Administrator

Administrator

 ክፍል 3
በ5ሺ ሜ በሁለቱም ፆታዎችና በሴቶች ማራቶን ተጨማሪ ሜዳልያዎች ይኖራሉ፡፡
ገንዘቤ በ5ሺ ለሁለተኛ የወርቅ ሜዳልያ ተጠብቃለች፤ ሪከርዱን ለመስበር እንደምትችልም ተናግራለች
በታክቲክ መበላሸት፤በቡድን ስራ ማነስና በአጨራረስ ድክመት ውጤት ጎድሎበታል፡፡
ከ1 ዓመት ያነሰ ጊዜ ለቀረው ኦሎምፒክ ከሳምንት በፊት በወንዶች ማራቶን የተጀመረው 15ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና  ነገ በሴቶች ማራቶን ፍፃሜውን ያገኛል፡፡ በዓለም  ሻምፒዮናው ኢትዮጵያ ከ2 ዓመት በፊት በሞስኮ ያገኘችውን የ3 ወርቅ፤ ሁለት ብር እና የነሐስ ሜዳልያ ስኬት ለማሻሻል ይቅርና ለመድገም ፈተና ይሆንባታል፡፡ ሻምፒዮናው ዛሬ እና ነገ ሲቀጥል ኢትዮጵያ በ5ሺ ሜትር በሁለቱም ፆታዎች ለተጨማሪ ሜዳልያዎች ተጠብቀዋል፡፡ ዛሬ በወንዶች 5ሺ ሜትር የ18 ዓመቱ ዮሚፍ ቀጀልቻ እና፤ ኢማና መርጋ ከ32 ዓመቱ ሞ ፋራህ ጋር ከባድ ትንቅንቅ ውስጥ ይገባሉ፡፡ ሞፋራህ በዓለም ሻምፒዮናው በ5ሺ ሜትር ለሶስት ጊዜያት አከታትሎ ለማሸነፍ የበቃ አትሌት መሆን እንደሚፈልግ ተናግሯል፡፡ በሌላ በኩል በነገው እለት በሴቶች ምድብ ማጣርያውን በከፍተኛ ብቃት ለማለፍ የቻሉት ገንዘቤ ዲባባ እና አልማዝ አያና በዋናነት እርስ በራሳቸው በሚያደርጉት ፉክክር የዓለም 5ሺ ሜትር ሪከርድ ሊሰበር እንደሚችል ግምት እየተሰጠ ነው፡፡ በጉዳዩ ላይ አስተያየት የሰጠችው የ1500 ሜትር የወርቅ ሜዳልያ አሸናፊ ገንዘቤ ዲባባ ‹‹ በ1500 ሜትር ማሸነፌ በራስ መተማመኔን ጨምሮታል፡፡ በፍፃሜ ሊገጥም የሚችለውን ማወቅ ባይቻልም፤ በጥሩ ብቃት ከተወዳደርኩ የ5ሺ ሪከርድን ሊሰብር የሚችል ፈጣን ሰዓት የማስመዘግብ ይመስለኛል፡፡›› በማለት ተናግራለች፡፡
ኬንያ እና የሜዳልያ ስብስብ ደረጃ
በቤጂንግ ከተማ በሚገኘው የወፍ ጎጆ ስታድዬም ላለፉት  ሰባት ቀናት ሲካሄድ በቆየው 15ኛው የዓለም አትሌቲስ ሻምፒዮና 207 አገራትን የወከሉ 1933 አትሌቶች በሁለቱም ፆታዎች በ47 የውድድር መደቦች  በመሳተፍ ላይ ናቸው፡፡ 36 አገራት ቢያንስ አንድ ሜዳልያ በማግኘት የደረጃ ሰንጠረዥ ውስጥ ገብተዋል፡፡ በሜዳልያ ስብስብ  ኬንያ 6 የወርቅ፤ 3 የብር እንዲሁም 2 የነሐስ ሜዳልያዎች በማስመዝገብ የደረጃ ሰንጠረዡን በአንደኝነት እየመራች ነው፡፡  አሜሪካ 3 የወርቅ፤4 የብር እና 5 የነሐስ ፤ጃማይካ 3 የወርቅ እና 2 የነሐስ ሜዳልያዎች፤ ታላቋ ብሪታኒያ 3 የወርቅ፤ ፖላንድ 2 የወርቅ፣ 1 የብርና 3 የነሐስ ፤ኩባ 2 የወርቅ ፣ 1 የብር፤ ቻይና 4 የወርቅ ፣ 1 የብርና 4 የነሐስ፤  ጀርመን 1 የወርቅ፣ 2 የብርና 2 የነሐስ፤ ኢትዮጵያ 1 የወርቅ እና ሁለት የብር ፤ እንዲሁም ካናዳ 1 የወርቅ 1 የብር እና 2 የነሐስ ሜዳልያዎች በመሰብሰብ እስከ አምስት ያለውን ደረጃ አከታትለው ይይዛሉ፡፡  ቤጂንግ ላይ ኬንያ በዓለም ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪኳ ከፍተኛውን ስኬት እያስመዘገበች ነው፡፡ ሻምፒዮናው ሲጠናቀቅ የሜዳልያ ሰንጠረዡን በመሪነት የመጨረስ እድልም ይኖራታል፡፡ በሻምፒዮናው ለኬንያ  የወርቅ ሜዳልያዎች ያስመዘገቡት  በ800 ሜትር ዴቪድ ሩዲሻ፤ በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ በ400 ሜትር መሰናክል ኒኮላስ ቤት፤ በ3ሺ ሜትር መሰናክል ወንዶች እዝኬል ኬምቦሚ፤ በ10ሺ ሜትር ሴቶች ቪቪያን ቼሮይት፤ በ3ሺ ሜትር መሰናክል ሴቶች  ኪያን ጄፕኮሚ እንዲሁም በጦር ውርወራ ጁሌዬስ ዮጎ ናቸው፡፡ ከእነዚህ የኬንያ የወርቅ ሜዳልያ ውጤቶች በ400 ሜትር መሰናክል እና በጦር ውርወራ ያገኘቻቸው በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ነው፡፡ በ3ሺ ሜትር መሰናክል የሚያሳዩት የበላይነት መቀጠሉም የሚያስገርም ይሆናል፡፡ ኬንያ በ1970ዎቹ እና 80ዎቹ በአጭር ርቀት ምርጥ አትሌቶች የነበሯት ሲሆን ማናጀሮች እና አሰልጣኞች ወደ ረጅም ርቀት በማተኮራቸው አት ውጤታማነታቸው ቀንሷል፡፡ በሜዳ ውድድር ግን ኬንያ የሜዳልያ ስኬት ስታገኝ በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ሲሆን ለኢትዮጵያም ትልቅ ትምህርት የሚሆን ነው፡፡ ኬንያ ባለፉት ሁለት ዓመታት ከዶፒንግ በተያያዘ 40 አትሌቶች በላይ መከሰሳቸው  በስፖርቱ ያላትን ክብር እያጎደፈው ነበር፡፡ ሰሞኑን ደግሞ ከዓለም ሻምፒዮናው ጋር በተያያዘ 2 አትሌቶች ከዶፒንግ በተያያዘ መከሰሳቸው የኬንያን ሰኬት ያደበዘዘው መስሏል፡፡ 2 አትሌቶች በ400 ሜትር ወንዶች እና በ400 ሜትር መሰናክል የሚሳተፉት ናቸው፡፡
ኢትዮጵያን የከዳችው ማራቶን ልዕልቷ
በማራቶን በዓለም ሻምፒዮና ታሪክ ወጣቱ የማራቶን አሸናፊ ለመሆን የበቃው የ19 ዓመቱ ግርማይ ገብረስላሴ ነው፡፡ የወርቅ ሜዳልያውን የወሰደው ርቀቱን  በ2 ሰዓት ከ12 ደቂቃዎች ከ27 ሰከንዶች በመሸፈን ነው፡፡  ኢትዮጵያዊው የማነ ፀጋዬ የዓመቱን የግሉን ፈጣን ሰዓት በ2 ሰዓት ከ13 ደቂቃዎች ከ07 ሰከንዶች  በሆነ ጊዜ አስመዝግቦ የብር ሜዳልያውን ወስዷል፡፡ የኡጋንዳው ሙኖዮ ሰለሞን በ2 ሰዓት ከ13 ደቂቃዎች ከ29 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ የነሐስ ሜዳልያውን ለመጎናፀፍ በቅቷል፡፡  በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪኳ ኢትዮጵያ በሁለቱም ፆታዎች ከ1 በላይ የወርቅ ሜዳልያ አግኝታ አለማወቋ ከቤጂንግ በኋላም ቀጥሏል፡፡ በ15ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የመክፈቻ ውድድር በሆነው ማራቶን ላይ የምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች የበላይነት ይታይበት ነበር፡፡ የጣሊያን አትሌቶችም ያሳዩት ፉክክር ሊደነቅ ይገባል፡፡ የኢትዮጵያ አትሌቶች  ግን ባላቸው ልምድ ተጠቅመው ውጤታማ መሆን ሲገባቸው ውድድሩን በመቆጣጠር ማራቶኑን መቆጣጠር አልቻሉም፡፡  በማራቶን አሰልጣኞች በኩል የሚሰሩ ተግባራት ተገምግመው የሆነ መዋቅር ሊፈጠር ይገባዋል፡፡ ግማሾቹ አትሌቶች በራሳቸው፤ ሌሎቹ በባሎቻቸው እንዳንዶቹ በማናጀሮቻቸው የሚሰለጥኑበት ሁኔታ ውጤት እያበላሸ መቀጠል የለበትም፡፡  በሌላ በኩል የዓለም ማራቶን ሪከርድን አከታትለው የሰበሩት ሁለት ኬንያውያን  አትሌቶች ከሜዳልያ ውጭ መሆናቸውም ያልተጠበቀ ሲሆን፤ በሌላ በኩል የኦሎምፒክ ሻምፒዮኑ ስቴፈን ኪፕሮችም ሳይሳካለት ቀርቷል፡፡ ከየማነ ፀጋዬ የብር ሜዳልያ ባሻገር  ኢትዮጵያዊያኑ ሌሊሳ ዴሲሳ 7ኛ እንዲሁም ለሚ ብርሃኑ 15ኛ ደረጃ አግኝተው ውድድሩን የጨረሱት፡፡ የብዙ የኢትዮጵያ አትሌቶች ማናጀር የሆኑት ሆላንዳዊው ጆስ ሄርማንስ ስለ ኤርትራዊው አትሌት ግርማይ ገብረስላሴ በሰጡት አስተያየት በቺካጎ ማራቶን በአሯሯጭነት መሳተፉን በዱባይ ማራቶን ሲሳተፍ አቋርጦ መውጣቱን ገልፀው ሳይጠበቅ ማሸነፉ አስገርሞኛል ብለዋል፡፡ በሞቃት አካባቢ ልምምምድ ሲሰራ መቆየቱን የገለፀው ኢትዮጵያዊው የብር ሜዳልያ ባለቤት የማነ ፀጋዬ በበኩሉ ልምድ እንዳለኝ የሚታወቅ ቢሆንም፤ ውድድሩ አስቸጋሪ ነበር፡፡ ከ35 ኪሎሜትር በኋላ ጨጓራ ህመም ገጠመኝ በዚህ ምክንያት ግርማይ አምልጦኝ በመሄድ ሊያሸንፍ ችሏል ብሎ ተናግሯል፡፡
