Administrator

Administrator

   ታዋቂው የኳታር አየር መንገድ ካተሪንግ አገልግሎት፤ አዲስ ዓለም አቀፍ ካተሪንግ (የምግብና የመጠጥ ዝግጅት) ‹‹የ2016 ምርጥ የአፍሪካ ምግብ አዘጋጅ›› በሚል ለሁለተኛ ጊዜ ሸለመ፡፡ ከአሁን ቀደምም በ2014 በተመሳሳይ መሸለሙ አይዘነጋም፡፡
የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ አባል የሆነው አዲስ ዓለም አቀፍ ካቴሪንግ፣ ለኢትዮጵያና ለሌሎች አገሮች አየር መንገዶች፣ ለዓለም አቀፍ ጉባዔዎችና በአዲስ አበባ አካባቢ ለሚደረጉ ትላልቅ ዝግጅቶች ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው ምግብ ለማቅረብ በ1998 የተመሠረተ ተቋም ነው፡፡
በመላው ዓለም ከ150 በሚበልጡ መዳረሻዎች የሚበረው ባለ 5 ኮከቡ የኳታር አየር መንገድ፣ በሚበርባቸው አገሮች 105 የምግብና መጠጥ አዘጋጆች (ካተርስ) ሲኖሩት በአፍሪካ ወደ 24 መዳረሻዎች  ይበራል፡፡ የተሳፋሪዎችን አስተያየት፣ ወቅታዊ (ኦን ታይም) አቅርቦት፣ የተሳፋሪዎች ግብረ-ምላሽና ከምግብና ከደህንነት ጋር የተያያዙ በርካታ ጉዳዮችን የመዘኑ መሆኑን የጠቀሰው መግለጫው፤ ከምግብ አዘጋጆች ናሙና እንደሚወስዱ፣ መሳሪያዎች እንደሚመረምሩ፣ ግንኙነት እንደሚታይ፣ የአለቃ ሪፖርትና የአዘጋጃጀት ቅልጥፍና እንደሚታይ ተገልጿል፡፡
አዲስ ዓለም አቀፍ ካተሪንግ ከኳታር አየር መንገድ በተጨማሪ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ለሚጠቀሙ ሌሎች ደንበኞች ለምሳሌ ለጂቢቲ፣ ለግብፅ፣ ለኢምሬትና ለኬንያ አየር መንገዶች አገልግሎት እንደሚሰጥ የጠቀሰው መግለጫው፤ ለቪአይፒ፣ ለኪራይና በግል ለሚንቀሳቀሱ አውሮፕላኖች፡- እንደ አቢሲኒያ ፍላይት ሰርቪስና እንደ ትራንስ ኔሽን ላሉ ትናንሽ በረራዎች አገልግሎት እንደሚሰጥ አስታውቋል፡፡  በተጨማሪም፣ አዲስ ዓለም አቀፍ ካተሪንግ፣ ለጀርመን ኤምባሲ ት/ቤት፣ ለዓለም አቀፍ ኮሙኒቲ ት/ቤት፣ ለየን ኻርት አካዳሚና ለሳንፎርድ ዓለም አቀፍ ት/ቤቶችን ጨምሮ በተለያዩ ኤምባሲዎች፣ ባንኮችና ለግል ዝግጅቶች አገልግሎት ይሰጣል ተብሏል፡፡

  ከሰባት ዓመት በፊት በ2002 ዓ.ም በ15 ሚሊዮን ብር ካፒታል የተቋቋመው ኢትዮ ሃይላንድ ማራቶን ኤቨንትስ ኦርጋናይዝ ኩባንያ ከነሐሴ 12-14 ቀን 2009 ዓ.ም በሚሌኒየም አዳራሽ የትራንስፖርትና ሎጂስትክስ ዓለም አቀፍ ኤግዚቢሽን እንደሚካሄድ አስታወቀ፡፡
አዘጋጆቹ ባለፈው ሳምንት በካሌብ ሆቴል ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፣ ትራንስፖርት ያለ ሎጂስቲክ (የጭነት ዕቃ) የተሟላ አገልግሎት እንደማይሰጥ ሁሉ፣ ሎጂስቲክም ያለ ትራንስፖርት ብቻውን መቆም አይቻልም፤ ሁለቱ የተጣመሩና የተጎዳኙ ናቸው ብለዋል፡፡ ኤግዚቢሽኑን ያዘጋጁበት ዓላማ፣ ዘርፉ በሀገር ልማት ያበረከተውን አስተዋጽኦና መንግሥትን ጨምሮ ሁሉም ባለድርሻ አካላት የተጫወቱትን ሚና ለማሳየት፤ በትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዘርፍ የተሰማሩ ተዋናዮችና ባለድርሻ አካላት ልምዶቻቸውንና ስኬቶቻቸውን የሚለወዋወጡበት መድረክ ለመፍጠር መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ በዘርፉ ውስጥ ያሉ አካላት ምርቶቻቸውንና አገልግሎታቸውን የሚያስተዋውቁበት ሰፊ የገበያ ዕድል ለመፍጠርና በኤግዚቢሽኑ የትራንስፖርትና የሎጂስቲክ ችግሮችና ተግዳሮቶች እንዲሁም ያሉት መልካም ጎኖች ተፈትሸው ጥናታዊ ጽሑፍ የሚቀርብበትን ወርክሾፕ ለማዘጋጀት ነው ብለዋል፡፡
ኤግዚቢሽኑ የአንድ ጊዜ ብቻ ሳይሆን፣ ኢትዮ ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ፌር በሚል ስያሜ በየዓመቱ የሚቀጥል መሆኑን ጠቅሰው ጠቀሜታውንም ሲገልጹ፣ ዘርፉ ለአገር ኢኮኖሚ ያለውን ፋይዳ ለማሳደግ የሚያስችል ዕድል ይፈጥራል፣ በዘርፉ ያሉ ተዋናይና ባለድርሻ አካላት ምርትና አገልግሎታቸውን ያስተዋወቁበታል፣ ተዋናዮቹ፣ በጋራ ችግሮቻቸው ላይ ተቀራርበው በመነጋገር የመፍትሄ ሀሳቦችን ያፈልቁበታል በማለት አስረድተዋል፡፡
በዚህ ኤግዚቢሽን ላይ የትራንስፖርት ሚ/ር፣ የክልልና የከተማ አስተዳደር ትራንስፖርት ቢሮዎች፣ የሕዝብና የዕቃ ማጓጓዣ ትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎች፤ የባህር፣ የአየር፣ የየብስ፣ የባቡር፣ የወደብ አገልግሎት ሰጪዎች፣ ዕቃ አስተላላፊዎች፣ ዕቃ የማሸግና ለጉዞ የማመቻቸት አገልግሎት ሰጪዎች፣ ልዩ ልዩ የተሽከርካሪ መለዋወጫ አምራቾች፣ አስመጪና ላኪዎች፣ ጋራዦች፣ የንግድ ወኪሎች፣ የነዳጅ ኩባንያዎች፣ ባንኮችና ኢንሹራንሶች፣ ጎሚስታዎች፣… እንደሚሳተፉ ተገልጿል፡፡

   ‹‹በዩኒቨርሲቲ ለማጥናት የመጀመሪያ ምርጫዬ ህክምና ነው፤ ካልሆነ ስፔስ ሳይንስ ባጠና አይከፋኝም››

     ኦልማርት ሱፐር ማርኬት ከቅድስት ማሪያም ዩኒቨርሲቲና ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የትምህርት ቢሮ ጋር በመተባበር “Excellence for Education” የተሰኘና በአዲስ አበባ የሚገኙ 20 የመንግስት መሰናዶ ት/ቤት ተማሪዎች
የሚወዳደሩበት የጥያቄና መልስ መርሀ ግብር አዘጋጅቶ ነበር፡፡ በዚህ መርሀ ግብር ለ6530 ተማሪዎች እድል ተሰጥቶ ሚያዚያ 26 ቀን 2009 ዓ.ም 3 ሺህ ተማሪዎች ለፈተና የቀረቡ ሲሆን ባለፈው ቅዳሜ ማጣሪያ ካለፉት 100 ተማሪዎች ምርጥ አስሩ ተለይተው፣ ባለፈው ሰኞ ምሽት በራዲሰን ብሉ ሆቴል ሽልማታቸውን ወስደዋል፡፡ በሽልማት ስነ ስርዓቱ ላይ የተገኘችው የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ በውድድሩ 1ኛ ከወጣውና የአየር ጤና መሰናዶ ት/ቤት ተማሪ ከሆነው የ19 ዓመቱ ወጣት አቤል ሽፈራው ጋር ተከታዩን ቃለ ምልልስ አድርጋለች፡፡

