Administrator

Administrator

ሠኞ እለት አንድ ሰው በባቡር አደጋ ህይወቱ አልፏል የኢትዮ - ጅቡቲ መስመርን ሁለቱ ሃገራት በጋራ ያስተዳድራሉ  

    በአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ትራንስፖርት አገልግሎት ላይ እያጋጠመ ያለውን የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ ለመቋቋም ጀነሬተር ሊገዛ መሆኑ የተገለፀ ሲሆን ባቡሩ ባለፈው ሠኞ ሥራ ከጀመረ ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ በደረሰ አደጋ የአንድ ሠው ህይወት ጠፍቷል፡፡
የጀነሬተር ግዢውን ለማከናወን የምድር ባቡር ኮርፖሬሽንና የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል በጋራ አጥተነው ወደ ሂደት እየተገባ መሆኑን የኮርፖሬሽኑ የኮሚኒኬሽን ኃላፊ ገልፀዋል፡፡
የትራንስፖርት አገልግሎቱ ዋነኛ ችግር የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ መሆኑን የጠቀሱት ኃላፊው፤ የሚገዙት ጀነሬተሮች መብራት እንደጠፋ ወዲያው የሚንቀሳቀሱ በመሆኑ ትራንስፖርቱ ሳይቋረጥ ያለ እንከን አገልግሎቱን ለመስጠት ያስችላል ብለዋል፡፡
የከተማዋ ቀላል ባቡር ትራንስፖርት ከጀመረ ወዲህ አንድም አደጋ ደርሶ እንደማያውቅ የጠቀሱት ኃላፊው፤ ባለፈው ሠኞ ከምሽቱ 4 ሰዓት ላይ በኡራኤልና መገናኛ መሃል ባለው መስመር አጥሩን በመዝለል ቀጥታ የባቡሩ መስመር ላይ የገባ ግለሰብ ህይወቱ ማለፉን  ገልፀዋል፡፡ ግለሰቡ የአዕምሮ ህመምተኛ ሳይሆን እንደማይቀር መጠርጠሩንና በህክምና ለማረጋገት እየተሞከረ እንደሆነ የጠቀሱት ኃላፊው፤ ባቡሩን ማቆም በማይቻልበት ቅርብ ርቀት ላይ የነበረ በመሆኑ ህይወቱን ማትረፍ ሳይቻል መቅረቱን ኃላፊው ጠቅሰዋል፡፡ ባቡሮቹ ጠዋት 12 ሰዓት ስራ ከመጀመራቸው በፊት በየቀኑ ከሌሊቱ 10 ሰዓት ጀምሮ ተሳፋሪ ሳይጭኑ ሙከራ እንደሚያደርጉና አጠቃላይ የቴክኒክ ፍተሻ ተደርጎላቸው የሚጀምሩ በመሆኑና ህብረተሰቡ ለአደጋ ያለው ግንዛቤ እያደገ በመምጣቱ፣ የተፈራውን ያህል አደጋ አለመከሰቱን ተናግረዋል ኃላፊው፡፡
በአሁን ሰዓት ለከተማዋ ትራንስፖርት በሁለቱ መስመሮች 28 ባቡሮች የተመደቡ ሲሆን 10 ባቡሮች በቅርቡ ይጨመራሉ ተብሏል፡፡ አሁን ያሉት በቀን እስከ 120 ሺህ ሰው በማጓጓዝ በቀን እስከ 4 መቶ ሺህ ብር ገቢ እያስገቡ መሆኑንም ኃላፊው ጠቁመዋል፡፡ ለአካል ጉዳተኞችና ለአቅመ ደካሞች ታስበው በተወሰኑ ባቡር ጣቢያዎች የተዘጋጁ ሊፍቶችና ስካሌተሮች ቀደም ብሎ አገልግሎት እንዲሰጡ በተደረገበት ወቅት በጥንቃቄና በአጠቃቀም ችግር ጉዳት አጋጥሟቸው እንደነበር ያወሱት አቶ ደረጃ፤ ጥገና ከተደረገላቸው በኋላ በዚህ ወር መጨረሻ አገልግሎት መስጠት ይጀምራሉ ብለዋል፡፡ የወረቀት ቲኬቶች ለመጭበርበር ምቹ መሆናቸውን የጠቀሱት ሃላፊው፤ የኤሌክትሮኒክስ ቲኬት አገልግሎትን ተግባራዊ ለማድረግ ቲኬቶቹ በውጭ ሃገር እንዲዘጋጁ መታዘዙንና የሂሳብ መሙያ ማሽኖች ተከላ እየተከናወነ መሆኑን ጠቁመው፤ በቅርቡ አገልግሎቱ ይጀምራል ብለዋል፡፡
የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ትራንስፖርት ሲጀምር 58 በመቶ ያህሉ የባቡር ሠራተኞች ቻይናውያን፣ 42 በመቶ ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን ያስታወሱት ኃላፊው፤ በአሁን ወቅት ኢትዮጵያውያኑ በረዳትነት በስፋት ባቡሩን እየዘወሩ መሆኑንና ከ3 ዓት በኋላ ሙሉ ለሙሉ ከቻይናውያኑ እንደሚረከቡ ኃላፊው አስረድተዋል፡፡
የድርጅቱ ባለሙያዎች ተቋሙ ያለውን አቅም ከግምት ውስጥ ያስገባ ደሞዝ እንደሚከፈላቸውና ጥቅማ ጥቅም እንደሚያገኙ የጠቀሱት አቶ ደረጀ፤ በቃሊቲና በሃያት የባቡር ማሳደሪያዎች አካባቢ የመኖሪያ ቤት እንደተሰጣቸውና የምግብ አገልግሎት እንዲያገኙም ተደርጓል ብለዋል፡፡   
የአዲስ አበባ - ጅቡቲ የባቡር መስመርን የስራ ክንውን በተመለከተ የተጠየቁት ኃላፊው፤ አጠቃላይ ስራው ከ90 በመቶ በላይ መጠናቀቁን፣ በአሁን ሰዓት የኤሌክትሪክ መስመር ዝርጋታና ከባቡር ጣቢያዎች ወደ ዋና አውራ ጎዳናዎች የሚያደርሱ መንገዶች እየተገነቡ መሆኑን በመጥቀስ ባቡሩ በቅርቡ አገልግሎት መስጠት ይጀምራል ከተባለው ጊዜ የዘገየ ቢሆንም በዚህ ሰዓት ሙሉ ለሙሉ ሰራ ይጀምራል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል፡፡ አንገብጋቢ ለሆነው የድርቁ ችግር ሲባል ይፋዊ የሙከራ ስራ አለመጀመሩን ያወሱት አቶ ደረጀ፤ ከህዳር 11 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ ለ14 ጊዜ ያህል በዲዝል በሚሰሩ ባቡሮች የእርዳታ ስንዴ እስከ አዳማ ድረስ መጓጓዙን አስታውቀዋል፡፡
ባቡሩን ሥራ ለማስጀመር የጅቡቲና የኢትዮጵያ መንግስታት ስምምነት እንደሚያስፈልግ ያወሱት አቶ ደረጀ፤ የባቡር አገልግሎቱን የሚያስተዳድር ኩባንያ ለማቋቋምና የማናጅመንት ኮንትራት ለመስጠት በሁለቱ ሃገራት መካከል ውይይት እየተካሄደ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ የኢትዮ-ጅቡቲ ባቡር መስመር የሁለቱ ሃገራት የጋራ ንብረት መሆኑንና የትርፍ ክፍፍልንና የእዳ አከፋፈልን በተመለከተም ሀገራቱ እየተወያዩ እንደሆነ ተገልጿል፡፡ ለወደፊት በመስመሩ ላይ የሚሰሩ ባለሙያዎችም ከሁለቱ ሃገሮች የተውጣጡ ይሆናሉ ተብሏል፡፡

