Administrator

Administrator

• የግል ቤት የሌላቸው የክልሉ ተወላጆችና የኦሮሚያ ዳያስፖራዎች ተጠቃሚ ይሆናሉ
• የመጠጥ አምራች ኩባንያና የሲሚንቶ ፋብሪካ አክሲዮኖች ለክልሉ ተወላጆች ይቀርባሉ

የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት፣ ተወላጆቹ በሙሉ በክልሉ ከተሞች የመኖሪያ ቤት መስሪያ የከተማ ቦታ በነፃ እንዲያገኙ ወሰነ፡፡
በክልሉ የሚገኙ አርሶ አደሮች፣ አርብቶ አደሮች፣ የግል መኖሪያ ቤት የሌላቸው የከተማ ነዋሪዎች፣ ወጣቶች፣ መምህራንና የመንግስት ሰራተኞችን ጨምሮ የኦሮሚያ ዳያስፖራዎች በሙሉ የመኖሪያ ቤት መስሪያ የከተማ ቦታ በነፃ እንዲያገኙ መወሰኑን የኦሮሚያ የከተማ ቤቶች ልማት ም/ሃላፊ አቶ ሽመልስ አብዲሣ ለአዲስ አድማስ አስረድተዋል፡፡
የክልሉ መንግስት ከዚህ ውሣኔ ላይ የደረሰው የክልሉ ከተሞች የተወላጆችን ጥቅም ባማከለ መልኩ እንዲያድጉና ተወላጆች በከተሞች ድርሻ እንዲኖራቸው ለማድረግ መሆኑም ተገልጿል፡፡ የክልሉ መንግስት ባደረገው ግምገማ፤ የቤት ኪራይ ዋጋ ውድነት ነዋሪዎችን ላልተፈለገ ወጪ መዳረጉንና እንዳይረጋጉ ማድረጉን፣ ቀደም ሲል በነበረው አካሄድ የክልሉ ከተሞች እድገትም በሚፈለገው መጠን አለመሆኑን እንዲሁም የክልሉን መሬት ለህገ ወጥ ደላሎች ያጋለጠ አሰራር እንደነበረ ደርሶበታል፡፡ እነዚህን ችግሮች ከግምት ውስጥ በማስገባትም ዜጎች የቤት መስሪያ የከተማ ቦታ እንዲያገኙ የሚያስችለው ደንብና መመሪያ ሊወጣ መቻሉን ም/ሃላፊው ጠቁመዋል፡፡
‹‹ህብረተሰቡ የከተማ ህይወት እንዲኖር ይፈለጋል›› ያሉት አቶ ሽመልስ፤ ይህ የክልሉ መንግስት እቅድ ይሄን ለማሳካት ያለመ በመሆኑ አርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ በዚህ ማዕቀፍ እንዲካተቱ መደረጉን አብራርተዋል፡፡ ከመከላከያ ሰራዊት ጡረታ የወጡ ግለሰቦችና ሌሎች የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችም የዚህ ፕሮጀክት ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ታውቋል፡፡  
በአካባቢው ለሁለትና ከዚያ በላይ ዓመት የኖሩ፣ የቤት መስሪያ ገንዘብ መቆጠብ የሚችሉና ቀሪ ገንዘብ መንግስት በሚያመቻቸው ብድር ለማግኘት ፍቃደኛ የሆኑ ግለሰቦች የቤት መስሪያ ቦታ ለማግኘት መደራጀት እንደሚችሉ ሃላፊው አስረድተዋል፡፡
ቦታ ፈላጊዎች የሚደራጁት በ4 አይነት አማራጮች ነው ተብሏል፡፡ በጋራ አፓርትመንት ለመገንባት የሚፈልጉ፣ G+1 እና ከዚያ በላይ መገንባት የሚፈልጉ እንዲሁም ቪላ ቤት መስራት የሚችሉ በሚል ሲሆን ይሄን ለማድረግ አቅም የሌላቸው መለስተኛ ቤቶችን ለመስራት የሚችሉባቸው አማራጮች መቀመጣቸውን አቶ ሽመልስ አብራርተዋል፡፡
የክልሉ መንግስት በዝቅተኛ ወጪ ቴክኖሎጂ ተጠቅመው የሚገነቡ የቤት አማራጮችን እያጠና መሆኑም ተገልጿል፡፡ አንድ ግለሰብ ለመኖሪያ ቤት መስሪያ የተሰጠውን ቦታ መሸጥ መለወጥና ከህጋዊ ወራሾች በስተቀር ለ3ኛ ወገን ማስተላለፍ እንዲሁም በውክልና ማሰራት አይችልም ብለዋል፤ ሃላፊው፡፡ እስከ 10 ዓመት ድረስም ካርታ እንደማይሰጥ አክለው ገልፀዋል፡፡ በነዚህ ጥብቅ መመሪያዎች እንዲታጠር የተደረገው የመሬት ብክነትንና ያለአግባብ መገልገልን ለማስቀረት በማሰብ ነው ተብሏል፡፡  
በክልሉ ከ9 ዓመት በላይ መሬት በዚህ መልክ ተሰጥቶ እንደማያውቅ የጠቆሙት አቶ ሽመልስ፤ የክልሉ መንግስት ይሄን ሰፊ እቅድ ሲተገብር ሊያጋጥሙ የሚችሉ ተግዳሮቶችንም በዝርዝር መለየቱን አስታውቀዋል፡፡ ከተለዩ ተግዳሮቶች መካከል የመሬት አቅርቦት አንዱ መሆኑን የጠቀሱት ሃላፊው፤ በተለይ ለአርሶ አደሮች የሚከፈል የመሬት ካሳና መንግስት መሬቱን ያለምንም የሊዝ ክፍያ ገቢ ሳያገኝበት በነፃ ለፈላጊዎች ማስተላለፉ ጫና ሊፈጥርበት እንደሚችል ጠቁመው፣ ለዚህም የተለያዩ አማራጮች እየተፈተሹ መሆኑን አስረድተዋል። ሌላው ተግዳሮት ለብድር አቅርቦት የሚሆን የፋይናንስ አቅም ሲሆን ይህንንም የቁጠባ ባህልን በማሳደግ ለመፍታት ጥረት ይደረጋል ብለዋል፡፡
የክልሉ መንግስት ለዚህ ፕሮጀክት ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ ሰፊ ዝግጅት ማድረጉ የተገለጸ ሲሆን በአሁን ወቅትም ቤት የሌላቸውን ሰዎች ለይቶ የማደራጀት ስራ እየተሰራ ነው ተብሏል፡፡ የመሬት አቅርቦቱም ሰዎች በፈለጉት የቤት አይነት ተደራጅተው ሲቀርቡ ወዲያው የሚፈፀም መሆኑ ተገልጿል፡፡
በሌላ በኩል የክልሉ መንግስት ይፋ ባደረገው ‹‹የኢኮኖሚ አብዮት››፣ ከኦዳ ትራንስፖርት አክሲዮን በተጨማሪ በቅርቡ የተለያዩ መጠጥ አምራች ኩባንያና የሲሚንቶ ፋብሪካ አክሲዮኖችን ለክልሉ ተወላጆች በሽያጭ ለማቅረብ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የክልሉ የመንገድ ትራንስፖርት ሃላፊ አቶ ታከለ ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡

