Administrator

Administrator

   ሀገራችን ኢትዮጵያ ባለፉት ዘመናት አያሌ የቅኝ ግዛት ወረራዎች ሙከራ ቢደረግባትም አያት ቅድመ አያቶቻችን ባደረጉት ተጋድሎ፣ታፍራ የተከበረች ኢትዮጵያን ተረክበናል፡፡ ከእነዚያ አኩሪ ድሎች ውስጥ አንዱ ሆኖ ለአፍሪካውያን ጸረ ቅኝ ግዛት እንቅስቃሴ በአርአያነት የሚጠቀሰው የአድዋ ጦርነት ነው፡፡ ጣልያኖች እጅግ ዘመናዊና የሰለጠነ ጦር እየመሩ ቢመጡም በዳግማዊ ሚኒሊክ የሚመራውና ከአልደፈርም ባይነት ወኔ በቀር ዘመናዊ ሊባል የሚችል ጦር መሳሪያ ያላነገበው የኢትዮጵያ ሰራዊት፣ጣልያኖችን አይቀጡ ቅጣት እየቀጣ ጦርነቱን በድል አጠናቋል፡፡
እንደምናውቀው ከቅኝ ግዛት ማክተም በኋላ ምዕራባውያን ሀገራት ከአፍሪካውያን ጋር ልዩ ልዩ የዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቶችን በመፍጠር ለሀገራቸው ገጽታ ግንባታ ጠቃሚ ነው ብለው የሚያምኑትን ተግባራት ያከናውናሉ፡፡ በትምህርት፣ በጤና፣ በኢኮኖሚ፣ በባህልና ወታደራዊ ትብብሮች ይሳተፋሉ፡፡
ዛሬ የትምህርት ትብብር ላይ እናተኩርና ሀገራችን ኢትዮጵያ ውስጥ ከቅኝ ግዛት ማክተም በኋላ ብዛት ያላቸው ኢንተርናሽናል ኮሚዩኒቲ ት/ቤቶች ተከፍተዋል፡፡
የአሜሪካን አይ ሲ ኤስ፣ የእንግሊዙ ሳንድ ፎርድ፣ የፈረንሳዩ ሊሴ ገ.ማርያም፣ የጀርመኑ ጎቴ ኢንስቲትዩት እንዲሁም የጣልያን ት/ቤት ይጠቀሳሉ፡፡ እነዚህ ት/ቤቶች ከትምህርት ሚኒስቴር ጋር ባላቸው ስምምነት፣ በሀገራቸው የትምህርት ስርአት መሰረት ትምህርት የሚሰጡ ቢሆንም በሀገሪቱ ካሌንደር  የሚከበሩ ሀገራዊም ሆነ ሀይማኖታዊ በአላትን የማክበር ግዴታ ይኖርባቸዋል ብዬ አምናለሁ፡፡ መሬቱ የኢትዮጵያ ነውና፡፡ አለም አቀፍ ተቋማትና የውጭ ድርጅቶችም የኢትዮጵያን ሀገራዊ በዓላት ማክበር ይጠበቅባቸዋል! በዚህ መሰረት አብላጫዎቹ ኤምባሲዎችና ት/ቤቶቻቸው በዓላትን ያከብራሉ! ት/ቤቶቻቸውን ይዘጋሉ፡፡ ያም ሆኖ፤ የኢጣልያን ኮሙኒቲ ት/ቤት፣ የአድዋ ድል በዓል በሚከበርበት የካቲት 23 አንድም ቀን ዘግቶ እንደማያውቅ፣ እንዲሁም ከሌላው ቀን በተለየ በዚያ እለት ከት/ቤት የቀረ ተማሪን የተለየ ቅጣት እንደሚቀጣ አንድ ልጁን እዚያ የሚያስተምር ወዳጄ ቢነግረኝ፣ጉዳዩ ከንክኖኝ ነው ይህን ትዝብት ለመጻፍ የተገደድኩት፡፡
ኧረ ለመሆኑ የኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት ይሄንን ያውቁ ይሆን? እነዚህ ሰዎች እኮ ያንን ለአፍሪካውያን ምሳሌ የሆነውን ታላቅ ድል በዘመናት ሂደት ከኢትዮጵያውያን አእምሮ ውስጥ አደብዝዞ ለማጥፋት ተግተው እየሰሩ ነው ለማለት ይቻላል፡፡ በቅርቡ 75ኛ ዓመት የድል በዓል አራት ኪሎ አደባባይ ላይ በተከበረበት ወቅት የኢጣልያ አምባሳደር ተገኝተው ይህንኑ ሀሳብ ሲያጠናክሩ በጆሮዬ ሰምቻለሁ፡፡ ጎበዝ … የጀግንነታችን አሻራ ያረፈበት አኩሪ የድል ቀናችንን ጣልያኖቹ ሲክዱትና ሲያናንቁት መመልከት ለማንም ኢትዮጵያዊ የማይዋጥና የሚያንገበግብ በመሆኑ፣የሚመለከተው የመንግስት አካል ጉዳዩን በቸልታ ሊያየው አይገባም እላለሁ፡፡ ልብ ያለው ልብ ይበል ነው ነገሩ፡፡
-ከሙሉጌታ ጅኒ

ምክንያቱና ሰበቡ ምንድነው?