አጨራረሱ የማያምረው የኢትዮጵያ አትሌቶች  የመሰናክል ሩጫ
በ3ሺ ሜትር መሰናክል ውድድሮች ከኢትዮጵያ አትሌቶች የተሻለ ፉክክር ማሳየት የሆነላቸው ሴቶች ናቸው፡፡  በሁለቱም ፆታዎች በ3ሺ መሰናክል ኬንያውያን ፍፁም የበላይነት ማሳየታቸው አልቀረም፡፡ በወንዶች ምድብ ኬንያዊው ኢዝኬል ኬምቦሚ ለ4ኛ ተከታታይ የዓለም ሻምፒዮና የወርቅ ሜዳልያ በመውሰድ ሲሳካለት እስከ አረተኛ ደረጃም ተከታትለው ገብተዋል፡፡ ማጣርያውን አልፈው ለፍፃሜ መድረስ የቻሉት ቶሎሳ ኑርጊ እና ሃይለማርያም አማረ በፍፃሜው ሲሳተፉ የተለየ ቴክኔክ እና የቡድን ስራ ስላልነበራቸው በአጨራረስም ደካማ በመሆናቸው ከሜዳልያ ፉክክር ውጭ የሆኑት በቀላሉ ነው፡፡ በፍፃሜው ውድድር አሁንም ለኢትዮጵያ የሜዳልያ እድል አጠያያቂው  ሁኔታ የወንዶቹ አትሌቶች የአጨራረስ ብቃት ደካማ መሆኑ ነው፡፡በ3ሺ መሰናክልም በሴቶች ለፍፃሜ የበቁት  ሶፍያ አሰፋ እና ህይወት አያሌው ያላቸውን የዳበረ ልምድ በመጠቀም የተሻለ ፉክክር ቢያሳዩም አጨራረስ ላይ የተለየ ዝግጅት ስላልነበራቸው ውጤቱ ሳይሆንላቸው ቀርቷል፡፡
ለኢትዮጵያ ዱባ እዳ እየሆነ የመጣው 10ሺ
በ10ሺ ሜትር ወንዶች የሞ ፋራህ የበላይነት በቤጂንግም ቀጥሏል፡፡ በውድድሩ የታየው ፉክክር የምንግዜም ምርጥ እየተባለም ሲሆን የኢትዮጵያውያኑ ከጨዋታ ውጭ መሆን ብዙዎችን እያነጋገረ ነው፡፡ የኬንያ አትሌቶች በውድድሩ ላይ በተጠቀሙት የቡድን ታክቲክ ኢትዮጵያውያንን ከፉክክር ውጭ ማድረግ ቢችሉም  ከሞፋራህ ጋር ከባድ ትንቅንቅ ገጥሟቸው የወርቅ ሜዳልያውን ሊነጥቁት አልቻሉም፡፡ ሞፋራህ በ10ሺ ሜትር ንግስናውን ለመቀጠል የበቃው ርቀቱን በ27 ደቂቃዎችከ01.13 ሰከንዶች ጊዜ በመሸፈን ሲሆን፤ ሁለቱ ኬንያያን ጄዮፍሪ ኪፕሳንግ እና ፖል ታንዊ የብርና የነሐስ ሜዳልያዎች አግኝተዋል፡፡ የአሜሪካው ጋለን ሩፕ ደግሞ ከኢትዮጵያውያን የተሻለ ብቃት አስመዝግቦ ሲጨርስ፤ ድሮ ከፍተኛ የበላይነት በማሳየት የሚታወቁት የኢትዮጵያ አትሌቶች ዙር ማክረራቸው ሲጠበቅ ዙሩ ከሮባቸው ከፉክከሩ ተቆርጠው ለመውጣት ተገደዋል፡፡ ይሄው የኢትዮጵያ አትሌቶች ደካማ ብቃት የረጅም ርቀት የምንግዜም ምርጥ አትሌት የሆነው ቀነኒሳ የታል የሚል ጥያቄም በስፖርቱ ቤተሰብ እንዲፈጠር ምክንያት ሆኗል፡፡ ባለፉት 20 ዓመታት የኢትዮጵያ  አትሌቶች በወንዶች 10ሺ ሜትር ከ1 እስከ 10 ባለው ደረጃ ይወጡ የነበረ ቢሆንም ቤጂንግ ላይ የተሳተፉት አትሌቶች ባልተጠበቀ ሁኔታ ከዚህ ብቃት መውረዳቸው  አሳሳቢ ሁኔታ ነው፡፡ በከፍተኛ ደረጃ የተጠበቀው ኢማና መርጋ ውድድሩን አቋርጦ ለመውጣት ሲገደድ ሌሎቹ አትሌቶች ከ10ኛ በኋላ በመጨረስ በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ታሪክ የወረደ ውጤት ለማስመዝገብ ተገድደዋል፡፡
በሴቶች 10ሺ ሜትርም ብዙ የሚያበረታታ ነገር አልታየም፡፡ የወርቅ ሜዳልያውን የወሰደችው ወልዳ ከተነሳች 1 ዓመት እንኳን ያልሞላት ቪቪያን ቼሮይት ናት፡፡ ኬንያዊቷአትሌት ለሁለተኛ ጊዜ በዓለም ሻምፒዮና ጥሩነሽ በሌለችበት የተለመደውን የወርቅ ሜዳልያ ከኢትዮጵያ በመንጠቅ ማሸነፏም ነው፡፡ የምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች ለ10ኛ ጊዜ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የወርቅ ሜዳልያ መውሰዳቸው አንድ የሚያኮራ ሁኔታ ነው፡፡በዚህ ውድድር በርቀቱ ብዙም ልምድ የሌላት ገለቴ ቡርቃ በሩጫ ዘመኗ ከፍተኛ የሚባለውን ውጤት በብር ሜዳልያ ማስመዝገቧም ጥሩ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ይሁንና በመጨረሻዎቹ 100 ሜትሮች ገለቴ ቡርቃ የወርቅ ሜዳልያውን ለመውሰድ ያደረገችው ሙከራ በአጨራረስ ላይ ብዙ ባለመስራቷ የተሳካ አልነበረም፡፡ ከሁለት ዓመት በፊት የወርቅ ሜዳልያ ያሸነፈችውን ጥሩነሽ ዲባባ ተከትላ በመግባት የብር ሜዳልያ የወሰደችው በላይነሽ ኦልጅራ ከሜዳልያ ውጭ ሆና ስትጨርስ ብዙም ልምድ ያልነበራት አለሚቱ ሃሮዬ ተፎካካሪነት አልነበራትም፡፡ አሜሪካዊት አትሌት በዚህ ውድድር የነሐስ ሜዳልያ ለመውሰድ መብቃቷ ተፎካካካሪነታቸው እያደገ መምጣቱን ያሳየ ነበር፡፡
በ1500 ሜትር የገንዘቤ ወርቅ የተሻለው ውጤት
በ1500 ሜትር ሴቶች ገንዘቤ ዲባባ የወርቅ ሜዳልያውን በፍፁም የበላይነት ለመውሰድ በቅታለች፡፡ እስከትናንት ኢትየቶጵያ ያስመዘገበችው ትልቁ ስኬትም ነው፡፡ ገንዘቤ የዓለም ሪከርድን ዘንድሮ እንደማስመዝገቧ ውጤቱን የተለየ ባያደርገውም የወርቅ ሜዳልያው በርቀቱ በኢትዮጵያ የዓለም ሻምፒዮና ታሪክ ለኢትዮጵያ የመጀመርያው፤ ለራሷ ገንዘቤ በዓለም ሻምፒዮናው በትራክ የመጀመርያ የወርቅ ሜዳልያ ሆኖ ተመዝግቧል፡፡ በሴቶች 1500ሜ ለሶስቱ ሜዳልያዎች ጠቅላይነት የኢትዮጵያ 3 አትሌቶች ከመጀመርያው ዙር ማጣርያ በኋላ ተጠብቀው ነበር፡፡ ከገንዘቤ ጋር ለፍፃሜ የደረሰችው ዳዊት ስዩም ሜዳልያ ውስጥ ለመግባት ከባድ ፉክክር የገጠማት ከትውልደ ኢትዮጵያዊቷና ለሆላንድ የምትወዳደረው ሰይፋ ሃሰን ነበር፡፡ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ታሪክ ለኢትዮጵያ ብቸኛውን የሜዳልያ ድል ያስመዘገበችው በ1999 እኤአ ላይ የነሐስ ሜዳልያ የወሰደችው ቁጥሬ ዱለቻ  የነበረ ሲሆን ገንዘቤ ዲባባ የወርቅ ሜዳልያ ካገኘች በኋላ ግን በርቀቱ በሴቶቹ ምድብ በዓለም ሻምፒዮናው የተሻለ ውጤት ተመዝግቧል ለማለት ይቻላል፡፡
የመሃመድ  ክብርን የማስጠበቅ ህልም በቴክኒክ ስህተት መበላሸቱ
በ800 ሜትር ወንዶች የመሃመድ አማን ክብር የማስጠበቅ  ከፍተኛ ትንቅንቅ በግማሽ ፍፃሜ  በተፈጠረው ያልተጠበቀ ሁኔታ ተበላሽቶበታል፡፡  በ3 ምድብ በተካሄደው የግማሽ ፍፃሜ ፉክክር በመጀመርያ ዙር ገብቶ የነበረው የወቅቱ ሻምፒዮን መሃመድ አማን በመጨረሻዎቹ ሁለት መቶ ሜትሮች የገጠመው ነገር በወቅቱ ውድድሩን ሲያስተላልፍ በነበረው ኮሜንታተር አገላለፅ እሱን ከመሰለ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው አትሌት የማይጠበቅ ነበር፡፡  መሃመድ አማን የ800 ሜትር ውድድሩ ሊጠናቀቅ በቀሩት የመጨረሻዎቹ ሁለት መቶ ሜትሮች በተፎካካሪ አትሌቶች ከተከበበበት  ሁኔታ ለመውጣት  በግራ በኩል ለማለፍ ያደረገው ሙከራ በሱ እና በሌላ አትሌት ላይ በፈጠረው መደነቃቀፍ ተበላሽቶበታል፡፡
 ሻምፒዮናነቱን የማስጠበቅ እድሉ አጣብቂኝ የገባውም በዚህ ክስተት ነበር፡፡ በሶስቱ የግማሽ ፍፃሜ ማጣርያዎች አንደኛና ሁለተኛ የወጡት በቀጥታ አልፈው መሃመድ አማን በግማሽ ፍፃሜው ያገኘው ፈጣን ሰዓት ከሶስተኛ ደረጃው ጋር በምርጥ ሶስተኛነት ሊያሳልፈው ቢችልም በተሰጠው እድል መሰረት ለፍፃሜ ቢያደርሰውም  ከውድድሩ ውጭ የሆነው በዚያው መደነቃቀፍ ነው፡፡ በኢትዮጵያ የዓለም ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪክ በ800 ሜትር ወንዶች ብቸኛውና  የመጀመርያው የወርቅ ሜዳልያ ድል የተመዘገበው ከሁለት ዓመት በፊት በመሃመድ አማን እንደነበር ይታወሳል፡፡

