Administrator

Administrator

አንድ ባቡር በአንድ ጉዞ ከ300 በላይ ተጓዦችን ያሳፍራል
. ባቡሩ 80 ኪሎ ሜትር በሠአት የመብረር አቅም ይኖረዋል
. በአፍሪካ የከተማ ባቡር ተጠቃሚዎች ሰባት ብቻ ናቸው

የአዲስ አበባ ከተማ ቀላል ባቡር ፕሮጀክት በሁለት ምዕራፎች ተከፍሎ የሚከናወን ሲሆን በጠቅላላው 32 ኪሎ ሜትር ገደማ የሚደርሠው የመጀመሪያው ምዕራፍ ግንባታ፣ በ2007 ዓ.ም መጨረሻ ላይ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት ይጀምራል፡፡ ሁለተኛው ዙር ፕሮጀክት፤ የባቡር መስመር ዝርጋታውን ወደ 75 ኪሎ ሜትር የሚያደርስ ሲሆን ይህ የማራዘሚያ ፕሮጀክት የሚከናወነው በ2006 ዓ.ም ነው፡፡ 
አሁን በግንባታ ሂደት ላይ የሚገኘው የመጀመርያ ምዕራፍ የባቡር መስመር ዝርጋታ መነሻው ሃያት ሲሆን በመገናኛ፣ 22፣ ኡራኤል፣ መስቀል አደባባይ፣ ሜክሲኮና ልደታ አድርጐ ጦር ሃይሎች የሚደርስና የ16.3 ኪ.ሜ ርዝመት ያለው ነው፡፡ ከሠሜን ወደ ደቡብ የሚጓዘው ደግሞ መነሻው ከፒያሣ (ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን) ሆኖ በአዲስ ከተማ፣ አውቶቡስ ተራና 7ኛ አድርጐ፣ ከጦር ሃይሎች ከሚመጣው መስመር ጋር በጥምረት እስከ መስቀል አደባባይ ከመጣ በኋላ እስከ ቃሊቲ ማሠልጠኛ አደባባይ የሚዘልቅና የ17.5 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው ነው፡፡
በኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ፕሮጀክት ስራ አስኪያጅ ኢ/ር በሃይሉ ስንታየሁ፤ ስለባቡር መስመር ዝርጋታው፣ ስለባቡሮቹ አቅምና የቴክኖሎጂ ደረጃ፣ እንዲሁም ስለፌርማታና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ተጠይቀው የሠጡትን ምላሽ ጠቅለል አድርገን በሚከተለው መልኩ አጠናቅረነዋል፡፡

የባቡሮች አቅም እና የአገልግሎት ዘመን
የፕሮጀክቱ ምዕራፍ አንድ ሲጠናቀቅ 41 ባቡሮች ወደ አገልግሎት ይሠማራሉ፡፡ አንድ ባቡር 3ዐ ሜትር ርዝመት ያለው ሲሆን ይህም ማለት ከሁለት ባለ ተቀጣጣይ የቢሾፍቱ አውቶብሶች ርዝማኔ ላይ 6 ሜትር ብቻ መቀነስ ማለት ነው፡፡ የአንዱ ተቀጣጣይ አውቶቡስ ርዝመት 18 ሜትር ሲሆን የሁለት አውቶብሶች ሲደመር 36 ይሆናል፡፡ በባቡሩ ውስጥ 64 መቀመጫዎች ብቻ ይኖራሉ፡፡ እነዚህ ወንበሮች ለአቅመ ደካሞችና ለአካል ጉዳተኞች እንዲሁም ለረጅም ርቀት ተጓዦች የተሠናዱ ሲሆን አብዛኛው ተጠቃሚ ቆሞ እንዲሄድ ይጠበቃል፡፡ በአንድ ካሬ ሜትር ውስጥ ከ6-8 ሠው ሊቆም ይችላል በሚል ሲሠላ፣ በአጠቃላይ አንድ ባቡር በአንድ ጉዞ ከ268 እስከ 317 ሠዎችን ማጓጓዝ ይችላል ማለት ነው፡፡ በዚህ አይነት በሁለቱ አቅጣጫ የሚጓዙት ባቡሮች፣ በጋራ በሚጠቀሙት ከልደታ እስከ መስቀል አደባባይ ባለው መስመር እስከ 15ሺህ ሠው በአንድ ሠአት ውስጥ ማጓጓዝ የሚቻል ሲሆን በተናጠል በሚጓዙባቸው መስመሮች ቁጥሩ እስከ 7ሺህ ይጠጋል፡፡
የባቡር መሠረት ልማቱ (ሃዲዱ) በየጊዜው ተገቢው ጥገና እየተደረገለት እስከ መቶ አመት ድረስ እንዲያገለግል ታስቦ ነው የሚሰራው፡፡ ከኤሌትክሪፊኬሽንና ሲግናል (ማመላከቻ) እንዲሁም ከዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች ጋር የተያያዙት ደግሞ አስፈላጊው እድሣትና ጥገና እየተደረገላቸው እስከ 40 አመት እንዲያገለግሉ ተደርገው ይሠራሉ፡፡