    በእንግሊዝ ፓርላማ ከ99% በላይ መቀመጫ በመያዝ የሚታወቁ አራቱ አውራ ፓርቲዎች፤ ለወትሮው በአይነ ቁራኛ የሚተያዩ ብርቱ ተፎካካሪዎች ናቸው፡፡ በትናንቱ ምርጫ ግን እርስ በርስ አልተፎካከሩም፡፡ ያለወትሯቸው ለአንድ ዓላማ በጋራ ለሁለት ወራት ቀስቅሰዋል፣ “እንግሊዝ ከአውሮፓ ህብረት አባልነት መፈናቀል የለባትም” በማለት፡፡
የገዢ እና የተቃዋሚ ፓርቲ ዋና ዋና መሪዎች፣ እንዲህ ተባብረው ቢቀሰቅሱም፣ አልተሳካላቸውም፡፡ አብዛኛው እንግሊዛዊ፣ የመሪዎቹን ቅስቀሳና ማስጠንቀቂያ ወደ ጎን ትቶ፤ በትናንቱ ምርጫ፣ “ከአውሮፓ ህብረት ለመገላገል” ወስኗል - 51 በመቶ ያህሉ መራጭ፡፡
ዋና ዋናዎቹ የፓርቲ መሪዎች ብቻ አይደሉም የተሸነፉት፡፡ የእንግሊዝ ብሄራዊ ባንክ፣ የአውሮፓ ህብረት ፕሬዚዳንት፣ የዓለም ገንዘብ ድርጅት … የማስጠንቀቂያ መዓት ሲያዥጎደጉዱ ከርመዋል፡፡ እንግሊዝ ከአውሮፓ ህብረት አባልነት ከለቀቀች፣ ኢኮኖሚዋ በ6% ያሽቆለቁላል፤ ፓውንስ ስተርሊንግ ይረክሳል፤ ዋጋ ይንራል፤ የዜጎች ገቢ በ3ሺ ዶላር ይቀንሳል … ማስፈራሪያው ስፍር ቁጥር የለውም፡፡
ከአውሮፓ አንጋፋ መሪዎች በተጨማሪ፣ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማም፣ እንግሊዛውያንን አስፈራርተዋል፡፡ “በንግድና በኢንቨስትመንት ዙሪያ፣ ቅድሚያ ሰጥተን የምንደራደረው ከአውሮፓ ህብረት ጋር ነው፤ እንግሊዝ ከህብረቱ ከወጣች ውራ ትሆናለች” ሲሉ አስጠንቅቀዋል ኦባማ፡፡
ይሄ ሁሉ የማስፈራሪያ ውርጅብኝ ውጤት አላስገኘም፡፡ በተለይ ደግሞ፤ የአገሪቱ አንጋፋ ፓርቲዎችና ዋና ዋና መሪዎች፣ እንዲህ ተሰሚነት ማጣታቸው አስገራሚ ነው፡፡ እነማን እንዳሸነፉ ደግሞ ተመልከቱ፡፡ ከኮንሰርቫቲቭ ፓርቲ ያፈነገጡ የተወሰኑ ፖለቲከኞች፣ እንዲሁም  ለዓመታት በፓርላማ አንዲት ወንበር ለማግኘት ያቃተው ፓርቲ… እነዚህ ናቸው “ከአውሮፓ ህብረት መገላገል አለብን” በማለት ሲቀሰቅሱ የነበሩት፡፡ እናም፣ ነባሮቹ አውራ ፓርቲዎችና መሪዎች ተሸንፈው፣ ድል የአፈንጋጮች ሆነ፡፡
በምርጫው ሽንፈት ማግስት፣ ዳቪድ ካሜሮን፣ ከጠቅላይ ሚንስትርነት እና ከኮንሰርቫቲቭ ፓርቲ መሪነት ለመልቀቅ ተገደዋል፡፡
ተቃዋሚያቸው የሌበር ፓርቲ መሪም፣ ከሃላፊነታቸው እንዲወርዱ፣ ከራሳቸው ፓርቲ ፖለቲከኞች ጥያቄ ተነስቶባቸው፣ አፋፍ ላይ ደርሰዋል፡፡
ይበልጥ አስገራሚ የሚሆነው ግን፤ ሌሎች የአውሮፓ አገራትም በተመሳሳይ አስደንጋጭ ማዕበል እየተናጡ መሆናቸው ነው፡፡ ባለፈው ሳምንት፣ በጣሊያን ከተሞች በተካሄዱ ምርጫዎች፤ በተለይ በዋና ከተማዋ በሮም እንዲሁም በቱሪን፣ ነባሮቹ ፓርቲዎች አሸናፊ አልሆኑም፡፡ እስከዛሬ ስልጣን በወጉ ያልቀመሰ ፓርቲ ነው ገንኖ የወጣው፡፡
ይህም ብቻ አይደለም፡፡ በኦስትሪያ ለ60 ዓመታት ስልጣን ላይ ሲፈራረቁ የነበሩ ሁለት ነባር ፓርቲዎችም፣ ተዘርረዋል፡፡ ከስድስት ዓመት በፊት በተካሄደ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ላይ፣ የሁለቱ ነባር ፓርቲዎች ድርሻ 80% ያህል ነበር፡፡ ባለፈው ወር በተካሄደው ተመሳሳይ ምርጫ ግን፣ ነገሩ የተገላቢጦሽ ሆኗል፡፡ የሁለቱ ነባር ፓርቲዎች ድርሻ ቁልቁል ወርዶ ተፈጥፍጧል፡፡ ከ11% የበለጠ ድምፅ ስላላገኙ፣ በማጣሪያው ከምርጫ ተሰናብተዋል፡፡
በተቃራኒው ስልጣን ቀምሰው የማያውቁ … በጭራሽ ከስልጣን አጠገብ ደርሰው የማያውቁ … በአንድ ወገን ከኢንቨስትመንት ይልቅ ድጎማን የሚያወድሱ የሶሻሊዝም ግርፍ፣ በሌላ ወገን ደግሞ ዘረኝነትን የሚያናፍሱ የፋሺዝም ግርፍ ፖለቲከኞች ከፍተኛ ብልጫ አግኝተዋል፡፡
በግሪክም፣ ነባሮቹ ፓርቲዎች ተሸንፈው፣ የሶሻሊዝም አራጋቢዎች ስልጣን ይዘዋል፡፡ በስፔንም እንዲሁ፣ አምስት ዓመት ያልሞላቸው ፓርቲዎች፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ በመግነናቸው፣ ነባሮቹ ፓርቲዎች፣ የፓርላማ አብላጫ ወንበር መያዝ አልቻሉም፡፡ ምን ይሄ ብቻ! የአየርላንድ ነባር ፓርቲዎች፣ ተመሳሳይ ፅዋ ተጎንጭተዋል፡፡ ፊንላንድና ዴንማርክም እንዲሁ፣ ነባር ፓርቲዎችን በሚያናጋ ማዕበል ተመትተዋል፡፡ በጀርመን ዘንድሮ በተካሄደ የክልሎች ምርጫ፣ ከአምስት ዓመት በፊት ያልነበረ አዲስ ፓርቲ፣ ከነባሮቹ የበለጠ ድምፅ ሲያገኝ ታይቷል፡፡ በፈረንሳይም እንዲሁ፡፡ ….