 የአሜሪካ ሴቶች ከ95 አመታት በፊት የተጎናጸፉት መብት ነው
                   70 ሴቶች በዕጩ ተወዳዳሪነት እንደሚቀርቡ ይጠበቃል
    የሳኡዲ አረቢያ ሴቶች በመጪው ታህሳስ ወር በሚካሄደው የከተማ አስተዳደር ምርጫ በዕጩ ተወዳዳሪነትና በድምጽ ሰጪነት በመሳተፍ በአገሪቱ በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የምርጫ ተሳትፎ እድል ተጠቃሚ እንደሆኑ  ሲኤንኤን ዘገበ፡፡በምርጫ ተወዳዳሪነትም ሆነ በመራጭነት የመሳተፍ መብት ተነፍጓቸው የኖሩት የሳኡዲ አረቢያ ሴቶች፤በታሪካቸው ለመጀመሪያ ጊዜ ካለፈው ቅዳሜ ጀምሮ በመራጭነት እየተመዘገቡ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፣ ከነገ ጀምሮም በዕጩ ተወዳዳሪነት ይመዘገባሉ ብሏል፡፡የቀድሞው የአገሪቱ መሪ ንጉስ አብደላ የአገሪቱ ሴቶች እ.ኤ.አ ከ2015 ጀምሮ በምርጫ ተወዳዳሪነትና በድምጽ ሰጪነት መሳተፍ እንደሚጀምሩ ከአራት አመታት በፊት ማስታወቃቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ይሄም ሆኖ ግን ሴቶች ይሳተፉበታል በተባለው ቀጣይ የከተማ አስተዳደር ምርጫ የሚያሸንፉ ሴቶች የተገደበ ስልጣን እንደሚኖራቸው ገልጧል፡፡
በመጪው ምርጫ ሴቶች እንዲሳተፉ መፈቀዱ የአገሪቱን ሴቶች የፖለቲካ ተሳትፎ ተጠቃሚ በማድረግ ረገድ ተስፋ ሰጪ እርምጃ ነው መባሉን ዘገባው ገልጾ፣የሳኡዲ አረቢያ ሴቶች አሁንም ድረስ ከፍተኛ በደልና ተጽዕኖ እንደሚደርስባቸው ጠቁሟል፡፡
የሳኡዲ አረቢያ መንግስት ሴቶችን የምርጫ ተሳታፊ ለማድረግ መወሰኑ በሴቶች መብት ጥሰት ከፍተኛ ውግዘት ስታደርስበት ከኖረችው አሜሪካ ጋር የተሻለ ግንኙነት እንዲፈጥር በር ሊከፍትለት ይችላል ያለው ዘገባው፣ የአሜሪካ ሴቶች በምርጫ የመሳተፍ መብታቸው የተረጋገጠላቸው ከ95 አመታት በፊት እንደነበር አስታውሷል፡፡በመጪው ምርጫ 70 ያህል የሳኡዲ አረቢያ ሴቶች በዕጩ ተወዳዳሪነት ይሳተፋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅና ሌሎች 80 ሴቶችም በምርጫ ዘመቻ ሃላፊነት ለመስራት መመዝገባቸውን የዘገበው ዴይሊ ሜይል በበኩሉ፣ ይሄም ሆኖ ግን የአገሪቱ ሴቶች አሁንም ድረስ መኪና መንዳት፣ የባንክ ሂሳብ መክፈት፣ ከባላቸው ውጪ ፓስፖርት ማግኘትና ወደፈለጉት አካባቢ መዘዋወር እንደማይፈቀድላቸውና ዘርፈ ብዙ የጾታ ጫና እንደሚደርስባቸው ጠቁሟል፡፡
በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጾታዊ እኩልነት መለኪያ መስፈርት መሰረት፤ ሳኡዲ አረቢያ ከአለማችን 140 አገራት 136ኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ዘገባው አክሎ አስታውቋል፡፡

   የጦር ሃይሉ መቀመጫ በአገራቱ መካከል አለመግባባት ፈጥሯል
    የአረብ ሊግ አባል አገራት የመከላከያ ሚኒስትሮች የጋራ የጦር ሃይል ለማቋቋም የሚያስችላቸውን ስምምነት ከትናንት በስቲያ ለመፈረም ይዘውት የነበረውን ዕቅድ ላልተወሰነ ጊዜ ማራዘማቸውን ኤቢሲ ኒውስ ዘገበ፡፡አባል አገራቱ ግጭት በሚከሰትባቸው አካባቢዎች የሰላም ማስከበር ስራ የሚሰራ የጋራ የጦር ሃይል ለማቋቋም የሚያስችላቸውን ስምምነት ባለፈው ሃሙስ ሊፈርሙ ቀጠሮ ይዘው የነበረ ቢሆንም፣ ሊጉ በዋዜማው ባወጣው መግለጫ እቅዱ ላልተወሰነ ጊዜ መራዘሙን አስታውቋል፡፡አንዳንድ የፖለቲካ ተንታኞች ግን፣ እንደ ሊቢያ ባሉ አገራት መንግስትን ለሚቃወሙ ሃይሎች ድጋፍ የሚሰጡ የአረብ አገራት ባሉበት ሁኔታ፣ የሚያቋቁሙት የጋራ የጦር ሃይል ጣልቃ ይግባ አይግባ የሚለው ጉዳይ በአገራቱ መካከል አለመግባባት ሊፈጥር ይችላል ማለታቸውንም ዘገባው ጠቁሟል፡፡ የጦር ሃይሉ መቀመጫ የሊጉ ዋና ጽህፈት ቤት በሚገኝባት ካይሮ ይሁን የሚለው ሃሳብ በአገራቱ መካከል አለመግባባት ፈጥሮ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ ስምምነቱ የተራዘመው ሳኡዲ አረቢያ፣ ባህሬን፣ ኩዌት፣ ኳታር፣ የተባበሩት አረብ ኢሜሬትስና ኢራቅ ባቀረቡት ጥያቄ መሰረት መሆኑንም ገልጧል፡፡አገራቱ የጦር ሃይሉን ለማቋቋም ፈቃደኛ መሆናቸውን ባለፈው መጋቢት ወር በይፋ ማስታወቃቸውንና በግንቦትም ስምምነቱን ማርቀቃቸውን ዘገባው አስታውሶ፣የተራዘመው ስምምነት የሚፈረምበትን ቀን አገራቱ ወስነው እንደሚያስታውቁ ጠቁሟል፡፡

  - ለ4 ተከታታይ አመታት በደካማነት የሚስተካከለው አልተገኘም
                - ላለፉት 20 አመታት አዲስ አውሮፕላን ገዝቶ አያውቅም
                - አብዛኞቹ አውሮፕላኖቹ በ1960ዎቹ የተመረቱ ናቸው
                - ተሳፋሪዎች እቃቸውን በእቅፋቸው ይዘው ይጓዛሉ
    ላለፉት ሶስት አመታት በዓለማችን ከሚገኙ አየር መንገዶች ደካማው ሆኖ የተመረጠው የሰሜን ኮርያው የአየር መንገድ ኩባንያ ኤር ኮርዮ ዘንድሮም የደካማነት ክብረወሰኑን ማስጠበቁን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
ተቀማጭነቱ በእንግሊዝ የሆነውና የዓለማችንን አየር መንገዶች በተለያዩ መስፈርቶች በመገምገም በየአመቱ ይፋ የሚያደርገው ስካይትራክስ የተባለ አለማቀፍ የአቪየሽን አማካሪ ኩባንያ፣ዘንድሮም ደረጃ ከሰጣቸው 600 የተለያዩ አገራት አየር መንገዶች መካከል የሰሜን ኮርያውን ኤር ኮርዮ በመጨረሻ ደረጃ ላይ አስቀምጦታል፡፡
በስድስት አገራት ወደሚገኙ 14 መዳረሻዎች በረራ የሚያደርገው ኤር ኮርዮ፣ ከዚህ በፊትም አብዛኞቹ አውሮፕላኖቹ በ1960ዎቹ የተመረቱና ያረጁ ናቸው በሚል መቀጣቱን ያስታወሰው ዘገባው፣ አየር መንገዱ ላለፉት 20 አመታት አዲስ አውሮፕላን ገዝቶ እንደማያውቅ ገልጧል፡፡
አብራሪዎቹ ዲጂታል ድጋፍ ሳያገኙ ለአደጋ በሚያጋልጥ ሁኔታ እንደሚያበሩ፣ ተሳፋሪዎች እቃቸውን በእቅፋቸው ይዘው እንደሚጓዙ፣ ለመዝናኛ ተብለው የሚከፈቱ ሙዚቃዎችና ቪዲዮዎችም የአገሪቱን መሪ የሚያንቆለጳጵሱ ብቻ እንደሆኑ ኩባንያው ገምግሟል፡፡
ስካይትራክስ አየር መንገዶችን በአውሮፕላኖች ብቃት፣ በደንበኞች አገልግሎት ጥራትና በሌሎች የአቪየሽን መስክ ጥራት መመዘኛ መስፈርቶች እየለካ በየአመቱ ደረጃ እንደሚሰጥ ይታወቃል፡፡

Monday, 31 August 2015 09:13

የዘላለም ጥግ

 የስኬትንቁልፍ አላውቀውም፤ የውድቀት ቁልፍ ግን ሁሉን ሰው ለማስደሰት መሞከር ነው፡፡
       ቢል ኮዝቢ
ህይወት ተፅዕኖ የመፍጠር ጉዳይ እንጂ ገቢ የመፍጠር ጉዳይ አይደለም፡፡
      ኬቪን ክሩስ
ሁሉም ሰው ዓለምን ስለመለወጥ ያስባል፤ማንም ግን ራሱን ለመለወጥ አያስብም፡፡
      ሊዮ ቶልስቶይ
ሁላችንም እናልማለን፡፡ ደግነቱ ደግሞ ህልሞች እውን ይሆናሉ፡፡
       ኬቲ ሆልመስ
ህይወት ከባድ ነው፤ደደብ ስትሆን ግን የበለጠ ከባድ ይሆናል፡፡
       ጆን ዋይኔ
ህይወት በጣም አጓጊ ነው-----አንዳንድ ትላልቅ ህመሞችህ የማታ ማታ ትላልቅ  ጥንካሬዎችህ ይሆናሉ፡    ፡
       ድሪው ባሪሞር
አዎንታዊ ህይወትና አሉታዊ አዕምሮ     ሊኖርህ አይችልም፡፡
      ጆይስ ሜየር
የህይወታችን ዓላማ መደሰት ነው፡፡
     ዳላይ ላማ
ህይወትን መኖር እንጂ መመዝገብ አልፈልግም፡፡
      ጃኪ ኬኔዲ
ቀኑን አንተ ትመራዋለህ ወይም ቀኑ አንተን ይመራሃል፡፡
      ጂም ሮህን
ትግል ከሌለ ዕድገት የለም፡፡
      ፍሬድሪክ ዳግላስ
ለውጥ ዕድል ይዞ ይመጣል፡፡
      ኒዶ ኪውቤይን
ህይወትህ የስዕል ሸራ ነው፤በቀለም ሙላው፡፡
      ያልታወቀ ፀሐፊ

