Administrator

Administrator

- በኢትዮጵያ የስነ-ጽሁፍ ታሪክ ረጅሙ ልብወለድ ነው

   በአንጋፋው ደራሲ አዳም ረታ የተጻፈውና ዘጠነኛ ስራው የሆነው “የስንብት ቀለማት” የተሰኘ የረጅም ልቦለድ መጽሃፍ በቅርቡ ለንባብ እንደሚበቃ ደራሲው ለአዲስ አድማስ  መግለጫ አስታወቀ፡፡
ደራሲ አዳም ረታ ከሁለት አስርት አመታት በላይ ሲያስተዋውቀው የነበረውን ‘ሕጽናዊነት’ የተባለ ልዩ የአጻጸፍ ስልት በስፋትና በጥልቀት ያሳየበት “የስንብት ቀለማት”፣ በቅርጹም ሆነ በይዘቱ የተለየ እንደሚሆን የተነገረ ሲሆን ደራሲው ከዚህ ቀደም ባሳተማቸው መጽሃፍት ውስጥ የሚጠቀማቸው ምስሎች፣ ቻርቶች፣ ግራፊክ ዲዛይኖችና ሰንጠረዦች በአዲሱ መጽሀፍም መካተታቸውንና ባለ ሙሉቀለም የግርጌ ስታወሻዎችና ሌሎች አዳዲስ ይዘቶች እንዳሉት ታውቋል፡፡
በመጨረሻ ገፆቹ የአንጋፋውን የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የስነጽሁፍ መምህር ረዳት ፕሮፌሰር ቴዎድሮስ ገብሬ ዳሰሳ “ድሕረ ቃል” በሚል ርዕስ ያካተተው መፅሀፉ ፤ በ960 ገጾች በኢትዮጵያ የሥነ ፅሁፍ ታሪክ ረዥሙ ልብወለድ ለመሆን በቅቷል፡፡  8 አቢይ ምዕራፎችና 46 ንኡስ ምዕራፎች ያሉት ልብ ወለዱ፤ ዋጋው 350 ብር እንደሆነ ታውቋል፡፡

