Administrator

Administrator

ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ዘማሪ ወፍ በወጥመድ ተይዛ በቆንጆ ድምጽዋ ትዘምራለች፡፡ ድምፁዋ በጣም ከማማሩ የነሳ ሌሎች ወፎች ሁሉ ፀጥ ብለው ያዳምጡዋታል፡፡
“ስበር እውላለሁ፡፡
ስከንፍ አረፍዳለሁ፡፡
ማን ይየኝ ማን ይስማኝ
መች እጨነቃለሁ?
የምሮጥ ለራሴ፣
የመኖር ለራሴ፣
ይድከመኝ ይመመኝ፣
ራሴ ነኝ ዋሴ፡፡
ሰው ግን ይከፋዋል፣
ጥላዬ ሲያርፍበት
ላይከብደው ላይጐዳው፣
ድንገት ባለፈበት፡፡
ሊያጠምደኝ ይለፋል፤ ጉዳዩ አይገባኝም፡፡
ወፍ ይዞ በማሰር፣ ምን እንደሚጠቀም?
ሽቦ - ቤት ባልገባም፤ መዘመሬ አይቀርም…
ሽቦ ቤት ብገባም መዘመሬ አይቀርም!!”
ይህን መዝሙሯን ሁሌ ማታ ማታ ስታሰማ የሌሊት - ወፍ መጥታ በጥሞና ታዳምጣታለች፡፡ አንድ ቀን እንዲህ ስትል ጠየቀቻት፤
“እመት ወፊት?”
“እመት” አለች ወፊት፡፡
የሌሊት ወፍ - “ሁሌ ስትዘምሪ እሰማሻለሁ”
ወፊት - “አዎን”
የሌሊት ወፍ - “ለተኙት ወፎች?”
ወፊት - “አይደለም”
የሌሊት - ወፍ- “ታዲያ ለማነው?”
ወፊት - “ለራሴ!” አለች ፍርጥም ብላ፡፡
የሌሊት ወፍ - “ግን ሁሌ ማታ ማታ ነው የምትዘምሪው?”
ወፊት - “አዎን”
የሌሊት - ወፍ - “ለምን ቀን ቀን አትዘምሪም”
ወፊት - “ቀን ቀን ችግር ነው፡፡ ከዚህ ቀደም ቀን ቀን ስዘምር የሰው ልጅ ሰማኝ፡፡ ‘መጥቼ አጠገብሽ ቁጭ ብዬ ላድምጥሽ፡፡ በጣም ቆንጆ ነው የምትዘምሪው’ አለኝ፡፡
እሺ ብዬ አጠገቡ ሆኜ ስዘምር ድንገት ቀጨም አደረገኝ፡፡ ይሄው እዚህ የሽቦ እሥር ቤት ውስጥ ከተተኝ!”
የሌሊት ወፍም፤ “እመት ወፊት፤ ሰው ጠላትሽ መሆኑን ማወቅሽ ድንቅ ነው፡፡ ግን አንድ ነገር ልብ በይ። አንዴ እሥር ቤት ከገባሽ በኋላ ቀንም ዘመርሽ ማታም ዘመርሽ ለውጥ የለውም፡፡ ሰውዬው ለሁለተኛ ጊዜ ሊያጠምድሽ አይመጣም፡፡ ምክንያቱም በእጁ ነሻ!” አለቻት
* * *
የማናቸውም ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ ቁልፍ ጉዳይ ጊዜ ማወቅ ነው (timing)፡፡ ከዕለቱ አስቀድሞም መንቀሳቀስ፣ ዕለቱ ካለፈም በኋላ መንቀሳቀስ፣ ችግር ላይ ይጥላል፡፡ ትክክለኛ የጊዜ ምጣኔ ያለው የፖለቲካ ሰው፤ ብዙውን የጨዋታውን ሰዓት በእጁ ያስገባ ኳስ ተጨዋች እንደማለት ነው - የሚቀረው ጐል ማግባት ብቻ ነው!
የቅርጫት ኳስ ተጨዋችን ምሳሌ ብናደርገው ደግሞ የመጨረሻዋ ሶስት - ሴኮንድ - ክልል በምትባለው ሳጥን ውስጥ ከገባ፤ ያለው ዕድል ወደ ቅርጫቱ መወርወር ብቻ ነው፡፡ ከዘገየ ቀለጠ፡፡ “ቦታን ደግመን ልንይዘው እንችላለን፡፡ ጊዜን ግን በጭራሽ ደግመን አናየውም” እንዳለው ነው ናፖሊዮን ቦናፓርት፡፡ የጥንቱ የጧቱ ፖለቲከኛ ሌኒንም “Seize the time, seize the gun” ይለዋል፡፡ “ጊዜን ያዝ፣ ጠመንጃህን ጨብጥ!” እንደማለት ነው፡፡
“ለድል የሚያበቃህ፤ አደለም ጀግንነት
አዛዡ ጊዜ ነው፣ በጊዜ እወቅበት!” እንዳለው ነው የአገራችን ገጣሚ፡፡
ባለፈው ሥርዓት ዝነኛ ከነበሩት መፈክሮች አንዱ፤ “ማፍረስ ቀላል ባይሆንም መገንባት የበለጠ ከባድ ነው” የሚል ነበር፡፡ ዕውነት ነው፡፡ የምናፈርሰውን በጊዜ ማፍረስ፣ እምንገነባውን በጊዜ መገንባት፣ ፍፁም ብልህነት ነው፡፡ በእርግጥም ከማፍረስ ይልቅ መገንባት የበለጠ ከባድ ነው፡፡ የምናፈርሳቸው ቤቶች የሚተኩበትን ህንፃ በማሰብ ብቻ ከተጓዝን፣ የሚያመጣውን አፍራሽ ውጤት (Repercussions) ልብ ሳንል እንቀራለን፡፡ ደምረን ማስተዋል አለብን፡፡ “ነገሮች ምድር ላይ ሰላም ሆነው ይታያሉ፤ እሳቱ ያለው ከሥር ነው” ይላሉ ቱርኮች፡፡ ምንጊዜም ተናጠል ሁነቶች አድገው አስተፈሪ የማይሆኑ ይመስሉናል፡፡ ድምር ውጤታቸውን ግን ዐይን ያለው ነው የሚያይ፡፡ ስለዚህ እንይ! እንይ! እንይ! የቅሬታዎች ሥርና ክር፤ የቱን ያህል እንደሚርቅና የቱን ያህል እንደሚከር እናስተውል፡፡ ካፈረስን በኋላ የፈረሰባቸው ምን ሆኑ? በፈረሰው ቦታ ላይ ምን ተካን? ብለን ደጋግመን እንጠይቅ!
“ብዙዎች የነዳጅ ታንካቸውን ለመሙላት ሲጨነቁ ሌሎች በዓለም ዙሪያ ያሉ ደግሞ ሆዳቸውን ለመሙላት ይታገላሉ፡፡ ይሄ ደግሞ ከቀን ቀን እየባሰ፣ ከቀን ቀን እየከፋ ነው የመጣው” ይላሉ፤ የዓለም ባንኩ ፕሬዚዳንት ሮበርት ዞሊክ፡፡ (ዳምቢሣ ሞዮ)
የኑሮ ልዩነት ክፍተት እየሰፋ፣ ጥቂቶች እየተመቻቸው ብዙዎች እየተራቡ የሚሄዱበት ሁኔታ ውሎ አድሮ ጦሱ አይጣል ነው፡፡
ዛሬ ሰላም የሚመስለን ጐዳና ነገ በብሶተኛ ይሞላል፡፡ ጐርፉ መቼ እንደሚሞላ አናውቅም፡፡ የጐርፉን ምንጭ ግን እናውቃለን፡፡ እሱን ለማድረቅም እንችላለን - ልብ ካለን! ነገሮችን በትክክል አይተን በትክክል ካልፈታናቸው፣ በተለይ ትክክለኛ የጊዜ አጠቃቀም ከሌለን፤ እያደር ከድጡ ወደማጡ እንዳንሄድ፣ ወይም እንደዱሮው አነጋገር “ወጣ ወጣና እንደሽምበቆ ተንከባለለ እንደሙቀጫ” ዓይነት ሁኔታ እንዳይገጥመን፤ በእጅጉ መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ መተው ያለብንን መተው፣ በጊዜ መራመድ ያለብንን መራመድ ያሻናል፡፡ አለበለዚያ የትግሪኛው ተረት እንደሚነግረን፤ “ዘወር ካለማለት ነገሩ ሰፋ፣ ቶሎ ካለመሻገር ጐርፉ ሞላ”፤ ማለት ይሆናል ትርፋችን፡፡

