Administrator

Administrator

ከአንድ የተረት ስብስብ መጽሀፍ የተገኘ ተረት የሚከተለውን ይመስላል፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ በጣም ቁጠኛ የሆነ ልጅ ነበር፡፡ አባቱ የልጁን አመል ለመግራት አንድ ካርቶን ሙሉ ሚስማር ሰጠውና፤ “ቁጠኝነት ሲሰማህ አንድ አንድ ሚስማር እያወጣህ ከጣውላ በተሰራው ግድግዳ ላይ በመዶሻ ምታ” አለው፡፡
ልጁ የአባቱን ትዕዛዝ አክብሮ በመጀመሪው ቀን ሃያ አምስት ሚሥማር ግድግዳው ላይ ሲመታ ዋለ፡፡ ሃያ አምስት ጊዜ ተናዶ ነበር ማለት ነው፡፡ በሚቀጥለው ቀናት ግን ቁጣው እየቀነሰ ሄደ፡፡ ግድግዳ ላይ የሚመታቸው ሚስማሮች ቁጥር ቀስ በቀስ እየቀነሰ መጣ፡፡
በዚህም አንድ ግንዛቤ አገኘ፡፡ “ቁጣን መቆጣጠር ከመዶሻ ሥራ የቀለለኮ ነው” አለ፡፡ በመጨረሻው፤ ቁጣውን ሙሉ በሙሉ ተገላገለው፡፡ ወደ አባቱ ሄዶ፤ “አባዬ ቁጣ አቁሜያለሁ” አለው፡፡
አባትዬውም፤ “ለያንዳንዱ ሳትቆጣ ለዋልክበት ቀን አንድ አንድ ሚስማር ከግድግዳው ንቀል” አለው፡፡ ቀስ በቀስ ልጁ ሚስማሮቹን እየነቀለ ጨረሰና፤ “አባዬ ትዕዛዝህን ፈፅሜያለሁ፡፡ አንድም ሚስማር ግድግዳው ላይ የለም” አለው፡፡
አባት ልጁን ወደ ግድግዳው ወስዶ፤ ‹‹ጥሩ አድርገሃል ልጄ! ግን እስቲ ግድግዳው ላይ የቀሩትን ቀዳዳዎቹን ተመልከታቸው፡፡ ቀዳዳዎቹ አይጠፉም። በተቆጣህ ቁጥር አካባቢህ ላይ ቁስል ትተዋለህ፡፡ አንድን ሰው በጩቤ ወግተህ ጩቤውን ልትነቅልለት ትችላለህ፡፡ ቁስሉ ግን እዛው ነው። ጠበሳው አለ፡፡
ለቁጣህ ሺ ጊዜ ይቅርታ ልትጠይቅ ትችላለህ፡፡ ቁስሉ ግን እዚያው አለ። የቃልህ ቁጣ በአካል ላይ ጠባሳ እንደመተው ሁሌ ይኖራል፡፡ አስከፊነቱን ተገንዝበህ ከእንግዲህ አትድገመው!›› አለው፡፡
*   *   *
ንዴት፣ ቁጣ፣ ስሜታዊነትና ኃይል መጠቀም የሁልጊዜ ማሽነፍ ምልክቶች አይደሉም፡፡ ይልቁንም ጉጂነታቸው ያመዝናል፡፡ ኃይል ሚዛናዊ የአዕምሮ ቁጥጥርን ያዛባል፡፡ የድንገቴ ሁኔታን በቁጣና በኃይል ለመፍታት መሞክር ብዙ ሚስማር ግድግዳችን ላይ በመዶሻ እንድንመታ ያደርገናል፡፡ ሲበርድልን ደግሞ የሚተወው ጠባሳ አይጣል ነው! ጊዜያዊ መፍትሔ የዘላቂ ጠባሳ ወላጅ ነው፡፡ ሰላማዊ ውይይትን ከሁሉም ነገር አስቀድመን እንደ ጥሞና ገበታ መቁጠር ብልህነት ነው፡፡ ችግር መኖሩን ከመካድ፤ አምኖ መፍትሔ መሻት፣ የቀና አመራር ብርቱ እጅ ነው፡፡ የረጋ ወተት ቅቤ ይወጣዋል! ርኩቻ ለሀገርም፣ ለህዝብም ጤና አይደለም፡፡ ቸኩሎ እርምጃ መውሰድም ከጥቅሙ ጉዳቱ ይበልጣል፡፡ ‹‹ቁጣና ስሜታዊነት ከሩቅ ግብ አንፃር ሲታዩ ፀረ-ምርታማነት ናቸው፡፡ ሁልጊዜ ረጋ- ያልክና እሙናዊ ሁን፡፡ አንተ የረጋህ ሆነህ ባላንጣህ እንዲቆጣ ካደረግኸው፣ ጠቀሜታው ያንተ ነው! ባላንጣዎችህን ሚዛን አሳጣቸው፡፡ እነሱ ይሯሯጡ-ገመዱን ግን አንተ ያዝ!›› ይለናል ሮበርት ግሪን። ልብ ያለው ልብ ይበል ነው ነገሩ፡፡ ከተሳሳትን ማስተካከያውን እናብጅ- እንጂ ‹‹ካፈርኩ አይመልሰኝ›› አንበል፡፡ ‹‹አንጋጠው ቢተፉ ተመልሶ ባፉ›› ነው መጨረሻው!
“አትጣደፍ፡፡ ጥድፊያ  ራስህን ለመቆጣጠር እንዳትችል ያደርግሃል፡፡ ጊዜንም በቅጡ እንዳትጨብጥ ያስገድዱሃል፡፡ ሁሌ ታጋሽ ሁን፡፡ የመጨረሻው ቀን ያንተ ይሆናል፡፡ ትክክለኛዋን ቅፅበት ሰልላት፡፡ ወደ አሸናፊ ኃይል ትቀየር ዘንድ ጊዜን የማሽተት አቅምህ ወሳኝ ነው፡፡ ጊዜህ ካልበሰለ አፈግፍግ፡፡ ከበሰለ ግን አትዘግይ፤ ጥርቅም አድርገህ ምታ” ይለናል ከላይ የጠቀስነው ደራሲ፡፡
በሀገራችን ጉዳይ ያገባናል የሚሉና በውይይት የሚያምኑ፣ ችግሮችን ለመፍታት አቅም ይኖራቸዋል፡፡ ሀገራችን ልበ - ብሩሃን ሰዎችን ትሻለች፡፡ ሆደ - ሰፊና ከስሜታዊነት ለመታቀብ ብቃቱ ያላቸውን ብልህ ሰዎች ትፈልጋለች። ችግሮቻችን በርካታና ሥር የሰደዱ እንደመሆናቸው  ሁሉ፣ የአንድ ሰው ሳይሆን የብዙዎችን ትከሻ፣ የብዙዎቹን ርብርቦሽ፣ የብዙዎችን አዕምሮ - ለአዕምሮ መናበብ የግድ ይሻሉ፡፡ አንድ ድርጅት፣ አንድ ማህበር፣ አንድ ተቋም ብቻ የሚፈታቸው አይደሉም፡፡ ‹‹ብቻውን የሚሮጥ የሚቀድመው የለ፣ ብቻውን የሚሟገት የሚረታው የለ›› የሚለው ተረት፤ ሌሎችን የማያሳትፍ አመራር ፋይዳው ትንሽ መሆኑን ነው የሚጠቁመን!!

