ እያጣጣሉ በከንቱ መንዘላዘል፣ ወይም በዝርፊያ ጉራንጉር ውስጥ መደናበር... የእያንዳንዱ ሰው ምርጫ ነው።
ግን፣ እያንዳንዱ ምርጫ... ከእለት እለት ሲደጋገም፣ የየራሱ ውጤትና መዘዝ አለው፡፡ በዚህም የእያንዳንዱ ሰው ‘ማንነት’ ይቀረፃል፣ ይሸረሸራል ወይም ይጣመማል። እንደየምርጫው፣ ከቀን ወደ ቀን፣… እየጠነከረ፣ እየተልፈሰፈሰ ወይም እየደደረ የሚሄድ የተለያየ ‘ሰብእና’ ይፈጠራል።
በአንድ በኩል፤ በራሱ ብቃትና ማንነት የሚተማመን፣ መልካምና ቀና ሰብእና ይኖራል፡፡ ይሄ ሰዎችን በተግባራቸውና በባሕርያቸው የሚመዝን ፍትህን የሚወድ ስብዕና ነው - ጥሩ ሰዎችን የሚያደንቅ የፍቅር ሰብዕና
በሌላ በኩል፤ በአቅመ ቢስነት  የሚንከላወሱ፣ የሰው ፊት እያየ ወዲህና ወዲያ የሚወዛወዝ ደካማና አስመሳይ ሰብእና ይኖራል፡፡ ይሄ፣ ሰዎችን የሚመዝንበት አንዳች ሚዛን የለውም፡፡ ከመንጋው አቧራ ጋር፣ ከአውራው ጩኸት ጋር፣ ከሰፈሩ ሆይሆይታ ጋር አብሮ የሚነፍስ ገለባ ነው። ጭፍን ቲፎዞ ስለሆነ፤ በዘር ሲያቧድኑት ይቧደናል፤ በሃይማኖት ሲያቧድኑትም እንደዚሁ። ይሄ አስቀያሚ ርካሽ ሰብዕና ነው።
ሌላ ደግሞ አለ - በጥላቻና በምቀኝነት ስሜት የሚንቀሳቀስ፣ ሰዎችን በማሰቃየትና በመግዛት እርካታ ለማግኘት የሚመኝ ጠማማ እኩይ ሰብእና። በአጥፊ የጭካኔ ተግባሩ፣ በእኩይ የምቀኝነት ባሕሪው...ምክንያት ውግዘት አይደርስበትም? ሊደርስበት ይችላል፡፡ ነገር ግን ማምለጫና ማመካኛ መንገዶችን ይጠቀማል፡፡ ደግሞም መንገድ አያጣም። እያንዳንዱ ሰው፣ እንደየ ተግባሩና እንደየ ባሕሪው እንዳይመዘን ማድረግ ነው - ዘዴው፡፡ ማለትም፣... ሰዎችን በዘር ማቧደን፣ በሃይማኖት ማቧደን፣ በሃብት ልዩነት ማቧደን ...!
የእኩልነት ማመካኛ ዘዴዎችን…እናውቃቸዋለን?