የድርድሩ ቀጣይ እጣ ፈንታ በኢህአዴግ እጅ ነው”

ከገዥው ፓርቲ ጋር የቅድመ ድርድር መመሪያ ላይ ውይይት እያደረጉ ያሉት 20 ተቃዋሚ ፓርቲዎች፣ ያለ ገለልተኛ አካል ድርድር እንደማይኖር ያስታወቁ ሲሆን ኢህአዴግ ጉዳዩን ለማጤን ቀጠሮ ወስዷል፡፡
ፓርቲዎቹ ባለፈው ቅዳሜ መጋቢት 9፣ ቀኑን ሙሉ ባደረጉት ውይይት ቀደም ሲል በዙር መድረክ እየመራን እንደራደር የሚል ሃሳብ ያቀረቡ ተቃዋሚዎች አቋማቸውን ለውጠው፣ ድርድር ያለ ገለልተኛ አደራዳሪ አይሆንም ሲሉ የተፈጠሙ ሲሆን ኢህአዴግና አንድ ተቃዋሚ ፓርቲ በዙር መድረክ እየመራን መደራደር አለብን በሚል አቋም በመጽናታቸው መግባባት ላይ ሳይደረስ ቀርቷል። ይሄን ተከትሎም ኢህአዴግ ጉዳዩን በድጋሚ ለማጤን ጊዜ እንዲሰጠው የጠየቀ ሲሆን በመጪው ረቡዕ መጋቢት 20፣ አቋሙን እንደሚያሳውቅ ይጠበቃል፡፡
የቅዳሜውን ውይይት አስመልክቶ ያነጋገርናቸው የመኢአድ ም/ፕሬዚዳንት አቶ ሙሉጌታ አበበ፤ በእለቱ ሁሉም ተቃዋሚዎች ገለልተኛ አካል ያደራድረን የሚል አቋም መያዛቸው ያልጠበቁት መሆኑን ገልፀው፤ “ፓርቲያችን በአደራዳሪዎች ገለልተኛነት ላይ የተሸራረፈ አቋም የለውም›› ብለዋል፡፡ ኢህአዴግ አቋሙን ካልቀየረ የድርድሩ ቀጣይነት ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ እንደሚኖረውም አቶ ሙሉጌታ አስታውቀዋል፡፡
የኢዴፓ ዋና ፀሃፊ አቶ ዋሲሁን ተስፋዬ በበኩላቸው፤ ከአንድ ተቃዋሚ ፓርቲ በስተቀር ሌሎቹ ገለልተኛ አካል ያደራድረን የሚለው አቋማቸው የፀና መሆኑን ጠቁመው፤ ኤዴፓም ይሄን አቋም እንደማይቀይር ተናግረዋል፡፡ ‹‹ገለልተኛ አካል ካላደራደረ ኢዴፓ በድርድሩ ሊቀጥል አይችልም›› ብለዋል - አቶ ዋሲሁን፡፡
“ኢህአዴግ ወደ ብዙኃኑ አቋም ይመጣል የሚል ተስፋ አለኝ” ያሉት የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር አቶ የሸዋስ አሰፋ፤ የድርድሩ ቀጣይ እጣ ፈንታ በኢህአዴግ እጅ ነው ብለዋል፡፡  
21 ፓርቲዎች የሚያደርጉት ስብሰባ ውይይት እንጂ ድርድር ሊባል አይችልም የሚል አቋሙን ያፀናው መድረክ በበኩሉ፤ በዚህ ሁኔታ በድርድሩ እንደማይቀጥል የአመራር አባሉ አቶ ጥላሁን እንደሻው ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል። መድረክ ለገዥው ፓርቲ ሁለት አማራጮችን ማቅረቡን የጠቆሙት አቶ ጥላሁን፤አንደኛው ተቃዋሚዎች በመድረክ እንዲወከሉና ከኢህአዴግ ጋር እንዲደራደሩ አሊያም ኢህአዴግ ከሌሎቹ ጋር ከሚያደርገው ድርድር ጎን ለጎን ለብቻው ከመድረክ ጋር እንዲደራደር ሀሳብ አቅርቦ ምላሹን በመጠባበቅ ላይ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ኢህአዴግ ለዚህ ፍቃደኛ ካልሆነ መድረክ ከ21 ፓርቲዎች ጋር  ለድርድር እንደማይቀርብና ከድርድሩ እንደሚወጣ አቶ ጥላሁን አስታውቀዋል፡፡
‹‹ምንም ውጤት ያላመጣውን የፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤትን የሚመስል ውይይት እንዲደረግ አንፈልግም” ያሉት የአመራር አባሉ፤ ‹‹የህዝቡን ችግር ነቅሰን አውጥተን ተጨባጭ መፍትሄ እንዲሰጥባቸው ነው የምንፈልገው” ብለዋል፡፡ ‹‹የታሰሩ ፖለቲከኞችም እንዲፈቱ ከተፈለገ ጠንካራ ድርድር ማድረግ አለብን›› ሲሉም አክለዋል፡፡   