Monday, 29 August 2016 10:21

ዳግማዊ ኦሮማይ

ኢህአዴግ ሕገ መንግሥት አርቅቆ ቢነሣም ሕገ መንግሥታዊነትን አላሰፈነም
          የሕዝብ ብሶት ሲያይል ሽንገላና ጊዜያዊ መፍትሔዎች ቀልቡን አይስቡትም
          በሥርዓቱ በመሾምና ንብረት በማግበስበስ መካከል እምብዛም ልዩነት የለም
                    ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ
   ለበዓሉ ግርማ ሞት ምክንያት የኾነው፣ ‹‹ኦሮማይ›› በሚል ርእስ የጻፈው መጽሐፍ እንደ ኾነ ይታወቃል፡፡ እንደ እርሱ አተረጓጎም፣ ኦሮማይ ማለት አለቀ፣ ተፈጸመ፣ ሰዓቱ ደረሰ የሚል አንድምታ ያለው ቃል ነው፡፡ የበዓሉ ትረካ የደርግን ሥርዓተ መንግሥት ማብቂያ የሚጠቁም ሲኾን፣ ኒኮሎ ማኪያቬሊ የዛሬ አምስት መቶ ዓመት፣ ‹‹ስለ ልዑላኑ ማውራት ከአንገት ያሳጥራል›› እንዳለው የበዓሉም መጨረሻ በዚኹ መንገድ ተጠናቋል፡፡
የዚህ መጣጥፍ ዋና ዓላማ፣ በዓሉ፣ ‹‹ኦሮማይ›› በሚለው መጽሐፉ የደርግ ሥርዓት እያበቃለት መኾኑን እንደጠቆመው፣ እኔም በአኹኑ ወቅት በአገራችን እየተከሠተ ያለው ቀውስ፣ የኢሕአዴግ የፖለቲካ ሥርዓት ወደ ማብቂያው እየተጓዘ መኾኑን እንደሚያመለክት ለማሳየት ነው፡፡ ለመጣጥፌ ‹‹ኦሮማይ›› የሚለውን የበዓሉን ቃል በመዋስና የእርሱን ትረካ እንደ ‹‹ቀዳማዊ ኦሮማይ›› በመውሰድ፣ አኹን ኢሕአዴግ ያለበትን የፖለቲካና የሥርዓት ቀውስ ‹‹ዳግማዊ ኦሮማይ›› ብዬዋለኹ፡፡ እዚኽ ላይ ቀዳማዊም ኾነ ዳግማዊ ኦሮማይ የአንድን ሥርዓት የፍጻሜ ደውል የሚያስተጋቡ መኾናቸውን ልብ ይሏል፡፡
ኢሕአዴግ የሚመራውን ሥርዓት ከኦሮማይ ኹኔታ ጋር አዛምዶ ለማየት የሚያስችሉ በርካታ መገለጫዎች ቢኖሩም፣ ለዚኽ ጽሑፌ የሚከተሉትን ሦስት ነጥቦች እንደ ማሳያ አቀርባለኹ፡፡  
አገር በጄ
በዚኽ ነጥብ የማነሣው ዋነኛ ርእሰ ጉዳይ፣ ከኢሕአዴግ በፊት የነበሩት የፖለቲካ ሥርዓቶች የነበረባቸውን ግድፈቶች በማስወገድ፣ ለሕዝቦች ነጻነት እና ለጠንካራ አገራዊ አንድነት ዋስትና በሚል መርሕ የተመሠረተው ፌዴራላዊ የፖለቲካ ሥርዓት መከተል የሚገባውን ፈር ለቆ፤ ከዚኽ በፊት ‹‹አገር በጄ›› ብለው እንደተነሡት ነገሥታት ኢሕአዴግም፣ ያንኑ የጠቅላይነት ሥርዓት በፓርቲ የበላይነት እንደተካው ለማሳየት ነው፡፡
ፕሮፌሰር ሺፈራው በቀለ አሰባስበው በአሰናዱትና፣ ‹‹Kasa and Kasa›› በሚል ርእስ በታተመው መጽሐፋቸው፣ ስለ ዘመነ መሳፍንት አስደናቂና ፈር ቀዳጅ የታሪክ እይታ ያላቸውን ነጥቦች አቅርበዋል፡፡ እንደ ፕሮፌሰሩ አቀራረብ፣ ዐፄ ቴዎድሮስ ቀደም ሲል ከነበረው የአገዛዝ ሥርዓት የተለየና አዲስ ሥርዓት መሥርተዋል። ይህንኑም አዲስ ሥርዓት፣ ‹‹አገር በጄ›› የሚል ስያሜ ሰጥተው ካብራሩት ሦስት ምሁራን (ነጋድራስ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝ፣ ብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደ ሥላሴና ብላቴን ጌታ ማኅተመ ሥላሴ ወልደ መስቀል) መነሻ ሐሳብ በመውሰድ የራሳቸውን ትንተና አቅርበዋል፡፡
ፕሮፌሰር ሺፈራው በቀለ በዚኹ ትንታኔአቸው፣ ዐፄ ቴዎድሮስ ‹‹አገር በጄ›› ብለው መሳፍንቱንና መኳንንቱን እንዲኹም ከፍተኛ ማዕርግ ያላቸውን ባላባቶች ወደ ጎን በመገፍተር በምትካቸው ራሳቸው በመረጧቸውና ዝቅተኛ የሹመት ደረጃ ባላቸው ምስለኔዎች ማስተዳደር እንደ ጀመሩ አብራርተዋል፡፡ እንግዲኽ ይህ በዐፄ ቴዎድሮስ የተወጠነው የ‹‹አገር በጄ›› መርሕ ነው፣ ከዐፄ ቴዎድሮስ ጀምሮ እስከ ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ድረስ ተጠናክሮ የቀጠለው፡፡ ይህ መርሕ በዐፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመን ይበልጥ ተጠናክሮ፣ ‹‹ጠቅል›› የሚል ስያሜ በመያዝ ሙሉ ለሙሉ ጠቅላይ አሐዳዊ ሥርዓት ኾነ፤ ደርግም ቢኾን ይህን አሐዳዊ ሥርዓት በሶሻሊስት ሥርዓት መርሕ አስቀጠለው፡፡
በደርግ ውድቀት ዋዜማ የኢሕአዴግ አዲስ ሕገ መንግሥት ተረቆ አገሪቷ፣ ወደ አገር በጃችን (ፌደራላዊ) ሥርዓት መሸጋገሯን ይደነግጋል፡፡ ይህንንም የፌደራል ሥርዓት ተግባራዊ ለማድረግ አገሪቱ በተለያዩ የክልል መንግሥታት ተዋቀረች፡፡ ይኸው፣ ሕዝቦችን የፖለቲካ ሥልጣን ባለቤት የሚያደርግ ነው በሚል መርሕ የተመሠረተው አዲሱ ፌዴራላዊ ሥርዓት ጥቂት መንገድ ከተጓዘ በኋላ በሒደት፣ አገር በጃችን ቀርቶ አገር በፓርቲዬ መኾን ጀመረ፡፡
በዚኽ የ‹‹አገር በጄ›› መርሕ፣ አንድ ገዢ ፓርቲ ፍጹም የበላይነት ከተቀናጀ በኋላ የፈለገውንና የተመቸውን የክልሎች ግዛትና ሀብት፣ ‘የፓርቲዬና እኔ ወክዬዋለኹ የሚለው ሕዝብ ንብረት ነው’ ብሎ በተስፋፊነት ቢራመድ የሚያስገርም አይኾንም፡፡ የገዢው ፓርቲ የበላይነት ሥር ከሰደደ በኋላ የሕዝቦች ራሳቸውን በራሳቸው የማስተዳደር መብት በእጅጉ እየተገደበ ሔዷል፡፡ በየክልሉ የሚነሡ የማንነት ጥያቄዎች፣ በኢንቨስትመንት ስም የሚካሔደው የመሬት ወረራ፣ ‘ራሳቸውን የማስተዳደር አቅም የላቸውም’ በሚል ሰበብ የሕዝቦችን ሉዓላዊነትና የራሳቸውን ክልል በራሳቸው የማስተዳደር መብት የመጣስ ችግሮች፤ በአኹኑ ወቅት አስከፊ ደረጃ ላይ ደርሰዋል፡፡
አገር በጄ በሚለው ፅንሰ ሐሳብ፣ ነገሥታቱ በተበታተነ መልኩ በተለያዩ መሳፍንት ይተዳደሩ የነበሩ ግዛቶችን አዋሕደው አገራዊ አንድነትን አጠናክረዋል። ይህን በሚያደርጉበት ጊዜ ግን፣ ለአገር አንድነት የነበራቸውን ትልቅ ግምትና ቦታ ያኽል፤ ለሕዝቦች ነጻነት፣ ማንነትና መብት መጠበቅም ተገቢውን ትኩረት አልሰጡትም ነበር፡፡ ኢሕአዴግ በበኩሉ፣ ሕገ መንግሥት ቀርፆ ፌዴራላዊ ሥርዓት ሲመሠርት፣ የግዛት አንድነት ብቻ ሳይኾን የሕዝቦች ነጻነትም ለአንድ አገር ህልውና አስፈላጊ ነው፤ በሚል መርሕ ከአሐዳዊ አገዛዝ ወደ ፌዴራላዊ አገዛዝ ማለትም ከ‹‹አገር በጄ›› ወደ ‹‹አገር በጃችን›› ለማሸጋገር በማለም ነበር፡፡
የዚኽም ሽግግር ዓላማ፣ የአገሪቱን አንድነት አስጠብቆ ለዜጎች መብትንና ነጻነትን የሚያጎናጽፍ የፌደራል ሥርዓትን በሕገ መንግሥት ለመመሥረትና ሕገ መንግሥታዊነትን ለማስፈን ነበር፡፡ ይህ ዓላማም ኢትዮጵያ፣ የብዙ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች አገር መኾኗን በመገንዘብ የአገሪቷን አንድነት ለማስጠበቅና የሕዝቦችን መብት ለማስከበር ነበር፡፡
ነገር ግን፣ የኢሕአዴግን አገዛዝ ስንመለከት፣ አገር በጄ ወይም አገር በፓርቲዬ የሚለው አካሔድ፣ የአገሪቱን የአንድነት ጉዞም ኾነ የሕዝቦችን የነጻነትና የመብት ፈለግ አልተከተለም፡፡ ይልቁንም የተወሰኑ ወገኖችን ጥቅምና የበላይነት ማእከል በማድረግ፣ ነገሥታቱ ያስጠበቁትን የአገር አንድነት በማፋለስና በፌዴራሊዝሙ አስከብረዋለሁ ያለውን የአገር አንድነትም ኾነ የሕዝቦች መብትና ነጻነት በመጋፋትና በመፈታተን አዝማሪው እንዳለው ‹‹...ኹለተኛ ጥፋት›› ኾኗል፡፡
ኢ-ዴሞክራሲያዊነት
የኢሕአዴግ የፖለቲካ ሥርዓት ሲጀምር፣ ሕገ መንግሥት በወረቀት ላይ አርቅቆ በአንድ በኩል፣ ከአሐዳዊ ወደ ፌደራላዊ ሥርዓት ሽግግር ሲደነግግ በሌላ በኩል ደግሞ፤ ከግለሰባዊ አገዛዝ፤ የሥልጣን ክፍፍልን መሠረት ወደ አደረገ ዴሞክራሲያዊ ጎዳና ለመግባት የሚያስችል መንገድ ከፍቶ ነበር፡፡ እዚኽ ላይ ቁልፍ ጉዳይ የሚኾነው፣ በሕገ መንግሥቱ ውስጥ የተደነገጉ ሠናይ ትልሞች አኹን ባለንበት የፖለቲካ ምዕራፍ በምን ደረጃ ላይ እንዳለ ስንጠይቅ ነው፡፡
ይህን ጥያቄ ይዘን፣ የኢሕአዴግን የ21 ዓመት የሕገ መንግሥት ጉዞ ስንገመግመው፣ ሥርዓቱ ሕገ መንግሥት አርቅቆ ቢነሣም ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓተ ወግን ሊጎናጸፍ ግን አልቻለም፡፡ ይኸውም ኢሕአዴግ፣ ሕዝቦችን ለሉዓላዊ የፖለቲካ ሥልጣን ባለቤት ከማብቃት ይልቅ በጥቂት ሰዎች እንዲከማች ያደረገ፤ ሕገ መንግሥትን ማጽደቅ እንጂ ሕገ መንግሥታዊነትን ያላሰፈነና በኹሉም መልኩ የበላይነት የተጎናጸፈ ሥርዓት መኾኑ ነው፡፡ ለዚኽም እውነታ የሚከተሉትን ነጥቦች በማሳያነት ማቅረብ ይቻላል፡፡
አንደኛ፣ ማንኛውም ዴሞክራሲ በመሠረቱ የፖለቲካ ሥልጣን ክፍፍል እንዲኖር ያስገድዳል፡፡ የኢትዮጵያን የፖለቲካ ምኅዳር በምናይበት ጊዜ፣ ሥርዓቱ፣ ‹‹የፖለቲካ ሥልጣንን ለሕግ አውጭው፣ ለሕግ አስፈጻሚውና ለሕግ ተርጓሚው ያከፋፈለና የመንግሥት ሥልጣንን የገደበ ነው፤›› ቢባልም፤ የሕግ አስፈጻሚው ክፍል በአንድ በኩል ፌዴራሊዝሙን በሌላ በኩል ደግሞ፣ በሕግ አውጪውና በሕግ ተርጓሚው ላይ ትልቅ ጫና በማሳረፍ ሥልጣናቸውን በእጅጉ ገድቦታል፡፡ በመኾኑም የሕግ አስፈጻሚው ተቋም ራሱን እያፋፋና እያጠናከረ በአንፃሩ ሌሎቹን የመንግሥት ተቋማት እያሽመደመደ ሔዷል፡፡
ኹለተኛ፣ ከአገራችንም ኾነ ከሌላው አገር ታሪክ እንደምንረዳው፣ ሕግ ለነጻነት ትልቅ ዋልታ ነው፡፡ በመኾኑም የአንድን አገር ፍትሕም ኾነ ነጻነት ለማስከበር የፍትሕ ተቋማት በነጻነትና በገለልተኛነት መንቀሳቀስ መቻል አለባቸው፡፡ ኾኖም በአገራችን የፍትሕ ተቋማት የራሳቸው ልዕልና ኖሯቸው የሚንቀሳቀሱ አይደሉም፡፡ የራሳቸውን ልዕልና ያላስከበሩ ተቋማት ደግሞ የዜጎችን ነጻነት ያስከብራሉ ለማለት አይቻልም፡፡ በዚኽም የተነሳ የሕግ የበላይነት ሳይኾን የፖለቲካ ፍላጎት የበላይነት ትልቁን ድርሻ ይወስዳል፡፡ ሕግ ባለሥልጣናትን መቆጣጠር ሲገባው በተቃራኒው ባለሥልጣናት ሕግን እንዳሻቸው ለመቆጣጠር አስችሏቸዋል፡፡ በመኾኑም አገሪቱን የሚያስተዳድሩ መሪዎች የሕግ ማህቀፍ ሳይጣልባቸው በዘፈቀደ ሕግ እያወጡ ለፖለቲካ መሣርያነት እንዲጠቀሙበት ኾኗል፡፡
ሦስተኛ፣ ማንኛውም ሕገ መንግሥት በዜጎችና በመንግሥት መካከል የሚገኝ የውል ሰነድ ነው፡፡ ይኹንና የውል ፍጥጥሙን፣ በብሔርና በመንግሥት መካከል ያደረገው የኢትዮጵያ ሕገ መንግሥት ግን፣ ለዜግነት ተገቢውን ቦታና ዋጋ አልሰጠም፡፡ በመኾኑም ብሔር የሚለው እሳቤ ጎልቶ ሲቀርብ፣ ዜጋ የሚለውን እሳቤ አኮስሶታል፡፡ ይህን የዜጋ እሳቤ ማኮሰሱ ሦስት ዐበይት ችግሮችን ፈጥሯል፡፡
አንደኛው፣ ዜጎች በብሔራቸው ከተመደበላቸው ክልል ውጭ ተንቀሳቅሰው መኖር እንዳይችሉ አድርጓቸዋል፡፡ ኹለተኛው፣ ከተለያዩ ብሔሮች የሚወለዱትንና ራሳቸውን ከብሔር ማህቀፍ ያወጡ ዜጎችን ብሔር አልባ እንዲኾኑ አድርጓቸዋል፡፡ ሦስተኛው፣ መጽሐፍ ቅዱስ እስራኤሎችን፣ ‹‹የተመረጡ ሕዝቦች›› እንደሚላቸው ኹሉ፣ በእኛ አገር የፖለቲካ ሒደትም በአገሪቷ ውስጥ ካሉ ብሔሮች መካከል ‘የተመረጠ ብሔርና ሕዝብ’ በሚል መድልዎ ይካሔዳል፡፡
ሥርዓቱ ፍጹም የበላይነትን ያሰፈነ ለመኾኑ አራተኛው ማሳያ፣ በአንድ ማኅበረሰብ ውስጥ የዴሞክራሲ ግብ የሚሠምረው፣ በአገሪቱ ውስጥ የሚተገበሩ ፖሊሲዎችን ከማርቀቅ ጀምሮ እስከ አፈጻጸም ያለው ሒደት፣ ኅብረተሰቡን ባሳተፈ መልኩ ሲከናወን ነው፡፡ በዚኽ ረገድ ኢሕአዴግ የሚያወጣቸው ፖሊሲዎች፥ ኅብረተሰቡን ያሳተፉ፣ የሕዝቡን አስተያየት ያካተቱና የሕዝቡን ይኹንታ አግኝተው የሚተገበሩ አይደሉም፡፡ ይልቁንም የምናወጣቸው ፖሊሲዎችና የምናስፈጽማቸው ተግባራት፣ ትክክለኛውን አቅጣጫ የተከተሉ ናቸው ብለው ስለሚያምኑ የተለያዩ ሐሳቦችና አመለካከቶች በግልጽና በሐቅ እንዲንሸራሸሩ ቦታ አይሰጡም፡፡ ይህ ፍጹም ርግጠኝነት ለዴሞክራሲ ማበብ ትልቅ መሰናክል እንደሚኾን መረዳት ተስኗቸዋል። ይህም ሕዝቦች በነጻነት ሐሳባቸውን የሚያቀርቡበት መድረክና የሚደመጡበት ተቋም (የብዙኃን መገናኛ) በአገሪቷ ውስጥ እንዳይኖር ምክንያት ኾኗል፡፡
ሙሰኝነት
በአማርኛ፣ ‹‹ሙስና›› በእንግሊዝኛ፣ ‹‹Corruption›› የሚባለው ስያሜ በጣም ሰፊና በተለያዩ የታሪክ ዘመናት የራሱ የኾነ ይዘት፣ ቅርፅና ትርጉም እየያዘ የመጣ ፅንሰ ሐሳብ ነው፡፡ ‹‹ሙስና›› ለሚለው ቃል አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ የሚከተለውን ፍች ሰጥተዋል፡፡ ሙስና ማለት ‹ጥፉነት›፣ ‹ጥፋት›፣ ‹መፍረስ›፣ ‹መበስበስ›፣ ‹መከራ›፣ ‹መቅሠፍት›… ወዘተ ማለት ነው፡፡ እንዲኹም ‹‹ሙሱን (Agent)›› ‹የማሰነ›፣ ‹ጥፉ›፣ ‹መጥፎ›፣ ‹ብልሹ›፣ ‹ግም›፣ ‹ድፍር› …ወዘተ. ማለት ነው፡፡ እንደ እንግሊዝኛው ኦክስፎርድ መዝገበ ቃላት ፍች ደግሞ፣ ‹‹Corruption›› ማለት በዋናነት ‹መበስበስ›፣ ‹መቆርቆዝ›፣ ‹መበታተን›፣ ‹መዝቀጥ›… ወዘተ ሲኾን፣ ከእነዚህ ገለጻዎች የምናገኘው ምስል፥ ‹‹መበከል›› እና ‹‹ከተፈጥሯዊ ማንነት መውጣትን›› ነው፡፡
ልብ ብለን መገንዘብ የሚኖርብን ነገር ቢኖር፣ የአማርኛውም ኾነ የእንግሊዝኛው ትርጓሜ በሐሳብ ደረጃ ተቀራራቢነትና ተያያዥነት እንዳላቸው ነው። በተጨማሪም የአማርኛውም ኾነ የእንግሊዝኛው ፍቺ፣ አኹን በዘመናችን ካለው እሳቤ ጥልቀትና ስፋት ያለው ኾኖ እናገኘዋለን፡፡ ይህንንም የምንልበት ዐቢይ ምክንያት፣ ዘመናዊው አተያይ ሙስናን፣ ከኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ውጭ የማያይ፤ በግለሰብና በማኅበረሰብ ጥቅም መካከል የሚገኝ ሽኩቻ ብቻ አድርጎ ስለሚያቀርብ ነው፡፡
በአገራችን ያለውን የሙስና ደረጃና ኹኔታ በሚገባ ለማየት ግን የጥንቱንና ዘመናዊውን አተረጓጎምና አተያይ በድምር መውሰድ ይኖርብናል፡፡ እኔም ከፈላስፎች ጥቂት ብሂላትን በመውሰድ፣ ኹለቱንም አተያዮችና አተረጓጎሞች በጥቂቱም ቢኾን ማየቱ ጠቀሜታ ይኖረዋል፤ እላለኹ፡፡ የአራት ፈላስፎችን ሐሳብ አጠር አድርገን እንመልከት፡-
አርስቶትል፡-
እንደ ጥንታዊው የግሪክ ፈላስፋ አርስቶትል አስተምህሮ፣ የአንድን የፖለቲካ ማኅበር እንደ ሰንሰለት የሚያያይዘው ተቀዳሚ ዕሴት ፍትሕ ነው፡፡ ያለ ፍትሕ ማንኛውም ማኅበረሰብ በሰላምና በጸጋ ሊኖር አይችልም። ሙስና፣ ይህን ወሳኝ የሞራልና የሕግ ዕሴትና አውታር ስለሚያበትከውና ስለሚያመክነው ለማኅበረሰቡ ህልውና ትልቅ አደጋ ነው፡፡
ሲሰሮ፡-
ለሲሰሮ፣ የሙስና ተቀዳሚ መሠረቱ፣ ማኅበረሰቡን ለማስተዳደር ሓላፊነት የተቀበሉ ሰዎች በፍቅረ ንዋይ እየተነዱ ከዋናው ተግባራቸው መውጣታቸው ነው። ለዚኽ ፈላስፋ፣ ሙስና፣ ሰፋ ያለ የሞራል፣ የሕግና የፖለቲካ ብልሹነትን የሚጠቁም ጉዳይ ነው፡፡
ቅዱስ ኦገስቲን፡-
እንደ ቅዱስ ኦገስቲን አባባል፣ የሰውነት ክፍሎቻችን የየራሳቸው የሥራ ድርሻ እንዳላቸው ኹሉ፤ በአንድ ማኅበረሰብ ውስጥ የሚኖሩ ተቋማትም የየራሳቸው የሥራ ድርሻ አላቸው፡፡ እንደ እርሳቸውም እሳቤ፣ የሰው ልጅ አንድ አካሉ ሲታመም መላው ሰውነቱ እንደሚታወክ ኹሉ፤ ሙስናም፣ በአንደኛው የማኅበረሰብ አካል ከታየ ሌሎቹንም ክፍሎች እንደሚበክል ይናገራሉ፡፡
ኒኮሎ ማኪያቬሊ፡-   
እንደ ማኪያቬሊ አገላለጽ፣ የጥንት ሮማውያን ወታደራዊ ድል ከተጎናጸፉ በኋላ ግዙፍ ግዛተ ዐፄ/ኢምፓየር/ ገነቡ፡፡ በዚኽም ብዙ ሀብት እና ትልቅ የፖለቲካ ኃይል ማግኘት ቻሉ፡፡ ኾኖም ግን ያገኙት ሀብት እና ምቾት የተንደላቀቀ አኗኗር እንዲያገኙ ቢያስችላቸውም፣ ከንዋይ ጋር ተያይዞ ከሚመጣው የሞራል ዝቅጠት ሊያመልጡ አልቻሉም፡፡ ማኪያቬሊ፣ ይህን የታሪክ እውነታ ዋቢ በማድረግ ስለ ሙስና የጻፈውን በኹለት ነጥቦች አሳጥሬ ላቅርብ፡፡
ሀ/ ሙስና፣ ከምቾት እና ከቅምጥል ኑሮ የሚነሣ የሥነ ምግባር እና የዲስፕሊን ጉድለት ነው፡፡
ለ/ የግል ጥቅም ከማኅበረሰብ ጥቅም የበላይነት ይዞ ሲገኝ፣ ‹‹የእኔ…›› የሚለው የራስ ወዳድነት መንፈስ ከሪፐብሊኩ ፍላጎት እና መንፈስ ጋር ሲጋጭ ነው፡፡