ሰዎችን በጅምላ ማቧደን ከቻለ፣ በቃ፣ የቱንም ያህል ጥፋት ቢፈፅም፣ የቱንም ያህል እኩይ ቢሆን፣ “ወገናችን” ብለው በጭፍን የሚቀበሉት ሰዎችን አዘጋጀ ማለት ነው። ቀን ከሌት አሉቧልታ የሚያናፍስ፣ ፕሮፖጋንዳ የሚነዛ፣ ዝባዝንኬ የሚያወራ ውሸታም ቢሆንም እንኳ፤ አጨብጫቢ እንደማያጣ ያውቃል፡፡ ንብረት ቢዘርፍ ወይም ቢያቃጥል፣ ሰውን ቢያሰቃይ ወይም ቢገድል... አያስጨንቀውም። ማመካኛ አዘጋጅቷል - “ለአገር አስቤ፣ ለብሔረሰብ ተቆርቁሬ፣ ለሕዝብ ወግኜ፣ ለሃይማኖት ብዬ ያደረግኩት ነው” ይላል። እንደ ወንጀለኛ ሳይሆን፣ እንደ ጀግና እንዲታይ ይጠብቃል።
የሚቃወመው ሰው ከመጣ፣ መፍትሄው ቀላል ነው፤ “የውጭ ሃይሎች ተላላኪ፣ የአገር ጠላት፣ የባዕዳን ቅጥረኛ፣ ባንዳ፣ ሰርጎ ገብ፣ ከሃዲ....” ተብሎ እንዲፈረጅ ማድረግ ይቻላል። የማይደግፉትን ሰዎች እንዲህ እያንበረከክ፣ ከነጥፋቱና ከነእኩይነቱ፣ እንዳሻው ይፈነጫል።
በእርግጥ፣ በፅናት ከተጋፈጥነው፣ እርቃኑ ተጋልጦ፣ በሽንፈት ሊፈጠፈጥ ይችላል። ነገር ግን፣ እኩይነት አንዴ ስለተከሰከሰ፣ እስከ ዘላለሙ ተሸነፈ ማለት አይደለም። ለጊዜው ይሸነፋል እንጂ፣ ጨርሶ አይሞትም። የሃሪ ፖተር ዋና ጠላት የሆነው ቮልድሞት የተሰኘው የፅልመት ጌታ፣ እንዲህ አይነት እኩይ ገፀ ባህርይ ነው። ምንም ቢሸነፍ፣ ጠፍቶ የማይጠፋ እኩይነት!
እንዴት ብትሉ፤ ..አዎ፣ አንድ እኩይ ተግባር ሊከሽፍ ይችላል፡፡ ነገር ግን ..እነዚያ የእኩይነት ምንጮች፣... እነዚያ የጭፍንነት፣ የጥፋትና የክፋት አስተሳሰቦች ሁሌም ይኖራሉ። ለጊዜው ተቀባይነታቸው ሊከስም ይችላል፡፡ የጠፋም ይመስላሉ፡፡ ግን አይጠፉም። በአንድ ሰው ጭንቅላት ውስጥ ተጣብቀው፣ የጭንቅላቱ ጓሮ ውስጥ ስር ሰደደው ቀስ በቀስ ነፍስ ለመዝራት ሲፍጨረጨሩ ልናገኛቸው እንችላለን፡፡ (እንዲህ አይነት ሃሳቦችን ተዓማኒ በሆነ መንገድ ወደ መሳጭ ታሪክ መቀየር ከባድ ነው፡፡ ጄኬ ሮውራን ግን በሚገርም ጥበብ ምርጥ ድርሰት ሰርታበታለች፡፡
የሃሪ ፖተር የመጀመሪያ የሞት ሽረት ትግል ከዚህ ጋር ይመሳሰላል - Harry Potter and the Philosopher’s Stone)።
የእኩይነት አስተሳሰብ፣ ለጊዜው ባይሳካለት እንኳ፣ ከአንዴም ሁለቴ ቢሸነፍም እንኳ፣ አይሞትም። እዚህኛው ወይም እዚያኛው መፅሃፍ ውስጥ አድፍጦ ይቀመጣል፡፡ ይሄ አይገርምም፡፡ በጭፍን የማመን አክራሪነትን፣ ሳያመርቱ ንብረት የመውረስ ሶሻሊዝምን፣ የጅምላ ጥላቻ ዘረኝነትን የሚሰብኩ መፃህፍት፣ ሁሌም ይኖራሉ። በእነዚህ መፃህፍት የሚመረዙ፣ የሚማረኩና የሚሰክሩ ሰዎችም ያጋጥማሉ። እናም፣ እኩይነት እንደገና ነፍስ ዘርቶ፣ ለመንገስ ጊዜ አይፈጅበትም።
መፃህፍት ውስጥ የተሰገሰጉ እኩይ አስተሳሰቦች፣ ፊት ለፊት ተጋፍጠን በትክክለኛ አስተሳሰብ አፍረጥርጠን ካላመከንናቸው፣ ብዙም ሳይቆይ፣ አገር ምድሩን የሚያናውጥ፣ በጭፍን ሁላችንንም የሚሰለቅጥ ግዙፍ አውሬ ይሆኑብናል፡፡ ይሄ በሃሪ ፖተር ሁለተኛው ታሪክ ውስጥ፣ ዋና ማጠንጠኛ ሃሳብ ነው (Harry Potter and the Chamber of Secrets የተሰኘው ሁለተኛው የሃሪ ፖተር ታሪክን ይመልከቱ።)
እኩይነት ድብቅ ሴራ ወይስ የአደባባይ ድግስ?
