Administrator

Administrator

Saturday, 21 February 2015 13:29

የፍቅር ጥግ

ማን እንደሚያደንቅህና እንደሚወድህ ንገረኝና ማንነትህን እነግርሃለሁ፡፡
ኢሪክ ፍሮም
የማያፈቅር ልብ ከሚኖረኝ ይልቅ የማያዩ ዓይኖች፣ የማይሰሙ ጆሮዎች፣ የማይናገሩ ከናፍሮች ቢኖሩኝ እመርጣለሁ፡፡
ሮበርት ቲዞን
ፍቅር፤ ለሁሉም እጅ ቅርብና በማንኛውም ወቅት የሚበቅል ፍሬ ነው፡፡
ማዘር ቴሬዛ
ሰዎች ኢ-ተጠያቂያዊ፣ በምክን የማይመሩና ራስ ወዳድ ናቸው፡፡ ሆኖም ውደዷቸው፡፡
ኬንት ኤም.ኪዝ
በህልምና በፍቅር ውስጥ የማይቻሉ ነገሮች የሉም፡፡
ዣኖስ አራኒ
አፍቅሮ ማግኘት ምርጥ ነው፡፡ አፍቅሮ ማጣት ሁለተኛው ምርጥ ነገር ነው፡፡
ዊሊያም ሜክፒስ ቻክሬ
ብዙ ጊዜ ፍቅር ይዞኛል … ሁሌም ካንቺ ጋር ነው፡፡
ማንነቱ ያልታወቀ ፀሓፊ  
ፍቅር ዓመታትን የመቁጠር ጉዳይ አይደለም … ዓመታቱን ትርጉም ያላቸው ማድረግ እንጂ፡፡
ሚሼል አማንድ
ገነት ሁሌም ፍቅር በከተመበት ስፍራ ይገኛል፡፡
ጆሃን ፖል ፍሬድሪክ ሪሽተር
እውነተኛ የፍቅር ታሪኮች ጨርሶ ማለቂያ የላቸውም፡፡
ሪቻርድ ባች
ለመፋቀር በተመሳሳይ መንገድ ማሰብ የለብንም፡፡
ፍራንሲስ ዴቪድ
ጨቅላ ፍቅር፤ “ስለምፈልግሽ እወድሻለሁ” ሲል፣
የበሰለ ፍቅር፤ “ስለምወድሽ እፈልግሻለሁ” ይላል፡፡
ኤሪክ ፍሮም

Saturday, 21 February 2015 13:03

ወንጀል-ነክ እንቆቅልሾች?

ሰውየው የሆቴል ክፍል ውስጥ ጋደም ብሎ በር ይቆረቆራል፡፡ ከአልጋው ውስጥ ይወጣና በሩን ይከፍታል፡፡ በሩ ላይ የቆመው የማያውቀው እንግዳ ሰው ነበር፡፡ እንግዳውም እየተጣደፈ፤ “ይቅርታ አድርግልኝ፤ ሳልሳሳት አልቀረሁም፤ የእኔ ክፍል መስሎኝ ነው” ይልና ከመቅፅበት የፎቁን ደረጃ ወርዶ ይሄዳል። ሰውየው የክፍሉን በር ዘግቶ ሲያበቃ የሆቴሉ የፀጥታ ሰራተኞች ጋ ይደውልና በሩን የቆረቆረውን ሰውዬ በፍጥነት እንዲይዙት ይጠቁማቸዋል፡፡
ለምንድነው በሩን የቆረቆረው ሰውዬው
እንዲያዝ የጠቆመው?
ሰውየውን ለመጠርጠርስ ምንድነው
ያበቃው?
አንድ ሽማግሌ በተንጣለለ ሰፊ መኖሪያ ቤታቸው ውስጥ ለብቻቸው ይኖራሉ። በዕድሜያቸው መግፋት የተነሳ እንደልባቸው መንቀሳቀስ ስለማይችሉ የሚያስፈልጓቸው ነገሮች ሁሉ እቤታቸው ድረስ ይመጡላቸዋል።
አርብ ዕለት ፖስተኛው ፖስታ ሊያደርስ
ሲመጣ አካባቢው ጭር ይልበትና አንድ
ነገር ጠርጥሮ፣ በበሩ ቁልፍ ቀዳዳ አጮልቆ
ይመለከታል፡፡ ባየው ነገርም ይደነግጣል
ሽማግሌው ወለሉ ላይ በደም ተለውሰው
ይታያሉ፡፡
የወንጀል መርማሪ ከመቅጽበት ከስፍራው
ይደርሳል፡፡
መርማሪው፤ ከመኖሪያ ቤቱ ውጭ ሁለት
ጠርሙስ ወተት፣ የማክሰኞ ጋዜጣ፣ ጥቂት
ያልተከፈቱ ፖስታዎችና ስጦታዎችን
ያገኛል። መርማሪው ነፍሰ ገዳዩን ለማወቅ
ጊዜ አላጠፋም፡፡
ነፍሰ ገዳዩ ማነው?

መልስ
በሩን የቆረቆረው እንግዳ ሰውዬ “የእኔ ክፍል መስሎኝ ነው” ብሎ ነበር፡፡ እንዲያ ቢሆን ኖሮ ግን የክፍሉን ቁልፍ መያዝ ነበረበት፤ በሩንም መቆርቆር አልነበረበትም፡፡
ነፍሰ ገዳዩ፤ ጋዜጣ አዳዩ ሰውዬ ነው፤ ምክንያቱም የረቡዕና ሐሙስ ጋዜጦችን አላመጣም፡፡  ይሄንንም ያደረገው ጋዜጦቹን የሚያነብ እንደሌለ ስላወቀ ነው፡፡


ሰማያዊ ፓርቲ የገባ የአንድነት አመራር የለም
ለኢህአዴጎች ትክክለኛውን የህዝብ ስሜት ነግሬአቸዋለሁ
ለ“አንድነት” ችግር የመጀመሪያው ተጠያቂ መንግስት ነው

በ2002 ምርጫ አሸንፈው ፓርላማ የገቡት ብቸኛው የተቃዋሚ ፓርቲ ተወካይ የተከበሩ አቶ ግርማ ሰይፉ፤ ምርጫ ቦርድ አንድነት ፓርቲን ለእነ አቶ ትዕግስቱ አወሉ ማፅደቁን ተከትሎ በዘንድሮ ምርጫ እንደማይወዳደሩ ገለፁ፡፡
ቦርዱ አንድነትን በተመለከተ የሰጠውን ውሳኔ ክፉኛ የሚተቹት አቶ ግርማ፤ በግንቦቱ ምርጫ ዙሪያና የፓርላማ ቆይታቸውን እንዲሁም ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮችን በተመለከተ ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር ተከታዩን ቃለምልልስ አድርገዋል፡፡