በአገራችን ያለው የኢሕአዴግ ሥርዓት በሙስና የተዘፈቀ በመኾኑ ሳቢያ፣ ከላይ የተጠቀሱትን ችግሮች ከተሟሉ መገለጫዎቻቸው ጋር ተሸክሞ እንደሚገኝ አምናለኹ፡፡ የኢሕአዴግ ሥርዓት በአስከፊ ሙስና ውስጥ እንዲዘፈቅ በምክንያትነት ከሚጠቀሱ ነጥቦች መካከል የሚከተሉት ዋነኞቹ ናቸው፡፡
አንደኛው ምክንያት፣ መንግሥቱም ኾነ ዜጎች፣ በአገሪቱ የፖለቲካና የኢኮኖሚ መዋቅሮች የየራሳቸው ሓላፊነትና ድርሻ ሊኖራቸው ሲገባ፣ ይህ ካለመኾኑ የመነጨ ነው፡፡ ሥርዓቱ፣ እኒኽ ዜጎች በመንግሥት የተለያዩ መዋቅሮች ተገቢው ሓላፊነትና ድርሻ እንዳይኖራቸው በማድረግ ራሱ የፖሊሲ አውጪ፣ ራሱ አስፈጻሚና ራሱ ዋነኛ የኢኮኖሚው ተዋናይ ኾኗል፡፡
ከዚኽ ጎን ለጎን ሳይጠየቅ የማይታለፈው ደግሞ፣ ሥርዓቱ በሕዝብና በግለሰብ መብት መካከል ያለውን ልዩነት ማየት የተሳነው መኾኑ ነው፡፡ አንድ ግለሰብ፣ ፍትሕ ላይ የተመሠረተ፣ የማይሻርና የማይገሰስ መብት አለው፡፡ በመኾኑም ብዙኃኑን ይጠቅማል በሚል እሳቤ የግለሰቡን የማይገሰስ መብት መጣስ ፍትሐዊ አይደለም። በዚኽ ሥርዓት ግን የማኅበረሰቡን ወይም የብዙኃኑን ጥቅም ለማስከበር በሚል ሰበብ የግለሰቡ መብትና ህልውና ሲጨፈልቅ ይታያል፡፡ ይህም በዋነኛነት የግለሰቡ ጉዳት ፖለቲካዊ ኪሳራ አያመጣብኝም ከሚል እሳቤ የመነጨ ነው፡፡
ይህም መንግሥት ለግለሰቡና ለሲቪል ማኅበረሰቡ መላወሻ የማይሰጥ፣ አንድ ወጥ መንግሥታዊ ሥርዓት እንዲኾን አድርጎታል፡፡ እነዚኽ የሥርዓቱ ባሕርያትም፣ መንግሥት በኹሉም የአገሪቱ ሀብትና ንብረት ላይ እጁን እንዲዘረጋ፣ የመንግሥት የአስተዳደር ሕጎች በትክክል እንዳይተገበሩ፣ የአሠራር ብልሹነት እንዲስፋፋ፤ የመንግሥትና የሕዝብ ሀብት በማባከን ሥርዓቱ የሙስና መናኸሪያ እንዲኾን አድርጎታል፡፡
ከላይ የጠቀስናቸውን ፈላስፎች ሐሳብ አጠቃለን ስናየው፣ ሙስና የሚከተሉትን አሉታዊ ተጽዕኖዎች እና ውጤቶች ያስከትላል፡፡ እነርሱም፡- ኢፍትሐዊነት፣ የግል ጥቅም አሳዳጅነት፣ ሥርዓተ ብልሹነት፣ አድልዎና የሞራል ዝቅጠት ናቸው፡፡
በአገራችንም ያለው የኢሕአዴግ ሥርዓት፣ ከላይ የተጠቀሱትን ችግሮች ከተሟሉ መገለጫዎቻቸው ጋር የተሸከመ እንደኾነ ስለምናምን፣ ሥርዓቱ ደግሞ እንዴት ወደ እነዚኽ አስከፊ የሙስና ኹኔታዎች እንደገባ በሚከተሉት ነጥቦች ማሳየት ይቻላል፡፡
አንደኛ፡- የኢሕአዴግን የፖለቲካ ሥርዓት ስንመለከት፣ በይዘቱ በጣም ሰፊና ትልቅ መንግሥት ነው፡፡ ይህም አንዱ፣ በመንግሥትና በሲቪል ማኅበረሰብ መካከል ልዩነት እና ወሰን መኖሩን የማይቀበል ሲኾን፤ በሌላ በኩል ደግሞ፣ በሕዝብና በግለሰብ መካከል ያለውን መሠረታዊ ልዩነት በመናድ አንድ ወጥ የኾነ የጠቅላይ አገዛዝ መንግሥት የዘረጋ ኃይል ነው፡፡ ይህ ደግሞ፣ በኹሉም የአገሪቷ ንብረት ላይ በበላይነት እጁን እንዲከትና የብክነት እክሎችና የትግበራ እንከኖች ብሎም የሙስና መናኸሪያ እንዲሆን አድርጎታል፡፡     
ለሥርዓቱ በሙስና መዘፈቅ ኹለተኛው ምክንያት፣ ከፍትሐዊ የሀብት ክፍፍል፣ በብቃት ላይ የተመሠረተ ውድድር፣ ከጤናማ የኢኮኖሚ ፉክክር፣ ከሕጋዊ የሀብት ምንጭ… ወዘተ አኳያ ትልቅ ክፍተት ያለበት ሥርዓት መኾኑ ነው፡፡ በእኔ ግምት ይህ ክፍተት ካለማወቅ የመነጨ ሳይኾን፣ ኾነ ተብሎ የፖለቲካ ሥልጣን ከጨበጡት ሹመኞች ጋር የብሔር ትስስር ያላቸውንና የእኛ የሚሏቸውን ወገኖች ለመጥቀም በማሰብ የተደረገ ነው፡፡ በዚኽ መልኩ ፍትሐዊነት በጎደለው በአንድ አገር የፖለቲካ ሥርዓት ውስጥ፣ እነዚህ ዕሴቶች በሚጓደሉበት ወቅት ደግሞ፣ አኹን በአገራችን እንደምናስተውለው፣ የአገሪቷ ሀብት የጥቂት ቡድኖች መጠቀሚያና ችሎታን መሠረት ያላደረገ ኢፍትሐዊ ውድድር ተጠቃሚ እንዲኾኑ አስችሏቸዋል፡፡
በአጠቃላይ በኢሕአዴግ ሥርዓት ውስጥ ያለውን የሙስና ደረጃ ስናየው፣ ሌቪ የተባለው የጥንታዊ ሮማ የታሪክ ምሁር ስለ ሙስና ያለውን ያስታውሰናል። ሌቪ እንደሚለው፣ ‹‹ሙስና የተንሰራፋበት ሥርዓት ዝም ብለው ቢተዉት ሥርዓቱን ማፍረሱ አይቀርም፡፡ በአንፃሩ ደግሞ፣ የተስፋፋውን ሙስና ለመግታት ሙከራ ቢደረግም እንኳ ሥርዓቱ መፍረሱ አይቀርም፡፡››
ከላይ ያነሣናቸው የአገር በጄ፣ የኢ-ዴሞክራሲና የሙስና መንሰራፋት ችግሮች፣ አኹን ሥርዓቱ ለአጋጠመው ሕዝባዊ ተቃውሞና ዐመፅ መንሥኤዎች ናቸው፡፡
ወደ ኦሮማይ ጎዳና
ሌኒን፣ በ1920 (እ.ኤ.አ)፣ አንድ አገር ዐብዮታዊ ኹኔታ ውስጥ ስትገባ የሚከተሉትን አራት ክሥተቶች እንደ ምልክት እናያለን ብሎ ነበር፡፡ እኔም ሥርዓቱ ወደ ዳግማዊ ኦሮማይ ድባብ እየገባ ነው፣ ብዬ ስለማምን የሌኒንን አራት መገለጫዎች አንሥቼ የራሴን አተያይ ለማቅረብ እሞክራለኹ።
1ኛ/ ለዐብዮቱ ጠላት የኾኑ መደቦች በመካከላቸው ባለው ውስጣዊ ትግል ምክንያት ወደ ውዥምብርና ክፍፍል ያመራሉ፡፡ ይህ ውስጣዊ ውዥምብር ደግሞ ለድክመት ይዳርጋቸዋል፡፡ በመኾኑም ድሮ በሚተገብሩት መንገድ ሥርዓታቸውን ማስቀጠል አይችሉም፡፡  
2ኛ/ ከሥርዓቱ ተጠቃሚነት አልፎ ተቀባይነትና አመኔታ ያለው የንኡስ ከበርቴ መደብ፣ በሕዝቡ ዘንድ ማንነቱ በሚገባ ታውቆና በሕዝቡ ፊት ተጋልጦ፣ በጥቂቱም ቢኾን የነበረውን ሕዝባዊ ቅቡልነት ሙሉ ለሙሉ ያጣል፡፡
3ኛ/ ዐብዮተኞቹ ከቡርዣው መደብ ጋር የሚያደርጉትን ቁርጠኛ ትንቅንቅ ሰፊው የሠራተኛው መደብ መደገፍ ይጀምራል፡፡
4ኛ/ የገዢው መደብ ሠራዊት እርስ በርስ መከፋፈል፣ መፈረካከስና ማመፅ ይጀምራል፡፡
እንደሚታወቀው እነዚህ ነጥቦች፣ የሩስያ ዐብዮት መሪ የዛሬ መቶ ዓመት ለዐብዮት መፈጠር አመልካች ክሥተቶች ናቸው በሚል የጠቀሳቸው ናቸው፡፡ በመኾኑም ሌኒን ያለውን በንባቡ ( ቃል በቃል) በመውሰድ፣ ዛሬ አገሪቷ ያለችበትን ኹኔታ ለመግለጽ ሳይኾን፣ ከእነዚህ ነጥቦች መካከል የተወሰኑት አኹን ባለው የአገራችን የፖለቲካ ኹኔታ ላይ እንዴት እንደሚስተዋሉ ቀጥሎ እንመለከታለን፡፡
ሀ/ ‹‹በድሮው መንገድ ሥርዓቱ መቀጠል ሲሳነው››
በፍትሕ፣ በዴሞክራሲና በመብት ዙሪያ የተነሡ ጥያቄዎች፣ ሥርዓቱ እስከ ዛሬ በሚያስተዳደረው መንገድ ሊፈቱ እንደማይችሉ ሕዝቡ ርግጠኛ ኾኗል፡፡ በመኾኑም እነዚህን ጥያቄዎች ለመመለስ የሚቻለው የሥርዓት ለውጥ ሲመጣ ብቻ እንደ ኾነ ሕዝቡ ተገንዝቧል፡፡ ሌኒንም፣ እንደ ድሮው ሥርዓቱ መቀጠል አይችልም፤ በሚልበት ጊዜ፣ በሕዝቡ ለተነሡት ኹለንተናዊ ጥያቄዎች መልስ ማግኘት የሚቻለው፣ በድሮው መንገድ ሳይኾን አዲስ የሥርዓት መንገድ መከተል እንደሚያስፈልግ ሕዝቡ ሲያምን እንደኾነ መናገሩ ነው፡፡  
ለ/ ‹‹የሕዝብ ቅቡልነት ማጣት››
ለአንድ ሥርዓት የቅቡልነት ጥያቄ ቁልፍ ጉዳይ ነው፤ ቅቡልነቱም በተለያየ መንገድ ሊመጣ ይችላል፤ መንገዶቹም፡- ባህላዊ፣ ሃይማኖታዊ፣ ሕገ መንግሥታዊ… ወዘተ ሊኾኑ ይችላሉ፡፡ የአንድ ሥርዓት ዕድሜ፣ ቀጣይነት ወይም ዘላቂነት የሚወሰነው፣ ከሕዝብ ከሚያገኘው ቅቡልነት የተነሣ ነው፡፡
አገዛዙ የሕዝብ ቅቡልነትን ሲያጣ በመሣሪያ ኃይል ሥርዓቱን ማስቀጠል ይፈልጋል፡፡ አኹንም በአገራችን እያየን ያለነው የሕዝብን ጥያቄ በመሣሪያ ለመግታት የሚደረግን ጥረት ነው፡፡ ነገር ግን፣ ይህ የኃይል አካሔድ እንደማያዛልቅ የታወቀ ነው፡፡ በዚኽ ረገድ ፈረንሳዮች አንድ ትምህርታዊ  አባባል አላቸው፡፡ ይህም ‹‹መሣሪያን ብዙ ነገር ያደርጉበታል፤ ኾኖም ለብዙ ጊዜ አይቀመጡበትም›› የሚል ነው፡፡
ሐ/ ‹‹የሕዝብ ቁርጠኝነት››  
የሕዝብ ብሶት ከፍተኛ ደረጃ በደረሰ ጊዜ ሽንገላና ጊዜያዊ መፍትሔዎች ቀልቡን አይስቡትም፡፡ ቀደም ሲል፣ ሕዝቡ፣ መንግሥት ወይም የአስፈጻሚ አካላት ሕገ መንግሥቱን ቢያስከብሩ ችግራችን በሒደት ሊፈታ ይችላል የሚል ተስፋ ነበረው፡፡ አኹን ግን ያለው የፖለቲካ ሥርዓት ሕገ መንግሥቱን መሠረት አድርጎ የሕዝቡን ጥያቄ ለማስተናገድም ኾነ መፍትሔ ለመስጠት ከማይችልበት ደረጃ ላይ መድረሱን ከመረዳት አልፎ፣ ሥርዓቱ ሕገ መንግሥቱን ለመተግበር የሚያስችል ባሕርይና ፈቃድ እንደሌለው ተገንዝቧል፡፡ በዚኽ ምክንያት በተነሣሣው ሕዝባዊ ዐመፅ፣ መንግሥት በብቸኛነት በሚቆጣጠረው የብዙኃን መገናኛ የተለያየ ምክንያት ቢያቀርብም ሕዝቡ ልቡንም ጆሮውንም ሳይሰጠው የተቃውሞ እንቅስቃሴውን ቀጥሏል፡፡
ማጠቃለያ  
እንደ ኢትዮጵያ የተለያዩ ማኅበረሰቦች ባሉበት አገር፣ የሚዘረጋው የፌዴራል ሥርዓት ቢያንስ የሚከተሉትን ኹለት ወሳኝ ጉዳዮች ማሟላት እንደሚገባቸው በዘርፉ ለበርካታ ዓመታት ጥናትና ምርምር ያደረገው አረንድ ሊፕሐርት ይገልጻል፡፡ እነርሱም፡-
አንደኛ፡- በአገሪቷ ውስጥ ባሉት ማኅበረሰቦች መካከል ፍትሐዊ የሥልጣን ክፍፍል እንዲኖር ያስፈልጋል፡፡ ሁለተኛ፡- በአገሪቷ ውስጥ ያሉት ማኅበረሰቦች፣ ራሳቸውን በራሳቸው የማስተዳደር መብት መጎናጸፍ ይኖርባቸዋል፡፡ ሊፕሐርት፣ የሥልጣን ክፍፍል እንዲኖር ያስፈልጋል፣ ሲል ኹሉም ማኅበረሰቦች ውሳኔ በመስጠት ሒደት ላይ ቀጥተኛና ተገቢውን የተሳትፎ ሚና ሊኖራቸው ይገባል ማለቱ ነው፡፡
ኹሉም ማኅበረሰቦች ራሳቸውን በራሳቸው ያስተዳድሩ ማለትም፣ የራሳቸውን ቋንቋ፣ ባህል፣ ሥልጣኔ፣ ሃይማኖት… ወዘተ እንዲያሳድጉና በአገሪቷ ላይ የሚኖራቸውን የጋራ የባለቤትነት ስሜት እንዲያጎለብቱ እንዲያስችላቸው ነው። ከእነዚኽ ኹለት ነጥቦች አኳያ የኢሕአዴግን መንግሥት አመራር ስናየው፣ ፌዴራላዊ ሥርዓትን በመተግበር በባህልና በትምህርት መስኮች ማኅበረሰቦች ያላቸውን ማንነት እንዲያስጠብቁ ቢሞክርም፣ ጅማሮው እየዋለ ሲያድር መልሶ የማኅበረሰቦችን ማንነት ወደ መጨፍለቅ፣ እኔ የሰየምኩኽን ማንነት መላበስ አለብኽ፣ ወደሚል ዓምባገነናዊ አካሔድ ተለውጧል፡፡
ይህም ብቻ አይደለም፣ በፖለቲካ ሥርዓቱ ውስጥ የሕዝቦችን ዴሞክራሲ መብት በጉልበት በመገደብ ፍትሐዊ የሥልጣን ውክልና እንዳይኖራቸው እስከ ማድረግም ደርሷል። እንደሚታወቀው ዴሞክራሲ፣ ለኹሉም እኩል የኾነ መንገድ ትከፍታለች፡፡ ኾኖም በአንድ ጉዳይ ላይ ‹‹የመድልዎ›› ስሜት ይታይበታል፡፡ ይህም ዴሞክራሲ በተፈጥሮዋ ግቧን ለማሳካት በዋናነት የቁጥርን መርሕ መከተሏ ነው፡፡ በኢሕአዴግ ሥርዓት ግን፣ ዴሞክራሲ፣ ይህን መርሕ ተከትላ ለሕዝቦች የሥልጣን ውክልናና ትክክለኛውን ምላሽ እንዳትሰጥ በጉልበት ተገድባለች፡፡ ለዚኽም በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከፍተኛ የመቀመጫ ቁጥር ያላቸው ሕዝቦች ወደ ኋላ ተገፍተው፣ ከእነርሱ በእጅጉ ያነሰ የመቀመጫ ቁጥር ያላቸው ሕዝቦች በመንግሥት ሥልጣን ውስጥ ከፍተኛ ቦታ ይዘዋል፡፡ ይህን ሕዝቦች ባላቸው የመቀመጫ ቁጥር ውክልና መሠረት ተገቢውን ሥልጣን አለማግኘታቸው እንደ ማሳያ መውሰድ ይቻላል፡፡
በእነዚህ ኹለት መሠረታዊ ችግሮች ሳቢያ፣ በአኹኑ ወቅት የኢሕአዴግ ሥርዓት ፍትሐዊ የሥልጣን ክፍፍልን ለመተግበርም ኾነ ሙሉ ለሙሉ አስጠብቄዋለኹ በሚለው የሕዝቦች የማንነት ጥያቄ ዙሪያ ለሚነሡ ጥያቄዎች ተገቢውን ምላሽ መስጠት ተስኖታል፡፡ ከሁሉም በላይ የሚያስገርመው፣ ትላንት የነበሩት ሥርዓቶች የሕዝቦችን ማንነት አላከበሩም፤ እያለ ሲወነጅል የነበረው መንግሥት፣ አኹን ካለፈው በከፋ መልኩ ለማኅበረሰቡ ባይተዋር የኾነ ማንነት እየለጠፈ ባለኽበት እርጋ ማለቱ ነው፡፡
አኹን የተነሣው ጥያቄ፣ በዴሞክራሲ ዕጦት አካባቢና አብረው የሚሔዱት የሕግ የበላይነት፣ ፍትሐዊ የሀብት ክፍፍል እንዲኹም፣ በሰብአዊ መብት ረገጣ ጉዳዮች ላይ ነው፡፡ አንዳንድ ምሁራን፣ ከአኹን በኋላ ኢሕአዴግ ሕገ መንግሥቱን ማክበር ቢጀምር ነገሮች ይስተካከላሉ፤ የሚል አቋም ይዘው እየተሟገቱ ነው፡፡ እንደ እኔ አስተሳሰብ፣ በአንድ በኩል፣ ኢሕአዴግ ሥልጣን ላይ ለመቆየት ባለው ፍላጎትና ዴሞክራሲ ራሷ እንዲተገበርላት በምትፈልገው መካከል ትልቅ ቅራኔ ስላለ፣ ሥርዓቱ፣ ሕገ መንግሥቱን በሥራ ላይ ያውላል ብሎ መመኘቱ ትልቅ ስሕተት ነው የሚኾነው። በሌላ በኩል፣ ዴሞክራሲ በሌለበት ቦታ የመናገርና ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት ብሎም ኹሉም ወገኖች የሚደመጡበትና ሐሳባቸውን የሚገልጹበት መድረክ ሊኖር አይችልም፡፡
አንዳንድ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን በብዙኃን መገናኛ እየቀረቡ፣ ‹‹አኹን የተፈጠረው ችግር በውይይት ይፈታ፤ ሕዝቡም ሐሳቡን በግልጽ ተወያይቶ መፍታት ይኖርበታል›› ሲሉ ይሰማሉ፡፡
የእኒኽን ምሁራን ሐሳብ ስሰማ የሚገርመኝ ነገር ቢኖር፣ በአገር አቀፍ ደረጃ የተነሣውን ችግር ቀርቶ፣ የሐሳብ መፈተሻና የነጻ ውይይት መዲና ሊኾን በሚገባውና ዛሬ የዶ/ር አድማሱ ጸጋዬ በኾነው ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ሐሳብን በነጻነት መግለጽ እንደማይቻል እየታወቀ፣ ምሁራኑ ራሳቸውም ሐሳባቸውን በነጻነት የማንሸራሸር መብታቸውን ተገፈው ባሉበት ወቅት፣ ‹‹ሕዝቡ በነጻ ውይይት ችግሩን ይፍታ›› ማለታቸው ነው፡፡
ሙስና ለአንድ የፖለቲካ ሥርዓት ኢፍትሐዊነት ማሳያ ነው፡፡ የመንግሥት የአስተዳደርና የአገልግሎት ተቋማት በሕጉ መሠረት ለዜጎች ፍትሐዊ አገልግሎት የሚሰጡና ኹሉንም ዜጎች በእኩልነት የሚያስተናግዱ አይደሉም፡፡ የአገሪቱን የልማትና የንግድ ሥራዎች በበላይነት የሚመሩት የመንግሥት ተቋማትም በአገሪቱ ሕግ መሠረት በዘርፉ ለተሰማሩ ዜጎችም ኾነ የግል ድርጅቶች ከአድልዎ የጸዳ ፍትሐዊ አገልግሎት የሚሰጡ አይደሉም፡፡ በዚኽም ምክንያት በንግድ፣ በኢንቨስትመንት፣ በኮንስትራክሽንና መሰል የአገሪቱ ወሳኝ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች ጥቂቶች ብቸኛ ተጠቃሚ ኾነዋል፡፡
ይህም በሥርዓቱ ውስጥ የሕግና የፖለቲካ አይነኬ ሕዋሶችን ፈጥሯል፡፡ እነዚህ ሕዋሶች ሥርዓቱ የሕግ የበላይነትን በመጣስ የፈጠራቸው ከመኾኑ አኳያ፣ የእነዚኽ ሕዋሶች ህልውና እስከ ቀጠለ ድረስ ሙስናን ለመቆጣጠር የሚያስችል ርምጃ ለመውሰድ አይቻልም፡፡ በኢሕአዴግ ሥርዓት በመሾምና ንብረት በማግበስበስ መካከል እምብዛም ልዩነት የለም፡፡ በመኾኑም አንድ ሰው ተሾመ ማለት ከበረ እንደ ማለት ነው፡፡ ይህ ችግር በአገሪቷ ውስጥ በዜጎች መካከል ፍትሐዊ የሀብት ክፍፍልና ነጻ የኢኮኖሚ ውድድር እንዳይኖር ከማድረጉም በላይ አገሪቷን ወደማትወጣው አዘቅት ውስጥ ጨምሯታል፡፡
በመሆኑም ከላይ ያነሣናቸው የፌዴራሊዝም፣ የዴሞክራሲና የሙስና ችግሮች ባለው የኢሕአዴግ ሥርዓት መፍትሔ የሚያገኙት፣ ቀደም ብሎ እንደዚኽ ዓይነት ጥያቄዎችን የሚያስተናግድና የሚፈታ አሠራርና ተቋም ቢኖር ነበር፡፡ ኾኖም ይህ በሌለበትና ሕዝቡ ውስብስብና አስቸጋሪ ጥያቄ ባነሣበት በዚኽ ወቅት፣ አገዛዙ ሥርዓቱን ለማዳን የሚያስችል መፍትሔ ይዞ ይቀርባል ብሎ ማመን በጣም አስቸጋሪ ነው፡፡ ከእነዚኽ መፍትሔ አልባ ችግሮች ተነሥቼ፣ ኢሕአዴግ ወደ ‹‹ኦሮማይ ቀጣና›› እየገባ ነው ብዬ አምናለኹ፡፡
መጣጥፌን የምደመድመው፣ ከደበበ ሰይፉ፣ ‹‹ለራስ የተጻፈ ደብዳቤ›› ግጥም፣ በአኹኑ ወቅት እየተከሠተ ያለውን የፖለቲካ ቀውስ ያሳያል ብዬ ያመንኩበትን ስንኞች በማቅረብ ነው፡፡
---- በእሱ ውድቀት እናንተ እርካብ ብትመቱ
በብሶቱ ብትፈይዱ
በመክሊቱ ብትነግዱ፤…
ይህ ፍጹም ባድማ፣ ይህ ፍጹም ድቅድቅ ጨለማ
እሚበራ እንዳይመስላችሁ በእናንተ የይስሙላ ቁራጭ ሻማ፡፡
ግን መጋረጃው ያልተነሣ ተውኔት፣
ያልተፈታ ዕንቆቅልሽ፣ አለውና ጨለማ
           ነፋስ - እሳት ገሞራን፣ ሊታቀፍ ይችላልና ጠፍ ባድማ
ዐይን ያለው ይይ!
ልብ ያለው ያስተውል!
ጆሮ ያለው ይስማ!
********   **********
ከአዘጋጁ፡- ጽሁፉ የጸሃፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ  መሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን፡፡