      ከመጀመሪያ አንስቶ አየር ጤና ነው ትምህርትህን የተከታተልከው?
አየር ጤና አካባቢ ባሉ ት/ቤቶች ነው የተማርኩት፤ የተወለድኩት ግን መሀል አዲስ አበባ አራዳ ክ/ከተማ ውስጥ ነው፡፡ ቤተሰቦቼ በቤት ኪራይ ይኖሩ ስለነበር፣ ከዚያ ቤት ሰርተው ወደ ወለቴ ሄድን፣ አንደኛ ደረጃም ሆነ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን የቀጠልኩት ከ1-10ኛ ክፍል ካራ ቆሬ ረጲ 1ኛና መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ሲሆን ለመሰናዶ ትምህርት ነው አየር ጤና መሰናዶ የገባሁት፡፡
የቤተሰብህ የኑሮ ሁኔታ ምን ይመስላል?
ቤተሰቤ እንደ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ቤተሰብ ተቸግረው ነው ያስተማሩኝ፡፡ እነሱ በቅጡ ባልተማሩበትና ባልተደላደሉበት ሁኔታ ውስጥ ሆነው ነው፣ እኔንም ሆነ ከእኔ በላይና በታች ያሉ እህትና ወንድሞቼን እያስተማሩ ያሉት፡፡ እነሱ ለእኔ አርአያዎቼ ናቸው፤ እኔም የእነሱ ውጤትና መገለጫ ነኝ፡፡ በጣም ነው የማመሰግናቸው፡፡
ከ1ኛ ክፍል ጀምሮ እስካሁን በትምህርት ውጤትህ እንዴት ነህ?
የሚገርምሽ ከ1ኛ ክፍል ጀምሬ ጎበዝ ተማሪ ነበርኩ፤ በተለይ ከ3ኛ ክፍል ጀምሮ በከፍተኛ ትኩረት ነው ትምህርቴን ስከታተል የነበረው። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በሁሉም የትምህርት አይነት ጥሩ ውጤት በማምጣት የደረጃ ተማሪ ሆኜ ነው የቀጠልኩት፡፡ አሁንም ወደ ዩኒቨርሲቲ ለመግባት በዝግጅት ላይ ነኝ፤ የ12ኛ ክፍል ፈተናዬን በደንብ ለመስራት በመትጋት ላይ እገኛለሁ፡፡
እንደነገርከኝ እድሜህ 19 ዓመት ነው፡፡  16 እና 17 ዓመት ወጣቶች በአቻዎቻቸው ግፊት ወደ ብዙ ነገሮች የሚገቡበት እድሜ ነው፡፡ አንተ ይህን ተቋቁመህ ጎበዝ ተማሪ የሆንክበት ምስጢር ምንድን ነው?
በጣም ከባድ ጊዜ ነው፡፡ እንደምታውቂው ጊዜው የግሎባላይዜሽን ነው፡፡ ይህ ማለት ብዙዎቻችን በውጭ የኑሮ ዘይቤ ተፅዕኖ ውስጥ ነው ያለነው። ይህንን ተፅዕኖ ተቋቁሞ ማለፍ ራሱን የቻለ ሌላ ፈተና ነው፡፡ እኔ በበኩሌ፤ ከዚህ ፈተና ለማምለጥ ስል ከሚዲያ የራቅኩ ነኝ፡፡ ኢንተርኔትና ፌስቡክ ሁሉንም አልጠቀምም፤ ትኩረቴን ወደ ትምህርት ነው ያደረግሁት፡፡ ስልክ እንኳን ለመደወልና ለጥሪ ብቻ ነው የምጠቀመው፡፡ እነዚህን ነገሮች ልጠቀም ብዬ  ቤተሰቤን ብጠይቅ፣  የራሳቸውን ነገር ወደ ጎን አድርገው እንደሚያሟሉልኝ አምናለሁ፡፡ ግን በዚህ ወቅት ላይ ለእኔ አስፈላጊ ስላልሆነ አልፈልግም በሚል ወደ ትምህርቴ አዘንብያለሁ፡፡ በአጠቃላይ በትምህርቴ ላይ ተፅዕኖ የሚያሳድር ማንኛውንም ነገር ትቼ፣ ትምህርቴ ላይ ማተኮር ቅድሚያ የምሰጠው ተግባሬ ነው፡፡
ኦልማርት ያዘጋጀውን ውድድር እንዴት አገኘኸው ወይስ ኦልማርትን ከዚህ በፊት ታውቀው ነበር?
እውነት ለመናገር ኦልማርትን ከዚህ በፊት አላውቀውም፤ እንዲህ የሚባል ድርጅት ስለመኖሩም መረጃ አልነበረኝም፡፡ ውድድሩ ተዘጋጀ ተብሎ ለፈተና ልንቀመጥ ሲቀበሉን በጣም ነበር የገረመኝ። የሄድንበት አውቶቡስ፣ የአዘጋጆቹ ትህትና፣ በአጠቃላይ የሰጡን ዕድል ከእኔ ግምት በላይ ነው፡፡  በቀጣይ ትልልቅ ፈተና ለሚጠብቃቸው የመንግሥት የ12ኛ ክፍል ተማሪዎች ይህ ፈተና መዘጋጀቱ ትልቅ ዕድል ነው፤ ምክንያቱም ለዋናው ፈተና ያነቃቃቸዋል፡፡ በሌላ በኩል ሽልማቱና ከዚህ ሁሉ ሰው አንደኛ ሆኖ መውጣት ትልቅ እድልና በራስ  ይበልጥ መተማመንን ያጎለብታል። በሌላ በኩል ከተመለከትነው እኛ ይህን ዕድል በኦልማርት ማግኘታችንና እዚህ በመድረሳችን ለሌሎች ተማሪዎች መነቃቃትን ይፈጥራል፡፡ በጣም የገረመኝ ከ1-10 የወጣነውን የሸለሙን ባለ 5 ኮከብ ሆቴል ውስጥ በትልቅ ክብር ነው፡፡ ይህንን ሁሉ ስመለከተው እንኳን 1ኛ ወጥቼ አይደለም ተሳታፊ ሆኜ ብሸኝ እንኳን ለእኔ ለቤተሰቤም ኩራት ነው። በአጠቃላይ ውድድሩ እንዲህ ደረጃውን የጠበቀ ይሆናል ብለን አልጠበቅንም፡፡ እኔም ሆንኩ ከኔ ቀጥሎ እስከ 10ኛ የወጡት ልጆች በጣም ደስተኞች ነን፡፡
አንደኛ እወጣለሁ ብለህ ጠብቀህ ነበር?
አልጠበኩም፡፡
ለምን አልጠበክም?
ምክንያቱም የሌሎች ጎበዝ ተማሪዎችን ውጤት መገመት ይከብዳል፡፡ የዛሬ ሳምንት ቅዳሜ ምርጥ 10ሮቹ ውስጥ መግባታችን ሲነገረን፣ ማንኛችን አንደኛ እንወጣ ይሆን በሚል ስጨነቅ ነበር፤ ሆኖም ምርጥ 10 ውስጥ መግባቴን ራሱ እንደ ቀላል ውጤት አልቆጠርኩትም፡፡ ለምን ቢባል መጀመሪያ ከሶስት ሺህ ተማሪ ምርጥ መቶዎቹ ውስጥ መግባት በራሱ ትልቅ ነው፡፡
ከዚያ ምርጥ አስሩ ውስጥ በመጨረሻም አንደኛ መውጣት በጣም ያስደስታል፡፡ ያልጠበቀኩት ነገር ስለሆነ እኔ ብቻ ሳልሆን ቤተሰቦቼ በጣም ተደንቀዋል፡፡ አባቴና ሌሎች ቤተሰቦቼ እዚህ አዳራሽ ይገኛሉ፡፡ መወዳደሬን ራሱ ምርጥ 10 ውስጥ ከገባሁ በኋላ ነው የነገርኳቸው፡፡ በተለይ አባቴ ደስታውን መቆጣጠር አቅቶታል፡፡ ቤተሰቦቼም እንዲህ ትልቅ ውድድር መሆኑንና አንደኛ ይወጣል ብለውም አልጠበቁም ነበር፡፡
የፈተናው ሂደት ምን ይመስል ነበር፡ የቅድስት ማሪያም ዩኒቨርስቲ የፈተና አወጣጥ እንዴት ነበር? ጥያቄዎቹ ከባድ ናቸው ቀላል? ምን ምን ያህል ጥያቄዎችና ምን ያህል ሰዓት ነበር የተመደበው? እስኪ ጠቅለል አድርገህ መልስልኝ?
ቅድስት ማሪያም ዩኒቨርሲቲ ጥያቄዎቹን ያወጣው የፈተኑን ደረጃውን በጠበቀ መልኩ ነው። ማንኛውም አገር አቀፍ ፈተና ስንፈተን የሚሟላው ነገር ተሟልቷል፡፡ በራሳቸው መምህራን ነው የፈተኑን፡፡ ፈተናውም ከታሸገበት እዚያው ፊት ለፊታችን ነው የተቀደደው፡፡ ፈተናዎቹ በጣም ደስ ይላሉ፡፡ ሌላ ፈተና ለመስራት ያነቃቃሉ፣ ከዝግጅታቸው ጀምሮ ጥሩ የፈተና ሂደቶችን እንድናልፍ አደርገዋል፡፡ ወደ መፈተኛ ቦታው ስንሄድ ራሱ የተጓጓዝንበት አውቶቡስ ያነቃቃ ነበር፤ ያለማጋነን ነው የምነግርሽ፡፡ የምሰጠው አስተያየት በተለይ የሂሳብ ጥያቄዎቹን ትንሽ ጠንከር አደርገው ቻሌንጅ ቢያደርጉን ጥሩ ነበር፡፡ ምክንያቱም እዚህ ፈተና ላይ የተቀመጠው ሁሉም ተማሪ ብቃት ያለው ነው፡፡ ጥያቄዎቹ በእኔ እይታ ትንሽ ላላ ብለዋል፤ ይሄ የእኔ የግል አስተያየት ብቻ ነው፡፡ ጥያቄዎቹን በተመለከተ በተለይ ሁለተኛው ፈተና ላይ ውጤት ባይነገረንም ሂሳብ ምንም የከበደኝና የሳትኩት ጥያቄ እንደሌለ እርግጠኛ ነኝ፡፡ እንግሊዝኛ ትንሽ ከበድ የሚሉ ጥያቄዎች ነበሩት፡፡ የጥያቄው ብዛት እንግሊዝኛ መቶ ጥያቄ ሲሆን ሂሳብ 60 ጥያቄ ነው የቀረበልን፡፡ 2፡30 ለሂሳብ፣ ሁለት ሰዓት ደግሞ ለእንግሊዝኛ ተፈቅዶልናል፡፡ በዚህ ሰዓት ነው ሰርተን ያጠናቀቅነው፡፡ ትንሽ እንግሊዝኛ ላይ  ብዙዎቻችን የተቸገርን ይመስለኛል ምክንያቱም እርስ በእርሳችን የምንግባባው በአማርኛ ነው፡፡ በተረፈ ግን ይህ ፈተና ወደ ዩኒቨርሲቲ የሚያስገባንን ዋናውን ፈተና በምን ያህል አቅምና ዝግጅት እንሰራለን የሚለውን ያሳየንና ራሳችንን የለካንበት በመሆኑ፣ አዘጋጁንና አጋሮቹን ደጋግሜ ማመስገን እፈልጋለሁ፡፡
ከዚህ በፊት እንዲህ አይነት የውድድር እድሎች ገጥመውህ ያውቃሉ?
በፍፁም ተወዳድሬ አላውቅም፡፡ ይሄ የመጀመሪያዬ ነው፡፡ በእርግጥ ወደ 10ኛ ክፍል እንዳለፍኩ ስኮላርሺፕ የሚሰጥ አንድ ድርጅት መጥቶ ውጤቴን አስገብቼ ነበር፤ የመፈተን እድል ግን አልገጠመኝም፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው እንዲህ አይነት ቦታ መጥቼ ይህን እድል ያገኘሁት፡፡
ከትምህርት ውጭ ሌላ ምን ዝንባሌ ወይም ተሰጥኦ አለህ?
ሌላ ተሰጥኦ ለጊዜው የለኝም፡፡ ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ ሙሉ ትኩረቴን የማደርገው ትምህርቴ ላይ ነው፡፡ በእርግጥ ት/ቤት ውስጥ ተሰጥኦም ባይባል ርዕሰ መምህራንንና መምህራንን ለማገዝ አንዳንድ ጥረቶችን አደርጋለሁ፡፡ አየር ጤና መሰናዶ ት/ቤት ውስጥ በጣም ብዙ ተማሪ ነው ያለው፡፡ መምህራንና ርዕሰ መምህራን ያንን ሁሉ ተማሪ ለመግራትና ብቁ ዜጋ ለማድረግ የሚወጡት የሚወርዱት መከራ፣ የሚያሳልፉት ስቃይ በጣም ያሳዝነኛል፡፡ እውነት ለመናገር እንደነዚህ ያለ ለዜጋ የሚቆረቆሩ መምህራን አይቼ አላውቅም፡፡ እኔንም ለዚህ ስላበቁኝ ክብር ይገባቸዋል፡፡ ያበረታቱናል፤ በተቻላቸው አቅም የእኛን ባህሪና ውጤት ለማሻሻል ይደክማሉ፡፡ ይህን የሚያደርጉት ብዙ ነገር ባልተሟላበት የመንግስት ት/ቤት በመሆኑ ክብርና ሽልማት ይገባቸዋል፡፡ ከዚህ ት/ቤት የሚወጡ ብዙ ተማሪዎች በጥሩ ውጤት ነው ትምህርታቸውን የሚጨርሱት፡፡ ይህ ሁሉ የመምህራኑና የማኔጅመንቱ ልፋት ነው፡፡
ወደ ዩኒቨርስቲ ለመግባት የሚያስችልህን ፈተና ለመፈተን ጥቂት ቀናት ናቸው የቀሩህ፡፡ ምን ያህል እየተዘጋጀህ ነው?
በጥሩ ዝግጅት ላይ ነኝ፡፡ ት/ቤትም የሞዴል ፈተናዎችን እየተፈተንን ነው ያለነው፡፡ አሁን ተወዳድሬ ያለፍኩበትም ፈተና ጥሩ መነቃቂያ ሆኖልኛል፡፡
ዩኒቨርስቲ ስትገባ ማጥናት የምትፈልገው ምንድ ነው?
እግዚአብሔር ፈቅዶ ጥሩ ውጤት አምጥቼ ዩኒቨርሲቲ ከገባሁ፣ ለማጥናት የመጀመሪያ ምርጫዬ ህክምና ነው፤ ይሄ የምንጊዜም ህልሜ ነው፡፡ ቢሳካልኝ ደስ ይለኛል፡፡ ይህ ካልሆነ ስፔስ ሳይንስ በጣም ስለምወድ እሱን ባጠና አይከፋኝም፡፡
በውድድሩ 1ኛ በመውጣትህ 15 ሺህ ብርና ለትምህርት የሚረዳ ታብሌት ኮምፒዩተር ተሸልመሀል፡፡ ብሩን ምን ልታደርግበት አስበሀል?
እኔ እንደዚህ አይነት ብር በእጄ ይዤ አላውቅም። ከብር ጋር የተነካካ ነገርም የለኝም፡፡ ያው ቤተሰቦቼ የሚፈልጉትን ሊያደርጉበት ይችላሉ። ግን በመሸለሜ ደስተኛ ነኝ፡፡ ታብሌት ኮምፒዩተሩ አሁን አያስፈልገኝም፡፡ ወደፊት ስለምጠቀምበት አስቀምጠዋለሁ፡፡
በመጨረሻ ማለት የምትፈልገው ካለ?
በመጀመሪያ ለዚህ ያበቃኝን ልዑል እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ፡፡ በመቀጠል ብርቱዎቹን ቤተሰቦቼን አመሰግናለሁ፡፡ ታላላቅ ወንድሞቼ ለእኔ አርአያ ናቸው፡፡ ታላላቅ ወንድሞቼ በርትተው ተምረው ጥሩ ደረጃ ላይ ደርሰዋል፡፡ እኔም ውጤታማ እንድንሆን ለሚያደርጉት ድጋፍ አከብራቸዋለሁ፡፡
እናቴና አባቴ በጣም መልካም ሰዎች፣ ልጆቻቸውን በጥሩ ስነ ምግባር የሚያንፁ ናቸው፡፡ ያው እኔም ነፀብራቃቸው እንድሆን ለፍተዋልና አመሰግናለሁ፡፡ ይህንን ውድድር አመቻችቶ፣ በዚህ ሁኔታ የሸለመንን ኦልማርትንና አጋር ድርጅቶቹን አመሰግናለሁ፡፡ ኦልማርት በዚህ ረገድ በር ከፋች ነው፡፡ በቀጣይ ሚኒስትሪ ለሚፈተኑም የ8ኛ ክፍል ተማሪዎች ጭምር ይህን እድል ቢያመቻችላቸው ጥሩ ነው የሚል አስተያየት አለኝ ሁሉንም ግን አመሰግናለሁ፡፡   

     የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር ጤና ቢሮ ከአስትራዜንካ ጋር በመተባበር በሳምንቱ አጋማሽ ላይ በስድስት ክፍለ ከተሞች  ነፃ የደም ግፊት ምርመራዎችን አከናወነ፡፡ በአዲስ አበባ የተለያዩ ክፍለ ከተሞች የተካሄደው የነፃ ምርመራ አገልግሎት በአህጉራዊው ተቋም አስተርዜንካ ልዩ ፕሮግራም ሔልዚ ኸርት አፍሪካ (HHA) አማካኝነት ሲሆን በመላው ዓለም ከሚከበረው የዓለም የደም ግፊት ቀንን ምክንያት በማድረግ የተከናወነ ነው፡፡
“በደም ግፊት ማም ሰው መሞት የለበትም” በሚል መርህ የሚንቀሳቀሰው አስትራዜንካ፤ ከኢትዮጵያ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ጋር በአጋርነት ለመስራት ስምምነት ያደረገው ባለፈው ዓመት ሲሆን በኸልዚ ኸርት አፍሪካ ፕሮግራሙ፣የደም ብዛት በሽታን ለመዋጋት የሚደረገውን እንቅስቃሴ ለማገዝ እንዲሁም በሽታውን ለመከላከል የሚያስችሉ የአሰራር መዋቅሮችን ከአገሪቱ የጤና አስተዳደር ጋር አጣጥሞ ለማከናወን ድጋፍ እየሰጠ ይገኛል፡፡
በዚህ መሰረትም ከዓመት በፊት ከመላ አፍሪካ የተውጣጡ ታዋቂ የህክምና ባለሙያዎች ወደ ኢትዮጵያ መጥተው በአገር አቀፍ ደረጃ በመንቀሳቀስ ለሃኪሞችና ሌሎች የጤና ባለሙያዎች እንዲሁም የህክምና ተቋማት የግንዛቤ ማስጨበጫና የስልጠና መድረኮችን በማዘጋጀት ሰርተዋል፡፡ የአስትራዜንካ ኸልዚ ኸርት አፍሪካ ፕሮግራም ከኢትዮጵያ በፊት በጎረቤት  አገር ኬንያ ተግባራዊ በመሆን ከፍተኛ ውጤት እንደተገኘበትም ለማወቅ ተችሏል፡፡ ሰሞኑን ‹‹የዓለም የደም ግፊት ቀን››ን ምክንያት በማድረግ በተከናወነው ነፃ የደም ግፊት ምርመራ ተጠቃሚ የሆኑት የጤና ማዕከላት በየካ፤ በልደታና አብነት፤ በአዲሱ ገበያ፣ፒያሳና ቀጨኔ፤ በሩፋኤል ማዞርያ በቃሊቲና አቃቂ የሚገኙ እንደሆኑ ታውቋል፡፡ አስትራዜንካ  የኸልዚ ኸርት አፍሪካ ፕሮግራምን በማከናወን ለ900 የጤና ባለሙያዎችና የህክምና ድጋፍ ሰጪዎች ስልጠና የሰጠ ሲሆን በሰባት የአገሪቱ ክልሎች በሚገኙ 12 ሆስፒታሎችና 36 የጤና ማዕከላት የተቀናጀ የአሰራር መዋቅርን መዘርጋቱ ታውቋል፡፡
ባለፈው አንድ ዓመት ለ100ሺ ሰዎች ነፃ የደም ግፊት ምርመራ በማካሄድ 13ሺ ግለሰቦች በሽታው እንዳለባቸው ለመጀመርያ ጊዜ ያረጋገጠው ፕሮግራሙ፤ከደም ግፊት ጋር በተያያዘ ደረጃውን የጠበቀ ህክምና፤ እንክብካቤና የተሟላ አገልግሎት የሚሰጥበትን ሁኔታ በመላው ኢትዮጵያ ለማስፋፋት በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡
የደም ግፊት ለልብ ህመምና ሌሎች ተያያዥ በሽታዎች የሚያጋልጥ ሲሆን የዓለም ጤና ድርጅት እንደሚያመለክተው፤በአፍሪካ ከደም ግፊት ጋር በተያያዘ ያለው የግንዛቤ ማነስ በበሽታው የሚከሰተውን የሞት አደጋ አሳሳቢ አድርጎታል፡፡  

Sunday, 21 May 2017 00:00

ጉድ‘ኮ ነው! አሰፋ ጫቦ

  ሲያስቡት? ጉድ! እንዲያው ጉድ እኮ ነው!
ያንዱ ሥጋ ወነፍስ፣
የሌላው ቀለብ፣ ድግስ፤
ምሳ ራት ቁርስ፡፡
እኔኮ የሚገርመኝ፣
የሚከነክነኝ፣
      ይኸ ሰርቶ አፍራሹ
ፈጣሪው ደጋሹ     
ከያሊው ፈዋሹ፡፡
ያኔ ሲነገር፣ ስንማር፣ ስንመከር፣
ምሉእ በኩሌሐ
ወይትባረከ ሰመ ስብቲሐ
እስመ አልቦ ነገር አሚረ ኩሉ
መአቱ የራቀ ምህረቱ ሙሉ
ብለው አሳምነው አልነበር?
ያልነገሩን ተረፈሪ ሚስጥር ነበረ?
ምነው ልቤ ጠረጠረ?
ሰማይን ያለባላ፣ ያለምሶሶ
ምድርን ያለካስሚያ፣
የዘረጋ፣ የወጠረ፣
ኁልቆ መሳፍርቱን የፈጠረ፣
ዝንፍ፣ እልፍ የማይል
      የማይልበት
የወርቅ ሚዛን ያለው፣
     የሚለካበት፣
የውሃ ልክ ያለው የሚለስንበት፣
             የተባለለት፡፡
አድሎ የሌለበት፣
ከዘላለም በፊት የነበር፣
ከዘላለም በኋላም የሚኖር፣
ህጸጽ አልባ ሚስጢር፣
ነው-ው-ው! ተብየም አልንበር?!
እና!? እኮ!? ያ ሁሉ የት ሔደ?
እንደጉም በነነ? እንደኬላ ተናደ?
ይኸው ነው የዚያ ሁሉ ስብከት ውጤት?
አንዱ የሌላ ቁርስ ምሳ ራት
ማነው ስቶ ያሳተኝ?
ካናቱ ወደ ደቀ መዛሙርታት?
 
ልቤ የሚጠረጥረው?
እንዲያው ድንገት ለምናልባት፣
ባራያ በምስሉ የፈጠረን ለት፣
ሲወጥር፣ ሲተክል፣
ሲያቆም ሲጥል፣ ሲነቅል፡፡
ሲዘረጋ፣ ሲሸበሽብ፣
ጎንበስ ቀና እስኪያልብ፡፡
ቀና ደፋ ሲል ደክሞት፣
ታክቶት፣ ሰልችቶት፣
የሰአት እላፊም ደርሶበት፣
ሲጣደፍ ኮታ ለመሙላት፣
ጀምበር ጠልቆ፣ መሽቶበት፡፡
አላልቅ ብሎ ሲጣደፍ፣
ለሚኒሞው ገረፍ ገረፍ፣
በዊክ ኤንድ ለማረፍ፡፡
በድንግዝግዙ ለድንገት ዞር ባለበት፣
ሚዛኑ ላፍታ፣ ለድንገት
ደፋ፣ ቀና፣ አለበት?
ተንጋዶ? ሔድ መለስ አለበት?
ላንዳች ቅጽበት፣ ሰውን ፈጠርኩ ባለበት?
እንጅማ!
እንደ መሸታ ስራ ሠንካላ፣
በቅጡ ያልበሰለ ያልተብላላ፣
ተሟሽቶ ያልተሞከረ፣ ያለየ፣
ጉዳት ጠቀሜታው ያልታየ፣
ሰንካላ፣ ግርድፍ፣ ያልተበራየ፡፡
በቃ ሂድ፣ ወግዱ፣
ከዚህ ጥፉ፣
ብሉ፣ ተባሉ፣
ምድርንም አጥፉ!
ይኸውልህ! እች ያንተ ነፍስ፣
ትሁን ለነንትና ድግስ፤
ምሳ፤ራት፣ቁርስ፣
ነውር አይደለም እንዴ በኔ ሞት!?
ተፈቶ ይለቀቃል እንዴ መጠፋፋት?
መተላለቅ መሟሟት?
ደሞም!
ስራውን አያቅም፤
አይችልምም አልተባለም!!
እኔማ የሚገርመኝ
መንጋ ጉሮሮ ከፍቶ፣
መዝጊያ፣ መቀርቀሪያ ሳይሰራ ትቶ
ግበረ-በላ አብዝቶ፣ ለቆ ፈቶ፣
ቀለብ ሳይሰራለት፣ ሳይቀርጥለት፣ ሳይሰፍርለት፣
እንዲኖር ተናንቆ፣
ተነጣጥቆ፣
ተጠባብቆ፡፡

ጎብዝ! እኔ የምለው!
ምነ አንድ እድል ቢሰጠን፣
ያለፈውን፣ ያለውን፣
ሙከራ ነበር! ተሞክሮ ነበረ፤
አልተሳካም ከሸፈ ከሰረ!
ፋይሉም ፋብሪካውም ይዘጋ፣
ይቆጠር እንዳልነበረ፡፡
እናም እንዳያዳግም፣ እንዳያደጋግም፣
በትርፍ ሰአት ክፍያም ቢሆንም፡፡
ስድስቱ ቀን ቀርቶ፣
አዲስ ተዘርቶ፣ ታጭዶ፣ ተወቅቶ፣
አብሲት ተጥዶ፣ በቅጡ ቦክቶ፣
ስምንትም ይሁን ሰማኒያ ቀን ተፈጭቶ፣ ተፋጭቶ፣
ሰውን የሚያክል ነገር አደል?
የፍጥረታት የበላይ አካል?
የሚፈጠር ባምላክ አምሳል?
አዲሱ ሰው ይሰራ ቢባል!?
አንገቱን ረዘም መለል ማሰኘት፣
ተነቃናቂ ተጣጣፊ ብሎ ማስገባት፣
ለስላሳ ኩሺኔትም ጨምሮ መክተት፣
ዙርያ-ገቡን ሁሉ-ገቡን እንዲያይበት፣
እዝነ ልቦናውም አይነ ልብናውም፤
ዳጎስ፣ ጎላ ቢልለት፤
የሰማው ያየው፤ እንድያርበት፣ እንዲያድርለት፤
እንዲሰነብት፤ እንዲሰነባብት፡፡፡
ዘኃለፈ ሰርየትም እንዲለበት፣
ከማት አምጭነት እንዲታቀብበት!
ሰፋፊ ልብም፣ ልቦናም የሰጠው!
ትልቁ ቱቦ፣ ትልቅ ቧንቧ ያለው፤
ሰው የሚሔድበት፤
ሰው የሚመጣበት፡፡
ሰው የሚመላለስበት፣
ሰው አድሮ የሚውልበት፣
ሰው የሚታቀፉበት፣
ሰው የሚታቀቡበት፣
…. የሚሰነባብትበት!
የሰራ አካላቱ እንዲሁ፣
…. ዚኒ ከማሁ፡፡

ወይስ ከነአካቴው!
እንበል እንዴ ሰሪም ተሰሪም፣
ፈጠሪም ተፈጣሪም አልነበረም!?
ይኽ ክርቲካል ማስ ያሉት ሲገጣጠም፤
ሰኔና ሰኞ ፍጥምጥም!
አስቀድሞ የነበር፣ ያልነበር አንድ ትልቅ ዝም!
አንድ ቀን ቡም! ቡም! ቡ-ም-ቡ-ም!
………… ቡምቡም!
መሰባሰብ! መጠረቃቀም!
ከመሀል አልቦ የትም!
ወደዝንተ አለም ምንም!
ወደ ዘላለም እርም!
…. አበስኩ! ገበርኩ!
April 1,1995
Los Angeles, California, USA

 እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ሰውየው መሥሪያ ቤት ውሎ ቤቱ ይገባል፡፡ መሥሪያ ቤት ደግሞ ስብሰባ ነበር፣ ለሦስተኛ ቀን። ቤቱ ሲገባ ሚስት ሆዬ ግንባሯን ከስክሳ “ማነሽ፣ እራት አቅርቢለት…” ብላ የአቴዝና ባህርን  መጨረሻ ለማየት ቴሌቪዥኗ ላይ ማፍጠጥ፡፡
እሱ ሆዬ “ኤሊፍን ስንገላገል ባህር የሚሏት መጣችብን!” እያለ ቀመስ፣ ቀመስ አድርጎ መኝታ ቤት ይገባል፡፡ የዕለት ማስታወሻውን ያወጣል…ይጽፋልም፡፡ ይሄ የዕለት ማስታወሻ ከዕለታት አንድ ቀን ‘ለልማት ተብሎ የሚፈርስ ጎጆ ስር’ (ቂ…ቂ…ቂ…) መገኘቱ አይቀርም፡፡ ቀኑ ይጻፋል፣ ይጀመራልም፡፡
ደከሞኛል በጣም ደክሞኛል፡፡ ሰሞኑን በስብሰባ ተንበሸበሽናል፡፡ የስብሰባ ብዛት አንገት ቀና የሚደረግ ቢሆን ኖሮ ይሄኔ አንገታችን ፕሉቶ ማዶ አዲስ ወደተገኘችው ፕላኔት ይደርስ ነበር፡፡ ምን ላድርግ፣ ልቀልድ እንጂ!
በአሁኑ ሰዓት የምፈልገው መኝታዬ ውስጥ ገብቼ ጥቅልል ብዬ መተኛት ነበር፡፡ ግን የዕለት ማስታወሻዬን መጻፍ አለብኝ፡፡ ምክንያቱም…እንደ እውነቱ አሁን ስምንተኛው ሺህ ለመድረሱ እርግጠኛ ነኝ፡፡ ስምንተኛው  ሺህ ባይደርስ ኖሮ እንዲሀ መጫወቻ አንሆንም ነበራ!
የአዳራሹ ግድግዳ ጨርቅ ላይ በተጻፉ መፈክሮች ተዥጎርጉሯል፡፡ ጠረዼዛው በባንዲራና በወረቀት መፈክሮች ተብለጭልጯል፡፡
‘የተጀመረውን ልማት አጠናከረን ለማስቀጠል በቁርጠኝነት እንሠራለን…’ ይላል ትልቀኛው መፈክር። ደግነቱ “እስከ ዛሬ የምትሠሩት በቁርጠኝነት አልነበረማ!” ብሎ የሚመጣ ቢኖር ምን እንል ይሆን ብሎ የሚጨነቅ የለም፣ ጠያቂ አይኖርማ!  የጊዜው የስብስባ ‘ኮምፐልሰሪ’ መፈክር ከተለጠፈ በቂ ነው፡፡  ስብሰባ አዳራሹ በሰው ጢም ብሏል…‘የቀረ ሰው ይጠቆራል’ ስለተባለ የቀረ የለም፡፡ በሰበብ አስባቡ የሚያስጠቁር በበዛበት ዘመን ማን ጥርስ ውስጥ ይገባል! ደግሞ ዘንድሮ ስብበሳ አዳራሽ የምንቀመጠው እየበዙ በሄዱ ‘መለኪያዎቻችን’ በመፈላላግ ሆኗል፡፡ እንደ አንድ መሥሪያ ቤት የሥራ ባልደረቦች ሳይሆን እንደ ቤተ ዘመድና እንደ ‘አገር ልጅ’ ተፈላልገን ትከሻ ለትከሻ መግጠም የጋራ መግባቢያ አይነት ነገር የሆነ ይመስላል፡፡ በተለይ ይቺ ‘የአገር ልጅነት’ መፈላለግ በየስፍራው እየገባች ግራ እያጋባችን ነው፡፡
ሦስት ሰዓት የተጠራው ስብሰባ አራት ሰዓትም አልተጀመረም፡፡ የክብር እንግዳው አልመጣማ! የእሱ መክፈቻ ንግግር ከሌለበት ስብሰባው ለአቅመ የምሽት ዜና አይበቃማ!
አብዛኛውን ጊዜ የክብር እንግዳ የሚባሉት ወይ የመሥሪያ ቤቱ ሥራ አስኪያጅ ወይም ዳይሬክተር ናቸው፡፡ ቆይማ…ሰዎቹ በድርጀቱ ፔይሮል ላይ እየፈረሙ ደሞዝ የሚነጩ ሠራተኞች አይደሉም እንዴ! ታዲያ ‘የክብር እንግዳ’ የሚለው ቅጥያ ምን አመጣው! በገዛ ቤታቸው!
እንደዛም ሆኖ ሰዓት አክብሮ ቢመጣ ጥሩ፡፡ እሱ ልክ ለአራት ሰዓት ሰባት ደቂቃ ሲቀረው ይመጣል፡፡ (አርፍዶ መምጣት ‘የክብር እንግድነት’ አንዱ መለያ የሆነ ይመስላል፡፡) እናማ…ጭብጨባ ይጀመራል። ከበሩ ጀምሮ መቀመጫው እስኪደርስ ድረስ በጭብጨባ እናጅበዋለን፡
የሰለቸኝ ይሄ ጭብጨባ ነው፡፡ የአሥር ሺህ ሜትር ሬከርድ አልሰበረ!… ማራቶን ከሁለት ሰዓት በታች አልገባ! በቃ፣ እንደኛው የድርጅቱ ቅጥር ሠራተኛ ነው፡፡ እንደውም በየቢሯችን ስለ እሱ የምንንሾካሾከው ነገር አደባባይ ቢወጣ፣ ካሊም ተከናንቦ ቤቱ ይከረቸም ነበር፡፡ ለነገሩ አብዛኞቻችን የምናጨበጭበው ‘ላለመጠቆር’ ነው፡፡ ሰው ሁሉ ሲያጨበጭብ እኛ ዝም ብለን ከቆምን አለቀልና! የዚህ አገር ነገር እንደዚህ ሆኗላ! “ትጉህ ሠራተኛ ነው?” ከማለት ይልቅ “ትጉህ ደጋፊዬ ነው?” የሚለው ጥያቄ ይቀድማላ!
ቀጥሎ የስብሰባ መሪው የአስተዳደርና የፋይናንስ ኃላፊው ወደ መናገሪያው ሲሄድ እሱንም በጭብጨባ እናጅበዋለን፡፡ ቲማቲም ሲወደድ ጭብጨባ የረከሰባት አገር! …ቂ…ቂ…ቂ…
መሥሪያ ቤቱ ውስጥ የምድር ኑሯችንን የገሀነም የሰቆቃ ኑሮ አደረግብን የምንለው አንዱ የአስተዳደርና የፋይናንስ ኃላፊው ነው፡፡ የስብሰባ መሪ ሆኖ ሳንወድ ያስጨበጭበናል! እሱ በ‘ውሀ ቀጠነ’ ደሞዝ የቆረጠብን ሰዎች ብንሰባሰብ አንድ ዕድር መመስረት እንችላለን፡፡ የዛሬ ዓመት የደሞዜን እሩብ ሲገነድስብኝ “ሆድ ይፍጀው” ብዬ ዝም ብያለሁ፡፡ ዝም ባልልስ ምን እንዳላመጣ!
ጉሮሮውን አሥር ጊዜ ያጠራል፡፡
ታዲያላችሁ…የክብር እንግዳውን ልክ በሆነ ነገር ኦስሎ ላይ የኖቤል ሽልማት ተሸልሞ የተመለሰ ይመስል አናታችን ላይ ይቆልለዋል፡፡ “ውድ ጊዜዎን ሰውተው በዚህ ስብሰባ ላይ በክብር እንግድነት በመገኘትዎ በድርጅቱ ሠራተኞችና በራሴ ስም የከበረ ምስጋናዬን አቀርባለሁ፣...” ይላል፡ እንደፈረደብን አዳራሹን በጭብጨባ እናናጋዋለን፡፡ ወይም… ‘ከስብሰባ የቀረ አስተዳደራዊ እርምጃ ይወሰድበታል’ የሚለው ማስጠንቀቂያ ተሻሽሎ… ‘ከስብሰባ የቀረ፣ ተገኝቶም ያላጨበጨበ’ በሚል ይስተካከል፡፡ ሌላ ጊዜ “በቃሪያ ጥፊ ባጠናገርኩት እንዴት ደስ ይለኝ ነበር!” የምንለውን ሰው በጭብጨባ ትከሻው ላይ የኮከብ መአት እንደረድርለታለን፡፡
ሌላው ደግሞ ሥራ አስኪያጁ “ውድ ጊዜዎን ሰውተው…” ብሎ ነገር ምን ማለት ነው! እሱም እንደ እኛ የመስሪያ ቤቱ ሠራተኛ አይደለም እንዴ!….የእሱ ጊዜ ‘ውድ’ ሲሆን የእኛ ‘ርካሽ’ ነው ማለት ነው! እናማ…ብዙ ጊዜ የክብር እንግዶች ለስብስባው የሚያመጡት የተለየ ግብአት የለም፡፡ ያው “የዛሬውን ስብሰባ ልዩ የሚያደርገው…”
“በተያያዝነው የእድገት ጎዳና…”
“ከመካከለኛ ገቢ አገሮች ጎን ለመሰለፍ…ምናምን የሚሉ ሀረጋትን መደርደር ነው፡፡
የእኛም ሥራ አስኪያጅ ሁሉም በገዛ ድርጅታቸው ‘የክብር እንግዳ’ የሆኑ ሥራ አስኪያጆች የሚያደርጉት ንግግር ይደርጋል፡፡ በአንድ ሺህ አንድ ችግሮች የተተበው መሥሪያ ቤታችን፤ “በእውነቱ የሠራተኛው የሥራ ፍላጎትና ትጋት ለሌሎች ምሳሌ የሚሆን ነው፣” ይላል፡፡ ምነው፣ ስንተዋወቅ! የእኛ ድርጅት ለሌላው ምሳሌ ከሆነ፣ በርከክ ያለች አገር አንደኛዋን በእንትኗ ዘጭ ነው የምትለው፡፡
ሌላ ግራ የሚገባኝ ነገር ደግሞ የዘንድሮ ‘የስብሰባ ቋንቋ!’ “መሥሪያ ቤቱ የእድገት አጀንዳውን ለማስቀጠል ከባለድርሻ አካላት ጋር በጋራ ሆኖ ለስኬት ለማብቃት…” ምናምን የሚሉት ፈሊጥ አለ፡፡ እኔ የምለው…ለምን በሌላ አቀራረብ ሊሉት አይሞክሩም! ለምን ድግምግሞሽ እንደሚያሰለች አውቀው ለየት ለማለት አይሞክሩም! ሁሉም ሰው “ደመቅሽ አበባዬ…” እያለ መዝፈን አለበት እንዴ! አሀ… አንዱ “ደመቅሽ አበባዬ…” ካለ ሌላኛው  “አገሯ ዋርሳ መገና…” ለምን አይልም!
ስብሰባው ዛሬ ሦስተኛ ቀኑ ነበር፡፡ ነገ ያልቃል ተብሏል፡፡ ሥራ አስኪያጁ ትናንት ከ‘በላይ አካል’ ምን እንደተባለ እንጃ ዛሬ ሲያንጫጫን ዋለ፡፡ ስብሰባውን ሲከፍት ለሌሎች ምሳሌ እንደምንሆን ሲነግረን የነበረ ሰው፣ ዛሬ ቀኝ ኋላ ዞሮ የእኛንም ናላ አዞረው፡፡ “በዘንድሮ ዓመት ድርጀቱ የእቅዱን ሀምሳ ሦስት ነጥብ ሰባት በመቶ አሳክቷል፡፡”
አጨበጨብን፣ ልባችን እስኪጠፋ አጨበጨብን። ምን! ለሀምሳ ሦስት በመቶ ጭብጨባ! እንደውም ከእቅዳቸው ከሰማንያ በመቶ በታች የሚያስመዘግቡ ሁሉ አይደለም ማጨብጨብ በሀዘን የአንድ ደቂቃ የህሊና ጸሎት ማድረግ ነበረባቸው፡፡
ከዚያም አለቃችን “በመሆኑም፣ ድርጀቱ በዚህ ዓመት ቦነስ መስጠት አይችልም፡፡”
አናጋነዋ! አዳራሹን በተቃውሞ ጫጫታ አናጋነዋ! አይደለም ሀምሳ ሦስት ለምን ሀያ ሦስት በመቶ አይሆንም… ለምንድነው ቦነሳችንን የሚከለክሉን! ለእሱ በየወሩ መኪና ይለዋወጥለት የለ እንዴ! በዓመት ውስጥ የቢሮው ምንጣፍ ስንቴ ነው የተለወጠው!  ለሥራ ጉዳይ ተብሎ ስንት አገር እየዞረ ሲዝናና ከርሞ የለም እንዴ!  
ይሄ ሁሉ ገንዘብ ከየት መጣ?
ማጉረመረማችን ጠንከር ሲል አለቃችን… “ይህ እኮ የስብሰባ ቦታ ነው፣ መርካቶ አይደለም..” ብሎ ሲቆጣ በአብዛኛው ድምጻችን ቀነሰ፡፡ ጥቂት ሰዎች ግን ማጉረመረማቸውን ቀጠሉ፡፡ ይሄኔ… “እዚህ አዳራሸ ውስጥ ሆነ ብለው ስብሰባውን ለመረበሽ የሚፈልጉ የእነእንትና ተላላኪዎች አሉ…” ሲል የሰፈነው ጸጥታ ትንኝ ብታነጥስ ይሰማ ነበር፡፡ ነገ ስብሰባው ይዘጋል፡፡ ምን በሚባል ሆቴል የእራት ግብዣ አለን ተብሏል፡፡
“ለእኛ ቦነስ የጠፋ ገንዘብ ለግብዣ ከየት መጣ?” ብለን አንቃወምም፡፡“ከእቅዳቸን ሀምሳ ሦስት በመቶ ብቻ አሳካን ተብሎ የምን በገንዘብ ጨዋታ ነው!” አንልም፡፡
“ለእራት የሚወጣው ገንዘብ ለተሰባበሩት ወንበሮችና ጠረጴዛዎች መጠገኛ አይውልም!” አንልም፡፡
እንበላለን፡ እንጠጣለን፡፡ የአለቆቻችንን የዘወትር ኑሮ እኛ በዓመት አንድ ምሽት ብናየው ምናለበት!
ደግሞ…አይ ባለቤቴ እየመጣች ነው፡፡ ይበቃኛል። ምነው የእሷ ፊትም እንደኔው ቀጨመ! ያ አቴዝ ባህርን ደግሞ ምን አድርጓት ይሆን! ልጄ… ስንት የደላው አለ!
እንግዲህ ይኸው ነው… እንሰበሰባለን፣ እናጨበጭባለን ‘እንክት አድርገን’ እራት እንበላለን! ቀን በነገር የምንሞላው ሳያንስ… ማታ በእራት ‘ሆዳችንን የሚሞሉልን’ እንደ ቦነስ እየቆጠሩት ይሆን እንዴ!
እንዲህም ሆኖ የዕለት ማስታወሻው ተገባደደ፡፡ አራት ነጥብ፡፡
ደህና ሰንብቱልኝማ!

