Administrator

Administrator

   የቅንጦት ኑሮ የሚገፋው ተዋናዩ፣ የወር ወጪው 2 ሚ. ዶላር ነው
     “ፓይሬትስ ኦፍ ዚ ካረቢያን” በሚለው ድንቅ ፊልም የሚታወቀው ዝነኛው የፊልም ተዋናይ ጆኒ ዲፕ፣ ለመጠጥ በወር 30 ሺህ ዶላር እንደሚያወጣና በተለያዩ የቅንጦት ነገሮች በየወሩ በድምሩ በአማካይ 2 ሚሊዮን ዶላር እንደሚረጭ የዘገበው ቢቢሲ፤ ይህ ያልተገባ አባካኝነቱ ለከፋ የገንዘብ ቀውስ እየዳረገው እንደሚገኝ መነገሩንም ገልጧል፡፡
የጆኒ ዲፕ የቢዝነስ ማናጀሮች፣ግለሰቡ እንዳሻው በሚበትነው የገንዘብ አወጣጡ ሳቢያ ለከፋ ቀውስ እየተዳረገ እንደሚገኝ ማስታወቃቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ 14 ያህል እጅግ ውድ የመኖሪያ ቤቶችንና 12 የውድ ንብረቶች ማከማቻ ቤቶችን ለመግዛት ብቻ ከ75 ሚሊዮን ዶላር በላይ ወጪ ማድረጉን መግለጻቸውን አስረድቷል፡፡
የተዋናዩ የቢዝነስ ማኔጅመንት ቡድን አባላት ይህንን መረጃ ይፋ ያደረጉት፣ ግለሰቡ ተገቢውን ግብር በወቅቱ ባለመክፈል ለከፍተኛ የገንዘብ ቅጣት ዳርገውኛል፤ በወጉ አላስተዳደሩልኝም በሚል በአባላቱ ላይ የ25 ሚሊዮን ዶላር ክስ መመስረቱን ተከትሎ እንደሆነም ዘገባው ገልጧል፡፡  
የቡድኑ አባላት በበኩላቸው፤ የጆኒ ዲፕ ዝርክርክነትና ገንዘብ አባካኝነት ራሱን ለቀውስ እየዳረገው እንደሚገኝ በመግለጽ፣ በወር 30 ሺህ ዶላር በማውጣት ከውጭ አገራት ገዝቶ ያስገባቸውን የወይን መጠጦችና ለግል አውሮፕላኑ ያወጣውን 200 ሺህ ዶላር ጨምሮ ያለአግባብ ያወጣቸውን ወጪዎች ዘርዝረው ይፋ አድርገዋል፡፡

  ብራንድ ፋይናንስ የተባለው አለማቀፍ ተቋም ባለፈው ረቡዕ ይፋ ባደረገው የ2016 እጅግ ከፍተኛ ዋጋ ያላቸው የዓለማችን ታዋቂ የንግድ ምልክቶች ዝርዝር ውስጥ ጎግል በቀዳሚነት ተቀምጧል፡፡
ተቋሙ በ500 የዓለማችን ታዋቂ የንግድ ምልክቶች ዙሪያ የሰራውን ጥናት ጠቅሶ ዘ ኢንዲፔንደንት እንደዘገበው፣ ታዋቂው የቴክኖሎጂ ኩባንያ ጎግል ባለፈው የፈረንጆች አመት 2016 የገበያ ዋጋውን በ24 በመቶ በማሳደግ፣ 109.5 ቢሊዮን ዶላር በማድረስ ቀዳሚነቱን ይዟል፡፡ ጎግል በተጠናቀቀው የፈረንጆች አመት 2016 የአለማችን እጅግ ውድ ያለው የንግድ ምልክት ሊሆን የበቃው፣ በአመቱ ያስመዘገበው የማስታወቂያ ገቢ በማደጉ ምክንያት ነው ያለው ዘገባው፤ የኩባንያው የማስታወቂያ ገቢ በዓመቱ የ20 በመቶ እድገት ማሳየቱንም አስታውቋል፡፡
ለአምስት ተከታታይ አመታት የአለማችን ቁጥር አንድ ውድ የንግድ ምልክት ሆኖ የዘለቀው አፕል በበኩሉ፣ በ2015 የነበረው 145.9 ቢሊዮን ዶላር የገበያ ዋጋ በአመቱ የ27 በመቶ ቅናሽ አሳይቶ ወደ 107.1 ቢሊዮን ዶላር ዝቅ በማለቱ ወደ ሁለተኛ ደረጃ የወረደ ሲሆን፣ ታዋቂው አማዞን በ106.4 ሚሊዮን ዶላር ሶስተኛ ደረጃን መያዙ ተነግሯል፡፡ ኤቲ ኤንድ ቲ በ87 ሚሊዮን ዶላር አራተኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ፣ ታዋቂው ማይክሮሶፍት ኩባንያ በ76.3 ሚሊዮን
ዶላር አምስተኛ ደረጃ መያዙን ዘገባው ገልጧል፡፡