       አምናና ዘንድሮ፣ ከፍተኛ እርዳታ ካገኙ ሦስት አገራት አንዷ ኢትዮጵያ ናት።
       ለረሃቡ 1.4 ቢ ዶላር (30 ቢ. ብር) እርዳታ ተገኝቷል። ግማሹ ከአሜሪካ! (የዩኤን መረጃ)፡፡
       3ቱ ትልልቅ ለጋሾች፣ የአሜሪካ፣ የእንግሊዝና የጀርመን መንግስታት ናቸው።
       ረሃብ የሚከሰተው፣ የእህል ምርት ምን ያህል ሲቀንስ ነው?
       በ1966 ዓ.ም፣ የእህል ምርት 13 ሚ. ኩንታል ቀንሶ ነበር። በ77ም እንዲሁ
            (የዓለም ባንክመረጃ)፡፡
       በ2007 ዓ.ም? ረሃብ የተከሰተው፣ የእህል ምርት በ5ሚ ኩንታል ስለቀነሰ ነው።                    (ስታትስቲክስ ኤጀንሲ)።

    አዴግ ሰሞኑን ያወጣውን ረዥም መግለጫ ሰምታችኋል? ከመግለጫው ውስጥ ጥቂት ዓረፍተ ነገሮችን በመመልከት፣ የአገራችን ፖለቲካ ምን እንደሚመስል መታዘብ እንችላለን። እንደተለመደው፣ እንደወትሮው፣ ተቃዋሚም፣ ደጋፊም እንደሚያደርገው፣ ለፕሮፓጋንዳ እስከጠቀመ ድረስ፣ ፍሬ እና ገለባውን እያደበላለቁ የመንጎድ ፖለቲካ፣ የአገራችን ባህል ነው፡፡  
በኢትዮጵያ ታሪክ ታይቶ የማይታወቅ ኃይለኛ ድርቅ መከሰቱን ይጠቅሳል መግለጫው። ከዚያስ? “ትርጉም ያለው እርዳታ” ባናገኝም፤ የረሃብ አደጋውን በራሳችን አቅም መቋቋም ችለናል ብሏል ኢህአዴግ፡፡ የአገሪቱ ኢኮኖሚ ስለተሻሻለ የረሃብ አደጋው እጅግ የከፋ ጥፋት እንዳላደረሰም ተናግሯል፡፡
እስቲ፣ እውነተኛውን መረጃ … እውነተኛውን ፍሬ ከገለባው ለመለየት እንሞክር፡፡ አዎ፣ የአምናው ድርቅ፣ ባለፉት 50 ዓመታት ከተከሰቱት የዝናብ እጥረት አደጋዎች ሁሉ የከፋ እንደሆነ አለማቀፍ የሙያ ተቋማት ገልፀዋል።  በዚሁ ድርቅ ሳቢያ ብዙ ሰው በረሃብ አለማለቁም፣ ደግ ነገር ነው፡፡ “ትርጉም ያለው እርዳታ አላገኘንም” የሚለው የኢህአዴግ አባባል ግን፣ ፍሬ የሌለው ገለባ ነው። ደግሞም ያስተዛዝባል። ዘንድሮ፣ ከሶሪያ በመቀጠል፣ ኢትዮጵያ ከፍተኛ የነፍስ አድን እርዳታ አግኝታለች፡፡ ይሄ፣ ትርጉም የለውም?
በደፈናው ሳይሆን፣ በቁጥር ቁልጭ ብሎ ይታያልኮ። ኢትዮጵያ፣ ባለፉት ሃያ ወራት ብቻ 1.4 ቢሊዮን ዶላር (30 ቢ. ብር) ነፍስ አድን እርዳታ እንዳገኘች የዩኤን መረጃ ይገልፃል፡፡
ይሄ ቀላል እርዳታ አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ እስከዛሬ ካገኘችው የረሃብ እርዳታ ሁሉ ይበልጣል፡፡ ያው፣ እንደሌላው ጊዜ፣ ዋናዋዎቹ ለጋሾች፣ የአሜሪካና የአውሮፓ መንግስታት ናቸው - በተለይም የአሜሪካ መንግስት፡፡ ከጠቅላላው እርዳታ ውስጥ፣ ግማሹ ከአሜሪካ መንግሥት የተሰጠ ነው - 684 ሚሊዮን ዶላር (15 ቢሊዮን ብር ገደማ)፡፡
ከአሜሪካ በመቀጠልስ?
በአውሮፓ ህብረት በኩልና በተናጠል በሚሰጡት እርዳታ፣ የእንግሊዝና የጀርመን መንግስታት ይጠቀሳሉ። እያንዳንዳቸው ከ140 ሚሊዮን ዶላር በላይ ለረሃቡ ለግሰዋል፡፡
እነዚህን እውነታዎች መካድ፣ ያስተዛዝባል፡፡ ምስጋና ቢስ መሆን ምን ጥቅም አለው? በእርግጥ፣ “እርዳታ መገኘቱ በቂ ነው” ማለት አይደለም፡፡
እርዳታው በጊዜ ካልደረሰና በወጉ ካልተሰራጨ፣ ብዙ ጥፋት ይከሰታል፡፡ የእርዳታ እህል ደግሞ፣ ቶሎ አይደርስም፡፡ እናም፣ መንግስት ቀደም ብሎ፣ እህል ገዝቶ ማምጣቱ ጥሩ ነው፡፡ ወጪውን በእርዳታ ያካክሳል፡፡
ይህም ብቻ አይደለም፡፡ መንግስት፣ በየመስኩ ሲዝረከረክና ችግሮች ሲያባብስ እንደምናየው፣ የእርዳታ ስርጭት ላይ ቢዝረከረክ ኖሮ ብዙ ጥፋት በደረሰ ነበር። ይህ አለመሆኑ መልካም ነው። ምን ለማለት ነው? ከፍተኛ እርዳታ መገኘቱን መካድ ሳያስፈልገው፣ “እኔም አደጋውን ለመቋቋም ጥሬያለሁ” ማለት ይችል ነበር፡፡ ፍሬውን ከገለባው መለየት ከጀመርን? “የአገሪቱ ኢኮኖሚ ስለተሻሻለ፣ የረሃብ አደጋው የከፋ አደጋ አላደረሰም” የሚለውን አባባል ደግ እንይ፡፡ የእህል ምርት አድጓል ማለት ነው፡፡ እንዴት ነው ነገሩ? የእህል ምርት ካላደገማ በረሃብ እናልቃለን፡፡ በሃያ ዓመት ውስጥኮ፣ የአገሪቱ የህዝብ ቁጥር በእጥፍ ጨምሯል፡፡ የእህል ምርት ካላደገ፣ በእርዳታም መዳን አይቻልም፡፡ ይልቅስ፣ ዋናው ጥያቄ፣ “የእህል ምርት በምን ያህል መጠንና በምን ያህል ፍጥነት አደገ?” የሚል ነው፡፡
የእህል ምርትን ከህዝብ ብዛት ጋር ማገናዘብ እንችላልን፡፡ ከ1950 ዓ.ም ጀምሮ፣ ንጉሱ እስከወረዱበት ድረስ የተመረተውን የእህል ምርት እንመልክት፡፡
የዓለም ባንክ መረጃ እንደሚያመለክተው፣ ያኔ በየዓመቱ በአማካይ፣ ለአንድ ሰው 180 ኪሎ እህል ይመረት ነበር፡፡ ለሃያ ዓመታት፣ እስከ 1966 ዓ.ም ድረስ፣ እንዲህ ነበር የቀጠለው፡፡ ንጉሱ እስከወረዱበት ዓመት ድረስ ማለት ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ግን፣ ማሽቆልቆል ጀመረ። በደርግ ዘመን፣ አመታዊው የእህል ምርት፣ ለአንድ ሰው ከ140 ኪሎ ግራም በታች ነበር ይላል መረጃው፡፡ በኢህአዴግ ዘመንም ቶሎ አልተሻሻለም፡፡ የእህል ምርት በንጉሱ ዘመን ወደነበረበት ደረጃ የተሻሻለው፣ በ2002 ዓ.ም ነው፡፡
ምን ማለት ነው? “የእህል ምርት አድጓል” ተብሎ ሲነገር፤ “አገሬው አለፈለት፤ በለፀገ፤ ተትረፈረፈ” ማለት አይደለም፡፡ “ከ35 ዓመታት በፊት ወደነበረበት የምርት ደረጃ ተሻሽሏል” እንደማለት ነው፡፡ በሌላ አነጋገር፣ ያው፣ … እንደያኔው፣ ዛሬም ድህነት ውስጥ ነን፡፡ እንደያኔው ዛሬም፣ ለድርቅ እና ለረሃብ በጣም ቅርብ ነን፡፡ አፋፍ ላይ ነን ከታች ገደል፣ ከላይ ናዳ፡፡

· ሳንፈራረጅ በውይይት ችግሮቻችንን መፍታት አለብን
· ጥያቄዎች ሳይወሳሰቡ በጊዜ መፈታት አለባቸው
· ህዝብ መተንፈሻ ሲያጣ አደባባይ ይወጣል

“ኢትዮጵያዊነት ላይ ስራ አልተሰራም”
ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ በርሄ (የኢኮኖሚ ባለሙያ)

ህገ መንግስቱ በሚፈቅደው መሰረት የህዝብ ድምፅ    መሰማት አለበት፡፡ የህዝብ ድምፅ በሚሰማበት ጊዜ በተለይ ህዝብ ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ ሲፈልግ ለመንግስት ማሳወቅ ያስፈልጋል። ይሄ በሰለጠኑ ሀገራትም የሚደረግ ነው፡፡ መንግስት አስፈላጊውን ጥበቃ እንዲያደርግ ነው ይህ የሚሆነው፡፡ እኛ ሀገር አሁን ባለው ሁኔታ መንግስት ራሱ እንደሚናገረው የሙስና መስፋፋት፣ የመልካም አስተዳደር እጦት፣ በተለይ ወጣቱ የስራ እድል አለማግኘቱ፣ መንግስት ከዩኒቨርስቲ ተመርቆ ለሚወጣው በመቶ ሺዎች የሚቆጠር የተማረ ኃይል የስራ እድል አለመፍጠሩ ----- በሀገሪቱ ካሉ ወቅታዊ ችግሮች ተጠቃሽ ናቸው፡፡
በሌላ በኩል በዋናነት በህገ መንግስቱ አንቀፅ 39 ላይ የተጠቀሰው የማንነት ጉዳይ እየተስፋፋ ሄዶ የት ነው የሚደርሰው የሚለው አሳሳቢ ነው። ህገ መንግስቱ የማንነት ጥያቄን እስከፈቀደ ድረስ መንግስትም ማክበር አለበት፡፡ ግን እኔ እንደማስበው ከሆነ፣ እኛም በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ሆነን ካነሳናቸው ጥያቄዎች መካከል የመሬትና የብሔር ብሔረሰቦች ጉዳይ ዋነኞቹ ነበሩ፡፡ አሁን ኢትዮጵያ ውስጥ ብሔር ብሔረሰቦች ቋንቋቸው ባህላቸው ተከብሮላቸዋል፡፡ ግን ይሄ ከተረጋገጠ በኋላ “ኢትዮጵያዊነት” የሚለው ላይ ስራ አልተሰራም፡፡ ሁላችንም ኢትዮጵያውያን ነን የሚለውን በተለይ አዲሱ ትውልድ እንዲያወቀው የማድረጉ ጉዳይ ብዙ ትኩረት አልተሰጠውም፡፡ ሌላው የሰብአዊ መብት አከባበር ጉዳይ ነው፡፡ ትልቁ የመንግስት ስራ ያለው ወረዳዎች አካባቢ ነው፡፡ የመሬት፣ የፍትህ፣ የፀጥታ የመሳሰሉ ጉዳዮች በቀጥታ ከህዝቡ ጋር በሚገናኙት በነዚህ የወረዳ አመራሮች እጅ ነው ያለው፡፡ እነዚህ ሰዎች ብቃት ያላቸው መሆን አለባቸው፡፡ መንግስት ልማቱን የሚያቀነባብሩትና ከህዝቡ ጋር በቀጥታ የሚገናኙት ወረዳዎችና ዞኖች መሆናቸውን በመገንዘብ፣ በከፍተኛ ደረጃ ብቃት ያላቸው ሰዎች መመደብ አለበት፡፡ ከማንም በላይ እነዚህ ሰዎች ህዝቡን አዳምጠው ምላሽ የሚሰጡ መሆን አለባቸው፡፡ በክልል ወረዳ ድንበሮች አካባቢ ያለ ግንኙነትና የልማት ሁኔታዎችን ብቃት ያላቸው ሰዎችን በመመደብ መስራት ያስፈልጋል፡፡
ራሳቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃ/ማርያም፤ በኦሮሚያ በደረሰው ጉዳይና ባጋጠመው ችግር ይቅርታ መጠየቃቸው በራሱ መንግስት ህዝቡን እያዳመጠ ነው እንድል ያደርገኛል፡፡ ከዚያም አልፎ በመግለጫዎች የህዝብን ጥያቄ እያዳመጠ መሆኑን ለመገንዘብ ያስችላሉ፡፡ የአዲስ አበባ ፊንፊኔ ዙሪያ ማስተር ፕላን እንዲቆም ማድረጉ ሌላው ትልቁ ነገር ነው፡፡
ከህዝቡ የሚነሱ ጥያቄዎች ብዙ አይነት ናቸው፡፡ አንዳንዱ የማንነት ጥያቄ ነው፡፡ ቅማንት፣ ወልቃይት የመሳሰሉት ተጠቃሽ ናቸው፡፡ እነዚህ ጥያቄዎች ህገ መንግስቱን መሰረት በማድረግ በቀላሉ መፈታት የሚችሉ ይመስለኛል፡፡ በመንግስት ደረጃ ደግሞ በከፍተኛ ስልጣን ላይ ያሉት ጥያቄው ቢገባቸውም፣ በቀዬው ያሉት ባለስልጣናት ግንዛቤው ይኖራቸው ይሆን የሚለው ሌላው ጥያቄ ነው፡፡ በመልካም አስተዳደርና በሙስና ጉዳይ ላይ ዋና ተዋናይ ሊሆኑ የሚችሉት መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችና ነፃ ፕሬስ ናቸው፡፡ ነፃ ፕሬስ በተለይ የምርመራ ጋዜጠኝነትን ተግባራዊ አድርጎ፣ እንዲህ ያሉ ንቅዘቶችን መርምሮ ማውጣት አለበት። በተለይ ሙስና ላይ ብዙ ሊሰሩ ይገባል፡፡ ግን ይሄን ለማድረግ አሁን ያሉት ነፃ ሚዲያዎች አቅም ተፈጥሮላቸዋል ወይ የሚለው የኔም ጥያቄ ነው፡፡ በሽግግሩ ጊዜ ወደ 90 ጋዜጦች ነበሩ፡፡ እነዚህ ጋዜጦች ሁሉንም ነገር በድፍረት ያወጡ ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ እያነሱ መጥተው አሁን ያለበት ደረጃ ደርሷል፡፡ አሁን እንደምናየው ቅዳሜና እሁድ የሚወጡ ጋዜጦች፤ በማተሚያ ቤት ችግር ለረቡዕ ነው እየደረሱ ያሉት። መንግስት ይሄን የሚዲያ ዘርፍ ማነቆዎች መፍታት ይገባዋል፡፡
ህዝብ የታመቀ ችግር ሲመጣ ነው ሰላማዊ ሰልፍ የሚወጣው፡፡ መተንፈሻ ሲያጣ አደባባይ ይወጣል። እነዚህ ነገሮች ወደ ንብረት ውድመትና የህይወት ጥፋት እንዳይሄዱ ጥንቃቄ ይሻል፡፡ ምናልባትም እንደ ደቡብ ሱዳን፣ በአራት ወገን ጦርነት ውስጥ እንዳለችው ሱዳን (ኮርዶፋን፣ ዳርፉር፣ አቢዬ፣ ብሉ ናይል-----ጦርነት ላይ ናቸው)፣ ሶማሊያ ወዘተ-- እንዳንሆን ከወዲሁ ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ እንዲህ ያሉ ተቃውዎችም ሲነሱ የሀገሪቱን ሉአላዊነት ሳይፈታተኑ መንግስት ማስተካከል ያለበትን ነገር ቢያስተካክል፤ መቀየር ያለበት ነገር ቢቀይር፤ የተቃውሞ ኃይሎችም ራሳቸውን አደራጅተው፣ ህዝቡን አሳምነው የመንግስትን ስልጣን በሰላማዊ ምርጫ የሚይዙበት አካሄድ ነው መከተል ያለባቸው፡፡ አሁን በሀገሪቱ ያሉት ፓርቲዎች 90 ቦታ የተከፋፈሉ፣ አንድ አጀንዳ ይዘው መውጣት ያልቻሉ ናቸው፡፡  የ97 ምርጫ ጊዜ የቅንጅት ኃይሎች፣ በፓርላማው 172 ያህል ወንበር ነበር ያገኙት። የእነሱ ወደ ፓርላማ አለመግባት የኢትዮጵያን ዲሞክራሲ ክፉኛ የጎዳው ይመስለኛል፡፡ ያኔ ህዝቡ መርጧቸው ፓርላማ አለመግባታቸው፣ብዙዎችን ተስፋ አስቆርጧል፡፡ አሁን ህዝቡ አደባባይ ወጥቶ የሚናገረው ስለከፋውና ስለቸገረው ነው፡፡
በአረብ ሀገራት በእነ ቱኒዚያ፣ ግብፅ፣ ሊቢያ በመሳሰሉት ሲካሄድ የነበረው አመፅ በሶሻል ሚዲያ ብቻ አልነበረም የተመራው፡፡ እርግጥ ነው ሶሻል ሚዲያ አገልግሎት ነበረው፡፡ ዋናው ግን የሙስሊም ወንድማማቾች ህብረት የሚባሉ ከ50 ዓመታት በላይ ሲደራጁ የቆዩ ኃይላት ነበሩ አመፁን በባለቤትነት የመሩት፡፡ እኛ ሀገር ዋናው ችግር ሀገር ሳይፈርስ ፀጥታ ሳይደፈርስ፣ የህዝብ ህይወት ሳያልፍ፣ ንብረት ሳይጠፋ ሰላማዊ የመንግስት ስልጣን ሽግግር ማድረግ ይቻላል ወይ የሚለው ነው። ተቃዋሚዎች ይሄን ለመፍጠር አስበው መደራጀት ያስፈልጋቸዋል። ምናልባት የቅንጅት ምሳሌ ጥሩ ሊሆን ይችላል፡፡ ግን ህዝቡ ብቻ የሚንቀሳቀስ ከሆነ የትም አያደርስም፤ ሀገር ነው የሚያፈርሰው። መንግስት ደግሞ የሀገሪቱንና የህዝቡን ፀጥታ ማስከበር አለበት፡፡ ሰላማዊ ሰልፍ ከመደረጉ በፊት ለመንግስት ማሳወቅ ያስፈልጋል፡፡ መንግስትም እንዲህ ያሉ ሰልፎችን መፍቀድ አለበት። ምክንያቱም በሌላ መድረክ ሊሰማ የማይችለውን የህዝብ ቅሬታዎች የሚሰማበት መድረክ ይሆናል፡፡
እነ ሂውማን ራይትስ ዎች፣ እነ አምነስቲ ኢንተርናሽናልም የሰብዓዊ መብት ጥሰት ሪፖርቶችን የሚያወጡት በስልክና በመሳሰሉት በሚያገኙት መረጃ ላይ ተመስርተው ነው፡፡
ምናልባት እነዚህ ድርጅቶች ሀገር ውስጥ ገብተው የሚከናወኑ ነገሮችን ተመልክተው፣ የሰብአዊ መብቶች መጓደልን ሪፖርት ቢያደርጉ መንግስትን ይጠቅመዋል እንጂ አይጎዳውም፡፡ አሁን በውጭ ሆነው የሚያቀርቡት ሪፖርት ችግሩን እያባባሰው ያለ ይመስለኛል፡፡ በሌላ በኩል በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ብዙ ቅሬታ እንዳላቸው ያስታውቃሉ፡፡
መንግስት እነዚህ ሰዎችን በመቅረብ ሀገራቸውን የሚያገለግሉበትን ነገር ማመቻቸት አለበት፡፡ ጥያቄያቸው ላይ መነጋገር ያስፈልጋል፡፡ በዜግነታቸው የሚገባውን ክብር ሰጥቶ መንግስት ማነጋገር አለበት፡፡   

==================================

“በውይይት ችግሮቻችንን መፍታት አለብን”
ፕ/ር አህመድ ዘካሪያ (የዓለም እርቀ ሰላም ግብረ ሰናይ ድርጅት አመራር)

እኛ እንደ ሀገር ሽማግሌዎች የማረጋጋት ስራ ነው በዋናነት መስራት ያለብን፡፡ መፍትሄውን የሚያወያዩ አካላት ናቸው የሚያስቀምጡት፡፡ እንደ ሀገር ሽማግሌ፣ የህግም የፖለቲካም ስልጣን ስለሌለን የሞራል ጫና የማሳረፍ ሚና ነው የሚኖረን። እኛ ሰላም እንዲሰፍን፣ የተጋጩ እንዲታረቁ ነው የምንጠይቀው፡፡
ጦርነትን አንፈልግም፡፡ የሀሳብ ግጭት ከሆነ በጠረጴዛ ዙሪያ ይፈታል፡፡ ደም መፋሰስ ለዚህች ሀገር አይበጅም፡፡ ህገ መንግስቱን አይቶ እንደገና ማስተካከል የሚያስፈልገው ነገር ካለም ማስተካከል ይገባል፡፡  
አሁን ያለው ጥያቄ ከአስተዳደር ጉዳይ ጋር የሚያያዝ ይመስላል፡፡ ጥያቄውን ህገ-መንግስቱን መሰረት አድርጎ መፍታት ያሻል፡፡ የሰለጠኑት ሀገራትም የራሳቸው ችግር አለባቸው፤የመፍትሄ አሰጣጣቸው ነው ከኛ የሚለየው፡፡ የሰው ልጅ ትልቁ ከፈጣሪ ያገኘው ችሮታ የማስተዋል፣ የማመዛዘንና የመፍረድ ኃይልን ነው፡፡ ፈጣሪ እኒህን ከሰጠን የመፍትሄ ምንጮች መሆን አለብን፡፡ ህዝቡን በነዚህ ባህሪዎች ውስጥ እንዲገባ ማድረግ አለብን። ያለበለዚያ እቺ ሀገር ለማንም የማትሆን አገር ትሆናለች፡፡
አሁን ትልቁ ጦርነታችን ረሀብ ነው፤በየጊዜው እየመጣ የሚፈታተነን፡፡ ግን እሱንም ማሸነፍ ያቃተን ይመስላል፡፡ አንዳንዴ ረሀብን ማሸነፍ ስላቃተን ይሆን የምንጣላው ብዬ አስባለሁ። እንደ ኢትዮጵያዊነታችን አንድ የሆንን ህዝቦች፣ እርስ በእርስ የምንናቆርበት ምክንያት አይገባኝም፡፡ ለኢኮኖሚ በሽታው መድኃኒት ብንፈልግለትና ትንሽ ችግር ባያጣላን ጥሩ ነው፡፡ እኔ መንግስት፤ ህዝብ ለማለት አልፈልግም፡፡ ምክንያቱም መንግስትም ህዝብ ነው፡፡ ከኛው ነው የመጡት፡፡ ሳንፈራረጅ በውይይት፣ በንግግር ችግሮቻችንን መፍታት አለብን፡፡

======================================

“ህገ መንግስቱ ለህዝብ እንጂ፣ህዝብ ለህገ መንግስቱ አይደለም የተሰራው”