ባለፈው ጥቅምት 1 ሚ. ቶን ስንዴ ለመግዛት ጨረታ አውጥቶ ነበር

   በአንዳንድ አካባቢዎች ድርቅ መከሰቱን ተከትሎ የምግብ እህል ክምችቱን ለማሳደግ እየሰራ የሚገኘው የኢትዮጵያ መንግስት፣ 70 ሺህ ቶን ስንዴ ለመግዛት ሰሞኑን አለማቀፍ ጨረታ ማውጣቱን ኤዢያዋን የተባለው ድረገጽ የአውሮፓ የንግድ ኩባንያዎችን ጠቅሶ ትናንት ዘገበ፡፡መንግስት ግዢውን የሚፈጽመው ከአለም ባንክ አለማቀፍ የልማት ማህበርና ከሌሎች ለጋሾች ባገኘው ገንዘብ እንደሆነ ኩባንያዎቹ መግለጻቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ጨረታው የሚዘጋውም በመጪው ማክሰኞ እንደሆነ መጠቆማቸውን ገልጧል፡፡የኢትዮጵያ መንግስት ባለፉት ወራት ተደጋጋሚ ጨረታዎችን ማውጣቱን ያስታወሰው ዘገባው፣ ባለፈው በጥቅምት ወር 1 ሚሊዮን ቶን ስንዴ ለመግዛት ጨረታ አውጥቶ እንደነበርና የመጨረሻው ጨረታም በጥር ወር መጀመሪያ ላይ 70 ሺህ ቶን ለመግዛት ያወጣው አለማቀፍ ጨረታ እንደሆነ ገልጧል፡፡የዝናብ እጥረት መከሰቱን ተከትሎ በአገሪቱ የምግብና የውሃ እጥረት መከሰቱንና መንግስት የከፋ የምግብ እጥረት ችግር ተጠቂ የሆኑ 10.2 ሚሊዮን ዜጎችን ለመታደግ እየተደረገ ያለውን ጥረት እንዲደግፉ ባለፈው ወር ለአለማቀፍ ለጋሾች ጥሪ ማቅረቡንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

   በየውብዳር አንበሴ ተጽፎ የተዘጋጀውና የገዳ ስርዓት ከዘመናዊ ዲሞክራሲ ጋር ያለውን አንድነት የሚያስቃኘው “Gada System፡ A blue Print for Democracy” የተሰኘው ዘጋቢ ፊልም፤  ከትላንት በስቲያ ምሽት በኦሮሞ ባህል ማዕከል ተመረቀ፡፡ የ38 ደቂቃ ርዝመት ያለውና በተስፋዬ  ፊልም ፕሮዳክሽንና ፕሮሞሽን የተሰራው ዘጋቢ ፊልም ቀረፃው በጉጂ ዞን የተካሄደ ሲሆን በገዳ ስርዓት ስር ያሉ ህዝቦች ዲሞክራሲን እንዴት እንደሚተገብሩ በስፋት ያስቃኛል ተብሏል፡፡ በምርቃቱ ላይ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች፣ የአካባቢው ህዝብ ተወካዮችና የባህልና ቱሪዝም ሃላፊዎች  እንደተገኙ አርቲስት ተስፋዬ ማሞ ተናግሯል፡፡

