Administrator

Administrator

   ሰሜን ኮርያ የአገሪቱ ወንዶች ጸጉራቸውን ከ2 ሴንቲ ሜትር በላይ እንዳያሳድጉ የሚከለክል ትዕዛዝ ያስተላለፈች ሲሆን የመዲናዋ ባለስልጣናት ጸጉራቸውን ከዚህ በላይ ያሳደጉትን ዜጎች በቁጥጥር ስር እያዋሉ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ኪም ጆንግ ኡን በሚታወቁበት የጸጉር ስታይል አሳጥረው እንዲቆረጡ እያስገደዱ መሆኑ ተዘገበ፡፡
ዘ ቴሌግራፍ፣ ቾሱን ኢቦ የተባለው የደቡብ ኮርያ ጋዜጣ ሰሞኑን ያወጣውን ዘገባ ጠቅሶ እንዳለው፣ የመዲናዋ አስተዳደር የፒንግያንግ ነዋሪ የሆኑ ወንዶች ጸጉራቸውን በኪም ጆንግ ኡን ስታይል በመቆረጥ፣ለፕሬዚዳንቱ ያላቸውን ክብር እንዲያሳዩ ትዕዛዝ አስተላልፏል፡፡
የከተማዋ ባለስልጣናት ያሰማሯቸው የዩኒቨርሲቲ ተማሪ ተቆጣጣሪዎች፣ መቀስ ይዘው በየቦታው እየተዘዋወሩ፣ረጃጅም ጸጉር ያላቸውን ወንዶች አሳጥረው ማስተካከል መጀመራቸውም ተነግሯል፡፡
የከተማዋ ሴቶችም ቢሆኑ የጸጉር አሰራራቸውን የፕሬዚዳንቱ ሚስት የሆኑት ቀዳማዊት እመቤት ሪ ሶል ጁ፣ በሚያዘወትሩት የጸጉር አሰራር መልክ እንዲያስተካክሉ ታዝዘዋል ብሏል ዘገባው፡፡

ከ5 አመታት በኋላ ከ30 ዜጎቿ አንዱ ሚሊየነር ይሆናል
   ዌልዝ ኢንሳይት የተባለው አለማቀፍ የኢኮኖሚ መረጃ ተንታኝ ተቋም፣ ሲንጋፖር በመጪዎቹ አምስት አመታት በየአመቱ በአማካይ 37 ሺህ 600 ያህል ተጨማሪ አዳዲስ ሚሊየነሮችን ታፈራለች ተብሎ እንደሚገመትና በ2020 የፈረንጆች አመት ከ30 ሲንጋፖራውያን አንዱ ሚሊየነር ይሆናል ተብሎ እንደሚጠበቅ መግለጹን ሲኤንኤን ዘገበ፡፡
ይህ የአዳዲስ ሚሊየነሮች ቁጥር በአገር ውስጥ የሚፈጠሩ ሚሊየነሮችን ብቻ ሳይሆን፣ ከውጭ አገራት ወደ ሲንጋፖር የሚገቡትንም ይጨምራል ያለው ዘገባው፣ ሲንጋፖር በአሁኑ ወቅት በድምሩ 806 ቢሊዮን ዶላር የሚደርስ የተጣራ ሃብት ያካበቱ 154 ሺህ ያህል ባለ ከፍተኛ ገቢ ዜጎች እንዳሏትና እነዚህ ሚሊየነሮች ከአጠቃላዩ የአገሪቱ የህዝብ ቁጥር 3 በመቶ ያህሉን እንደሚይዙም ጠቁሟል፡፡
ወደ አገሪቱ የሚጎርፉና በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች የሚሰማሩ ህንዳውያንና ቻይናውያን ሚሊየነሮች ቁጥር እየጨመረ እንደሚገኝ የጠቆመው ዘገባው፣ በሲንጋፖር የቀጠለው የፋይናንስ ገበያ መሟሟቅ፣የግል ባንኮች መስፋፋታቸውና የላቀ ጥራት ያለው የአኗኗር ዘዬዋ፣ ከፍተኛ ሃብት ያላቸውን በርካታ የተለያዩ አገራት ዜጎች ወደ አገሪቱ መሳባቸውን ይቀጥላሉ መባሉንም አስታውቋል፡፡