እኩይነት፣.. ከአንድ ሰው ጭንቅላት ላይ ተጣብቆ ወይም አንድ መፅሃፍ ውስጥ መሽጎ... ቀስ በቀስ ነፍስ ዘርቶ ሊነግስብን ይችላል ሲባል፣… “በቀላሉ የማይታይ ስውር ሴራ” ይመስላል። ግን ስውር ሴራ አይደለም። ይልቅስ፣ እኩይነት፣ በግላጭ የሚዘጋጅ ድግስ ነው።
ባለፉት መቶ አመታት፣ ዛሬም ድረስ ብዙ ቀውስንና እልቂትን እያስከተሉ የሚገኙ አመፆችን፣ ግጭቶችንና አምባገነን አገዛዞችን ተመልከቱ። ሁለተኛውን የአለም ጦርነት የለኮሱ ሦስቱ መንግስታት (የጀርመን፣ የጣሊያንና የጃፓን መንግስታት)፣ በየአገሮቻቸው የገነኑት፣ በስውር ሴራ አይደለም። “ከራስህ በፊት አገርህን አስቀድም፣ ከራስህ በፊት ብሄርህን አስቀድም” በሚል የአደባባይ መፈክር ነው፣ በአምባገነንነት ለመግዛት የቻሉት።
ብዙ ስቃይ የፈፀሙት። ከዚያም፣ ሌሎች አገራት ላይ በመዝመት፣ ከ60 ሚሊዮን በላይ ሰዎችን ለእልቂት ዳርገዋል። በዩጎዝላቪያና በሩዋንዳ ብቻ ሳይሆን፣ አሁን ድረስ በበርካታ አገራት፣ “ከራስህ በፊት ብሔር፣ ብሔረሰብን አስቀድም... በብሔረሰብ፣ በጎሳ ተቧደን”... በሚል መፈክር ብዙ እልቂት ደርሷል።
ይህም ብቻ አይደለም። “ከራስህ በፊት፣ ሌሎች ሰዎችን አስቀድም... ከራስህ በፊት፣ ሰፊውን ህዝብ አስቀድም” የሚሉ ኮሙኒስቶችና ሶሻሊስቶች፣ አለምን በደም አጥበዋል። ከመቶ ሚሊዮን በላይ ሰዎችን ጨርሰዋል።
“ከራስህ በፊት፣ የሃይማኖት ሰባኪውን አስቀድም፤... ከራስህ በፊት፣ የሃይማኖት ትዕዛዛትን አስቀድም” የሚሉ አክራሪዎችም እንዲሁ ከጥንት እስከ ዛሬ፣ ብዙ ጥፋት አድርሰዋል።
የግል አእምሮን በማጣጣል ጭፍን እምነትን እያወደሱ የሚሰብኩን የግል ንብረትን በማጣጣል፣ መስዋዕት መሆንን እያደነቁ የሚደሰኩሩብን.... የግል ማንነትን በማጣጣል በጅምላ ፍረጃ መቧደንን እያራገቡ ዘረኝነት የሚለፍፉብንኮ በአደባባይ ነው። እነዚህ የእኩይነት አስተሳሰቦች፣ ስውር ሴራዎች አይደሉም - በአደባባይ የተሰበኩ፣ የተደሰኮሩ፣ የተለፈፉ አስተሳሰቦች ናቸው - በግላጭ የቀረቡ ድግሶች።
ቅዱስ የሆኑት፣ የግል አእምሮ፣ የግል ንብረትና የግል ማንነት ደግሞ፤ እንደ መጥፎ ነገር ተቆጥረው ተንቋሽሸዋል - በአደባባይ። እኩይነት በእንዲህ አይነት “መፈንቅለ ሃሳብ” አማካኝነት እንደገና ነፍስ ዘርቶ ይነግስብናል -  ትክክለኛው እንደ ስህተት፣ ጠቃሚው እንደ ጎጂ፣ ቅዱሱ እንደ እኩይ ተቆጥሮ እንዲወገዝ፣ እንዲወነጀል፣ እንዲፈረድበት በማድረግ! ... (Harry Potter and the Prisoner of Azkaban በተሰኘው ሦስተኛው የሃሪ ፖተር ታሪክ ውስጥ፣ ይህንን ቁም ነገር አጉልቶ የሚያሳይ ተመሳሳይ ማጠንጠኛ ጭብጥ እናገኛለን)።
ምን ይሄ ብቻ!