የመጽሐፍ ቅኝት - በአብነት ስሜ)

ካለፈው የቀጠለ
ተራኪው እና ደራሲው
የልቦለዱ ተራኪ እኔ ሞኝ ነኝ፤ እኔ ፈሪ ነኝ ይላል። ነገር ግን፣ ሞኝነቱ ውስጡ አስተዋይነትን፣ ፍርሀቱ ውስጥ ደግሞ ድፍረትን ማየት ይቻላል። ተራኪው ከክርስቶስ ይልቅ ለደቀመዝሙሩ ለጴጥሮስ ይቀርባል። ጴጥሮስ እንደ ህፃን የዋህ፣ ጉጉ፣ ችኩል፣ ፈጣንና ፍርሀት አልባ ነው። ብዙ ይጠይቃል። ይጋፈጣል። ለክርስቶስ በጣም ቅርቡ ነበር። ውሀ ላይ እንደ ክርስቶስ መራመድ ከጀመረ በኋላ መሀል ላይ ራሱን ይጠረጥራል። እናም ይፈራል። መስጠም ሲጀምር ወደ ክርስቶስ ይጮሀል።  ከመስጠምም ይድናል። ጌታውን ሊይዙ ከመጡት ውስጥ ያንዱን ጆሮ በሰይፍ ቀንጥሷል። በዚህም ግን ተገስፆአል። ክርስቶስ በተያዘ ጊዜ ከደቀመዛሙርቱ ውስጥ ለረዥም ጊዜ በድፍረት የተከተለው ጴጥሮስ ነው። በተጠየቀ ጊዜ ግን ስለፈራ፣ “ይህንን ሰው አላውቀውም” ብሎ ሦስቴ ካደ። ድፍረቱ ሳይታይለት በክህደቱ ብዙ ተወቀሰ፤ ተገሠፀ፤ ተሣቀቀ።  ሌሎች ኢየሱስን ጥለውት የሔዱ ደቀመዛሙርት ግን እንደ እርሱ አልተወገዙም። ሐዋርያው ጴጥሮስ የዋህ ቢመስልም ብልህ ነበር፤ ጀግና ቢመስልም ፈሪ ነበር።
የወሪሳ ልቦለድ ተራኪም ለኢየሱስ ሳይሆን ለጴጥሮስ ነው የሚቀርበው።  በተራኪው ውስጥ የምናየው ደራሲውም የተላበሰው ሰብእና ኢየሱሳዊ ሳይሆን ጴጥሮሳዊ ነው።  የዋህና ፍርሀት አልባ ሕፃን ባይሆን ኖሮ እንዲህ ዓይነቱን ህልም አይጽፍልንም ነበር። ይህንን ዘግናኝ ነውራችንን የህፃን የዋህነት የሌለው ደራሲ ካልሆነ ማንም አይነግረንም።
ክርስቺያን አንደርሰን የተባለው ኖርዌጂያዊ እንደዚህ እንደ ዓለማየሁ ገላጋይ ጴጥሮሳዊ ህፃንነትና የዋህነትን የተላበሰ ደራሲ ነበር። “የንጉሱ ልብስ” በተሰኘ ልቦለዱ እንደራሱ ያለ አንድ ህፃን ፈጥሮልን አልፏል። ታሪኩን አብረን እናስታውስ። ንጉሡ ማጌጥ ይወድዳል። ለየት ያሉ አልባሳትን ያደንቃል። ይህን የተረዱ ሁለት አታላዮች ከንጉሡ ዘንድ ይቀርቡና ልዩ የሆነ ትንግርታዊ መጎናፀፊያ ለንጉሡ ለማዘጋጀት እንደአቀዱ ይናገራሉ። ልብሱን ለየት የሚያደርገው በክፉና በተንኮለኛ ሰው ዓይን አለመታየቱ ነው።  አንዱ  የንጉሡ ሚኒስትር ልብሱ ከሚደወርበት ሔዶ እንዲያይ ተላከ። ባዶ የሽመና ዕቃ ብቻ አየ። ልብስ የሚባል የለም። “አይ ክፉና ተንኮለኛ ከምባልስ” በሚል መንፈስ ያላየውን እንደ አየ አድርጎ ተናገረ። ሌሎች ሹማምንትም  እንዲሁ አደረጉ። ልብሱ ተጠናቀቀ ተባለና ወደ ንጉሡ ተወሠደ። ንጉሡም በግብዝነት ያላየውን እንደ አየ፣ የሌለውን እንደ አለ አድርጎ “ልብሱን ለበሰና” በሰልፍ ወጥቶ ወደሚጠብቀው ህዝብ በሰረገላ ሆኖ መታየት ጀመረ። ተመልካቹ ሁሉ “ክፉና ተንኮለኛ” ላለመባል  ሲል “ግሩም ድንቅ” እያለ የንጉሡን አዲስ መጎናጸፊያ አደነቀ። ንጉሡ ግን ራቁቱን ነበር። ታዲያ ከሰልፈኛው ህዝብ መካከል አንድ ህፃን ልጅ እንዲህ አለ፤ “እናንተ ንጉሡ ራቁቱን ነው።” ከዚህ ቃል በኋላ የታወረው ህዝብ አየ። ንጉሡም ከቀን እንቅልፉ ነቃ።
ሐዋርያው ጴጥሮስ በአንደርሰን ተረት ውስጥ እንዳለው ህፃን ነው። የአንደርሰን የራሱም ተፈጥሮ በተረት እንደተፈጠረው ህፃን ነው። ህፃኑ ራሱ አንደርሰን ነው። ዓለማየሁ ገላጋይም ጴጥሮሳዊ ነው። ነገረሥራው ሁሉ እንደ ደራሲው አንደርሰን ነው። የወሪሳ ተራኪና የአንደርሰን ተረት ውስጥ ያለው ህፃንም አንድ ናቸው። ገበናችንን ይገልጡታል፤ጉዳችንን ያሣዩናል።
ወሪሳዊ ተውሳክ
ወሪሳ ስርቆትና ዝርፊያ የነገሡበት የጉድ ሠፈር ነው። በዚያ ሰፈር “ቢዝነስ” መስራት ማለት መስረቅ፣ ማጭበርበር፣ መዝረፍና መግደል ነው።  ይኸ በሀገር ደረጃ የተዋቡና የሚያደናግሩ ቃላት እየተጠቀምን “ሙስና እና ኪራይ ሰብሳቢነት” የምንለው ነገር በወሪሳ ሰፈር ውስጥ ራቁቱን የሚመላለስ ጀግና ነው። በወሪሳ ውስጥ ሰርቶ የሚበላው ሞኙ ተራኪ ብቻ ነው። በዚያ ምድር ሰርቶ የሚበላ “ፋራ” ነው። የሚበላው፣ የሚሰረቀው ግን ማን ነው? የሚበላው ወደ ሥራ የሚሠማራው ሞኝ ወይም ፋራ ነው።  ስለዚህ ወሪሳ ፓራሳይት ወይም ተውሳክ ነው። ተውሳክ በሽታ ነው። የራሱን ምግብ አያመርትም። በተክል ወይም በሰው ላይ ሰፍሮ ሰለባውን እስኪሞት ድረስ ይበላዋል። ሌባ፣ ዘራፊ፣ ጉቦኛ፣ ሙሰኛ፣ ወይም ኪራይ ሰብሳቢ የህብረተሰብ ተውሳክ ነው።
በሀገር ደረጃ ሲታይ ኢትዮጵያም ትልቋ ወሪሳ ነች። ሳንሰራ የምንበላ ሌቦችና ለማኞች እየሞላናት ነው። ሰርቶ የሚበላው ሁሉ እንደ ወሪሳው ተራኪ ፋራ ነው። በዚሁ ከቀጠልን የሚቀሩን ፋራዎች ቁጥር እየተመናመነ ይሔድና ምንም ይሆናል። ያኔ እንግዲህ በአሪፍ የሚበላው ፋራ ይጠፋል። ከዚያ ትልቁ አሪፍ ትንሹን አሪፍ መብላት ይጀምራል። የወሪሳ ነዋሪዎች ሁሉም “ብልጥ” ናቸው። ስለዚህ አይሠሩም። ይሠርቃሉ። የኢትዮጵያ ሰዎችም እንደ ወሪሳ ሰፈር ሰዎች ብልጠታቸው እየጨመረ “ፋራነት” የተባለውን ሠርቶ መብላትን እያስወገዱ ነው።
በ1980ዎቹ አጋማሽ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪ እያለሁ የሰማሁት አንድ ነገር ሁሌም ከአእምሮዬ አይጠፋም። ሴትየዋ በስድስት ኪሎ ካምፓስ አቅራቢያ ጠላ ቤት አላቸው አሉ። ልማደኛ ተማሪዎች እዚያ ያመሻሉ። ኮማሪትዋ የልጆቹን የትምህርት መስክ እየደጋገሙ በመጠየቅ ብዙ አውቀዋል። ታዲያ አንድ ቀን፣ “እኔ ምለው” አሉ። “እኔ ምለው፣ አንዳችሁም እንኳ ጉምሩክ የሚባል ትምህርት አትማሩም?”
የትምህርት ባህላችንም ከሞላ ጎደል ይኸው ነው። ድሮም ሆነ አሁን ያው ነው። ከጥቂት “ፋራዎች” በስተቀር የትምህርት ሥርዓቱ ያፈራልን የወሪሳ መዓት ነው። እንደ አማርኛ አስተማሪው ተራኪ ፋራ የሚሆኑ ጥቂት ናቸው። ሌላው “ግራጁዌት” ሁሉ ወሪሳዊ ነው። አሁን ደግሞ ሁሉም “ነቄ” ሆኗል። ሠርቶ የሚበላ ፋራ እንደ ዳይኖሰር ጠፍቶ ሊያበቃ የቀረው አንድ ሐሙስ ነው። ዛሬ ረቡዕ ነው። ነገ ማለዳ ላይ “አሪፍ” ነን ያሉ ሁሉ “ፋራ” እንደሆኑ ይረዱታል። አጉል አሪፍነታችንን በቶሎ ካላቆምን መጨረሻችን አያምርም። ተረቱ የፉክክር ቤት ሳይዘጋ ያድራል ይላል። ፉክክር የብልጥ ነው፤ብልጠት እናበዛለን።
ገዢዎቻችን
በሀገራችን አንድ የሚገርመኝ ነገር አለ። ሁሉም ፖለቲከኛ ነው። ሁሉም ለፍላፊ ነው።  ሁሉም ሥልጣን ይፈልጋል። ሁሉም መግዛት ይፈልጋል። ሰርቶ የሚበላ ገበሬ ብቻ ነው። ሌላው ገበሬ የሚያመርተውን ይበላል። ከዚያም አልፎ የገበሬው የበላይ ይሆናል።
ስንትና ስንት ህዝብ እያለበት አገር የንጉሥ ነች ይባላል። ንጉሥ ዘራፊ ነው። ዘራፍ ማለት ዘራፊ ከሚለው ቃል የወጣ ነው። ዘራፊ ጀግና ነው። የሚሰርቅና የሚዘርፍ ጀግና ነው ይባላል። ንጉሡ ዘራፊ ነው። ሀገር ሙሉ የኔ ነው ብሏል። የንጉሡ አንጋሾች ዘራፊዎች ናቸው። ሳይሠሩ ነው የሚበሉት። የንጉሡ ወታደሮችም ዘራፊዎች ናቸው። ሳይሠሩ ነው የሚበሉት።
መንግስቱ ለማ የአባታቸውን ትውስታዎች “ትዝታ ዘ አለቃ ለማ” በሚል መጽሐፍ አሳትመውታል። በዚህ መጽሐፍ ውስጥ አስደማሚ ትረካዎች አሉ። አለቃ ለማ አባታቸውን ወደ ትምህርት ላከኝ ብለው የሙጥኝ ይላሉ። ይኸ የዛሬ 150 ዓመት ገደማ ነው። ለማ ካልተማሩና ካህን ካልሆኑ አራሽ ገበሬ ሊሆኑ ነው። በወቅቱ፣ ገበሬ በወታደር ይዋረዳል። ንብረቱን ይቀማል። ሚስቱን ይነጠቃል። በዚያ ሳቢያ እርሻውን እየተወ “የጌታ የሚያድር” ይበዛ ነበር። እንግዲህ አገሩ ሁሉ ገበሬ ነው። የሚያመርት እሱ ነው። እሱ ግን ይዘረፋል፤ ይዋረዳል። ከዚህ ውርደት የሚተርፍ ፍጡር ቢኖር ካህን ብቻ ነው።  ስለዚህ አለቃ ለማ፣ አልቅሰውና ጮኸው ወደ ዘመኑ ትምህርት ተላኩ።