የባቡር ፌርማታዎች
ከሰሜን ደቡብ፣ ከምስራቅ ምዕራብ በሚዘረጉት እያንዳንዱ መስመር 22 ፌርማታዎች የሚኖሩ ሲሆን በጠቅላላው 39 ፌርማታዎች ይዘጋጃሉ፡፡ ከነዚህ ውስጥ አምስቱ ከልደታ እስከ መስቀል አደባባይ በሚዘልቀው የጋራ መስመር ላይ የሚገኙ ናቸው፡፡ በየፌርማታዎቹ መካከል በአማካይ እስከ 700 ሜትር ርቀት የሚኖር ሲሆን በአንዳንድ ቦታ እስከ 400፣ ረጅም በሆኑት ለምሣሌ እንደጐተራ ማሳለጫ አካባቢ ደግሞ እስከ 1.2 ኪሎ ሜትር ርቀት ይኖራል፡፡ ተገቢው ፌርማታ ጋ ለመድረስ አንድ ተጠቃሚ ከ300 እስከ 400 ሜትር ብቻ በእግሩ መጓዝ ይጠበቅበታል ማለት ነው፡፡
ፌርማታዎቹ ሦስት አይነት ናቸው ይላሉ -ስራ አስኪያጁ፡፡ አንደኛው መሬት ላይ የሚሠራ ፌርማታ ነው፡፡ ሁለተኛው የድልድይ ላይ ፌርማታ ሲሆን ሦስተኛው የመሬት ውስጥ ፌርማታ ናቸው፡፡ የመሬት ላይ ፌርማታ በሚሆንበት ጊዜ፣ ተጠቃሚዎች ለዚሁ አገልግሎት ብቻ በሚሰራ 60 ሜትር በሚረዝም ወለል (ፕላት ፎርም) ላይ ሆነው ይጠብቃሉ፡፡
ጀድልድይ ፌርማታ ደግሞ ከድልድዮቹ በቀጥታ በግራና ቀኝ በኩል ወደ እግረኞች መንገድ ዳር የሚወርዱ የመተላለፊያ ደረጃዎችና ሊፍቶች ይኖራሉ፡፡ አንድ ሰው በድልድዩ ፌርማታዎች መጠቀም ከፈለገ፣ በአስፓልቱ ዜብራዎች በኩል በእግሩ ግራና ቀኝ አስፓልቱን አቋርጦ፣ ደረጃው ጋ ከደረሰ በኋላ ከፈለገ በደረጃው፣ ካሻውም በሊፍቱ ሽቅብ ወደ ድልድዩ መውጣት ይችላል፡፡ በተለይም አቅመ ደካሞችና አካል ጉዳተኞች ሊፍቱን እንዲጠቀሙ ቅድሚያ ይሰጣል፡፡
በመሬት ውስጥ ፌርማታዎችም በሁለቱም አቅጣጫ ወደ ውስጥ የሚያስገቡና የሚያስወጡ ደረጃዎች እና ሊፍቶች ይኖራሉ፡፡ በዚያ መሠረት ሁሉም ሰው የሚመቸውን አማራጭ በመጠቀም ወደ ውስጥ መግባትና መውጣት ይችላል፡፡

የባቡሮቹ ፍጥነትና የቴክኖሎጂ ደረጃቸው
የመጀመያው ምዕራፍ ግንባታ በ2007 ዓ.ም ከተጠናቀቀ በኋላ ወደ አገልግሎት ይገባሉ ተብለው የሚጠበቁት ባቡሮች፤ በሰአት 80 ኪሎ ሜትር የመብረር አቅም እንዲኖራቸው ተደርገው ዲዛይን የሚደረጉ ሲሆን ወደ አገልግሎት ሲሰማሩ ግን በአማካይ በየ700 ሜትር ርቀት ፌርማታ ስለሚኖር ፍጥነታቸው በሰአት ከ30 እስከ 40 ኪሎ ሜትር ዝግ እንዲል ይደረጋል፡፡ የቀላል ባቡር ፕሮጀክቱ በጀት የባቡሮቹን ዋጋም የሚያጠቃልል ነው፡፡ ኮንትራክተሩ ከመከላከያ ኢንጅነሪንግ ጋር በጋራ የሚገጣጥማቸውን ባቡሮች ጨምሮ ከውጭ ተገዝተው የሚመጡ ባቡሮችም ይኖራሉ፡፡
የቴክኖሎጂ ደረጃቸውን በተመለከተ አሁን የብዙሃን ትራንስፖርት አገልግሎት በተስፋፋባቸው ሃገሮች ያለውን የሲግናል (ማመላከቻ)፣ የኮሚኒኬሽንና የኤሌክትሪክፊኬሽን ሲስተም ያሟላ እንደሚሆን ኢንጂነር በኃይሉ ይገልፃሉ፡፡ ለምሳሌ የትኬት አገልግሎት ሲስተሙን ስንመለከት፣ ሁለት አይነት ትኬት ይኖራሉ፡፡ የኤሌክትሮኒክስ እና የወረቀት ትኬቶች፡፡ በዋናነት ጥቅም ላይ የሚውለው የኤሌክትሮኒክ ቲኬቱ ሲሆን ማንኛውም ባቡር ተጠቃሚ ያንን ትኬት ከኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ከገዛ በኋላ፣ በየጊዜው ሂሣብ እያስሞላ መጠቀም ይችላል፡፡ በየቦታው የተዘጋጁ የሂሳብ መሙያ ጣቢያዎችም ይኖራሉ፡፡ ተጠቃሚው ልክ ወደ ባቡሩ ሲገባ፣ በሩ ላይ ወደሚገኘው ትኬት አንባቢ መሣሪያ (SVT Reader) ቲኬቱን በማስጠጋት እንዲነበብለት ያደርጋል፡፡ በቂ ሂሣብ ካለው እንዲገባ ይፈቀድለታል፡፡ ይህን ሂደት የሚቆጣጠሩ መኮንኖችም በባቡሩ ውስጥ ይኖራሉ፡፡ ተጠቃሚው መውረጃው ጋ ሲደርስ በድጋሚ የኤሌክትሮኒክስ ትኬቱን በሩ ጋ ወዳለው አንባቢ መሣሪያ በማስጠጋት እንዲነበብና ለተጓዘባት ኪሎ ሜትር ተገቢው ክፍያ እንዲቆረጥ ያደርጋል፡፡ አንባቢ መሣሪያውም ተጠቃሚው የተጓዘበትን ርቀት አስልቶ ሂሣቡን ይቆርጣል፡፡ አንድ ተሣፋሪ ይህን ሳያደርግ ከወረደ፣ መሣሪያው እስከ መጨረሻው ፌርማታ ድረስ ያለውን ታሪፍ አስልቶ ይቆርጥበታል፡፡ በዚህ ሂደት የባቡሩ ሠራተኞች (መኮንኖች) የት ኬት ማንበቢያ መሣሪያውን በእጃቸው ይዘው ተገቢውን ቁጥጥርና ክትትል ያደርጋሉ፡፡
የወረቀት ትኬቱ በአብዛኛው ከክፍለ ሀገር ለሚመጡና የአጭር ጊዜ ቆይታ ላላቸው የአንድ ጊዜ ተጓዦች የሚዘጋጅ ይሆናል፡፡ የጉዞ ታሪፍ በተመለከተ አሁን የተወሰነ ነገር ባይኖርም የአብዛኛውን ህብረተሰብ አቅም ያገናዘበ ይሆናል ተብሎ ይገመታል፡፡
ባቡሩ ከትኬት አቆራረጥ ዘመናዊነቱ ባሻገር፣ የባቡሩን መነሻና መድረሻ እንዲሁም እያንዳንዱን የሚቆምበትን ፌርማታ ለተሳፋሪዎች በድምጽና በጽሑፍ ያሳውቃል፡፡
ለዚሁ በተዘጋጀው ስክሪን ላይ ቀጣይ ፌርማታ የቱ እንደሆነም ይገልፃል፡፡ በድምጽም ጭምር፡፡ በአሁኑ ወቅት የባቡር ኦፕሬተሮች፣ ቲኬተሮች፣ የቁጥጥር ባለሙያዎችና የመሳሰሉትን ለማሰልጠንም ዝግጅት እየተደረገ ነው፡፡