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) በአገሪቱ የተለያዩ ከተሞች በሚገኙ አመራሮችና አባላቱ ላይ በገዢው ፓርቲ የድብደባ፣ የእስርና የግል ሚስጥር መበርበርና በተደራጀ ሁኔታ የመዝረፍ ድርጊት እየተፈፀመ መሆኑን ገለፀ፡፡
ፓርቲው “ህጋዊና ሠላማዊ ትግላችን በህገወጥ የአፈና ስልት ሊደናቀፍ አይችልም” በሚል ትናንት ባወጣው መግለጫ ላይ፤ መንግስት አንድነት ፓርቲን በሀሰት ፕሮፖጋንዳ ከማጣጣልና ያለ አግባብ ከአክራሪነት ጋር ለማቆራኘት ከመስራት አልፎ ሠላማዊ ሠልፎችና ህዝባዊ ስብሰባዎቹ እንዲደናቀፉ አፈና እያደረገበት እንደሚገኝ ገልጿል፡፡
በወላይት ሶዶና በመቀሌ የፓርቲው አመራሮችና አባላት ላይ የመደብደብ፣ የማሰር፣ የግል ሚስጥር የመበርበርና በተደራጀ ሁኔታ የመዝረፍ ድርጊት እንደተፈፀመበት ጠቅሶ፣ ፖሊስ ድርጊቱን አይቶ እንዳላየ ማለፉን ገልጿል፡፡
ፓርቲው በነገው እለት በጂንካ፣ በአርባ ምንጭ፣ በመቀሌ፣ በወላይታ፣ በባህርዳርና በአዲስ አበባ የሚያካሂዳቸውን ሠላማዊ ሰልፎችና ህዝባዊ ስብሰባዎችን ለማደናቀፍ በገዢው ፓርቲ አፈናና ወከባ እየተፈፀመበት እንደሚገኝም ጠቁሟል፡፡
አንድነት ህግን መሰረት አድርጐ እየተንቀሳቀሰ በመሆኑ በነገው ዕለት ሊካሄዱ የታሰቡት ሁሉም ሠላማዊ ሰልፎችና ህዝባዊ ስብሰባዎች በተያዘላቸው እቅድ መሰረት እንደሚከናወኑና ህጋዊ እርምጃው በህገወጥ አፈናው ምክንያት እንደማይቀለበስ በመጥቀስ፣ መላው አገሪቱ ህዝብ በነቂስ ወጥቶ የታፈነ ድምፁን እንዲያሰማ ጥሪውን አስተላልፏል፡፡