እንደ ነባሮቹ ፓርቲዎች ሁሉ፣ ነባሩ የኢኮኖሚ ስርዓትም እየተንገራገጨ ነው፡፡ መንግስታት በየጊዜው የድጎማ መዓት ይፈለፍላሉ፡፡ ከዜጎች ገቢ ግማሽ ያህሉን ታክስ እየቆረጡ ይወስዳሉ፡፡  ይህም  አልበቃቸውም፡፡ መረን የተለቀቀ ወጪያቸውን ለመሸፈን፣ መንግስታት በትሪሊዮን ዶላሮች ብድር ተዘፍቀዋል፡፡ እንዲህ በመንግስታት ጣልቃ ገብነት የተቀየጠው የአውሮፓ የኢኮኖሚ ስርዓት፣ ከቀውስ መውጣት አቅቶታል፡፡ ከመንፏቀቅ ያለፈ እድገት ማስመዝገብ ተስኖታል፡፡ስራ አጥነት፣ ከ10% በታች አልወርድ ብሏል፡፡
ነባሮቹ ፓርቲዎች፣ ቅይጥ ኢኮኖሚያቸውን ለማሻሻልና የነፃ ገበያ ስርዓትን ለማስፋፋት አልቻሉም፡፡ ተሰሚነታቸውም ከኢኮኖሚው ጋር ተዳክሟል፡፡
ችግሩ ምንድነው? በነባሮቹ ምትክ፣ በምድረ አውሮፓ እየገነኑ የመጡ ብዙዎቹ ፖለቲከኞችና ፓርቲዎች፣ ከቀድሞዎቹ የባሱ እንጂ የተሻሉ አይደሉም፡፡ በተጨማሪ የታክስ ጫናና በተጨማሪ የድጎማ ብክነት፣ ኢኮኖሚን የሚያዳክሙ የሶሻሊዝምና የፋሺዝም ግርፍ ናቸው - እንደ አሜሪካውያኑ በርኒ ሰንደርስ እና እንደ ዶናልድ ትራምፕ፡፡

ኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ፌ ስቡክ የሰመረላቸው የመንግስት ባ ለስልጣናትና ተ ቋማት ጥ ቂት ናቸው ብሏል

   ኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር በኢትዮጵያውያን የፌስቡክ ማህበራዊ ድረገጽ ተጠቃሚዎች ላይ ባደረገው የናሙና ጥናት፣ ኢትዮጵያውያን በፌስቡክ በኩል የሚያስተላልፏቸው የጥላቻ መልዕክቶችና አስተያየቶች መጠን፣ ከተጠቃሚዎች ብዛት አንጻር እጅግ አነስተኛ ሆኖ እንዳገኘው አስታወቀ፡፡
ዩኒቨርሲቲው የኢትዮጵያውያንን የፌስቡክ አጠቃቀም በተመለከተ ለሁለት አመት ያህል ያከናወነውና ሰሞኑን ይፋ ያደረገው “መቻቻል” የተሰኘ ርዕስ ያለው ይህ ጥናት፤ በናሙናነት ከተወሰዱት የፌስቡክ ተጠቃሚዎች አስተያየቶች መካከል ብሄርን፣ ዜግነትን፣ ሃይማኖትን ወይም ጾታን መሰረት በማድረግ ግለሰቦችን ወይም ቡድኖችን የሚያገልሉ የጥላቻ መልዕክት ያዘሉት 0.7 በመቶ ያህሉ ብቻ እንደሆኑ ገልጿል፡፡
በ2007 ዓ.ም ከየካቲት እስከ ሃምሌ በነበሩት ወራት ኢትዮጵያውያን የፌስቡክ ተጠቃሚዎች ከሰጧቸው አስተያየቶችና መልዕክቶች ውስጥ 13 ሺህ ያህሉን በናሙናነት ወስዶ የተነተነው ጥናቱ፣ አደገኛ ወይም ጠብ አጫሪ ተብለው ከተመደቡት የፌስቡክ አስተያየቶችና መልዕክቶች መካከል 21.8 በመቶ የሚሆኑት የፖለቲካ ልዩነቶችን መሰረት ያደረጉ እንደሆኑና ሃይማኖትና ብሄር 10 በመቶ እና 14 በመቶ ያህል ድርሻ እንዳላቸውም ገልጧል፡፡
በጥናቱ የጥላቻ አስተያየቶችንና መልዕክቶችን አስተላልፈዋል ከተባሉት ኢትዮጵያውያን የፌስቡክ ተጠቃሚዎች መካከል 92 በመቶ ያህሉ፣ ትክክለኛ ማንነታቸውን ደብቀው በሃሰተኛ የፌስቡክ ስም የሚጠቀሙ እንደሆኑ ተጠቁሟል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናትና የመንግስት ተቋማት ፌስቡክን እንደ አንድ የመረጃ ማሰራጫ መንገድ ለመጠቀም ሙከራ እያደረጉ ነው ያለው ጥናቱ፤ ይሄም ሆኖ ግን ተጽዕኖ መፍጠርና ተሰሚነት ማግኘት የቻሉት በጣም አነስተኛ ናቸው ብሏል፡፡
ኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ያከናወነው ይህ ጥናት፤ ከ2007 የካቲት እስከ ሃምሌ ባሉት ወራት፣ በ1ሺህ 55 የፌስቡክ ገጾች ላይ የተሰጡ ከ13 ሺህ በላይ አስተያየቶችና መልዕክቶችን በናሙናነት ወስዶ መተንተኑ ተገልጧል፡፡