Sunday, 05 February 2017 00:00

ማራኪ አንቀፅ

  ብሔርተኝነት፣ ፅንሰ ሐሳቡና መዘዙ

     ብሔርተኝነት ከብሔር ጋር ተጣምሮና ተያይዞ የሚፍታታ አይዲዮሎጂ፣ ስሜትና በሁለቱ ላይ ተመርኩዞ የብሔሩን ዓላማ ለማሳካት የሚደረግ እንቅስቃሴ ብቻ አይደለም፡፡ ከዚያ በላይ ደርዝና ጥልቀት ያለው ፅንሰ ሐሳብ ነው፡፡ በቅድሚያ ብሔር የተሰኘውን ግንዛቤ ፍቺና ለፈረንጂኛው አቻ ትርጉም ማግኘቱ ነው ለብዙዎቹ የሚቀለው፡፡ የኢትዮጵያ የተማሪዎች እንቅስቃሴ የጆዜፍ እስታሊንን ስመ ጥር ፍቺ ዋና ማጠንጠኛ በማድረግ የተከተለውም ይህንን አቅጣጫ ነው፡፡ እሱም ቀደም ሲል የተጠቀሰውን ብሔር ማለት በታሪክ ሂደት በጋራ ቋንቋ፣ መሬት፣ ኢኮኖሚያዊ ህይወትና በጋራ ባህል (ካልቸር) በሚገለጽ/ በሚንጸባረቅ ስነ ልቦናዊ ቅኝት (Make Up) ላይ የተመሰረተ የተረጋጋ ሕዝብ ነው የሚለው ነው፡፡ በፍቺው ውስጥ ስለተቀመጠው እያንዳንዱ ቃል ብዙ፣ ብዙ ማለት ይቻላል፣ ተብሏልም፡፡ ይህንን ትርጉም እስታሊን አቶ ባወር (1881-1938) ከተባለው የኦስትሪያ የትዮሪ አፍታችና ፖለቲከኛ የተዋሰው ነው የሚሉ አሉ፡፡ ወደ እዚያ አንገባም፡፡
ፅንሰ ሀሳቡን ከበርካታ የእይታ ማዕዘናት ሲመለከቱት፣ ልክ እንደ ማንነት አስቸጋሪ ንባብ ቃል ነው፡፡ በርካታ መጽሐፍትና ድርሳናት እንደሚያመለክቱት፤ በዚያ የታሪክ መጋጠሚያ ላይ ብሔሩ ወይም ስብስብ ማጠንጠኛ አድርጎ አፅንኦት በመስጠት የራሱን ጥቅልል መንግስት ወይም መንግስት አከል አሃድ ለመመስረት ይገባኛል ጥያቄ አስነስቶ፣ የራሴ ወገን የሚላቸውን መቀስቀስ መቻሉ ላይ ነው የቁም ነገሩ እንብርትና አንደርዳሪው ግፊት። ይህ ስሜት፣ አይዲዮሎጂና እንቅስቃሴ ነው በአንድ ላይ ብሄርተኝነት የሚሰኘው፡፡ ዓላማውን ከግቡ ለማድረስ ብሔርተኝነት ከላይ ያመለከትናቸውን የጋርነቶች ሁሉ መቀስቀሻ ሊያደርግ ይችላል፤ ተራ በተራ ወይም ሁሉንም በአንድ ላይ፡፡
ኤትኔሲቲ ማኅበራዊ አደረጃጀት ነው ከተባለ ደግሞ፣ እሱም በተራው ከብሔርተኝነት ጋር ያለውን ተዛምዶና ተያያዥነት መመልከቱ ተገቢ ይሆናል። ልክ እንደ ብሔርተኝነት ኤትኒሲቲም አንድ ዓላማ ግብ ለማስመታት እስከ ተደረጀ ድረስ በሦስቱም የጋራነቶች ቀስቃሽነት በዓላማው ላይ ያነጣጠረ አካሄድ ይከተላል፡፡ ለዓላማው ግብ መምቻ ሌሎች የጋራነቶችንና አላባዎችንም ለመጠቀም ይሞካክራል። ለቅስቀሳውና ለውዝግብ የሚቀርቡት የመፍትሔ ሀሳቦች ግን የተለያዩ መሆናቸው አይቀርም፡፡ ዛሬ በኢትዮጵያ የዘር ፖለቲካ የተሰኘው መስተጋብር ከአጠቃቀሙ አኳያ ሲታይ ይበልጥ ኤትኒሲቲን የሚገልጽ ይመስላል፡፡
ብሔርተኝነትን እንደማንነት ማደራጃ፤ እንደ ስሜት እንደ እንቅስቃሴና እንደ አይዲዮሎጂ ጠልቀን ለመተንተንና ለማፍታታት መሞከሩ የሚያዛልቅ አይሆንም፡፡ ስብስቦችን የሚያፋጥጣቸውና የሚያጋጥማቸው የጋራነትን መመርኮዣ አድርገው በአንድ ርእሰ ጉዳይ ላይ ሳይስማሙ ሲቀሩ (ሲወዛገቡ) ነው ብለናል፡፡ በሌላ አባባል በመሃላቸው የውዝግብ ምክንያት ሲፈጠር ነው፡፡ የውዝግቡ መነሻም በአመዛኙ ብሔርተኝነተ እራሱ ነው፡፡ እሱም በተራው ከብሔራዊ መንግሥታት ምሥረታ ወዲህ የተለያዩ ስብስቦች ተቧድነው የሚሻኮቱበት፣ በአንድ መንግሥት ሥር ተጠቃልለን በአንድነት እንኑር ወይስ እያንዳንዳችን ለየራስ መንግሥት ምሥረታ እውን መሆን በየፊናችን እንንቀሳቀስ በሚለው ርእሰ ጉዳይ ላይ መስማማት ሲያቅታቸው ነው ጠቡ የሚጫረው፣ ከታሪክ መዛግብት እንደታየው፡፡ በዘመነ መንግሥተ ብሔር ምሥረታ የአብዛኛው የውዝግቦች መነሾ ይኸው ብሔርተኝነት ነበር፡፡ ገባ ተብሎ ማፍታታት ሊያስፈልግ ነው፡፡
ብሔርተኝነት ብሔሮች (ብሔረሰቦች፣ ሕዝቦች) የራሳቸውን መንግሥት ለመመሥረት ማንኛውም መብቶች የሚሏቸውን ሁሉ ለማስከበር ወይም ለማስመለስ የሚያደርጉት እንቅስቃሴ በሙሉ በዚህ ውስጥ መካተታቸው ሊያነጋግር ይችል ይሆናል። በዚህ መጽሐፍ ይህን የተጠቀምኩት የራስን መንግሥት ለመመሥረት ከሚደረገው ተጋድሎ ጋር በአመዛኙ የተያያዙ ስሜቶችን፣ እንቅስቃሴዎችንና አይዲዮሎጂን እንዲያመለክት ነው፡፡ ከዚህ በታች የሚገኙትን ወይም እንደ ልዕለ ብሔርተኝነት ያሉትን ስሜትም ሆነ አይዲዮሎጂ ወይም እንቅስቃሴ አልፎ አልፎ ካልሆነ በስተቀር አልተካተቱም፡፡
በኋላ ላይ እንደምንመለከተው በኦሮሞ ጥያቄ ዙሪያና ሳቢያ የተቀሰቀሰውን ስሜትና የተቀረፀውን ርዕዮተ ዓለም እንዲሁም መመለሻ ሐሳቦች ብሔርተኝነት ነው ያልኳቸው፡፡ በስልጤና በጀበርቲ የመብት ጥያቄ ሳቢያና ዙሪያ የተቀሰቀሱትን ግን እንደ ትሕተ ብሔርተኝነት ስለተመለከትናቸው ብሔርተኛ አልተባሉም፡፡ ነገር ግን ከወዲሁ ተገቢ ግንዛቤ ማግኘት ያለበት፣ ጉዳዩ መታየት የሚኖርበት ስብስቡ ካነሳው የመብት ጥያቄ አንፃር እንጂ ከእድገት ደረጃው ጋር ምንም ተዛምዶ ወይም ግንኙነት ሊኖረው እንደማይገባ ነው፡፡ በዚህ መጽሐፍ በአገራችን የሚገኙ ሁሉም ስብስቦች የእድገት ደረጃቸው ምንም ይሁን ምን ብሔረሰብ የተሰኘው፣ በተቻለ መጠን፣ የተጋነነ ግምትና ትርጉም እንዳይሰጠው ተብሎ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ብሔረሰቦች ጥናት ኢንስቲትዩት አጠቃቀምን በመከተል በማንኛውም የእድገት ደረጃ ላይ ሲገኝ ማንኛውም ስብስብ፣ ብሔረሰብ በሚለው አማካይ ስያሜ እንዲታወቅ መመረጡን የቱን ያህል ችግሩን እንዳቃለለ አናውቅም፡፡
ናሽናሊዝም ወይም ብሔርተኝነት ያንድ ስብስብ አባላት ከየብሔራቸው (ኔሽን) ጋር የፈጠሩት ጠንካራ ቁርኝት ነው ሊባል ይችላል፡፡ ይህ ትስስር አይዲዮሎጂ ሆኖ ከሌሎቹ ተለይተን የራሳችን መንግሥት መመሥረት አለብን ሲሉ ነው፣ ከስሜት አልፎ ከሌሎች ስብስቦች ጋር ወደ መፋጠጥና ግብግብ ተግባራዊ እንቅስቃሴ የሚገቡት፡፡ በዚህ መነሻነት ከሌሎች ዓላማቸውን ከሚፃረሩ ወይም የሚፃረሩ ከሚመስሏቸው ጋርም ይጋጫሉ፡፡ ይህ ስሜትና አይዲዮሎጂ ከጥንቱ ከጧቱ የነበረና ወደፊትም የሚኖር ነው ባዮች አሉ፡፡ በእነሱ አመለካከት መሰረቱና መነሻው ደምና የአጥንት የዘር ትውልድ ዝምድና ነው፡፡ ይህንን አመለካከት ነው ፈረንጆቹ The primordialist perspective/ የበኩራዊነት አተያይ ብለው የሚጠሩት፡፡
ሌላው አመለካከት ፈረንጆቹ The modernist perspective/ የዘመነኝነት አተያይ የሚሉት ፍረጃ ነው፡፡ እሱም ብሔርተኝነት ከተወሰነ የማኅበረሰብ አወቃቀር ጋር ተያይዞ በቅርብ ዘመን ብቅ ያለ ክስተት እንደሆነ አድርገው የሚመለከቱበት አረዳድ ነው። ዋናው ቁም ነገር ግን ስብስቡ በአባላቱ መካከል ባለው የዘር፣ የካልቸር፣ የሃይማኖትና የሌሎች ተዛማጅ የጋራነቶች ምክንያት እያንዳንዱ ብሔረሰብ በራሱ ጠቅልል መንግሥት ሥር መጠቃለል አለበት የሚለውን መሠረተ ሀሳብ የሚያቀነቅን መሆኑ ነው፡፡ በባለብዙ ብሔር አገር ውስጥ የጋራነቶችን የማይጋሩትን ራሳቸውን በራሳቸውን የሚያስተዳድሩበት አደረጃጀት ይኑር ባዮች በዚህ ውስጥ ይካተቱ ወይስ አይካተቱ የሚለው ደግሞ ራሱን የቻለ ክርክር ነው፡፡ ለጊዜው እዚያ ውስጥ እንገባም፡፡     
ምንጭ፡- (ከደራሲ ዩሱፍ ያሲን ‹‹ኢትዮጰያዊነት፤ አሰባሰቢ ማንነት፤ በአንድ አገር ልጅነት›› የተሰኘ መፅሃፍ
የተቀነጨበ፤ ህዳር 2009)