በህንዳዊው መምህርና ፀሐፊ ሚ/ር ጆሴፍ ፍራንሲስ የተዘጋጀ “የድንቂቱ ኢትዮጵያ ድንቃድንቆች” (“This is Ethiopia – A Book of Fascinating Facts”) የተሰኘ ስለ ኢትዮጵያ የተለያዩ ድንቅ መረጃዎችን ያካተተ አዲስ መፅሐፍ የፊታችን ረቡዕ ከምሽቱ 12 ሰዓት ሚኒስትር ዴኤታ ሙሉጌታ ሰኢድ ዳምጠው በተገኙበት በካፒታል ሆቴል ይመረቃል፡፡
መፅሐፉ፤ ኢትዮጵያን ልዩ የሚያደርጋትን ከ245 በላይ መረጃዎች ያካተተ ሲሆን የተዘጋጀበትም ዓላማ፤ በተለይ የውጭ አገር አንባቢያንና ዳያስፖራዎች፣ ስለ ኢትዮጵያ መረጃዎችን በቀላሉና በአጭሩ እንዲቀስሙ ለማድረግ ነው ተብሏል፡፡ በመፅሐፉ ጀርባ ላይ አስተያየታቸውን ያሰፈሩት የታሪክ ባለሙያው ፕ/ር ሪቻርድ ፓንክረስት፤ “ስለ ኢትዮጵያ ብዙ የማናውቃቸው አስደናቂ ነገሮች መኖራቸውን… መፅሃፉ እንድንገነዘብ ያደርገናል፡፡ መፅሃፉ ያካተታቸው መረጃዎች ብዙ አንባቢዎችን ሊያስደምሙ የሚችሉ ናቸው” ብለዋል፡፡
መፅሃፉ በእንግሊዝኛና በአማርኛ የተዘጋጀ ሲሆን ትርጉሙን የሰራው ደራሲ አማረ ማሞ ነው፡፡ የውስጥ ገፆቹ ሁሉ ባለቀለም ሆነው የተዘጋጀው “የድንቂቱ ኢትዮጵያ ድንቃድንቆች” መጽሐፍ መረጃዎች በተዋቡ ምስሎች ተደግፈው ቀርበውበታል፡፡ ላለፉት 30 ዓመታት ኢትዮጵያ ውስጥ በመምህርነት ያገለገለው ሚ/ር ጆሴፍ ፍራንሲስ፤ ከዚህ ቀደም “የአድዋ ጦርነት”፣ “ዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ” እና “የአፄ ቴዎድሮስ ልጅ፣ ልዑል ዓለማየሁ” የተሰኙ የልጆችና ወጣቶች መፃህፍትን አሳትሟል፡፡