      የ2016 ዳይመንድ ሊግ ከትናንት በስቲያ በ8ኛዋ ከተማ ስዊድን ስቶክሆልም ተካሂዷል። 11 የኦሎምፒክ የወርቅ ሜዳልያ ባለቤቶች፤ 59 የዓለም ሻምፒዮኖች እንዲሁም 7 የዓመቱን ፈጣን ሰዓት እና ምርጥ ውጤት ያስመዘገቡ አትሌቶች ተሳትፈውበታል፡፡ በዳይመንድ  ሊጉ በሁለቱም ፆታዎች ከ4 በላይ የውድድር መደቦችን  ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ይካፈላሉ፡፡ በ800 ሜትር፤ በ1500 ሜትር ፣ በ3000 ሜትር መሰናክል ሴቶች እና በ3000 ሜትር ወንዶች እንዲሁም በ5000 ሜትር  ጠንካራ ተፎካካሪም ናቸው፡፡  
ባለፈው ሐሙስ ስቶክሆልም ላይ  በ800 ሜትር ወንዶች ቤጂንግ አስተናግዳ በነበረው 15ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ከ1 እስከ 5 የወጡ አትሌቶች ተሳትፈዋል፡፡ በተለይ የኦሎምፒክ ሻምፒዮኑ ዴቪድ ሩድሻ እና የዓለም ሻምፒዮኑ መሐመድ አማን ከ3 ዓመት በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ መገናኘታቸው ትኩረት የሳበ ነበር፡፡
በ5ሺ ሜትር ወንዶች በ3ሺ ሜትር የዓለም ሻምፒዮን የሆነው የሆነው ዮሚፍ ቀጀልቻ፤ በ2011 በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ10ሺ የወርቅ ሜዳልያ የወሰደው ኢብራሂም ጄይላንና በውድድር ዘመኑ በ5ሺ ፈጣን ሰዓት ያስመዘገበው ሙክታር ኢድሪስ ፈታኝ ውድድር አድርገዋል፡፡  ኢማና መርጋ እና የኔው አላምረውም ከተፎካካሪዎቹ መካከል ይገኙበታል፡፡ በሴቶች ደግሞ በ3ሺ ሜትር መሰናክል ሶፍያ አሰፋ፤ በ1500 ዳዊት ስዩም፤ ጉድፍ ፀጋይ እና በሱ ሳዶ ተሳትፈዋል፡፡
የ2016  ዳይመንድ ሊግ በውድድር ዘመኑ አጋማሽ ላይ ይገኛል፡፡ በስዊድን ስቶክሆልም ጨምሮ በስምንት ከተሞች  ተካሂዷል፡፡  በኳታሯ ከተማ ዶሃ የተጀመረ ሲሆን ከዚያም በቻይና ሻንጋይ፤ በሞሮኮ ራባት፤ በጣሊያን ሮም፤ በእንግሊዝ በርሚንግሃም እና በኖርዌይ ኦስሎ ከተሞችም ተከናውኗል፡፡ ከ2016 የሪዮ ኦሎምፒክ በፊት 10 የዳይመንድ ሊግ ውድድሮች በ10 ከተሞች ይደረጋል፡፡ ከሪዮ ኦሎምፒክ በፊት ቀጣዮቹ የዳይመንድ ሊግ አዘጋጅ ከተሞች የፈረንሳይ ከተማ ሞናኮ እና የእንግሊዟ ከተማ ለንደን  ናቸው፡፡ ከሪዮ ኦሎምፒክ በኋላ በስዊዘርላንድ ሎዛን፤ በፈረንሳይ ፓሪስ መደበኛዎቹ የዳይመንድ ሊግ ውድድሮች የሚካሄዱ ሲሆን በስዊዘርላንድ ዙሪክ እና በቤልጄይም ብራስልስ ከተሞች ሁለቱ የዳይመንድ ሊግ የፍፃሜ ውድድሮች ያስተናግዳሉ፡፡
የ2016 ዳይመንድ ሊግ  በሪዮ ኦሎምፒክ ዓመት መካሄዱ ለየት ያደርገዋል፡፡ በኦሎምፒክ በመካከለኛና በረጅም ርቀት የአትሌቲከስ ውድድሮችና የሜዳ ላይ ስፖርቶች የሚያሰልፏቸውን ምርጥ ኦሎምፒያኖች ለመለየት የሚያግዝ  ነው፡፡ ዘንድሮ በተለይ በ5ሺ ሜትር በሁለቱም ፆታዎች የኢትዮጵያ አትሌቶች በዳይመንድ ሊጉ ከፍተኛ ውጤት እያስመዘገቡ ናቸው፡፡ ይህ ሁኔታም በሪዮ ኦሎምፒክ ለሚኖር የሜዳልያዎች ስኬት ከፍተኛ ተስፋ ሊፈጥር ይችላል፡፡
በዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር አይኤኤኤፍ የሚዘጋጀው ዳይመንድ ሊግ  ዘንድሮ በ7ኛ የውድድር ዘመኑ ላይ ይገኛል። አስቀድሞ ይካሄድ የነበረውን ጎልደን ሊግን በተሻለ ደረጃ የተካ ዓመታዊ የአትሌቲክስ መድረክ ሆኖ በስኬት የቀጠለው ዳይመንድ ሊግ በየዓመቱ በ32 የውድድር መደቦች (16 የወንድ 16 የሴት) የሚካሄደ ሲሆን በርካታ ምርጥ አትሌቶች የሚሳተፉበትና ከፍተኛ ፉክክር የሚታይበትም ሆኗል፡፡ በ4 አህጉራት ፤  በ11 የተለያዩ አገራትና 15 ከተሞች የሚካሄደው የዳይመንድ ሊግ ውድድር በሁለቱም ፆታዎች የብሔራዊ፣ የዓለምና፣ የኦሎምፒክ ሻምፒዮን የሆኑ ብዛት ያላቸው አትሌቶችን ማሳተፉ ልዩ ያደርገዋል፡፡ በከፍተኛ የውድድር ደረጃው ሪከርዶች እና የውድድር ዘመኑ ፈጣን ሰዓቶች የሚመዘገቡበት መድረክም ነው፡፡በሻምፒዮንሺፕ ደረጃ ባይሆንም በርካታ ምርጥ አትሌቶችን በከፍተኛ የፉክክር ደረጃ የሚያሳትፍ የአትሌቲክስ ታላቅ መድረክ እየሆነ መጥቷል፡፡
ኢትዮጵያውያን
በ7ኛው ዳይመንድ ሊግ ላይ
ዳይመንድ ሊጉ በ8ኛዋ ከተማ ስቶክሆልም ከቀጠለ በኋላ በ5 ሺህ ሜትር ወንዶች ኢትዮጵያውያን አትሌቶች  በሁለት ተከታታይ ውድድሮች ተከታትለው በመግባት ፍፁም የበላይነት በማሳየት ላይ ናቸው፡፡  ከሳምንታት በፊት አትሌት ሐጎስ ገብረህይወት፣ ሙክታር እድሪስ እና ዮሚፍ ቀጀልቻ ከአንድ እስከ ሶስተኛ ደረጃ በማግኘት ተከታትለው ገብተዋል፡፡ ከትናንት በስቲያ ደግሞ በስዊድን ስቶክሆልም ኢብራሂም ጄይላን፤ ዮሚፍ ቀጀልቻ እንዲሁም ሙክታር ኢድርስ ሆነው ከ1 እስከ 3 ደረጃ አግኝተዋል። በ5ሺ ሜትር ወንዶች ሙክታር ኢድሪስ በ4 ውድድሮች 30 ነጥብ አስመዝግቦ 1ኛ ሲሆን፤ ሃጎስ ገብረህይወት በ2 ውድድሮች 12 ነጥብ አስመዝግቦ 2ኛ፤ ዮሚፍ ቀጀልቻ በ3 ውድድሮች 11 ነጥብ አስመዝግቦ 3ኛ ደረጃ ላይ ነው፡፡ ኢብራሂም ጄይላን በስዊድን ስቶክሆልም ካሸነፈ በኋላ በ10  ነጥብ 4ኛደረጃ ሲይዝ ይገረም ደመላሽና አባዲ አምባዬ በእኩል 3 ነጥብ ዘጠነኛ፤ እንዲሁም ደጀን ገብረመስቀል በ1 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ናቸው፡፡
በአምስት ሺህ ሜትር ሴቶች ደግሞ በሞሮኮ ራባት እና በጣሊያን ሮም ያሸነፈችው አልማዝ አያና ለዓለም ሪከርድ እጅግ የቀረበ የዓመቱን ፈጣን ሰዓት በማስመዝገብ የበላይነቷን እያሳየች ነው፡፡ አምና በ6ኛው ዳይመንድ ሊግ በ5ሺ ሜትር ያሸነፈችው ገንዘቤ ዲባባ ስትሆን ዘንድሮ ግን አልማዝ አያናን የሚቀናቀን ያለ አይመስልም። በ3 ውድድሮች በማሸነፍ በ30 ነጥብ አንደኛ ደረጃ ላይ ናት፡፡ የኬንያዎቹ ሜርሲ ቼሮኖ በ18 እንዲሁም ቪቪያን ቼሮይት በ13 ነጥብ ይከተላሉ፡፡ ሌሎቹ አትሌቶች ሰንበሬ ተፈሪ በ7 ነጥብ 6ኛ፤ ገለቴ ቡርቃ በ4 ነጥብ 7ኛ፤ ሃፍታምነሽ ተስፋዬ በ3 ነጥብ 9ኛ፤ እቴነሽ ዲሮ እና አባቤል የሱፍ በእኩል 2 ነጥብ 9ኛ እንዲሁም አለሚቱ ሃሮዬ በ1 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ናቸው፡፡