አቶ ክቡር ገና

ጥያቄውን ያነሳው አካል በግልፅ ባይወጣም ጥያቄ ተነስቷል፡፡ ጥያቄዎቹ የአንድ አካል ብቻ ሳይሆኑ በብዙ ሰዎች የሚንሸራሸሩም ሆነዋል። ስለዚህ መልስ አሰጣጥ ላይ ከፍተኛ ጥንቃቄ ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡ አንደኛ በህዝቡ የተነሱትን ችግሮች መሰረታዊ ምክንያት ሳይሆን ከላይ የሚታዩትን ብቻ ለመቅረፍ ከተጣረ ችግሩ ለጊዜው ጋብ ይላል እንጂ አይጠፋም። በአጠቃላይ አሁን የተነሱ ጥያቄዎች ከጊዜ በኋላ ሊነሱ እንደሚችሉ ይታወቁ የነበሩ ጥያቄዎች ናቸው፡፡ እነዚህን ጥያቄዎች በሁለት አይነት መንገድ መመለስ ይቻላል፡- በኃይልና  በፖለቲካዊ መፍትሄ፡፡ የኃይል አማራጭ ምን ያህል ምላሽ ይሰጣል የሚለው አጠያያቂ ነው። ፖለቲካዊ መፍትሄ ይሰጥ ከተባለ ግን ረጅም ጊዜ ቢወስድም፣ ቁጭ ብሎ መነጋገርና መደራደር ያስፈልጋል፡፡ ለአንድ ጥያቄ አንድ መልስ በሚል ብቻ ሊታለፍ የሚችል ችግር አይደለም፡፡ መጀመሪያ መሰረታዊ ችግሩን መመርመር ያስፈልጋል፡፡ ጥያቄው ከጠያቂዎች ሲመጣ በትክክለኛ መንገድ ስላልመጣ፣በትክክል ላልመጣ ጥያቄ በትክክል ምላሽ ላይሰጥበት ይችላል፡፡ ነገር ግን አንዳንዴ መንግስትም ጥያቄው ባይመጣም፣ጥያቄውን ራሱ ፈጥሮ መመለስ አለበት።
ጥያቄዎቹን በአጠቃላይ ስናያቸው ፍትሃዊ የሀብት ክፍፍል፣ የአመራር ሁኔታ፣ የአገልግሎት አሰጣጥ ፍትሃዊነት፣የሙስና ችግርን በሙሉ የሚያካትቱ ነው የሚመስሉት፡፡ ጎንደር የተነሳውን ጥያቄ ስንመለከት፣ ከግዛት ጋር የተያያዘ ነው፡፡ እነዚህን ጥያቄዎች በጊዜ ምላሽ መስጠት ያስፈልጋል። ሳይወሳሰቡ በጊዜ መፈታት አለባቸው፡፡ ትክክለኛ ምላሽም ማግኘት አለባቸው፡፡ እንደኔ እነዚህ ብቻ አይመስሉኝም ምክንያቶቹ፡፡ ህዝቡ የመተንፈሻ መድረክ ማጣቱ አንዱ ምክንያት ይመስለኛል። የኢትዮጵያ ህዝብ በየ5 ዓመቱ አንዴ ድምፁን እንዲሰጥ ብቻ ነው በምርጫ የሚጠየቀው፡፡ ከዚያ በኋላ መነጋገሪያ መድረክ የለም፡፡ ለምሳሌ አሁን ፓርላማውን ስናይ፣መቶ በመቶ አንድ አካል ሆኖ ሃሳብ እንደተፈለገው እንዳይንሸራሸር አድርጓል። ምላሽ የማያገኙ ነገር ግን በየጊዜው የሚነሱ ጥያቄዎችም አሉ፡፡ ግን ብዙ ጊዜ የሚደረገው መልዕክቱን ትቶ መልዕክተኛውን መደብደብ ነው። እነዚህ ነገሮች ሲደማመሩ ነው ህዝቡ እንዲህ ያለ እርምጃ የሚወስደው፡፡
እንዲህ ያለውን ችግር ያስተናገዱ በርካታ የዓለም ሀገራት አሉ፡፡ በእንዲህ ያለው ችግርም የጠፉ ሀገራት አሉ፡፡ ዩጎዝላቪያ የምትባለው ሀገር ልክ እንዲሁ በዘር በብሄር ተለያይታ፣ኋላ ላይ በ1980 ከሀገራት ዝርዝር ጠፍታለች፡፡ ከዚህ እኛም መማር አለብን፡፡ ህገ-መንግስቱ ለህዝብ እንጂ ህዝብ ለህገ-መንግስቱ አይደለም የተሰራው፡፡ ስለዚህ ጥያቄዎቹ በሙሉ በፍርሃት ሳይሆን በግልፅ መውጣት አለባቸው፡፡ የችግሩ ፈቺ የተባለው አካልም ከህዝቡ ሳይጠብቅ ራሱ ጥያቄዎቹን ፈጥሮ ለመፍታት መንቀሳቀስ አለበት፡፡ ችግሩ ሊፈታ የሚችለው ሁሉም በእኩል ለችግሩ መፍትሄ ለማምጣት ሲረባረብ ብቻ ነው፡፡

1- ለተቃውሞ አደባባይ በተወጣ ቁጥር ግጭቶች
እየተከሰቱ፣የዜጎች ህይወት እንዳይጠፋና ንብረት
እንዳይወድም ምን ይደረግ ይላሉ?
ሀ) ህገ-መንግስቱን አክብሮ ማስከበር!
ለ) የዳበረ የዲሞክራሲ ባህል ካላቸው አገራት ልምድ
መውሰድ!
ሐ) ለሰዎች ህይወት ትልቅ ዋጋ መስጠት!
መ) ተቃውሞውንም ምላሹንም ሰላማዊ ማድረግ!
ሠ) ጥይት ከመተኮስ፤አስለቃሽ ጭስ መተኮስ!
2- የጎንደር ነዋሪዎች ሰሞኑን ለ3 ቀናት ሰላማዊ የቤት
ውስጥ አድማ አድርገዋል፡፡ ብዙዎች በትብብራቸውና
በጽናታቸው ተደንቀዋል፡፡ እርስዎስ ምን አሉ?
ሀ) ቁጥር 1 አድናቂያቸው ነኝ!!
ለ) አድማው ህይወትና ወጪ ቆጣቢ ነው!!
ሐ) ትብብሩ ለተቃውሞ ብቻ ሳይሆን ለዕድገትም
ይቀጥል!
መ) ህዝባዊ ተቃውሞን ሳያዘምኑት አይቀርም!
ሠ) የጸጥታ ሃይሉ ቤት ልግባ አለማለቱ!
3. የፌደራል ሥርዓቱ ለአንድነታችን አደጋ ነው ወይስ
ዋስትና ነው?
ሀ) እያየነው፤ከባድ አደጋ ነው እንጂ!
ለ) አደጋም ዋስትናም አይሆንም!
ሐ) እንደ አገር የምንቀጥለው በፌዴራል ሥርዓቱ
ብቻ ነው!
መ) ለአንድነታችን አደጋም ዋስትናም እኛው ነን!
ሠ) ኢትዮጵያዊነት ዳግም ያንሰራራል!
4. በየአካባቢው የሚከሰቱ ህዝባዊ ተቃውሞዎች
በእርግጥ መንግስት እንደሚለው፣በውጭ ሐይሎች
የሚመሩ ናቸው ብለው ያምናሉ?
ሀ) ሰላማዊ ተቃዋሚዎችን የሚገድሉት የውጭ
ሃይሎች እንዳይሆኑ!
ለ) የሰለቸ ፕሮፓጋንዳ ነው!
ለ) አሁንም መንግስት የነቃ አይመስልም!
ሐ) የእኔ ማመን አለማመን ለውጥ አያመጣም!
ሠ) መንግስት ወደ ውጭ ከሚጠቁም ቤቱን ያጽዳ?!
5. በቅርቡ በኦሮሚያና በአማራ ክልሎች የተነሱ ህዝባዊ
ተቃውሞዎችን ተከትሎ በተከሰቱ ግጭቶች በጸጥታ
ሃይሎች የተገደሉ ዜጎችን ቁጥር የሚያጣራ ታዛቢ ቡድን
ለመላክ ተመድ ጥያቄ ቢያቀርብም መንግስት ውድቅ
አድርጎታል፡፡ የመንግስት ውሳኔ ተገቢ ነው ይላሉ?
ሀ) አይደለም ብል ምን አመጣለሁ!
ለ) ራሱ አጣርቶ ተመጣጣኝ እርምጃ ነው ይለናል!
ሐ) እንኳን ተመድን ህዝብንስ መች ተቀበለ!
መ) መንግስት አዛዥ ናዛዥ ሆኗል!
ሠ) አልልም!
(N.B- ከተሰጡት ምርጫዎች ውስጥ ለእርስዎ
የሚስማማ ከሌለ፣
የራስዎትን ምርጫ (ረ) የማካተት መብትዎ የተጠበቀ
ነው!!!)

Sunday, 21 August 2016 00:00

‘ያላየነው ጉድጓድ…’

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ሰዉ ክፉ ሆኗል…ምናምን ስንል…አለ አይደል… ‘ጨለምተኛ’ ምናምን የሚባልበት ዘመን ነበር፡፡
እዛ ማዶ ሆኖ ክፉ ሰው ተጣራ
እዚህ ማዶ ሆኖ ክፉ ሰው ወይ አለው
ጎበዝ ጠንቀቅ በል ይህ ነገር ለእኛ ነው
የሚሏት መአት ጊዜ የምንጠቅሳት ስንኝ ዘንድሮም…ድምጿን ጨምራ እያቃጨለች ነው፡፡
እኔ የምለው…ክፋት እንዲህ በእግረ ሙቅ ጠፍሮ የያዘን፣ የሆነ በጨረር ምናምን የላኩብን ነገር አለ እንዴ! ቂ…ቂ…ቂ… ልክ ነዋ…የክፋታችን ልክ እኮ ወሰንም እያጣ ነው፡፡
የዚህ የእንጀራና ጄሶ ቅልቅል ነገር እኮ…አለ አይደል…‘ትልቁን ስዕል’ የሚያሳይ ነው፡፡ ይሄ አላግባብ ትርፍ የማግኘት ምናምን አይነት ነገር ብቻ አይደለም፡፡ ይልቁንም…አለ አይደል… የክፋት፣ የሰብአዊነት ማጣት፡ የሞራል ዝቅጠት ምልክት ነው።
የምግብ ነገር ካነሳን አይቀር ይቺን ስሙኝማ… ሴትዮዋ ምግብ ቤት ገብታ አሳ ታዛለች፡፡ እናላችሁ…አሳው በደንብ ሳይበስል ይመጣላታል፡፡ በለብ ለብ ነው የተሠራው፡ ኃላፊው ይጠራልኝ ብላ ይጠራላታል፡፡ ሰውየውንም…
“ይሄ አሳ ሲያዩት አያምርም፣” ትለዋለች፡፡ ኃላፊው ምን ቢላት ጥሩ ነው…
“እመቤቴ፣ ለአሳው እዘኚለት እንጂ…አንቺም ሞተሽ እንዲህ ለብ ለብ ቢያደርጉሽ አታምሪም ነበር፣” ብሏት አረፈ፡፡
እግረ መንገዴን…ከተማ ውስጥ አንዳንድ ቦታ… ‘አንቺም ሞተሽ እንዲህ ለብ ለብ ቢያደርጉሽ አታምሪም’ አይነት ስሜት የሚያሳዩ አስተናጋጆች አሉ፡፡ ኮሚክ እኮ ነው…“ይሄ ምግብ በምን የሚሠራ ነው?” ስትሉ… “ቆይ ጠይቄ ልምጣ…” እያሉ ማድቤት የሚመላለሱ አስተናጋጆች ስታዩ አስቸጋሪ ነው፡፡
እናማ…‘ያላየነው ጉድጓድ እየዋጠን’ ተቸግረናል፡፡
መንገዱ ‘ወርቅ ነው፣ ጨርቅ ነው’ ምናምን ብለን ስንሄድ ያላየነው ጉድጓድ ውስጥ ዘው ማለት ዕጣ ፈንታችን አይነት ነገር ሆኗል፡፡
ጉዳይ ለማስፈጸም ከዚህ ቢሮ እዛኛው ቢሮ ስንንከራተት ‘ያላየነው ጉድጓድ’ ይደነቀርብናል፡፡
“አንተ እኮ ብትባበር…”
“ዝም ብለህ በባዶ ሜዳ ከምትሮጥ…”
ምናምን እየተባለ ‘ቋንቋው’ ከእኛ እየቀደመ አፍ መፍቻ ቋንቋችን እንኳን አልገባን እያለ አስተርጓሚ እያስፈለገን ነው፡፡ “ግዴታዬን ተወጥቻለሁ፣ መብቴ ይከበርልኝ…” ማለት የ‘ስታንድ አፕ ኮሜዲ’ ጸሁፍ ምናምን እየመሰለብን… አለ አይደል… “እውነቱን እኮ ነው…” ከመባል ይልቅ “ድንቄም…” እየተባልን መንገዳችን ጉድጓድ በጉድጓድ ሆኗል፡፡
እናማ…‘ያላየነው ጉድጓድ እየዋጠን’ ተቸግረናል፡፡
ከሰዎች ጋር ባለን ግንኙነት ‘ጥሬና ብስሉ’ እየተቀላቀለ የእኛንም ስሜቶች እያደበላለቀብን ግራ ገብቶናል፡፡ “መልካም ወዳጄ ነው፣ ለችግር ጊዜ ይደርስልኛል፣ ጉልበተኛ ቢያጠቃኝ የብረት አጥር ይሆነኛል፣ ቢከፋኝ ደገፍ ብዬ የማለቅስበት ትከሻ ይሆነኛል…” ያልነው ሰው ሳናስበው ‘አያ ጅቦ’ አይነት ነገር ይሆንብንና ከእሱ መሸሹ ሌላ ‘የህይወት ጥሪ’ ምናምን ይሆናል፡፡ በችግሩ ጊዜ ውለታ ውለንለታል፣ አይዞሀ ባይ ወዳጅ፣ ዘመድ ያጣ ጊዜ ከጎኑ ቆመናል…” ምናምን ያልነው ሰው ‘ዋናው ችግራችን’ ሆኖ ቁጭ ይላል፡፡
እናማ…‘ያላየነው ጉድጓድ እየዋጠን’ ተቸግረናል፡፡
ስሙኝማ…አሜሪካኖቹ በፕሬዝዳንቶቻቸው፣ በፖለቲከኞቻቸው፣ በሙያተኞቻቸው ላይ ቀልደው የሚበቃቸው አይመስሉም፡፡…ይኸው ሰሞኑን በትረምፕ ላይ የሚጻፍባቸውን እናይ የለ! እናላችሁ… ሦስት የቀዶ ጥገና ሀኪሞች ስለ ችሎታቸው ራሳቸውን ከፍ እያደረጉ ይናገራሉ፡፡ አንደኛው የቀዶ ጥገና ሀኪም…
“አንድ ሰው ድንገት በባቡር ሀዲድ ላይ ወደቀና ባቡሩ በላዩ ላይ ሄዶበት ሁለት እግሮቹ ከጉልበቱ በታች ተቆረጡ፡፡ እነሱን በቀዶ ጥገና አስተካክዬለት የኦሎምፒክ ማራቶን አሸናፊ ሆነ…” አለ፡፡ ሁለተኛው ደግሞ…
“አንዲት ሴትዮ ከመኪና መስታወት ጋር ትጋጭና ፊቷ ሙሉ ለሙሉ ይበላሻል፡፡ የተጎዳው ፊቷን በቀዶ ጥገና ካስተካከልኩላት በኋላ የሚስ አሜሪካን ውድድር አሸንፋለች…” ይላል፡፡ ሦስተኛው ምን ቢል ጥሩ ነው…
“አንዱ ሰው በድንገት አውሮፕላን ሞተር ውስጥ ገብቶ ሰውነቱ እንዳለ ይበታተናል፡፡ ከዛም ከአእምሮው ምስር የምታክል ቁራጭ …አገኘሁና ወደ ላቦራቶር ወስጄ እንደገና ሙሉ ሰው አደረግሁት፡፡ አሁን የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ሆኗል…”   ቂ…ቂ…ቂ…  ትረምፕ የሚሏቸው ሰውዬ ይሄንን አልሰሙም እንዴ!  
እናማ…አገሩ ሰው የሌለበት ምድረ በዳ የሆነ ይመስል ፎካሪና ጉራ ቸርቻሪ በዝቷል፡፡
እናማ…‘ያላየነው ጉድጓድ እየዋጠን’ ተቸግረናል፡፡
አንድ የቴክሳስ ሰው እንግሊዛዊው ላይ ቴክሳስ በጣም ትልቅ ግዛት ስለመሆኗ እየተነሰነሰበት ነበር… “ሰኞ ጠዋት ምስራቅ ቴክሳስ ውስጥ ባቡር ትሳፈራለህ፣ በምዕራብ አቅጣጫ ሙሉ ቀን ትሄዳለህ፣ ሌሊቱንም ስትሄድ ታድራለህ፣ በማግስቱ ጠዋት ገና ከቴክሳስ አትወጣም…” ይለዋል፡ እንግሊዛዊው ምን ቢል ጥሩ ነው…
“የእንግሊዝ ባቡሮችም እንዲህ ቀርፋፋ ናቸው…” አለውና አረፈው፡፡
እናማ…ለበጎ ብለን የተናገርነው ነገር፣ ለጨዋታ ብለን የቀለድነው ቀልድ፣ ለመተባበር ብለን ያቀረብነው ሀሳብ ጅራትና ቀንድ እየተተከለላቸው የምንለውን የሚሰማን ማግኘት የሰማይ ያህል ርቆናል፡፡ መንግሥተ ሰማያት የሚያደርስ ግንብ እየገነባን መቅሰፍት የወረደብን ይመስል አንዳችን የምንለው ለሌላኛችን ‘አልገባ’ እያለ… ሁሉም ተናጋሪ ሆኖ አንድም አድማጭ እየጠፋ ነው፡፡ አንዳንዴ ነገራችን የሞኝ ቢያስመስለንም ያን ያህል ሞኝነት እንኳን የለብንም፡ እናውቃለን፣ ግን ያላወቅን እንመስላለን…  ማወቅ ሁልጊዜም ያስከብራል ማለት አይደለምና፡፡
እሱስ ውሸቴን ነው
እኔም ብቻ አይደለሁ
በጣም እናውቃለን ሁላችን ሁላችን
አውቀን ባንፈጽምም
አውርተን ባንሠራም
ሰምተን ባናሰማም
በጣም እናውቃለን ሁላችን ሁላችን፣
የምትል የፈቃደ አዘዘ ግጥም አለች፡፡ እናማ… በባዶ ሜዳ ሲፎከርና፣ ጉራ ሲነዛ ዝም ብለን ስናዳምጥ ሞኝ መስለን ከታየን ‘ታሪካዊ’ ስህተት ነው፡፡
እናማ…እንዲህም ሆኖ ‘ያላየነው ጉድጓድ እየዋጠን’ ተቸግረናል፡፡
የሆነ ግንባታ ላይ የሚሠራ ሰው “የእኔን ያህል ጠንካራ ሰው የለም…” ምናምን እያለ የሥራ ባልደረቦቹ ላይ ይፎክራል፡፡ በተለይም አንድ በዕድሜ የገፉ ባልደረባውን ሁልጊዜ ይጨቀጭቃቸዋል፡፡ ሰውየውም ፉከራው እጅ፣ እጅ ይላቸውና…
“እሺ ከእኔ በላይ ጠንካራ ከሆንክ በገንዘብ እንወራረድ…” ይሉታል፡፡ ሰውየው ይስማማል፡፡ ሰውየውም…
“እኔ በዚህ ጋሪ ጭኜ እዛ ማዶ የማደርሰውን ማንኛውንም ነገር አንተ ጋሪው ላይ ጭነህ እየገፋህ መልሰህ ማምጣት አትችልም፣ ለዚህም የሳምንት ደሞዜን አስይዛለሁ ይላሉ…” ጉረኛውም…
“ሽሜው ትንሽ ነካ ሳያደርገው አይቀርም፡፡ እስማማለሁ…” ይላል፡፡
ከዛ ሰውዬው ጋሪውን ቀረብ አደረጉና ጉረኛውን ምን ቢሉት ጥሩ ነው… “በል ጋሪው ላይ ውጣ…” አሪፍ አይደል! ሰውየው ጋሪው ላይ ከሆነ እንዴት አድርጎ መልሶ እየገፋ ሊያመጣ ይችላል!
እናማ… ዝም ብሎ መፎከር፣ አገሩ ሰው የሌለበት ይመስል ጉራ መንዛት አሪፍ አይደለም፡፡ ብልጦቹ በሙሉ ተሰደው ሞኞች ብቻ ቀሩ ተብሎ ሹክ ተባለብን እንዴ!
እናማ…እንዲህም ሆኖ ‘ያላየነው ጉድጓድ እየዋጠን’ ተቸግረናል፡፡
ስሙኝማ…የሞኝነት ነገር ከተነሳ ይቺን ስሙኝማ…አንዱን ሰውዬ ማጅራት መቺዎች ከበው ሊዘርፉት ሲሉ በአልሞት ባይ ተጋዳይነት ልቡ እስኪጠፋ ይቧቀሳቸዋል፡፡ ከዛም ያሸነፉትና የገንዘብ ቦርሳውን ወስደውበት ሲከፍቱት ሁለት ዶላር ብቻ ያገኛሉ፡፡ ይሄኔ ተደንቀው…
“እንዲህ እስክትገጣጠብ የተቧቀስከው ለሁለት ዶላር ብለህ ነው!” ይሉታል፡፡ ሰውየው ምን አለ መሰላችሁ…
“እፎይ፣ ካልሲዬ ውስጥ የደበቅሁትን ሁለት መቶ ዶላር ታገኙብኛላችሁ ብዬ ፈርቼ ነበር…” ብሏቸው አረፈ፡፡  
‘ከማይታይ ጉድጓድ’ ይሰውራችሁማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