ካህንና ወታደር የገዥዎች እጅ ናቸው። ካህን ህዝቡን በመስበክ መንፈሱን ያኮላሸዋል። ወታደር ደግሞ ህዝቡን በጦር እየወጋ አካሉን ያደቅቀዋል። በመንፈስና  በአካል የተኮላሸ ህዝብ ብቻ ነው ሊገዛ የሚችል። በወቅቱ ይገዝዛ የነበረው ገበሬው ነው። ከባህላዊው ወደ ዘመናዊው ትምህርት ስንሸጋገርም የሰው ዓላማ ተምሮ ለመሥራት አልነበረም። ይህ መንፈስ አሁንም አለ። የተማረ ሁሉ ስሙ ይለያይ እንጂ ያው ካህንና ወታደር ነው የሚሆነው። የገዥ እጅ ነው። ገዥው የውጭም የሀገር ውስጥም ሊሆን ይችላል። ቁጭ ብዬ ልብላ ብሎ የሚማር ሁሉ ጤነኛ አይደለም። ተውሳክ ነው። ትምህርትን እንደ ጽድቅ ነው የምናየው።  ከጭለማ ወደ ብርሃን የምንወጣበት መንገድ ነው እየተባለ ብዙ ተሰብኳል። እውነታው ግን እሱ አይደለም። ትምህርት የሰለጠኑ ባሮች የማፍሪያ መሣሪያ የሆነበት ጊዜ ብዙ ነው። ትምህርት የዕድገት መሠረት ነው እያልን ስንዘምር አንድ መቶ ዓመት ደፍነናል። እውነታው ግን እድገት የትምህርት መሠረት መሆኑ ነው። አድጎ የተማረ እንጂ ተምሮ የበለፀገ ሀገር የለም።
እነዚህ ሁሉ ውዥንብሮች ወሪሳዎችን እያበዙና “ፋራዎችን” እየቀነሱ ነው። ወደ እውነታው ብንመለስ ይሻላል። እንደ ግብዙ ንጉሥ የዘመኑ ሥልጣኔ ያስገኘውን ድንቅ መጎናጸፊያ ለብሰናል ብለን ራሳችንን ባናታልል ይበጀናል። በብዙ ቦታ እርቃናችንን ነን። ብልጠት አብዝተን የወሪሳ አገር እየሆንን ነው።
ሺ-ትርገጥ እና ጭፍን
ሺ-ትርገጥ የአምበርብር ልጅ ነች። አባትና ልጅ በቀመሩት ታላቅ ሤራ ሺ-ትርገጥ የተራኪው ህጋዊ ሚስት ትሆናለች። ባህሪዋ ጥልቅና ድብልቅልቅ ነው። በአካላዊ መጠን አባትዋ ደቃቃ ነው። እሷ ግን በእናትዋ ወጥታ ግዙፍ ወይም መንዲስ ነች። ግዙፍነትዋ ልዩ ነው። ለእኔ ከጉማሬ እናትና ከዳይኖሰር አባት የተወለደች ሆና ትታየኛለች። ተራኪው በአነስተኛ የሥጋ ተራራ ይመስላታል። አንዳንዴም ከደብረ ዳሞ ተራራ ጋር ያመሳስላታል። ተራኪው በገመድ እየተጎተተ ይወጣል። የገመዱ ጎታች የአማቱ፣ የሺ-ትርገጥ አባት አምበርብር ነው። ይህ ገለፃ የተራኪው ነፍስ በማን እጅ እንደሆነች ይነግረናል።
እዚህ ላይ ፃድቁን ያመላልስ ነበር የተባለው ዘንዶም በማን እንደሚመሰል መገመት ይቻላል። ሺ-ትርገጥ ተራኪውን የምታጠምደው በአልጫና በቀይ የበግ ወጥ ነው። ተራኪው በሆዱ ተጠምዷል። ደሞዙ ከወር ወር አይደርስም። ይርበዋል። በተለይ አንድ ቀን አሜሪካ በ77ቱ ረሀብ ለኢትዮጵያ እንደደረሰችላት ዓይነት ነው ሺ-ትርገጥ አገልግል ተሸክማ በረሀብ ዝሎ በ7 ሰዓት ላይ ከቤቱ አልጋ ላይ ለተንጋለለው ተራኪ የምትደርስለት። ሺ-ትርገጥ ተራኪውን ጭፍን ከተባለች ወዳጁ፣ አሜሪካ ደግሞ ኢትዮጵያን ከሶቪየት ኅብረት ወይም ከሶሻሊስቱ ጎራ ትነጥላታለች።
ሺ-ትርገጥ ተራኪውን ከማግባትዋ በፊት አንድ አገር ልጆች ወልዳለች። በቁጥር ግን አራት ናቸው። ቤት ሞልተው ይንጫጫሉ። የቤቱ ግድግዳ “ፖሊስና እርምጃው” በተሰኘ ጋዜጣ ከዳር እስከ ዳር ለብሷል። ልጆቹ በአያታቸው እየተመሩ እነዚህን ጋዜጦች ያነባሉ። ተራኪው ባልወለዳቸው ልጆች ይከበባል። በህልም አፈታት እነዚህ ልጆች ማን ናቸው?
የተራኪው የፀሐይ ኮከብ ሐመል እሳት ወይም ኤሪስ ነው። ኮከቡ ከኢትዮጵያ የምድር ኮከብ ጋር ይገጥማል። እሱ የኢትዮጵያ ጭንብላዊ ተምሳሌት ነው። ባልወለዳቸው ልጆች የአሳዳጊነት እዳ ገብቷል። የርሱ ገቢ ለነዚህ ሁሉ ልጆች ማሳደጊያ አልበቃም ማለት ይጀምራል። ልጆቹ የዐባይ ወንዝ ጥገኛ የሆኑት ሀገሮች ህዝቦች ናቸው። ግዙፍዋ ሺ-ትርገጥ የአሜሪካ ተምሳሌት ነች። ከዚህ በላይ ለብልህ አይነግሩም፤ ለአንበሳ አይመትሩም ነው ተረቱ። አሁን ደቃቃው የተራኪው አማት፣ የሺ-ትርገጥ አባት የየቷ ሀገር ተምሳሌት እንደሆኑ መገመት የማይችል አንባቢ አይኖርም።
ከሺ-ትርገጥ በተጓዳኝ ሌላ ገፀባህሪ አለች። ጭፍን በመባል ትታወቃለች። ለልቦለዱ ተራኪ ብዙ ተረት ትነግረዋለች። በጭፍን አንደበት የአማርኛ ተረትና ምሳሌዎች ኩላሊታቸው ፈርጦ ጨጓራቸው ይዘረገፋል። ፍቅር እስከ መቃብር የተባለው ልቦለድ በጭፍን “ቨርዥን” ሲተረክ ከፍ ያለ የእሳት እቶን ወይም “ካምፋየር” ውስጥ የገባ ጀሪካን ይሆናል። ሀዲስ ዓለማየሁ ሊብራ ናቸው።
ተራኪው ከጭፍን ጋር አፍላጦናዊ ወደ አልሆነ “ሮማንቲክ” ፍቅር ውስጥ ይገባል። ልቡ አብዝቶ ወደርሷ ይሳባል። ከጭፍን ጋር ያለው ፍቅር በሺ-ትርገጥ የጋብቻ ሤራ ይጨናገፋል። ተራኪው ውሎና አዳሩን የአማቹ ሰፈር ከሆነው ከእሪበከንቱ ሲያደርግ ከአክስቱ የወረሰው የወሪሳ ቤት ወና ይሆናል። ኋላ ላይ ቤቱ በጭፍን እየተጎበኘ እንደሆነ እናውቃለን። ጭፍን የምሥራቁ ዓለም ሀገራት ተምሳሌት ነች። ከቻይና፣ ከጃፓን፣ ከህንድ፣ እና ከኮሪያ አንዱን መምረጥ ይቻላል። የቻይና ኮከብ ሊብራ ነው።
በወናው ቤት ውስጥ ተዳብሎ መኖር የሚጀምር ሌላም አስር ዓመት ያልሞላው የእሪበከንቱ ልጅ አለ። ይህ ልጅ ድመት በሸምቀቆ አድርጎ በሰንደቅ መስቀያ ሲሰቅል የኢትዮጵያን የህዝብ መዝሙር ይዘምራል። ይህ ልጅ ማንን ይወክላል? ማለፊያ የሆነ ህልም ፈቺ ያስብበት። የወና ቤቱ፣ የጭፍንና የሰይጣን ግልገል የሆነው ልጅ ህልማዊ ትንታኔ ብዙ ትንቢታዊ ድምፆች አሉበት። የድመት ገዳዩ ልጅ ዓላማ አንበርብርን ለመግደል ነው። ይኸ ነገር በአጠቃላይ የፀረአይሁድን በተለይ ግን የኢራንና የእስራኤልን ባላንጣዊ ጠላትነት ይወክላል። ልጁ በተለይ የሚወክለው ኦሳማ ቢን ላደንን ነው። እርሱ የሺትርገጥን ልጅ ለመግደል ሙከራ አድርጎ ሸሽቷል፤ በመጨረሻም በወሪሳ ሰፈር በተራኪው ቤት ተሸሽጓል።
የስምንት ዓመቱ የመጣባቸው ልጅ የሺ-ትርገጥን የመጨረሻ ልጅ በገመድ ሸምቅቆ ለመግደል ሙከራ አደረገ። ከዚያ በኋላ ከእሪበከንቱ የወንዝ ጉራንጉር ውስጥ ሸፈተ። በመቀጠል ወሪሳ ከሚገኘው ከተራኪው ቤት ውስጥ ተሸሸገ። አንበርብር እያሳደዱት ነው። የአሜሪካን የ “ናይን ኢለቨን” (9/11) ሽብር ያደራጀ ነው የሚባለው ኦሳማ ቢን ላደን በመጨረሻ ተሸሽጐ የተገኘው የአሜሪካ ተባባሪ ከተባለች አገር ጉያ ውስጥ ነው።
ሺ-ትርገጥ ከተራኪው አርግዣለሁ የምትለው ልጅ የመጣባቸውን የመሰለ ሆኖ እንዲወለድ ትመኛለች። ከዚያም ያለፈ ጥረት ታደርጋለች። ሐሳቧ የመጣባቸውን ልጅ ከበራፍ ተቀምጣ እሱ ሲያልፍና ሲያገድም ማየት ነው። እርጉዝ ሴት ደጋግማ ያየችውን ሰው የመሰለ ትወልዳለች ከሚል እምነት ተነስታ ይመስላል። የሷ ታሪክ ከምን እንደደረሰ ሳናውቅ ነው የ“ወሪሳ” ትረካ የሚያበቃው።
አሜሪካ የኦሳማ ቢን ላደን ነገር ሲያንገበግባት ቆየ። በርሱ ዳፋ ኢራቅ ተደበደበች። ወረራው ወደሌላም አገር ተዛመተ። ይህ እንግዲህ በጆርጅ ደብሊዉ ቡሽ ዘመን ነው። አሜሪካ በቀጣይ ያገኘችው መሪ ባራክ ሁሴን ኦባማ ሆነ። ይህ ሰው ቢያንስ በስሙ ከኦሳማ ቢን ላደን ጋር አንዳች መመሳሰል  አለው። አሜሪካ እንደ ሺ-ትርገጥ የልጇን ገዳይ የመሰለ መውለድ ተመኝታ ነበርን የሚያስብል ግርምታ ይጭራል።
ኮከብን በተመለከተ ጥቂት ቃላትን እንጨምር። የሺ-ትርገጥ ኮከብ ካንሰር ወይም ሸርጣን ውሀ ነው። የጭፍን ኮከብ ሊብራ ነው። ከውጭ ስትታይ ወንዳወንድ የምትመስል ነች። በቅርበት ግን ሞንሟና የሆነች ሴት ነች። ደራሲው ዓለማየሁ ገላጋይ፣ የልቦለዱ ተራኪ ገፀባህሪ፣ ክርስቺያን አንደርሰን፣ በአንደርሰን ተረት ውስጥ ያለው ህፃንና ችኩል የሆነው ሐዋርያው ጴጥሮስ ሁሉም ኤሪስ ናቸው።