በርካታ የአንድነት አመራር አባላት ወደ ሰማያዊ ፓርቲ ገብተዋል ተብሏል፤ እርስዎ ለምን ፓርቲውን አልተቀላቀሉም? ከዚህ በኋላ የእርስዎ የፖለቲካ ትግል አቅጣጫ ምንድን ነው የሚሆነው?
በርካታ የአንድነት አመራር አባላት ወደ “ሰማያዊ” ገብተዋል የሚለው ስህተት ነው፡፡ አንድም የካቢኔ አባል የነበር ሰው ወደ ፓርቲው አልገባም፡፡ የፈለገ ሰው ግን ያሻውን  ፓርቲ መቀላቀል እንደሚችል አቅጣጫ አስቀምጠናል። መንግስት አንድነት ላይ እንዲህ ያለ “ነውረኛ” እርምጃ ከመውሰዱም በፊት ቢሆን ሰዎች ወደ ፈለጉት ፓርቲ መሄድ ይችሉ ነበር፡፡ አሁን መንግስት በያዘው አካሄድ የመድብለ ፓርቲ ስርአት መሸከም የሚችል መንግስታዊ መዋቅርም ሆነ ፍላጎት የለም፡፡ ስለዚህ የሰላማዊ ትግሉ በምን አይነት መንገድ ሲመራ የተሻለ ለውጥ ያመጣል የሚለውን አስበንበት አቅጣጫ ማስቀመጥ እንዳለብን ወስነናል፡፡
ፓርቲውን ያልተቀላቀላችሁበት ምክንያት ምንድንነው?
ሰማያዊ ፓርቲ ገብተን ብናጠናክረው፣ ሲጠናከር እግሩን የሚቆርጡት ከሆነ ትርፉ አጉል ድካም ነው የሚሆነው፡፡ አንድነት ፓርቲ የሊበራል አስተሳሰብ  የሚከተል እንደመሆኑ የግለሰቦችን መብት ያከብራል፡፡ የፈለገ ሰው ወደ ፈለገው ፓርቲ የመግባት መብት አለው፡፡ ነገር ግን ብዙዎች ወደ ሰማያዊ ገብተዋል የሚለው ፖለቲካ ለምን እንዳስፈለገ አልገባኝም፡፡ ከኛ አመራር ውስጥ ግን ማንም የስራ አስፈፃሚ  አባል ወደ ሰማያዊ አለመግባቱን አረጋግጣለሁ። ይሄ ለሰማያዊ ከጠቀመውና የኢትዮጵያን  የፖለቲካ ሁኔታ ማሻሻል የሚችል ከሆነ በኛ በኩል ቅሬታ የለንም፡፡
አንድነትን ያለአግባብ “ተነጥቀናል” የምትሉ አመራሮች ምንድን ነው ያሰባችሁት?
አስር ጊዜ እየተፈተነ የሚወድቅ የፍትህ ስርአት ቢኖረንም የፍትህ ስርአቱን ለመፈተሽ ፍ/ቤት ሄደናል፡፡ ፍ/ቤቱ ፖለቲካዊ ውሳኔ ነው የሚሰጠው ወይንስ ማስረጃን ተንተርሶ ነው የሚወስነው የሚለውን ወደፊት የምናየው ይሆናል፡፡ ጉዳያችንን ግን ፍ/ቤት አቅርበናል፡፡ ፍ/ቤቱ ትክክለኛ ውሳኔ የሚወስን ከሆነ፣ እኛ ከ2007 ምርጫ ጋር ምንም የተለየ ፍቅር የለንም። ፓርቲያችንን በተሻለ ሁኔታ በመምራት፣ እንደነ ትዕግስቱ አይነት “ሰንኮፎችን” የነቀልንበት ሂደት አድርገን ልንወስደው እንችላለን፡፡
በሌላ በኩል ከእንደነዚህ አይነት ሰዎች ጋር ሌላ ተጨማሪ ጊዜ እንዳናጠፋ የተፈጠረ እድልም ሊሆን ይችላል፡፡ ለወደፊት የሰላማዊ ትግሉን ለማጥራት የሚረዳ አጋጣሚ ነው ብዬም እቀበለዋለሁ፤ ግን በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ በመንግስት ደረጃ እንዲህ ዓይነት “አስነዋሪ” ድርጊት ሲፈፀም ማየትና የዚያ አካል መሆን በጣም ያሳፍራል፡፡ ሁሉም የሚያፍሩ ይመስለኛል፣ ካላፈሩ ደግሞ ህሊና አላቸው ብዬ አላስብም፡፡ በኛ በኩል ግን ባደረግነው ሁሉ ምንም የሚቆጨን ነገር የለም፡፡ በነገራችን ላይ ሲጀመር አንስቶ “ውጤቱን በኋላ ታዩታላችሁ” እያለ ትዕግስቱ ሲያስፈራራን ነበር፤ ስለዚህ እሱ ጨዋታ ውስጥ የገባው ውጤቱን አውቆት ነው፤ እኛ ግን ጊዜና ገንዘባችንን እያባከንን ነበር፡፡
አንድነት ውስጥ በየጊዜው “ደንብና መርህ ይከበር” የሚሉ ውዝግቦች መከሰታቸው ምክንያቱ ምንድን ነው?
በ2002 ምርጫና አሁን የተደረገው ተመሳሳይ ነገር ነው፤ ምንም ልዩነት የላቸውም፡፡ በ2002 በተፈጠረው ሁኔታ መንግስት አንድነትን ለእነ ፕሮፌሰር መስፍን ወይስ ለእነ ኢንጅነር ግዛቸው ብሰጥ ይሻላል የሚል ምርጫ ውስጥ ነው የገባው፡፡ ለኢ/ር ግዛቸው ብሰጠው ይሻላል ብሎ ወሰነ፡፡ አሁን ደግሞ ከእነ በላይ እና ከእነ ትዕግስቱ የቱ ይሻላል ብሎ መረጠ፡፡ ለትዕግስቱ ተሰጠው፡፡
በ2002 ውሳኔ አሰጣጣቸው ላይ  በጣም ጠንቃቃ ነበሩ፤ አሁን ደግሞ ምንም ቀዳዳ ሊያገኙ ስላልቻሉ በጣም አሳፋሪ የሆነ ውሳኔ ወሰኑ፡፡ ለምንድን ነው አንድነት ላይ እንዲህ የሚደረገው? ምንም ጥርጥር የለውም፤ አንድነት አስቦ የሚሰራ ፓርቲ በመሆኑ ነው፡፡ በሳምንት ሁለት ጋዜጣ ያሳትማል፡፡ ኢህአዴግ ራሱ ሁለት ጋዜጣ በሳምንት አያትምም፡፡ ሁለት ጋዜጣ የሚያሳትም ፓርቲን ኢህአዴግ እንዴት አድርጎ መቋቋም ይችላል? እኛ የሚዲያ ቅስቀሳና ክርክር ሲጀምር እንደምንበልጣቸው እርግጠኞች ነበሩ፤ ስለዚህ ይሄን ቡድን ማፍረስ ነበረባቸው፡፡ 13 ያህል የብሮድካስትና ፕሪንት ባለሙያዎችን አዘጋጅተን  ስንጠብቃቸው ነበር፤ ይሄ ያስደነግጣቸዋል፡፡
ሌላው እስከ 500 እጩዎች አቀርባለሁ ብሎ የተዘጋጀ ፓርቲ የለም፡፡ አብዛኞቹ ይሄን የማድረግ አቅም አልነበራቸውም፡፡ ህዝቡ ጋ ተደራሽ ሆኖ፣ ፓርቲው ባለው ጥንካሬ ብቻ ሳይሆን ኢህአዴግ ባለው ደካማ አስተዳደር የሚፈጠረውን የተቃውሞ ድምፅ ሊሰበስብ የሚችለው አንድነት ብቻ እንደሆነ ኢህአዴግ ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ በእርግጥም ይሄን ማድረግ የሚችለው አንድነት ብቻ ነበር፡፡ ታዲያ ይሄን ኃይል ፈርተው ካላፈረሱ ምን ሊያፈርሱ ይችላሉ? በ2002 ዓ.ም ተመሳሳይ ነገር ነው ያደረጉት፡፡ የመድረክ ጥንካሬ የነበረውን አንድነት ማተራመስ፣ መድረክን ለማተራመስ ይጠቅማቸው ስለነበር ያንን አድርገዋል፡፡ አሁን መድረክን ለምን አይነኩትም? በኛ ሰበብ ነበር መድረክን ሲጨፈጭፉ የነበሩት፤ ስለዚህ አንድነትን ለማዳከም በቂ ምክንያት ነበራቸው፡፡
እርስዎ በአንድነት ውስጥ ለተፈጠረው ምስቅልቅል የመጀመሪያ ተጠያቂ የሚያደርጉት ማንን ነው?
ምንም ጥርጥር የለውም መንግስትን ነው። የደህንነት አካሉ ነው ይሄን ያደረገው።  ኃላፊነቱን በመውሰድ ያስፈፀሙት ደግሞ ምርጫ ቦርድና ሚዲያዎች ናቸው፡፡ የመጀመሪያ ተኩስ የተጀመረው በአንድ የግል ጋዜጣ ላይ ነው - ከኮሙኒኬሽን የሚታዘዝ ግለሰብ አንድም ነገር ሳይኖር “አንድነት እየተከፋፈለ ነው” ብሎ ፃፈ፡፡ ከዚያ ሬዲዮ ፋና፣ ኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ሌሎች ሚዲያዎች ተግተውበታል፡፡ እኛ መልስ እንስጥ ብንል ተቆርጦ ተቀጥሎ ነው የሚቀርበው፡፡ ለሬዲዮ ፋና ለምንድን ነው መልስ እማትሰጡት ተብለን መልስ ስንሰጥ፣ በቪዲዮ በተደራጀ መልኩ ቀርፆ ከኢቢሲ ጋር ግንባር በመፍጠር በአካል ያልተገናኘን ሰዎችን ስንከራከርና ስንሰዳደብ እንደነበር አድርጎ አቅርቧል፡፡ ከዚያ ውጪ ግን የአባላት ምልመላችን “ሆዳሞችን” እንዳያፈራ መጠንቀቅ እንዳለብን  ተረድተናል፡፡ ከብዙ ሺህ አባላት ሦስትና እና አራት “ሆዳሞች” ቢኖሩ የሚገርም ባይሆንም ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለብን ተገንዝበናል፡፡