ርዕስ - በፍቅር ስም
ደራሲ - ዓለማየሁ ገላጋይ
የሕትመት ዘመን - 2009
የገጽ ብዛት - 216
የመሸጫ ዋጋ - 71.00 ብር
ማተሚያ ድርጅት - Eሪቴጅ ኅትመትና
ንግድ ኃ/የ/የግል ማህበር
የታተመበት ቦታ - አዲስ አበባ
             (ቅኝት - መኩሪያ መካሻ)

    በፍቅር ስም የዓለማየሁ ገላጋይ የአእምሮ àማቂው ስድስተኛ ልብ - ወለድ ነው፡፡  ዘንድሮ ለጥበብ አድባር ያቀረበው ግብር መሆኑ ነው፡፡  ጥበብ ምሷን አገኘች፡፡ ስራዎቹ የአዳዲሶቹ ደራሲዎቻችን አዲስ ማዕበላዊ (new  wave) አጻጻፍ አካል ነው፡፡ እኛም አዲስ የአጻጻፍ ስልት ወደ ያዘው በፍቅር ስም ድርሰት ስናመራ ፍጹም ወደ አልተጠበቀ የከተማ ዳርቻ እንደርሳለን፡፡  በመጀመሪያ ከድህነት ወለል በታች የሚኖሩ የቤተሰብ አባላትን እናገኛለን፡፡  ፍጹማዊው ድህነት ቀይዶ ይደቃቸዋል፡፡  መቸቱ ግልጽ ነው - የምናውቀው የጉለሌው የሩፋኤል ሠፈር ስለሆነ።  ጊዜው ከደርግ ዘመን ጀምሮ እስከ መጀመሪያው የኢህአዴግ ድል ማድረጊያ ወቅት የትረካ መስመሩን ይዞ ይጓዛል፡፡  ማህበራዊ አካባቢው በጊዜው በነበረ አንባገነናዊ ሥርዓት ውስጥ ይካሄዳል፡፡  በመሠረቱ የሩፋኤል ሠፈር ለኢትዮጵያ የሥነ -ጽሁፍ ታሪክ አዲስ አይደለም፡፡ በሀዲስ ዓለማየሁ፤ በብርሃኑ ድንና በሌሎችም ሥራዎች የትወና መድረክ ነበር።  በአሁኑ ጊዜ ደግሞ የከተማችን ኋላ ቀር አካባቢ ሳይሆን አይቀርም፡፡  የተረሱ፤ የተገፉ - የተገፊዎች ሠፈር መሆኑን እንገነዘባለን፡፡
የዓለማየሁ ድርሰቶች በደምሳሳው ሲታዩ የደስተዮቭስኪ፤ የቼሆቭና የላቲን አሜሪካው ገብርኤል ጋርሻ ማሪኩዝ ተጽዕኖ ይታይባቸዋል፡፡  ዓለማየሁ ልክ እንደ ማርኩዝ ሁሉ “የራሱን ዓለም“ ፈጥሯል፡፡  ይህ የራስ ዓለም ከገጽ ወደ ገጽ በተለያየ መንገድ የሚገለጽና አንባቢን ባልተለመደ ጉራንጉር ይዞ የሚነጉድ መገነጢሳዊ ልጓም አለው፡፡ የአእምሮ ምግብነቱም (መገብተ-አእምሮነቱ) እንደተጠበቀ ሁኖ፡፡
ገጾቹን በገለበጥን ቁጥር የዚች ምስኪኖች ሠፈር ሰዎች ማን እንደሆኑ? ለምን እንደሚኖሩ፤ እንዴት እንደሚኖሩ? እንመለከታለን፡፡  በዚያ ፉርጎ ቤት ውስጥ የሚኖሩት አባላት ዥንጉርጉር ናቸው፡፡  ኢትዮጵያዊ ዥንጉርጉርነት፡፡  በመካከላቸው ግጭት አለ፡፡  ድርሰቱን ያቆመውም ይኸው ነው፡፡  የሥነ - ልቡናና የዕምነት አለመጣጣም ይስተዋላል፡፡  ልክ ቼሆቭ ሲጠቀምበት እንደነበረው ሁሉ ዓለማየሁም አንባቢው በግሉ እንዲያስብ ያደርጋል፡፡  በድርሰቱ እሱ ያላሟላውን አንባቢው እንዲያሟላ ዕድል ይሰጠዋል፡፡ ለዚህ ነው በአንዳንድ የድርሰቱ ክፍሎች የተንጠለጠሉ የሚመስሉንን ጉዳዮች ራሳችን በዕዝነ-ልቡናችን እንድናጠናቅቃቸው የምንገደደው፡፡
በድርሰቱ ውስጥ የሚታዩት “ትንንሽ ሰዎች“ በውስጣዊ ማንነታቸው “ትልቅነታቸው“ ይወጣል።  ትንንሽ እንዲሆኑ ኮድኩዶ የያዛቸውን ሰንካላ ጉዳይ ዓለማየሁ አንጥሮ ያሳያል፡፡  በቀድሞ የማንነት ኩራት ውስጥ ወደፊት የተስፋ ህይወት ይታሰባል። ግን ደግሞ ህይወታቸው ከእጅ አይሻል ዶማ ነው፤ ተለውጦ አናይም፡፡  በወንፊት ላይ የሚወርድ ውሃ ይመስል ምንም አይቋጥርም፡፡ ፀሐፊው በዘÈና በሚያስደምም መንገድ ለወታደራዊው ኦሊጋርኪ ያለውን ጥላቻም አስመስክሮበታል፡፡ በደሉን ያጋልጣል፡፡
ዓለማየሁ ከአሁን ቀደም ባሳተማቸው ድርሰቶቹ በኢትዮጵያዊያን አንባቢያን ዘንድ መልካም ሥፍራን አግኝቷል፡፡  የጥበብ አድባር እጣኗን አጢሳ፤ ሽቱዋን ነስንሳ ተቀብላዋለች፡፡  የአሳታሚን ክፉ ወጥመድ አልፎ ለዚህ መብቃት በራሱ መታደል ነው፡፡  ካለፉት ድርሰቶች ለእኔ በግል «አጥቢያ» እና «ቅበላ» ማርከውኛል፡፡  ጥልቀት አላቸውና፡፡
ከላይ ለመጥቀስ እንደሞከርኩት ደራሲው የጊዜውን አምባገነንነት ለማሳየት ቀጥታ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ አይከፍትም፡፡ እንደ ልብ - ወለድ ፀሐፊነቱ ሰዋዊ ሁኔታን (Human situation) ማሳየት ግዴታው መሆኑን በውል ተገንዝቧል።  ምንም እንኳ ግላዊ የፖለቲካ አቋም ሊኖረው ቢችልም “ትክክል“፤ “ስህተት“ በሚል የፖለቲካ አቋም ይዞ አይፈርድም፡፡  “የትናንሾቹ ሰዎች“ ህይወት እንዲህ በቀላሉ እንደማይከናወን በሰራተኛ ሠፈር ወጣቶች አሳይቷል፡፡ ገላጭ ቃላቶቹ፤ ፍልስፍናዊ ማነጻጸሪያዎቹ ወደር የላቸውም፡፡ የነፍስ ሲቃቸው ፍንትው ብሎ ይታየናል፡፡ በተለይ አንዳንድ የሚጠቀምባቸው ቃላቶቹ የቦረን ጎረምሳ የወረወረው ጦር ሆኖ ይሰማናል፡፡ አብዛኞቹ ደግሞ ሮማውያን የገነቡአቸው የዕብነበረድ ሀውልቶች ወይም እንደ ፋርስ ወላንሳ ትንቡክ ትንቡክ ስለሚሉ አይጎረብጡንም፡፡ ይዘው ያንፈላስሱናል፡፡ አቤት ምቾት - ጣ!