   እስካለፈው ጥቅምት በነበሩት አስራ ሁለት ወራት የተመዘገበው አለማቀፍ አማካይ የሙቀት መጠን በታሪክ ከፍተኛው እንደሆነና ሊጠናቀቅ አንድ ወር ብቻ የቀረው የፈረንጆች አመት 2015 በአለማችን እጅግ ሞቃቱ አመት ይሆናል ተብሎ እንደሚጠበቅ የአለም የሜቲሪዮሎጂ ድርጅት ማስታወቁን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
ከ2011 እስከ 2015 የነበረው የአምስት አመታት ጊዜ፣ በአለማችን ታሪክ እጅግ ከፍተኛው ሙቀት የተመዘገበበት እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ የድርጅቱ ተመራማሪዎች የዘንድሮው የአለማችን አማካይ የሙቀት መጠን ከፍተኛ ሊሆን የቻለው የሰው ልጅ የሚፈጥረው የአለም የሙቀት መጠን በመጨመሩና የኤል ኒኖ ክስተት ባደረሱት የከፋ ተጽዕኖ ሳቢያ ነው ማለታቸውን ጠቁሟል። በተገባደደው የፈረንጆች ዓመት በአለማችን የበካይ ጋዞች ልቀት መጠን ከዚህ በፊት ታይቶ የማይታወቅበት ከፍተኛ ደረጃ ላይ ደርሷል ያለው የአለም የሜቲሪዮሎጂ ድርጅት፣ የውቅያኖሶች የሙቀት መጠንም እስካሁን ከተመዘገቡት መጠኖች ከፍተኛው ደረጃ ላይ እንደደረሰ አስታውቋል፡፡
በዘንድሮው አመት በርካታ የአለማችን አገራት በታሪካቸው ከፍተኛውን የሙቀት መጠን አስተናግደዋል ያለው ዘገባው፣ ቻይና ባለፉት 12 ወራት አይታው የማታውቀውን ሙቀት እንዳሳተናገደች ጠቁሞ፣ አፍሪካም በአመቱ ከፍተኛውን ሙቀት እንዳስመዘገበች አውስቷል፡፡

   መኖሪያቸውን ለንደን ባደረጉት ደራሲ ኤርሚያስ ሚካኤል (ሕርይቲ) የተፃፈው “የሚበርድ ፀሐይ” የተሰኘ የግጥም መድበል፤ ነገ ጠዋት ከ3፡00 ሰዓት ጀምሮ በሀገር ፍቅር ቴአትር ቤት ትንሷ አዳራሽ ይመረቃል፡፡ መጽሐፉ በተለያዩ ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ ትኩረት አድርገው የተፃፉ 78 ግጥሞችን አካትቷል፡፡ በምረቃው ሥነሥርዓት ላይ ወጣትና አንጋፋ ገጣሚያን የግጥም ስራዎቻቸውን የሚያቀርቡ ሲሆን ታዳሚያን በኮሜዲ ዝግጅቶች እንደሚዝናኑም የዝግጅቱ አስተባባሪ አብርሃም ግዛው ኢንተርቴይመንት የፕሬስ ስራዎች ድርጅት ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡

Saturday, 28 November 2015 14:11

የዘላለም ጥግ

(ስለ ጦርነት አስከፊነት)
• ኦ ሰላም! በስምሽ ስንት ጦርነቶች ታወጁብሽ።
አሌክሳንደር ፖፕ
• ጦርነት ጀብዱ አይደለም፡፡ በሽታ ነው፡፡ እንደ
ታይፈስ ዓይነት በሽታ፡፡
አንቶይኔ ሊ ሴይንት አክሱፔሪ
• ጦርነት እንደ ወንጀል መቆጠር አለበት፤
ቀስቃሾቹም እንደ ወንጀለኞች መቀጣት
አለባቸው፡፡
ቻርለስ ኢቫንስ ሁግስ
• ሰዎች አሁን ጦርነትን ማጥፋት ካልተሳካላቸው፤
ስልጣኔና የሰው ልጅ አከተመላቸው፡፡
ሉድዊግ ቮን ሚሴስ
• ጦርነት ለተሸናፊው ብቻ ሳይሆን ለአሸናፊውም
ጭምር ጐጂ ነው፡፡
ሉድዊግ ቮን ሚሴስ
• “እማዬ፤ ጦርነት ምንድን ነው?” ብሎ የሚጠይቅ
ህፃን ለመውለድ አልማለሁ፡፡
ኢቭ ሜሪያም
• አሜሪካ በ ሁሉም ነ ገር የ ዓለም መ ሪ መ ሆን
አለባት የሚለውን ሃሳብ ማስወገድ አለብን፡፡
ፍራንሲስ ጆን ማክኮኔል
• ጦርነቶችን የሚጀምሩት ወታደሮች አይደሉም፤
ፖለቲከኞች ናቸው፡፡
ጀነራል ዊሊያም ዌስትሞርላንድ
• ሰላም ከማስፈን ይልቅ ጦርነት መፍጠር በጣም
ቀላል ነው፡፡
ጆርጅስ ክሌሜንስዩ
• ጦርነት የፖሊሲ ክስረት ነው፡፡
ሃንስ ቫን ሲክት
• የታላላቅ መንግስታት ኃላፊነት ማገልገል እንጂ
ዓለም ላይ መግነን አይደለም፡፡
ሃሪ ኤስ. ትሩማን
• ለወታደራዊ ጀግንነት ትኩረት መስጠት
የፍልስፍና ድህነትን አመልካች ነው፡፡
ሄንክ ሚድልራድ
• በሰላም ጊዜ ልጆች አባቶቻቸውን ይቀብራሉ፤
በጦርነት ዘመን አባቶች ልጆቻቸውን
ይቀብራሉ፡፡
ሔሮዱተስ

Saturday, 28 November 2015 14:09

የጸሐፍት ጥግ

(ስለ ፕሬስ)