መድረክን ወክለው ነው ፓርላማ የገቡት። ከእዚህ አንፃር ለምርጫው በፓርላማ መቀመጫ የሚሰጠውን የገንዘብ ድጋፍ መድረክ ይጠቀምበታል?
 መድረክን ወክዬ ነው የገባሁት፤ ስለዚህ ይችላል፡፡ በእርግጥ መድረክን ወክዬ ከተወዳደርኩ በኋላ የህዝብ ወኪል ነው የሆንኩት፡፡ ካልሆነ “አንድነት” ከመድረክ ሲወጣ “ግርማ የመድረክ ተወካዩ አይደለም” ወይም የወረዳ 6 ሰዎች “ግርማ የመድረክ ተወካይ ካልሆነ አንፈልገውም” ብለው ፊርማ ማስገባት ቢፈለጉ ማስተባበር የሚችለው መድረክ ነው፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ በፓርቲ ጥቅማ ጥቅም ደረጃ መድረክ የሚጠቀም ይመስለኛል፡፡
ላለፉት አምስት ዓመታት በፓርላማ ብቸኛ የተቃዋሚ በፓርላማ ቆይታዎ የሚጠበቅብኝን  ተወጥቻለሁ ብለው ያስባሉ?
 እኔ በህይወቴ ከወሰንኳቸው ውሳኔዎች ሁሉ የማይቆጨኝ ፓርላማ ለመግባት የወሰንኩት ውሳኔ ነው፡፡ ያደረግሁት አስተዋፅኦ አደርገዋለሁ ብዬ ከገመትኩት በላይ ነው፡፡ ብዙ ነገሮችን አነብ ነበር፤ የማነበው የሚጠበቅብኝን ኃላፊነት ለመወጣት ነው፡፡ መደገፍ ያለብኝን ለመደገፍ፣ የህዝብ ጥያቄ ነው ያልኩትን ለመጠየቅ፡፡ እናም በኔ በኩል ብዙ ደክሜያለሁ ብዬ አምናለሁ፡፡ ሁሉም የም/ቤቱ አባላት ይሄን ያደርጋሉ ወይ ካልከኝ አያደርጉም፡፡ ምክንያቱም ምንም የሚጠየቁበት ነገር ስለሌላቸው ኃላፊነት የለባቸውም፡፡
አንድ ሰው ብቻውን ፓርላማ ውስጥ መቆየት በጣም ከባድ ነው፡፡ እንደ አንድ ሰው ሳይሆን እንደ ሺህ ሆኜ ሰርቻለሁ ብዬ አስባለሁ። ስገባም አዋጅ ላፀድቅ ወይም ለመረጠኝ ህዝብ መሰረተ ልማት ላሟላ አልነበረም - አማራጮችን ለማቅረብና የህዝቡን ስሜት ለማስተጋባት ነው። እስካሁን ካገኘሁት አስተያየት የአብዛኛው ህዝብ ድምፅ ሆኜ አገልግያለሁ ብዬ አምናለሁ። ለኢህአዴጎች ትክክለኛውን የህዝብ ስሜት ነግሬያቸዋለሁ፡፡ ተጠቅመውበታል ወይ ከተባለ አልተጠቀሙበትም ምክንያቱም እነሱ የሚሰሙ ሰዎች አይደሉም፡፡
የቀድሞውን ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስንም ሆነ አቶ ኃይለማርያምን በጥያቄ የመሞገት ዕድል ነበርዎት፡፡ ከሁለቱ የትኛው የተሻለ አሳማኝ ምላሽ ይሰጥዎት  ነበር? በአጠቃላይ ሃገር በመምራት ረገድስ…
ሁለቱም ለህዝብ ምላሽ የሚሰጡ አይደሉም፡፡ ለጥያቄም ምላሽ አይሰጡም፡፡ ግን ቢያንስ መለስ ጥያቄ ሲመልስ ብልጥ ነበር ብዬ አምናለሁ፡፡ ለምሳሌ አቶ ኃይለማርያም ባለፈው ጥያቄ ሲመልሱ “ባለኝ መረጃ መሰረት” እያሉ ነነር፤ እርግጠኛ ባልሆኑበት መረጃ ሃገር እያስተዳደሩ ነው፡፡ በኔ እምነት መለስ በከፍተኛ ስልጣን ነበር የሚመራው፡፡ ኃይለማርያም ያ ስልጣን አላቸው ብዬ አላስብም፡፡
አንድነትን የመሳሰሉ ትላልቅ ፓርቲዎች “ፅንፍ በመያዝ ገዥው ፓርቲ ጥላቻ እንዲያድርበት ይገፋፉታል” የሚሉ አስተያየቶች ይሰነዘራሉ፡፡ እርስዎ ምን ይላሉ?
በመጀመሪያ ደረጃ አንድነት ከጥላቻ ፈፅሞ ነፃ የሆነ ፓርቲ እንደሆነ ነው የሚታወቀው፡፡ እኔ እንደውም የምታማው ለኢህአዴግ ቅርብ ሆኗል እየተባልኩ ነው፡፡ አንድነት ውስጥ ቂም በቀልና ስድብ የለም፡፡ በተለይ የአሁኑ አሰራራችን የሰለጠነ ነበር፡፡ አንድ ጓደኛዬ፤ “ኢህአዴግ ከሚዲያዎች ‹አዲስ ነገር› ጋዜጣን ከፓርቲዎች ‹አንድነትን› መሸከም ካቃተው የፖለቲካ ጨዋታ አይችልም ማለት ነው” ብሎ ነበር፡፡ ኢህአዴግ ነፃ ሚዲያና የመድብለ ፓርቲ ስርአት መሸከም የማይችል እንደሆነ የሚያረጋግጠው ይሄ ነው። ለምርጫው ስትራቴጂና ፕላን አውጥተን ኢህአዴጐችን በግልፅ በዚህ መንገድ ነው የምናሸንፋችሁ ያልነው እኛ ብቻ ነን፡፡ የጥላቻ ፖለቲካን እናስወግዳለን ብለን ነበር ስንሰራ የቆየነው፡፡
ከዘንድሮ ምርጫ  ምን ይጠብቃሉ?
በመጀመሪያ ደረጃ ምርጫ  የሚባል አለ? እኔ ምርጫው አልቋል ብዬ ነው የማስበው፡፡ አሁን እየተደረገ ያለው የሃብት ብክነት ነው፡፡ አንድም መንግስት ለመሆን የሚያስችላቸውን እጩዎች ያላቀረቡ ፓርቲዎች የሚወዳደሩበት ምርጫ‘ኮ ነው፡፡ ለሁለት ወንበር የሚወዳደሩ ፓርቲዎች አሉ፤ እነዚህ በቃ አላማቸው ፓርላማ መግባት ብቻ ነው፡፡ እንደ ፓርቲ የሚወዳደሩትም እንኳ ቢሆኑ ሙሉ ለሙሉ አያሸንፉም እንጂ ቢያሸንፉ መንግስት አይሆኑም፡፡ መንግስት ለመሆን ሳያስቡ መወዳደር ምን ማለት ነው? ስለዚህ ኢህአዴግ መንግስት እንደሚሆን አረጋግጧል፡፡
በእርስዎ አመለካከት፣ አሁን ባለው የሃገሪቱ ተጨባጭ ሁኔታ በምርጫ ተወዳድሮ ስልጣን መያዝ ይቻላል?
እኛ በምርጫ እምነት ነበረን፡፡ ህዝቡ “ስልጣን ለእገሌ ሰጥቻለሁ፤ እሱ ይምራኝ” የሚለው በምርጫ ብቻ ነው፡፡ ይሄ ስልጡን መንገድ ግን እየተጭበረበረ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን እኮ ከማይችሉት ቡድኖች ጋር እየተጋጠመ በማሸነፍ የዋንጫ ጥማቱን ማርካት ይችላል። ጥንካሬና ጉብዝና የሚለካው ከሚመጥኑት ቡድን ጋር ሲወዳደሩ ነው፡፡ ያለዚያ አነስተኛ ኪሎ ያለውን ቡድን መርጠህ በዝረራ እያሸነፍክ  ሁሌም ሜዳሊያ መውሰድ ትችላለህ፡፡
ምርጫ ስልጡን መንገድ ቢሆንም ገዥው ፓርቲ ይሄንን ሊጠቀምበት አልቻለም፡፡ እነዚህ ሰዎች በምርጫ አልጫወትም ካሉ፣ ህዝቡ በሌላ መንገድ  እሞክራቸዋለሁ ሊል ይችላል፡፡ አብዮት ግን በእቅድ የሚመራ አይደለም፤ ሁሉን እንዳልነበረ የሚያደርግ ነው፡፡ አብዮት በዕቅድ የሚመራ ቢሆን እኔ እመራ ነበር፡፡
ጥያቄዬን አልመለሱልኝም፡፡ እምነት አሁን ባለው ሁኔታ  በምርጫ ስልጣን መያዝ ይቻላል አይቻልም?
የ2007 ምርጫ እኮ አበቃ!
ለወደፊትስ?
እርሱን እንግዲህ እኔ ጠንቋይ አይደለሁ፤ በምን አውቃለሁ፡፡ ሆኖም ግን አንዱ ተስፋህ እየጨለመብህ ሲሄድ ሌሎች የሚለመልሙ ተስፋዎች ይኖራሉ፡፡ እኔ በበኩሌ፤ ስልጡኑ መንገድ ምርጫ ብቻ ነው የሚል ጠንካራ እምነት አለኝ፤ ግን ሰይጣናዊ መንገድም አለ። በሰይጣናዊ መንገድ ሲሆን መሳሪያ ያድነኛል ማለት አያስኬድም፤ ሙባረክና ጋዳፊንም አላዳናቸውም፡፡    