የጀርመን የውጭ ጉዳይ ሚ/ር ህገ-መንግስታዊ መብቶች ይከበሩ ብሏል

   የአለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ባለፉት ሳምንታት በኦሮሚያና በአማራ ክልሎች ለተቀሰቀሱ ተቃውሞዎችና ውጥረቶች ምክንያት በሆኑ ወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት እንዲያደርጉ ለኢትዮጵያ መንግስት፣ ለጸጥታ ሃይሎችና ለተቃዋሚዎች ጥሪ አቀረበ፡፡
በኢትዮጵያ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት መሪዎች በላኩልኝ መረጃ፣ ተቃውሞውን ተከትሎ በአገሪቱ የተፈጠረው ውጥረት አሁንም አለመርገቡንና በተቃዋሚዎችና በጸጥታ ሃይሎች መካከል የሚከሰቱ ግጭቶች እንደቀጠሉ መሆናቸውን ተገንዝቤያለሁ ብሏል - ምክር ቤቱ ትናንት ባወጣው መግለጫ፡፡ የፀጥታ ሃይሎች ባልታጠቁ ዜጎች ላይ ተመጣጣኝ ያልሆነ ሃይል እንዳይጠቀሙ የጠየቀው ምክር ቤቱ፣  ተቃዋሚዎችም ለግጭቱ መንስኤ በሆኑ ጉዳዮች ዙሪያ ከመንግስት ጋር ግልጽ ውይይት የሚደረግበትን መንገድ መሻት አለባቸው ብሏል፡፡
“በተቃውሞዎቹ ለህልፈተ ህይወት በተዳረጉት ዜጎች እንዲሁም በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች በተቃዋሚዎች ላይ በተፈጸመው እስርና ድብደባ ማዘናችንን እንገልጻለን” ብለዋል፣ የምክር ቤቱ የአለማቀፍ ጉዳዮች ኮሚሽን ዳይሬክተር ፒተር ፕሮቭ፡፡
በጀርመን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የሰብዓዊ መብቶች ፖሊሲና እርዳታ ኮሚሽነር ባረቤል ኮፍለር በበኩላቸው ባለፈው ረቡዕ ባወጡት መግለጫ፣ በአገሪቱ የተከሰቱት ግጭቶች በእጅጉ እንደሚያሳስቧቸው ጠቁመው፣ ሁሉም ወገኖች ከቀጣይ ግጭቶች እንዲታቀቡና በውይይት ችግሮችን በጋራ እንዲፈቱ ጠይቀዋል፡፡
የአገሪቱ ህገ- መንግስት ለዜጎች ያጎናጸፋቸው ሃሳብን በነጻነት መግለጽና ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግን የመሳሰሉ መብቶች መከበር አለባቸው ያሉት ኮሚሽነሩ፤ የጸጥታ ሃይሎች በተቃዋሚዎች ላይ የወሰዷቸው እርምጃዎችም የተመጣጣኝነት መርህን መጣስ አልነበረባቸውም ብለዋል፡፡

ግድያውን የፈጸሙት ለበቀል ነው ተብሏል

ባለፈው ሚያዝያ ወር ላይ በጋምቤላ ክልል በሚገኝ የስደተኞች የመጠለያ ጣቢያ የሚሰሩ 10 ኢትዮጵያውያንን በአሰቃቂ ሁኔታ ገድለዋል የተባሉ 23 ደቡብ ሱዳናውያን ስደተኞች ባለፈው ሰኞ በግድያ ወንጀል መከሰሳቸውን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
በጋምቤላ ጀዊ የስደተኞች የመጠለያ ጣቢያ ውስጥ ሁለት ደቡብ ሱዳናውያን ህጻናት በመኪና አደጋ ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ እነዚሁ 23 ደቡብ ሱዳናውያንም የህጻናቱን ሞት ለመበቀል በማሰብ፣ በስደተኞች ጣቢያው ውስጥ ተቀጥረው የሚሰሩ 10 የግንባታ ሰራተኞችን በአሰቃቂ ሁኔታ ደብድበው በመግደላቸው ክስ እንደተመሰረተባቸው ጠቁሟል፡፡
በተከሳሾቹ የግድያ ሰለባ የሆኑት አስሩ ኢትዮጵያውያን በህጻናቱ ግድያ ላይ እጃቸው እንደሌለበት የክስ መዝገቡ መግለጹን የጠቆመው ዘገባው፤ ግድያው መፈጸሙን ተከትሎ በአካባቢው ብጥብጥ መፈጠሩንና አንዳንድ ደቡብ ሱዳናውያን ስደተኞችም ጥቃት እንደደረሰባቸው አስታውሷል፡፡ በደቡብ ሱዳንያውያኑ ስደተኞች ከተገደሉት 10 ንጹሃን ኢትዮጵያውያን መካከል ሁለቱ ሴቶች መሆናቸውም ተነግሯል፡፡ በጋምቤላ ክልል ከ270 ሺህ በላይ ደቡብ ሱዳናውያን ስደተኞች እንደሚገኙም ዘገባው አስታውሷል፡፡


• ዘረኝነት፣ … ማብሪያና ማጥፊያ የለውም። ዛሬ ‘ኦን’፣ ነገ ‘ሳይለንት’ ማድረግ አይቻልም።
• በዘፈቀደ ማበላሸትና ማፍረስ እንጂ፣ በዘፈቀደ መገንባትና ማስተካከል አይቻልም።
 
ያረጀ ቴሌቪዥን፣ ብዥ ብዥ፣ እያለ ሲያስቸግር ምን እናደርጋለን? ‘ግራና ቀኝ’ ማንገራገጭ፣ መደለቅ!
ነቅነቅ ነቅነቅ ሲደረግ፣ ይስተካከል ይሆናል። መቼም፣ ምኞት አይከለከልም። ግን፣ ምኞት ብቻውን፣ አያዘልቅ። ያለ እውቀት፣ ያለ ሞያና ያለ ጥረት፣... ሌጣ ምኞት ብቻውን፣ እያሳሳቀና እያታለለ ገደል ይከታል። ግራ ቀኝ በማንገራገጭና በመነቅነቅ፣ የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎችን ማስተካከል ቢቻል ኖሮ፣... የተበላሹ ኮምፒዩተሮችና ቴሌቪዥኖች፣ መጋዘን ባላጣበቡ ነበር። ቴሌቪዥን መጠገኛ ቤት ሂዱ፣... ከወለል እስከ ጣሪያ ድረስ ተደራርበው አቧራ የለበሱ የቴሌቪዥን አይነቶችን ታያላችሁ።
ማንገራገጭና መነቅነቅ፣ አልፎ አልፎ ብልሽትን ያስተካክል ይሆናል። ግን ብልሽትንም ሊያባብስ ይችላል። ለዘለቄታው፣ የዘፈቀደ ንቅናቄ... መፍትሄ አይሆንም።
አሳዛኙ ነገር፣ አገራችን ኢትዮጵያ፣ እንደ ተበላሸ ቲቪ፣ ግራና ቀኝ የሚደልቅና የሚያንገራግጭ እንጂ፣ በእውቀት፣ በሙያና በጥረት፣ ላይ ተማምኖ፤ አሳምሮ የሚጠግንና የሚያስካክል ብልህ፣ ጥበበኛና ጀግና አላገኘችም። አንዱ፣ እንደመጣለት ሲደልቅ፣ ሌላኛው በተራው ለማንገራገጭ እየተነሳሳ፣ በዙር እየተቀባበሉ ያጦዙታል፡፡ በእርግጥ ይሄ፤ የኛን አገር ብቻ የሚመለከት ችግር አይደለም፡፡ ጦዘው ጦዘው መውጫ ወደታጣለት ትርምስ ውስጥ ገብተው የተዘፈቁ አገራት በየአቅጣጫው እያን ነው። እንዲያም ሆኖ፣ … ይሄን ሁሉ እያየንም፣ ትንሽ ቆም ብሎ ከምር የሚያስብ፣ እውነታን አገናዝቦ የጠራ የነጠረ ሀሳብ ለማበጀት የሚሞክር ሰው ብዙም የለም፡፡
በአንድ በኩል ነባሩን ፕሮፓጋንዳ እየዘረፉ፣ በሌላ በኩል በአፀፋ ምላሽ ነባር የአሉባልታ ባህልን እያቀጣጠለ አገሬውን ቀውጢ ያደርጉታል፡፡ በአንድ በኩል፣ መንግስት፣ ባለሀብቶች ላይ ጥርሱን እየነከሰና ሰዎችን ከመኖሪያቸው እያፈናቀለ፣ እንዳሻው በሰው ኑሮ ላይ አድራጊ ፈጣሪ ይሆናል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ፤ የባለሀብቶችን ስም በማጥፋት ንብረት የሚያቃጥል “የነፃነት ታጋይ” ዙሩን ያጦዘዋል፡፡
በአንድ በኩል፣ መንግስት በብሄር ብሄረሰብ ፖለቲካዊ አማካኝነት፣ ሰዎችን በጅምላ የማቧደን ቁማር ይጫወታል፡፡ በሌላ በኩልስ? ያው፣ በተመሳሳይ ቁማር፣ አደጋውን የሚያጋግሉ “ተቃዋሚ ታጋዮች” ተጨምረውበት አገሪቱ ትቀወጣለች፡፡
ፕሮፓጋንዳን በአሉባልታ፣ ጉልበትን በስድብ
መንግስት፣ ከእውነታ የራቀ የፕሮፓጋንዳ አባዜ እንደጠናወተው ራሱም አይክደውም፡፡ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን፣ የተነገረውን የሚደጋግም ተራ አዝማሪ እንዲሆን አድርገነዋል በማለት ባለስልጣናት ራሳቸውን ሲተቹ ሰምተናል፡፡ ከሌላ ሰው የሚመጣ ትችትንና አቤቱታን መስማት ግን አይፈልጉም፡፡ በጉልበት ማፈን፣ መፍትሄ ይመስላቸዋል፡፡
ትክክለኛው መፍትሄ ግን፣ እውነትን የሚያከብር ሃሳብና ውይይት ነው፡፡ አይደለም እንዴ? ነው እንጂ። ግን፣ ከበርካታ “ተቃዋሚ ታጋዮች” ብዙ ጊዜ የሚቀርበው መፍትሄ፣ ከመንግስት ፕሮፓጋንዳ ጋር የሚፎካከር አሉባልታ ነው፡፡
እንደ መንግስት ለጊዜው ጉልበት ባይኖራቸውም፣ ስልጣን እስኪይዙ ድረስ፣ የስድብ ዱላ ያዥጎደጉዱታል፡፡ የነሱ የአሉባልታና የስድብ ዘመቻ፣ ለመንግስት ጥሩ ሰበብ ይሆንለታል - ፕሮፓጋንዳና አፈና ለማስፋፋት። ፕሮፓጋንዳውና አፈናው ደግሞ በተራው፣ የአሉባልታና የስድብ አፀፋ ለማዝነብ ሰበብ እየሆነ፤ አገሬው የቅዠት አዙሪት ውስጥ ተዘፍቋል፡፡
“ችግሮችን በውይይት መፍታት ይቻላል” ብለው የሚያምኑ ሰዎች የሉም ማለቴ አይደለም። መኖርማ አሉ፡፡ ነገር ግን፣ ይህንን ምኞት እውን ለማድረግ፣ በቅድሚያ፣ “እውነትን የሚያከብር ስልጡን አስተሳሰብ” እንደሚያስፈልገን ይረሱታል። እውነትን ከምር የሚያከበር አስተሳሰብ ለመፍጠር ካልጣርን፣ “ውይይት … ውይይት” እያልን ብንውልና ብናድር ዋጋ የለውም፡፡ እውነት የማያከብር አገር ውስጥ፣ ፕሮፓጋንዳና አሉባልታ፣ አፈናና ስድብ እርስበርስ እየተቀባበሉ መንገሳቸው አይቀርም፡፡
የቅፅበት የቅፅበቷን፣ “ስዎች ኦን” “ስዎች ኦፍ”
በኑሮና በኢኮኖሚ ዙሪያ፣ ዋናዎቹ ጥያቄዎች “ሀብት ፈጠራ” እና “የንብረት ባለቤትነት መብት” ናቸው፡፡ በሌላ አነጋገር፣ በእያንዳንዱ ሰው ፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ ነፃ የገበያ ኢኮኖሚ… ወይም ደግሞ ጉልበተኛ እንዳሻው አዛዥ ናዛዥ የሚሆንበት “የእዝ ኢኮኖሚ” ናቸው አማራጮቹ፡፡
ያው፣ ብዙውን ጊዜ፣ ጉልበተኛው አዛዥ ናዛዥ፣ መንግስት ነው፡፡ አንዳንዴ፣ አልፎ አልፎ፣ “ተቃዋሚ ታጋዮች”፣ ከሰልፈኛ መሃል ገብተው፣ የሰውን ንብረት ያቃጥላሉ - ጉልበተኛ በሆኑበት ቅፅበት። ስልጣን ከያዙ ደግሞ፣. እንደዛሬው መንግስት፣ መደበኛ ጉልበተኛ ይሆናሉ፡፡ አዙሪት ነው፡፡
እንግዲህ አስቡት፡፡ መንግስት፣ ስለ “ንብረት ባለቤትነት መብት” በቁም ነገር ሲናገር ሰምታችሁ ታውቃላችሁ? እንዲው፣ ለወግ ያህል ብቻ ስለ “ነፃ ገበያ ኢኮኖሚ” ማውራት እንኳ ትቷል - ስንት አመቱ! ዛሬ የንብረት ባለቤትነት መብትን ሲያናንቅ፣ ነገ ንብረት ለሚያቃጥሉ ሰዎች አገሬውን እያመቻቸ መሆኑን ለማገናዘብ አይፈልግም፡፡ የዛሬ የዛሬዋን ብቻ ነው የሚያየው፡፡
እና፣ በዚህኛው ወር፣ በዚያኛው ከተማ፣ በተቃውሞ ሰልፍ መሃል፣ ጥቂት ነውጠኞች፣ የሰውን ንብረት ቢያቃጥሉ፣ … ምን ይገርማል? አብዛኛው ጨዋ ሰልፈኛ፣ ጥቂት ነውጠኞችን ለመከላከል የሚሳነው አለምክንያት አይደለም፡፡ ለሃብት ፈጠራና ለንብረት ባለቤትነት መብት ብዙም ክብር የለውም፡፡ ያኔ ጉልበተኞችና ነውጠኞች ይመቻቸዋል፡፡ በአንድ በኩል መደበኛው ጉልበተኛ መንግስት፣ በሌላ በኩል ነውጠኛ “ታጋዮች” እየተቀባበሉ፣ አገሬውን ያንገጫግጩታል፡፡
የብሄር ብሄረሰብና የሃይማኖት ፖለቲካ ቁማር
ሰዎችን በጭፍን ስሜትና በመንጋ ለማነሳሳት፣ የድጋፍ ሆይ ሆይታ ለመፍጠር፣ ተቀናቃኝን ለማጥፋት ነው፤ የቁማር ጨዋታውን የሚጀምሩት፡፡ ነገር ግን፤ ዛሬ የብሄር ብሄረሰብ ፖለቲካን እያራገበ፣ ቁማር የሚጫወት መንግስት፣ ነገ ሌሎች ተመሳሳይ ቁማርተኞች እንደሚመጡ ማወቅ የለበትም?
ዛሬ፣ ሃይማኖትን በመጠቀም፣ ጭፍን ስሜትን የሚያጋግል መንግስት፤ … ነገ፣ ከነገ ወዲያ በጭፍን የሚነሳሱ ብዙ መንጋዎችን እየፈለፈለ እንደሆነ መገንዘብ አይገባውም?
በዘር የማቧደን ዘመቻ የሚያካሂድ ተቃዋሚ፣ ለተመሳሳይ የዘረኝነት ቁስቁሾች አገሬውን እያመቻቸ እንደሆነ፣ አይታየውም?
አይታያቸውም የቅፅበት የቅፅበቷን በቁንፅል ለማየት ነው የሚፈልጉት፡፡ ነገር ግን ዘረኝነትና በጅምላ የመቧደን አስተሳሰብ፣ ጭፍን ስሜትና ጭፍን እምነት …  ስንፈልግ “ስዊች ኦን”፣ ስንፈልግ “ስዊች ኦፍ” ልናደርገው አንችልም፡፡
አገር ስንቀውጥበት ውለን፣ ማታ “ሳይለንት” አድርጎ መተኛት አንችልም፡፡