  በቲያትር መልክ ተዘጋጅቶ ለእይታ ይበቃል
    ደራሲ ጄ ኬ ሮውሊንግ፤ ሃሪ ፖተር በሚል ርዕስ በተከታታይ ስታሳትመው የቆየችው ተወዳጅ መጽሃፍ 8ኛው ክፍል ሃሪ ፖተር ኤንድ ዘ ከርስድ ቻይልድ በሚል ርዕስ በመጪው ሃምሌ ወር ለንባብ እንደሚበቃ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የደራሲዋ ስምንተኛ መጽሃፍ ለገበያ እንደሚበቃ ባለፈው ረቡዕ ይፋ መደረጉን ተከትሎ በመጽሃፍ ሽያጭ ሰንጠረዥ በቀዳሚነት መቀመጧ ተነግሯል፡፡ የታተመው መጽሃፍ በ29.99 ዶላር፣ በሶፍት ኮፒ የተዘጋጀው ደግሞ በ14.99 ዶላር በገበያ ላይ እንደሚውል በተነገረለት የመጽሃፉ የምረቃ ስነስርዓት ላይ የመጽሃፉ ታሪክ በቲያትር መልክ ተዘጋጅቶ በለንደኑ ፓላስ ቲያትር ለእይታ ይበቃል ተብሏል፡፡
የሃሪ ፖተር የመጨረሻው ክፍል እ.ኤ.አ በ2007 ለንባብ መብቃቱ ይታወሳል፡፡

  - በሙስና ተጠርጥረዋል ቢባልም፣ በስነ-ምግባራቸው እንደሚታወቁ ተነግሯል
           - ፕሬዚዳንቱ በቅርቡ የመከላከያ ሚኒስትሩን በሞርታር አስገድለዋል
    የሰሜን ኮርያ የጦር ሃይል አዛዥ ጄኔራል ሪ ያንግ ጊል፤ በሙስናና የግል ጥቅምን በማካበት ህገወጥ ተግባር ተሰማርተው ተገኝተዋል በሚል ባለፈው ሳምንት በአገሪቱ ፕሬዚዳንት ኪም ጆንግ ኡን ትዕዛዝ መገደላቸውን ውስጥ አዋቂ ምንጮች እንደገለጹ ስካይ ኒውስ ዘገበ፡፡
ላለፉት ሶስት አመታት የአገሪቱ የጦር ሃይል አዛዥ ሆነው ያገለገሉት ጄኔራል ሪ ያንግ ጊል ለስነ-ምግባር መርሆዎች ተገዢ መሆናቸው የተመሰከረላቸው ግለሰብ ናቸው ያለው ዘገባው፣ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ጄኔራሉን ያለአግባብ የወነጀሉት ለግድያው ሰበብ ለመፈለግ ነው መባሉን ፀቁሟል፡፡ ግድያውን በተመለከተ ተጨባጭ ማረጋገጫ ባይገኝም፣ ፕሬዚዳንት ኪም ጆንግ ኡን ከወራት በፊት የቀድሞውን የአገሪቱ  የመከላከያ ሚኒስትር በሞርታር ማስገደላቸው ይህንን ግድያም ሊያስፈጽሙት እንደሚችሉ ያመላክታል መባሉን ዘገባው ገልጧል፡፡
ፕሬዚዳንቱ በቅርቡ የፓርቲ መሪዎችን በቁልፍ የአገሪቱ ጦር ሃይል የስልጣን ቦታዎች ላይ መሾማቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ይህም በጄኔራሉ ላይ ተፈጸመ ከተባለው ግድያ ጋር ሊያያዝ እንደሚችልና አዲሶቹ ባለስልጣናትም በጄኔራሉ ግድያ ውስጥ እጃቸው ሊኖርበት ይችላል መባሉንም አብራርቷል፡፡

 የቀድሞዋ  እጣ እንዳይደርስባት፣ የአደጋ መቆጣጠሪያዋ ተሻሽሏል
   ከ104 አመታት በፊት በሰሜን አትላንቲክ ውቅያኖስ በደረሰባት አደጋ በሰጠመችው ታዋቂዋ ታይታኒክ መርከብ ዲዛይን የተሰራችውና ታይታኒክ ሁለተኛ የሚል ስያሜ የተሰጣት አዲስ መርከብ፣ ከሁለት አመት በኋላ መቅዘፍ እንደምትጀምር ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
ብሉ ስታር ላይን የተባለው ታዋቂ ኩባንያ ባለቤት የሆኑት አውስትራሊያዊው ቢሊየነር ክሊቭ ፓልመር ያሰሯት ዳግማዊት ታይታኒክ፣ ከቀድሞዋ ታይታኒክ ጋር ዲዛይኗ ተመሳሳይ ቢሆንም፣ ከዘመኑ የባህር ሃይል ደህንነት መመሪያ ጋር በሚስማማ መልኩ የተወሰነ ማሻሻያ እንደተደረገባት ተነግሯል፡፡
270 ሜትር እርዝማኔ ያላት ዳግማዊት ታይታኒክ፣ ቁመቷ 53 ሜትር ሲሆን ክብደቷም 40 ሺህ ቶን ይደርሳል ተብሏል፡፡ ዘጠኝ ወለሎች ያሏት ሲሆን 2ሺህ መንገደኞችንና 900 የቀዘፋ ሰራተኞችን የመያዝ አቅም እንዳላትም ተነግሯል፡፡ ይህቺኛዋ ታይታኒክ አያድርግባትና የቀድሞዋ ታይታኒክ ክፉ ዕጣ ቢደርስባት፣ የከፋ ጥፋት እንዳይከሰት በሚል በቂ የአደጋ ጊዜ ማምለጫ ጀልባዎች እንድትይዝ ተደርጋለች፡፡ ሌሎች የባህር ላይ አደጋ መቆጣጠሪያና የህይወት አድን መሳሪያዎች በበቂ መጠን የተገጠሙላት ዳግማዊት ታይታኒክ፣ በ2008 መጀመሪያ ጂያንዙ ከተባለችው የምስራቃዊት ቻይና ከተማ ወደ ዱባይ የመጀመሪያዋን ጉዞ ታደርጋለች ተብሎ እንደሚጠበቅም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

   የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታኒያሁ አገሪቱን ከሰርጎ ገቦች ጥቃት ለመከላከል የሚያስችልና ሁሉንም የአገሪቱ ድንበር የሚከልል አጥር የማሰራት እቅድ እንዳላቸው ማስታወቃቸውን ዘ ጋርዲያን ዘገበ፡፡ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ ከፍልስጤምና በእስራኤል ዙሪያ ከሚገኙ የአረብ አገራት ድንበር ጥሰው የሚገቡ ሰርጎ ገቦችን የመከላከል አላማ ያነገበ ነው ያሉትን ይህን ድንበርን የማጠር እቅድ ይፋ ያደረጉ ሲሆን፣ አጥሩ ከዚህ በተጨማሪም ከጋዛ ወደ አገሪቱ የሚገቡ የሃማስ ታጣቂዎችን ለመከላከል ተግባር ይውላል ተብሏል፡፡
የድንበር አጥር ፕሮጀክቱ አገሪቱን በረጅም አመታት ሂደት ሙሉ ለሙሉ በደህንነት አጥር ለማጠር የተያዘው ሰፊ እቅድ አካል እንደሆነ የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ በነባር የድንበር አጥሮች አካባቢ የሚታየውን ክፍተት ለመዝጋት እየተሰራ እንደሚገኝም አስታውቀዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአጥር ፕሮጀክቱ ለአገሪቱ ደህንነት ወሳኝ ነው ቢሉም፣ የእስራኤል የሚኒስትሮች ምክር ቤት አባል የሆኑትና ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በደህንነት ፖሊሲ ዙሪያ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር በተደጋጋሚ አለመግባባት እየፈጠሩ ነው የተባሉት የአገሪቱ የትምህርት ሚኒስትር ናፍታሊ ቤኔት ግን እቅዱን መቃወማቸው ተነግሯል፡፡

 የግብጹ ፕሬዚዳንት አብዱል ፈታህ አል ሲሲ ባለፈው ጥቅምት ወር መጀመሪያ ላይ በርዕሰ መዲናዋ ካይሮ አቅራቢያ የተሰራን የመኖሪያ ቤቶች ፕሮጀክት መርቀው በከፈቱበት ወቅት የተነጠፈላቸው እጅግ ረጅም ቀይ ምንጣፍ ሰፊ ተቃውሞ እንደገጠመው ዘ ዴይሊ ሜይል ዘገበ፡፡
4 ኪሎ ሜትር እርዝማኔ እንዳለውና 143 ሺህ ፓውንድ እንደሚያወጣ የተነገረለት የፕሬዚዳንቱ የክብር ምንጣፍ፣ በአገሪቱ ጋዜጦችና በማህበራዊ ድረገጾች ከፍተኛ ውግዘት እንደደረሰበት የጠቆመው ዘገባው፣ ባለፈው ሰኞ ለንባብ የበቃው አል ማቃል የተባለ የአገሪቱ ጋዜጣም፣ አብዛኛውን የፊት ገጹን ምንጣፉን በሚተች ዘገባ መሙላቱን ጠቁሟል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከአንድ አመት በፊት ያወጣው ሪፖርት ከሩብ በላይ ግብጻውያን ከድህነት ወለል በታች እንደሚገኙ መግለጹን ያስታወሰው ዘገባው፣ ለፕሬዚዳንቱ የክብር ምንጣፍ ይሄን ያህል ገንዘብ መውጣቱ ብዙዎችን ማሳዘኑንና ትችት ማስተናገዱን አስታውቋል፡፡ የአገሪቱ መንግስት የጦር ሃይል ተወካይ ብርጋዴር ጄኔራል ኢሃብ አል አህዋጊ በበኩላቸው፤ አወዛጋቢው ምንጣፍ በወቅቱ ፕሬዚዳንት የአብዱል ፈታህ አልሲሲ አስተዳደር የተገዛ አለመሆኑን በማስታወስ፣ ምንጣፉ ከሶስት አመታት በላይ ለሚሆን ጊዜ በመሰል ስነስርዓቶች ላይ አገልግሎት ሲሰጥ የቆየ ነው ሲሉ ሊያስተባብሉ ሞክረዋል ተብሏል፡፡

Saturday, 13 February 2016 11:59

ሀበሻ ዊክሊ ----- ከየት ወዴት?