      ከዕለታት አንድ ቀን ጦርነት አለ ተብሎ ጐበዝ ሁሉ ክተት ሠራዊት ተባለና ዝግጅት ተጀመረ፡፡
ከአንድ መንደር ወደጦርነቱ የሚሄድ ጐበዝ ሚስቱ ነብሰጡር ነበረችና፤
“ድንገት ጦርነቱ ረዥም ጊዜ ከፈጀ፣ አሊያም አንዳች አደጋ ከገጠመኝ የልጄን ነገር አደራ” ብሏት ተሰናብቶ ወጣ፡፡
ጦርነቱ ከሁለት ዓመት በላይ ፈጀ፡፡ ያ ጀግናም በሰላም ወደ ቤቱ ተመለሰ፡፡
እንደደረሰ “ደህና ከረማችሁ?” አለ፡፡
“ደህና ነህ? እንኳን ደህና መጣህ የኔ ጌታ!” አለች ባለቤቱ፡፡
“ብዙ ሰው ተጐዳባችሁ?”
“ብዙም አይደል፡፡ እኛ ደህና ቦታ ላይ መሽገን ስለነበር ለጠላት አልተመቸንም ነበር፡፡”
ባለቤቱ ወደ ጓዳ ጉድ ጉድ ማለቷን ቀጠለች፡፡
ባልየው አንድ ነገር ግር ብሎታል፡፡ ምንም ዓይነት የህፃን ልጅ ድምፅ አይሰማውም፡፡
“ልጄ የት አለ?” “፣ “ምን ሆነ?” “ወደ እናቴ ልካው ሊሆን ይችላል?” ብዙ ጥያቄዎች ተመላለሱበት፡፡
ሚስቲቱ ምግብ ሠርታ በሉ፡፡ የሚጠጣም ተጠጣና ባል ወደማይቀረው ጥያቄ ሄደ፡፡
“የልጄ ነገር ምን ሆነ?” አለ፡፡
“ልጃችን መወለዱን ደህና ተወልዶ ነበር፡፡ ነገር ግን አንድ ዓመት ተኩል ያህል እንደሆነው በድንገት የብርድ በሽታ አጣደፈው፡፡  በዚያው ህይወቱ አለፈ፡፡”
ባል አዘነ፡፡ ጥቂት ጊዜ ካለፈም በኋላ፤
“ለመሆኑ ስሙን ማን አላችሁት?” አለና ጠየቀ፡፡
“በታወቀው የአካባቢያችን ጀግና ስም ነበር የሰየምነው” አለችው፡፡
“አይ በቃ፤ ልጄ በምን እንደሞተ አወቅሁት” አለ፡፡
“እንዴት? በምንድነው የሞተው?”
“ስሙ ከብዶት ነው!!” አለ፡፡
*   *   *
ስማቸው የከበዳቸው አያሌ ናቸው፡፡ ግማሾቹ ድርጅት ናቸው፡፡ ግማሾቹ ፓርቲ ናቸው፡፡ ግማሾቹ ግንባር ናቸው፡፡ በቅጡ ሳይወለዱ የሞቱ አሉ፡፡ የጨነገፉ እንደማለት፡፡ ተወልደው ብዙም ሳይቆዩ የሞቱ አሉ፡፡ ገና እሚኖሩና ገና እሚሞቱ አሉ፡፡
በተለይ በፖለቲካ ትግል ጉዞ ውስጥ የሆነውን ለምን ሆነ ብሎ ወደኋላ መጨናነቅ እርባና የለውም፡፡ ለትምህርቱና ለተመክሮነቱ ካልሆነ ያዙኝ ልቀቁኝ ቢባል ፍሬ የለውም፡፡ ይልቁንም የተሻለ መንገድን ማቀድና መቀየስ ነው የሚያዋጣው፡፡
“አንዴ ቮልካኖው [አሳተ - ገሞራው] ከፈነዳ በኋላ ላቫውን (ብታኙን) እንደገና መልሶ ወደ እሳቱ ሆድቃ መክተት አይቻልም፡፡ ስለዚህ ማድረግ ያለብን አትክልት መትከል፣ ሣሩን ማጨድና በጐቹን ለግጦሽ ማሰማራት ነው” ይሉናል ፀሐፍት፡፡ የሀገራችንን ነባራዊ ሁኔታ ላስተዋለ የረዥም ጊዜ ሙሾ - አውራጅነት ይበዛዋል፡፡ ውሃ ወቀጣ ነው፡፡ ልብ አላልን ይሆናል እንጂ ከቶም ውሃ - ቅዳ ውሃ መልሱና ድግግሞሹ የትም አላደረሰንም፡፡ ታሪኩና ወቅታዊ ድርጊቱ ተሰምሮ አይለይም፡፡ ሲወድቁ ተስፋ አለመቁረጥና በአጭር ጊዜ የድል ባለቤት ለመሆን መጣደፍ ረብ ያለው ውጤት አያመጡም፡፡ ጥፋትና ጥቃት ደረሰብኝ ብሎ ባንዴ መበታተንም የማለዳ ኢላማን መዘንጋት ነው፡፡
“እያንዳንዱ ወንጀል ፍርሃት መቀፍቀፉ አይቀርም”፡፡ ይሄ ደግሞ ፍርሃትን ለማስወገድ በሚወሰድ የኃይል እርምጃ ይተካና ዲሞክራሲያዊ እንቅስቃሴን ያጨልማል፡፡ አለመዘንጋት ያለብን ዲሞክራሲ አዳጊ ሂደት እንደሆነ ሁሉ አምባገነናዊ ሥርዓትም አዳጊ ሂደት እንጂ ያንድ ጀንበር ጉዳይ አለመሆኑን ነው፡፡ ድንገት የበቀለ አገር እንደሌለ ሁሉ ድንገት ዱብ - ዕዳ የሚሆን ሥርዓት አይኖርም፡፡ የብራ - መብረቅ የሆነ (a Bolt from the blue) ዲሞክራሲ የለም፡፡ በልክ የተሰፋ ዲሞክራሲም ባንድ አፍታ ተፈጥሮ አያውቅም፡፡ ሁሉ ነገር በተዛማጅነት ነው ወደ ዕድገት የሚያመራው፡፡ ያ ማለት ግን ሲያመች በእጅ ሲያቃጥል በማንኪያ በማድረግ ለራስ እንደሚጣፍጥ አርጐ መዋጥ አይደለም፡፡ ሁሌም ማዕከሉ የሀገርና የህዝብ ጥቅም መሆን አለበት!
በኢትዮጵያ ምድር ፖለቲካ ከውሸት ጋር መያያዙ የጥንት የጠዋት ጉዳይ ነው፡፡ “መቦልተክ”፣ መዋሸት የሚል ትርጉም ይዞ ነው የኖረው፡፡ “እገሌ ቦለቲከኛ ነው” ከተባለ ይዋሻል ነው፡፡ ሁሉም ወደወንበር ያመራ ሁሉ ጠዋት ስለህዝብ፤ ማታ ስለራሱ ማውራቱ ነው አስቸጋሪው፡፡ በሀቅ ስለሀቅ በመጓዝ አለመዝለቁ ነው አበሳው፡፡ የየሥርዓቱ ጣጣ መፈክሩ፤ መሸጫው ይሁን መሳቢያው፣ አለመለየቱ ነው፡፡ የሚባለው ሁሉ በሥራ መተርጐም አለመተርጐሙን ለማረጋገጥ ሙስናዊ ግብዓቶቹ እንቅፋት መሆናቸው ነው፡፡ ሙስናው በሙስና መሸፈኑ የባሰ ውስብስብ ሁኔታ ውስጥ እየከተተን መምጣቱ ነው፡፡ ህግ ሽፋን የሚሰጠው ለማን ነው? በሙስና ውስጥ አንበሳው ድርሻ የማነው? የሚለው ጥያቄ እንጂ ሙስናው ራሱን መፈተሽ የቀረ ይመስላል፡፡ ራሳቸው በወንጀል ተጠያቂ የሆኑት በወንጀል ጠያቂ ከሆኑ ወንጀሉ እንዴት መፍትሔ ያገኛል? “የሚያባርረኝ ጣሊያን እንቅፋት መቶት በሞተ ጀግና ነህ ብለው አሠሩኝ እንጂ እኔስ ዓርበኛ አይደለሁም” የሚለው የዓርበኛው ደምበል ንግግር የየዘመኑ ፖለቲካና ፖለቲከኛ መልክ ነው የሚባለው ለዚህ ነው፡፡  