 አንዳንድ ዕውነቶች ሲያረጁ ተረት ይመስላሉ፡፡ ትምህርትነታቸው ግን ዘመን - ተሻጋሪ ነው፡፡ ባለፈው ዘመን አንድ ሰው ጐረቤቱን በፖለቲካ ሰውነት (በመንግሥት ወጋኝነት) ይጠረጥረዋል፡፡ በጣም ስለሚፈራውም  ግራ ቀኙን እያጣራ ነው መንገድ የሚሄደው፡፡ ሲወጣ ሲገባ ባየው ቁጥር እየተሸማቀቀ ነው የሚያልፈው፡፡ ጐረቤትዬው ኮስታራ ነው፡፡ ግን ሰው ቀና ብሎ አያይም፡፡ ልጆቹ ከልጆቹ ጋር ሊጫወቱ ሲመጡ፤ “እናንተ ልጆች አርፋችሁ ቤታችሁ ተቀመጡ፡፡
ኋላ ጣጣ ታመጡብኛላችሁ!” እያለ ይቆጣቸዋል፡፡ የልጆቹ ኳስ ጐረቤትየው ግቢ ከገባ፤ ጭንቅ ነው። “ይሄዋ እንደፈራሁት መዘዝ ልትጐትቱብኝ ነው!” ብሎ ያፈጥባቸዋል፡፡ ሚስት ትሄድና ኳሱን ታመጣለች፡፡ ጐረቤታሞቹ ሚስቶች ቡና ይጠራራሉ፡፡
ይሄኛው ባል፤ “ኋላ ነግሬሻለሁ፡፡ አፍሽን ሰብስበሽ ተቀመጪ፤ ምን ፍለጋ ቡና እንደሚጠሩሽ አይታወቅም” እያለ ያስጠነቅቃታል፡፡
 “ኧረ እኛ ምንም የፖለቲካ ነገር አናወራም፡፡ ሞኝ አደረከን እንዴ” ትለዋለች ሚስት፡፡
ባል፤  “አሄሄ አይምሰልሽ! ዛሬ ሣር - ቅጠሉ የሰው አፍ ጠባቂ ነው፡፡ ይቺ ሴትዮ እያዋዛች እንዳታወጣጣሽ!”
ሚስት፤
“ቆይ፤ መጀመሪያ ነገር፤ እኔ ምን አለኝና ነው እምታወጣጣኝ? ምን የደበቅኩት ፖለቲካ አለኝ?”
ባል፤
“እኔ አላውቅልሽም ወዳጄ! ብቻ ጠንቀቅ ነው!” ይላትና ይወጣል፡፡
አንድ ቀን እዚሁ ጐረቤት ጠበል ተጠሩ፡፡
ሚስት ለባሏ፤
“ጠበል ተጠርተናል ጐረቤት፡፡ እንሂድ?”
ባል፤ “አልሄድም” ይላል፡፡
ሚስት፤ “አክብረው ጠርተውሃል ምናለ ብትሄድ” ብላ ትሞግተዋለች፡፡
ባል፤ “አልሄድም ብያለሁ አልሄድም”
“እሺ፤ ለምን ቀረህ ቢሉኝ ምን እመልሳለሁ?”
“ትንሽ አሞት ተኝቷል በያቸው በቃ” አለ ቆጣ ብሎ፡፡
 ሚስት ሄደች፡፡ ባል ቀረ፡፡
አንድ ቀን ታዲያ አጋጣሚ ሆኖ ባል ወደ ሥራ ሊሄድ ውይይት ላይ ተሳፍሯል፡፡ ጫፍ በሩ ጋ ነው የተመቀመጠው፡፡
ጐረቤትየው በዛው ታክሲ ሊሳፈር ይመጣል፡፡ ሳያስበው እግሩን ረግጦት ይገባል፡፡
ይሄኔ ባል ወደ ሰውዬው ዞር አለና፤
“ወንድሜ፤ የከፍተኛ ሊቀመንበር ነህ እንዴ?” ብሎ ይጠይቃል፡፡
“አይደለሁም” ይለዋል ጐረቤትዬው፡፡
“የቀበሌ ሊቀመንበር ነህ?”
“አይደለሁም”
“የአብዮት ጥበቃስ?”
“አይደለሁም”
“እሺ ካድሬ ነህ?”
“አይደለሁም”
“ታዲያ ምናባክ ያራግጥሃል? ና ውጣ ከፈለክ ይዋጣልን!”
“ኧረ ወዳጄ እኔ ምንም ጠብ ውስጥ የምገባ ሰው አይደለሁም፡፡ አሁን የጠየከኝን ሁሉ አንተ ነህ ብዬ ስንት ዘመን ስሰጋና ስፈራህ ኖርኩኮ!” አለው፡፡
*    *    *
ጥርጣሬ ቤቱን የሠራበት ማህበረሰብ ደስተኛና በተስፋ የተሞላ አይሆንም፡፡ መጠራጠርና መፈራራት ባለበት ቦታ ግልጽነት ድርሽ አይልም፡፡ አሜሪካዊው የንግድ ሰው ማክዳግላስ፤ “ጭምት ነብሶችን ትናንሽ ጥርጣሬዎች ለውድቀት ይዳርጓቸዋል፡፡ ጠባብ አመለካከት ያለው፤ ፍርሃት የወረረውና አመንቺ ህብረተሰብ ሽንፈቱን ያረጋገጠ ነው” ይለናል፡፡
“ጠርጥር” የሚል ዘፈን በሚያስደስተው ህብረተሰብ ውስጥ እርግጠኝነትን ፈልጎ ማግኘት ከባድ ነው። ይሄ ሥር ከሰደደ ደግሞ መድሐኒት አይገኝለትም፡፡ “በሽታው ሥር-የሰደደ ከሆነ ሞቱንም መዳኑንም መተንበይ አስተማማኝ አይደለም” ይለናል የግሪኩ የህክምና አባት፤ ሒፖክራተስ፡፡
ጥርጣሬ የበዛበት ማህበረሰብ አገር ለመገንባት አስተማማኝ ኃይል አይሆንም፡፡ መልካም አስተዳደርን ለማበልፀግ ይከብደዋል፡፡ ከእያንዳንዱ ድርጊት ጀርባ አንድ ጥርጣሬ እየኖረን ወደፊት መራመድ አይቻልም፡፡ ግልፅነት ከሌለ ዴሞክራሲ ደብዛው ይጠፋል፡፡ ኢፍትሐዊነት ይነግሣል፡፡ ሙስና ያጥጣል። ሚስጥራዊነት ያይላል፡፡ በመጨረሻም፤ “በልቼ ልሙት!” መፈክር ይሆናል!! በሀገራችን ታሪክን እንኳ በጥርጣሬ ማየት የተለመደ ሆኗል፡፡ የተዘመረላቸው አሉ፡፡ ያልተዘመረላቸው አሉ፡፡ እየተዘመረላቸው የማይታወቁ አሉ፡፡ ለምሳሌ የሰላሌው ጀግና አቢቹ፡፡ አዶልፍ ፓርለሳክ እንደፃፈው፤ “ይቺ አንድ ፍሬ ደጃዝማች! ከኛ በላይ ጀብዱ እየሰራች መሆኑን እንሰማለን!” አሉ አሉ ጃንሆይ፤ ስለ አቢቹ ሲናገሩ፡፡
“አቢቹ ነጋ ነጋ …. ቆሬን ሲወራኒኒ ለቺቱ ነጋ ነጋ …… አምቱን ሲላሊኒ”
“አቢቹ ሰላም ሰላም አቢቹ እሾህ አይውጋህ አቢቹ ክፉ አይይህ አቢቹ ዐይን አያይህ” እንደማለት ነው፡፡
 ይህ የተዘፈነው ለአቢቹ ነው፡፡ ዛሬም ይዘፈናል፡፡ ግን አቢቹን ሰው አያውቀውም “ዛሬ አዝማሪው ሳይቀር ስለራሶች ጀግንነትና ስለንጉሠ ነገሥቱ ታላቅነት፤ ማንጎራጎሩን ርግፍ አድርጎ ትቶታል…” ይለናል፤ ያው ፀሐፊ፡፡ ልብ ያለው ግን የለም፡፡ ምናልባት የነገሥታቱ
ጀግኖች እንዲወደሱ ሆን ተብሎም ታሪክ ተጋርዶ ይሆናል፡፡ ይሄም ያው ጥርጣሬ ነው፡፡
ስለ መሪዎች ትተን ስለ ህዝብ ወይም ስለ ህዝባዊ ጀግኖች እንዘምር ነው ነገሩ፡፡ ያልነቃ ህብረተረሰብ ተጠራጣሪነቱ ያይላል፡፡ በዕውቀትና በትምህርት ያልዳበረ ማህበረሰብ ተጠራጣሪነቱ ያይላል። የማይተማመኑ ፖለቲከኞች ያሉትና የሚመሩት ማህበረሰብ ተጠራጣሪነቱ ያይላል፡፡ በዚህ ላይ ከፖለቲካው ሥርዓት ጋር አለመግባባት ከተጨመረበት ጨርሶ ማበድ ነው፡፡ “ማሰብም ሊገታ ይችላል” እንዳለው ነው ፤ቲዮዶር አዶርኖ-የጀርመኑ ፈላስፋ፡፡ “አንበሳና የበግ ግልገል አብረው ሊተኙ ይችላሉ፡፡ ችግሩ የበግ ግልገሏ እንቅልፍ አይኖራትም” ይላሉ ፀሐፍት፡፡ እንደተጠራጠረች መንጋቱ ነው ማለታቸው ነው፡፡
ከጥርጣሬ የምንወጣው ዕውነቱን በማወቅ ነው፡፡ መረጃዎች በቀጥታ ሲደርሱ ነው፡፡ መረጃ ሲጠራ ዕውነት ማየት ይጀመራል፡፡ ካልጠራ ጎሾ ያጎሸናል፡፡ የተማሩ ያስተምሩ፡፡ የነቁ ያንቁ፡፡ ያወቁ ያሳውቁ፡፡ “አውራ ዶሮ ራሱ ሳይነቃ ሌላውን አይቀሰቅስም” የሚባለውን ልብ እንበል፡፡

   ጥናቶች ምን ይላሉ?
   የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (EBC) ተጠሪነቱ ለህዝብ እንደራሴዎች ነው፡፡ ነገር ግን ኮርፖሬሽኑ የህዝብ ሚዲያ አልሆነም የሚሉ ትችቶችና ቅሬታዎች ሲቀርቡበት ቆይቷል፡፡ ኢህአዴግ በ10ኛው ጠቅላላ ጉባኤ ማጠናቀቂያ ላይ ባወጣው መግለጫ፤ ኢቢሲን ጨምሮ የህዝብ መገናኛ ብዙሃን ለህዝብ ወገንተኛ መሆን እንዳልቻሉ አመልክቶ
ነበር፡፡ ከሰሞኑም ኮርፖሬሽኑ ያሉበትን ችግሮች የሚቀርፍ ስር ነቀል ለውጥ እንዲያደርግ በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ታዟል፡፡ ይህን መነሻ በማድረግ የኮርፖሬሽኑ ዋነኛ ችግሮች ምንድን ናቸው? ለምን የህዝብ አመኔታ ማግኘት ተሳነው? እንዴትስ ተሻሽሎ የህዝብን ቀልብ መግዛት ይችላል? በሚሉ ጥያቄዎች ዙሪያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፤ የተለያዩ የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች የጋዜጠኝነትና ኮሚዩኒኬሽን መምህራንን አነጋግሮ አስተያየታቸውን
እንደሚከተለው አጠናቅሯል፡፡
    
              “የአመለካከት ለውጥ ካልመጣ በቀር ሚዲያው ብቻ አይቀየርም”
               እንግዳወርቅ ታደሰ (በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነትና ኮሚዩኒኬሽን መምህር)