ዋናው ገፀ - ባህርይ ሆኖ የሚቀርበው አባቱ (ቢዘን) ህዝባዊ ብሔርተኛ ነው፡፡ “ብዜን በሰሜን ኢትዮጵያ በኩል የገንጣይና አስገንጣይ ጫና ተቋቁሞ ኤርትራን ለጓድ መንግሥቱ ያስረከበ ተራ ኢትዮጵያዊ“ ሲል ይገልፀዋል፡፡  ይህን ሰው የዚያን ዘመን ብሔራዊነት የተጎናጸፈ ነውና የጎሳ ወይም የመንደር ልጅነት አይበግረውም፡፡  የሀገር ጉዳይ ዋነኛው የህይወት እሳቤ የሆነባቸው እልፍ አእላፍ ሰዎች ተምሳሌት ነው፡፡  በተቃራኒው ሌሎች በየመሸታ ቤቱ አሸሼ ገዳሜ ሲሉና ልጆቻቸውን ሲያሳድጉ (እሱ ልጆቹን በትኖ) እንደ ቢዘን ያሉ ሰዎች ብቻ ሞተው እንዲያኖሯቸው የሚጥሩ ስግብግብ ዜጎች መኖራቸውንም እንመለከታለን፡፡ “የሞተልሽ ቀርቶ፤ የገደለሽ በላ“ ይባል የለ? ለዚህም ነው ቢዘን ለሁለተኛ ጊዜ እንዲዘምትላቸው (እንዲሞትላቸው) የሚላከው፡፡  እዚህ ላይ ነው እንግዲህ ስለ ሀገር ጉዳይ ዕዳ የመክፈል ጣጣ በእነዚህ ልዩ በሆኑ “ትናንሽ ሰዎች“ ጫንቃ ላይ የወደቀው፡፡  ዓለማየሁ በዝምታ አልተመለከታቸውም፡፡ በስስ ብዕሩና በአሽሙራዊ አፃፃፉ ወጋ፤ ወጋ ያደርጋቸዋል፡፡
የዓለማየሁ ቀልዶችና ገለፃዎች ሠርሥረው ደም ስር ውስጥ የሚቀሩ ናቸው፡፡  አልፎ አልፎ ለማዋዣነት ስለሚያገለግሉ ጣዕም ያለው ዜማ ሆነው ይሰሙናል፡፡  የታሪክ መስመሩን ተከትለን እንድንጓዝ የሚያደርጉ ፊት ለፊታችን የተወረወሩ የወርቅ ሣንቲሞች ናቸው ብንል ማጋነን አይሆንም።  ለምሣሌ ጥሩንባን እንውሰድ፤ - “የፀበኛ በሬ ቀንድ ይመስላል፡፡  ከቅርብ አይቼው አላውቅም፤ ጉርብርብ መዳብ ነው፡፡ ፈንጣጣ ውግ የመሰሉ ጉድጓዶቹ በዕድፍ ጠቁረዋል፡፡ አፉ በክርና በፕላስቲክ ተጠቅልሎ ወፍሯል …”
ባልና ሚስቱ መሓል ዕውነተኛ የትዳር መሠረት ተጥሏል፡፡  የማይሰበር ግንኙነታቸው ጥሩና መጥፎን አሳልፎ ቆይቷ    ል፡፡  ባለቤቱ የባዕድ አምልኮና የቤተክርስቲያን ሰው ናት፡፡  ሁለቱን በአንድ ላይ ታራምዳለች፤ እንደ ማንኛውም የሰፈር ባልቴት። እናት የቤተሰቡ ዋና የህይወት ድልድይ፤ ለፍቶ አዳሪና የቤቱ ዋልታ ናት! ወጥዋ ከሩቅ የሚጣራ ባለ ሙያ፡፡
የበፍቅር ስምን የአጻጻፍ ስልት ደግሞ ለማየት እንሞክር፡፡  የዓለማየሁ የአጻጻፍ ስልት እምን ላይ እንደሚወድቅ ለመለየት አስቸጋሪ ሆኗል።  በምናባዊና በዕውኑ አጻጻፍ ስልት መሃል እንጎቻ ትረካዎች እንደ ሰንሰለት ተያይዘው የሚቀርቡ ናቸው፡፡ በሀገራችን አልተለመደም፡፡ ባለፉት 300 ዓመታት የተፈጠረውን የበርሌክስን የሥነ-ጽሁፍ (Burlesque Literature) መንገድ የተከተለ ይመስለኛል፡፡ በኋላም በ1960ዎቹ የተፈጠሩ new waves::  በርሌክስን “ወዘበሬታ አጻጻፍ“ እንበለው ይሆን? (የሥነ - ጥበብ ጠበብት አስተያየት ቢሰጡበት መልካም ይመስለኛል)፡፡ የበርሌክስ  ዋናው መለያው ህይወትን በቧልታይና አቋራጭ መንገድ ማቅረብ ነው፡፡ አጻጻፉ ያልተለመደና በፈጠራውና በድርጊቱ  መካከል አለመመሳሰል ይታያል፡፡ በድርሰቱ ውስጥ የቀረቡት ገፀ-ባህሪያትም “በአጭር ቁመት፤ በጠባብ ደረት” እንዲሉ እጥር ምጥን ያሉ ናቸው።  ወለፈንዳዊነትም ይታይባቸዋል፡፡ እንደነ ቹቹ ወይም እንደነ ቻይና ሆነው ሲቀርቡ እንመለከታለን።  አይነኬ አባባሎች ወይም ልምዶች ወደ አደባባይ ይወጣሉ፡፡
“በፍቅር ስም“  የትረካ ሰንሰለቱ ክፍል ሁለት ላይ ሲደርስ ውጥረቱ ጥልቀት ያገኛል፡፡  ታለ በመጀመሪያ መደብ (እኔ) ውስጣዊ የባህሪያት ግጭት ውስጥ የወደቀ ነው፡፡ የሚወዳት ሲፈን ስለምትወልድለት ብቻ የሚጠላት ትሆናለች፡፡  
ልክ እንደ ካፍካ ሜታሞሪፎሲስ ከአንድ አካልነት ወደ ሌላ ልዩ  አካልነት የመለወጥ አባዜም ይጠናወተዋል፡፡  በአንድ ጊዜ ከአልአዛርነት (ታለ) ወደ ቹቹነት ይለወጣል፡፡ ነፀብራቅነት ይገለጣል። ያ ከጉለሌ የተነሳው ፍቅር፤ ሠራተኛ ሠፈር ድረስ ተጋግሎ ይዘልቅና መጨረሻው ግን ፍሬ አልባ ይሆናል፡፡  ፍቅር ሲደምቅ፤ እንደ አበባ ሲፈካና  ፍሬነቱ ሲጎመራ አናይም፡፡  ፍሬው በመፈጠሩ ወይም በማርገዟ ምክንያት ከጉለሌ ላትመለስ ትወጣለች፡፡  መጥፎ ቆሌ ሆና ትቀራለች፡፡
በፍቅር ስም ከአንዳንድ ህፀፆች የፀዳ አይደለም።  በተለይ አንዳንድ ቦታ ላይ የንባብ ፍሰቱን የሚያዘናጉሉ፤ ትርጉሙን የሚያደበዝዙ አሉበት (ገፅ 133)፡፡  በክፍል አንድ የተዘጋ ፋይል በክፍል ሁለት ካለ ምክንያት ሲደገም ትኩረትን ይፈታተናል።  አንዳንድ የሰደራቸው መጠይቆችና ምልልሶች  ወደ ተራ - ፈላስፋነት እንዳያወርደው መጠንቀቅ አለበት።
ክፍል ሦስት በትንቢተ ኢሳያስ ይደመደማል። ይደመደማል ከማለት ይልቅ ንግር (foreshadow)  ሆኖ ይጠናቀቃል፡፡ ምናልባትም ደራሲው ወደፊት ጀባ ሊለን የፈለገውን የፈጠራ ሥራ ጠቁሞን ይሆን? ጊዜ መልስ ይሰጠናል። Jean-Paul Sartre የተባለው ደራሲ፤ “ለምን እንጽፋለን?“  በሚለው ጽሑፍ አንድ ገጠመኙን ያጋራናል። አንድ ጀማሪ ሰዓሊ አስተማሪውን፤ “መቼ ይሆን ስዕሌ መጠናቀቁን የማውቀው?” ሲል ይጠይቀዋል።  አስተማሪውም፤ “በመደመም ስሜት ውስጥ ሆነህ ስዕልህን ስትመለከትና ለራስህ እኔ ነኝ ይህን የፈጠርኩት! ማለት ስትችል ነው” ብሎ መለሰለት ይለናል፡፡  ስለዚህ ዓለማየሁም “ፈጠርኩ እንጂ” “አላደርገውም!” እንዳይል የጥበብ አድባር ትታደገው።    