በ3ሺ ሜትር መሰናክል ሶፊያ አሰፋ በ3 ውድድሮች 12 ነጥብ አስመዝግባ በ3ኛ ደረጃ ላይ ናት፡፡ በሴቶች 3ሺ መሰናክል ላይ ሶፊያ አሰፋ በዳይመንድ ሊግ በ35 ውድድሮች በመሳተፍ በዳይመንድ ሊጉ የተሳትፎ ልምድ አራተኛ ደረጃ ያላት ሲሆን፤ በ22 ደውድድሮች ከ1 እስከ 3 ባሉ ደረጃ በመጨረስ ውጤቷ በ10ኛ ደረጃ የተመዘገበ ነው፡፡ እቴነሽ ዲሮ በበኩሏ በ1 ውድድር 4 ነጥብ አስመዝግባ 4ኛ ደረጃ ላይ ናት፡፡ በ800 ሜትር ወንዶች መሃመድ አማን በ4 ነጥብ 9ኛ ደረጃ ላይ ሲሆን  በ1500 ሜትር ወንዶች አማን ወቴ በ3 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ነው፡፡በ800 ሜትር ሴቶች ሃብታም አለሙ በ3 ውድድሮች 8 ነጥብ አስመዝግባ 5ኛ ደረጃ ላይ ስትገኝ፤ በ1500 ሴቶች ዳዊት ስዩምና ጉድፍ ፀጋይ በ2 ውድድሮች 10 ነጥብ በማስመዝገብ 3ኛ ደረጃ ላይ ሲሆኑ በ6 ነጥብ በሱ ሳዶ 8ኛ ነች፡፡
ስለ ዳይመንድ ሊጉ
ባለፉት ስድስት የዳይመንድ ሊግ የውድድር ዘመናር ኤስያ፤ አውሮፓ፤ መካከለኛው ምስራቅ እና አሜሪካን ያካለለው ውድድሩ ዘንድሮ ደግሞ  በአፍሪካ መካሄድ ጀምሯል፡፡ በአሜሪካዋ ኒውዮርክ የሚዘጋጀውን ግራንድ ፕሪ በመተካት በአፍሪካ የዳይመንድ ሊግ አዘጋጅ ሆና የተመረጠችው የሞሮኮዋ ከተማ ራባት ስትሆን ውድድሩን በመሀመድ አምስተኛ ስታድዬም በተሳካ ሁኔታ ለማስተናገድ በቅታለች፡፡ በሌላ በኩል ተግባራዊ የሆነ የዳይመንድ ሊግ አዲስ አሰራር የነጥብ አሰጣጡ ነው፡፡ ባለፉት 6 የውድድር ዘመናት ከ1 እሰከ 3 ለሚወጡ አትሌቶች ብቻ  ነጥብ ይሰጥ በር፡፡ ዘነድሮ ከ1 እሰከ 6ኛ ደረጃ ለሚያገኙ አትሌቶች ነጥቦች ይሰጣሉ፡፡  በዳይመንድ ሊግ የውድድር ዘመን አሸናፊ የሚሆኑ አትሌቶች ከሚያገኙት የገንዘብ ሽልማት እና የዳይመንድ ዋንጫ በተጨማሪ በቀጣይ የውድድር ዘመን በቀጥታ ተሳታፊ በመሆናቸው ከፍተኛውን ነጥብ ለማስመዝገብ ፉክክሩ ከባድ ነው፡፡ በዳይመንድ ሊግ በየውድድር አይነቱ በሚሰጥ ነጥብ መሰረት ዳይመንድ ሬስ ተብሎ ደረጃ ይሰጣል፡፡  በውድድር ዘመኑ መጨረሻ ከፍተኛውን ነጥብ ያስመዘገቡ አትሌቶች በአልማዝ ማእድን የተሰራ ልዩ ዋንጫ እና 40ሺ ዶላር ተሸላሚ ይሆናሉ፡፡ የዳይመንድ ሊግ ዋንጫው ተቀማጭነቱ በዙሪክ የሆነው፤ ከ18ኛው መቶ ክፍለዘመን ጀምሮ በመስራት ከፍተኛ ተወዳጅነት ያለው ቤዬር የተባለ ተቋም ይሰራዋል። በዳይመንድ ሬስ ፉክክር ለመግባት አትሌቶች ውድድሮቹ ከሚደረጉባቸው 14 ከተሞች በ7ቱ የግድ መሳተፍ ይኖርባቸዋል፡፡
በዳይመንድ ሊጉ አዲስ የነጥብ አሰጣጥ መሰረት በአንደኝነት የሚያሸንፍ አትሌት በመደበኛ ውድድሮች 10 ነጥብ በፍፃሜ 30 ነጥብ፤ 2ኛ ደረጃ የሚያገኝ በመደበኛ 6 ነጥብ በፍፃሜ 12 ነጥብ ፤ 3ኛ ደረጃ የሚያገኝ አትሌት በመደበኛ 4 ነጥብ በፍፃሜ 8 ነጥብ፤ 4ኛ ደረጃ የሚያገኝ አትሌት በመደበኛ 3 ነጥብ በፍፃሜ 6 ነጥብ፤ 5ኛ ደረጃ የሚያገኝ አትሌት በመደበኛ 2 ነጥብ በፍፃሜ 4 ነጥብ እንዲሁም 6ኛ ደረጃ የሚያገኝ በመደበኛ 1 ነጥብ በፍፃሜ 2 ነጥብ ይሰጣቸዋል፡፡ በዳይመንድ ሊጉ ማጠቃለያ አትሌቶች በየውድድር መደቡ በእኩል ነጥብ የሚጨርሱ ከሆነ ባሸነፉት የውድድር ብዛት፤ ይህም አቻ የሚያደርጋቸው ከሆነ በተሻለ ሰዓት እና ውጤት መሰረት አሸናፊዎቹ የሚለዩ ይሆናል፡፡
በዳይመንድ ሊጉ በእያንዳንዱ ከተማ በሚደረግ ውድድር  እሰከ 8ኛ ደረጃ ላገኙ አትሌቶች የሚበረከተው የሽልማት ገንዘብ ዝርዝር እንደሚከተለው ሲሆን ለ1ኛ 10ሺ ዶላር፤ ለ2ኛ 6ሺ ዶላር፤ ለ3ኛ 4ሺ ዶላር፤ ለ4ኛ 3ሺ ዶላር፤ ለአምስተኛ 2500 ዶላር፤ ለስድስተኛ 2ሺ ዶላር፤ ለ7ኛ 1500 ዶላር እንዲሁም ለ8ኛ 1000 ዶላር ይሆናል፡፡
የምንግዜም ውጤት ደረጃ
ባለፉት 6 የዳይመንድ ሊግ የውድድር ዘመናት 48 የዳይመንድ ሊግ አሸናፊዎች ያስመዘገበችው አሜሪካ አንደኛ ደረጃ ሲኖራት፤ ኬንያ በ30 ሁለተኛ ደረጃ ላይ ናት፡፡ ጃማይካ በ14 የዳይመንድ ሊግ ድሎች ሶስተኛ ደረጃ ስትይዝ፤ ኢትዮጵያ በ2012 እኤአ ላይ አበባ አረጋዊ በ1500 ሜትር ዜግነቷን ሳትቀይር ያስመዘገበችውን ድል ጨምሮ በ10 የዳይመንድ ሊግ ድሎች አራተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች፡፡ የኢትዮጵያ 10 የዳይመንድ ሊግ ድሎች በአምስት አትሌቶች የተመዘገቡ ናቸው፡፡ በ800 ሜትር መሃመድ አማን በ2012 እና በ2013 እኤአ አሸንፏል። በ5ሺ ሜትር ወንዶች ካላፉት አምስት የዳይመንድ ሊግ የውድድር ዘመኖች አራቱን ሁለት ኢትዮጵያውያን አትሌቶች አሸንፈዋል፡፡ በ2010 እና 2011 እኤአ ኢማና መርጋ እንዲሁም በ2013 እኤአ የኔው አላምረው ናቸው፡፡ አበባ አረጋዊ ዜግነቷን ሳትለውጥ በፊት በ1500 ሜትር በ2012 እኤአ ላይ አሸናፊ ነበረች፡፡ በሴቶች 5ሺ ሜትር መሰረት ደፋር በ2013 እኤአ ያሸነፈች ሲሆን በ3ሺ ሜትር መሰናክል ደግሞ 2014 እኤአ ላይ ህይወት አያሌው ድል አድርጋለች፡፡ በ2015 ደግሞ ዳይመንድ ሊጉን በ5ሺ ሜትር ለማሸነፍ የበቃችው ገንዘቤ ዲባባ ነበረች፡፡
ባለፉት ስድስት የዳይመንድ ሊግ የውድድር ዘመናት ኢትዮጵያውያን ያስመዘገቧቸው የዳይመንድ ሊግ ክብረወሰኖችን የሚከተሉት ናቸው፡፡
በ3ሺ ሜትር የኔው አላምረው በኳታር ዶሃ በ2011 እኤአ ላይ በ7፡27.26
በ5ሺ ሜትር ደጀን ገብረመስቀል በፈረንሳይ ፓሪስ በ2012 እኤአ 12፡46.81
በሴቶች 1500 ሜትር ገንዘቤ ዲባባ በፈረንሳይ ሞናኮ በ2015 እኤአ ላይ 3፡50.07
በሴቶች 5ሺ ሜትር አልማዝ አያና በሮም ጣሊያን 14፡12.59