     ኢቢሲ እድሜ ጠገብና ግዙፍ ተቋም በመሆኑ በአሁን ውቅት በዘርፉ ጥናት የሚያደርጉ ምሁራንን ትኩረት የሳበ ሆኗል፡፡ በርካቶች ጥናት ሰርተውበታል፡፡ እኔም ከነዚህ ጥናቶች ተነስቼ ነው አስተያየቶችን የምሰጠው፡፡
በአጠቃላይ ይህ የሚዲያ ነፃነት ችግር የአፍሪካ ሀገራት ችግር ነው፡፡ ደግሞ ከህትመቱ ይልቅ ብሮድካስት ሚዲያው ላይ ችግሩ ይጠነክራል። ጥናቶች ይሄን ያሳያሉ፡፡ የብሮድካስት ሚዲያ ያልተማረውን የህብረተሰብ ክፍልንም ስለሚያዳርሱና ለጠንካራ የሀሳብ መንሸራሸሪያነት ምቹ ስለሆኑ መንግስታት የበለጠ ቁጥጥርና ክትትል ያደርጉባቸዋል፡፡ የኛም ሀገር ሁኔታ እንዲሁ ነው፡፡ ለምሳሌ የሬዲዮን ጉዳይ ብቻ ነጥለን ብንመለከተው፣ የአፍሪካ መሪዎች ሬዲዮንን በእጅጉ ይፈልጉታል፤ ስለዚህ ለማንም አሳልፈው መስጠት አይፈልጉም። ይሄን ባህሪ ደግሞ የወረሱት ከቅኝ ገዥዎቻቸው ነው፡፡ እኛ ሀገር ጣሊያን 5 ዓመት በቆየበት የወረራ ጊዜ እንኳን ይህቺን ልምድ ነው ትቶ ያለፈው፡፡ ሳንሱር ማድረግና ሬዲዮውን ለፕሮፓጋንዳ ጥቅም ማዋል የመሳሰሉ ልምዶችን ትቶልን ነው ያለፈው፡፡
የሀገራቱ መንግስታትም ሚዲያን የሚያስፋፉት ከራሳቸው ሁነቶች ጋር በማስተሳሰር ነበር፡፡ ለምሳሌ ቴሌቪዥን የተጀመረው ከአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምስረታ ጋር በተገናኘ ነበር፡፡ ከፖለቲካ ጉዳዮች ጋር ለራሳቸው ጥቅም ሲሉ ነበር እንጂ በእርግጥም ህዝባችን ሚዲያ ያስፈልገዋል ከሚል መነሻ አልነበረም፡፡ ይሄ ሁኔታ እያደገ መጥቶ ነው አሁን ያለው ችግር ላይ የጣለን፡፡ ጥናቶችም የሚያሳዩት ይሄንን ነው፡፡ አሁንም ጡንቻና አቅም ያለው አካል ሚዲያውን ለመሳሪያነት ይጠቀመዋል። የፕሮፓጋንዳና ፖሊሲ ስርፀት የሚሰራው ሚዲያውን አንቆ በመያዝ ነው፡፡
አንድ ኖርዬአዊ አቢሲ ላይ ያጠናው ጥናት አለ። በጥናቱ ላይ ሌሎች የመንግስት መገናኛ ብዙኃንም ተካተውበታል፡፡ ግለሠቡ በዚህ ጥናቱ፤ ላይቤሪያና ኢትዮጵያ ቅኝ አለመገዛታቸው መልካም አጋጣሚ እንደፈጠረላቸው ይጠቅሳል፡፡ ሚዲያዎቻቸው የሃገር ውስጥ ጉዳዮችን በስፋት እንደሚዘግቡ ያስቀምጣል፡፡ ብዙዎቹ የአፍሪካ ሃገሮች ግን የትኩረት አቅጣጫቸው ከውጭ ሚዲያዎች የሚቀዳ ነው ይላል፡፡ ግን ይሄም ቢሆን ሚዲያው ነፃ እንዳልሆነ ይጠቁማል፡፡ ከፍተኛ ክፍተት ያለውም አመራሩ ላይ እንደሆነ ይጠቅሳል፡፡ የፖለቲካው ጣልቃ ገብነት እንዳለ ይገልፃል፡፡ እኔም ራሴ ጥናቴን የሰራሁት በዚህ ጉዳይ ላይ ነበር፡፡ እንዴት ነው ነፃነት አላችሁ ወይ ብዬ ስጠይቅ፣ “ወቅቱ ክፉ ካልሆነ ነፃ ነን፤ ጠንካራ  ጉዳይ ከተነሣ ግን ቀጥተኛ ጣልቃ ገብነት ይኖራል” የሚል መልስ ነው ያገኘሁት፡፡
እነዚህ ሁኔታዎች ባሉበት እንዴት ነው ‹‹ሪፎርም›› ይደረግ የሚባለው? አስቸጋሪ ነው። ብዙዎቹ አመራሮች የሙያ ብቃትና ችሎታ ያንሣቸዋል። ታማኝ በመሆናቸው ብቻ ወደ አመራርነት ስለሚመጡ ብዙም ለውጥ አያመጡም፡፡ ኢቢሲ ሙያን የመረዳት ውስንነትና በራስ የመተማመን ችግር ያለበት አመራር እንዳለው ጥናቶች በግልፅ አስቀምጠዋል፡፡ አመራሩ ከገዥው መደብ ጋር የተገናኘ ነው፡፡ ዋናው ችግርም ይሄ ነው፡፡
ጋዜጠኞቹን ስናይ ሁለት መልክ አላቸው፡፡ አንዳንዶቹ ለሙያው ብቻ ይተጋሉ፡፡ ሌሎች ደግሞ የዚህ ባህሪ የላቸውም፡፡ በሌላ በኩል በየክፍሉ  የተመደቡ ኤዲተሮች /አዘጋጆች/ አመዳደብም ተፅዕኖ እንደሚያደርግ ግልፅ ነው፡፡ አዘጋጅ ሆነው የሚቀመጡ ሰዎች ብቃት ወሳኝነት አለው፡፡
እኔ አጠቃላይ የአመለካከት ለውጥ ካልመጣ በስተቀር ሚዲያው ብቻ ይቀየራል የሚል እምነት የለኝም፡፡ እኔ ለማስተምራቸው ልጆች የምነግረው ወገንተኛ እንዳይሆኑና ሙያውን እንዲያከብሩ ነው፡፡ ነገር ግን ችግሩ የኛ ጋዜጠኞች መጀመሪያ በኢኮኖሚ አቅማቸው በሁለት እግራቸው መቆም ይፈልጋሉ፡፡

------------

                     “የኢቢሲ ጋዜጠኞች ነፃነታቸውን ማስከበር አለባቸው”
                       ሄኖክ ንጉሴ (በዲላ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነትና ኮሚዩኒኬሽን መምህር

      ኢቢሲ የጋዜጠኝነትን ንድፈ ሀሳብ ከመከተል አኳያ ብዙ ችግር አለበት፡፡ በ2008 እ.ኤ.አ የመንግስት ሚዲያ ልማታዊ ጋዜጠኝነት እንደሚከተል ታውጆ ነበር፡፡ ኢቢሲም ይሄን እንዲከተል ነው የተባለው። ግን ከልማት ጋዜጠኝነት አተገባበሩ ጋር በተያያዘ ብዙ ጉድለትና ክፍተት አለበት፡፡ አንደኛ የልማት ጋዜጠኝነት በተለያዩ ሀገራት የተለያየ አተረጓጎምና አተገባበር ነው ያለው፤ ቁርጥ ያለ መርህ የለውም። መንግስታት በራሳቸው አካሄድ እንዲተረጉሙት መንገድ የሚከፍት ነው፡፡
ለምሳሌ የፊሊፒንስ መንግስት የልማታዊ ጋዜጠኝነትን በራሱ የፖለቲካ አስተሳሰብ በመተርጎም፣ ያንን ለጋዜጠኞች በመስጠት እንዲመሩበት ያደርጋል። የኛም ሀገር እንዲህ ያለ ባህሪ ነው ያለው፡፡ ይሄ ደግሞ ለባለስልጣናት ጣልቃ ገብነት በር ይከፍታል፡፡ ጋዜጠኛውን ነፃነት የማሳጣት ነገሮች እንዲበራከቱ ያደርጋል፡፡ ኢቢሲም የዚህ ችግር ተጠቂ ሆኖ ነው የምናየው፡፡ ልማታዊ ጋዜጠኝነት ለእንደዚህ ያለ ጣልቃ ገብነት የተጋለጠ ነው፡፡
ኢቢሲ ለፓርላማው በሰጠው ማብራሪያ ጣልቃ እየተገባብኝ ነው ማለቱም ከዚህ አንፃር የሚፈጠር ነው፡፡ የልማታዊ ጋዜጠኝነት ፅንሰ ሀሳብን ለመተግበር ከተፈለገ በራስ ብቻ ከመተርጎም ይልቅ ምሁራንን በሚገባ አነጋግሮ፣ ጋዜጠኞችንም አማክሮና በሚገባ አሰልጥኖ ወደ አሰራር ማምጣት ቢቻል  ውጤታማ ለመሆን ይቻል ነበር፡፡
ለኔ በዋናነት በኢቢሲ የሚታየኝ ችግር የልማታዊ ጋዜጠኝነት ፅንሰ ሀሳብን አዛብቶ ተርጉሞ የመተግበር ነገር ነው፡፡ እኛ በቅርብ ጊዜ በመንግስት ሚዲያዎች ላይ ያከናወንናቸው ጥናቶች ሳይቀሩ የመንግስት ባለስልጣናት ጣልቃ ገብነት እንዳለ ያረጋግጣሉ። ጋዜጠኛው ነፃ እንዲሆን አልተደረገም። ነፃነት ደግሞ ለጋዜጠኛ ዋናው መርህ ነው፡፡ ከዚህ አንፃር ይህ አሁን እየተተገበረ ነው የሚባለው የልማታዊ ጋዜጠኝነት ሞዴል በድጋሚ ለውይይት  ሊቀርብ ይገባል፡፡
የልማታዊ ጋዜጠኝነት መርህ የምርመራ ጋዜጠኝነትን ያቀጭጫል የሚሉ ክርክሮች አሉ። በእርግጥም ይሄን በኛ ሃገርም እየተመለከተነው ነው፡፡ አንድ ባለስልጣን በዚህ ደረጃ ጣልቃ ገብነት ካለው የምርመር ጋዜጠኝነትን ለመስራት አስቸጋሪ ነው ማለት ነው፡፡
ኢቢሲ ውስጥ ባለስልጣናት ጣልቃ እንዳይገቡ የሚገድብ ህግ መኖር አለበት፡፡ ሌላው አቢሲ የህዝብን ፍላጎት አዳምጦ የመዘገብ ባህል ማዳበር አለበት፡፡ ያን ጊዜ ነው ኢቢሲ የህዝብ ነው የሚባለው፡፡ ግጭት ሲኖር የመንግስት ጥቅም እንጂ የህዝብ ጥቅም ሲንፀባረቅበት አይታይም። መነሻቸው የመንግስት ምላሽ ነው እንጂ የህዝብ ቅሬታ አይደለም፡፡ ይሄ ሁሉ የሚስተካከለውና ጣቢያው በተግባር የህዝብ የሚሆነው ነፃነቱን ሲያረጋግጥ ነው፡፡
በሌላ በኩል የኢቢሲ ጋዜጠኞች ራሳቸውን ከባለስልጣናት ጣልቃ ገብነትም ሆነ ከሌሎች አካላት ለመከላከል የሙያ ማህበር ሊመሰርቱ ይገባል። በአጠቃላይ የሙያው ማህበራት መጠናከርና የራሳቸውን ነፃነት ማስከበር አለባቸው። የጋዜጠኝነት ትልቁ መርህ ነፃነት ነው፡፡ ነፃነትን የምታመጣው በጋራ ሆኖ በመንቀሳቀስ ነው፡፡
አንድ በቅርቡ የተጠና ጥናት፤ በመንግስት ሚዲያዎች ያሉ ጋዜጠኞች የፓርቲ አባላት እንደሆኑና ሙያዊ ጉዳዮችን ሲነጋገሩ፤ ከፓርቲያቸው አሸማቃቂ ትችቶች እንደሚደርስባቸው ያትታል፡፡ ስለዚህ ለሙያው ሳይሆን ለድርጅታዊ መርህ ታማኝ መሆንና እንጀራዬን አጣለሁ ብሎ የመስጋት ችግር እንዳለ ያመላክታል፡፡ ስለዚህ የሙያ ማህበራት መቋቋምና መጠናከር አለባቸው፡፡ ከጣልቃ ገብነትም ራስን ለመከላከል አንዱ መሳሪያ ነው፡፡

---------------

                   “በህዝብ ተአማኒነት ያጣ ሚዲያ እንደሌለ ነው የሚቆጠረው”
                   በለው አንለይ (በሐዋሣ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነትና ኮሚዩኒኬሽን መምህር)