     ከብራዚልና ከሜክሲኮ ዋና ከተሞች፣ ከካልታና ከኢዝላማባድ … ከሃጋሪና ከፖላንድ እንዲሁም ከዩክሬንና ከማሌዥያ ዋና ከተሞች ይልቅ፣ የአዲስ አበባ የኑሮ ውድነት ይከፋል፡፡ ከካናዳ ኦታዋ እና ጊታሞና ሞንትሪያል፤ ከጀርመን ሊፕዚግ እና ኑርንበርግ ከተሞች ጋር ሊነፃፀርም፣ የኑሮ ውድነት በአዲስ አበባ ይከብዳል፡፡ ሜርሰር የተባለው አለማቀፍ የጥናት ተቋም ከትናንት በስቲያ ይፋ ባደረገው አመታዊው የዓለማችን ከተሞች የኑሮ ውድነት ደረጃ፣ መዲናችን አዲስ አበባ 143ኛ ደረጃን መያዟን አስታወቀ፡፡
ተቋሙ ለ22ኛ ጊዜ በ209 የዓለማችን አገራት ላይ ባደረገው የዳሰሳ ጥናት ላይ ተመስርቶ ይፋ ያደረገው የዘንድሮ ሪፖርት እንደሚለው፣ በአለማችን ከሚገኙ ከተሞች ለመኖር ከፍተኛ ወጪን በመጠየቅ ቀዳሚውን ስፍራ የያዘቺው ሆንግ ኮንግ ስትሆን የአንጎላ መዲና ሉዋንዳና የስዊዘርላንዷ ዙሪክ ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል፡፡
ዝቅተኛ ወጪን የሚጠይቁ የዓለማችን ከተሞች ተብለው የተዘረዘሩት ደግሞ የናሚቢያዋ ዊንድሆክ፣ የደቡብ አፍሪካዋ ኬፕታውንና የካይሬጊስታኗ ቢሽኬክ ሲሆኑ በአፍሪካ አህጉር ከሚገኙ ከተሞች የአንጎላ ዋና ከተማ ሉዋንዳ ከፍተኛ የኑሮ ውድነት ያለባት ከተማ ናት ያለው ሪፖርቱ፤ የኮንጎዋ ኪንሻሳና የቻድ ርዕሰ ከተማ ጃሜና ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃን መያዛቸውን አብራርቷል፡፡
ተቋሙ የከተሞችን የመኖሪያ ቤት፣ የትራንስፖርት፣ የምግብ፣ የአልባሳትና የመሳሰሉትን ከ200 በላይ የሚሆኑ ምርቶችና አገልግሎቶች ዋጋ እና ሌሎች ተያያዥ የፋይናንስ ሁኔታዎችን በመገምገም የየከተሞችን የኑሮ ውድነት ደረጃ ማውጣቱን አስታውቋል፡፡

የቴሌቪዥን ጣቢያ ስርጭት እንዲቋረጥ አድርጓል ተብሏል
የኢትዮጵያ መንግስት ባለፈው ሰኞ ዋጃሌ በተባለቺው የኢትዮ-ሶማሊላንድ የድንበር ከተማ አምስት የሶማሊላንድ ጋዜጠኞችን በቁጥጥር ስር አውሎ ማሰሩንና አራቱ ከቆይታ በኋላ ሲለቀቁ አንደኛው አሁንም በእስር ላይ እንደሚገኝ ዳስላን ሬዲዮ ከትናንት በስቲያ ዘገበ፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት ጋዜጠኞቹን ከማሰር ባለፈ፣ ሆርን ኬብል የተባለው የቴሌቪዥን ጣቢያ በቅርቡ ያስተላለፈው ዘገባ ተገቢ አይደለም በሚል ታይኮም ለተባለው የሳተላይት ተቋም ባቀረበው ቅሬታ፤ጣቢያው በአካባቢው ያሰራጭ የነበረው ፕሮግራም እንዲቋረጥ ማድረጉንም ሶማሊላንድ ኢንፎርመር ዘግቧል፡፡
ጋዜጠኞቹ በዋጃሌ ከተማ በተዘጋጀ ሃሰተኛ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንዲገኙ ከተጋበዙ በኋላ በመንግስት ልዩ ሃይል ፖሊሶች በቁጥጥር ስር መዋላቸውንና ወደ ጂግጂጋ ከተማ ተወስደው እንደታሰሩ የጠቆመው ዘገባው፣ አራቱ ሲፈቱ ሆርን ኬብል ቲቪ የተባለው የሶማሊላንድ የሳተላይት ቴሌቪዥን ጣቢያ ባልደረባ፣ጋዜጠኛ ሙክታር ኑር ግን አሁንም በኢትዮጵያ መንግስት ቁጥጥር ስር እንደሚገኝ አመልክቷል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት ጋዜጠኞችን ያሰረበት ምክንያት ግልጽ አይደለም ያለው ዘገባው፤ሶማሊላንድና ኢትዮጵያ ጋዜጠኞችን በማሰር ረገድ ተባብረው ሲሰሩ እንደነበርና ከዚህ ቀደም በተመሳሳይ ሁኔታ የታሰሩ የአገሪቱ ጋዜጠኞች በሃርጌሳ በፍርድ ሂደት ላይ መሆናቸውን ጠቁሞ ሌሎች ጋዜጠኞችም በኢትዮጵያ በእስር ላይ እንደሚገኙ አስታውሷል፡፡የሶማሊላንድ ጋዜጠኞች ማህበር፣ ናሽናል ዩኒየን ፎር ሶማሊ ጆርናሊስትስ እና ሶማሊ ኢንዲፔንደንት ሚዲያ ሃውስስ አሶሴሽን የተባሉት የጋዜጠኞች ማህበራት፣ድርጊቱን የፕሬስ ነጻነት ጥሰት ነው በማለት ያወገዙት ሲሆን በእስር ላይ የሚገኘው ጋዜጠኛ ሙክታር ኑር፣ በአፋጣኝ ከእስር እንዲለቀቅ ጠይቀዋል፡፡