• አንድ ሚሊዬነር 10 ጋዜጦች ስላሉት የፕሬስ
ነፃነት የተቀዳጀን ይመስለናል፡፡ 10 ሚሊዮን
ሰዎች ግ ን ም ንም ጋ ዜጦች የ ላቸውም - ይ ሄ
የፕሬስ ነፃነት አይደለም፡፡
አናስታስ ማኮያን
• በሌሎች አገራት ፕሬሱ፣ መፃህፍትና
ማናቸውም ዓይነት የሥነጽሑፍ ሥራዎች
ሳንሱር የሚደረጉ ከሆነ፣ እነሱን ነፃ ለማውጣት
ጥረታችንን እጥፍ ማድረግ አለብን፡፡
ፍራንክሊን ዲ. ሩስቬልት
• ሌላ ቦታ እንደተናገርኩት፤ ነፃ ፕሬስ አንድን
አገር ጠንካራና የበለጠ ስኬታማ ለማድረግ
ያግዛል፤ እኛን መሪዎችንም የበለጠ ውጤታማ
ያደርገናል፤ ምክንያቱም ከፍተኛ ተጠያቂነትን
ይፈልጋል፡፡
ባራክ ኦባማ
• በእኔ አስተያየት፣ የዲሞክራሲ የማዕዘን ድንጋይ
ነፃ ፕሬስ ነው እሱ - ነው የማዕዘን ድንጋዩ፡፡
ሚሎስ ፎርማን
• ነፃ ፕሬስ ጥሩ ወይም መጥፎ ሊሆን
እንደሚችል የታወቀ ነው፡፡ በእርግጠኝነት ግን
ያለ ነፃነት ፕሬሱ መጥፎ ከመሆን ውጭ ፈጽሞ
ሌላ አማራጭ የለውም፡፡
አልበርት ካሙ
• ነፃ ፕሬስ የተከበረ ፕሬስ መሆን አለበት፡፡
ቶም ስቶፓርድ
• የፕሬስ ነፃነት የተረጋገጠው የፕሬስ ውጤት
ባለቤት ለሆኑት ብቻ ነው፡፡
ኤ.ጄ ላይብሊንግ
• ፕሬሱን መገደብ ህዝብን መስደብ ነው፤
የተወሰኑ መፃሕፍት እንዳይነበቡ መከልከል
ነዋሪዎች ሞኞች ወይም ባሪያዎች ናቸው ብሎ
ማወጅ ነው፡፡
ክላውዴ አድሬይን ሄልቬቲየስ
• ጋዜጠኝነት የተደራጀ ሃሜት ነው፡፡
ኤድዋርድር ኤግልስቶን
• የዲሞክራሲ ጫጫታ ደስ ይለኛል፡፡
ጄምስ ቡቻናን
• ሚዲያ የባህላችን የነርቭ ሥርዓት ነው፡፡
ጌሪ ማልኪን

    ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አባት፣ ወንድ ልጁን ይዞ፣ አህያውን ለመሸጥ ወደገበያ እየሄደ ነበር፡፡ መንገድ ላይ የሆኑ ኮረዶች እየሳቁ እያላገጡ፣
“እንደነዚህ አባትና ልጅ ያሉት ጅሎች በዓለም ላይ ታይተው አይታወቁም፡፡ በዚህ አቧራማ ጎዳና አህያው ላይ ወጥተው እየጋለቡ መሄድ ሲችሉ፤ በእግራቸው ይኳትናሉ!” አሉ። አባትየው ኮረዶቹ ያሉት ልክ ነው ብሎ አሰበ፡፡ ስለዚህ ልጁን አህያው ላይ አወጣውና እሱ በእግሩ መጓዝ ጀመረ፡፡ ጥቂት እንደተጓዙ የዱሮ ወዳጆቻቸው አዩዋቸው፡፡
እንዲህም አሉ፤
“ይሄን ልጅ በጣም አወማጠልከው፡፡ አንተን የሚያህል ሽማግሌ በእግሩ እየሄደ ይሄ ወጣት በአህያ መሄዱ ነውር ነገር ነው፡፡ “ኧረ በእግሩ ይሂድ፡፡ ወጣት ሮጠና አይደለም እንዴ?!”
አባት የዱሮ ወዳጆቹን ምክር ተቀበለ፡፡ ልጁን ና ውረድ ብሎ ሲያበቃ፣ በእሱ ቦታ ራሱ ፊጥ አለ፡፡ ብዙም ሳይሄድ እናቶችና ልጆቻቸው ብቅ አሉ፡፡ እነሱም፡-
“ምን ያለው ራስ - ወዳድ አባት ነው እባካችሁ! ራሱ ተዝናንቶ በምቾት እየጋለበ፣ ልጁን በእግሩ መከራ ያሳየዋል!” እያሉ ሲሳለቁ አባትየው ሰማ፡፡ ይሄንንም አመዛዘነና ትችቱን ተቀብሎ ልጁን ከጀርባው አፈናጠጠው፡፡
አሁንም ብዙም ሳይጓዙ መንገደኞች ያገኟቸዋል፡፡ እነሱም፤ “ለመሆኑ ይቺ አህያ የራስህ ንብረት ናት፤ ወይስ እንዲያው ከጫካ ያገኘሃት የዱር አውሬ ናት”
አባትየውም፤ “ኧረ የራሴ ናት! እንዲያውም እዚህ ታች ገበያ ልሸጣት አስቤ ነው የምሄደው”
“ኧረ የሰማያቱ ያለህ! እዚያ ስትደርስ‘ኮ አንደኛዋን ሞታ ነው የምትገኘው! ይልቁንም ተሸክማችሁ ብታደርሷት ነው የሚሻለው!
አባትየው - “ዕውነታችሁን ነው!” ብሎ ምክሩን ተቀብሎ ሁለቱም ወረዱና አህያዋን አሰሩዋትና በትልቅ እንጨት አንጠለጠሉ፡፡ ወደሚቀጥለው ከተማም ደረሱ፡፡
አባትና ልጅ አህያ ያንጠለጠሉበትን ትርዒት ያየ የከተማው ሰው ሁሉ፤ ግማሹ ዕብድ ናቸው አለ፡፡ ግማሹም በዱላ ይመቷቸው ጀመር፡፡ አህያውን ተሸክመው በወንዝ ላይ ወዳለው ድልድይ ሄዱ፡፡ አህያው የህዝቡ ጩኸት በእንግዳ ሆኖበት እየተንፈራገጠ፣ የታሰረበትን ገመድ በጠሰና ተስፈንጥሮ ወንዙ ላይ ወደቀ፡፡ በዚያው ሰምጦ ሞተ፡፡ ዕድለ ቢሱ አባት በመከራ ወደ ቤቱ ተመለሰ፡፡ ሁሉንም ሰዎች አረካለሁ ብሎ አንዱንም ሰው ሳያረካ፤ አህያውንም አጥቶ ቀረ።
*           *            *
አማካሪን ሁሉ ከየአቅጣጫው እንዲያውም ተቃራኒውን ሀሳብ ጭምር፣ መስማትና መቀበል፣ ማታ ማንም ፍሬ ሳያፈራ እንዲቀር ያደርገዋል፡፡ በየጊዜው የሚለዋወጥ አቋም አንዱንም በወግ ለመያዝ ሳንችል እንድንቀር ያደርገናል፡፡ በዚያ ላይ ደግሞ አንዱን በሥነ ስርዓት ለፍፃሜ ሳናበቃ ሜዳ ላይ እንድንወድቅ እንሆናለን፡፡ ዕቅደ ብዙ መሆን ብቻውን ከግብ አያደርስም፡፡ ይልቁንም ቅደም ተከተል አስይዘን፣ የከፋውን ችግር መጀመሪያ መፍታት፣ ምንም ይሁን ምን ችግርን አለመሸሸግ፣ በግልፅ ድክመትን ማመን፣ አለቃ እንዳይቆጣ ተብሎ እቅጩን አለመናገርን ማስወገድ፣ ሀገርን ከፓርቲ፣ ከቡድን ወይም ከግለሰብ ጥቅም ማስቀደም ወዘተ መልካም አካሄድ ነው፡፡ ከሁሉም ቁልፍ ነገር በዕውቀት ማመን ነው። በዕውቀት ላይ የተመሰረተ የሀገር ግንባታ ርዕዩ ሩቅ ይሆናል፡፡ የተገነባው እንዳይፈርስ ባለቤት ሊኖረው እንደሚገባ አለመዘንጋት ነው፡፡ የተሰራው መንገድ፣ ባቡሩ፣ ግድቡ ወዘተ. በኃላፊነት የሚይዛቸው ከወራት የዘለለ ሀገር ወዳድነት ያለው አመራር ይሻሉ፡፡
ድርቁን እኛው በኛው እንመክተው ካልን ቁርጠኝነታችንን በውል መፈተሽ ደግ ነው፡፡ ምግብና ሌላ እርዳታ በአግባቡ መዳረሱን ለማየት ረዥም መንገድ ተጉዞ የደረሰው ባቡር “ላሜ ወለደች” ያሰኘን ቢሆንም፤ ቀጣዩ ተግባር ስኬታማ እንዲሆን ጠንቃቃ ትኩረት ይጠይቃል፡፡
የሀገራችን የኢኮኖሚ ዕድገት ነገር ሁሌም አሳሳቢ እንደሆነ ነው፡፡ እንኳን ለአዘቦቱ ሰው፣ ለክቱ የኢኮኖሚክስ ባለሙያም አወዛጋቢና አነጋጋሪ ነው! ለኢኮኖሚው ዕድገት ችግር የሚሆነው የሰለጠነ የሰው ኃይል ማነስ ነው የሚሉ ያሉትን ያህል፣ የሰው ኃይል እጥረት አሳሳቢ አይደለም የሚሉም አሉ፡፡ መዋቅራዊ ለውጥ ያስፈልጋል የሚሉና ለጊዜው አያስፈልግም የሚሉም ይኖራሉ፡፡ ከገጠር ወደ ከተማ ፍልሰት፣ ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ መር ሥርዓተ ኢኮኖሚ ስንሸጋገር፣ አይቀሬ ክስተት ይሆናል ሲባል የህዝብ ብዛት ፍንዳታ ምን መፍትሔ ይኖረው ይሆን ብሎ መጠየቅም ያባት ነው፡፡ የአገሪቱ የቅጥር ሁኔታም አሳሳቢ ስለመሆኑና ለውጥ ስለማስፈለጉ ብዙ እየተነገረ፣ “ቄሱም ዝም፤ ዳዊቱም ዝም” እንደሆነ አለ፡፡
አሁንም ከዘርፈ ብዙ ችግሮቻችን አኳያ ቅደም  - ተከተል ማበጀት ወሳኝ ነው፡፡ ሳይታሰብ ቅድሚያ የተሰጠው፣ ግን ሊዘገይ ይችል የነበረ ጉዳይ ካለ፤ ቆም ብሎ መፈተሽ ተገቢ ነው። ባንድ ወቅት አሳሳቢ የመሰለን ችግር በሌላ ወቅት ቀላል ሆኖ ሊገኝ እንደሚችል ማስተዋል ያሻል፡፡ መሥሪያ ቤቶች “በጉዳይ - ገዳይ” እጅ ላይ እየተንሳፈፉ፣ ቀልጣፋ የሥራ አመራር አለ ለማለት ያዳግታል፡፡ አገራችን “አንዱ ያለማ አንዱ ያደለማ” አጣብቂኝ ውስጥ ናት፡፡ በዚህ ዓይነት ወደፊት ፈቀቅ እያልን ነው ብንል የዋህነት ያለብን ያስመስላል፡፡ በየቢሮው የምናየውና በአደባባይ የምንሰማው መራራቅ የለበትም፡፡ አንዱ በታታሪነት ደፋ - ቀና ሲል ሌላው በዳተኝነት “ከልኩ አያልፍም” እያለ የምንጓዘው ጉዞ እየፃፉ እንደማጥፋት ነው፡፡ የሩቅ ዕቅዳችንንና የረዥም ጊዜ ራዕያችንን እያወደስን የቅርብ - የቅርብ ፍሬዎቻችንን በወጉ ሳንሰበስብ ከቀረን፣ ከአፍ እስከገደፉ የሞላውን ወሬ ነጋሪና ጉዳይ አስፈፃሚ በጊዜ ካልገደብን፤ “እሾክ ብቻ ሆነ እግሬን ብዳብሰው እንዴት መራመጃ መሄጃ ያጣል ሰው” እንደሚባለው ነው የምንሆነው፡፡ ከልብ አገርን ማሳደግ የምንሻ ከሆነ፣ “ብዙ ከያዘ ነገረኛ፣ ትንሽ የያዘ ሀቀኛ ይስጥህ” የሚለውን ተረት ልብ እንበል!