“ቦሌ ፒኮክ ጋ ጠብቂኝ” በተሰኘው የሰለሞን ፍስሀ መጽሐፍ ላይ ነገ ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ በብሔራዊ ቤተመዛግብት እና ቤተመጻሕፍት አዳራሽ ውይይት እንደሚካሄድ ሚዩዚክ ሜይደይ አስታወቀ፡፡ ውይይቱን የሚመሩት ሃያሲ እና የወግ ጸሐፊ መስፍን ሀብተማርያም እንደሆኑ ለማወቅ ተችሏል፡፡

 

የጋዜጠኛና ገጣሚ ተስፋዬ ገብረማርያም “የማይሆን ዓለም” የተሰኘ ግጥሞች፣ አጫጭር ልቦለዶች እና ወግ የተካተቱበት መጽሐፍ ነገ በሐገር ፍቅር ትያትር ቤት ትንሿ አዳራሽ እንደሚመረቅ “ሀሳብ መልቲሚዲያ” አስታወቀ፡፡ በ62 ገፆች የተቀነበበው መፅሀፉ፣ በ20 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ ጋዜጠኛና ገጣሚ ተስፋዬ በ“ኢትዮ ቻናል” ጋዜጣ ማህበራዊ ጉዳዮች አምድ ጸሐፊነቱና በዛሚ 90.7 ኤፍ ኤም ሬዲዮ በሚያቀርበው “ድርሻችን” የተሰኘ በአካል ጉዳተኞች ላይ ያተኮረ ፕሮግራም ይታወቃል፡፡

“ዜማ ቃል” የተሰኘ ወርሃዊ የጥበብ ምሽት ሐሙስ ከቀኑ 10፡30 ጀምሮ  በሐገር ፍቅር ትያትር ቤት ትንሿ አዳራሽ እንደሚቀርብ አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡ ለአንድ ዓመት በሚዘልቀው ዝግጅት፣ የገጣሚያን፣ ጸሐፍትና ኮሜዲያን  ሥራዎች የሚቀርብበት ሲሆን የመግቢያ ዋጋው በነፍስ ወከፍ 50 ብር እንደሆነ ዝግጅቱን የሚያስተባብረው ፈለቀ ካሳ ጥንድ ፕሮሞሽን  ጠቁሟል፡፡ 

በዶ/ር ሱዛን ጄፈርስ የተፃፈው “Feel the Fear and Do it Anyway” የተሰኘ መፅሃፍ፤“ፍርሃትን ማሸነፍ” በሚል ርእስ በቢኒያም አለማየሁ ተተርጉሞ ለንባብ በቃ፡፡ መጽሐፉ አሉታዊ አመለካከትን ስለማስወገድ፣ ውሳኔዎችን በሥራ ስለ መተግበር፣ ፍርሃትን ስለ ማጥፋት እና ሌሎች ተያያዥ ቁም ነገሮችን የያዘ ነው፡፡ 192 ገፆች ያሉት መፅሃፉ፤ ዋጋው 40.50 ብር ነው፡፡
በሌላም በኩል “በአራጣ የተያዘ ጭን” የተሰኘ የአጫጭር ልቦለዶች መድበል ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ በዮፍታሔ ካሳ የተደረሰው መጽሐፍ፤ በ233 ገፆቹ አስራ ዘጠኝ አጫጭር ልቦለዶች ይዟል፡፡ በኤች ዋይ ኢንተርናሽናል ማተሚያ ቤት የታተመውን መጽሐፍ፤ ሊትማን ጀነራል ትሬዲንግ የሚያከፋፍለው ሲሆን ዋጋውም 46.99 ብር ነው፡፡
በተመሳሳይ “ከመለስ ሞት በስተጀርባ” የተሰኘ መጽሐፍ በዚህ ሳምንት ለንባብ በቃ፡፡ መፅሃፉ በኢትዮጵያ፣ በግብፅ፣ በአባይ ግድብ፣ በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ እና ሌሎች ጉዳዮች ዙርያ ያጠነጥናል፡፡ በ70 ገጾች የተዘጋጀው መጽሐፉ፤ ለገበያ የቀረበው በ32 ብር ነው፡፡ በመፅሃፉ ውስጥ ከተካተቱት ፎቶግራፎች መካከልም በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግስት የሃምሳ ብር ኖት ላይ የወጣው የአባይ ግድብን የሚያሳይ ምስል ይገኝበታል፡፡