“ከ7 ወር በኋላ ከድርቅና ተረጂነት ዜጎች ይላቀቃሉ” መንግስት

   የበልግና የክረምቱ ዝናብ በአግባቡ ጥቅም ላይ የሚውል ከሆነ በድርቅ የተጎዱ ዜጎች በመጪው ጥር 2009 ዓ.ም ሙሉ ለሙሉ ከተረጂነት ይላቀቃሉ የተባለ ሲሆን በግብርና ላይ የሚሰሩ አለማቀፍ ተቋማት በበኩላቸው፤ መንግስት ለግብርናው በቂ ዝግጅት አላደረጉም ብለዋል፡፡
በሀገሪቱ የክረምቱ ዝናብ በሚፈለገው መጠን እየዘነበ መሆኑን የጠቀሰው በአፍሪካ ግብርና ላይ ትኩረቱን ያደረገው የአርካ አረንጓዴ አብዮት ጥምረት የተሰኘው ተቋም፤ መንግስት እርዳታ በማቅረብ ላይ ብቻ በመጠመዱ የዘር አቅርቦቱን ቸል ብሎታል ብሏል፡፡ የዘር አቅርቦቱ እጥረት እያጋጠመው ነው ያለው ተቋሙ፤ ይህም የድርቁን ችግር ሊያራዝመው ይችላል ብሏል፡፡
የብሄራዊ አደጋ መከላከል ኮሚሽን ኮሚሽነር በበኩሉ፤ ከ7 ወር በኋላ ሀገሪቱ ሙሉ ለሙሉ ከድርቅ ተረጂነት ትላቀቃለች ተብሎ እንደሚጠበቅና የድርቁን ወቅታዊ ችግርና የተረጅዎችን ሁኔታ የሚያጠና ቡድን ወደየአካባቢዎቹ መላኩን ጠቁመዋል፡፡
“እስካሁን የድርቅ ተረጂዎች ቁጥር ከ10.2 ሚሊዮን አልዘለለም” ያሉት ኮሚሽነር ምትኩ ካሣ፤ የበልጉ ዝናብ ምን ያህል ተረጅዎችን ከተረጅነት አላቀቀ የሚለውን ቡድኑ ካጠና በኋላ የተረጂዎች ቁጥር አሁን ካለበት ሊቀንስ ይችላል ብለዋል፡፡ የበልግና የክረምቱን ዝናብ በአግባቡ ተጠቅሞ የሚሰራው ስራ ቀጣዩን ሁኔታ ይወስነዋል ያሉት ኮሚሽነሩ፤ ወደ 15 ሚሊዮን ያሻቅባል ተብሎ የተሰጋው ግን እስካሁን አልደረሰም ብለዋል፡፡
የመንግስት ሙሉ ትኩረት የእርዳታ ስራው ላይ መሆኑ የተገኘውን ዝናብ በአግባቡ በመጠቀም ረገድ ክፍተት እየፈጠረ ነው ያለው የአፍሪካ አረንጓዴ አብዮት ጥምረት በበኩሉ፤ ዝናቡ ትርጉም የሚኖረው አርሶ አደሮች በቂ ዝግጅት ሲያደርጉ ነው፤ ይህ ደግሞ አሁን ባለው ሁኔታ እየተስተዋለ አይደለም ብሏል፡፡
የእርሻና ተፈጥሮ ሃብት ሚኒስቴር በበኩሉ፤ የክረምቱን ዝናብ ለመጠቀም “በዘር ሳይሸፈን የሚቀር መሬት መኖር የለበትም” በሚል አቋም፤ የዘር አቅርቦቱን ባለው አቅም ሁሉ እያቀረበ መሆኑን እምብዛም እጥረት ሊያጋጥም አይችልም ብሏል፡፡

   ሞሓ የለስላሳ መጠጦች ፋብሪካ፣ ለመቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከል አንድ ሚሊዮን ብር ግምት ያለው ሁለተኛ አምቡላንስ በዕርዳታ ሰጠ፡፡ ርክክቡ የተከናወነው መንግሥት ለመቄዶንያ በነፃ በሰጠውና አያት ኮንዶሚኒየም አጠገብ በሚገኘው 30ሺ ካ.ሜ ቦታ ላይ ሲሆን በስፍራው 5 ብሎክ ቤቶች ተሰርተው ኮተቤ የነበሩ 350 ተረጂዎች ገብተውበታል፡፡
በአያት ኮንዶሚኒየም አጠገብ የሚሰራው የመቄዶንያ አረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከል፤ ከ300 ሚሊዮን ብር በላይ የሚፈጅ ስለሆነ፣ የኮንስትራክሽን ድርጅቶች ኤክስካቫተር፣ ሎደር፣ ሚክሰር፣ ሲኖትራክ፣ የመሳሰሉትን ለተወሰነ ሰዓት ወይም ለአንድ ቀን ይዘው በመምጣት በሕዝብ ድጋፍ የሚሰራው ማዕከል ግንባታ አካል እንዲሆኑ መቄዶንያ ጠይቋል፡፡