Sunday, 05 February 2017 00:00

የግጥም ጥግ

  እኛ እና እድገት
እንደ ዜናውማ ….. እንደሚናፈሰው፣
ቀድመነው ሄደናል ….. እድገትን አልፈነው፣
ግን ወሬውን ትተን ….. እውነቱን ካሰብነው፣
ለእኛ የመሰለን ….. ጥለነው የሄድነው፣
ብዙ ዙር ደርቦን ….. ከኋላ ቆሞ ነው፡፡

     የቀን ጨረቃ
ፀሐይ ከለገመች
ቀን ላይ መውጣት ትታ፣
ለጉም ለደመናው
ካሳለፈች ሰጥታ፣
ታስረክባትና
የራሷን ፈረቃ፣
ትምጣና ታድምቀው
የእኛን ቀን ጨረቃ፡፡

    እንባህን ቅመሰው
መስታወት አትሻ
ሰውም አታስመሰክር
እንባህን ቅመሰው
ለማንም ሳትነግር፡፡
ውሃ ውሃ ካለህ
የጨው ጣዕም ከሌለው
ኡኡታህን አቁም
ለቅሶህ የውሸት ነው!
        (ከገጣሚ ሳምሶን ይርሳው ጌትነት “ምልክት” የግጥም መድበል