የመደናበርና የድንዛዜ ዥዋዥዌ
“ኧረ እንንቃ፡፡ እኩይነት ነፍስ ዘርቶ እየመጣብን ነው!” ብለው እነ ሃሪ ፖተር፣ አዳሜን ለማስጠንቀቅ ሲሞክሩ፣ ብዙም ሰሚ  አያገኙም፡፡ አዎ፣ አብዛኛው ሰው፣ እኩይነት እንዳይነግስ ይፈራል፡፡ ግን በጥንቃቄ አስቦ፣ እኩነትን ለመመከት አይጣጣርም፡፡
ከዚያ ይልቅ ፍርሃትን እያግለበለበ፣ (እንደ ዶናልድ ትራም፣ ጭፍን ስሜትንና ዘረኝነት እየቆሰቆሰ) በአዳሜ ዘንድ ተቀባይነት ለማግኘትና ስልጣን ለመያዝ የሚፍጨረጨር የሚደናበር ይበራከታል፡፡ በተቃራኒው ደግሞ፣ “የውሾን ስም ያነሳ…” እንደሚባለው፤ “እኩይነት ነፍስ እየዘራ ነው፤ ቮልድሞት እየመጣብን ነው” ብሎ በግልጽ አደጋው እንዲገለጽ የማይፈልጉ የድንዛዜ ሰዎች ብዙ ናቸው፡፡
ቮልድሞት የሚለውን ስም የሚተነፍስ ሰው መኖር የለበት ይላሉ፡፡ “አጅሬው”፣ “ስም አይጠሬ”፣ “ያ የምናውቀው”…በማለት ያድበሰብሱታል (እንደ ሂላሪ እና እንደ ኦባማ ማለት ነው፡፡ የሃይማኖት አክራሪነት አደገኛ መሆኑን በግልጽ ለመናገር አይፈልጉም አይደል?)