ለቴዲ አፍሮ ኮንሰርት ከ3 ሚ. ብር በላይ በጀት ተይዟል

    አዲስ አበባ ነው ተወልዶ ያደገው፡፡ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን በኮከበ ፅባህ፣ የመሰናዶ ትምህርቱን ደግሞ በዳግማዊ ምኒልክ ት/ቤት ተከታትሏል፡፡ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አራት ኪሎ ካምፓስ፣ በኮምፒዩተር ሳይንስ በድግሪ ተመርቋል፡፡ በልጅነቱ ነፍሱ ወደ ኪነ-ጥበቡ ታደላ ስለነበር ፊልም ፕሮዱዩስ የማድረግና የመተወን ህልም ነበረው፡፡ ፓይለት ለመሆን ሁለት ጊዜ ጥረት ቢያደርግም በአንድ ሴንቲ ሜትር የቁመት ማነስ ምክንያት ሳይሳካለት ቀርቷል፡፡
የዩኒቨርስቲ ተማሪ እያለ በተደጋጋሚ ስኮላርሺፕ ሞክሮ አሜሪካና ካናዳ ያሉ ሁለት ዩኒቨርስቲዎች ቢቀበሉትም ኤምባሲዎቹ ቪዛ አልፈቀዱለትም፡፡ በዚህ ተስፋ የቆረጠው የ28 ዓመቱ ወጣት አዶኒክ ወርቁ ፊቱንና ልቡን ሙሉ በሙሉ ወደ አገሩ መልሶ በትጋት መስራት ጀመረ፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ ከሀበሻ ዊክሊ ፕሮሞሽን መሥራችና ሥራ አስኪያጅ አዶኒክ ወርቁ ጋር በህይወቱና በቢዝነስ ሥራው፣ በህልሙና ራዕዩ ዙሪያ ቃለ ምልልስ አድርጋለች፡፡ ዝነኛው ድምጻዊ ቴዲ አፍሮ የሚያቀነቅንበት ኮንሰርት በጊዮን ሆቴል እንደሚያዘጋጅም አውግቷታል፡፡ እነሆ፡-  
   