አክሰስ ሪል እስቴትን ለማስቀጠል ያቀረቡት ጥናት አዋጪ ነው ተብሏል

ከሁለት አመታት በፊት በአክሰስ ሪል እስቴት ውስጥ የተፈጠረውን ቀውስ ተከትሎ አገር ጥለው የተሰደዱት አቶ ኤርሚያስ አመልጋ፤ ከመንግስት አካላት ጋር በተደረገ ድርድር ወደ አገራቸው ገብተው የጀመሯቸውን ስራዎች ለማስቀጠልና ከተለያዩ አካላት ለቀረቡባቸው ጥያቄዎች ተገቢውን ምላሽ ለመስጠት በመስማማት ከትናንት በስቲያ አዲስ አበባ ገቡ፡፡
አክሰስ ሪል እስቴት አክስዮን ማህበር ክፍያ የተቀበለባቸውን ቤቶች በወቅቱ ሰርቶ ማጠናቀቅና ለቤት ገዢዎች ማስረከብ ባለመቻሉ ከቤት ገዢዎችና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ከቀረቡባቸው ክሶች ለመሸሽ አገር ጥለው የወጡት የአክሰስ ሪል እስቴት፣ የአክሰስ ካፒታልና የዘመን ባንክ መስራች አቶ ኤርሚያስ አመልጋ፤ በሺህዎች ለሚቆጠሩ ዜጎች ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት ሲባል መንግስት በሰጣቸው ያለመከሰስ ዋስትና ወደ አገር ቤት መመለሳቸውን ምንጮች ገልጸዋል፡፡
የአክሰስ ሪል እስቴት ቤት ገዢዎችና ባለአክስዮኖች በጋራ ባቋቋሙት ኮሚቴ አማካይነት በኩባንያው ውስጥ የተፈጠረውን ቀውስ ለመፍታት ያደረጉት ጥረት ውጤት አልባ መሆኑን ተከትሎ፣ መንግስት በጉዳዩ ጣልቃ እንዲገባ ባመለከቱት መሰረት የሚመለከታቸው የመንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናትን ያቀፈ ኮሚቴ ተቋቁሞ ጉዳዩን ሲያጣራ ቆይቷል፡፡
የአክሰስ ሪል እስቴትን ችግር ለመፍታት ያስችላል በሚል አቶ ኤርሚያስ አዘጋጅተው የላኩትን የአክሲዮን ማህበሩ ወቅታዊ ሁኔታና የቀጣይ አቅጣጫ አመላካች ሰነድና የማገገሚያ ዕቅድ ማስፈጸሚያ ዝርዝር ሃሳብ ሲመረምር የቆየው ኮሚቴው፤ የግለሰቡን ሃሳብ አዋጭነት በመገንዘብ ያወጡትን ዕቅድ ተግባራዊ ማድረግ የሚችሉበትን ሁኔታ ለማመቻቸት ሲሰራ ቆይቷል፡፡
አቶ ኤርሚያስ ችግሩን መፍታትና ዕቅዱን በአግባቡ ተግባራዊ ማድረግ የሚችሉት፣ ከተመሰረቱባቸውና ሊመሰረቱባቸው ከሚችሉ ክሶች ነጻ ሆነው መንቀሳቀስ ሲችሉ እንደሆነ ያስቀመጡትን ቅድመ ሁኔታ ያጤነው ኮሚቴው፤ ከሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ጋር ባደረገው ውይይት ያለመከሰስ ዋስትና ተሰጥቷቸው ወደ አገር ውስጥ እንዲገቡ መደረጋቸውንም ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡
ኮሚቴው ከወራት በፊት በሰጠው መግለጫ፤ አክሰስ ሪል እስቴት አክሲዮን ማህበር ካሉበት እዳዎች ይልቅ ሃብቱ እንደሚበልጥ ጠቅሶ፤ ተገቢው የተቀናጀ ስራ ከተሰራ ኩባንያው ማገገምና የጀመራቸውን ስራዎች ማጠናቀቅ እንደሚችል መገለፁን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

       የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅ/ሲኖዶስ፣ ‹‹ቤተ ክርስቲያንን አዋርደዋል፤ አባቶችን ዘልፈዋል›› ያላቸው አለቆች ቀኖናዊ ምክርና ተግሣጽ እንዲሰጣቸው ያሳለፈው ውሳኔ በፓትርያርኩ ትእዛዝ መታገዱ ከአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አድባራትና ገዳማት ሰንበት ት/ቤቶች ተቃውሞ ገጠመው፡፡
የአ/አበባ ሀገረ ስብከት ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ባለፈው ሳምንት እሑድ በሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት አዳራሽ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ባካሔደው የግማሽ ቀን ውይይት ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት፤ ቅዱስ ሲኖዶስ በጥቅምቱ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባው ‹‹አማሳኝ አለቆች›› ተግሣጽና ማስጠንቀቂያ እንዲሰጣቸው ያሳለፈው ውሳኔ ባለመፈጸሙ ቤተ ክርስቲያኒቱ በከፋ ኹኔታ እየታወከችና እየተመዘበረች እንደምትገኝ ገልጸዋል፡፡
ፓትርያርኩ ውሳኔ እንዲቆዩ ማዘዛቸውን ተከትሎ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ውሳኔውን ለማስፈጸም ባለመቻሉ፣ ‹‹አማሳኝ አለቆች›› በሚል የተገለጹ የአድባራት ኃላፊዎች እንቅስቃሴያቸውን ለሚቃወሙ አገልጋዮች ስም እያወጡ፣ በገንዘብ ኃይል ከሥራቸው እንዲፈናቀሉና ያለፈቃዳቸው እንዲዘዋወሩ፤ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች የድርሻቸውን እንዳይወጡ ከመዋቅር ውጭ ባደራጇቸው አካላት እየከፋፈሉና በፖሊቲከኛነት እየወነጀሉ ከአገልግሎት በማገድ ለእስርና እንግልት እየዳረጉ እንደኾነ በውይይቱ ላይ ተጠቅሷል፡፡
“የአማሳኝ አለቆች” ቡድኑ ‹‹ፓትርያርኩ በእጃችን ናቸው፤ የምንፈልገውን እናስፈጽማለን›› በሚል ዕድገትና ሹመት ለማሰጠት ወደኋላ እንደማይልና ድጋፍ በማሰባሰብ ላይ እንደሆነ አስተያየት ሰጪዎቹ ተናግረዋል፡፡ ቡድኑ በዋናነት ‹‹ሊያሠሩን አልቻሉም›› ያላቸውን የወቅቱን የሀገረ ስብከቱን ረዳት ሊቀ ጳጳስ የመወንጀል እንቅስቃሴ እያደረገ መሆኑን የጠቆሙት ተሳታፊዎቹ፤ ከመጪው የግንቦት ቅ/ሲኖዶስ ስብሰባ በፊት ከሓላፊነታቸው የሚነሡበትን ተቃውሞ የማጠናከር ዓላማ እንዳለውም ገልጸዋል፡፡  ቅ/ሲኖዶሱ በ‹‹አማሳኝ አለቆች›› ላይ ያሳለፈው ውሳኔ አለመፈጸሙ፣ ‹‹እነ እገሌ ምን ኾኑ? እኛስ ምን እንኾናለን?›› በሚል እየተዘበተበትና ‹‹በእግሩ የመጣ በመኪና ይሔዳል›› በሚልም ለከፋ ሙስና በር እንደከፈተ ተናግረዋል፡፡