ሦስት አህዮች በጠፍ ጨረቃ ሣር ሊግጡ ወደ ሜዳ ተሰማርተዋል፡፡ ጅቦች ደግሞ ርቧቸው ሲዞሩ አምሽተው፣ በመጨረሻ አህዮቹ ሣር ወደሚግጡበት አካባቢ ይመጣሉ፡፡
“በዚህ ሌሊት፣ በእኛ ሰዓት፣ በእኛ ግዛት እንዲህ ፍንድቅድቅ ያሉት ማንን ተማምነው ነው? ከመብላታችን በፊት እንጠይቃቸው” አሉና ጅቦቹ አህዮቹን ተራ በተራ ለፍርድ እንዲቀርቡ አደረጉ፡፡
የጅብ መሀል ዳኛ የመጀመሪያዋን አህያ አስቀርቦ፤
“ወ/ሮ አህያ፣ በጠፍ ጨረቃ፣ በእኛ ግዛት መጥተሽ ሣር የምትግጪው ማንን ተማምነሽ ነው?” ሲል ጠየቃት፡፡
ወ/ሮ አህያም፤
“አምላኬን ተማምኜ ነው፡፡ ማንም ጥቃት ቢያደርስብኝ አምላክ ይበቀልልኛል ብዬ ነው” ስትል መለሰች፡፡
ሁለተኛዋን አህያ አስጠሩና ዳኛው ጅብ፤
“አንቺስ በጠፍ ጨረቃ በእኛ ግዛት ሣር የምትግጪው ማንን ተማምነሽ ነው” ሲሉ ጠየቋት።
ሁለተኛዋ ተከሳሽ አህያም፤
“እኔ ጌታዬን ተማምኜ ነው የወጣሁት፡፡ ማንም ጥቃት ቢያደርስብኝ፤ ጌታዬ ተከታትሎ ይበቀልልኛል” አለች፡፡
ሦስተኛዋ ተከሳሽ አህያ ቀረበች፡፡
“ማንን ተማምነሽ ነው በእኛ ሰዓት፣ በእኛ ግዛት ሣር የምትግጪው?” ሲሉ ጠየቋት፡፡
አህይትም፤ “እናንተን ተማምኜ፣ እናንተን አምኜ ነው ከቤቴ የወጣሁት” ስትል መለሰች፡፡
ሶስቱ ጅቦች ዳኞች,ኧ ሶስቱን ተከሳሽ አህዮች ወደ ጥግ እንዲቆሙ አድርገው ይመካከሩ ጀመር፡፡
“የመጀመሪያዋን አህያ ብንበላት፤ እንዳለችው አምላክ ሊበቀለን ይችላል፡፡ ለእኛ ለይቶ ባይልከውም ነጐድጓድ ሊያወርድብን፣ መብረቅ ሊልክብን፣ ድርቅ ሊያመጣብን ይችላል”
“ሁለተኛዋን ብንበላትስ?” አለ ግራ ዳኛው ጅብ፡፡
“የእሷም ጌታዋ ሊበቀለን ይችላል፡፡ አሁንም ፍለጋ መምጣቱ አይቀርም፡፡ ስለዚህ እሷንም ብንተዋት ይሻላል፡፡ ይልቅ እቺን እኛን የተማመነችውን ብንበላት ማናባቱ ይጠይቀናል?” አሉና ሁለቱን አሰናብተው ሶስተኛዋ ላይ ወረዱባት፡፡
*   *   *
በርትቶ ራስን ማዳን ነው እንጂ “እናንተን ተማምኜ” ማለት አብዛኛውን ጊዜ አያዋጣ። ምንጊዜም በራስ መተማመንን የመሰለ ነገር የለም፡፡ በራስ ለመተማመን የራስን ብቃት ማረጋገጥ ያስፈልጋል፡፡ የራስን ብቃት ለማረጋገጥ ራስን በመሠረታዊ ዕውቀት መገንባት፣ ሁሌ መትጋት፣ ሁሌ መማር ያሻል፡፡ ትምህርት ከመሠረቱ ካልተስተካከለ የተጣመመ ግንድ ለማቃናት እንደመሞከር ይሆናል፡፡ ዛሬ ትምህርት በእጅጉ ቁልቁል እየወረደ ነው፡፡ ገጣሚ ፀጋዬ ገ/መድህን፤ “ቁልቁል ማደግ” እንደሚለው ነው፡፡
“በጠቅል ጊዜ ያልተማረ
ማዘኑ አይቀርም እያደረ
ዐይናችን ታሞ ታውረን
ኃይለሥላሴ አዳኑን”
ለማለት እንኳ አቅም የለም፡፡ ለመማር አቅም የሌላት አገር የበለፀገ ትውልድ ለማፍራት አትችልም፡፡ የተልፈሰፈሰና የተቆለመመ ህብረተሰብ ነው የምትፈጥረው፡፡ እንዲያ ያለ ህብረተሰብ ደግሞ ነገው የተጭለመለመ ነው የሚሆነው፡፡ ስለዚህ “መማር፣ መማር፣ መማር” የሚለው የዱሮ መፈክር፤ የሸረሪት ድርም አድርቶበት ከሆነ ተጠራርጐ ጐላ ብሎ ቢታይ በጐ ነው፡፡
ቻይናዎች፤
“ዕቅድህ ለዓመት ከሆነ ሩዝ ዝራ፡፡
ዕቅድህ ለአምስት ዓመት ከሆነ ባህር ዛፍ ትከል፡፡
ዕቅድህ ለዘለዓለም ከሆነ ልጅህን አስተምር” ይላሉ፡፡
(“If your plan is for a year, plant rice;
If your plan is for five years, plant a eucalyptus tree;
If your plan is for ever educate your child.)  
ይህንን አስተምህሮ ሶስት ወገኖች በቅጡ ሊጨብጡት ይገባል፡- አንደኛ ወላጆች፡፡ ሁለተኛ መምህራን፡፡ ሶስተኛ መንግሥት፡፡ ይህ የሶስትዮሽ ትሥሥር (Network) ብቻ ነው የኋሊት እየተንደረደርን ካለንበት አዝቅት ታኮ ሆኖ ሊያቆመን የሚችለው፡፡ ኩረጃን እንደ ባህል እንዳንይዝ በግሮ የሚከላከልልን ይኼው የሶስትዮሽ አጥር ነው፡፡ ታሪካዊ ምፀቱ ቢያስገርምም እዚህ ተጠቃሽ ቢሆን አግባብ ነው የምንለው ነገር አለ፡፡ የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር “ከሌሎች አገሮች የዕድገት አካሄድ ቢያንስ በአግባቡ መኮረጅ እንቻል”፡፡ ያን ያሉት ለትምህርት ቤት ፈተና ኩረጃ አልነበረም! ያ የበለጠ ለመሥራት፣ የበለጠ ለመትጋት፣ የበለጠ ለመነሳሳት ነበረ። አሁን የሚታየው ግን ሥንፈተ - ትምህርት ነው! ይህ አደጋ ነው፡፡ ትልቅ ሥጋት፣ ትልቅ ጥንቃቄ፣ ትልቅ ቆራጥነት ይጠይቃል፡፡ በገጣሚ መንግሥቱ አገላለጽ፣ “መርፌ ትሠራለህ?” ከሚል ማህበረሰብ ተነስተን “መኮረጅ ትችላለህ?” ወደሚል ትውልድ ማቆልቆላችን አሳዛኝ ነው፡፡ ከቶማስ ኤዲሰን 128 የውድቀት ልምድ ባንማር፣ እንደቅዱስ ያሬድ ስምንቴ ከወደቀችው ትል መማር አቅቶናል፡፡
ጥንካሬያችን በሰው ኃይል ጥራት የተገነባ ይሆን ዘንድ የትምህርትን መሠረታዊ ጉዘት እናጢን፡፡ የመምህራኖቻችንን ሙያዊ ብቃትና ስብዕና እንፈትሽ፡፡ የመንግስትን፤ የትምህርት ላይ ትኩረት፤ ከልብ እንመርምር! “ከእሾህ አጥር የሰው አጥር ይጠነክራል” የሚለው ተረት በቅጡ የሚባን ያኔ ነው!!