    እንዴት ነው በቀጥታ ወደ ሁነት አዘጋጅነትና ወደ ቢዝነስ ስራ የገባኸው?
እኔ ኤቨንት ኦርጋናይዝ ማድረግ የጀመርኩት በ1997 ዓ.ም የ12ኛ ክፍል ተማሪ ሆኜ ነው፡፡ ያኔ ስኩል ካርኒቫል በማዘጋጀት እና፣ ዲጄ ሆኜ እሰራ ነበር፡፡ እነዚህ በዋናነትም ባይሆን ፍላጐቶቼ ነበሩ፡፡ ቢዝነስን በተመለከተ አብዛኛው ቤተሰቤ በንግድ ስራ ላይ የተሰማራ ስለነበር ተማሪም ሆኜ ቤተሰቤን በስራ አግዝ ነበር፡፡ ሆኖም ብዙ ወደ ኪነ ጥበቡ ስለማደላ ፊልሞችን እመለከት ነበር፡፡  
ወደ ውጭ አገር የመሄድ ጉጉት እንደነበረህ ሰምቻለሁ -----
ጉጉቴ ውጭ ሄዶ ለመኖር ሳይሆን ለመማርና ቶሎ ለመለወጥ ነበር፡፡ እንደነገርኩሽ ሆሊውድ የሚሰሩ ፊልሞችን በዲሽ ላይ አያለሁ፡፡ እያንዳንዱ ዲሽ ላይ የማየውን ነገር እመኛለሁ፤ያንን ነገር ለማግኘት የግድ እዛው ቦታው መገኘትና መማር አለብኝ ብዬ አስብ ነበር፡፡ በጣም ልቤ ተሰቅሎ ነበር፡፡ ሆኖም ከአንዴም ሁለት ሶስቴ አልተሳካም፤በዚህ ምክንያት ውጭ የመሄዱን ነገር እርግፍ አድርጌ ተውኩት፡፡
ከዩኒቨርሲቲ ተመርቀህ እንደወጣህ ሥራ የጀመርከው የት ነው?
ከዩኒቨርሲቲ እንደተመረቅሁ ወደ ቤተሰቤ የቢዝነስ ስራዎች ገባሁ፡፡ እንደ ነገርኩሽ ተማሪም ሆኜ ከቤተሰቤ ጋር በትርፍ ሰዓቴ እሰራ ስለነበር ስራውን አውቀዋለሁ፤ስለዚህ ቤተሰቤን እየወከልኩ በተለያዩ የስራ ቦታዎች ላይ ማገዝ ጀመርኩኝ፡፡ ከዚያም ካሉን በርካታ እህት ኩባንያዎች “ሻካይና” በተባለው ውስጥ ማርኬቲንግ ማናጀር ሆኜ መስራት ቀጠልኩ ማለት ነው፡፡
የራስህን ኮምፒዩተር ቤት የከፈትከው መቼ ነው?
በዚያው ዓመት የ“ሻካይና” ማርኬቲንግ ማናጀር ሆኜ እየሰራሁ “አዶኒክ ኮምፒዩተር ሶሉሽን” የተባለ የራሴን ድርጅት ከፈትኩት፡፡ እንደነገርኩሽ በኮምፒዩተር ሳይንስ ነው የተመረቅሁት፡፡ እውቀቱና ክህሎቱ አለኝ፤ስለዚህ እውቀቴን ወደ ቢዝነስ መለወጥና ራሴን ማሳደግ ስለምፈልግ አብረውኝ የተማሩና ደህና ውጤት የነበራቸውን ልጆች አሰባስቤ፣ የራሴንም እውቀት ጨምሬበት ጥሩ ጥሩ ስራዎችን መስራት ጀመርን፡፡ ለምሳሌ ድርጅቱ ገና እንደተከፈተ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ጽ/ቤትን ዌብሳይት ዴቨሎፕ አደረግን፡፡ በጣም የሚገርምሽ ብዙ ልምድ ከነበራቸው በርካታ ድርጅቶች ጋር ተወዳድረን፣ የሥራ ልምድ ሳይኖረን የከንቲባውን ጽ/ቤት ዌብሳይት መስራት ለእኔ ትልቅ ስኬት ነበር፡፡
በመቀጠል “አዶኒክ ጆብስ” የተሰኘ ብዙ ወጪ የወጣበት፣ ሥራንና ሥራ ፈላጊዎችን የሚያገናኝ ዌብሳይት ሰራን፡፡ ሥራ ፈላጊዎች ሲቪ ይዘው ገና ማስታወቂያ አንብበው ነው ስራ የሚፈልጉት፡፡ ይህን ድካም የሚቀንስ ነው፤ አዶኒክ ጆብስ ዌብሳይት፡፡ ሆኖም በወቅቱ እንዲህ አይነት ዌብሳይቶች ስላልተለመዱ እንዲታወቁ ለማድረግ ብዙ ጣርን፤ ነገር ግን አለማምደን ገቢ ለማግኘት በጣም ፈታኝ ነበር፡፡ ለአንድ ዓመት በዚህ መልኩ ከሰራሁ በኋላ ፊቴን ወደ ኪነጥበብ ማዞር ፈለግሁኝ፡፡
ኢቢኤስ ላይ ሀበሻ ዊክሊ የተሰኘ የቴሌቪዥን ፕሮግራም እንደነበረህ አስታውሳለሁ፡፡ ለምን ቆመ?
ዌብሳይት የሚሰራው የኮምፒዩተር ድርጅት እንዳለ ሆኖ፣ ወደ አርቱ የመግባት ፍላጎት ቀድሞም ስለነበረኝ አመቺ ሁኔታዎችን እየጠበቅኩኝ ነበር፡፡ ኢቢኤስ መከፈቱ ጥሩ አጋጣሚ ፈጠረልኝና ጥሩ ፕሮፖዛል ሰርቼ አስገባሁ፤ተቀባይነትም አገኘሁ፡፡ ሁሌም የውጭዎቹን የፊልምና የሙዚቃ ቦክስ ኦፊስ ስመለከት፣ ለምን የእኛ አገር ፊልሞችስ ቦክስ ኦፊስ አይኖራቸውም እላለሁ፡፡ በወቅቱ በእኛ አገር ቴሌቪዥንም ሆነ ሬዲዮ በስፋት የሚያወራው ስለ ውጭ ፊልሞች፣ ስለ ውጭ አክተሮች፣ ስለ ውጭ ሙዚቃ ነበር፡፡ ለምን የሀገራችን ዝነኞች (ሰለብሪቲዎች) አይወራላቸውም የሚል ቁጭት ነበረብኝ፡፡ ይህንን ለመስራት