ምን ለማለት ፈልጌ ነው? የጄ.ኬ ሮውሊን ድርሰቶች፣ እጅግ መሳጭና ልብ አንጠልጣይ የመሆናቸው ያህል፣ በዚያው ልክ ከላይ በጠቀስኳቸው አይነት... በርካታ ጥልቅ ሃሳቦችና ጭብጦችም የበለፀጉ ድርሰቶች ናቸው።

“የኢሳያስን መንግስት ማስወገድ ያስፈልጋል”
የቀድሞ የአየር ሃይል አዛዥ ሜ.ጀ አበበ

የኢትዮጵያ መንግስት
• በከባድ ውጊያ፣ ከፍተኛ ኪሳራ አድርሻለሁ
• ትንኮሳ እንዳይፈጽም ትምህርት ሰጥተነዋል
• ካለረፈ ግን፣ በተመጣጣኝ እርምጃ እንቀጣዋለን
የኤርትራ መንግስት
• ሁለት መቶ ወታደሮችን ገድያለሁ፤ አቁስያለሁ
• የአሜሪካ መንግስት ፣ እጁ አለበት፤ ጥቃት አነሳስቶብኛል
• የኢትዮጵያ ጦር ወደ ድንበር በብዛት ተሰማርቶብኛል

የኢትዮጵያ መንግስት በፆረና ግንባር ከባድ ውጊያ ተካሂዶ እንደነበር ገልፆ፣ ትንኮሳ በፈፀመው የኤርትራ ጦር ላይ ከፍተኛ የህይወት ኪሳራ አድርሻለሁ፤ እርምጃውም ለሻዕቢያ መንግስት አስተማሪ ነው ብሏል፡፡ የኤርትራ መንግስት በበኩሉ ባልታወቀ ምክንያት የኢትዮጵያ ጦር በብዛት ወደ ድንበር እንደተሰማራና የአሜሪካ እጅ እንዳለበት የተናገረ ሲሆን፤ 200 ወታደሮችን ገድያለሁ ብሏል፡፡
በኤርትራ መንግስት ላይ አስተማሪ እርምጃ መስደናል ያሉት የኢትዮጵያ መንግስት የኮሚኒኬሽን ሚኒስትር ጌታቸው ረዳ፤ “ሌላ ትንኮሳ ያደርጋል ብለን አንጠብቅም፤፡፡  በድንበር አካባቢ ሌላ ግጭት የሚፈጠር ከሆነ ግን፣ የግጭቱ ብቸኛ ተጠያቂ የሚሆነው የኤርትራ መንግስት ነው” ብለዋል፡፡
መንግስት፣ ትንኮሳዎችን ለማስታገስና ለመቅጣት ተመጣጣኝ እርምጃ መውሰዱን ይቀጥላል ያሉት አቶ ጌታቸው፤ የኢያሳያስን መንግስት የማውረድ ኃላፊነት ግን ኢትዮጵያን ብቻ ሳይሆን የአለማቀፉ ህብረተሰብም የሚመለከት ቢሆንም፣ በዋናነት የኤርትራ ህዝብ ጉዳይ ነው ብለዋል -  ሚኒስትሩ ገልፀዋል፡፡
“ተመጣጣኝ እርምጃ” የሚባለው ሃሳብ እንደማያዛልቅ የተናገሩት የቀድሞ የአየር ኃይል አዛሽ ሜ/ጀነራል አበበ ተ/ሃይማኖት በበኩላቸው፤ ተመጣጣኝ እርምጃ ማለት እነሱ 200 ከገደሉ፣ እኛ 1000 በመግደል እንቀጣቸዋለን በሚል ስሌት እንደመመራት ስለሆነ አያዋጣም ብለዋል፡፡ የኢሳያስ አፈወርቂ መንግስት ሙሉ ለሙሉ መወገድ አለበት ያሉት ሜ/ጀ አበበ፣ ተመጣጣኝ እርምጃ የሚባለው ሃሳብ ትርፉ እልቂት ነው ብለዋል፡፡
የአፍሪካ ህብረት፣ የተባበሩት መንግስታት እና የአሜሪካ መንግስት፣ የድንበር ግጭቱ እንዳሳሰባቸው በመጥቀስ፤ ኢትዮጵያና ኤርትራ ከግጭት እንዲታቀቡ መክረዋል፡፡
የኤርትራ መንግስት በኢንፎርሜሽን ሚኒስቴሩ ባወጣው መግለጫ፣ ባልታወቀ ምክንያት ጥቃት እንደተፈፀመበት ጠቅሶ፣ ከ200 በላይ የኢትዮጵያ ወታደሮችን ገድያለሁ፣ 300 አቁስያለሁ ብሏል፡፡