      በአንድ ሀገር ውስጥ የዲሞክራሲ ስርአት ለመገንባት፤ ተጠያቂነትን ለማስፈን፣ ሙስናን ለመከላከል፣ የመገናኛ ብዙኃን ሚና በጣም ከፍተኛ ነው፡፡ በሀገራችን በመንግሥት ስር በርካታ መገናኛ ብዙኃን አሉ፡፡ እነዚህ መገናኛ ብዙኃን ከፓርቲ ፍላጎት ነፃ ሆነው እንዲሰሩ ቢደረግ የተጠቀሱትን ህዝባዊ አገልግሎቶች መስጠት ይችላሉ፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ ኢቢሲ ህዝብ የሚፈልገውን ማድረግ አልቻለም፡፡ “የብዝኃነትና የህዳሴ ድምፅ” የሚል መሪ ቃል ባለቤት ቢሆንም ተግባሩ መሪ ቃሉን በትክክል የሚገልፅ አይመስለኝም፡፡
የህገ መንግስቱ አንቀፅ 29 ንፁስ አንቀፅ 5፤ የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን የተለያዩ አስተያየቶችንና ሀሳቦችን ለማስተናገድ በሚያስችል ሁኔታ እንዲሰራ ይደረጋል ነው የሚለው፡፡ እንግዲህ ኢቢሲም የተመሰረተበት አላማ ይሄው ነው፡፡ በህገ መንግስቱ ኢቢሲ የህዝብ መሆኑ በግልፅ ተቀምጧል። ጥያቄው እንደ ህዝብ መገናኛ ብዙኃንነቱ የህዝብ ሆኗል ወይ የሚለው ነው። እንደ መሪ ቃሉ የብዝኃነት ድምፅ መሆን ችሏል ወይ? ጣቢያው የህዝብ ፍላጎቶችን እያንፀባረቀ አይደለም፡፡ ለዚህም ብዙ ማሳያዎችን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ለምሳሌ በመንግሥት እንደሚነገረው፤ ሙስና በከፍተኛ ደረጃ ተስፋፍቷል፡፡ እንዲህ ያሉ ጉዳዮችን ተከታትሎ ለህዝብ ማጋለጥ ያለበት ደግሞ የህዝብ የተባለው ኢቢሲ ነው፡፡ እኔ ከተሳሳትኩ እታረማለሁ፤ እስካሁን ኢቢሲ አጋልጦት የታሰረ ወይም ከስልጣኑ የተባረረ ባለስልጣን አናውቅም፡፡ ምናልባት መንግሥት ራሱ ባለሥልጣን ካሰረ በኋላ ነው ከስር ከስር የሚዘግበው እንጂ አስቀድሞ አጋልጦ ሲያቀርብ አላየሁም፡፡ የምርመራ ጋዜጠኝነት ሙከራ ሊኖር ይችላል እንጂ በተግባር በሚገባ ሲውል አናይም፡፡ ይሄ የሚያሳየው የፓርቲ ወገንተኝነት እንደሚያጠቃው ነው፡፡ ይህ ደግሞ የህዝብ ተአማኒነትን ያሳጣዋል፡፡ እንዲህ ያለ ተአማኒነትን ያጣ ሚዲያ ደግሞ እንደሌለ ነው የሚቆጠረው፡፡ ለአንድ ሚዲያ ተአማኒነትን ከማጣት በላይ የሚጎዳው ነገር የለም፡፡
አሁን ኢቢሲ እንደሚመራበት ጋዜጠኝነት፣ ልማታዊ ጋዜጠኝነት ብቻ ነው ብልን ከተረጎምነው ትልቅ አደጋ አለው፡፡ ይሄ ኢቢሲ ከተመሰረተበት የህገ መንግስቱ አላማ ጋርም ይጋጫል፡፡ ጋዜጠኝነት ልማታዊ ጋዜጠኝነት ብቻ አይደለም፡፡ ልማታዊ ጋዜጠኝነት ቁንፅል ነው፡፡ በኛ ሃገር ልማታዊ ጋዜጠኝነት ለመንግስት እንዲጠቅም ተደርጎ ነው የተተረጎመው፡፡ ጋዜጠኝነት ማለት ሃሳብን መግለፅ ማለት ነው፡፡ ሃሳብን መግለፅ ደግሞ ስለ ልማት ብቻ ማውራት አይደለም፡፡ ይሄ የሚዲያን ታሪካዊ ሚና ወደ ጎን ገሸሽ የሚያደርግ ነው፡፡
ኢቢሲ የህዝብ ሚዲያ እንዲሆን ከተፈለገ ብዙ መድከም ሳያስፈልግ ህገ መንግስቱ ላይ ያለውን ነገር ወደ ተግባር ማውረድ በቂ ነው፡፡ ብዝኃነት ስንል የአስተሳሰብ ብዝኃነትም ስለሆነ የተቃዋሚ ድምፆች እንዲሰሙ ማድረግ የመሳሰሉትን በሙሉ ሽፋን መስጠት አለበት፡፡ይህን ለማድረግ ይሄ ሚዲያ ዕውቀት ባላቸው ሰዎች መመራት አለበት፡፡ ሁለተኛ በፓርቲና በመንግስት መካከል ያለው ልዩነት በግልፅ መታወቅ መቻል አለበት፡፡
ፓርቲ የራሱን ሚዲያ መመስረት መቻል አለበት። መገናኛ ብዙኃንን የፓርቲ፣ የህዝብ/የመንግስት ወይም ነፃ ሚዲያ ብለን በሶስት ልንከፍላቸው እንችላለን፡፡ መንግስታዊ/ ህዝባዊ ሚዲያ የምንለው ሙሉ ነፃነት ሊኖረው ይችላል፡፡ የፓርቲ ሚዲያ ግን የፓርቲው አቋም ብቻ የሚንፀባረቅበት ነው የሚሆነው፡፡ ከፓርቲ አመለካከት ውጪ ከሆነ ፓርቲው የራሱን እርምጃ ሊወስድ ይችላል፡፡ ከዚህ አንፃር የኛ ሃገር ችግር የፓርቲና የመንግስት/ህዝብ ሚዲያ ልዩነት ጠርቶ አለመቀመጡ ነው፡፡ ይሄ መስመር ከጠራ ብቻ ነው ኢቢሲ ትክክለኛ የህዝብ ሚዲያ መሆን የሚችለው፡፡

-------------

                “የጋዜጠኞች ገለልተኛ አለመሆን ትልቁ ችግር ነው”
                አስማማው አዲስ (በጎንደር ዩኒቨርሲቲ የቋንቋና ጋዜጠኝነት መምህር)

      በቅርቡ የምሁራንንና የሚዲያዎች ግንኙነት ላይ ያተኮረ አንድ ጥናትእያጠናሁ በነበረበት ወቅት ኢቢሲ ተአማኒነቱን ማጣቱን ከጥናቴ ውጤት ተገንዝቤአለሁ፡፡ ለጣቢያው ተአማኒ አለመሆን ዋናው መንስኤ ደግሞ የጋዜጠኞች ከመንግስታዊ አካል ተፅዕኖ ነፃ አለመሆን ነው፡፡ ሁለተኛው ሚዲያው የሚመራበት ፍልስፍና ችግር ነው። ልማታዊ ጋዜጠኝነት ነው የሚለው፡፡ ግን ይሄ በትክክለኛው ትርጉም አልተያዘም፡፡ በመሰረቱ ልማታዊ ጋዜጠኝነት በሶስት ይከፈላል፡፡ አንደኛው Pro-process የሚባለው ነው፡፡ ይሄ ለሂደቱ ድጋፍ ማድረግ የሚል መርህን ያነገበ ነው፡፡ ከመንግስት ጋር በመሆን ለመንግስት ስትራቴጂዎች አስተዋፅኦ ማድረግ የሚል ነው፡፡  
መንግስት የሚሰራውን ከስር ከስር እየተከታተሉ መዘገብ ማለት ነው፡፡ ሌላኛው የልማታዊ ጋዜጠኝነት መርህ Pro-participation የሚባለው ነው፡፡ ይሄ ዜጎች መብታቸው እንዲከበር አተኩሮ የሚሰራ መርህ ነው፡፡ ሌላኛውና ሶስተኛው Pro-government የሚባለው ነው፡፡ ይሄኛው በመንግስት ፖሊሲ ጥላዎች ስር ሆኖ የመንግስትን ፖሊሲዎች ማስፈፀም ነው፡፡ የኛ ሀገር ሚዲያ በዚህ ስር ያለ ይመስለኛል፡፡ ይሄ በራሱ የጣቢያው ችግር ነው፡፡
በሌላ በኩል የጣቢያው ፕሮግራም ይዘቱ አሰልቺ ነው፡፡ ተደጋጋሚና አታካች ናቸው፡፡ ጣቢያው የጋዜጠኞች የእውቀትና የክህሎት ችግር አለበት፡፡ ይሄን ነው ጥናቴ ያመላከተኝ፡፡ ለዚህ ነው ከምሁራን ጋር እንዳይሰራ የሆነውም፡፡ በጣቢያው ላይ ያለበቂ ጥናትና ምርምር የሚቀርቡ ፕሮግራሞችም በርካታ መሆናቸው በጥናቴ ተመላክቷል፡፡ ይሄ ነው በህዝብ ዘንድ ለትችት የሚዳርገው፡፡
በጋዜጠኝነት ውስጥ ቀላሉ መርህ “እውነትን መናገር” የሚለው ነው፡፡ ይሄ በኛ ሀገር ገና አልመጣም። የባለስልጣናት ጉዳይ እንጂ ህዝብ ጋ ያለ እውነትን ለማግኘት ጥረት አይደረግም፤ የህዝብ እውነታም ሲቀርብ አይስተዋልም። ሌላው የፕሮፓጋንዳ ተጠቂ መሆን ወይም ለፕሮፓጋንዳ ማስተላለፊያነት የተመቻቸ መሆኑ ነው፡፡ ገለልተኝነት ማጣት ሌላው ትልቁ ችግር ነው፡፡ ጋዜጠኞች ከባለስልጣናት ራሳቸውን አለማግለላቸው ይባስ ብሎ ከነሱ ጋር እጅና ጓንት መሆን ይታያል፡፡ ኃይልና ስልጣን ላላቸው ሰዎች ተገዢ የመሆን ነገር ይታያል፡፡ ለህሊና ተገዥ ያለመሆን ችግር በስፋት እንደሚታይ በጥናቱ ተመልክቷል፡፡ አንዳንዴ ባልተፃፉ የጋዜጠኝነት መርህና ህግ ሁሉ ነው የሚንቀሳቀሱት፡፡
ጣቢያው ልማታዊ ጋዜጠኝነት እከተላለሁ ካለ፣ በሚገባ መርሁን መተግባር አለበት፡፡ ለምሳሌ የህዳሴው ግድብ ያለበትን ደረጃ ለመግለፅ የሚሰራ ዘገባ፤ ከጊዜው የዘገየ ከሆነ ለምን ዘገየ ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡
ጣቢያው በአጠቃላይ መሻሻል ከፈለገ፣ ጋዜጠኞች ሙሉ ነፃነት ማግኘት አለባቸው። ተቋሙም ነፃ ሆኖ መንቀሳቀስ መቻል አለበት፡፡

--------------

                     ‹‹ኢቢሲ አለቃው ህዝብ ነው››
                      ተሻገር ሽፈራው (በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነትና ኮሚዩኒኬሽን መምህር)

     የመንግስት መገናኛ ብዙሃን የሚመሩት ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች በተወጣጡ የቦርድ አባላት ነው፡፡ የቦርድ አባላቱ ከሚዲያዎቹ ህዝቡ ፍትሃዊ የሆነ ዘገባ እንዲቀርብለት፣ በመንግስትና በህዝብ መካከል ድልድይ ሆኖ እንዲያገለግል፣ የዲሞክራሲ ባህልን እንዲያሣድግ የመሣሰሉ ጉዳዮችን የመከታተል ሃላፊነት አለባቸው፡፡
ይሄ በማቋቋሚያ ደንቦችም ተደንግጓል፡፡ ሚዲያዎቹ የህዝብና ሃብት መሆናቸው፣ እያንዳንዱ ጉዳይ ላይ ህዝብን አሳታፊ እንዲሆን በድንጋጌዎቹ ተቀምጠዋል፡፡ አሁን ዋናው ችግር እየታየ ያለው ይሄን ወደ ተግባር መለወጡ ላይ ነው፡፡
በተግባርና በሙያ መርሀ መካከል ያለውን ክፍትት መሙላት ከተቻለና መርሆዎቹ መሬት ከወረዱ እነዚህ የመንግስት መገናኛ ብዙሃን የሚጠበቅባቸውን ሊሠሩ ይችላሉ፡፡ ትልቁ ችግር ይሄ እየተፈፀመ አለመሆኑ ነው፡፡ለምሳሌ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል እንደተጨባጭ ሁኔታ ትክክለኛና ፍትሃዊ የዜና ሽፋን ማግኘት መብቱ ቢሆንም በተግባር እየታየ ያለው ከተማ ተኮር ወይም ባለስልጣናት ላይ የሚያተኩር ዘገባ ነው የሚቀርበው፡፡ ህዝብ ስለእያንዳንዱ ነገር ማወቅ አለበት፤ ይሄ እየሆነ አይደለም፡፡
በመንግስትና በህዝብ መካከል ድልድይ መሆን አለበት ስንል የውይይት መድረክ ያዘጋጃል፡፡ በዚህም ሃሣብ ከላይ ወደታች ብቻ ሳይሆን ከታችም ወደ ላይ ይወጣል ማለት ነው፡፡ ይሄ እስካሁን አልተሠራም። አሁን ግልፅ ልዩነት ያለው በአዋጆቹና በተግባር መካከል ነው፡፡ ያንን ማቀራረብ ከተቻለ ነው የሚፈለገው ለውጥ የሚመጣው፡፡
ኢቢሲ ለህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ተጠሪ ሲሆን አለቃው ህዝብ ነው ማለት ነው፡፡ ነገር ግን በተግባር ስናየው የመንግስት ቢሮዎች ውስጥ ያሉ ባለስልጣናት ከፍተኛ ተፅዕኖ ይታይባቸዋል። ከነዚያ መስሪያ ቤቶች የሚገኙ መረጃዎች ናቸው እንጂ በሚዲያው በኩል ከፍተኛ ግምት ሊሠጣቸው የሚገባው፡፡ እነሱን የሚገዳደር ነገር መምጣት የለበትም፡፡ ኢቢሲ ከመንግስት አስፈፃሚ መሥሪያ ቤቶች ተፅዕኖ ወጪ መሆን አለበት፡፡ አለቃው ህዝብ ነው፤ ስለዚህ ህዝብ ነው የሚቆጣጠረው እንጂ አስፈፃሚ አካሉ አይደለም፡፡
ዋናው ኢቢሲ እንዲሻሻል ከተፈለገ፤ ሙያዊ ነፃነቱን፣ የጣቢያውን ኤዲቶሪያል ፖሊሲ ማክበር ነው፡፡ ኤዲተሮች/አዘጋጆች ራሳቸውን ከተፅዕኖ ነፃ አውጥተው፣ የተሠጣቸውን የሙያ ነፃነት መርህ በድፍረት ከተገበሩ ነው ሚዲያው የህዝብ መሆን የሚችለው፡፡