“ምን አይነቱ ነውር የማያውቅ አሳማ ነው!...” - ሪሃና
     “ያሉት ከሚጠፋ፣ የወለዱት ይጥፋ!...”
ብለዋል - ትራምፕ፡፡
በምርጫ ቅስቀሳ ዘመቻቸው ላይ፣ “ከተመረጥኩ ስደተኞች ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ እከለክላለሁ” ሲሉ የከረሙት አወዛጋቢው ዶናልድ ትራምፕ፤ በለስ ቀንቷቸው ባሸነፉና ወደ ነጩ ቤት ሰተት ብለው በገቡ በሳምንታት ጊዜ ውስጥ፣ ቃላቸውን ጠብቀው ያሉትን አደረጉና ብዙዎችን አስደነገጡ፡፡
“የአገሬንና የህዝቤን ደህንነት ለመጠበቅና ሰርጎ ገብ ሽብርተኞችን ለመከላከል ስል፣ ለማንኛውም አገር ስደተኞችና ለሰባት አገራት ዜጎች በጊዜያዊነት ድንበሬን ዘግቻለሁ!...” በማለት፣ በብዙዎች ዘንድ የሚወራ እንጂ የማይተገበር ተደርጎ የተወሰደውን አስደንጋጭ ነገር ማድረጋቸውን በይፋ አወጁ፡፡
ትራምፕ ባለፈው አርብ በሰባት የተለያዩ አገራት ላይ የጣሉት የጉዞ ገደብ፣ ብዙዎችን በድንጋጤ ክው ያደረገ አነጋጋሪ፣ አስደንጋጭ፣ አከራካሪ አለማቀፍ ክስተት ሆነ፡፡ ጉዳዩ የሰባቱ አገራትና የአሜሪካ አልያም የስደተኞችና የተወላጆች ብቻ ጉዳይ አልሆነም፡፡ የአለማችንን ህዝቦችና የአለማችንን መንግስታት ያነጋገረና ድንበር ሳያግደው ርቆ በመጓዝ በየጓዳው የገባ ሰሞንኛ ጉዳይ ሆነ፡፡
የትራምፕ ውሳኔ በአለማችን ፖለቲከኞች ብቻም ሳይሆን በመዝናኛው መስክ የአለማችን ከዋክብት ዘንድም ድንጋጤንና ቁጣን ፈጥሯል። ከእውቅ የሆሊውድ ተዋንያን እስከ አለማቀፍ የሙዚቃ ከዋክብት፣ በርካታ የአለማችን ዝነኞች በትራምፕ አስደንጋጭ ውሳኔ ዙሪያ አስተያየታቸውን በመስጠት ላይ ይገኛሉ፡፡
የአለማችን ዝነኞች ለትራምፕ ውሳኔ የሰጡትን ምላሽ በተመለከተ መገናኛ ብዙሃን ካወጧቸው ዘገባዎች በጥቂቱ እንጨልፍ!...
ከቀናት በኋላ በሎሳንጀለስ በደማቅ ሁኔታ ለሚከናወነው ታላቁ የኦስካር ሽልማት ከታጩት መካከል አንዱ ነው - ዳይሬክተሩ አስጋር ፋራዲ፡፡
“ዘ ሴልስማን” በሚለው ፊልሙ ለሽልማት የታጨውና ያቺን ልዩ ቀን በጉጉት ሲጠብቅ የሰነበተው ዳይሬክተሩ አስጋር ፋራዲ፤ ያቺ ልዩ ቀን ከመድረሷ በፊት ያልጠበቀውን መርዶ ሰማ፡፡ በዚያች ቀን በሎሳንጀለስ ተገኝቶ፣ የጓጓለትን ሽልማት መቀበል አይችልም፡፡ ምክንያቱም ኢራናዊ ነው። ኢራናዊ ደግሞ፣ በትራምፕ ትዕዛዝ ወደ አሜሪካ እንዳይገባ የተከለከለ የሽብር ተጠርጣሪ ነው፡፡
ዋታኒ - “ማይ ሆምላንድ” በሚለው ፊልሟ በዘንድሮው ኦስካር፣ በዘጋቢ ፊልም ዘርፍ ለሽልማት የታጨቺው ሶርያዊቷ ሃላ ካሚልም፣ ትራምፕ በክፉ አይናቸው ካዩዋት አገር የተገኘች ናትና፣ በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ እንድትገኝ አይፈቀድላትም፡፡ በዚህ አስደንጋጭ ውሳኔ ክፉኛ ማዘኗን ገልጻለች- ሃላ ካሚል፡፡
የትራምፕ ውሳኔ ካስደነገጣቸውና ካሳዘናቸው የአለማችን ዝነኞች መካከል ትጠቀሳለች - ዝነኛዋ ድምጻዊት ሪሃና፡፡ ድምጻዊቷ ትራምፕ ውሳኔውን ባስተላለፉ በነጋታው፣ ጉዳዩን በተመለከተ በትዊተር ባሰራጨቺው ጽሁፍ፣ “አስቀያሚ ነገር ነው!... የሰማሁት ነገር እጅግ አስደንጋጭ ነው!... አይናችን እያየ፣ አሜሪካ እየጠፋች ነው!...” ብላለች፡፡
ሪሃና ይህን ብላ አላበቃችም...
“ምን አይነቱ ነውር የማያውቅ አሳማ ነው!...” ስትል ጋሼ ትራምፕን በገደምዳሜ ወርፋቸዋለች፡፡
ታዋቂው የሆሊውድ የፊልም ዳይሬክተር ማይክል ሙር በበኩሉ፣ “በመላው አለም የምትገኙ ሙስሊም ጎረቤቶቻችን ሆይ፡ እኔ እና በአስር ሚሊዮኖች የምንቆጠር ሌሎች አሜሪካውያን ይቅርታ እንጠይቃችኋለን፡፡ አብዛኛው የአሜሪካ ህዝብ ለዚህ ሰውዬ ድምጹን አልሰጠም!...” በማለት በትዊተር ገጹ መልዕክቱን አስተላልፏል፡፡
ጆን ሌጀንድ በበኩሉ፤ “እኛ አሜሪካውያንና ፕሬዚዳንት ትራምፕ ለአሜሪካ ያለን ራዕይ ፍጹም ተቃራኒ ነው!...” ብሏል፤ ባለፈው ቅዳሜ ምሽት በተከናወነው የፕሮዲዩሰርስ ጊልድ ሽልማት ስነስርዓት ላይ ባደረገው ንግግር፡፡
በዚያው ዕለት የሙዚቃ ኮንሰርቱን ለአድናቂዎች ያቀረበው ድምጻዊው ብሩስ ስፕሪንግስተን በበኩሉ፤ “አሜሪካ የስደተኞች አገር ናት፡፡ የሰውዬው ውሳኔ ኢ-ዲሞክራሲያዊና ከአሜሪካ እሴቶች ውጭ ነው!...” በማለት በትራምፕ ውሳኔ ማዘኑን ገልጧል፡፡
“ወደ አሜሪካ የመጣሁት ከ32 አመታት በፊት ነው፡፡ በዚህች አገር ነዋሪ በመሆኔ ለመጀመሪያ ጊዜ ያፈርኩት ግን፣ ትናንት ነው!...” በሚል በትራምፕ ውሳኔ ማግስት በትዊተር ሃዘኑን የገለጸው ደግሞ፣ “ዘ ቲፒንግ ፖይንት” በሚለው መጽሃፉ የሚታወቀው ደራሲ ማልኮም ግላድዌል ነው፡፡
የተርሚኔተሩ ድንቅ ተዋናይና የቀድሞው የካሊፎርኒያ ገዢ አርኖልድ ሽዋዚንገርም በትራምፕ ውሳኔ መከፋቱን አልደበቀም፡፡ “ይህ እጅግ የለየለት እብደት ነው!... ደደቦች ተደርገን እንድንቆጠር የሚያደርግ አጉል ውሳኔ ነው!...” ብሏል ሽዋዚንገር ከ”ፒውፕል መጋዚን” ጋር ሰኞ ዕለት ባደረገው ቃለ ምልልስ፡፡
“ስደተኞች ሽብርን ሽሽት ርቀው የሚጓዙ እንጂ፣ ሽብርተኞች አይደሉም” የሚለው መረር ያለ ምላሽ ደግሞ፣  የአሜሪካዊቷ ድንቅ የፊልም ተዋናይ የኬሪ ዋሽንግተን ነው፡፡ ዝነኞች ምንም ይበሉ ምን፣ትራምፕ ግን በምርጫ ቅስቀሳቸው ወቅት ለአሜሪካውያን ቃል የገቡትን ሁሉ ሳያጓድሉ እንደሚፈጽሙና አሜሪካንን ዳግም ታላቅ እንደሚያደርጓት በአገኟት አጋጣሚ ሁሉ ከመናገር ወደ ኋላ ብለው አያውቁም፡፡ ለመተግበርም ወደ ኋላ እንደማይሉ ሰሞኑን በግልጽና በድፍረት አሳይተዋል።