“አገር በቀሉ መቄዶንያ እስካሁን እየተንቀሳቀሰ ያለውና አዲሱ ማዕከልም የሚሰራው በኢትዮጵያውያን በጎ አድራጎት ስለሆነ ለማዕከሉ ግንባታ ገረጋንቲ፣ የምግብ ማብሰያ እንጨት (የቤት ፍራሽ) ብሎኬት፣ አሸዋ፣ ጠጠር፣ ሚስማር፣ ቆርቆሮ የመሳሰሉትና የሙያ እገዛም በጣም ስለሚያስፈልገን፣ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን ወደ ማዕከሉ መጥተው በመጎብኘትና የጎደለውን በማሟላት፣በማዕከሉ ግንባታ አሻራቸውን እንዲያሳርፉ እንጠይቃለን” ብሏል፡፡
“ይበል ኢንዱስትሪያል፤ለመቶ ሰዎች በነፃ በብረት ተገጣጣሚ ቤት እየሰራ ነው፡፡ ቤቱን፣ በ3 ወር ሰርተው እንደሚያስረክቡን ነግረውናል፡፡ የአንቡላንስ ርክክብ ስነ ስርዓቱ የተከናወነበትን 4 ድንኳኖች በነፃ የሰጠን ልዩ የድንኳን ሽያጭና አከራይ ድርጅት ነው፡፡ ሌሎችም ያላቸውን ለአረጋውያኑ እንዲለግሱ እንጠይቃለን፡፡ ዳይፐር፣ ሞዴስ፣ ቅባት … ያስፈልገናል፡፡ በማዕከሉ ያሉት ብዙዎቹ የአዕምሮ ሕሙማን ናቸው፡፡ ሞዴስና ዳይፐር ሲታሰርላቸው ይቀዳሉ፣ አውልቀውም ይጥላሉ፡፡
 ያገለገሉ የቤት ዕቃዎች፣ ፖፖ፣ መዘፍዘፊያ፣ የሚገፋ ወንበር (ዊል ቸር) አልጋ፣ ፍራሽ፣ … በጣም ስለሚያስፈልጉን፣በተረጂዎቹ ስም እንጠይቃለን” ሲል ማዕከሉ ተማፅኗል፡፡
የአንቡላንሱን ቁልፍ ለመቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከል መስራችና ማኔጂንግ ዳይሬክተር ለአቶ ቢኒያም በለጠ ያስረከቡት የሞሓ ለስላሳ መጠጦች ፋብሪካ የማርኬቲንግ ኃላፊ አቶ ማሩ ሞላ፤ባዩት ነገር ከልብ መደሰታቸውን ገልጸው ወደፊትም አስፈላጊ በሆነው ነገር ሁሉ ከማዕከሉ ጎን እንደሚቆሙ እንዲያረጋግጡ መልዕክት እንደተሰጣቸው ተናግረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት መቄዶንያ፤ ምንም ጧሪና ደጋፊ ለሌላቸው ከአንድ ሺህ በላይ አረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን ምግብ፣ ልብስ፣ መጠለያ፣ ሕክምናና የቤተሰብ ፍቅር እየሰጠ እንክብካቤና ድጋፍ እያደረገ መሆኑን የገለፁት አቶ ቢኒያም፤በዕለቱ በስጦታ የተረከበው ሁለተኛ አንቡላንስ፣ በጎዳና ላይ የወቀዱትን ወገኖች ለማንሳትና ያሉትንም ተረጂዎች ወደ ሆስፒታል ለማድረስ ትልቅ እገዛ እንደሚያደርግ ጠቅሰው፣ለፋብሪካውና ለባለቤቱ ለሼሕ መሐመድ አላሙዲ ከፍተኛ ምስጋና አቅርበዋል፡፡

ፈረንጆች Good News and Bad News የሚሉት አላቸው፡፡ ደግ ወሬና ክፉ ወሬ
እንደማለት ነው፡፡ ይኸንን የተንተራሰ የአንድ ሀኪምና የታካሚው ንግግር የዛሬ ተረታችን ነው፡፡
እነሆ፡-
ሐኪም - እንኳን ደህና መጣህ ወዳጄ፡፡
ታካሚ - እንኳን ደህና ቆዩኝ ሐኪም፡፡
ሐኪም - ዛሬ፤ደግም ክፉም ወሬ ይዤ ነው የጠበቅሁህ፡፡
ታካሚ - ግዴለም ሐኪም፤ከክፉው ወሬ ይጀምሩልኝ፡፡
ሐኪም - መልካም፡፡ ግን ቅር እንዳይልህ፡፡
ታካሚ - በጭራሽ ቅር አልሰኝም፡፡
ሐኪም - እንግዲያው ልንገርህ፡፡ እህትህ በጠና ታማ፣ኮማ ገብታ፣እያጣጣረች ናት፡፡
ታካሚ - ይሁን እግዜር ካመጣው ምን ይደረጋል? ሌላስ?
ሐኪም - ወንድምህ ውሃ ውስጥ ሰጥሞ፣አሁን አምቡላንስ ተልኮለት እየመጣ ነው፡፡
ታካሚ - እግዚሀር ፈርዶበት ነው እንጂ ዋና ይችላልኮ! ሌላስ የሚነግሩኝ አለ?
ሐኪም - አዎ፡፡
ታካሚ - ቶሎ ቶሎ ይንገሩኝ ሐኪም!
ሐኪም - ባለቤትህ ልፈታው ነው ብላ ነግራኛለች፡፡
ታካሚ - ይሁን እንግዲህ ካመጣው ምን ይደረጋል! ሌላ አለ የሚነግሩኝ?
ሐኪም - ዛሬ በህይወት ሆነህ አንተን ማግኘቴ ገርሞኛል፡፡ ምክንያቱም ማታ ቤትህ መቃጠሉን
ሰምቻለሁ፡፡
ታካሚ - አዎ፤ ውጪ ነው ያደርኩት፡፡ ሌላስ  ምን የሚጨምሩልኝ ክፉ ወሬ አለ?
ሐኪም - ክፉውን ወሬ ጨርሻለሁ፤የቀረኝ ደጉ ወሬ ነው፡፡
ታካሚ - (በጣም ተጣድፎ) ሐኪም፤እሱን በደምብ ይንገሩኝ!