     የኢቢሲው ጋዜጠኛ ብሩክ እንዳለ ከድምጻዊ ቴዎድሮስ ካሳሁን /ቴዲ አፍሮ/ ጋር ካደረገውና ባለፈው ሳምንት በእሁድ መዝናኛ ፕሮግራም ላይ ይቀርባል ተብሎ ከተዋወቀ በኋላ በድርጅቱ የስራ ሃላፊዎች ውሳኔ ሳይተላለፍ ቀርቷል ከተባለው ቃለመጠይቅ ጋር በተያያዘ በፈቃዱ ስራውን መልቀቁን አስታወቀ፡፡
ላለፉት 4 አመታት በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ያገለገለው ጋዜጠኛ ብሩክ፣ ከድምጻዊ ቴዲ አፍሮ ጋር በስራዎቹና በግል ህይወቱ ዙሪያ ያደረገው ቃለ መጠይቅ እንዳይተላለፍ መታገዱ ከፈጠረው ውዝግብ ጋር በተያያዘ በተቋሙ ውስጥ ለመቀጠል የሚያስችል ሞራላዊ አቅም እንደሌለው በመጥቀስ፣ ስራውን በገዛ ፈቃዱ ለመልቀቅ መወሰኑን ትናንት ለድርጅቱ በጻፈው ደብዳቤ ገልጧል፡፡
በጉጉት ሲጠበቅ የነበረው የቴዲ አፍሮ ቃለመጠይቅ በተያዘለት ፕሮግራም አለመተላለፉ ብዙዎችን ያሳዘነና ያስቆጣ ጉዳይ ሲሆን፣ ጋዜጠኛውም ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ ከህሊናው ጋር እየታገለ ስራውን መቀጠል ስለማይችል፣ በገዛ ፈቃዱ ስራውን ለመልቀቅ መወሰኑን በፌስቡክ ገጹ ላይ ትናንት ባወጣው መረጃ አስታውቋል፡፡
“ጉዳዩ አንድን የኪነጥበብ ሰው የማቅረብና ያለማቅረብ ጉዳይ ብቻ አይደለም፤ የጋዜጠኝነት ልዕልናንም የሚጋፋ ጭምር እንጂ፤ ብዙዎች መስዋዕትነት የከፈሉለትን ሙያ ክብር ለመስጠት ስል ስራዬን የመልቀቅ ውሳኔ ላይ ደርሻለሁ” ብሏል፤ ጋዜጠኛው በዚሁ መረጃው፡፡
ከስራ ለመልቀቅ ሰበብ የሆነውን የቴዲ አፍሮ ቃለመጠይቅ በተመለከተ በቅርቡ ዝርዝር መረጃ እንደሚሰጥ የጠቆመው ጋዜጠኛው፤ ላለፉት አራት አመታት በድርጅቱ በነበረው የስራ ቆይታ መልካም ጊዜ ማሳለፉን በማስታወስ፣ ለድርጅቱ ሰራተኞችና በተለያዩ መንገዶች ከጎኑ ለነበሩ ሁሉ ምስጋናውን አቅርቧል፡፡
ጋዜጠኛው በቴዲ አፍሮ መኖሪያ ቤት በመገኘት ከድምጻዊው ጋር ያደረገው ቃለ መጠይቅ ባለፈው እሁድ በመዝናኛ ፕሮግራም ይተላለፋል የሚለው መረጃ በማህበራዊ ድረገጾች በስፋት ተሰራጭቶ ብዙዎች ዕለቱን በጉጉት እንዲጠብቁት ቢያደርግም፣ ቃለ መጠይቁ እንዳይተላለፍ መወሰኑን የሚገልጽ ሌላ መረጃ መውጣቱን ተከትሎ ደግሞ ጉዳዩ በድምጻዊው አድናቂዎች ዘንድ በማህበራዊ ድረገጾች ከፍተኛ ቅሬታንና ቁጣን መፍጠሩ ይታወሳል፡፡
“ኢትዮጵያ” የተሰኘውን አምስተኛ የሙዚቃ አልበሙን በቅርቡ ካወጣው ቴዲ አፍሮ ጋር የተደረገውን ቃለ መጠይቅ በተመለከተ በማህበራዊ ድረገጾች ከሚሰራጩ መረጃዎች በስተቀር የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን አመራሮችም ሆኑ የዝግጅት ክፍሉ ሃላፊዎች በይፋ ያስታወቁት ነገር የለም፡፡


“እምነትና ውኃ እንጂ ቅብዐ ቅዱስም ሜሮንም አልነበረም፤ ሰውዬውም አልቀባኝም”
ቅዱስ ሲኖዶሱ ከሹመታቸው በፊት ጉዳዩ እንዲጣራ አዝዟል
የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በመጪው ሐምሌ፣ 16 ኤጲስ ቆጶሳትን ትሾማለች

   የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ፣ በመጪው ሐምሌ ወር ኤጲስ ቆጶስነት የሚሾሙ 16 መነኰሳትንና ቆሞሳትን የመረጠ ሲሆን፤ ከተሿሚዎቹ አንዱ የሆኑት ዶ/ር አባ ኃይለማርያም መለሰ፤ በቤተ መቅደስ ውስጥ ከሃይማኖቱ ውጭ ከኾኑ ሌሎች የእምነት መሪዎች ጋራ “ቅብዓ ቅዱስ ተቀባብተዋል” በሚል የቀረበባቸውን አቤቱታ ድርጊቱን አልፈጸምኩም ሲሉ አስተባበሉ፡፡
የኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናትን ጨምሮ፣ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት አባላት የኾኑ የወንጌላውያን አብያተ እምነት መሪዎች በተገኙበት፣ ባለፈው የካቲት 22 ቀን፣ በአዲስ አበባ ደብረ ምጥማቅ ሰዓሊተ ምሕረት ቅድስት ማርያም ካቴድራል የተካሔደው መርሐ ግብር፣ በሚያሳስቡ የጋራ ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች ላይ ለመመካከር የተዘጋጀ የጸሎት ሥነ ሥርዓት እንጂ፣ የቡራኬና ቀኖናዊ እንዳልነበረ፣ ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም፣ ለቤተ ክርስቲያኒቱ የሳተላይት ቴሌቭዥን ጣቢያ (ኢኦተቤ-ቴቪ) በሰጡት ማስተባበያ ተናግረዋል፡፡
የመርሐ ግብሩ ጭብጥ፥ “ውኃ ለኹሉም ፍትሐዊ በኾነ መንገድ” በሚል በወርኃ ጾሙ፣ ንጹሕ ውኃ በተለይ ከሰሃራ በታች ላለው ክፍለ አህጉር በፍትሐዊ መንገድ እንዲዳረስና ውኃ ወለድ በሽታዎች እንዲወገዱ ለማሰብ እንደተዘጋጀና ፓትርያርኩና ሊቃነ ጳጳሳቱም መገኘታቸውን የጠቀሱት ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም፣ ሥነ ሥርዓቱን የመሩትም፣ መርሐ ግብሩን እንዲያስተባብሩ ከቤተ ክርስቲያኒቱ በመወከላቸውና በኅብረቱ ተከታታይ መርሐ ግብር ቤተ ክርስቲያኒቱ ተረኛ በመኾኗ እንደነበር አስረድተዋል፡፡
“ቤተ ክርስቲያኒቱን ወክዬ፣ ውኃ በእጅጉ አስፈላጊ የእግዚአብሔር ስጦታ ስለመኾኑ በመጽሐፍ ቅዱስ የሰፈረውንና በሀገራችን ክርስቲያናዊ ትውፊት በጠበልና በእምነት የሚሰጠውን ፈውስ ተናግሬአለሁ፤” ያሉት ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም፤ “የጸሎት ሥነ ሥርዓቱን የምትመራው የኅብረቱ አባል ቤተ ክርስቲያን፣ በመነካካትና በተግባር የምትፈጽማቸው ምልክታዊ መገለጫዎች (symbolic action) አሉ፤ እኔም ተበጥብጦ ከቀረበው ውኃና እምነት በጣቴ ጠቅሼ በተሳታፊዎቹ ግንባር ላይ በትእምርተ መስቀል ምልክት አድርጌያለሁ፤ ይህም፣ ቤተ ክርስቲያኒቱን በእምነትና በሥርዓት የሚመስሏት ሌሎች እኅት አብያተ ክርስቲያናትም፣ በመሰል መርሐ ግብሮች ላይ የሚያደርጉትና የተለመደ ነው፤” ብለዋል፡፡
ለሥነ ሥርዓቱ የቀረበው፣ “ቅብዓ ቅዱስ እና ሜሮን ነው፤ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሥርዓት ደግሞ በእምነት ከተለዩና ከተወገዙ ሰዎች ጋራ ይህ አይደረግም፤ መርሐ ግብሩም በቤተ መቅደስ ውስጥ መከናወን አልነበረበትም፤” በሚል ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም እንደቀቡና እንደተቀቡ የሚያሳዩ ምስሎችና ትችቶች በማኅበራዊ ድረ ገጽ በስፋት መሰራጨታቸውን በተመለከተ የተጠየቁት ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም፣ “ሰውዬው ጣቱን አስጠጋ እንጅ በፍጹም አልቀባኝም” ሲሉ ተቀብተዋል መባሉን አስተባብለዋል፡፡
“ቅብዓ ቅዱስም ቅብዓ ሜሮንም አልነበረም፤ እነርሱም አይቀበሉም፤ አይፈልጉም፤” ያሉት ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም፣ በምስሉ ላይ የሚታየው ሰው ጣቱን ወደ ግንባራቸው ሲያስጠጋ፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሥርዓት የተሾመ ካህን ሌላ ሰው ሊነካውና ሊባርከው እንደማይችል በሹክሹክታ እንደነገሩትና ጣቱን እንደመለሰ ገልጸዋል፡፡  
ሥነ ሥርዓቱ ከተካሔደ ወራት ማስቆጠሩን ያስታወሱት ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም፣ ምስሉን በማኅበራዊ ድረ ገጽ ያሰራጩት ሰዎች፣ ለቤተ ክርስቲያን የሚቆረቆሩ ከኾነ፣ በወቅቱ እንዲብራራላቸው ሊጠይቋቸው ይችሉ እንደነበር ጠቅሰው፤ ቅዱስ ሲኖዶሱ ተሿሚ ኤጲስ ቆጶሳትን እስከሚመርጥበት ሳምንት በማዘግየትና ከሢመተ ጵጵስናው ጋራ በማገናኘት በድረ ገጽ ማስፋፋታቸው፥ “ግላዊ ጥቅምና ተልእኮ እንዳላቸው ያሳያል፤ እኔን ሳይሆን የቤተ ክርስቲያንን ክብር ነው የነኩት፤“ ሲሉ ቅሬታቸውን አሰምተዋል፤ ለሹመቱም የተመረጡት፣ በቅርበትና በሓላፊነት ላይ ስላሉ ሳይሆን በፈቃደ እግዚአብሔር እንደኾነ ተናግረዋል፡፡
የኤጲስ ቆጶስ ተሿሚው ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም ይህን ይበሉ እንጂ፣ የጸሎት ሥነ ሥርዓቱን መርሐ ግብር ሙሉ በሙሉ የሚያሳይ ቪዲዮ፣ ለሊቃነ ጳጳሳት እና ለሊቃውንት ቀርቦ እንዲጣራ፣ ቅዱስ ሲኖዶሱ ከትላንት በስቲያ አዝዟል፡፡ ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም በኤጲስ ቆጶስነት ቢሾሙም ተመልሰው የሚያገልግሉት ምእመኑን በመኾኑ፣ ለቅዱስ ሲኖዶሱና ለቤተ ክርስቲያኒቱ ክብር እንዲሁም የሕዝቡን ኅሊና ነጻ ለማድረግ ሲባል፣ የተነሣው ጥያቄ ከበዓለ ሢመቱ በፊት ምላሽ ማግኘት እንዳለበት፣ ጉዳዩ ያሳሰባቸው ሊቃነ ጳጳሳት ተናግረዋል፡፡ ሌሎች ተችዎች በበኩላቸው፡- ‹‹አጣርቶ መምረጥ ወይስ መርጦ ማጣራት?›› ሲሉ በዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም ምርጫ ታይቷል ያሉትን የቅደም ተከተል ግድፈት ተችተዋል፡፡
በቤተ ክርስቲያኒቱ የአራቱ ጉባኤያት መምህርነት ከሚታወቁት ሌላው ዕጩ፣ ሊቀ ሊቃውንት አባ ዕዝራ ሐዲስ ጋራ ጎንደርን በመወከል ተወዳድረው፣ ሁለቱም የቅዱስ ሲኖዶስ አባላትን እኩል 18 ድምፅ በማግኘታቸው በተጣለው ዕጣ ለኤጲስ ቆጶስነት ተመርጠዋል የተባሉት አባ ኃይለ ማርያም፣ በነገረ መለኰት የዶክትሬት ዲግሪ እንዳላቸውና የጠቅላይ ቤተ ክህነት ምክትል ሥራ አስኪያጅ እንደኾኑ ተገልጿል፡፡
ግንቦት 2 ቀን የጀመረውን የርክበ ካህናት ምልአተ ጉባኤውን በትላንትናው ዕለት ያጠናቀቀው ቅዱስ ሲኖዶሱ፣ ክፍት በኾኑ መንበረ ጵጵስናዎች የሚሾሙ 16 ኤጲስ ቆጶሳትን ከትላንት በስቲያ ኃሙስ የመረጠ ሲኾን፤ ሢመተ ጵጵስናው፣ በመጪው ሐምሌ 9 ቀን እንደሚፈጸም ተጠቁሟል፡፡ ተሿሚዎቹ፣ ከ31 ተጠቋሚ መነኰሳትና ቆሞሳት መካከል፣ በክህነትና በምንኵስና ሕይወት፥ በትምህርት ዝግጅትና በአገልግሎት ልምድ በአስመራጭ ኮሚቴ ተለይተው ለቅዱስ ሲኖዶሱ እንደቀረቡና በምሥጢራዊ ድምፅ አሰጣጥ እንደተመረጡ ታውቋል፡፡
ከሢመተ ጵጵስናው በፊት ተሿሚዎቹ ኤጲስ ቆጶሳት፣ የቤተ ክርስቲያን አመራርና አስተዳደር እንዲሁም ቤተ ክርስቲያኒቱን እየፈተኗት በሚገኙ ዐበይት ወቅታዊ ጉዳዮችና እንደ አባትነታቸው የሚጠበቅባቸውን በተመለከተ፣ የአንድ ወር ሥልጠና እንደሚሰጣቸው፣ የቅዱስ ሲኖዶሱ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