የደብሩ አስተዳደር ይግባኝ ጠይቋል

       በአዲስ አበባ የካ ክፍለ ከተማ፣ ወረዳ 12 ውስጥ የምትገኘው፣ የየካ አባዶ ደብረ ልዕልና ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን፣ በሕገ ወጥ ይዞታ ላይ፣ ያለግንባታ ፈቃድ መሠራቷን የገለጸው ፍ/ቤት፣ እንድትፈርስ ወሰነ፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት፣ የካ ምድብ ችሎት፣ ባለፈው ረቡዕ በሰጠው ውሳኔ፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ እንዳትፈርስ በደብሩ ለቀረበው የ“ሁከት ይወገድልኝ” ክሥ፣ ኅዳር 28 ቀን 2009 ዓ.ም አስተላልፎት የነበረውን የእግድ ትእዛዝ ማንሣቱን አስታውቋል፡፡
በከሣሽ የደብረ ልዕልና ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያንና በተከሣሽ የወረዳው ደንብ ማስከበር ጽ/ቤት መካከል የቀረቡትን አቤቱታዎችና ሲካሔድ የቆየውን የቃል ክርክር መመርመሩን የገለጸው ፍ/ቤቱ፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ የተሠራችበትን ቤትና ቦታ፣ ከሰኔ 24 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ በስጦታ ያስተላለፉት ግለሰቦች፤ ይዞታውን በሕጋዊ አግባብ እንዳገኙት የሚያስረዳ ማስረጃ በከሣሽ በኩል አለመቅረቡን ጠቅሷል፡፡
ቤቱም፣ የሚመለከተው የከተማው አስተዳደር የግንባታ ፈቃድና ቁጥጥር ጽ/ቤት ፈቃድ ሰጥቶ ስለመሠራቱ ማስረጃ አለመቅረቡንና በመሥመር ካርታ ወይም በ1997 ዓ.ም የአየር ካርታ ላይ እንደማይታይ፣ የክፍለ ከተማው የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ጽ/ቤት ማረጋገጡን አስረድቷል፡፡
ለክሡ መነሻ የሆነው ቤት፣ የቤተ ክርስቲያን ቅርጽ እንዲኖረው ተደርጎ የተሠራውም፣ በሕግ ሥልጣን ከተሰጠው የከተማው አስተዳደር አካል፣ የግንባታ ፈቃድ ሳይገኝ መሆኑን በውሳኔው ጠቅሷል፡፡
የወረዳው ደንብ ማስከበር ጽ/ቤት፣ ቤተ ክርስቲያኒቱ እንድትፈርስ፣ ለደብሩ የሰጠው ማስጠንቀቂያ፣ በሕግ የተሰጠውን ሓላፊነት መወጣቱ እንጂ የሁከት ተግባር አይደለም፤ በደብሩ የቀረበውም ክሥ ተቀባይነት የለውም፤” ሲል ወስኗል፡፡ ለክሡ መነሻ በሆነው ግንባታ ላይ ቀደም ሲል ተላልፎ የነበረው የእግድ ትእዛዝ መነሣቱንም አስታውቋል፡፡  
በሌላ በኩል፣ የደብረ ልዕልና ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን አስተዳደር፣ የፍ/ቤቱን ውሳኔ በመቃወም ይግባኝ መጠየቁ ታውቋል፡፡  

  ሁለት ዳኞች አዲሱን የትራምፕ የጉዞ ገደብ አግደውታል

     ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ አሜሪካ በተባበሩት መንግስታት ድርጅትና በራሱ ለጋሽ ድርጅቶች በኩል ለአለማቀፍ እርዳታና ለልማት የምትሰጠውን የገንዘብ መጠን በ28 በመቶ ያህል ለመቀነስ የሚያስችል ምክረ ሃሳብ ማቅረባቸውን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ምክረ ሃሳቡ በኮንግረስ ተቀባይነት ካገኘ ኢትዮጵያን ጨምሮ ለበርካታ የአለማችን አገራት የልማት እርዳታ የሚያደርገው የዩኤስ አይዲ አመታዊ ድጋፍ በ28 በመቶ ያህል ይቀንሳል ያለው ዘገባው፤ በሌሎች ተቋማትና መስኮች የተያዙ በጀቶችም በከፍተኛ ሁኔታ ቀንሰው ብዙዎችን ተጎጂ እንደሚያደርጉ ገልጧል፡፡
አነጋጋሪ የሆነው የትራምፕ የበጀት ቅነሳ ምክረ ሃሳብ፣ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም በጀት በ31.4 በመቶ፣ የጤናና የሰብአዊ አገልግሎቶች በጀት በ16.2 በመቶ፣ የግብርና ዘርፍ በ21 በመቶ፣ የትራንስፖርት ዘርፍ በ13 በመቶ ቅነሳ እንዲደረግባቸው የሚጠይቅ መሆኑንም አስረድቷል፡፡
የትራምፕ የበጀት ቅነሳ ምክረ ሃሳብ ከፍተኛ ተቃውሞ ይገጥመዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የጠቆመው ዘገባው፤ ምክረ ሃሳቡ መከላከያን ጨምሮ በአንዳንድ ዘርፎች ከፍተኛ የበጀት ጭማሪ እንደሚያደርግ ገልጾ፣ ሃሳቡ ተቀባይነት ካገኘ የመከላከያ ወጪ በ10 በመቶ ወይም በ54 ቢሊዮን ዶላር እንደሚያድግ አብራርቷል፡፡
በተያያዘ ዜናም የሃዋይ እና የሜሪላንድ የፌዴራል ፍርድ ቤት ዳኞች ተሻሽሎ የወጣው የትራምፕ የጉዞ ገደብ ተፈጻሚ እንዳይሆን ማገዳቸው ተነግሯል። ዳኞቹ የስድስት አገራት ዜጎች ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ የሚከለክለውን አዲሱ የጉዞ ገደብ ትዕዛዝ ህጋዊነትም ሆነ አግባብነቱን የሚያረጋግጥ በቂ ማስረጃ የለውም በሚል እንዳይተገበር የሚያግድ ትዕዛዝ ማውጣታቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡

 ራፐሩ ስኑፕ ዶግ ትራምፕን ተኩሶ ሲገድላቸው የሚያሳይ ቪዲዮ ለቋል

      የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ የታንዛኒያውን አቻቸውን ጆን ማጉፋሊን በማድነቅ ሌሎች የአፍሪካ መሪዎችን አጣጣሉ የሚል ሃሰተኛ መረጃ ያሰራጩ ቲቢሲ የተሰኘው የታንዛኒያ የብሮድካስቲንግ ተቋም ባልደረቦች የሆኑ 9 ጋዜጠኞች ከስራ መታገዳቸው ተዘግቧል፡፡
ጋዜጠኞቹ “ትራምፕ ሙጉፋሊን የአፍሪካ ጀግና ሲሉ የአመራር ብቃታቸውን በማድነቅ አሞካሽተዋቸዋል፣ ሌሎች የአፍሪካ መሪዎች ግን አንዳች እንኳን ፋይዳ ያለው ነገር እየሰሩ አይደለም ሲሉ ተናግረዋል” የሚለውን ሃሰተኛ መረጃ በማሰራጨታቸው ከስራ መታገዳቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ትራምፕ የተቀሩት የአፍሪካ መሪዎች ከታንዛኒያው ፕሬዚዳንት ሙጉፋሊ ሊማሩ ይገባል ብለዋል በማለት ሃሰተኛ መረጃ ያሰራጩት ጋዜጠኞቹ፤ ከሙጉፋሊ ብቃቶች መካከል ሙስናን በመዋጋት ረገድ ያሳዩት ቁርጠኝነት አንዱ ነው ማለታቸውንም አትተዋል፡፡
በተያያዘ ዜና ደግሞ ታዋቂው ራፐር ስኑፕ ዶግ፤ ዶናልድ ትራምፕን ተኩሶ ሲገድላቸው የሚያሳይ የሙዚቃ ቪዲዮ ሰሞኑን መልቀቁን ተከትሎ፣ ፕሬዚዳንቱ “ስኑፕ ዶግ በዚህ አጉል ድርጊቱ ሳቢያ ሊታሰር ይገባል” ማለታቸው ተዘግቧል፡፡
ትራምፕ በትዊተር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ ስኑፕ ዶግ በቪዲዮው ሲገድል ያሳየው ኦባማን ቢሆን ኖሮ ወደ እስር ቤት ነበር የሚገባው ማለታቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ የትራምፕ የግል ጠበቃ ማይክል ኮሄን በበኩላቸው ቪዲዮውን ሲመለከቱ በእጅጉ መደንገጣቸውን በማስታወስ፣ ስኑፕ ዶግ ፕሬዚዳንቱን አዋርዷል ይቅርታ ሊጠይቃቸው ይገባል ማለታቸውን ገልጧል፡፡

  - ከ43 አመታት በፊት በፈጸመው ግድያ ተከስሶ ፍ/ ቤት ቀርቧል
                    - የእድሜ ልክ እስራት ተፈርዶበት ያለፉትን 23 አመታት በእስር አሳልፏል

      ካርሎስ ቀበሮው በሚል ስሙ የሚታወቀውና ከአለማችን ቀንደኛ ገዳዮች አንዱ እንደሆነ የሚነገርለት ኢሊች ራሚሬዝ ሳንቼዝ፣ እስር ቤት ከመግባቱ በፊት ብዙ ሰዎችን ባለመግደሉ እንደሚጸጸት፣ ከ43 አመታት በፊት በፓሪስ በሚገኝ የገበያ ማዕከል በተፈጸመ ወንጀል ተከስሶ ባለፈው ሰኞ ፍርድ ቤት በቀረበበት ወቅት መናገሩ ተዘገበ፡፡
እ.ኤ.አ በ1974 የተከሰተውንና 2 ሰዎች ለሞት፣ 34 ሰዎች ደግሞ ለመቁሰል አደጋ የተዳረጉበትን የቦምብ ጥቃት ፈጽሟል በሚል ፍርድ ቤት የቀረበው ካርሎስ፤ ከመታሰርህ በፊት በነበረህ የገዳይነት ህይወት ዘመንህ የምትጸጸትበት ነገር አለ? በሚል ከዳኛው የቀረበለትን ጥያቄ ሲመልስ፣ “አዎ… ልገድላቸው ሲገባኝ ያልገደልኳቸውን ሰዎች ሳስብ ይጸጽተኛል” ማለቱን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
የ67 አመቱ ካርሎስ፣ ባለፈው ሰኞ ፍርድ ቤት በቀረበበት ወቅት የሙያ መስክህ ምንድን ነው በሚል ከችሎቱ ለቀረበለት ጥያቄ፣ ብቁ አብዮተኛ ሲል ምላሽ ሰጥቷል፡፡ ዕድሜውን ሲጠየቅም፡- 17 ነው፤ ደስ ካላችሁ 50 አመት ጨምሩበት ሲል ያላገጠ ሲሆን  የተከሰሰበትን የወንጀል ድርጊት አለመፈጸሙን አስረድቷል፡፡
ካርሎስ ከ43 አመታት በኋላ የተከሰሰበትን የግድያ ወንጀል መፈጸሙን የሚያስረዱ 17 ያህል ምስክሮች በቀጣይ የምስክርነት ቃላቸውን እንደሚሰጡ የጠቆመው ዘገባው፤ የምስክሮችን ቃል የመስማቱ ሂደት በሁለት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ ይጠናቀቃል ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጧል፡፡
ከ23 አመታት በፊት በፈረንሳይ ልዩ ሃይል ክትትል በካርቱም በቁጥጥር ስር የዋለው ቬንዙዋላዊው አደገኛ ገዳይ ካርሎስ፤ በ1970 ዎቹ እና 80 ዎቹ በፈጸማቸውና ባስፈጸማቸው በርካታ የግድያ ወንጀሎች የእድሜ ልክ እስራት ተፈርዶበት ከዚያ ጊዜ አንስቶ በፈረንሳይ በእስር ላይ ይገኛል፡፡