አምበርብር የቶረስ፣ የስኮርፒዮ፣ የካፕሪኮርንና የአኳሪየስ ኮከቦች በጎጂ መልኩ ተሰባጥረው የሚታዩባቸው ገፀባህሪ ናቸው። ከዚህ ውስጥ የጨረቃ ኮከባቸው ካፕሪኮርን ነው። ይኸ ኮከብ የአይሁድ ወላጆች ኮከብ ነው ይባላል፤ በጨረቃና  በወላጅነት ውስጥ።
የግዙፎቹ የሺ-ትርገጥ ኮከብና የአሜሪካ ኮከብ ካንሰር ነው። የአሜሪካ ሙሉ ኮከብ ስብጥሩ በጥሩ ሁኔታ የተቀመረና የታሰበበት ቢሆንም አንድ ወሳኝ ጉድለት አለበት። አሜሪካ ውስጥ ያሉ እስቴቶች ኮከብም ይታወቃል። የትኞቹም ግዛቶች ግን የኤሪስ ኮከብ የላቸውም። በዚህ ሳቢያ አሜሪካ በጦርነቱ ዘርፍ የኤሪስን ጀግንነት አልታደለችም። በየወቅቱ በገጠመቻቸው ጦርነቶች እንደ ኤሪሶቹ እንግሊዞችና  ጀርመኖች የሚያኮራ ጀግንነት አሳይታ አታውቅም። ሀገሪቱ ውስጥ ኤሪስ ግዛቶች ስለሌሉ አሜሪካ የኤሪስ ኮከብ ላላቸው ሰዎች ብዙም አትመችም ይባላል። ይህ ግን ትንሽ የተጋነነ ነው። ለብዙ ኤሪሶች ገነት የሆነችባቸው ጊዜያቶች ብዙ ናቸው። እንዲያም ሆኖ ግን ለኤሪስ ግለሰቦች አስጨናቂ የምትሆንበት ጊዜ አለ። ከውሀ ኮከብዋ ጋር ያለው ሰፊ እንክብካቤዋ እሳቶቹን ኤሪሶች ቀዝቀዝ ያደርጋቸዋል። ችግሩ ከዚህ ብቻ የሚመነጭ ነው።
ካንሰርዋ ሺ-ትርገጥ በራስዋ ጥሩ እናትና ወላጅ ነች። ኤሪሱ ተራኪ ግን ይፈራታል። አፍና የምትገድለው ይመስለዋል። እሳት ውሀን የሚፈራውን ያህል ሲያያት ይርበደበዳል፤ ፍርሀቱ ውስጥ ግን ማሾፍም አለበት። የኤሪሱ ተራኪ ኮከብ የገጠመው ከሊብራዋ ጭፍን ጋር ነው። ኤሪስና ሊብራ ዋልታዊ ኮከቦች ናቸው። በተለይ በተቃራኒ ፆታዎች መካከል ሲሆን ሁለቱ ኮከቦች አብዝተው ይሳሳባሉ። ነገሩ ሁለት ማግኔቶች በተቃራኒ ጎናቸው ሲጠጋጉ እንደሚሳሳቡትና እንደሚሳሳሙት ዓይነት ነው። ሊብራዋ ጭፍን የኤሪሱ ተራኪ ተቆርቋሪ ነች። ከአደጋ ልትከላከለውም ትተጋለች። አልሆንለት ይላል እንጂ እርሱም ከእቅፏ ባይወጣ ይመርጥ ነበር።
የወሪሳ ሰፈር የአኳሪየሳዊት ኢትዮጵያ ተምሳሌት ነች። ሊነጋ ሲል በጣም ይጨላልማል እንደሚባለው ክፉ ዛር ለቋት ሊሔድ ሲቃረብ የእብደቷ መጠን ከፍተኛውን ደረጃ ይደርሳል።  የዚህ ውክልናም ወሪሳ ነች። ወሪሳ ወደ ሞት እንጂ ወደ ህይወት የምትሄድ አትመስልም። ነገር ግን የተስፋ ጭላንጭል አለ። ፀሐይ ትወጣለች። የኢትዮጵያ ኮከብም በቅርቡ ሙሉ በሙሉ ይወጣል። ከዚያ በኋላ ኢትዮጵያ ደጅ እያደረች ኮከብ አትቆጥርም። የእንጀራ እናትዋንም በወላጅ እናትዋ ትተካለች። ወሪሳንም እሪበከንቱንም አትሆንም። ምሥራቅም ምዕራብም አትልም፤ ራስዋን ትችላለች፤ ራስዋን ትሆናለች።
በወሪሳ አስራሁለቱም ኮከቦች መጥፎና ደካማ ጎናቸውን አፍርጠውና ገልጠው የዛር ድቤአቸውን ይደልቁባታል። የወሪሳ መንደር ሰዎች በኤሪሳዊ ድፍረትና ጭካኔ ይተራረዳሉ፤በቶረሳዊ ስግብግብነት ይቀማማሉ፤ በጄሚናዊ መንታ ምላስ ታሪካቸውን ይከታትፋሉ፤ በካንሰራዊ ጥፍር ይነጣጠቃሉ፤ በሊዮአዊ ማን አለብኝነት ያጓራሉ፤ በቪርጎአዊ ንዝንዝ ይጠቃጠቃሉ፤ በሊብራዊ ስንፍና ቀን ከሌት ያንኳርፋሉ፤ በስኮርፒአዊ በቀል በውድቅት ሌሊት ይገዳደላሉ፤ በሳጁታሪየሳዊ ልቅ አንደበት ይዘራጠጣሉ፤ በካፕሪኮርናዊ ቅዝቃዜ ይጠላለፋሉ፤ በአኳሪየሳዊ የቀውስ ዛር ልብሳቸውን ጥለው ያብዳሉ፤ በፓይሰሳዊ ቅዥት ውዥንብር ይፈጥራሉ። ሁሉም አብደዋል። የበረከትን ዝናብ ይናፍቃሉ። ሁሉም ታውረዋል። የበረከትን ጮራ ይሻሉ። ሁሉም እየጓጎሩ ነው። ከቅዠታቸውና ከአስፈሪ ህልማቸው ካልባነኑ አይድኑም።
አንድ ሀገር ልጅ ያላትን ሺ-ትርገጥን ያገባው ተራኪ የእንጀራ ልጆቹ ቀላቢ ይሆናል። ኋላ ላይ ሙሉ ደሞዙን ለሚስቱ ያስረክባል። ለራሱ የአውቶብስ መሳፈሪያ የሚሆነው አንድ ብር እንኳን ይከለከላል። ይኸ የዐባይ ወንዝ ተምሳሌት ነው።
ኢትዮጵያ የራሷንም ድርሻ እንኳን ስትከለከል ቆይታለች። የሺ-ትርገጥ ልጆች ከዐባይ ተፋሰስ አገሮች ውስጥ በተለይ የግብፅ አገር ህዝቦች ተምሳሌቶች ናቸው። አሁን ጥያቄው የአማርኛ አስተማሪ ነኝ የሚለው ተራኪ ሙሉ ደሞዙን እየተቀማ ለራሱ አንድ ብር እንኳን እየተከለከለ እስከመች ይቆያል ነው? ተራኪው በምግብም እየተበደለ ይራባል። አንድ ሁለቴ ጭፍን ሰርቃ ካገኘችው ስትጋብዘው እናያለን። ተራኪው ለነፃነቱ እየቃተተ ነው። ኢትዮጵያ የዐባይን፣ ተራኪው ደግሞ የደሞዙን ነፃነት ይሻሉ። ልቦለዱ በብዙ ዓለማቀፋዊ ትእምርቶች የተሞላ ነው፤ከላይ የዘረዘርኩት ጥቂቱን ብቻ ለቅምሻ ነው።  
ማጠቃለያ
የዓለማየሁ ገላጋይ ወሪሳ ለየት ያለ ድርሰት ነው። የልቦለዱ ፋይዳ ከመዝናኛ ግብአትነት አለፍ ይላል። ልቦለዱ ህልም ነው። ህልሙ ውስጥ ህመም አለበት። ህመሙ የኅብረተሰብ ህመም ነው። ህልሙ መፈታት፣ ህመሙ ደግሞ መዳን አለበት።
“ሀገሬ ኢትዮጵያ ሆይ! እስኪ ህልምሽን ንገሪን” ለምንል ዜጎችዋ፣ ጦቢያ ልክ የዛሬ 50 ዓመት ህልሟን በፍቅር እስከ መቃብር ነግራናለች፤ ዛሬ ደግሞ በወሪሳ። ያኔ በሊብራው ሐዲስ ዓለማየሁ፤ ዛሬ በኤሪሱ ዓለማየሁ ገላጋይ። ህልሟን መናገር የርሷ፣ ህልሟን መፍታት ደግሞ የኛ ድርሻ ነው። ያለፈውን ፈለግና መንገዳችንን ብቻ ሳይሆን የመፃኢውን ዒላማና ዓላማችንን ጭምር በሀገራችን ህልም ውስጥ እናነበዋለን፡፡  
ልቦለድን እንደ ህልም ስንፈታ የምናቀርበው ትርጓሜ ፈርጀ ብዙ ነው መሆን ያለበት። አንዱ ትእምርታዊ ገፀባህሪ ወይም የትረካ አንጓ ከአንድ በላይ ትርጓሜዎች ይኖሩታል። የዚህ ዓይነቱን የሥነኂስ ስልት በቅጡ ለመረዳት ብዙም ርቀን መሔድ አያስፈልገንም። እዚሁ ሀገራችን ለዘመናት የሰፈነ የአንድምታ ትርጓሜ የሚባል ባህልና ጥበብ አለን።
ይህን ሒሳዊ ብእሮግ ከአንድምታ ትርጓሜ ጠቅሼ ልቋጭ። በመጽሐፍ ቅዱስ በዘፀአት መጽሐፍ በምእራፍ ሁለት፣ በቁጥር አምስት ላይ እንዲህ የሚል ዓረፍተ ነገር አለ። “ወወረደት ወለተ ፈርዖን ከመ ትትሐፀብ በውስተ ተከዚ” [የፈርዖን ልጅ ገላዋን ትታጠብ ዘንድ ወደ ዐባይ ወንዝ ወረደች።] የሀገራችን ሊቃውንት ለዚህ ዐረፍተ ነገር ያስቀመጡት የአንድምታ ትርጓሜ ቀጥሎ ያለውን ይመስላል።
ተርሙት የምትባል የፈርዖን ልጅ ልትታጠብ ወደ ፈሳሹ ወረደች፤ ስለ ምን ቢሉ በፈሳሹ ዳር እንደ መዋት ያለ ነበር፤ ኮብሽ የሚባል ደዌ ነበረባትና ለመጠመቅ፤ አንድም ነጋዴ ወዳጅ ነበራትና ያንን ለመቀበል፤ አንድም አዞ ጉማሬ ታመልክ ነበረችና ስለዚህ፤አንድም በጎርጎራ ሳለ ያጤ መለክ ሰገድ ልጆች ውሀ ዋና ይማሩ እንደነበረ ውሀ ዋና ልትማር ነው።
የፈርዖኑ ልጅ የተርሙት ወደ ዐባይ ወንዝ መውረድ አራት አንድምታዊ ትርጓሜዎች ተሰጥተውታል፤ አንድም ለህክምና ጠበል፤ አንድም ለድብቅ ፍቅር፤ አንድም ለጉማሬ አምልኮ፤ አንድም ለውሀ ዋና ትምህርት በሚል። አንድምታዊ ትርጓሜ ጥልቅ ንባብ ነው። እንደ ቁጥር ስሌት ሁለት ሲደመር ሦስት አምስት ነው ብሎ አያቆምም፤ ከዚያ ብዙ ያልፋል።
 ይህን ድንቅ የሆነ የጥልቅ ንባብ ባህላችንን ወደ ልቦለዶቻችንም ልናመጣው ይገባናል ብዬ አስባለሁ። የወሪሳ ትንታኔ ብዙ የሚሔድ ነው፤ ላሁኑ ግን በዚሁ ይብቃኝ።
 [ድኅረ-ማስታወሻ፤ ፍካሬ ኢትዮጵያ በተባለው መጽሐፌ ውስጥ የፍቅር እስከ መቃብር የአንድምታ ትርጓሜ ይገኛል። የፈጠራ ድርሰትን እንደ ህልም የማየትን የሒስ ስልት፣ ሚካኤል ሺፈራው በምስጢረኛው ባለቅኔ መጽሐፉ ተግብሮታል። ስለእርሱ የሒስ ስልት በሌላ ጽሑፍ ለማቅረብ እቅዱ አለኝ።]