አብደላ እዝራ ከአባቱ ከአቶ መሐመድ ሳልህ አልአረግስኢ እና ከእናቱ ወ/ሮ መሪሃም በ1950 ዓ.ም በአዲስ አበባ፣መርካቶ አንዋር መስጊድ አካባቢ ተወለደ፡፡ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቱን ከ1ኛ-6ኛ ክፍል በአፍሪካ አንድነት ትምህርት ቤት የተከታተለ ሲሆን 7ኛ እና 8ኛን በልዑል ወሰን ሰገድ ትምህርት ቤት፣የ2ኛ ደረጃ ትምህርቱን ደግሞ በተፈሪ መኮንን ተምሯል፡፡ ወደ የመን፣ ሰንዓ በመጓዝም  የመጀመሪያ ዲግሪ ትምህርቱን አጠናቋል፡፡ እዚያው የመን ውስጥ በየመኒ ኤርዌይስ ተቀጥሮም ጡረታ እስከወጣበት ጊዜ ድረስ ሠርቷል፡፡
አብደላ አብላጫውን የሕይወት ዘመኑን በሥነጽሑፍ ሥራዎች ላይ ጥናትና ምርምር በማድረግ ያሳለፈ ሲሆን ወደ ኢትዮጵያ ከመጣ በኋላም የበርካታ ገጣምያንና ደራስያን ሥራዎችን በሂሳዊ ብዕሩ ጎብኝቷል፡፡ ሃያሲው ቀደም ባሉት ዓመታት በ“አዲስ ዘመን” እና “የዛሬይቱ ኢትዮጵያ” ጋዜጦች እንዲሁም የኢትዮጵያ ደራስያን ማኅበር (ኢደማ) በሚያዘጋጀው “ብሌን” መጽሔት ላይ ከዚህ ዓለም በሞት እስከተለየበት ጊዜ ድረስ ደግሞ በ“አዲስ አድማስ” ጋዜጣ ላይ ጥልቅ የሥነጽሁፍ ትንታኔዎቹን አቅርቧል፡፡ አንጋፋው ሃያሲ ሥራዎቻቸውን በጥበባዊ ሂስ ከተነተነላቸው ዕውቅና ድንቅ ደራሲያን መካከል በዓሉ ግርማ፣ ደበበ ሰይፉ፣ ሲሳይ ንጉሡ፣ አዳም ረታ፣ ስብሐት ገብረእግዚአብሔር፣ ነቢይ መኰንን፣ ዓለማየሁ ገላጋይ፣ አበራ ለማ፣ ኤፍሬም ሥዩም፣ ደምሰው መርሻና በድሉ ዋቅጅራ ይጠቀሳሉ፡፡  
 አብደላ እዝራ ድንገት ባደረበት ሕመም፣ለአጭር ጊዜ ሕክምና ሲከታተል ቆይቶ፣ባለፈው ቅዳሜ ግንቦት 27 ቀን 2008 ዓ.ም ከቀኑ10፡30፣ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል፡፡ በነጋታው እሁድ ሥርዓተ ቀብሩ ጥቂት ሰዎች በተገኙበት በቅዱስ ዮሴፍ ቤተክርስቲያን ተፈጽሟል፡፡  