ባለፈው ቅዳሜ ነሐሴ 7 ቀን 2008 ዓ.ም በወጣው የጋዜጣችሁ እትም ላይ ‹‹የድሬዳዋ 10ኛ ዓመት የጎርፍ አደጋ አከባበር ከፍተኛ ቅሬታ አስነሳ›› በሚል ርዕስ በትክክለኛ መረጃ ላይ ሳይመሰረት ለቀረበው ዘገባ እንደሚከተለው ምላሽ ለመስጠት እንወዳለን፡፡
የድሬዳዋ አስተዳደር ከዛሬ 10 ዓመት በፊት ሐምሌ 28 ቀን 1998 ዓ.ም ሌሊት በከተማው ተከስቶ በነበረው የጎርፍ አደጋ የበርካታ ሰዎች ህይወት የቀጠፈና በሺዎች ለሚቆጠሩ ነዋሪዎች መጠለያ ማጣትና ንብረት መውደም ምክንያት የሆነበትን ቀን ከዚህ በፊት በሐይማኖት ተቋማት፣ በበጎ አድራጊ ግለሰቦችና ማህበራት በየዓመቱ ሲከበር መቆየቱ የአደባባይ ሀቅ ነው፡፡ የዘንድሮውም የአደጋውን 10ኛ ዓመት መታሰቢያ አስመልክቶ፤ አስተዳደሩ ለተጎጂዎች ያለውን አጋርነት  በልዩ ሁኔታ እንዲታሰብ ለማድረግና የጎርፍ አደጋውን በዘላቂነት ለመፍታት በአስተዳደሩ እየተደረጉ ያሉ ጥረቶችን ህብረተሰቡ እንዲያውቃቸው በማድረግ፣ከአደጋው ስጋት ተላቆ የተረጋጋ ሕይወት እንዲመራ ማድረግን ያለመ ተግባር በመሆኑ፣ ይህን ቅዱስ ዓላማ ከሚደግፉ ድርጅቶች ጋር በመሆን አክብሯል፡፡
በዚሁ የተቀደሰ አላማ መሰረት ነው፤‹‹በጎርፍ የተጎዱ ወገኖቻችን ሁሌም እናስባለን፤ስጋቱንም ለመቀነስ ተግተን እንሰራለን›› በሚል መሪ ቃል በልዩ ልዩ ዝግጅቶች እንዲከበር የተደረገው፡፡ በመታሰቢያ ዝግጅቱ ላይም በድሬደዋ የጎርፍ አደጋና ጎርፉንም ለመቀነስ ባለፉት አስር ዓመታት በተሰሩት ስራዎች ዙርያ፤ ከብሄራዊ አደጋ ስጋት ሰራ አመራር ኮሚሽን የተዘጋጀ ጽሁፍ እንዲሁም በስነ ልቦና ባለሙያ የቀረበ  ጥናታዊ ፅሑፎች ቀርቦ የተጎጂ ቤተሰቦች፣ የሀይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎችና ተጋባዥ እንግዶችና የአስተዳደሩ ኃላፊዎች በተገኙበት የፓናል ውይይት ተካሂዷል፡፡ በሌላ በኩል የጎርፍ አደጋውን በዘላቂነት ሊቀንሱ ከሚችሉ ተግባራት አንዱ በሆነው የችግኝ ተከላ ላይ የአስተዳደራችን ነዋሪዎች፣ የሰራዊት አባላት፣ ታዋቂ የሀገራችን የኪነጥበብ ባለሙያዎችና ጋዜጠኞች ከ4ሺህ በላይ ችግኞችን የተከሉ ሲሆን በጎርፉ ጉዳት ደርሶባቸው የነበሩ ግለሰቦች ያሉበት ሁኔታ የተጎበኘና በአስተዳደሩ በወቅቱ የነበረውን አደጋ የሚያስታውሱና የሚዘክር ታዋቂ የፊልም ባለሙያዎች የተሳተፉበት የፊልም ምርቃትና የኪነ-ጥበብ ስራዎች በማቅረብ እንዲታሰብም ተደርጓል፡፡ በዚህም የአስተዳደሩ ኃላፊዎችና የአገሪቱ ታዋቂ የኪነጥበብ ባለሙያዎች በየዝግጅቱ ላይ በመገኘት ለአደጋው ተጎጂ ቤተሰቦች አጋርነታቸውን ማሳየት ችለዋል፡፡ በዚህም የተሳካ የአብሮነትና ፍቅር የተንፀባረቀበት የማይረሳ ቀን ሆኖ ተጠናቋል፡፡
እውነታውና አላማው ይሄ ሆኖ ሳለ ምንም ዓይነት ተጨባጭ መረጃዎች ባልቀረቡበት የአስተዳደሩን የአብሮነት፣ የመቻቻል፣ የፍቅርና ማንንም አግላይ ያልሆነ እንዲሁም የህዝቡን ባህልና እሴት የሚሸረሽርና መልካም ስማችንንና ገፅታችንን የሚያበላሽ ፅሁፍ በጋዜጣችሁ ላይ ወጥቷል፡፡ በፅሁፉ ለወጡት ለእያንዳንዱ ምላሽ መስጠቱ አስፈላጊ ባይሆንም ለዋና ዋናዎቹ በመረጃ ላይ ላልተመሰረቱት ሃሳቦች መረጃ መስጠቱ አስፈላጊ ሆኖ አግኝተነዋል፡፡
ጋዜጠኛዋ የጎርፍ አደጋውን 10ኛ ዓመት አስመልክቶ 13 ሚሊዮን ብር ወጪ የተደረገበት መታሰቢያ ተደርጓል በማለት ፅፋለች፡፡ የጠቀሰችው የቁጥር አሃዝ ከየት የመረጃ ምንጭ እንደተገኘ ያልገለጸች ሲሆን መረጃው የግለሰቦች ጥያቄና ቅሬታ ምንጭም ከሆነም በግልጸኝነት ከሚመለከተው አካል ተጠይቆ መረጃው መሰረተ ቢስ መሆኑ ምላሽ የተሰጣት ቢሆንም፣ ይህን መግለጽ ለምን አልተፈለገም? በተጨማሪም አስተዳደሩ ከህዝቡ የሚነሱትን የልማትና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት ጥረት እያደረገ ባለበት ወቅት ለሁለት ቀን ፕሮግራም 13 ሚሊዮን ብር ያወጣል ብሎ ማሰቡ ትልቅ ስህተት ነው፡፡ ሌላው አደጋው ከፍተኛና ሰፊ የህብረተሰብ ክፍሎችን የነካካ ከመሆኑ አንፃር ምን አልባትም ሁሉም ተጎጂዎች በመታሰቢያ ቀኑ ተካትተው ላይሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን 3 ተጎጂዎችን ብቻ አናግሮ፣ ከፍተኛ ቅሬታ አስነሳ ሊባል የሚችል አይደለም፡፡ በ10 ሺዎች ባፈናቀለና ከመቶዎች በላይ የሚቆጠር ሕይወት ለቀጠፈ አደጋ የ3 ሰዎች ሀሳብ ብቻ ተወስዶ የአብዛኛውን ተጎጂ ባልወከለ ሁኔታ ከፍተኛ ቅሬታ አስነሳ በሚል ርዕስ ሰጥቶ መፃፍ፣ ከጋዜጠኝነት ፅንሰ ሃሳብ ጋር የሚጣረስና ስነ ምግባር የጎደለው ተግባር ነው ብለን እናምናለን፡፡
ሌላው አርቲስቶችን በባለ 5 ኮከብ ሆቴል ሰብስቦ በማስጨፈር መከበሩ ተጎጂዎችን ማሳዘኑን ገልጻለች። ነገር ግን በየሆቴሉ ጭፈራ መካሄድ አለመካሄዱን ከአዘጋጆቹ ማጣራት ተገቢ ነበር፡፡ ታዋቂ የሀገራችን የኪነጥበብ ባለሙያዎችና ጋዜጠኞች በፕሮግራሙ የተገኙበት ዋና ዓላማ፣ አደጋው በደረሰ ጊዜ ተጎጂዎችን በመልሶ ማቋቋም ወቅት በአካል ተገኝተው ማጽናናታቸውና ድጋፍ ማድረጋቸው የሚታወስ ሲሆን አሁንም  አስተዳደሩ በዘላቂነት የጎርፍ አደጋ ለመከላከል የሚያደርገውን ጥረት ባላቸው አቅም ሁሉ ለመደገፍና ለድሬደዋ ህዝብ ያላቸውን አጋርነት ለመግለጽና ለማገዝ እንጂ ዘጋቢዋ  እንዳሉት ለመጨፈር አይደለም፡፡
በሌላ በኩል የጎርፍ ተጎጂዎችን በማቋቋም ረገድ በርካታ ድጋፎች የተደረጉ ሲሆን አስተዳደሩ ከጎርፍ አደጋ በኋላ ሰብዓዊና ቁሳዊ ድጋፎች አድርጓል፤ ዋና ዋናዎቹም 14 ሚሊዮን ብር ወጪ በማድረግ 699 የአጣዳፊ ቤቶች ተገንብተው ለተጎጂዎች ተላልፈዋል፤ቀሪዎቹን በካምፕ የነበሩ ለእያንዳንዳቸው የ6 ወራት የቤት ኪራይ በመስጠት ወደ ቀድሞ ኑሮአቸው እንዲመለሱ ተደርጓል። የግል መኖሪያ ቤታቸው በከፊል ለወደመባቸውና ጠግነው ሊኖሩበት ለሚችሉት በመሀንዲስ ግምት መሠረት የጥገና ወጪ ክፍያ እንዲፈፀምላቸው ተደርጓል። አደጋውን በዘላቂነት ለመቀነስ ከ10 ኪ.ሜ በላይ ሪቴይንግ ዎል ማሰራት የተቻለ ሲሆን ዘንድሮ  በድጋሚ በመጣ ጎርፍ በተወሰነ አካባቢዎች በግድቡ ላይ መጠነኛ ጉዳት ደርሶበት በድጋሚ ጥገና ተደርጎለታል፡፡ የጎርፍ መሄጃ የሆኑትን የደቻቱና ጎሮ ወንዞች ግራና ቀኝ ተከትሎ  የጎርፍ መከላከያ ተሰርቷል፤ በተጨማሪም  የመልካጀብዱ መሄጃ ድልድይም በቅርቡ በጣለው ከባድ ዝናብ በጎርፍ ጉዳት የደረሰበት እውነት ቢሆንም፣ ከድሬዳዋ መልካጀብዱ የ8 ኪሎ ሜትር መንገድ ግንባታ በፌደራል መንገዶች ባለስልጣን በ2009 በጀት ዓመት ከሚሰሩ አራት መንገዶች አንዱ ሲሆን  በአስፓልት ደረጃ በአዲስ የሚሰራና ቅድመ ሁኔታው ተጠናቆ ስራው ሊጀመር ያለበት ሁኔታ እንጂ የአስተዳደሩ ቸልተኝነት ተደርጎ መቅረቡ ትክክል አይደለም፡፡  
አስተዳደሩ የጎርፉን አደጋ ለመቀነስ ባሰራው ጥናት ላይ ተመስርቶ ከከተማዋ አጎራባች ወረዳዎች የሚመጣውን የጎርፍ ጉልበት ለመቀነስ ባለፉት 5 ዓመታት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎችን በመስራት፣ ከ75 በመቶ በላይ የነበረው የአካባቢ መራቆት ወደ 33 በመቶ ዝቅ ለማድረግ የተቻለ ሲሆን በቅርቡ በኢሊኖ ሳቢያ የተፈጠረው የአየር ንብረት ለውጥ ያስከተለው ጎርፍ በከተማዋ ላይ ያስከትል የነበረውን ከፍተኛ አደጋ መቀነስ ተችሏል፡፡ ዘጋቢዋ ይህን የአስተዳደሩን ተግባር ለማወቅ የፈለገች አትመስልም፡፡
ለእያንዳንዱ ሀቅን መሰረት ያላደረገ ፅሑፍ ምላሽ እየሰጡ መሄድ አስፈላጊ ነው ባንልም በድሬዳዋ አስተዳደር ነዋሪው ዘንድ ያለውን የመተሳሰብና የመረዳዳት ባህልና እሴት ካለማወቅና ካለመረዳት እንዲሁም ተቆርቋሪና አሳቢ መስሎ የምንታወቅበትን አብሮ የመኖር ባህል ለመጉዳት መነሳሳት በቀላሉ የሚሳካ አይሆንም፡፡ ዘጋቢዋ ለጽሁፉ በቂ ትኩረት ያለመስጠቷን የሚያሳየው የአስተዳደሩን የመንግስት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ ስም እንኳን በትክክል አጥርታ ያለመፃፏ ነው፡፡
በመጨረሻም ጎርፍን በዘላቂነት መከላከልና በሰው ህይወትና ንብረት ላይ ጉዳት እንዳያደርስ ማድረግ የአስተዳደራችን ትኩረት ከመሆኑ ባሻገር፤ ከተማችን ድሬደዋ ለነዋሪዎቿ ምቹ፣መልካም አስተዳደር የሰፈነባት በንግድ፣ በኢንዱስትሪና አገልግሎት ዘርፍ ላይ ያተኮረ ዘላቂ ኢኮኖሚ ለመገንባት ያስቀመጠችውን ራእይ እናም የምስራቅ ኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ኮሪደር እንድትሆን በፌደራል መንግስት በተወሰነው ውሳኔ መሰረት፣ በቀጣይ ግዙፍና ትልልቅ ኢንዱስትሪዎች የሚገነቡባት፣ ለሀገራችን ህዝቦች ሰፊ የስራ እድል የምትፈጥር ከተማ ናት፡፡ በመሆኑም ከዚህ አኳያ ያለተጨባጭ ማስረጃ የሚቀርቡ ፅሁፎች የአስተዳደሩን በጎ ገፅታ ከማጉደፍ በተጨማሪ የአስተዳደሩን ህዝብ ካለማክበር የሚመነጭ እንዲሁም የአዘጋጆቹን ልፋትና ድካም ሞራል መንካት እንደሆነ ለማሳሰብ እንወዳለን፡፡  
የድሬደዋ ከተማ አስተዳደር