ሃላፊነት በጎደለው ድርጊት ደም መፋሰስ እንዲከሰት የተደረገበት ምክንያት አናውቅም ያለው ይሄው መግለጫ፤ የአሜሪካ መንግስትንና አለም አቀፍ ተቋማትን ኮንኗል፡፡
ከጥቃቱ በፊትና በኋላ፣ የኢትዮጵያ መንግስትን እየደገፉ ነው በማለት፡፡ እነዚህ አካላት እውነታውን በመካድ ወራሪውንና ተወራሪውን እኩል ለማውገዝ ሞክረዋል ሲልም ገልጧል፡፡
በድንበር አካባቢ የኢትዮጵያ ጦር በብዛት ተሰማርቶብኛል፤ በዚህ ውስጥም የአሜሪካ መንግስት እጅ አለበት ብሏል - ትናንት የወጣው መግለጫ፡፡  
የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ንኮሳንዛና ድላሚኒ ዙማ፣ በኢትዮጵያ እና በኤርትራ መካከል የተፈጠረው የድንበር ግጭት እንደሚያሳስባቸው ገልጸው፣ ሁለቱም አገራት ከግጭት እንዲርቁ መክረዋል፡፡ ችግሩን ከሚያባብሱ ድርጊቶችና መግለጫዎች እንዲቆጠቡም ጠይቀዋል፡፡
የተመድ ዋና ጸሃፊ ባንኪ ሙን፣ ባለፈው ረቡዕ ባስተላለፉት መልዕክት፣ ሁለቱም አገራት ችግሩን ከማባባስ እንዲቆጠቡ ጥሪ ያቀረቡ ሲሆን፣ አገራቱ ልዩነታቸውን በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱና ከ15 ዓመታት በፊት እ.ኤአ. በ2000 የተፈረመውን የሰላም ስምምነት በተሟላ መልኩ ተግባራዊ ለማድረግ እንዲሰሩ ጠይቀዋል፡፡

“ቃና” 8 ስቱዲዮዎች ገንብቷል

በአጭር ጊዜ ውስጥ ከፍተኛ ተቀባይነትን ያገኘው “የቃና ቴሌቪዥን” ሥርጭትን ተከትሎ ሲኒማ ቤቶችና ቲያትር ቤቶች በተመልካች ድርቅ መመታታቸውን የኪነጥበብ ባለሙያዎች ለአዲስ አድማስ ተናገሩ፡፡ ባለፉት ሦስት ወራት የፊልምና ቲያትር ተመልካቾች ከግማሽ በላይ መቀነሳቸው ባለሙያዎቹን እንዳስደነገጣቸው ገልፀዋል፡፡
የቲያትር አዘጋጆችና ባለቤቶች እንደተናገሩት፤ በሣምንቱ የእረፍት ቀናት ከሚታዩ ቲያትሮች በስተቀር በስራ ቀናት ምሽት ላይ የሚቀርቡ ቲያትሮች ተመልካች አጥተዋል፡፡
በማዘጋጃ ቤት “እንግዳ” እንዲሁም በብሔራዊ ቲያትር “የፍቅር ማዕበል” የተሰኙ ቲያትሮችን የሚያሳየው አርቲስት ማንያዘዋል እንደሻው፤ ባለፉት ሶስት ወራት የቲያትር ተመልካቾች ከ30 በመቶ በላይ መቀነሳቸውን ገልጿል፡፡ ቀደም ሲል በማዘጋጀ ቤት እየታየ ያለውን ቲያትር እስከ 300 ሰዎች ይመለከቱት እንደነበረ የጠቆመው አርቲስቱ፤ በአሁን ወቅት የተመልካቹ ቁጥር በመቶ እንደቀነሰ ተናግሯል፡፡ “ቃና” ቴሌቪዥን ከመጣ ወዲህ የተመልካቹ ቁጥሩ መቀነሱ የጣቢያው ተፅዕኖ የፈጠረው ነው ብሎ እንደሚያምን የገለፀው ማንያዘዋል፤ በዚህ ሁኔታ የሚቀጥል ከሆነ ቲያትር ቤቶች ባዶአቸውን ሊቀሩ ይችላሉ ብሏል፡፡