ካለኝ ጉጉት ተነስቼ ነው የፕሮግራሙን ስም ራሱ “ሀበሻ ዊክሊ” ብዬ የሰየምኩት፡፡ በፕሮግራሙ ኢትዮጵያ ውስጥ በሳምንት ውስጥ ምን ምን ኪነጥበባዊ ክንውኖች እንደነበሩ የሚጠቁሙ መረጃዎችና መዝናኛዎች ይቀርቡበት ነበር፡፡ አዳዲስ ፊልሞች፣ አዳዲስ ሙዚቃዎች፣ አዳዲስ የአገራችን ሁነቶች፣ በፕሮግራማችን ይስተናገዱ ነበር፡፡ ወቅቱ ደግሞ አሪፍ አሪፍ ፊልሞች መውጣት የጀመሩበት ነበር፡፡ እነ ፔንዱለም፣ ሂሮሺማ፣ አባይ ወይስ ቬጋስ  መውጣት ስለጀመሩ ለፕሮግራማችን ጥሩ ግብአቶች እያገኘን መጣን፡፡
ታዲያ ለምን አቆማችሁት?
እንግዲህ “ሀበሻ ዊክሊ” አቅማችንን የፈተንንበት፣ወደ መዝናኛው ኢንዱስትሪ ይበልጥ የገባንበትና ከብዙ ሰዎች ጋር የተዋወቅንበት ፕሮግራም ነው፡፡ አንደኛ እኛ የመጀመሪያዎቹ አውት ሶርስ አድራጊዎች ነን፤ ሁለተኛ ኢቢኤስ ያን ጊዜ በ2003 ዓ.ም ማለት ነው በደንብ አይታወቅም ነበር፡
እነዚህ ነገሮች ስፖንሰር ለማግኘትም ሆነ ብዙ ነገር ለመስራት ፈትነውን ነበር፡፡ የቢሮ ኪራይ ነበረብን፣ ካሜራም ተከራይተን ነበር የምንሰራው፡፡ ኤዲተርም አስቸጋሪ ነበር፡፡ በዚያ ፈተና ውስጥ የአንድ የአንድ ሰዓት 50 ፕሮግራሞችን ለአንድ ዓመት ሰራን፡፡ ስራችን ደግሞ ቲቪ ሾው አይደለም፤ ሰባት አይነት የተለያዩ ፕሮግራሞች ይቀርቡበት ነበር፡፡ የተለያዩ ፈጠራዎችን በማከል ፕሮግራሙን ለየት ለማድረግ ሞክረናል፡፡ ያንን ከባድ ፈተና እየተጋፈጠን ነው የቆየነው፡፡ ቦክስ ኦፊስ ለማውጣት ሲኒማ ቤቶችን ማሳመን፣ የፕሮዲዩሰሮች ማህበራትን ማግባባት -----ስንቱ ነገር አሳልፈን መሰለሽ ቦክስ ኦፊስ የጀመርነው፡፡ ዱባይ ሳይቀር ሄደን የአመት በዓል ፕሮግራም ሰርተናል፡፡
ጥሩ እየሆንን፣ ገቢያችንም ደህና እየሆነ ሲመጣ የአንድ ዓመት ኮንትራታችን አልቆ እንቀጥላለን ብለን ስናስብ፣ኮንትራቱ ሳይታደስ ቀረ፡፡ እኛም ትንሽ ተቀይመን ስለነበር በዚያው ቆመ፡፡
አሁንም ሀበሻ ዊክሊ በሚለው ስም ነው ብዙ ስራ እየሰራችሁ ያላችሁት?
ልክ ነው፡፡ የቲቪ ፕሮግራማችን ሲቆም ስሙ በጣም ጥሩ ስለሆነ “አዶኒክ ግሎባል ኢንተርቴይንመንት” የሚለውን ወደ ሀበሻ ዊክሊ ፕሮሞሽን ቀየርነውና ቀጠለ፡፡ የኩባንያው ባለድርሻዎችም እኔና ባለቤቴ ሀና ሆንን ማለት ነው፡፡
ዘንድሮ በ15 ሚ. ብር ለአዲስ ዓመት ባዘጋጃችሁት ኤክስፖ፣ “በጊነስ ቡክ ኦፍ ሪከርድስ” ላይ ለማስመዝገብ በሂደት ላይ የነበሩ ሁለት የፈጠራ ሥራዎችን ለእይታ አቅርባችሁ ነበር፡፡ ሂደቱ ምን ላይ ደረሰ?
አዎ፤ትልቁን ፖስት ካርድ በ50 የበሬ ቆዳ ሰርተናል፡፡ በብራና ለመስራት ስለፈለግን ነው፡፡  በሻማ ትልቁን 15 ሜትር የገና ዛፍ ሰርተናል፡፡ እኛ አዳዲስ ፈጠራዎችን የምንሰራው ስለ አካባቢ ጥበቃ፣ ስለ አየር ንብረት ለውጥ ሰዎችን ለማስተማር ነው፡፡
በላቪሲን ኤክስፖ ትልቁን የገና ዛፍ ከወዳደቁ በርካታ የውሃ ላስቲኮች ሰርተን፣ አካባቢን ከማቆሸሽ በፈጠራ ስራ ላስቲኮችን ስራ ላይ ማዋል እንደሚቻል አስተምረናል፡፡ ብዙ የአገር ውስጥና የውጭ ሚዲያዎችም ሽፋን ሰጥተውት ነበር ብዙ የአገር ውስጥና የውጭ ሚዲያዎች ሽፋን ሰጥተውት ነበር፡፡ ረጅሙም ዛፍ ከሻማ የተሰራው ፀሐይ እየመታው ሲቀልጥ የዓለምን የሙቀት መጨመር ለማሳየት ነው፡፡ ፖስት ካርዱንና የሻማ ዛፉን ጊነስ ላይ ለማስመዝገብ ሂደት ላይ ነን፤ ሌሎች አሟሉ የተባልነውን ለማሟላት እየጣርን ነው፡፡
በዚህ ወር መጨረሻ ላይ በጊዮን ትልቅ የሙዚቃ ኮንሰርት ለማቅረብ ቴዲ አፍሮን አስፈርማችኋል፡፡ እስቲ ዝርዝሩን ንገረኝ ?