ለሀገረ ስብከቱ የታቀደው የአደረጃጀትና የአሠራር ለውጥ በ‹‹አማሳኝ አለቆችና ቲፎዞዎቻቸው የውኃ ሽታ›› መኾኑን የገለጹት ተሳታፊዎቹ፤ ያለተጠያቂነት የሚፈጽሙት ቤተ ክርስቲያኒቱን የመለያየትና የመመዝበር ድርጊት የሰንበት ት/ቤት ወጣቶችን የአገልግሎት ተነሣሽነት እየጎዳ ከመኾኑም በላይ ‹‹የቅ/ሲኖዶሱ ልዕልና ጠፍቶ ቤተ ክርስቲያኒቱ በግለሰቦቹ እጅ ላይ ያለች አስመስሏታል›› ብለዋል፡፡ ‹‹ወዳልተፈለገ ነገርስ አያመራም ወይ?›› ሲሉም ውይይቱን ለሚመሩት በሀገረ ስብከቱ የፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስና የአንድነቱ ሊቀ መንበር ጥያቄአቸውን አቅርበዋል፡፡
‹‹በሃይማኖት ሕጸጽ የሚጠረጠሩ ሰባክያን ተመድበውብናል›› ያሉ የመካነ ሰማዕት ቅዱስ ቂርቆስና የደብረ ናዝሬት ቅዱስ ዮሴፍ አድባራት ሰንበት ት/ቤቶች ተወካዮች በበኩላቸው፤ በቤተ ክርስቲያኒቱ ዐውደ ምሕረት በዝማሬና በስብከተ ወንጌል የመሳተፍ መብታቸው አስተምህሮዋን በሚፃረሩ የስብከተ ወንጌል ሓላፊዎችና ሕገ ወጥ ሰባክያን ስምሪት መታወኩን በምሬት ገልጸዋል፡፡ በሰሚት መድኃኔዓለም በግለሰቦች ፍላጎት የባለጸጋ ልጆች ብቻ ተሰብስበው የሚማሩበት ሁኔታ መፈጠሩን የጠቆሙት ተሳታፊዎቹ፤ ቤተ ክርስቲያኒቱን ‹‹የሀብታምና የድኃ›› ብሎ የመክፈል አዝማሚያ መስተዋሉን አስረድተዋል፡፡ የሰንበት ት/ቤቱ አመራር ይህ ዐይነቱ አካሔድ እንዲታገድ በጠየቀው መሠረት በሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት የተሰጠው መመሪያ በደብሩ አስተዳደር ተቀባይነት ባለማግኘቱ የአመራር አባላቱ እስከመታሰር መድረሳቸው በእንባ ተገልጧል፡፡
በውይይት መርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው ትምህርትና ቃለ ምዕዳን የሰጡት በሀገረ ስብከቱ የፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስና የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የበላይ ሓላፊ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፣ ጉበኞች ፈጽሞ እንደማይተኙ ጠቁመው እያደረጉ ስላሉት እንቅስቃሴም መረጃው እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡ እንቅስቃሴአቸው የተደራጀና በከፍተኛ ገንዘብ የተደገፈ እንደኾነ ሊቀ ጳጳሱ ገልጸው፣ ‹‹ጥቅማቸው እንዳይዘጋ በሰው ሕይወትም ከመምጣት ወደኋላ አይሉም›› ብለዋል፡፡ ይኹንና ቤተ ክርስቲያኒቱ ከፓትርያርኩ አንሥቶ ሙስናን ለመዋጋት ወደ ኋላ እንደማትል አረጋግጠዋል፡፡
‹‹መሾምና መሻር የእናንተ ድርሻ ባይኾንም ስለ ቤተ ክርስቲያን ግን አይመለከታችኹም አይባልም፤ እንዲያውም የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎች የአስተዳደሩ ሐሳብ መጋቢዎች ናቸው፤›› ያሉት ሊቀ ጳጳሱ፤ ወጣቱ በትጋትና በብልሃት አጥቢያ ቤተ ክርስቲያኑን አጥር ኾኖ ሊጠብቅ ይገባል ብለዋል፡፡ ከየአጥቢያው በተነሡት ችግሮች ዙሪያም የሚገባውን ያኽል አልሠራም ካሉት ከጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ አንሥቶ ኹሉም ራሱን እንዲፈትሽና የድርሻውን እንዲወጣ አሳስበዋል፡፡ ውይይቱ ቀጣይነት እንደሚኖረው አቡነ ቀሌምንጦስ አስታውቀው፤ ‹‹አማሳኞች›› የወጣቱን ጥያቄ ከመንገድ በማውጣት ከግንቦቱ ምርጫ ጋር በተያያዘ ትንኮሳ ከመፍጠር ስለማይመለሱ እንደ ዜጋም እንደ ሃይማኖተኛም በትዕግሥትና በሰላማዊ መንገድ መዋቅርን ጠብቆ በመንቀሳቀስ ማሳለፍ እንደሚያስፈልግ መክረዋል፡፡
ቁጥራቸው ከ780 በላይ የኾኑ የሰባቱም ክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቶች ሰንበት ት/ቤት ክፍሎች ሓላፊዎችና የ160 አጥቢያ አብያተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤቶች አመራሮች በተገኙበት በዚኹ የውይይት መርሐ ግብር÷ ሰንበት ተማሪው በሃይማኖት ሕጸጽ በሚጠረጠሩና አፍራሽ ተልእኮ ባላቸው ሰባክያን ዙሪያ ተጨባጭ ማስረጃዎችን በቅዱስ ሲኖዶስ ለተቋቋመው አጣሪ አካል እንዲያቀርብ ጥሪ ቀርቧል፡፡
በተያያዘ ዜና÷ የውይይት መርሐ ግብሩን እንደ ስጋት ከሚመለከቱ አካላት እንደኾነ የተጠረጠረ ዛቻና ማስፈራሪያ በሀገረ ስብከቱ የሰንበት ት/ቤት አንድነት አመራሮች ላይ እየተፈጸመ እንዳለ ተጠቁሟል፡፡ በዕለቱ ውይይቱን ሲመሩ በነበሩት የአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ሊቀ መንበር ቀሲስ ኄኖክ ዐሥራት ዛቻና ማስፈራሪያው ከደረሰባቸው አመራሮች አንዱ እንደሆኑ የጠቆሙት ምንጮች፤ ‹‹መንግሥት ከኛ ጋር ነው፤ አንተን ለማጥፋት ጥቂት ገንዘብ ይበቃናል›› የሚሉ ግለሰቦች ሳያቋርጡ በስልክ ዛቻና ማስፈራሪያ እንዳደረሱባቸው ገልጸዋል፡፡