የባቡሩና የመኪኖች መንገድ አጠቃቀም
መኪናዎችና ባቡሩ በመስቀለኛ መንገዶች ላይ እንዴት ይተላለፋሉ ብለን የጠየቅናቸው ኢንጂነር በሃይሉ፤ የባቡሩ መስመር አይነት በከፊል የተዘጋ የሚባለው ሲሆን ራሱን ችሎ ከመኪና መንገድ ጋር ሳይገናኝ የመጓዙን ያህል በሌላ በኩል ከመኪኖች ጋርም መንገድ የሚጋራባቸው ጥቂት ቦታዎች እንደሚኖሩ ይናገራሉ፡፡ ባቡሩ ከመኪኖች ጋር ሊገናኝ የሚችለው ወደ ኋላ በሚመለስበት ጊዜና በመስቀለኛ መንገድ ላይ ነው፡፡ ባቡሩ ከመኪናዎች ጋር በሚቆራረጥባቸው የተወሰኑ ቦታዎች አካባቢ ሲደርስ፣ ከርቀት የሲግናል ማመላከቻዎች በመጠቀም መኪኖች በቀይ መብራት እንዲቆሙ ይደረጋል፡፡ ባቡሩ በፍጥነት ሲያልፍ ወዲያው መኪኖቹ ይለቀቃሉ፡፡
የአፍሪካ ሃገራት ልምድ ምን ይመስላል?
በአፍሪካ ውስጥ የቀላል ባቡር አገልግሎት የተስፋፋ አይደለም ይላሉ - ኢንጂነሩ፡፡ ከ54 የአፍሪካ ሀገራት መካከል የከተማ ባቡር ተጠቃሚ የሆኑትና ለመሆን እየሰሩ ያሉት ኢትዮጵያን ጨምሮ ሰባት ሀገራት ብቻ ናቸው፡፡ እነሱም የሰሜን አፍሪካ ሀገራት እና ደቡብ አፍሪካ ናቸው፡፡ ከሰሜን አፍሪካ የካይሮ ሜትሮ ባቡር ተጠቃሽ ነው፡፡
በተመሳሳይ ኢትዮጵያ ልምድ የወሰደችበት የቱኒዚያ ቀላል ባቡር አገልግሎትም ተጠቃሽ ነው፡፡ በሌላ በኩል በአልጄሪያ፣ ሞሮኮ እንዲሁም በደቡብ አፍሪካ ጆሃንስበርግ፣ ፕሪቶሪያ እና ኬፕታውን የተለያየ አይነት የከተማ ባቡር ትራንስፖርት አገልግሎት አለ፡፡ በግንባታ ላይ ካሉት ደግሞ በናይጄሪያ ሌጐስ እና አዲስ አበባ ላይ የተዘረጉት ፕሮጀክቶች ተጠቃሽ ሲሆኑ የአዲስ አበባው ከሰሃራ በታች ካሉ ሃገራት ቀዳሚው ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