የጋናው ፕሬዚዳንት ናና አኩፎ አዶ በአገሪቱ ታሪክ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሚኒስትሮችና ምክትል ሚኒስትሮች የተካተቱበትንና 110 ያህል ዕጩዎች የተካተቱበትን ዝርዝር ባለፈው ረዕቡ ይፋ ማድረጋቸው አነጋጋሪ መሆኑን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ፕሬዚዳንቱ ይፋ ባደረጉት የዕጩ ሚኒስትሮች ዝርዝር የኢንፎርሜሽን ሚኒስቴርን ጨምሮ አምስት ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች እያንዳንዳቸው ሶስት ምክትል ሚኒስትሮች እንደሚኖራቸው የተገለጸ ሲሆን  የአገሪቱ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች “አዲሱ ሹመት የህዝቡን ገንዘብ የሚበሉ ሆዳሞችን ቁጥር ከማብዛት ባለፈ ፋይዳ የለውም” ሲሉ ሃሳቡን ተችተውታል፡፡
በርካታ ጋናውያን ፕሬዚዳንቱ ይህን ያህል ቁጥር ያላቸው ሚኒስትሮችን በዕጩነት ማቅረባቸውን በተለያዩ ድረገጾች እያጣጣሉት እንደሚገኙ የጠቆመው ዘገባው፤ የአገሪቱ የኢንፎርሜሽን ሚኒስትር ሙስጠፋ ሃሚድ ግን፣ መንግስት በርካታ ሚኒስትሮችን መሾሙ የተያዘውን ሰፊ የልማት ዕቅድ በማስፈጸም ረገድ ትልቅ አቅም ይፈጥራልና ሊተች አይገባውም ብለዋል፡፡