ከሁለት ወር በፊት ራሷን ከጡት ካንሰር ለመታደግ ሁለት ጡቶቿን በቀዶ ጥገና ያስወገደችው አንጀሊና ጆሊ፤ለመላው ዓለም ስለ ጡት ካንሰር አስከፊነት ባስጨበጠችው ግንዛቤ ከፍተኛ አድናቆትን እንዳተረፈች ተገለፀ፡፡ ዝነኛዋ የሆሊውድ አርቲስት ህክምናውን ለማግኘት የወሰደችው ፈጣን እርምጃና ለመላው ዓለም ግልፅ መረጃ በማቀበል ባሳየችው ድፍረት የተመላበት ተግባር በህክምና ባለሙያዎች ዘንድ ተወድሶላታል። “ተግባሯ በሙያችን መነቃቃትና ግንዛቤ እንዲፈጠር ከፍተኛ አስተዋፅኦ አበርክቷል” ብለዋል - ባለሙያዎቹ፡፡ የስድስት ልጆች እናት የሆነችው የ37 ዓመቷ አንጀሊና ጆሊ፤ሁለት ጡቶቿን የሚያስወግድ ቀዶ ህክምና ባታደርግ ኖሮ 87 በመቶ ለጡት ካንሰር፣ 50 በመቶ ለማህፀን ካንሰር ትጋለጥ እንደነበር ታውቋል፡፡ አንጀሊና በኒውዮርክ ታይምስ ላይ ባሰፈረችው ፅሁፍ፤ ህክምናውን ለመውሰድ የወሰደችው እናቷ በ56 ዓመታቸው በተመሳሳይ ችግር ለሞት በመዳረጋቸው እንደሆነ ገልፃለች። በመላው ዓለም በየዓመቱ ከ45ሺ በላይ ሴቶች በጡት ካንሰር እንደሚሞቱ መረጃዎች ያመለክታሉ።

“ኤ ሎንግ ዎክ ቱ ፍሪደም” በተሰኘው የኔልሰን ማንዴላ ግለታሪክ መፅሃፍ ላይ ተመስርቶ የተሰራው አዲስ ፊልም ከወር በኋላ በመላው ዓለም መታየት እንደሚጀምር ተገለፀ፡፡ ፊልሙ የደቡብ አፍሪካውያንን የነፃነት ትግል ለመላው ዓለም ለማስተዋወቅ ታልሞ የተሰራ ነው ተብሏል፡፡
በጉበት ኢንፌክሽን በጠና ታመው በሆስፒታል ህክምና ሲደረግላቸው የቆዩት ኔልሰን ማንዴላ፤ ከሳምንት በፊት 95ኛ ዓመት የልደት በዓላቸው የተከበረላቸው ሲሆን አሁን ከህመማቸው ማገገማቸው ታውቋል፡፡
“ማንዴላ፡ ኤ ሎንግ ዎክ ቱ ፍሪደም” በሚል ርእስ በተሰራው ፊልም ላይ የማንዴላን ገፀባህርይ የሚተውነው እንግሊዛዊው ተዋናይ ኤድሪስ ኤልባ እንደሆነ ታውቋል፡፡ የ40 ዓመቱ ኤዲሪስ ኤልባ በፊልሙ ላይ ልዩ የትወና ብቃት እንደሚያሳይ ከወዲሁ የተነበየው ዘ ጋርድያን፤ ይሄም ለኦስካር ሽልማት ሊያሳጨው እንደሚችል ግምቱን አስፍሯል። “ማንዴላ፡ ኤ ሎንግ ዎክ ቱ ፍሪደም” የተሰኘው ፊልም በነፃነት ታጋዩ የልጅነት፤ የአስተዳደግና የትምህርት ሁኔታ እንዲሁም የ27 ዓመታት የእስር ቆይታ እና ደቡብ አፍሪካን በፕሬዝዳንትነት እስከመሩበት ጊዜ ድረስ ያለውን ሂደት የሚተርክ መሆኑን “ዘ ስዌታን” ጠቁሟል፡፡ እ.ኤ.አ በ1994 ዓ.ም በማንዴላ ተፅፎ ለንባብ የበቃው ግለ ታሪክ መፅሃፍ በመላው ዓለም ከ15 ሚሊዮን በላይ ቅጂዎች እንደተሸጡ ለማወቅ ተችሏል፡፡