የባቡር መስመር ግንባታው ሂደት
በመሬት ላይ የሚገነባውና በድልድይ የሚገነባው የባቡር መስመር በጥሩ ሂደት ላይ ሲሆኑ እንደሆነ የሚናገሩት ኢንጂነር በኃይሉ፤ ከሁሉም የላቀ ስራ የተከናወነው በመሬት ውስጥ በሚገነባው የባቡር መስመር ነው ይላሉ፡፡
በድልድይ የሚገነባው መስመር ከወሰን ማስከበር ጋር በተያያዘ አንዳንድ ችግሮች እንዳጋጠሙት ግን አልሸሸጉም፡፡ በተለይ ከመስቀል አደባባይ እስከ ለገሃር ባለው መስመር ባለቤቱ የማይታወቅ ምናልባትም ጣልያን ሳያሰራው አይቀርም ተብሎ የተገመተ የውሃ ማስወገጃ ቦይ በግንባታው ላይ ጫና ፈጥሯል፤ ሌላው አካባቢ ግን በጥሩ ሂደት ላይ ነው ብለዋል - ኢንጂነር በኃይሉ፡፡
21 ኪሎ ሜትር በሚሆነው የፕሮጀክቱ አካል ላይ ሁሉም አይነት የግንባታ ክንውኖች እየተተገበሩ ሲሆን፤ አብዛኛው የግንባታ ስራ በ2006 ዓ.ም ይጠናቀቃል፡፡
የሃዲድ ማንጠፍ ስራዎችም በዚያው አመት ይጠናቀቃሉ ተብሎም ይጠበቃል፡፡ የኤሌክትሪፊኬሽን ስራዎችም በብዛት ይሰራሉ፡፡
በ2007 ዓ.ም መጨረሻ ላይ የመጀመሪያው ምዕራፍ ሙሉ ለሙሉ ተጠናቆ ስራ ይጀምራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ የባቡር ፕሮጀክቱ በቻይናው የባቡር መንገድ ግንባታ ድርጅት የሚከናወን ሲሆን የፕሮጀክቱ ጠቅላላ ወጪ 475 ሚ.ዶላር ነው፡

 

 