ሐኪም - አልዛይመር የሚባል በሽታ ይዞሃል፡፡
ታካሚ - ምን ማለት ነው?
ሐኪም - የማይድን በሽታ ነው፡፡ ማስታወስ የአለመቻል በሽታ ነው!
ታካሚ - ሐኪም፤በጣም ጨካኝ ነዎት፡፡ ይሄንን ነው ደግ ወሬ ብለው የሚነግሩኝ?
ሐኪም - ለምን መሰለህ እንድታውቅ ያደረኩህ?
ታካሚ - ለምንድነው ሐኪም?
ሐኪም - ምክንያቱም አሁን ከእኔ ስትለይ ያልኩህን ሁሉ ትረሳዋለህ፡፡ ለዚህ ነው ደግ ወሬ ነው
ያልኩህ!
***
የመከራና ችግሮቻችን መብዛት መርሳትን (አልዛይመርን) እንዳንመኝ ቢያደርገን መልካም ነበር፡፡
የበሽታችንን ስር ካላወቅን ሌላ በሽታ በራችንን ማንኳኳቱ አይቀሬ ነው፡፡ በሩ ሲንኳኳ ካላደመጥን
ደሞ ሌላ በሽታ አከልንበት ማለት ነው፡፡ “ሌባ!----ሌባ!” እያልን እንጮሃለን! በአደባባይ “እናሳየዋለን” እንላለን፤አንይዘውም፡፡ የጠራራ ፀሃይ ስርቆሽ፣ “የአየር ጊዜ መግዛትና” ፖሊሱ ዞር ብሎ እንዲቆይ ማድረግ፣ ፀሃይ የሞቀው እውነት ነው፡፡ ሌባውም አይያዝም፤ ፖሊሱም አይጠየቅም - መርካቶ ጉያዋ ብዙ ቢሆንም አደባባይዋ ግን ይህን ያሳየናል፡፡ የሞባይል ሌብነት፣አንድ ሌባ እንዳለው፤“የሥራ ፈጠራ እኮ ነው!” እንደ አራዶች አባባል፤ “ልማታዊ ሌብነት” መሆኑ ነው፡፡ የሴት ቦርሳ ምንተፋ ተጧጡፏል! የማን ያለህ እንበል? “በኃይለስላሴ አምላክ!” ይባል የነበረው ቀረ እንጂ ትንሽ ፋታ ይሰጥ ነበር፡፡ በ”ሕግ አምላክ”፣ ዛሬ እንኳን ወጣቱ የመንግሥት ሠራተኛም አያውቀው!
“ያባትህ ቤት ሲዘረፍ አብረህ ዝረፍ” የተሻለ መርህ ቃል (motto) ነው:: ቀን በቀን ከባንክ ጋር ተመሳጥሮ ከሚመዘበረው ገንዘብ አንስቶ በመሬት መልክ አገር እስከ መሸጥ ያለውን “የገበያ ውጣ-ውረድ”፣ በዓለም አቀፉ የገበያ ሥርዓት ወይስ በግሎባላይዜሽን እቅፍ ውስጥ እንደመድበው?
የታላላቅ ባለስልጣናት ወገናዊነት፣ እስከ ሰባት ቤት የኢ-ፍትሐዊ ሀብት ክፍፍል፣ የህዝብ ሀብት
ምዝበራ እንጂ የልማት ቀፎ ውስጥ የሚቀፈቀፍ የማር እንጀራ ሊባል ነው እንዴ?
ማ ባለስልጣን የማ ንግድ ድርጅት “ሼር ሆልደር” እንደሆነ ሳናውቅ ነው እንዴ ስለ ሙስና የምናወራው? የጦር አበጋዝ የንግድ ተቋራጭ የሚሆንበት አገር፣እዚሁ አኛ ዘንድ ካልሆነ የሮማ ነገስታትን ታሪክ አናመጣ?ስንቱን እንርሳ? በስንቱ “አልዛይመር” ይያዘን? ወይስ በተቋም ደረጃ የሚያም “አልዛይመር” ይኑረን?
ነገረ ስራችን ሁሉ ጥሩ ታቅዶ ነበር፡፡ ጥሩ ሥራ አመራር ተመድቦ ነበር - ታዲያ ምን ያደርጋል?
“የአፈፃፀም ችግር አለ” ይባላል፡፡ እስከ መቼ? “የአፃፀም ችግርን የሚያይ አገር አቀፍ ኮሚሽን”
ይቋቋም እንዴ? የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ከኮሌጅነት እስከ ዩኒቨርሲቲነት በሸፍጥ እስከመሰየም
ድረስ ከፍተኛ ሙስና ውስጥ ሲዘፈቅ ስናይ፣ እንዲህ በይፋ ምንም ሳያሟላ የተመረቀ ተማሪ ማስረጃ
አቅርብ ሲባል፤ እስከ መፋጠጥ ሲደርስ፣ ያስተማረው ዩኒቨርሲቲ እንዴት እንደተቀበለው ግራ  እስከመጋባት ሲደርስ ስናስተውል፤ “እዚህ አገር ስንቱን እንርሳ?” “በስንቱ አልዛይመር ይያዘን?”
ያሰኛል፡፡
በእውነት አገራችን እድገት ካላት፣የእድገቷ ታማሚ ናት ወይም ምርኮኛ ናት!
የቤቶች አስተዳደር ጣጣ ችግር ዛሬም ችግር ነው፡፡ ገቢዎችና ተገልጋዩ ነጋዴ ህብረተሰብ ዛሬም እንዳልተማመኑ፣ዛሬም እንዳልተዋደዱ ናቸው፡፡ የአደጉ አገሮችን የገቢዎች አስተዳደር ሥርዓት እንመኛለን፡፡ ግን በምን አንጀት? በማን ትከሻ? በምን እምነት?