Monday, 20 March 2017 00:00

መሙላት እና መጉደል

“መፅሐፍ ማንበብ ሙሉ ሰው ያደርጋል!”
                       ከሃምሌት

      መፅሐፍ አንብቦ የማያውቅ ሰው ሁሉ ይኼንን መፈክር እየተጋተ ይመላለሳል፡፡ ሙሉ ሰው ለመሆን የማይመኝ ማን አለ? … ሞልቶለት የማያውቅ ቢሆንም ሙሉ ሰው መሆንን ያልማል፡፡ ለመሆኑ መፅሐፍ … መፅሐፍ እየተባለ የሚጠራው ነገር በቅርፅ የተጠረዘ የወረቀት ክምር ከመሆን በዘለለ ይዘቱ ምንድነው? ብሎ የሚጠይቅ ይኖራል፡፡ ቅርፅ ላይ የመፅሐፉ ምንነት ትርጉም አሻሚ አይደለም፡፡ አወዛጋቢው የይዘት ጉዳይ ነው፡፡
መፅሐፍ አዟሪነት የስራ መደብ ነው፡፡ በዚህ የስራ መደብ የተሰማሩ ወጣቶች እንደ ታክሲ ተራ አስከባሪ የመፅሐፍት ተራራ ተሸክመው ወዲህ ወዲያ ይላሉ። ቀና ብዬ እንዳላያቸው ተጠንቅቄ አልፋቸዋለሁኝ። በአይኔ አይናቸውን ካየሁ የተሸከሙትን መሬት አስቀምጠው ጭቅጭቅ ይጀምሩኛል፡፡ “መርጠህ አንዱን ግዛ” ነው ጭቅጭቃቸው፡፡ የጭቅጭቃቸው ኃይል “መፅሐፍ ማንበብ ሙሉ ሰው ያደርጋል!” የሚለው መፈክር ነው፡፡ “መፅሐፍ መጥፎ ነው” ብሎ ሽንጡን ገትሮ የሚከራከር ማንም የለም፡፡
ማርያም ቤተ ክርስቲን ፊት ቆሞ በድፍረት “ማርያም አታማልድም!” ከማለት ያላነሰ ድፍረትና ጠብ አጫሪነት የተጠናወተው ብቻ ነው አፉን ሞልቶ “መፅሐፍ አያማልድም” ማለት የሚችለው፡፡
መፅሐፍትን ሳይሆን መፈክሩን ነው እኔ የምፈራው፡፡ ግን እየፈራሁም አሮጌ መፅሐፍት ተራ ኪሴ ከበድ ሲል እሄዳለሁኝ፡፡ ኪሴ ሲከብድ … አእምሮዬ የቀለለ ለምን እንደሚመስለኝ አይገባኝም።
ከብሔራዊ ትያትር ጀርባ … ከበድሉ ህንፃ ፊት ለፊት መደዳውን በትንንሽ አርከበ ሱቆች ውስጥ የተደረደሩ አሮጌ መፅሐፍ ሻጮች ይገኛሉ፡፡ … “መፅሐፍ ማንበብ ሙሉ ሰው ያደርጋል” የሚለው መፈክር የፈጠራቸው ነጋዴዎች ናቸው፡፡ ማንበቡ እንጂ ሙሉ ሰው የሚያደርገው ከመነበብ በፊት መፅሐፉን የሚፅፍ ስለማስፈለጉ ትንፍሽ የሚል አይገኝም፡፡ መፅሐፉን ለመፃፍ መጀመሪያ ሰውየው መሙላት ይኖርበታል፡፡ ከሙላቱ ቀንሶ ነው ወደ መፅሐፉ እውቀቱን የሚያፈሰው፡፡
ግዴለም! ለማንኛውም አሮጌ መጽሐፍት ተራ ኪሴ ሲሞላ ጎራ እላለሁኝ፡፡ አንዳንዴ እንደ ሴተኛ አዳሪ መንደር ይመስለኛል ቦታው፡፡ መስለው የታዩኝን ገልጬ ነግሬያቸው ግን አላውቅም፡፡ እደብቃቸዋለሁኝ፡፡ ምክኒያቱም መፅሐፍ ማንበብ ሙሉ ሰው ስለሚያደርግ ነው፡፡ መፅሐፍ ማንበብ ሙሉ ሰው የሚያደርግ ከሆነ ደግሞ መፅሐፍ አቅራቢውን በሴተኛ አዳሪ መመሰል … የጉድለት ሰባኪ መሆን ነው፡፡ ቅልብስ ስነ ልቦና አለው ይኼ ራሱ፡፡
ደንበኛ አለኝ፡፡ ገና ሲያየኝ ፈገግ ይላል፡፡ ከእኔ ኪስ ትንሽ ገንዘብ ተቀንሶ ወደሱ ኪስ እንደሚገባ እርግጠኛ ስለሆነ ነው ፈገግ የሚለው፡፡ አንዳንዴ ወደ እሱ ሱቅ ከመድረሴ በፊት … ደረሰልኝ ብሎ ለሀጩን እያዝረበረበ ሳለ ድንገት እጥፍ ብዬ ሌላ ነጋዴ ሱቅ ጥልቅ እላለሁኝ፡፡ በጠለቅሁበት መፅሐፍ ይቀርብልኛል፡፡ ያንንም ያንንም እያነሳ መጀመሪያ ይሰጠኛል፡፡ ምን አይነት መፅሐፍ እንደምፈልግ ለማወቅ ነው፡፡
በቀላሉ የሚገኙና በፍፁም የማይገኙ መፅሐፍትን አውቃለሁኝ፡፡ ለምሳሌ የኧርቪንግ ዋላስ መፅሐፍ ካልኩኝ በቀላሉ የሚገኝ መፅሐፍ ነው የጠራሁት፡፡ እንግሊዝኛ ማንበብ እንጂ ገና ማጣጣም ያልጀመረ አንባቢ ምርጫ ነው፡፡ ነጋዴው ደስ የሚለው ይኼን አይነቱ አንባቢ ነው፡፡ በቀላሉ ከደረደረው ክምር እየናደ፣ በዚህ መሰሉ መፅሐፍ ሊያጥለቀልቀው ይችላል፡፡
እኔ ግን ጨዋታ ሲያምረኝ እንደ ኧርቪንግ ዋላስ የመሰለ ቀላል ሚዛን ደራሲ እጠራለሁኝ፡፡ መፅሐፍቱን በእጄም በአገጬም በጥርሴም እንድነክስ አድርጎ ካዥጎደጎደብኝ በኋላ … በቀላሉ የማይገኝ የኧርቪንግ ዋላስን መጽሐፍ እጠራበታለሁኝ - “The Seventh Secret” የሚለውን ነው የፈለኩት እለዋለሁኝ፡፡ ድንገት ነጋዴው ኩምሽሽ ይላል። The Seventh Secret” በቀላሉ የማይገኝ ቀላል መፅሐፍ ነው፡፡ በከባድ ፍለጋ የሚገኝ የቀላል ሚዛን ደራሲ ስራ ነው፡፡ የነጋዴው አገጭ በተስፋ መቁረጥ ይንጠለጠላል፡፡ የተንጠለጠለውን አገጩን ትንሽ ተስፋ ሰጥቼ ሰብሰብ እንዲያደርግ እረዳዋለሁኝ፡፡
ኧርቪንግ ዋላስን ትቼ ኧርነስት ሄሚንግዌይን ስጠኝ እለዋለሁኝ፡፡ ሄሚንግዌይ የኖቤል ደራሲ ነው። ከባድ ሚዛን ነው፡፡ ግን ገበያ ላይ ይገኛል። ተንኮሉ ያለው የትኞቹ መጽሐፍቱ በገበያ ላይ እንደሚገኙ ማወቁ ላይ ነው፡፡ በህንዶች የታተመ “The Old Man and the Sea” መፅሐፍ እንደ አፈር ይገኛል፡፡ “The Snows of Kilimanjaro and other Stories” የሚለውም እንደ ቁንጫ ከሰው እጅ ወደ አሮጌ ተራ ሲፈናጠር ይገኛል፡፡
የማይገኘው የቱ እንደሆነ አውቃለሁኝ፡፡ ለምሳሌ፡- “For Whom the Bell Tolls” አይንህ እስኪፈስ፣ ጫማህ እስኪያልቅ ብትፈልግ አታገኘውም፡፡ እንዲያውም የአንድ ሰውን የአንባቢነት መፈተን የፈለገ የማይገኙ መፅሐፍት የት እና ማን ጋ ማግኘት እንደሚቻል በመጠየቅ ብቃቱን መፈተን ይቻላል፡፡ … ምናልባት መጽሐፍትን አድኖ ለማግኘት ብቁ ከሆነ ያደነውን አብስሎ መመገብ (ማንበብ) ላይከብደው ይችላል ተብሎ ይታሰባል፡፡
በዚህ ሁሉ ውስጥ ግን መፈክሯ “Operative phrase” ናት፡፡ መፈክሯ “መፅሐፍ ማንበብ ሙሉ ሰው ያደርጋል!” የምትለዋ መሆኗ እንዳትዘነጋ፡፡
የመፅሐፍቱን ሚዛን ከፍ እያደረኩ … ግን ከመደርደሪያው ላይ በቀላሉ አውርዶ “ይኼው!” እንዳይለኝ እየተጠበብኩ … ትንሽ ካንገላታሁት በኋላ … በተስፋ መቁረጥ ጭንቅላቴን ነቅንቄ ድንገት ከጠለቅሁበት ሱቅ እወጣለሁኝ፡፡ … መጽሐፍ ሸመታ የድርድር ጥበብ የሚንፀባረቅበት መድረከ ነው፡፡ ›