      በአባይ ወንዝ አጠቃቀምና በህዳሴ ግድብ ግንባታ ሳቢያ ለ5 ዓመት እየከረረና እየረገበ የዘለቀው የኢትዮጵያና የግብፅ ግንኙነት፤ ከሰሞኑ ትኩሳት አገርሽቶበታል፡፡
የግብፁ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፣ የህዳሴ ግድብ ግንባታ እንዲዘገይ ማድረግ እንችላለን በማለት እንደተናገሩ ሰኞ እለት የዘገቡ አልጀዚራና ምስር ጆርናል፤ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በበኩላቸው፤ “ግብፅ ኢትዮጵያን የመውረር አቅም የላትም” በማለት ምላሽ እንደሰጡ ፅፈዋል፡፡ ይህንን ሲዘግቡም፣ መረጃውን ያገኘነው ከአዲስ አድማስ ነው ብለዋል፡፡ ነገር ግን፤ በየትኛው የአዲስ አድማስ እትም ዘገባው እንደወጣ ቀኑን አልጠቀሱም፡፡ በቅርብ ሳምንታት ካገረሸው ትኩሳት ጋር ተያይዞ፤ እንዲህ አይነት ዘገባ በአዲስ አድማስ ባይወጣም፤ የግብፅ መንግሥት፣ በግድብ ግንባታው ላይ ተቃውሞ ከማሰማት አልፎ ዛቻና ማስፈራሪያ እስከመሰንዘር እንደሚደርስ ግን በተለያዩ ጊዜያት ተዘግቧል፡፡ የጦርነት ዛቻ ተቀባይነት እንደሌለውና እንደማያዋጣ የኢትዮጵያ መንግሥት በተደጋጋሚ መግለፁም ይታወሳል፡፡ በተለይ አሁን፣ የግብፅ ትኩረት በኢኮኖሚ ፈተናዎችና በአሸባሪዎች ጥቃት ላይ መሆን ሲገባው፤ ወደ ጦርነት ዛቻ ማዘንበል እንደማያዋጣም ይገለፃል፡፡
በቅርቡ የህዳሴ ግድብ፣ በከፊል ኤሌክትሪክ ለማመንጨት ውሃ የሚያጠራቅምበት ደረጃ ላይ መድረሱ የተዘገበ ሲሆን፤ የግብፅ መንግሥት በበኩሉ፤ የግድቡ ግንባታ ለ6 ወር እንዲቋረጥ ሊጠይቅ ይችላል የሚሉ መላምቶች ተሰንዝረዋል። ካሁን በፊትም በየጊዜው ተመሳሳይ ጥያቄዎች ተሰንዝረው የነበረ ቢሆንም፤ የግድቡ ግንባታ ለአንድ ቀንም አይቋረጥም በማለት የኢትዮጵያ መንግስት ምላሽ ሰጥቷል፡፡ 