Sunday, 05 February 2017 00:00

የፖለቲካ ጥግ

(ስለ ስደተኞች)

   · ትራምፕ የሽብር ጉዳይ ይሄን ያህል ካሳሰበው፣ ለምንድን ነው ሳኡዲ አረቢያ ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ እገዳ ከተጣለባቸው አገራት ዝርዝር ውስጥ ያልተካተተችው?
  ራይሞንድ ስሚዝ (ከአውስትራሊያ)
· ጥገኝነት መጠየቅ ሰብዓዊ መብት ነው፡፡
  አምነስቲ ኢንተርናሽናል
· እዚህ ስደተኞች የሉም፤ የተፈናቀሉ ሰዎችም የሉም፤ … እንግዶቻችን ናቸው፤ እናም የምናስተናግዳቸው በዚያ መልኩ ነው፡፡
  ማይክ ተርነር (በኮንግረስ የኦሃዮ ተወካይ)
· በሶሪያ የቀረን ምንም ነገር የለም፡፡ ውድመት ብቻ፡፡
  ኢብራሂም (የ21 ዓመት ሶርያዊ፤ለCNN የተናገረው)
· እዚህ የሚመጣ ስደተኛ ሁሉ በአምስት ዓመት ጊዜ ውስጥ እንግሊዝኛ መማር ወይም አገሪቱን ለቆ መውጣት አለበት፡፡
  ፕሬዚዳንት ቴዎዶር ሩስቬልት
· ስደተኞች ወንጀለኞች አይደሉም፡፡ እዚህ በመኖራቸውና ለኢኮኖሚው አስተዋጽኦ በማድረጋቸው ሊቀጡ አይገባም፡፡
  ሚሼል ሎፔዝ
· ሰዎች ህገ-ወጥ ስደተኞችን ሥራ መቅጠር ማቆም አለባቸው፡፡
  ሂላሪ ክሊንተን
· በአሪዞና ግዛት ከሽብርተኛ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት ያላቸው ስደተኞች አለመስፈራቸውን ማረጋገጥ አለብን ብዬ አምናለሁ፡፡
  ዶውግ ዱሴይ (የአሪዞና ገዢ)
· ዛሬ 75 በመቶ የሚሆነው የፍልስጤም ህዝብ ተፈናቅሏል፡፡ በመላው ዓለም 5 ሚሊዮን ፍልስጤማዊ ስደተኞች ይገኛሉ፡፡
  ኢስማይል ሃኒዬህ (የሃማስ ምክትል መሪ)
· ድንበሩን መቆጣጠር የማይችል አገር፣ ከአገር አይቆጠርም፡፡
  ፕሬዚዳንት ሮናልድ ሬገን
· አውሮፓ የስደተኞችን ጉዳይ ምላሽ መስጠት ከተሳናት፣ የምንመኛትን አውሮፓ አትሆንም።
  አንጄላ መርከል (የጀርመን ቻንስለር)

 ለምርምራቸው የ600 ሺህ ዶላር የገንዘብ ድጋፍ አግኝተዋል
    አሜሪካ በሚገኘው ኒው ሜክሲኮ ዩኒቨርሲቲ የኬሚስትሪና ኬሚካል ባዮሎጂ የትምህርት ክፍል መምህር የሆኑት ኢትዮጵያዊው ረዳት ፕሮፌሰር ተረፈ ሃብተየስ፣ የአገሪቱ ብሄራዊ የሳይንስ ፋውንዴሽን፣ በምርምር ዘርፍ የላቀ ውጤት ላስመዘገቡ ምሁራን የሚሰጠው “የታላቁ የፋካልቲ ኧርሊ ካሪየር ዲቨሎፕመንት አዋርድ” አሸናፊ መሆናቸው ተዘግቧል፡፡
ረዳት ፕሮፌሰር ተረፈ ሃብተየስ፤ በዩኒቨርሲቲው የላቀ ቴክኖሎጂ ቁሳቁስ ምርምር ማዕከል፣ ከግብረ አበሮቻቸው ጋር ለሚያከናውኑትና አምስት አመታትን ለሚወስደው የምርምር ፕሮጀክት ማስፈጸሚያ፣ የ600 ሺህ ዶላር የገንዘብ ድጋፍ ማግኘታቸውን ዩኒቨርሲቲው በሳምንቱ መጀመሪያ በድረገጹ ላይ ባወጣው መረጃ ጠቁሟል፡፡ ረዳት ፕሮፌሰሩ በምርምር ፕሮጀክቱ፣ እጅግ ጥቃቅን የሆኑ ረቂቅ አካላትን ለማየት የሚያስችል በአይነቱ  የተለየ ማይክሮስኮፕ ለመፍጠር እንደሚሰሩ የጠቆመው መረጃው፤ ማይክሮስኮፑ ለቀጣይ ምርምሮች ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክትም አመልክቷል፡፡
የመጀመሪያና የሁለተኛ ዲግሪያቸውን በኬሚስትሪ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የተቀበሉት እኒሁ ኢትዮጵያዊ ምሁር፣ የፒኤችዲ ትምህርታቸውን በዩኒቨርሲቲ ኦፍ አሪዞና ያጠናቀቁ ሲሆን በዩኒቨርሲቲ ኦፍ ካሊፎርኒያ የፖስት ዶክቶራል ምርምራቸውን እንደሰሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡ እ.ኤ.አ ከ2012 አንስቶ በታዋቂው ኒው ሜክሲኮ ዩኒቨርሲቲ በማስተማር ላይ እንደሚገኙም ተጠቁሟል፡፡