በድርድር ህግ፤ ቶሎ መስማማት የዋህነትን አመላካች ነው፡፡ ገንዘብ ከእኔ ኪስ በቀላሉ ወጥቶ ወደ መፅሐፍ ነጋዴው ኪስ ከገባ በጨዋታው ህግ ተሸናፊ ነኝ፡፡ ሞኝ፤ የዋህ እና ተሸናፊ ነው። ለመግዛት ወስኖ የመጣውን መፅሐፍ ከአንዱ ቢያገኝ እንኳን በአንዴ መግዛት የለበትም፡፡ ትንሽ ማልፋት አለበት። ሻጩም ገዥውም ትንሽ ላብ መጥረግ ይገባቸዋል። ይህ ደግሞ በግዢ እና ሽያጭ አለም ብቻ ሳይሆን በእንስሳትም ግዛት ተመሳሳይ ነው፡፡ አውሬም እኮ የቋመጠለትን በቀላሉ ካገኘ አቅሙን መፈተን ይሳነዋል፡፡ ይሰንፋል፡፡ ድመት አይጥን በቀላሉ ከያዘቻት በኋላ በአንዴ ወደ አፏ አትጨምራትም። ትጫወትባታለች፡፡ አቅሟን እንደ እስፖርት ለማሰልጠኛ ትጠቀምባታለች፡፡ ለቀቅ - ታደርጋትና ለማምለጥ ስትሞክር ዘላ ትይዛታለች፡፡
እኔ እያደረኩ ያለሁትም ተመሳሳይ ነው፡፡ የእኔን የመፅሐፍት እውቀት በሻጩ ላይ መሞከር አለብኝ። ሙከራዬን ደግሞ በተገቢው ሁኔታ አፀፋዊ ምላሽ የሚሰጥ ተፎካካሪ ካገኘሁ - አልፍቼ - እኔም ለፍቼ በመጨረሻ እገዛዋለሁኝ፡፡
ስለዚህ ተራ በተራ እፈትናቸዋለሁኝ፡፡ “የመጀመሪያውን እትም ካልሆነ አልፈልግም” ሁሉ ልላቸው እችላለሁኝ፤ በጨዋታው አስጨንቀው ሊረቱኝ እንደሆነ ከፈራሁኝ፡፡ ግን ሙሉ ጨዋታ ብቻም አይደለም አላማዬ፡፡ የእውነት የምፈልጋቸው መፅሐፍት አሉ፡፡ ለምሳሌ የቡካውስኪ ማንኛውንም መፅሐፍ ይዣለሁ የሚል ካገኘሁኝ … በአንድ አፍ መክፈሌ አይቀርም፡፡
ችግሩ መፅሐፉን ይቅርና ደራሲውን እንኳን ሰምተውት የሚያweቁ ገጥመውኝ አያውቁም፡፡ የደራሲውን ስም ከነገርኳቸው በኋላም ማስታወስ የቻሉ የሉም፡፡ ስለዚህ በስተመጨረሻ አሸናፊው እኔ እሆናለሁኝ፡፡ ማሸነፍ ማለት መሸነፍም ነው፡፡ ብር ሳላወጣ እንደ አመጣጤ መመለስ ማሸነፍ ከሆነ … “መፅሐፍት ማንበብ ሙሉ ሰው ያደርጋል›› በሚለው መፈክር አንፃር ደግሞ ተሸናፊ ነኝ፡፡
ምክኒያቱም፤ መጽሐፍ ተነቦ ወደ ሙሉ ሰውነት ከማደጉ በፊት ሙሉ አድራጊው መፅሐፍ መሸመት አለበት፡፡ ሳይሸመት የሚነበብ መፅሀፍ ገጥሞኝ አያውቅም፡፡ ተውሼ የማነበው መፅሐፍም… የሆነ ሰው ከሆነ ቦታ ገንዘቡን አውጥቶ የገዛው መሆኑ ግልፅ ነው፡፡
ደንበኛዬ ጋር የምደርሰው መጨረሻ ላይ ነው። እጄን ይመለከታል፡፡ መፅሐፍ ከሌሎቹ ገዝቻለሁ ወይንስ አልገዛሁም የሚለውን ለማረጋገጥ፡፡ መፅሐፍ ነጋዴ እንደ ሴተኛ አዳሪ ነው ያልኩት ለዚህ ነው፡፡ ከሌላ ሰው ከገዛሁ መፅሐፉን ነጥቆ ይመለከተዋል፡፡ ‹‹ምን አይነት መፅሐፍ ቢሆን ነው የገዛኸው?›› እንደ ማለት በቅናት ይመለከተዋል፡፡
ተመልክቶ ‹‹ልክ ነህ ይህ መፅሐፍ እኔ ጋ የለም›› ብሎ መልሶ አያውቅም፡፡ በቁጭት ‹‹እኔም ጋር እኮ ነበረ›› ይላል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ወደሱ ኪስ መግባት የነበረበት ሀብት ወደ ሌላ ባላንጣው መግባቱ ያበግነዋል፡፡ መብገኑ ያስደስተኛል፡፡ በጨዋታ ህግ ገዢ፣ ሻጭና ማብገን ከቻለ መጠነኛ ነጥብ ይቆጠርለታል፡፡
ያው ሴተኛ አዳሪዎች ‹‹ እሷ ላይ ከእኔ የተለየ ምን አይተህ ነው›› እንደሚሉት ነው ነገሩ፡፡ መፅሐፍ ሻጭም እንደ ዝሙት አዳሪ፣ የሚሸጠው መፅሐፍም በሴቶች ላይ የሚገኘውን ብልት ድንገት ተመሳስሎ ወይ የተመሳሰለ መስሎህ ታገኘዋለህ፡፡
ደንበኛዬ ጠባዬን ያውቃል… በቀላሉ ብር እንደማልሰጠው ከብዙ ተሞክሮ ጠንቅቆ አይቷል፡፡ ስለዚህ ጨዋታው ይከራል፡፡
‹‹ባለፈው አስመጣልኝ ያልከኝን ‹‹Holy blood, holy grail›› መፅሐፍ በስንት ልፋት አግኝቼልሀለሁ። እንዴት እንዳለፋችኝ አትጠይቀኝ›› ምናምን ይለኛል።
‹‹መች አስቀምጥልኝ አልኩህ›› ብዬ እሸመጥጠዋለሁኝ
እቺ እንኳን ተራ ማጭበርበር ናት፡፡ እሱ እየሣለ ይገዘታል፤ እኔ እሸመጥጣለሁኝ፡፡
መጨረሻ ላይ ሌላ ከባድ መፅሀፍ ያወጣል - ወይ የሩሶን ወይ የ‹‹MAUPASSANT››ን ሊሆን ይችላል። መፅሐፉ በሁሉም ደረጃ የእኔን ኪስ ገበብር ወደ ውጭ የሚለብጥ ነው፡፡ ከባድ ሚዛን ይዘት ያለው በከባድ ሚዛን ፈላስፋ የተፃፈ መሰረታዊ መፅሐፍ ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የትም ወድቆ የሚገኝ አይደለም፡፡ በአጭሩ በገፅ ሉኮች የተጠረዘ ወርቅ ነው፡፡
ግን እኔ ጨዋታ ውስጥ መሆኔን አልዘነጋም፤ በአንዴ አልዝረከረክም፡፡ በአድናቆ የአፌን በር ገርበብ አድርጌ አልከፍትም፡፡ ጨዋታ ውስጥ ነኝ፡፡
‹‹የእነዚህን የሞቱ የፈረንሳይ ፈላስፎች እና የ“Twist” ደራሲያን በቃ አትተውም… ደግሞ ሳልገዛው እቀራለሁ ብለህ ነው!... አዎ እንዲያውም ትዝ አለኝ፡፡ ገዝቼው ነበር … የሆነ ሰው አውሼው ሳይመልስልኝ ቀርቷል፡፡ ዋጋው ለመሆኑ ስንት ነው?››
ልክ ዋጋውን ስጠይቅ እየተሸነፍኩ እንደሆነ ያውቃል፡፡ ሸምቀቆውን ማጥበቅ ይጀምራል። ‹‹መቶ…ሃምሳ›› እላለሁኝ ‹‹ከሶስት መቶ ፈቅ አልልም›› ይላል፡፡ ‹‹በቃ ተወው እለዋለሁኝ››.. ወጣ እላለሁኝ፡፡… ጠርቶ ያመጣኛል፡፡ ሁለታችንም ህጉን ጠንቅቀን እናውቀዋለን፡፡ በቶሎ ‹‹በጄ›› ማለት መሸነፍ ነው፡፡ ጨዋታው አስፈላጊ ነው ወይ? ብዬ አንዳንዴ ራሴን በትዝብት እጠይቃለሁኝ፡፡ የቂል ጨዋታ ይሆንብኛል፡፡ ግን መፈክሩ ትዝ ይለኛል፡፡
“መፅሐፍ ማንበብ ሙሉ ሰው ያደርጋል”
በመፈክሩ እስማማለሁኝ፡፡ ከተስማማሁኝ ደግሞ ለስምምነቴ ዋጋ መክፈል አለብኝ፡፡ ግን ጀማሪ አይደለሁም፡፡ የመፈክሩን ትርጉም እኔ የምረዳበትና ሌላው ተራ የመፅሐፍ ሸማች የሚመነዝርበት የአረዳድ መንገድ ለየቅል ነው። እኔ መፅሐፉን በቅርፁ ብቻ ሳይሆን በይዘቱም እለካዋለሁኝ፡፡ ለመፅሐፍ ብዙ ብር የሚከፍል ሰው ለከፈለበት ምክኒያቱን ሲጠየቅ “ክብሩን ለመግለፅ” እንደሆነ ደረቱን ነፍቶ ይናገራል። ግን ደረቱን ነፍቶ እየተናገረ ያለው የምርጥ ነገሮችን ዋጋ ስላለማወቁ እና አለማወቁን ደግሞ በገንዘብ ሸፋፍኖ ለማለፍ ስለመሞከሩ ብቻ ነው፡፡
... ከብዙ ክርክር በኋላ መጀመሪያ የተጠራው ዋጋን በሚያሸማቅቅ ያሽቆለቆለ ተመን የፈለኩትን ገዝቼ እንደ አመጣጤ ወደምሄድበት እቀየሳለሁኝ፡፡
የምርጥ ነገሮች ዋጋ በመሰረቱ “ምንም” ነው። እውቀትና የፀሐይ ብርሐን የማንም አይደሉም፡፡ መፅሐፍ ሻጭ መሀል ቤት ተቀምጦ ሊደልልባቸው አይገባም፡፡ ስለማይገባ ግን አይችልም ማለት አይደለም፡፡ የድርድሩ ህግ ያስፈለገው ለዚህ ነው። “መፅሐፍ ማንበብ ሙሉ ሰው ያደርጋል” ሙሉ ለመሆን ሲባል ኪስን ያለአግባብ ማጉደል ግን ተገቢ አይደለም፡፡ 