ስሙ እንዲገለጽ ያልፈለገ ሌላ የቲያትር ባለሙያ በበኩሉ፤ የተመልካች ቁጥሩ መቀነሱ ኢንዱስትሪውን በእጅጉ እየጐዳው በመምጣቱ፣ በቲያትር ስራ የመቀጠል እምብዛም ፍላጐት የለኝም ብሏል፡፡ የቲያትር ባለቤቶችም ለከፍተኛ ኪሣራ እየተዳረጉ እንደሆነ ወዳጆቹ  እንደነገሩት ጠቁሟል፡፡
የ“ታምሩ ሲኒማ ቤት” ባለቤት አርቲስት ታምሩ ብርሃኑም፤ ባለፉት ሶስት ወራት የተመልካች ቁጥር በግማሽ መቀነሱን ይናገራል፡፡ ችግሩ የተፈጠረው “ቃና” ቴሌቪዥን ከመጣ በኋላ በመሆኑ ጣቢያው የፈጠረው ተፅዕኖ ሊሆን እንደሚችል አርቲስቱ ግምቱን ተናግሯል፡፡ “እንደ ቢዝነስ ሊጐዳኝ ቢችልም እንደ ሙያተኛ በቃና ደስተኛ ነኝ” ይላል፡፡ የተመልካች ቁጥር በትክክል የቀነሰበትን ምክንያት ለማወቅ ግን ጥናት ማድረግ ያስፈልጋል ባይ ነው፤ አርቲስት ታምሩ፡፡
የሴባስቶፖል ሲኒማ ባለቤትና የፊልም ባለሙያው አርቲስት ቴዎድሮስ ተሾመ፤ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ የተመልካች ቁጥር መቀነሱን ባይክድም የ “ቃና” ተፅዕኖ ነው በሚለው ግን አይስማማም፡፡ “ከዚያ ይልቅ በየቦታው በርካታ የግል ሲኒማ ቤቶች መከፈታቸው ተመልካቹ እንዲበታተን አድርጐታል” ብሎ እንደሚያምን ቴዎድሮስ ገልጿል፡፡
የቫይን ሲኒማ ስራ አስኪያጅ አቶ ብርሃኑ ገዛኸኝ (ብሩስ) በበኩላቸው፤ የተመልካች ቁጥሩ ከሚገመተው በላይ መቀነሱን ይናገራሉ፡፡ “ለምን ተመልካች አይመጣም?” የሚል መጠነኛ ጥናት ለመስራት መሞከራቸውን የጠቆሙት አቶ ብርሃኑ፤ አብዛኛው ተመልካች የማይመጣው ጥሩ ፊልሞች ስለማይቀርቡ እንደሆነ አረጋግጫለሁ ይላል፡፡ በ “ቃና” ቴሌቪዥን ምክንያት ከሲኒማ ቤት የቀሩም አሉ - ጥቂት ናቸው እንጂ፤ ብለዋል አቶ ብርሃኑ፡፡
የፊልም ዳይሬክተሩ ቢኒያም ወርቁ በሰጠው አስተያየት፤ ለተመልካች ቁጥር መቀነስ ዋነኛው ምክንያት “ቃና” ቴሌቪዥን ነው ብሎ እንደሚያምን የተገለፀ ሲሆን፤ ትክክለኛውን ምክንያት ለማወቅ ግን በማህበራቸው በኩል ጥናት ለማድረግ እየተሞከረ መሆኑን ጠቁሟል፡፡
በሌላ በኩል “ቃና” ቴሌቪዥን ተርጉሞ ከሚያቀርባቸው ፊልሞች በተጨማሪ ራሱ ለሚሰራቸው አገር በቀል ፊልሞችና አዳዲስ ፕሮግራሞች 8 ስቱዲዮዎች ተገንብተው መጠናቀቃቸውን የጣቢያው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ሃይሉ ተ/ሃይማኖት ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡ ስርጭት በጀመረ በ3 ወር ጊዜ ውስጥም የጣቢያውን ፌስ ቡክ ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ተመልካቾች እየተከታተሉት እንደሆነ ተናግረዋል፡፡