(ሃርያ ላግድ ጐስያ ጐችድ ጌድዋ ካልዮጌ ዮሳመለቼስ)
ከዕለታት አንድ ቀን አያ አንበሳና ሰው ወዳጅ ሆኑ አሉ፡፡ “እዚህ ከምንቀመጥ ለምን በጫካ ውስጥ ዞር ዞር እያልን እግራችንን አናፍታታም” አለ ሰው፡፡
አንበሳም፤ “እኔ ጫካው ሰልችቶኛል፡፡ መንቀሳቀስ ከሆነ የፈለግከው ወደሚቀጥለው ከተማ እንሂድ”
ሰው፤ “መልካም፡፡ እየተዘዋወርን የከተማውን ሁኔታ እንይ”
በዚህ ተስማምተው መንገድ ጀመሩ፡፡
መንገድ ላይ ጨዋታ አንስተው ሲወያዩ የየራሳቸውን ዝርያ አንስተው ማውራት ጀመሩ፡፡
“እናንተ የሰው ልጆች’ኮ የእኛን የአንበሶችን ያህል ጥንካሬ የላችሁም፡፡ እኛ የዱር አራዊትን ሁሉ አስገብረን በእኛ ሥር እንዲሆኑ አድርገናል፡፡ እናንተ ግን እርስ በርሳችሁ እንኳን መስማማት አቅቷችሁ፤ ጦርነት፣ ዝርፊያና እልቂት ውስጥ ትገኛላችሁ” አለ አንበሳ፡፡
ሰውም፤ “አይደለም፡፡ እኛ የሰው ልጆች፤ የዓለምን ሥልጣኔ ለመምራት ሁልጊዜም ከላይ ታች ስንል፣ ያለውን ሃብት በጋራ ለመጠቀም፣ በእኩል ለመከፋፈል፣ ስንጣጣር ነው ግጭት የሚፈጠረው፡፡ ሌላው ቀርቶ አንተ የምትኖርበትን ጫካና ደን እንዳይጨፈጨፍ ባንታገል ኖሮ ይሄኔ መኖሪያ አጥተህ ነበር” ይለዋል፡፡
አንበሳም፤
“እሱ ለእኛ በማዘን ሳይሆን የራሳችሁን ህይወት ለማራዘም ስትሉ የምታደርጉት ነው፡፡ እኛ የተፈጥሮ ጥንካሬያችን ብቻ ያኖረናል”
ሰው፤ “በሽቦ በታጠረ መናፈሻ ውስጥ እንድትኖሩ የእንስሳት ማቆያም እኮ አዘጋጅተንላችኋል፡፡ አንበሳ፤ “እሱም ቢሆን እኛን ለቱሪስት እያሳያችሁ ገንዘብ የምትሰበስቡበት ነው፡፡ ለእኛ እሥር ቤት ነው”
በዚህ ማህል አንድ አደባባይ ጋ ይደርሳሉ፡፡ አደባባዩ መካከል ሐውልት አለ፡፡ ሐውልቱ አንድ ሰው አንድ አንበሳን ታግሎ ሲጥለው የሚታይበት ስዕል አለው፡፡
ይሄኔ ሰውዬው በአሸናፊነት ስሜት፤
“ተመልከት፤ የሰው ልጅ አንበሳን እንዴት እንደሚያሸንፈው!” አለው፡፡
አንበሳም፤ “ይሄ ያንተ አመለካከት ነው፡፡ ይህንን ሐውልት የሠራነው እኛ አንበሶች ብንሆን ኖሮ፣ አንበሳውን ከላይ፣ የሰውን ልጅ ከታች አድርገን እንቀርፀው ነበር!” አለው፡፡
***
ሁሉ ነገር ሁለት ወገን እንዳለው አንርሳ፡፡ ከማን አቅጣጫ ነው የምንመለከተው ነው፤ ጉዳዩ፡፡ ሁሉም እኔ ነኝ ጠንካራ ይበል እንጂ ጠንካራው በመካያው ይለያል፡፡ ዕውነተኛው፤ የማታ የማታ መለየቱ የታሪክ ሂደት ነው፡፡
“ዳገት ከላይ የሚያዩት ቁልቁለት፣ ቁልቁለት ከታች የሚያዩት ዳገት” እንዳለው ነው ገጣሚው፡፡
መቼ ቁልቁለቱ ዳገት እንደሚሆንብን ካላስተዋልን “ያሰፈሰፈው መዓት” ይጠብቀናል (The impending catastrophe እንዲሉ)፤
ሐውልቱን፤ ጊዜ የሰጠው ይሠራዋል፡፡ አንድ የቀድሞ የደርግ ጄኔራል በሰጡት ኢንተርቪው፤ “ስለደርግ በሚያወራ የቴሌቪዥን ፕሮግራም በቀዳሚነት የሚታዩት እርሶ ነዎት - ውስኪ ሲጠጡ፡፡ ምን ይሰማዎታል?” ቢባሉ፤ “ይሄ ምንም አይገርምም፡፡ እኛ በጊዜያችን ውስኪ ጠጣን! እነሱም ይሄው በጊዜያቸው ውስኪ እየጠጡ ነው” ብለው መልሰዋል፡፡ ጊዜ ፈራጅ ዳኛ ነው፡፡
ዛሬም የሀገራችን ቁልፍ ጉዳይ መቻቻል ነው፡፡ መቻቻል ብስለትንና ዕውቀትን አጣምሮ የያዘና ጊዜን በቅጡ ግንዛቤ ውስጥ የሚያስገባ ዕሳቤ ነው፡፡ መልካም ባሕል ያለው ህዝብ የታደለ ነው፡፡ የባህሉ ጥንካሬ ለመቻቻሉ ብርቱ አስተዋጽኦ ያደርጋል፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ እንደዚያ ነው፡፡ እኔ ብቻ ነኝ ጠንካራ የሚል አመለካከት ከመቻቻል ጋር ግንባር ለግንባር ይጋጫል፡፡ “እኔ ነኝ የበላይ” የሚል አስተሳሰብን ያመላክታልና፡፡ መካረርና ማክረር ከጽንፈኛና ከፅንፈኝነት ጐራ መክተቱ እውን ነው፡፡ መጭው ነገር አስቀድሞ ጥላውን ይጥላል፡፡ (Coming events cast their shadows) እንደሚሉት ፈረንጆች) (ለላመት የሚቆስል እግር ዘንድሮ ዝምብ ይወረዋል፤ እንዳለውም አበሻ)
የሩቁን ያላስተዋለ አለቃ፣ ኃላፊ ወይም መሪ፣ አስተውሎም ያላመዛዘነ፤ አመዛዝኖም በጊዜ እርምጃ ያልወሰደ ከሆነ፤ በአደጋው ውስብስብ መረብ ውስጥ ገብቶ መተብተቡ አይቀሬ ነው፡፡ ብርቱ ጥንቃቄ ያሻል፡፡ ስለዲሞክራሲ መጠንቀቅ ዋና ጉዳይ ነው፡፡ ስለሃይማኖት መጠንቀቅ የበለጠ ዋና ጉዳይ ነው፡፡ ሰው እንደቤቱ እንጂ እንደጐረቤት አይኖርምና ሁሉም ወገን ሊያስብበት የሚገባ ጥልቅና ጥብቅ ጉዳይ ነው፡፡
እንደተጣደ ወተት መቼ ሊገነፍሉ እንደሚችሉ የማናውቃቸውን ነገሮች በዐይነ-ቁራኛ ማየት፤ ተገቢውን ማርከሻ ማወቅና መጠቀም ተገቢ ነው፡፡ እንደ ሙስና፣ ኢፍትሐዊነት፣ የዕምነት - ሽፋን ሂደቶች… ወዘተ ጉዳዮች በትኩረት መጤን ያለባቸው ናቸው፡፡
ሬዲዮው ያወራል በተግባር ምንም የለም፡፡ ቴሌቪዥኑ ያሳያል በተግባር የለም፡፡ ጋዜጣ ይፅፋል በግብር ምንም የለም፡፡
The rottener the time the easier it is to get promoted ይላል ሔልሙት ክሪስት የተባለ ፀሐፊ፡፡ (ጊዜው ወይም ዘመኑ እየተበሳበሰ ሲሄድ የሥራ ዕድገትና ሹመት በሽበሽ ይሆናል እንደማለት ነው፡፡) የተሾምንበት፣ የአደግንበት ሥራ ተግባርን ግድ እንደሚል ደጋግመን እናስብ፡፡ ምን አልሠራንም የምንለውን ያህል የሠራነው ተገቢ ነወይ? ብለንም ለመጠየቅ እንትጋ!
የትውልድ ዝቅጠትና መበስበስ (decadence) የፖለቲካውና የሶሺዮ ኢኮኖሚው ድቀት የሚያመጡት ክስተት ነው፡፡ እጅግ በከፋ ገፁ ሲታይ ከሀገራችን ከውይይት ይልቅ ግጭት፣ ከሰላም ይልቅ ጦርነት ይዘወተራል፡፡ በእንዲህ ያለው ዘመን አፍ ይበዛል፡፡ አዕምሮ ይደርቃል፡፡ አንድ ደራሲ እንደሚለው verbal diahria and mental constipation በይፋ ይታያል፡፡ (የአፍ - ተቅማጥና የአዕምሮ - ድርቀት ይንሰራፋል እንደማለት ነው፡፡ መለፍለፋ፣ መለፍለፋ፣ መለፍለፋ ብቻ፡፡ ሐሳብ የለም፡፡ ዕውቀት የለም፡፡ ጥበብ (wisdom) የለም፡፡ ተግባር - አልባ ልፍለፋ! ለዚህ ነው ከልኩ በላይ የተመኘነው ለውጥ በቀላሉ የማይመጣው፡፡ የአፍ መብዛት፣ የስብሰባ መብዛት… የግምገማ መብዛት ብቻውን ፍሬ እንደማያፈራ ደጋግመን ተናግረናል፡፡ የሚሰማ አለመኖሩ ነው ምላሹ፡፡
“የምንለውን ብለናል የምናደርገውን እንጀምር!” አሉ አሉ የቀድሞው መሪ፡፡ ስላልን የሠራን እንዳይመስለን ነው ነገሩ፡፡
“አህያ እየነዱ፣ ቅል እየሳቡ፣ ከኋላ ሲከተሉ፤ ወተት ያለቡ ይመስላል” የሚለው የወላይታ ተረት ሁኔታውን የበለጠ ይገልፀዋል፡፡

Saturday, 10 August 2013 10:33

ለካ ሞት ግጥም አይችልም!!