በአደረባት ድንገተኛ ሕመም ሕይወቷ ያለፈው  ደራሲና ጋዜጠኛ እቱ ገረመው የቀብር ሥነ ሥርዓት የካቲት 7 ቀን 2007 ዓ.ም በትውልድ ሀገሯ አርባ ምንጭ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን የክልሉ መንግሥት ባለሥልጣናት፣ በርካታ ወዳጅ ዘመዶቿና የከተማው ነዋሪዎች በተገኙበት ተፈጽሟል፡፡
የአንዲት ሴት ልጅ እናት የነበረችው ጋዜጠኛ እቱ ገረመው፥ በአዲስ አድማስ፣ በኔሽንና በኢትዮ- ቻናል ጋዜጦች፣ በእፎይታና በቢዝነስ ታይምስ መጽሔቶች፤ በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና በዛሚ ሬዲዮ ላይ በጋዜጠኝነት ሞያዋ ሠርታለች፡፡
ጋዜጠኛዋ ባለፉት ሦስት ዓመታት “ማሺሪያ” (በወላይትኛ ሴትዮዋ ማለት ነው) የተሰኘና በሴቶች ላይ ትኩረት አድርጐ የሚታተም መጽሔት ስታዘጋጅ የቆየች ሲሆን፤ በዚህ መጽሔት በአርባ ምንጭና በአካባቢው የሚታዩ የሙስናና ብልሹ አሠራሮችን በማጋለጥ፣ የክልሉ ሴቶችን ጭቆና በመታገልና መብታቸው እንዲከበር የበኩሏን ጥረት አበርክታለች፡፡ ጋዜጠኛዋ እቱ  “የጭን መነባንብ” የተሰኘ ልብወለድ መጽሐፍም ለኅትመት አብቅታለች፡፡
የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ዝግጅት ክፍል፥ በእቱ ገረመው ድንገተኛ ህልፈት የተሰማንን ጥልቅ ሐዘን እየገለፅን፤ ለልጇ፣ ለቤተሰቦቿና ለወዳጅ ዘመዶችዋ መጽናናትን እንዲሰጣቸው እንመኛለን፡፡