Saturday, 28 November 2015 08:56

የቀልድ ጥግ

(በፍቺና ጥርጣሬ ዙሪያ)
ሚስት የቤተሰቡ ጠበቃ ዘንድ ትደውልና
በአስቸኳይ እንደምትፈልገው ትነግረዋለች፡፡
ጠበቃውም ያለችበት ሥፍራ ከመቅጽበት
ይደርስና ለምን እንደፈለገችው ይጠይቃታል፡፡
“ምን ገጥሞሽ ነው እንዲህ በአስቸኳይ
የፈለግሽኝ?”
“ከባሌ ጋር መፋታት እፈልጋለሁ” አለች እሳት
ለብሳ እሳት ጐርሳ፡፡
“ምነው ደህና አልነበራችሁ እንዴ?”
“የመጨረሻ ልጃችን አባት እሱ አይደለም የሚል
ከፍተኛ ጥርጣሬ አለኝ” ብላው እርፍ!!
* * *
አዳም ያለ አመሉ ለተወሰኑ ቀናት ውጭ እያመሸ
በመግባቱ፣ ሄዋን ጥርጣሬ ቢጤ አደረባት፡፡
“እንዳትዋሸኝ…ከሌላ ሴት ጋር መቅበጥ ጀምረሃል
አይደል!?” ስትል ታፋጥጠዋለች፡፡
“የምን ሌላ ሴት ነው የምታወሪው? አንቺው ነሽ
ሌላ ማን አለ!” አዳም ግራ በተጋባ ስሜት መለሰላት፡፡
የዚያኑ ዕለት ሌሊት አዳም ጥልቅ እንቅልፍ ላይ
ሳለ፣ ሄዋን ደረቱ አካባቢ በጣቷ ስትጫነው ባንኖ
ይነሳና፤ “ምን እያደረግሽ ነው?” ይጠይቃታል፡፡
“ጐድንህን እየቆጠርኩ” መለሰችለት፡፡
(አዳም ምን ብሎ ይሆን?

12 ሄኮፕተሮችንና 4 ተዋጊ ጀቶችን ለመግዛት የተመደበ ገንዘብ በልተዋል ተብለዋል
    የቀድሞው የናይጀሪያ ብሄራዊ ደህንነት አማካሪ ሳምቦ ዳሱኪ የአገሪቱን አሸባሪ ቡድን ቦኮ ሃራም ለመታገል ለተጀመረው ብሄራዊ ወታደራዊ ዘመቻ ጥቅም ላይ የሚውሉ የጦር መሳሪያዎችን ለመግዛት የተመደበውን 2 ቢሊዮን ዶላር ለግል ጥቅማቸው አውለዋል በሚል የእስር ትዕዛዝ እንደተላለፈባቸው ቢቢሲ ዘገበ፡፡ግለሰቡ 12 ሄኮፕተሮችን፣ አራት ተዋጊ ጀቶችንና ተቀጣጣይ ፈንጂዎችን ለመግዛት በተደረገው ድርድር በነበራቸው ተሳትፎ ገንዘቡን ለግል ጥቅማቸው አውለዋል ቢባሉም፣ እሳቸው ግን ድርጊቱን እንዳልፈጸሙ ተናግረዋል፡፡
አዲሱ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ግለሰቡ እንዲታሰሩ ትዕዛዝ የሰጡት ሰሞኑን ቢሆንም፣ ግለሰቡ ግን ህገወጥ የጦር መሳሪያ ይዘው በመገኘት ወንጀል ተከሰው በቁም እስር ላይ እንደነበሩና ጉዳያቸውን የያዘው ፍርድ ቤትም ፓስፖርታቸው ተመልሶላቸው ህክምናቸውን በእንግሊዝ እንዲከታተሉ ቢፈቅድላቸውም መንግስት ከአገር እንዳይወጡ እንደከለከላቸው ዘገባው ገልጧል፡፡
የፕሬዚዳንት ቡሃሪ ቃል አቀባይ፣ ግለሰቡ የሰሩት የሙስና ወንጀል በሺህዎች የሚቆጠሩ የአገሪቱ ዜጎች በአሸባሪው ቦኮ ሃራም ለሞት እንዲዳረጉ ምክንያት ሆኗል ማለታቸውን ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡ግለሰቡ በስልጣን ላይ በነበሩበት ጊዜ ሁሉ የአገራቸውን ብሄራዊ ጥቅም የሚያስጠብቅ ህጋዊ ስራ ሲሰሩ እንደነበር ገልጸው፣ ይሄን ያህል ገንዘብ በሙስና ለግል ጥቅማቸው አውለዋል፤የተጠቀሱት የጦር መሳሪያዎችም በአግባቡ ተገዝተው ለመንግስት አልደረሱም የሚለው ውንጀላ እንዳሳቃቸው ተናግረዋል፡፡