አጓጊው ዜና ምንድነው?
ዋርነር ብሮስ የተባለው የፊልም ኩባንያ እና ዲሲ ኮሚክስ እ.ኤ.አ በ2015 ባትማንና ሱፐርማንን በማጣመር ልዩ ፊልም እንሰራለን ማለታቸው ነው፡፡ ፊልሙ በሚቀጥለው ዓመት ቀረፃው የሚጀምር ሲሆን እውቆቹ የ“ሱፐርማን ሪተርንስ” ዳሬክተር ዛክ ስናይደር እና የ“ባትማን” ፊልም አካል የሆነው “ዘ ዳርክ ናይትስ” ዳሬክተር ክሪስቶፈር ኖላን በጥምረት ይሰሩበታል ተብሏል፡፡
ፊልሙን ለመሥራት እንዴት ታሰበ ?
የልዕለ ጀግና ጀብደኛ ገፀባህርያትን በመፅሃፍ እና በፊልም በመስራት ስኬታማ የሆነው ዲሲ ኮሚክስ፤ ባትማንና ሱፐርማንን በአንድነት በማጣመር ለመስራት የወሰነው አምና ማርቭል ኮሚክስ፤ የልዕለ ጀብደኛ ገፀባህርያትን ያሰባሰበውን “ዘ አቬንጀርስ” ለእይታ በማብቃት በመላው ዓለም 1.5 ቢሊዮን ዶላር ገቢ መሰብሰቡን በማየት ነው፡፡
እነማን ይተውኑበታል?
ዘንድሮ ለእይታ በበቃው በ“ሱፐርማን ሪተርንስ” ፊልም ላይ በመስራት ባሳየው ብቃቱ የተደነቀው ሄነሪ ካቪል ሱፐርማንን ሲተውን ፤ ባትማንን ለመተወን ደግሞ በ“ዘ ዳርክ ናይትስ” ላይ የተወነው ክርስቲያን ቤል ታጭቷል - ማረጋገጫ ባይገኝም፡፡


ባትማንና ሱፐርማን በንፅፅር
*በካርቱን መፃህፍት ላይ ተመስርተው በመሰራት ትርፋማ ከሆኑት የሱፐርሂሮ ጀብደኛ ገፀባህርያት ባትማንና ሱፐርማን ግንባር ቀደም ናቸው፡፡
የባትማን ገፀባህርይ በመፅሃፍ፤ በፊልም፤ በዲቪዲ ሽያጭ እና ሌሎች ንግዶች በመላው ዓለም 12 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ሲያስገኝ የሱፐር ማን ገፀባህርይ ደግሞ በተመሳሳይ ዘርፍ 5 ቢሊዮን ዶላር አስገኝቷል፡፡
ዘንድሮ ለእይታ የበቃው እና በዳሬክተር ዛክ ስናይደር የተሰራው “ማን ኦፍ ስቲል ሱፕርማን ሪተርንስ” 700 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ተገኝቶበታል፡፡
ባትማን ሰብዓዊ ፍጡር ያለው ገፀባህርይ ሲሆን ሱፐርማን ግን ከሰብዓዊ ፍጡር የላቀ ተሰጥኦ ያለው ልዩ ፍጥረት ነው፡፡
ባትማን ልዩ ሃይልና ተሰጥኦ ባይኖረውም በሳይንስና ቴክኖሎጂ አጠቃቀም እና ጠቅላላ እውቀት የተገነባ የላቀ አዕምሮ ያለው ጀብደኛ የልዕለ ጀግና ገፀባህርይ ነው፡፡ ባትማን በምርመራ ችሎታው እና በሃብታምነቱም ይለያል፡፡ ሱፐር ማን ደግሞ መብረር የሚችል፤ከፍተኛ ጥንካሬ ያለውና በላቀ ተሰጥኦው የተለያዩ ጀብዶችን የሚያከናውን እንዲሁም ሰብዓዊ ፍጡር ሊያደርጋቸው የማይችላቸውን ተግባራት በቀላሉ የሚሰራ ገፀባህርይ ነው፡፡