እንደመግቢያ
ክፍት የሥራ ቦታ
ግጥም ፅፌ ፅፌ፣
አላነብም ብሎ ሰዉ ቢያስቸግረኝ
“ክፍት የሥራ ቦታ”፣ የሚል ከባድ ርዕስ-ያለው ግጥም ፃፍኩኝ!
ማ ጮክ በል አለኝ?... ተሻማ ህዝብ ሁሉ፣ግጥሜን ገዛልኝ!
በየቤቱ ሄዶ-ተስገብግቦ ጠግቦ፣ ዋለበት ቢመቸው-
ሦስቴ አራቴ፣ አምስቴ፤ ደጋግሞ አነበበው-
ግጥሙ እንዲህ አለቀ፡-
“ውድ አንባቢዬ ሆይ በቢሮ፣ በቤትህ፣ በፍራሽ ላይ ያለህ
መንግስት ያላየውን፣ ውለታ ዋልኩልህ፡፡
ምሁር ያልተካነው፣ ትምህርት አስተማርኩህ፡፡
ትግል ያልፈታውን፣ ቅን መላ ሰጠሁህ፡፡
ይህን በማንበብህ፣ የሥራ-አጥ ቁጥር፣ በጦቢያ ቀነሰ
ቢያንስ የዛሬውን ቀን፣ ስራ በማግኘትህ የልብህ ደረሰ!!
ግጥሜም ስራ አገኘ የአንጀት አደረሰ
እኔም ስራ አገኘሁ ምኞቴ ታደሰ!!
የዕድሜ ሙሉ መክሊት፣ ለዛ ነው አስቤዛ
እንዲህ ያለው ስራ በዋዛ አይገዛ!!

ውለሃል በል አንጋ
ፌዝ አይደለም ቅኔው፣የስራ ፍለጋ
ስራ ስትፈልግ ብቅ በል እኔጋ!...
ልምድ ይኑር አይኑርህ
አበባም ሁን ቀጋ
ወለላም ሁን ፉንጋ
ደማም ሁን ጠሟጋ፤
ወጣት ሆይ ነብር ጣት! ልክ እንደተመረቅክ፣ ብቅ በል ግጥም ጋ!!
ማስታወቂያ መስሎት ይህን ግጥሜን ሰምቶ
“ስራ እፈልጋለሁ” ብሎ ተሟሙቶ
ሞት መምጣቱን ሰማሁ እሱም ስራ ሽቶ!....
(ለዓለም ባንክ እና ለስራ - አጡ ወጣት እንዲሁም ለፀጋዬ ገ/መድህን
ሐምሌ 2005ዓ.ም
ለካ ሞት ግጥም አይችልም
ሰሞኑን፣
ሞትን መንገድ ላይ አየሁት፡፡
አለባበሱ ገረመኝ፡፡
ዥጉርጉር ቲ-ሸርት አድርጓል
ከታች ራንግለር ለብሷል!
አሃ?!
እሱም ፋሽን ይከተላል? ፍንዳታ መሆን ያምረዋል?
ያው እቲ-ሸርቱም ላይኮ፣ ከፊቱም ገፅ፣ ከኋላውም፤
መፈክር መሳይ ተፅፏል፡፡
ከፊት ለፊቱ በኩል፣ long live death ይላል
“ሞት ለዘላለም ይኑር”
ከጀርባው follow me ይላል “ተከተይኝ” ስለፍቅር!
ወይ ጉድ፤ ይሄስ ሞት ይገርማል!
ይሄ ጅል የጅል ቆንሲል
እሱም ህይወት ይፈልጋል?
ፍቅረኛ ማግኘት ያምረዋል?
ሞት፤የብርሃን ባላንጣ፣ ፀሀይ ይፈራል መሰል
ጥቁር ዣንጥላ ዘርግቷል፡፡
በእጁ ደሞ እንደወጉ፣ ደብተርና እርሳስ ይዟል!
እኔ፤ ገጣሚው ልቅሶ ቤት፤ ልቤን ላነባ ስገባ
ሞትም ተከትሎኝ ገባ፡፡
እኔ ወዲህ ማዶ ቆምኩኝ
እሱ ወዲያ ማዶ ቆመ
ከማህል ገጣሚው አለ
የፊደል አርበኛ አደለ? አስከሬኑ ጃኖ ለብሷል
ገጣሚ ማለት ፈሣሽ፣ ስደተኛ ወንዝ አደለ?-
ወንዝ አለት እንደሚንተራስ፣ ብረት ሳጥን ተንተርሷል፡፡
ሞትን ከገጣሚው ማዶ፣ በስሱ አሻግሬ እያየሁ፣
“ለምን መጣህ?” ብዬ ብለው
ሞት ፈጣጤ አፍ-አውጥቶ
“ግጥም ልማር!” አለኝ ኮርቶ፡፡
ይሄኔ ገጣሚው ነቃ!
አስክሬኑ ተግ አለና
ብድግ አለ ከተኛበት!
ሞትን በደም ዐይኑ አየና
“ሀጠራው!” አለ
‘ሞት ለዘላለም ይኑር!’
የሚል ሸቃባ መፈክር
እርኩስ ደረትህ ላይ ፅፈህ
ግጥም መማር ታስባለህ?
ግጥም የህያው ልሣን ነው፣ ለሞት አንደበት አይሆንም፡፡
የስንኝ ጠበል እሚፈልቅ፣ በድን አለት ውስጥ አደለም፡፡
ግጥም ከነብስ ቃል እንጂ፣ ከሥጋ ትንፋሽ አይነጥብም፡፡
አንዳች ህይወት ውስጥህ ሳይኖር፣ ፊደል በመቁጠር አትገጥምም!!
አንተ ግንዝ ነህ ግዑዝ!
ጥላ የነብስ ባላንጣ
ዛሬ ደግሞ ብለህ ብለህ፣ ግጥም ልትማር ትመጣ?
ሀጠራው! ዐይን - አውጣ! ውጣ!”
ይህን ሰምቶ መልስ ሲያጣ
ሞት የሚባለው ፈጣጣ
ጭራውን ሸጉቦ ወጣ፡፡