Monday, 31 August 2015 09:11

የግጥም ጥግ

አረማሞ
ተደባልቆ በቃይ
ሲናር አረማም
ሲዘራ ካልዘሩ
ምርጥ ዘር አክሞ
ገለባ ነው ትርፉ
ቀን ቆጥሮ ለከርሞ፡፡
ሙግት
ያኮረፈ ሌሊት
…መንጋቱን የረሳ
ውስጤ እያደመጠ
…የነፍሴን ጠባሳ
እርምጃ ውልክፍክፍ
…ጉዞውም የአንካሳ
የጨለማ ሙግት
…የንጋት ወቀሳ፡፡
ጀንበሩ ወልደዮሐንስ
(ከኒዮርክ ቡፋሎ)
* * *
“አንተ” - ማለት!...
“አንተ” ማለት፡-
ብዙ ነህ!
ብዙ - ብዙ! … የብዙ - ብዙ!
“አንተ” ማለት ….
አገር ነህ፣
አገር ከነጉዝጓዙ፡፡…
ያገር ጉዝጓዙ…
አቤትና አቤት … አቤት! ብዛቱ፡…
ጂባው፣ አጐዛው - ጀንዴው - ቁርበቱ፡፡…
ተራራው - ሸለቆው - ዱሩ፣
እንኮይ - መስኩ፣
መብሰክሰኩ…፤
እሾህ አሜኬላው - ቆንጥሩ…
ባንድ ሌማት
እሬት!
ምሬት!
የአጋም ፍሬው --- ጣዝማ ማሩ፣
ደግሞም፡-
አድባር! አውጋር! … ያለ መጣፍ፣
አማኝ - እምነት
በመጣፍም
ያለ መጣፍ፡፡…
መቼም - ሰው “አገር ነውና”
አገርም “ሰብዓ ምርቱ”
ታሪክ - ቋንቋ - ባህል - ቀኖናውና
- ትውፊቱ፣
እሱ ነው! የማንነትህ እትብቱ፡፡…
ከእኒህ - መነቀል…
ማለት፡-
ከሥር - መመንገል!
ካናት - መቃጠል!
ከእግር - መመንቀል!
ማለት ነው፣
አገር እንደ ሰው!!
ሰማህ!?
(ወንድዬ ዓሊ)

   መርዛማ የሃሞት ፈሳሾች በጉበታችን ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንደሚያስከትሉና የጉበት ሴሎችን ቀስ በቀስ ወደ ቲሹዎች በመቀየር ከጥቅም ውጪ ሊያደርጉት እንደሚችሉ ተጠቆመ፡፡
በሔድልበርና ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች የተደረገውና በቅርቡ ይፋ የሆነው አንድ ጥናት እንደሚያመለክተው፤ ሃሞት የጉበት ሴሎች ጋር እንዳይደርስ የሚከላከሉት አካላት ሲጠፉና መርዛማ የሃሞት ፈሳሾች የጉበት ሴሎች ጋር ደርሰው ጉዳት ሲያስከትሉ ጉበት Cirrhosis (ኪሮሲስ) ተብሎ ለሚጠራው የጉበት በሽታ ይጋለጣል፡፡ ይህ በሽታ ደግሞ ጉበታችን ተግባሩን በአግባቡ እንዳያከናውን እንቅፋት በመሆንና ሴሎቹን ወደ ቲሹዎች በመቀየር ጉበትን ሙሉ በሙሉ ከጥቅም ውጪ የሚያደርግ መሆኑን ጥናቱ አመልክቷል፡፡
ለዚህ ችግር መነሻ ምክንያቶች ሊሆኑ ይችላሉ ተብሎ በጥናቱ ላይ ከተገለፁት መካከልም የጉበት ቫይረሶች፣ ከፍተኛ የአልኮል መጠጥ፣ መድሃኒቶችና ልዩ ልዩ ኬሚካሎች እንደሚገኙበት ተጠቁሟል፡፡