    ለዘንድሮው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ የመጨረሻው ምዕራፍ ላይ የደረሱትና ወደ ዋይት ሃውስ የሚያቀናውን የፍጻሜ ጉዞ የጀመሩት ሁለቱ ዕጩ ተፋላሚዎች ታውቀዋል - ሄላሪ ክሊንተንና አወዛጋቢው ዶናልድ ትራምፕ፡፡
ዶናልድ ትራምፕ ሪፐብሊካኑን ወክለው እንደሚወዳደሩ ካረጋገጡ ሰንበትበት ቢሉም፣ ዲሞክራቷ ሄላሪ ግን ገና ባለፈው ማክሰኞ ነበር ፓርቲያቸውን ወክለው የሚወዳደሩ የመጀመሪያዋ ሴት ዕጩ መሆናቸውን ያረጋገጡት፡፡
ይሄን ተከትሎ የአሜሪካ ዝነኞች ከሁለቱ ዕጩዎች ለማን ድምጻቸውን እንደሚሰጡ አበክረው ማስታወቅ ጀምረዋል፡፡
የእንግሊዙ “ሚረር” ጋዜጣ የአሜሪካ ዝነኞች በየማህበራዊ ድረገጹና በየአጋጣሚው ማንን እንደሚደግፉ ያስተላለፉትን መልዕክት አሰባስቦ፣ ከትናንት በስቲያ ለንባብ አብቅቶ ነበር፡፡
ታዋቂዋ ድምጻዊት ሌዲ ጋጋ ባለፈው ማክሰኞ በማህበራዊ ድረገጽ በኩል ባስተላለፈቺው መልዕክት፤ በመጪው ምርጫ ለሄላሪ ክሊንተን ድምጽ እንደምትሰጥ የገለጸች ሲሆን፣ 17 ሚሊዮን ለሚደርሱ የማህበራዊ ድረገጽ ተከታዮቿም፣ ለውጥ ከፈለጋችሁ ሄላሪን ምረጡ ስትል ጥሪ አቅርባለች፡፡ ዝነኛው የሆሊውድ አክተር ጆርጅ ክሉኒም፣ ሰሞኑን በድረገጹ ላይ ባተመው ይፋ ደብዳቤ ለሄላሪ ክሊንተን ያለውን ድጋፍ ገልጾ፣ “ይሄ ትራምፕ የሚባል ሰው አገራችንን መቀመቅ ሊከት ያኮበኮበ ሰው ነውና ድምጻችሁን በመንፈግ ክንፉን ስበሩት” ሲል ለአድናቂዎቹ መልዕክቱን አስተላልፏል፡፡ ጆርጅ ክሉኒ ባለፈው ሚያዝያ ወር ላይም፣ ከባለቤቱ ጋር በመተባበር ለሄላሪ ክሊንተን የምርጫ ቅስቀሳ ገንዘብ ሲያሰባስብ መክረሙ ተገልጿል፡፡
ሄላሪን እንደሚደግፉ በይፋ ካስታወቁ ዝነኞች ሌላኛዋ፣ ታዋቂዋ ክርስቲና አጉሌራ ናት፡፡ ይህቺው ዝነኛ አርቲስት በትዊተር ገጽ ላይ ባስተላለፈቺው መልዕክት፣ ሄላሪን በመደገፏ ታላቅ ክብር እንደሚሰማት ገልጻለች፡፡ “ሄላሪ ክሊንተን ታሪክ የሰራቸው ለራሷ ብቻ አይደለም፤ በመላ አለም ለሚገኙ ሴቶች እንጂ!...” ስትልም፣ ለዲሞክራቷ ዕጩ ለሄላሪ ያላትን ክብር ገልጻለች፡፡ ለሄላሪ የገቢ ማሰባሰቢያ ታስቦ ባለፈው ሰኞ ምሽት፣ በካሊፎርኒያ በተዘጋጀው የሙዚቃ ኮንሰርት ላይም፣ ሪኪ ማርቲን፣ ክርስቲና አጉሌራ፣ ጆን ሌጀንድና ስቲቪ ዎንደርን የመሳሰሉ ድንቅ ድምጻውያን ስራዎቻቸውን በማቅረብ ለሴትዮዋ ያላቸውን ድጋፍ አሳይተዋል፡፡ ሄላሪ በዝነኞች ስትከበብ፣ አነጋጋሪው ትራምፕ ግን፣ እምብዛም የዝነኞችን ቀልብ አልሳቡም፡፡
ከትራምፕ ጎን ቀድሞ የቆመው ታይሰን ነው፡፡ የዓለም የከባድ ሚዛን ሻምፒዮኑ ማይክ ታይሰን፣ ለአገሬ የሚበጃት ሁነኛ መሪ ዶናልድ ትራምፕ ነው ባይ ነው፡፡
“ዶናልድ ትራምፕን እወደዋለሁ!... ዶናልድ በስደተኞች ላይ የያዘው አቋም ዘረኛ ነው ያስብለዋል ብዬ አላምንም” ያለው ታይሰን፤ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት መሆን ያለበት ትክክለኛው ሰው እሱ ነው!...” ሲል አቋሙን በግልጽ አንጸባርቋል፣ ሰሞኑን ከሃፊንግተን ፖስት ጋዜጣ ጋር ባደረገው ቃለ ምልልስ፡፡
ቫንዳምም የትራምፕ ደጋፊ ነው፡፡ ዝነኛው የሆሊውድ የፊልም ተዋናይ ዣን ክላውድ ቫንዳም፣ “ሌ ግራንድ” ለተባለው የፈረንሳይ ጋዜጣ፤ ዶናልድ ትራምፕን እንደሚደግፍ ተናግሯል፡፡
“ትራምፕ ቢመረጥ የአሜሪካን ኢኮኖሚ የሚያሻሽል ስርዓት ይፈጥራል ብዬ አምናለሁ፡፡ ምክንያቱም ጎበዝ የቢዝነስ ሰው ነው...” ያለው ቫንዳም፣ ትራምፕን እንደሚደግፍ ቢገልጽም፣ በምርጫው አያሸንፍም ብሎ እንደሚያምን አልሸሸገም፡፡ ዝነኛው የካንትሪ ሙዚቃ አቀንቃኝ ኬኒ ሮጀርስም ለትራምፕ ያለውን አድናቆት ገልጿል፡፡
“ሰውዬውን በጣም ነው የምወደው!... የሚናገራቸውን ነገሮች እወድለታለሁ፡፡ ሌሎች ሰዎች ለመናገር የማይደፍሯቸውን ነገሮች፣ እሱ ያለምንም ይሉኝታ ፍርጥርጥ አድርጎ ያወራቸዋል፡፡ እርግጥ ይህን ማድረጉ ትክክል ይሁን አይሁን አላውቅም!...” ብሏል የ77 አመቱ አቀንቃኝ ኬኒ ሮጀርስ፡፡ ታዋቂዋ የሆሊውድ ተዋናይት ክርስቲ አሊም፣ እንደ ኬኒ ሮጀርስ ሁሉ፣ ለትራምፕ ያላትን ድጋፍ ገልፃለች፡፡