ወይ ጉድ!
ስንቴ በኛ ቂም አርግዞ
ስንቱን ባለቅኔ ወስዶ፣ ስንቱን ቅኔ አግዞ አግዞ፤
“ግጥም ልማር መጣሁ” ይበል? ይሄ ሞት እሚባል ፉዞ
ያውም ከማይጨበጠው፣ ከእሳት አበባው ወዳጄ
ከንጋት ግጥም አዋጄ
ከሞት - ገዳዩ ቀኝ እጄ?
ግን፤
ምን ደስ አለህ አትሉኝም?
ለካ ሞት ግጥም አይችልም
ለካ ሞት ቅኔ አይገባውም!!
የካቲት 27/1998
(ለወዳጄ ለፀጋዬ ገ/መድህን እና ለጥበብ ለቀስተኞች)
/የጋሽ ፀጋዬ አስከሬን ከአሜሪካ መጥቶ፤ ቤቱ ሄጄ በተሰማኝ ስሜት መነሻነት የተፃፈ/ ብሔራዊ ቴያትር በፖለቲካ የግጥም ምሽት ላይ በነሐሴ ልደታ የተነበበ/

የመንግስት ስልጣን ገደብ ቢኖረው ኖሮ ሚኒስትር ዲኤታው ፍ/ቤት ይቆሙ ነበር - ኢ/ር ይልቃል ጌትነት፤ የሰማያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንት ናፍቆት ዮሴፍ “ሰማያዊ ፓርቲ፣ ግንቦት ሰባት እና አክራሪዎች ጋብቻ ፈጽመዋል” በሚል የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታ መናገራቸውን የተቃወሙት የሰማያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንት ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት፤ “የፀረ ሽብር አዋጁ ካልተቀየረ ማንም አይምርም፣ የመንግስት ስልጣን ገደብ ቢኖረው ኖሮ ሚኒስትር ዴኤታው ፍ/ቤት መቆም ነበረባቸው” በማለት ምላሽ ሰጡ፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ በህዝብ ስም የተቋቋመ ስለሆነ የመንግስት ድክመቶችንና ክፍተቶችን እንዲያስተካክል መታገል ስራው ነው ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ መንግስት የህዝብን ጥያቄ ከመመለስ ይልቅ መፈረጅ ይቀናዋል፤ ይህ ግን ከትግላችን አያግደንም” ብለዋል፡፡

“ከሁለት ወር በፊት የህዝብ ችግሮችና ጥያቄዎች ናቸው ብለን በሰላማዊ ሰልፍ ያሰማናቸው ጥያቄዎች አልተመለሱም” ያሉት ኢ/ር ይልቃል፤ ነሐሴ 26 ቀን 2005 ዓ.ም ሁለተኛውን ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ለማድረግ ዝግጅት እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡ “ኢትዮጵያ ከአገዛዝ ወደ ዴሞክራሲ ገና አልገባችም፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ገና የስልጣን ባለቤት አልሆነም” ያሉት ኢንጂነሩ፤ እነዚህ ነገሮች እውን እንዲሆኑ በምርጫ ቦርድ ህጋዊ እውቅና አግኝቶ በሰላማዊ መንገድ የሚታገልን ፓርቲ ከአሸባሪዎች ጋር ጋብቻ ፈጽሟል በማለት መወንጀል የአገዛዝ ባህሪ ነው ሲሉ ተችተዋል፡፡ አሸባሪ የሚለው ቃል ትርጉሙን ስቷል የሚሉት ኢ/ር ዘለቀ፤ የፀረ ሽብር አዋጁ እስካልተቀየረ ድረስም ማንንም ከመፈረጅ የሚያግድ ነገር የለውም ብለዋል።

ከደቡብ ኮሪያው ግዙፍ የኤሌክትሮኒክስ ኩባንያ ሳምሰንግ የመጡ 100 አባላት ያሉት የበጐ ፈቃደኞች ቡድን፣ በቢሾፍቱ የህክምና ስልጠናዎችን በመስጠትና አስፈላጊ ቁሳቁሶችን በመለገስ ለአምስት ቀናት አገልግሎት እንደሰጡ ተገለፀ፡፡ ከሐምሌ 29 ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ነሐሴ 3 ቀን 2005 ዓ.ም በተካሄደው የበጐ ፈቃድ አገልግሎት፣ ለቢሾፍቱና አካባቢዋ ነዋሪዎች የተለያዩ ህክምናዎችና የመድሀኒት አቅርቦት ተሰጥቷል፡፡ በርካታ ቁጥር ያላቸው ሕሙማን ወደ ኮሪያውያኑ በጎፈቃደኞች በመምጣት፣ የህክምና አገልግሎት ያገኙ ሲሆን ህክምናው ሙሉ ምርመራንና የመድሀኒት አቅርቦትን ያጠቃልላል፡፡
የበጐ ፈቃደኞች ቡድኑ ከህክምና ባለሙያዎች በተጨማሪ በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሙያ ላይ የተሰማሩ አባላትንም ያካተተ ሲሆን በቢሾፍቱ ቴክኒክና ሙያ ት/ቤት ግቢ ውስጥ ለአምስት ቀናት አገልግሎት ሲሰጡ መቆየታቸውም ታውቋል፡፡