አንድ ስዕል 300 ሚሊዮን ዶላር ተሽጧል
የኳታሩ ሚ/ር ከ1 ቢሊዮን ዶላር በላይ የመንግስት በጀት ለስዕል ግዢ አውጥተዋል

በፈረንሳዊው ሰዓሊ ፖል ጎጊን እ.ኤ.አ በ1892 የተሳለውና “ናፊያ ፋ ልፖኢፖ” የሚል ርዕስ ያለው ስዕል በአለማችን የስዕል ስራዎች ሽያጭ ታሪክ ክብረ ወሰን ባሰመዘገበ መልኩ በ300 ሚሊዮን ዶላር መሸጡን ኒውዮርክ ታይምስ ዘገበ፡፡
የሁለት ልጃገረዶችን ምስል የሚያሳየው ይህ ስዕል፣ ሩዶልፍ ስቴችሊን በተባሉት ስዊዘርላንዳዊ የስነጥበብ ስራዎች ሰብሳቢ ግለሰብ ባለቤትነት ኩንስት በተባለ ሙዚየም ውስጥ ለረጅም አመታት እንደቆየና ሰሞኑን በኳታር ለሚገኝ አንድ ሙዚየም እንደተሸጠ ዘገባው ጠቅሷል፡፡
በስቴችሊንና በኩንስት ሙዚየም መካከል በቅርቡ አለመግባባት መፈጠሩን ተከትሎ፣ ግለሰቡ ስዕሉን ለኳታሩ ሙዚየም ለመሸጥ መወሰናቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ኳታር ከዚህ ቀደምም በስዕል ሽያጭ ታሪክ ከፍተኛው ገንዘብ የተከፈለበትንና በሰዓሊ ፖል ሴዛኔ የተሳለውን የስዕል ስራ በ158 ሚሊዮን ፓውንድ መግዛቷን አክሎ ገልጧል፡፡
ኳታር ለስነጥበብ ስራዎች ግዢ ከፍተኛ ገንዘብ እንደምታወጣና፣ ባለፈው አመት ከዚህ አለም በሞት የተለዩት የቀድሞው የኳታር የባህል ሚኒስትር ሼክ ሳኡድ ቢን ሞሃመድ አል ጣኒ፣ ከ1 ቢሊዮን ዶላር በላይ ገንዘብ ከመንግስት ካዝና ወጪ በማድረግ ለስነጥበብ ስራዎች ግዢ ማዋላቸውንም አስታውሷል፡፡


“ምርጫውን ያራዘሙት ሽንፈት ስላሰጋቸው ነው” ተቃዋሚዎች
*የአሜሪካና እንግሊዝ መንግስታት ምርጫው መራዘሙን ተቃውመዋል


በዛሬው ዕለት ይከናወናል ተብሎ ቀን የተቆረጠለትን የናይጀሪያ ፕሬዚዳንታዊና የፓርላማ ምርጫ ለስድስት ሳምንታት አራዝመዋል በሚል በአለማቀፍ ደረጃ ትችት እየተሰነዘረባቸው ያሉት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ጉድላክ ጆናታን፣ ምርጫውን አላራዘምኩም ሲሉ አስተባበሉ፡፡
ቢቢሲ እንደዘገበው፤ ፕሬዚዳንቱ ምርጫውን ለማራዘም በተላለፈው ውሳኔ ውስጥ እጃቸው እንደሌለበትና ውሳኔውን ያስተላለፉት አካላት በጉዳዩ ዙሪያ እንዳላማከሯቸው አስታውቀዋል፡፡
የአገሪቱ የምርጫ አስፈጻሚ ባለስልጣናት፣ ቦኮ ሃራም የተባለው ጽንፈኛ ቡድን ምርጫውን የሚያስተጓጉል ድርጊት ሊፈጽም ይችላል በሚል ከጸጥታ ሃይሎች የተገለጸላቸውን ስጋት መነሻ በማድረግ ምርጫው ለስድስት ሳምንታት እንዲራዘም መወሰናቸውን ፕሬዚዳንቱ ጠቁመዋል።
የናይጀሪያ ምርጫ ኮሚሽን ሃላፊ አታሂሩ ጃጋ፣ ምርጫው ሊራዘም የቻለው መራጮችን ከቦኮ ሃራም ከሚሰነዘሩ የሽብር ጥቃቶ መከላከል የሚችል በቂ የጸጥታ ሃይል ባለመኖሩ ነው ቢሉም፣ በምርጫው ለመወዳደር የተዘጋጁ የአገሪቱ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች በበኩላቸው፤ፕሬዚዳንት ጉድላክ ጆናታን ምርጫውን ያራዘሙት እንዳይሸነፉና ስልጣናቸውን እንዳይነጠቁ በመስጋት ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡
ፕሬዚዳንት ጉድላክ ጆናታን እና ፓርቲያቸው ፒዩፕልስ ዲሞክራቲክ ፓርቲ፣ ከቀድሞው የአገሪቱ የጦር መሪ ሙሃማዱ ቡሃሪ እና ኦል ፕሮግሬሲቭስ ኮንግረስ ከተሰኘው ተፎካካሪ ፓርቲ ከፍተኛ ፉክክር ይጠብቃቸዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የገለጸው ዘገባው፤ቡሃሪ በስልጣን ላይ ያለው የጆናታን መንግስት የቦኮ ሃራምን የጥፋት እንቅስቃሴ ለመግታት አቅምም ሆነ ፈቃደኝነት ይጎድለዋል ሲሉ መተቸታቸውንና እሳቸው ስልጣን ላይ ከወጡ ቦኮ ሃራምን በወራት ጊዜ ውስጥ እንደሚያጠፉ ቃል መግባታቸውን ጠቁሟል፡፡
የናይጀሪያ መንግስት ምርጫው መራዘሙን ማስታወቁን ተከትሎ፣ ውሳኔው በአለማቀፍ ደረጃ እየተተቸ እንደሚገኝ የዘገበው ዘ ኢንዲፔንደንት በበኩሉ፤የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጆን ኬሪ በአገሪቱ ያሉ የጸጥታ ስጋቶች ምርጫን ለማራዘም በቂ ምክንያት ሊሆኑ አይችሉም ማለታቸውን ጠቁሟል፡፡
የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ጸሃፊ ፊሊፕ ሃሞንድ በበኩላቸው፤ ናይጀሪያ ሽብርተኝነትን ለመዋጋት የምታደርገውን ጥረት የምንደግፍ ቢሆንም፣ በአገሪቱ ያለው የጸጥታ ችግር ናይጀሪያውያን ዲሞክራሲያዊ መብቶቻቸውን እንዳይጠቀሙ ለማገድ ምክንያት ሊሆን አይገባም በማለት ምርጫው መራዘሙን ተችተዋል፡፡

ግብጽ ከሁለት አመታት በፊት በሚናያ ግዛት በሚገኝ የፖሊስ ማዘዣ ጣቢያ ላይ ጥቃት ፈጽመዋል በሚል ባለፈው ሰኔ ወር የሞት ፍርድ ከጣለችባቸው 183 የሙስሊም ብራዘር ሁድ አባላት መካከል፣ የሰላሳ ስድስቱን የሞት ቅጣት ማንሳቷንና የፍርድ ሂደቱ እንደገና እንዲታይ ባለፈው ረዕቡ መወሰኑን ቢቢሲ ዘገበ፡፡ ፍርድ ቤቱ ሞሃመድ ባዲ የተባሉትን መንፈሳዊ መሪ ጨምሮ በ36 ተከሳሾች ላይ ጥሎት የነበረውን የሞት ቅጣት ለማንሳትና ፍርዱ እንደገና እንዲታይ የወሰነበትን ምክንያት በግልጽ አለማስታወቁን ዘገባው አመልክቷል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅትን ጨምሮ በርካታ አለማቀፍ ተቋማት በ183 የሙስሊም ብራዘር ሁድ ደጋፊዎች ላይ ፍርድ ቤቱ የጣለውን የሞት ቅጣት በአጽንኦት ሲተቹት እንደነበርም አስታውሷል፡፡
የሞት ፍርዱ ከተጣለባቸው 183 ግብጻውያን መካከል 147 የሚሆኑት የፍርድ ሂደታቸው በሌሉበት ሲታይ መቆየቱንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