አሜሪካ በርካታ ሃያላን ሴቶችን በማስመዝገብ ከአለማችን ቀዳሚ ሆናለች


በየተሰማሩበት መስክ የላቀ ተሰሚነትን ያገኙ የአለማችንን 100 ሃያላን ሴቶች ዝርዝር በየአመቱ ይፋ የሚያደርገው ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት፣ ሰሞኑን ባወጣው የ2016 ሃያላን ሴቶች ዝርዝር ውስጥ የጀርመን መራሄ መንግስት አንጌላ መርኬልን ለስድስተኛ ጊዜ በቀዳሚነት አስቀምጧል፡፡
በፎርብስ አመታዊ ዝርዝር ውስጥ ላለፉት አምስት አመታት የዓለማችን ሃያል ሴት ሆነው የዘለቁትን አንጌላ መርኬልን በመከተል እንደ አምናው ሁሉ ዘንድሮም በሁለተኛ ደረጃ ላይ የተቀመጡት፣ በዘንድሮው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ፉክክር ላይ የሚገኙት ሂላሪ ክሊንተን ናቸው፡፡
የአሜሪካ የፌደራል ሪዘርቭ ሊቀመንበር ጃኔት ያለን ሶስተኛ ደረጃን ሲይዙ፣ በጎ አድራጊዋ ሚሊንዳ ጌትስና የጄነራል ሞተርስ ዋና ስራ አስፈጻሚ ሜሪ ባራ በአራተኛና አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል። የአለማቀፉ የገንዘብ ተቋም ማኔጂንግ ዳይሬክተር ክርስቲያን ላጋርድ፣ የፌስቡኳ ሼሪል ሳንበርግ፣ የዩቲዩቧ ዋና ስራ አስፈጻሚ ሱዛን ዎጅኪኪ፣ የኤህፒ ኩባንያ ዋና ስራ አስፈጻሚ ሜግ ዊትማንና ባንኮን ሳንታንደር የተባለው ድርጅት ሊቀመንበር አና ፓትሪሺያ ቦቲን እንደ ቅደም ተከተላቸው እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል፡፡
በዘንድሮው የፎርብስ 100 የአመቱ የዓለማችን ሀያላን ሴቶች ዝርዝር ውስጥ ከተካተቱት ሴቶች መካከል 26 ያህሉ የፖለቲካ መሪዎች መሆናቸው የታወቀ ሲሆን፣ ከአፍሪካ ፖለቲከኛ ሴቶች መካከልም የላይቤሪያ ፕሬዚዳንት ኤለን ጆንሰን ሰርሊፍና የሞሪሽየስ ፕሬዚደንት አሚና ጉሪብ ፋኪም በዝርዝሩ ተካትተዋል፡፡ በዝርዝሩ ውስጥ የተካተቱት ሌላኛዋ አፍሪካዊት ሴት ናይጀሪያዊቷ ባለሃብት ፎሎሩንሽኮ ኣላኪጃ ናቸው፡፡
አሜሪካ በርካታ ሴቶችን በሃያላኑ ዝርዝር ውስጥ በማስገባት ከአለማችን አገራት ቀዳሚቱን እንደያዘች የታወቀ ሲሆን 100 የተለያዩ አገራት ፖለቲከኞችን፣ የኩባንያ ስራ አመራሮችን፣ በጎ አድራጊዎችን፣ ስራ ፈጣሪዎችንና ሳይንቲስቶችን ባካተተው በዘንድሮው የፎርብስ ሃያላን ሴቶች ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት አሜሪካውያን ሴቶች 51 መሆናቸው ተነግሯል፡፡

የኤርትራ መንግስት የተመድን ሪፖርት አጣጥሎታል

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ምርመራ ኮሚሽን፣ የኤርትራ መንግስት ባለስልጣናት በዜጎቻቸው ላይ ለሩብ ክፍለ ዘመን በፈጸሙት የማሰር፣ የማሰቃየት፣ የመግደል፣ የአስገድዶ መድፈርና የመሳሰሉ ኢ-ሰብዓዊ የወንጀል ድርጊቶች በአለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት ቀርበው ሊጠየቁ ይገባል ማለቱንና፤ የጸጥታው ምክር ቤትም በአገሪቱ ላይ ማዕቀብ እንዲጥል መጠየቁን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
የኤርትራ መንግስት በበኩሉ፤ የተመድን ሪፖርት ፖለቲካዊና መሰረት የለሽ ነው ሲል በመተቸት፣ መሰል ውንጀላዎች በኤርትራ ላይ ብቻ ሳይሆን በመላ አፍሪካ ላይ የሚቃጡ ጥቃቶች ናቸው ብሏል።
አገሪቱ ነጻነቷን ከተጎናጸፈችበት ጊዜ አንስቶ መሪዎቿ በዜጎች ላይ ኢ-ሰብአዊ ድርጊቶችን መፈጸማቸውን ባለፈው ረቡዕ የገለጸው ኮሚሽኑ፣ የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት ለፈጸሙት ወንጀል ተጠያቂ መሆን እንዳለባቸው ጠቁሞ፣ በምርመራው ያገኘውን ውጤት ለአለማቀፉ ፍርድ ቤት ማስተላለፉንም አስታውቋል፡፡ ባለፉት 25 አመታት 400 ሺህ ያህል የአገሪቱ ዜጎች በወታደራዊ ግዳጅና በመሳሰሉት የግዳጅ ተልዕኮዎች የባርነት ህይወትን ሲገፉ ቆይተዋል ያለው መርማሪ ቡድኑ፣ በአገዛዙ ተማርረው ከአገሪቱ ለመውጣት የሚሞክሩ በርካታ ዜጎችም በአገሪቱ መንግስት የድንበር ጠባቂዎች እንደሚገደሉ አስታውቋል፡፡
በየወሩ በአማካይ 5 ሺህ ኤርትራውያን በአገዛዙ ተማርረው አገራቸውን ጥለው ይሰደዳሉ ያለው ኮሚሽኑ፤ዜጎችን በኢ-ሰብዓዊ መንገድ የሚያሰቃዩት እነዚህ ከፍተኛ ባለስልጣናት አለማቀፍ ህጎችን በመጣስ በሰሩት ከፍተኛ የወንጀል ድርጊት ተገቢውን ቅጣት ማግኘት እንዳለባቸው ጠቁሞ፣ በአገሪቱ ላይ ማዕቀብ እንዲጣል ጠይቋል፡፡
የኤርትራ ፕሬዝዳንት አማካሪ አቶ የማነ ገብረአብ ረቡዕ ዕለት በሰጡት መግለጫ፣ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ምርመራ ኮሚሽን ያወጣው ሪፖርት መሰረተ ቢስና ምንም አይነት ማስረጃ የሌለው መሆኑን በመጥቀስ፣ መንግስታቸው ሪፖርቱን እንደሚያወግዘው አስታውቀዋል፡፡
ኮሚሽኑ በኤርትራ ላይ አደረግሁት የሚለው የጥናት ሪፖርት፣  የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጥናት መርሆችን ያላከበረና ሙያዊነት የጎደለው ነው ያሉት አቶ የማነ፤አገሪቱ ነጻነቷን ከተጎናጸፈችበት ጊዜ አንስቶ የተመዘገቡ መልካም ለውጦችን ለማካተት ያልደፈረና ሚዛናዊነት የጎደለው ነው ብለዋል፡፡