Saturday, 03 August 2013 11:25

“የግጥም በጃዝ”

ሁለተኛ ሻማ ረቡዕ ይለኮሳል

በወጣት ከያንያን ተቋቁሞ ወጣትና አንጋፋ ገጣሚያን፣ ሙዚቀኞችና ሌሎች የጥበብ ባለሙያዎች የሚሳተፉበት “ግጥምን በጃዝ” ኪነጥበባዊ ዝግጅት፤ ሁለተኛ ዓመት ክብረ በዓሉን በመጪው ረቡዕ 11፡30 በብሔራዊ ትያትር እንደሚያከብር አስታወቀ፡፡ ላለፉት ሁለት ዓመታት ከቀረቡት ዝግጅቶች ላይ ተመርጠው የተሰናዱ ሥራዎች “ጦቢያ” በሚል ርዕስ በዲቪዲ የታተመ ሲሆን በ50 ብር ለገበያ እንደሚቀርብ ታውቋል።
በረቡዕ ዝግጅት ላይ በአንደበተ ርቱዕነታቸው የሚታወቁት መምሕር እሸቱ አለማየሁ በተመረጠ ርእሰ ጉዳይ ላይ ዲስኩር የሚያሰሙ ሲሆን ገጣሚ ነቢይ መኮንን፣ ተፈሪ አለሙ፣ ጌትነት እንየው፣ አበባው መላኩ፣ ግሩም ዘነበ፣ ምስራቅ ተረፈ፣ ምህረት ከበደ፣ ሜሮን ጌትነት፣ ደምሰው መርሻ እና ምንተስኖት ማሞ የግጥም ሥራዎቻቸውን ያቀርባሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በኤምቢዜድ ፊልም ፕሮዳክሽን የተዘጋጀው “ያልታሰበው” የተሰኘው ፊልም ነገ በአዲስ አበባ በሚገኙ የግል ሲኒማ ቤቶች ይመረቃል፡፡ የ103 ደቂቃ ርዝመት ያለው ፊልሙ ድራማቲክ ኮሜዲ ሲሆን፤ በማህበራዊ ህይወታችን ውስጥ የሚገጥሙንን ልዩ ልዩ ጉዳኞች በአዝናኝና አስተማሪ ትእይንቶች እያዋዛ ቁም ነገር የሚያስጨብጥ ነው ተብሏል፡፡ በፊልሙ ላይ ከ90 በላይ አንጋፋና ወጣት ተዋንያን ተውነውበታል፡፡    

“ሞት ያልገታው ጉዞ” በሚል ርዕስ የተዘጋጀ መጽሐፍ ዛሬ ከጠዋቱ 3፡00 ሰአት በሀገር ፍቅር ቲያትር ቤት ይመረቃል፡፡ በደራሲ ሶስና ደምሴና በበየነ ሞገስ የተዘጋጀው መጽሐፉ፤ በክቡር ብላታ ደምሴ ወርቅ አገኘሁ የህይወት ታሪክ ዙሪያ የሚያጠነጥን ሲሆን በአምስቱ ዓመታት የጠላት ወረራ ወቅት ወገኖቻችን የደረሰባቸውን ሰቆቃና ጀግኖች አርበኞች ለነፃነታቸው የከፈሉትን መስዋዕትነት ይተርካል፡፡ መጽሐፉ በቅርቡ በተለያዩ የመጽሐፍት መደብሮች ለሽያጭ ይቀርባል ተብሏል፡፡

ዘወትር ሐሙስ ከቀኑ 9-10 ሰዓት እና እሁድ ከ11-12 ሰዓት የሚቀርብ “እፎይታ” የተሰኘ የሬዲዮ ዝግጅት በኤፍኤም አዲስ 97.1 እንደሚጀምር ኪኖ ፕሮዳክሽን እና አርት ሶሉሽን አስታወቁ፡፡
ፕሮግራሙን “የወንዶች ጉዳይ” ቁጥር ፩፣ እና የ“ፔንዱለም” አዘጋጅ ሄኖክ አየለ፣ የ“ሚስኮል” ፊልም አዘጋጅ ደረጄ ምንዳዬ፣ አንጋፋዋ ድምጻዊት ነፃነት መለሰ እና ድምጻዊት አበባ ላቀው እንዲሁም የሙዚቃ ቪዲዮ ዳይሬክተሩ ፍፁም ይላቅ እንደሚያዘጋጁት ታውቋል፡፡

የሰዓሊ ሳሙኤል ሀብተአብ የፎቶግራፍ ሥራዎች የተሰባሰቡበት የፎቶግራፍ ትርዒት ትናንት ምሽት ሳር ቤት አካባቢ በሚገኘው ጋለሪአ ቶሞካ መቅረብ ጀመረ፡፡ ትርኢቱ እስከ ነሐሴ 23 ለተመልካች ክፍት ሆኖ የሚቆይ ሲሆን ነሐሴ 19 ከጧቱ 4 ሰዓት በሰዓሊው ሥራዎች ላይ ውይይት ይካሄዳል ተብሏል፡፡