የሰብዓዊ መብት ችግርና የመልካም አስተዳደር ጉድለት፣ይተሳሰር ዘንድ መከራችንን ስናይ ሰንብተናል፡፡ ግጭትን ባልተመጣጠነ ኃይል መፍታት የመልካም አስተዳደር የሁሉ-የሁሌ-ፍቱን  መድሐኒት (Panacea) አድርገን መውሰዱ በውል መጤን አለበት፡፡ ፍርድ ቤቶች ከሹማዊና ወገናዊ ሥርዓት መፅዳት አለባቸው፡፡ ስህተታችንን ስንሰማ አለመደናገር ቁልፍ ነገር ነው፡፡ በርትቶ ማረም ነው መድሐኒቱ! ችግሮቻችን አያሌ ናቸው፡፡ አልዛይመርም ቢይዘን አንረሳቸውም፡፡ ከሁሉም የሚልቀው “ችግር የለብንም፡፡ ይሄን ያህል ፐርሰንት አድገናል! የዓለም ባንክ ይሄን ይሄን ብሎናል፡፡” የሚለው ነገር ነው፡፡ “ይሄን አውጀናል፤ይሄን በጀት በጅተናል፤በሚቀጥሉት ይሄን ያህል አመታት ጉድ እናያለን” የሚለው ምኞትና ተስፋም፣ ዜጐች ብዙ ፍሬ እንድንጠብቅ ልባችንን ያንጠለጥለናል፡፡ “መሬት የያዘው የቱ ነው?” ማለታችን ግን አይቀርም፡፡ “የማያስተኛ ነገር ነግረውን ተኝተው አደሩ” የምንለው ያኔ ነው!

   በጋሻው መርሻ የተዘጋጀው በዕውቁ የቀዶ ጥገና ሃኪምና ፖለቲከኛ ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ ህይወት ላይ የሚያጠነጥነው “አንፀባራቂው ኮከብ፣ ፕ/ር አስራት ወልደየስ” የተሰኘ መፅሀፍ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ ፀሐፊው ለመፅሀፉ የሚውሉ ግብአቶችን ለማሰባሰብ ሶስት ዓመት፣ መረጃዎቹን አጠናቅሮ ወደፅሁፍ ለመቀየር አንድ ዓመት ከሁለት ወራት እንደፈጀበት ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡ ፕ/ሩ ከልጅነት ህይወታቸው ጀምሮ ስለትምህርታቸው፣ ስራቸው፣ በእስር ላይ በነበሩበት ጊዜ ስላደረጓቸው… ክርክሮች እስከ ዕድሜያቸው ፍፃሜ ድረስ ያለውን ህይወት በመፅሀፉ ለመዳሰስ ሞክሯል፡፡ ፀሐፊው ስለፕሮፌሰሩ ሙሉ ምስል ለማግኘት  ወዳጆቻቸውን፣ የስራ ባልደረቦችን ቤተሰባቸውን ያነጋገረ ሲሆን በተለያዩ ጊዜያት  የሰጧቸውን ቃለ ምልልሶች፤ የውጭና የአገር ውስጥ ሚዲያዎች ስለእሳቸው ያወጧቸውን ዘገባዎች መጠቀሙን ጠቁሟል፡፡ በ260 ገፆች የተቀነበበው መፅሀፉ፤ በ81 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

     በየዓመቱ የሚካሄደውና ዘንድሮ ለአራተኛ ጊዜ “New Trends in Art Education in Ethiopia” በሚል ርዕስ የተዘጋጀው የኪነ ጥበብ ጉባኤ ባለፈው ረቡዕና ሀሙስ ተካሄደ፡፡ ጉባኤው በዋናነት በኪነ ጥበቡ ላይ የሚታዩ ችግሮችን፣ የፖሊሲ ክፍተቶችንና መሰል ጉዳዮችን በጥናት አስደግፎ መፍትሄ ማፈላለግ ላይ እንደሚያተኩር የጉባኤው አዘጋጅ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቴአትር ጥበባት ት/ቤት ኃላፊ አቶ ተስፋዬ እሸቱ ተናግረዋል፡፡ ለጉባኤው ጥናቶች እንዲቀርቡ ት/ ቤቱ ከሁለት ወራት በፊት ባደረገው ጥሪ በርካታ ጥናቶች መግባታቸውን ሃላፊው ጠቁመው ከነዚህ ውስጥ ውሃ የሚያነሱና ጥልቀት ያላቸው 15 ያህል ጥናቶች ተመርጠው መቅረባቸውን ተናግረዋል፡፡ ከጥናቶቹ መካከል በረዳት ፕሮፌሰር በቀለ መኮንን የቀረበው “የሥነ ጥበብ ሁለንተናዊ ጉዞ
ከየወቅቱ ጥያቄዎች አንፃር”፣ በዓለም ፀሐይ ለማ የቀረበው “የከፍተኛ ትምህርት ተቋም የጥበብ ትምህርቶች ማስተማሪያ ዘዴ (ፔዳ ጎጂ) በቴአትር ትምህርቶች ላይ ያለው ሚና” እና በምስጋናው ዓለሙ የቀረበው “በኢትዮጵያ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ቴአትር የማስተማር ፈተናዎች” የሚሉት ይገኙበታል፡፡ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ፣ ተ/ፕሮፌሰር ተስፋዬ ገሰሰ አርቲስት ፍቃዱ ከበደ ወግና ፅሁፍ በማቅረብ ተሳትፈዋል፡፡፡ በአምስት ኪሎ ቴአትር ጥበባት ት/ቤት አዳራሽ በተካሄደው በዚህ ጉባኤ ላይ በኪነ-ጥበቡ ላይ ያሉትን ፈተናዎች ለመቅረፍና የትምህርት ፖሊሲው ለዘርፉ ሊሰጠው በሚገባው ትኩረት ላይ ውይይቶች እንደተካሄዱም ታውቋል፡፡