   ለዘንድሮ “የበጎ ሰው” ሽልማት በ10 ዘርፎች ህብረተሰቡ እጩዎች እንዲጠቁም ተጠየቀ፡፡ በመምህርነት፣ በሳይንስ፣ በድርሰት፣ በማህበራዊ ጥናት፣ መንግስታዊ የስራ ኃላፊነትን በብቃት መወጣት፣ በቅርስና ባህል፣ በስፖርት፣ በሚዲያና ጋዜጠኝነት፣ በበጎ አድራጎትና በንግድና ፈጠራ ዘርፎች ለሀገራቸው ጠቃሚ አስተዋፅኦ አበርክተዋል፤ የህዝቡን ህይወት የሚለውጥ የተሻለ ውጤት አምጥተዋል የሚላቸውን ሰዎች ህዝቡ እንዲጠቁም የሽልማቱ አዘጋጆች ጠይቀዋል፡፡
እስከ ሰኔ 24 ድረስ በስልክ ቁጥር 0915 44 55 55 ወይም በኢሜል This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it. አሊያም በአካል አዲስ አበባ ለም ሆቴል አካባቢ ማቲያስ ህንፃ ቢሮ ቁጥር 408 ድረስ በመቅረብ ጥቆማ ማቅረብ እንደሚቻል አዘጋጆቹ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡ የሽልማት ስነ ስርአቱ ነሐሴ 28 ቀን 2008 ዓ.ም በደማቅ ስነ ስርዓት ይከናወናል ተብሏል፡፡

ለ3 ሺህ 100 ዲያስፖራዎች የሸጠው ቦንድ ህገ-ወጥ ነው ተብሏል
መንግስት ጥፋቱን አምኖ ገንዘቡን ለመክፈል ተስማምቷል

የኢትዮጵያ መንግስት ለታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ገቢ ለማሰባሰብ በማቀድ በአሜሪካ ለሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ያደረገው የቦንድ ሽያጭ የአሜሪካ ህግ ከሚፈቅደው ውጪ በመሆኑና ህገወጥ መሆኑ በመረጋገጡ፣ ከሽያጩ ያሰባሰበውን 5.8 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር ጨምሮ በድምሩ 6.5 ቢሊዮን ዶላር መልሶ እንዲከፍል ተወሰነበት፡፡
የአሜሪካ የቦንድ ሽያጭና ግዢ የሚቆጣጠረው ሴኪዩሪቲስ ኤንድ ኤክስቼንጅ ኮሚሽን የተባለ ተቋም ከትናንት በስቲያ እንዳስታወቀው፣ የኢትዮጵያ መንግስት እ.ኤ.አ ከ2011 እስከ 2014 ባሉት አመታት የአሜሪካ ህግ ከሚፈቅደው ውጪ፣ በአገሪቱ ለሚኖሩ ከ3 ሺህ 100 በላይ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ባከናወነው ያልተመዘገበ የቦንድ ሽያጭ፣ የሰበሰበውን 5.8 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር እና 601 ሺህ የአሜሪካ ዶላር የወለድ ገንዘብ መልሶ እንዲከፍል ውሳኔ ተላልፎበታል፡፡
ተገቢውን ምዝገባ ሳያሟላ በአሜሪካ ዋና ዋና ከተሞች የባለሃብቶች ስብሰባዎችን በማካሄድ፣ የቦንድ ሽያጭ ማስታወቂያዎችን በኢምባሲው ድረ ገጽ፣ በሬዲዮና በቴሌቪዥን በማስተላለፍና ሽያጩን በማከናወን ህገወጥ ተግባር ፈጽሟል የተባለው የኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ሃይል አገልግሎት በበኩሉ የፈጠመውን ጥፋት በማመን፣ የተጠቀሰውን ገንዘብ እንዲመልስ የተላለፈበትን ውሳኔ ተቀብሎ ለመክፈል መስማማቱንም ኮሚሽኑ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡ ከኢትዮጵያ መንግስት ቦንድ የገዙ የዲያስፖራ ባለሃብቶች ያወጡትን ገንዘብ ከነወለዱና ከነካሳው እንደሚያገኙም ኮሚሽኑ አስታውቋል፡፡

ከ8 ዓመት በፊት በኢትዮጵያ በወይን ጠመቃ የተሰማራው ካስትል የወይን ጠጅ ፋብሪካ፣ ከነጭና ቀይ ወይን በተጨማሪ “ሮዜ” የተሰኘ አዲስ የወይን ጠጅ ለገበያ አቀረበ፡፡  
በወይን ጠመቃ አለማቀፍ እውቅና ያለው የፈረንሳውያኑ ካስትል ቤተሰቦች ወይን አምራች ኩባንያ በኢትዮጵያ ያለውን የወይን ጠጅ ገበያ ድርሻ እያሰፋ መሆኑን የገለጸ ሲሆን በዓመት ከ1.4 ሚ. ጠርሙስ በላይ ወይን ለገበያ እያቀረበ መሆኑንም አስታውቋል፡፡ አዲሱ “ሮዜ” የተሰኘው ምርቱ በኢትዮጵያ የወይን ወዳጆች በስፋት ከሚታወቁት “ነጭ” እና “ቀይ” ወይን የተለየ አዲስ የፈጠራ ምርት ነው ተብሏል፡፡ ይሄም ፈጠራ ካስትልን ብቸኛ ያደርገዋል፡፡
በተጨማሪም ኩባንያው በቀላል ዋጋ ተጠቃሚዎች ሊያገኟቸው የሚችሉ የካርቶን ወይኖችን  ለገበያ ለማቅረብ በዝግጅት ላይ መሆኑን የኩባንያው የማርኬቲንግና ሽያጭ ማናጀር ወ/ት አለም ፀሐይ በቀለ ገልፀዋል፡፡ የወይን ፋብሪካው አሁን ካለው 162 ሄክታር የወይን እርሻ በተጨማሪ 85 ሄክታር የማስፋፊያ ስራ እየሰራ መሆኑን ወ/ት አለምፀሐይ አስረድተዋል፡፡
የካስትል ወይኖች ለምን ዋጋቸው ተወደደ ተብለው የተጠየቁት ሃላፊዋ ሲመልሱ፤ነጋዴዎች ፋብሪካው ከተመነው ዋጋ በላይ ከ100--200 ፐርሰንት ጭማሪ እያደረጉ ስለሚሸጡ ነው ብለዋል፡፡ ኩባንያው ስለ ወይን ጠጅ አይነቶች ለመስተንግዶ ባለሙያዎች ስልጠና እየሰጠ መሆኑንም ለማወቅ ተችሏል፡፡