Sunday, 05 February 2017 00:00

የዘላለም ጥግ

(ዝነኞች በመጨረሻ ሰዓታቸው)
· “እየተሸነፍኩ ነው”
   ፍራንክ ሲናትራ
· “ብዕር ለመያዝ አቅም ቢኖረኝ ኖሮ፣መሞት እንዴት ቀላልና አስደሳች ነገር እንደሆነ እፅፍ ነበር”
  ዶ/ር ዊሊያም ሃንተር
· “የምሻው ገነት መግባት ሳይሆን ሲኦል መግባት ነው፡፡ በሲኦል የጳጳሳት፣ የነገስታትና የልኡላን ጓደኞች ይኖሩኛል፡፡ በገነት ግን የኔ ቢጤዎች፣ መነኩሴዎችና ሐዋርያት ብቻ ናቸው ያሉት”
  ኒኮሎ ማኪያቬሊ (የፍሎሬንቲን ዲፕሎማትና የፖለቲካ ፈላስፋ)
· “ሞቼአለሁ ወይም ሰዓቴ ቆሟል”
  ግሮቾ ማርክስ
· “እነዚህን መነኮሳት ከአጠገቤ ዞር አድርጉልኝ”
  ኖርማን ዳግላስ
· “ነገ ይዞ የሚመጣውን አላውቅም”
  ፈርናንዶ ፔሶ (የፖርቹጊዝ ገጣሚ)
· “ከእርስዎ ጋር ለምን አወራለሁ? አሁን ከአለቃዎት ጋር ስነጋገር ነበር”
  ዊልሰን ሚዝነር (ለቄስ የተናገረው)
  (ፀሐፌ ተውኔትና የስክሪፕት ፀሐፊ)
· “ተጣልተን እንደነበር አላውቅም”
    ሔነሪ ዴቪድ ቶሪዎ (ከእግዚአብሄር ጋር ሰላም እንዲፈጥር ሲጠየቅ)
  (አሜሪካዊ ደራሲ፣ ገጣሚ፣ ፈላስፋና የታሪክ ምሁር)
· “ሁሉንም ሰው ይቅር ብያለው፡፡ ሁሉም ሰው እኔንም ይቅር እንዲለኝ እፀልያለሁ። አሁን የሚፈሰው ደሜ ለሜክሲኮ ሰላምን ያሰፍንላታል፡፡ ሜክሲኮ ለዘላለም ትኑር፤ ነፃነት ለዘላለም ይኑር”
  ማክሲሚሊያን (የሜክሲኮ ንጉስ)
· “ዝናቡ ይሰማችኋል? ዝናቡ ይሰማችኋል?”
(አውሮፕላኗ ከመከስከሱ ከደቂቃዎች በፊት)
  ጄሲካ ዱብሮፍ

 ነፍሰ ጡርነቷን የሚያሳየው ፎቶ በተወዳጅነት ክብረወሰን ይዟል

     ታዋቂዋ ድምጻዊት ቢዮንሴ ኖውልስ፣ ነፍሰ ጡር መሆኗን ለአድናቂዎቿ በማብሰር ባለፈው ረቡዕ በኢንስታግራም ድረ-ገጽ በኩል ያሰራጨቻቸውን አነጋጋሪና ከፍተኛ ተወዳጅነት ያተረፉ ፎቶ ግራፎች ያነሳው ትውልደ ኢትዮጵያዊው የፎቶ ግራፍ ባለሙያ አወል ርዝቁ፣ አለማቀፍ ዝናን ያተረፈ የመገናኛ ብዙሃን መነጋገሪያ ሆኗል፡፡
ቢዮንሴ ከባለቤቷ ጄይዚ መንታ ልጆችን በማርገዟ የተሰማትን ደስታ በመግለጽ፣ በኢንስታግራም ያሰራጨቻቸው እርግዝናዋን የሚያሳዩ ፎቶግራፎች እጅግ በሚገርም ፍጥነት የአለምን ትኩረት የሳቡ ሲሆን፣ አንደኛው ፎቶ በአንድ ቀን ጊዜ ውስጥ ከ8.2 ሚሊዮን በላይ ‹‹ላይክ›› በማግኘት በኢንስታግራም ታሪክ ከፍተኛውን ተወዳጅነት በማትረፍ አዲስ ክብረ ወሰን ማስመዝገቡን የአለም የድንቃ ድንቆች መዝገብ ተቋም አስታውቋል፡፡
ያልተመዱትና እርግዝናዋን በግላጭ የሚያሳዩት ፎቶግራፎች አለማቀፍ መነጋገሪያ መሆናቸውን ተከትሎ፣ ፎቶግራፎችን ያነሳው ትውልደ ኢትዮጵያዊ ፎቶ ግራፈር አወል ርዝቁ ከፍተኛ ዝናን ያተረፈ ሲሆን፣ ታላላቅ የአለማችን መገናኛ ብዙሃንም እሱንና ለአመታት የዘለቀውን የስነ-ጥበብ ታሪኩን በተመለከተ በስፋት በመዘገብ ላይ ናቸው፡፡
በአዲስ አበባ የተወለደውና በአሜሪካ ያደገው የ28 አመቱ አወል ርዝቁ፤ በዋናነት የፎቶግራፍ ባለሙያ ቢሆንም፣ ተቀማጭነቱን በሎሳንጀለስ በማድረግ በርካታ ስራዎችን በመስራት ላይ የሚገኝ ሰአሊ፣ ቀራጺና የአጫጭር ፊልሞች አዘጋጅ መሆኑን የዘገበው ቢቢሲ፣ ከአሜሪካው ኮፐር ዩኒየን ኮሌጅ እ.ኤ.አ በ2010 በፋይን አርትስ የመጀመሪያ ዲግሪውን መቀበሉንና እ.ኤ.አ በ2014 ከታዋቂው የል ዩኒቨርሲቲ በፋይን አርትስ ሁለተኛ ዲግሪውን ማግኘቱንም አስታውሷል፡፡
ኒውዮርክ በሚገኘው ሚዩዚየም ኦፍ ሞደርን አርት እና በሌሎች የአሜሪካ ሙዚየሞችና ጋለሪዎች የፎቶግራፍና ሌሎች የስነ-ጥበብ ስራዎቹን በግልና በተናጠል በኢግዚቢሽን መልክ ለተመልካቾች ያቀረበው አወል፤ ከዚህ በፊትም ቢዮንሴን ጨምሮ የተለያዩ የአለማችን ታዋቂ ድምጻውያንን አስገራሚ ፎቶግራፎች በማንሳት ይታወቃል፡፡
በአነጋጋሪ ፎቶ ግራፎች የታጀበው የቢዮንሴ የእርግዝና ዜና በትዊተር ድረገጽ በከፍተኛ ፍጥነት የተሰራጨ ሲሆን፣ ረቡዕ ዕለት ብቻ በየደቂቃው በአማካይ 17 ሺህ ጊዜ ስለጉዳዩ ትዊት መደረጉንና የትዊተር ተከታዮቿ ቁጥርም በከፍተኛ ሁኔታ በማደግ 93.1 ሚሊዮን መድረሱን ሲኔት ድረገጽ ዘግቧል፡፡
እ.ኤ.አ በ2008 በትዳር የተሳሰሩት ታዋቂዎቹ የዓለማችን ዝነኛ ድምጻውያን ቢዮንሴ እና ጄይ ዚ፣ ከሶስት አመታት በኋላ የመጀመሪያ ልጃቸውን ብሉ ኢቪን ወልደው ለመሳም በቅተዋል፡፡