የፕሮፌሰር ማይክል ጄ. ሳንደልን “What Money Can’t Buy” የተሰኘ መጽሐፍ ተርጓሚ አካለወልድ ተሰማ “ዋጋችን ስንት ነው” በሚል ርዕስ ወደ አማርኛ መልሶት ለንባብ የበቃ ሲሆን መፅሐፉ ዛሬ ከረፋዱ 4፡00 ጀምሮ ቦሌ በሚገኘው ራማዳ አዲስ ሆቴል ይመረቃል፡፡ ዶ/ር ጠና ደዎ፣ ዶ/ር ዘሪሁን ሙላቱና መጋቢ ሀዲስ እሸቱ አለማየሁ በመፅሐፉ ላይ ዳሰሳዊ ጥናት እንደሚያቀርቡም ታውቋል፡፡ በገበያ ግብረ ገብነትና ከግብረ ገብነት ውጭ በሚደረጉ የሀብት መሰብሰብ ሩጫዎች ላይ የሚያጠነጥነው መፅሐፉ፤በአምስት ምዕራፎች ተከፋፍሎ በ203 ገጾች የተቀነበበ ሲሆን በ50 ብር ከ70 ሳንቲም እየተሸጠ ነው፡፡

 ከአሜሪካ የመጣው ኬግዊን ፕላስ ካምፓኒ የዳንስ ቡድንና የተለያዩ የኢትዮጵያ የዳንስ ቡድኖች የተሳተፉበት “ኑ እንደንስ” የዳንስ ትርኢት ባለፈው ሳምንት አጋማሽ በብሄራዊ ቴአትር አዳራሽ ተካሄደ። በዳንስ ሞሽን ዩኤስኤ በቀረበውና የአሜሪካ ኤምባሲ ባስተባበረው በዚህ የዳንስ ትርኢት ላይ ከአሜሪካው “ኬግዊን” የዳንስ ቡድን በተጨማሪ “ኢትዮጵያዊነት”፣ “ሚዩዚክ ሜይዴይ”፣ “ሀሁ” እና ሌሎችም የዳንስ ቡድኖች ስራዎቻቸውን
አቅርበውበታል፡፡ በትርኢቱ ላይ ባህላዊ፣ ዘመናዊና የፍቅር ዳንሶች ለታዳሚው የቀረቡ ሲሆን በመጨረሻም ሁሉም የዳንስ ቡድኖች በጋራ በመደነስ ትርኢቱ ተጠናቀቋል፡፡