ቴትራሳይክሊን፣ የደም ብዛትና የካንሰር ህመም መድሃኒቶች የጉበት ስብ በሽታን ሊያስከትሉ ይችላሉ

  ጉበት መርዛማ ንጥረ ነገሮች በደም አማካኝነት ወደተለያዩ የሰውነታችን ክፍሎች ውስጥ ዘልቀው ገብተው ጤናችን አደጋ ላይ እንዳይወድቅ ብርቱ ተጋድሎ የሚያደርግ የሰውነታችን ክፍል ነው፡፡ በምንመገባቸው ምግቦችና መጠጦች እንዲሁም ለተለያዩ በሽታዎች ማከሚያነት በምንወስዳቸው መድሃኒቶች ውስጥ የሚገኙና ለሰውነታችን አላስፈላጊ የሆኑ ንጥረ ነገሮች ሁሉ በጉበት አማካኝነት እየተመረጡ እንዲወገዱ ይደረጋል፡፡ ቀይ የደም ሴሎቻችን የአገልግሎት ዘመናቸውን ሲያጠናቅቁ የሚወገዱትም በዚሁ በጉበታችን አማካኝነት ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ጉበታችን ፋቲ አሲድ፣ ፕሮቲን፣ ጉሉኮስንና በሽታን ለመከላከል የሚያስችሉ ንጥረ ነገሮችን እያመረተ ለሰውነታችን ክፍሎች እንደዳረሱ ያደርጋል፡፡ የዚህ የሰውነታችን ዘርፈ ብዙ አገልግሎት ሰጪ የሆነው የሰውነታችን ክፍል በህመም መጠቃት በሰውነታችን ሥርዓተ ዑደት ላይ ከፍተኛ ተፅእኖን ያሳድራል፡፡
ጉበትን በእጅጉ በመጉዳት ከሚታወቁ ነገሮች መካከል አልኮል ዋንኛው ነው፡፡ በአልኮል ሳቢያ የሚከሰተው የጉበት ስብ በሽታ በርካቶችን ለሞት እየዳረገ እንደሚገኝ የህክምና ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡ በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የውስጥ ደዌ ሃኪም የሆኑት ዶ/ር አብርሀም ባየልኝ እንደሚናገሩት አልኮል አመጣሽ በሆነው የጉበት ስብ በሽታ የተጠቁ ሰዎች አምስት አመት በህይወት የመቆየታቸው እድል 50በመቶ % ብቻ ነው፡፡ በሽታው የጉበትን የመሥራት አቅም በፍጥነት የሚያዳክምና ከአገልግሎት ውጪ የሚያደርግ በመሆኑ በበሽታው የተያዙ ሰዎች ለህልፈት የመዳረጋቸው እድል ከፍተኛ ነው፡፡ በሽታው ምንም አይነት ምልክቶችን ሳያሳይ ሊቆይ እንደሚችል የሚገልፁት ሃኪሙ፤ ከ75% በላይ የሚሆኑት የጉበት ስብ ህሙማን በበሽታው የመያዛቸውን ምልክት የሚያሳዩት ጉበታቸው የመጨረሻ ደጃ ላይ ሲደርስና ውሃ መያዝ ሲያቅተው ነው ይላሉ፡፡ የበሽታው ስርጭት በአገራችን እየጨመረ መምጣቱን የጠቆሙት ዶ/ር አብርሃም፤ በተለይ እድሜያቸው ከአርባ ዓመት በላይ የሆኑና አልኮል አዘውታሪ ሰዎች በበሽታው የመያዝ እድላቸው ከፍተኛ እንደሆነና ከመጠን ያለፈ ውፍረት ያለባቸው ህፃናትም ለበሽታው ሊጋለጡ እንደሚችሉ ተናግረዋል፡፡
የጉበት ጤና በማቃወስ ከሚታወቁት ነገሮች መካከል አንዱና ዋንኛው በሆነው ስብ የተጠቃ ጉበት ለጉበት ስብ በሽታ የሚጋለጥ ሲሆን ይህም በሁለት ምክንያቶች የሚከሰትና ጉበትን ወደ ቃጫነት በመለወጥ ከጥቅም ውጪ የሚያደርግ በሽታ ነው፡፡ የጉበት ስብ በሽታ ከሚከሰትባቸው ሁለት ምክንያቶች መካከል አንደኛው የአልኮል መጠጥ ሲሆን ሌላው ከአልኮል ውጪ በሆኑ ሌሎች ምክንያቶች ማለትም ለተለያዩ በሽታዎች ማከሚያነት የምንወስዳቸው መድሃኒቶች እንዲሁም የስኳር በሽታ፣ ውፍረት፣ ጉሉኮስ የማከማቸት ችግርና ኮፐርና ዚንክ የተባሉ ማእድናትን በሰውነት ውስጥ ማከማቸት… ለጉበት ስብ በሽታ መነሻ ምክንያት ሆነው ይጠቀሳሉ፡፡ የአልኮል መጠጦች በጉበት ስብ በሽታ ለመጠቃት 40በመቶ ድርሻ እንዳላቸው ሃኪሙ ገልፀዋል፡፡
የአልኮል መጠጦች ለጉበት ስብ በሽታ መነሻ የሚሆኑባቸውን መንገዶች ሃኪሙ ሲያብራሩ “የአልኮል መጠጦችን በምንጠጣበት ጊዜ በአልኮሉ ውስጥ የሚገኙና ለሰውነታችን ጠቃሚ የሆኑ ነገሮች ጥቅም ላይ ከዋሉ በኋላ ቅሪቱ ንጥረ ነገር በጉበታችን ውስጥ ያልፋል፡፡ በዚህ ጊዜም የጉበታችን ሴሎች ጉዳት ይደርስባቸዋል፡፡ ይህ ደግሞ ጉበታችን በአግባቡ ሥራውን እንዳያከናውን ያደርገዋል፡፡ ጉበታችን ስራውን በአግባቡ ማከናወን ሲሳነው ወደ ሰውነታችን የገቡትና በጉበታችን አማካኝነት መጣራት የሚገባቸው ንጥረ ነገሮች በሰውነታችን ውስጥ ዝም ብለው ይከማቻሉ፡፡ በዚህ ጊዜም ጉበታችን ከመጠን በላይ በሆኑ ስቦች እንዲጨናነቅ ያደርጋል፡፡ ይህ ሁኔታ ደግሞ የጉበታችንን ሴሎች ወደ ቃጫነት በመቀየር ጉበታችን ፋትን ማመንጨትና መጠቀም እንዳይችል እንዲሁም ውሃ መያዝም እንዲያቅተው ያደርገዋል፡፡ ጉበት ሲታመም ፈሳሽ የመቋጠር አቅሙን ያጣል፡፡ ይህም ፈሳሽ በሆዳችን ውስጥ እንዲጠራቀም በማድረግ ሆዳችንን ያሳብጠዋል፡፡ መጣራት ሲኖርባቸው ሳይጣሩ ቀርተው በሰውነታችን ውስጥ የተጠራቀሙት መርዛማ ንጥረ ነገሮችም በደም አማካኝነት ወደ ጭንቅላታችን ውስጥ ገብተው ሩሃችን ያስቱናል፡፡ በተጨማሪም ፕሮቲን ጉሉኮስ፣ ፋትና በሽታን የሚከላከሉ ንጥረ ነገሮች በሰውነታችን ውስጥ መመረታቸው፣ መከማቸታቸውና በጥቅም ላይ መዋላቸው ያቆማል ብለዋል፡፡
ከአልኮል ውጭ የጉበት ስብ በሽታን ከሚያስከትሉ ነገሮች መካከል የሚጠቀሰው ለተለያዩ ህመሞች የምንወስዳቸው የተለያዩ ይዘቶች ያሏቸው መድሃኒቶች ናቸው፡፡ በተለይ ቴትራሳይክሊን፣ የደም ብዛት መድሃኒቶች፣ ለካንሰር ህሙማን የሚታዘዙ መድሃኒቶችና ሆርሞኖች በዋናነት እንደሚጠቀሱም ዶክተር አብርሃም ገልፀዋል፡፡ አብዛኛውን ጊዜ ከአቅም በላይ ካልሆነ በስተቀር መድሃኒቶች ተደራርበው እንዳይወሰዱ ለማድረግ የሚመከረው በመድሃኒቶች ሳቢያ የሚከሰቱ የጐንዮሽ ጉዳቶችን ለመቀነስ በማሰብ እንደሆነም ጠቁመዋል፡፡
የጉበት ስብ በሽታ ምንም አይነት ምልክቶችን ሳያሳይ የመጨረሻ ደረጃ ላይ ሊደርስ እንደሚችል የሚናገሩት ዶክተሩ፤ በአብዛኛው የችግሩ መኖር የሚታወቀው ጉበቱ ከጥቅም ውጪ ከሆነና ለመዳን እጅግ አስቸጋሪ ከሚሆንበት ደረጃ ላይ ከደረሰ በኋላ እንደሆነም አስረድተዋል፡፡
አንዳንድ የጉበት ስብ በሽታ ህሙማን የእግር ማበጥ፣ የአይን ቢጫ መሆን፣ በቀኝ ጐን በኩል የህመም ስሜቶች መኖር ሊያጋጥማቸው እንደሚችልም ገልፀዋል፡፡ በሽታው ስር ያልሰደደ ከሆነና ጉበቱ ሙሉ በመሉ ከጥቅም ውጪ ከመሆኑ በፊት ከተደረሰበት በተለያዩ ቫይታሚኖችና መድሃኒቶች በሽታውን አክሞ ማዳን እንደሚቻል ጠቁመው ከጥቅም ውጪ ለሆነ ጉበት የሚሰጥ ህክምና በአገራችን ደረጃ አለመኖሩን ተናግረዋል፡፡
አልኮልን አዘውትሮ አለመጠጣት፣ መድሃኒቶችን አብዝቶ አለመጠቀም፣ በአመጋገብ ላይ ጥንቃቄ ማድረግና የአካል ብቃት እንቅስቃሴዎችን ማድረግ የጉበት ስብ በሽታን ለመከላከል እንደሚረዱ ዶክተር አብርሃም ገልፀዋል፡፡

     ከተቋቋመ ስድስት ዓመታትን ያስቆጠረውና ልዩ ልዩ የህክምና ምርመራ አገልግሎት በመስጠት የሚታወቀው ውዳሴ ዲያግኖስቲክስ ማዕከል፤ 500 ለሚሆኑና የመክፈል አቅም ለሌላቸው ህሙማን ነፃ የሲቲስካንና የኤምአርአይ ምርመራ አገልግሎት ሊሰጥ ነው፡፡ማዕከሉ “ጳጉሜን ለጤና” በሚል መርህ በየአመቱ ነፃ የምርመራ አገልግሎት የሚሰጥ ሲሆን ዘንድሮም ከመንግሥት የህክምና ተቋማት ለሚመጡና አገልግሎቱን በክፍያ ለማግኘት አቅም ለሌላቸው ህሙማን ነፃ የሲቲስካንና የMRI ምርመራ እንደሚያደርግ የማዕከሉ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ዳዊት ኃይሉ ከትናንት በስቲያ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተናግረዋል፡፡ ከመንግሥት የጤና ተቋማት የሲቲስካንና የኤምአርአይ ምርመራዎች እንደሚያስፈልጋቸው በሃኪም የተፃፈላቸው ህሙማን ከነሐሴ 22 ጀምሮ በስልክ ቁጥሮች 0111574343 ወይም በሞባይል ቁጥር 0940040404 ደውለው በመመዝገብ፣ ወረፋ መያዝና የነፃ ምርመራው ተጠቃሚ መሆን እንደሚችሉ ዳይሬክተሩ ገልፀዋል፡፡
ማዕከሉ ከተቋቋመ ጊዜ ጀምሮ በየአመቱ በጳጉሜ ተመሳሳይ የነፃ ምርመራ አገልግሎቶችን እየሰጠ ሲሆን ባለፈው ዓመት ለ500 ሰዎች ነፃ የሲቲስካንና ኤምአር አይ ምርመራ አገልግሎት ለመስጠት አቅዶ፣ ለ820 ሰዎች ነፃ አገልግሎቱን እንደሰጠ ዳይሬክተሩ ተናግረዋል፡፡ የሲቲስካንና የኤምአርአይ ምርመራ አገልግሎት ለማግኘት ከአንድ ሺህ ብር እስከ ሶስት ሺህ ብር ክፍያን እንደሚጠይቅ ይታወቃል፡፡