እንደ ሁነት አዘጋጅነታችን ትልልቅ ሥራዎችን ሰርተን ተሳክቶልናል፤እየተሳካልንም ነው፡፡ ከቴዲም ጋር በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ በስራ የምንገናኝባቸው አጋጣሚዎች ነበሩ፡፡ እውነት ለመናገር ከቴዲ ጋር ኮንሰርት እንስራ ብለን ብዙም እቅድ ይዘንበት አናውቅም፡፡ ነገር ግን አጋጣሚው ከተፈጠረ ለምን አናደርገውም፣ ለምንስ አንሞክረውም? አልን፡፡ ምክንያቱም ጥሩ ስራ እንደምንሰራ እንተማመናለን፡፡ መጀመሪያ እርሱ አሜሪካ ስለነበረ ብዙ ጉዳዮችን ተወያይተን የጨረስነው ከባለቤቱ ከአምለሰት ሙጬ ጋር ነበር፡፡ ከዚያም ከእርሱ ጋር ተገናኘንና ተወያየን፡፡ አጋጣሚዎቹ ጥሩ ሆኑና ስምምነት ላይ ደረስን፡፡ ኮንሰርቱ የካቲት 26 ቀን የአብይ ፆም ከመግባቱ በፊት ባለው የመጨረሻው ቅዳሜ  ይካሄዳል፡፡ እንግዲህ ሶስት ሳምንት ነው የሚቀረን፡፡
በምን ያህል ክፍያ ተስማማችሁ?
ለቴዲ የምንከፍለውን ለመናገር የእሱን ይሁንታ ማግኘት አለብን፡፡ እኛ ለአጠቃላይ ፕሮግራሙ ግን ከ3 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት ይዘንለታል፡፡
ዝግጅቱ እንዴት ነው ታዲያ ?
አሁን ሩጫ ላይ ነን፡፡ ምክንያቱም ጥሩ ስራ መስራት አለብን፡፡ አንዳንድ ማሟላት ያለብንን ሁኔታዎች እያሟላን ነው፡፡ እነዚህን ጥንቅቅ አድርገን ስንጨርስ ስለ መግቢያ ዋጋው፣ ስለ ክፍያው  ወዘተ----በጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ይፋ እናደርጋለን፡፡
ከዚህ ቀደም የቴዲ የተለያዩ ኮንሰርቶች በተለያዩ ምክንያቶች ተሰርዘዋል፡፡ ተመሳሳይ ችግር እንዳይፈጠር የወሰዳችሁት የተለየ ጥንቃቄ አለ?
እኛ እንደ ሀበሻ ዊክሊ የምንናገረው፤ቴዲ ትልቅና ተወዳጅ ድምፃዊ መሆኑን ነው፤ገበያው እንደሚፈልገው እናውቃለን፡፡ ከዚህ በፊት ስለተሰረዙት ኮንሰርቶች እያሰብን፣ ስራችንን ከመስራት ወደ ኋላ አንልም፡፡ አሁንም በተወዳጅነቱ ከአድናቂዎቹ ጋር እንዲገናኝ በእኛም በእሱም በኩል ማድረግ ያለበንን እያደረግን ነው፡፡ እስካሁን ባለውም ሂደት የገጠመን እንቅፋት የለም፡፡ ተፈራርመናል፡፡ ለአዲስ አበባ አስተዳደርም የማሳወቂያ ደብዳቤ አስገብተናል፡፡
የኤፍኤም ሬዲዮ ጣቢያ ባለቤት ለመሆን መወዳደራችሁን ሰምቻለሁ፡፡ እንዴት ሆነ?
እንግዲህ የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለስልጣን ባወጣው ማስታወቂያ መሰረት በጣም ጥሩ የሆነ ፕሮፖዛል ቀርፀን አስገብተናል፡፡ ተፎካካሪ ከሆኑት ውስጥ እኛም አለንበት፡፡ ሀበሻ ዊክሊ ወደፊት እንደ ግብ ያስቀመጣቸው ትልልቅ ራዕዮች አሉት፡፡ አንዱና ትልቁ ራዕያችን፤ የራሳችን የቴሌቪዥን ጣቢያ መክፈት ነው፡፡ ሆሊዉድ ውስጥ ያለው የፊልም ደረጃ ወደ አገራችን እንዲመጣም እናስባለን፡፡ ከቴሌቪዥኑ ጣቢያ ሬዲዮው ስለቀደመ እድሉን ለመጠቀም ወደ ሬዲዮው ገብተናል፡፡ ብዙ ዝግጅት አድርገን ነው በውድድሩ የተሳተፍነው፡፡ ከፋይናንሱ ይበልጥ የሬዲዮ ፋይዳና ቴክኒክ ላይ ሰፊ ዝግጅት አድርገናል፡፡
ኤፍኤም ሬዲዮ ሲከፈት ያማከሩ፣ በሬዲዮ ኢንስታሌሽን ስራም ብቃት ያላቸው ባለሙያዎችን አዋቅረንበታል፡፡ ትልቅ ሬዲዮ ጣቢያን ያቋቋሙ ትልቅ ሰው በፕሮፖዛሉ ስራ ላይ ተሳትፈዋል፡፡ የተለየ የሬዲዮ ሀሳብ ይዘናል፤አሁን ያለውን የሬዲዮ ትሬንድ በዜናም፣ በዜና ሰዓትም፣ በአቀራረብም---- በተለይ ከውጭው ጉዳይ ይልቅ በአገራችን ጉዳይ ላይ አተኩረን ለመስራት ከፍተኛ ፍላጎት አለን፡፡
እዚህ አገር ባለሀብቱ ራሱ ስፖንሰር የሚያደርገው በብዛት የሚደመጠውን እንጂ የሚዘገበው ነገር ምንም ይሁን ምን ጉዳያቸው አይደለም፡፡ ይሄ የተበላሸ አስተሳሰብ ነው፤ ይሄን አስተሳሰብ እንቀይራለን ብለናል፡፡ በኦዲዮም በቪዲዮም በደንብ የተደራጀ ስቱዲዮ አለን፡፡ ወደፊት ደግሞ ወደ ቴሌቪዥን ባለቤትነቱ እንሄዳለን፡፡
ባለፈው ያሸነፈ ድርጅት አለ ተብሎ በስም ተጠቅሶ በማህበራዊ ሚዲያው ሲናፈስ ነበር፡፡ መጨረሻው ምን ሆነ?
ጨረታው ሲወጣ 40 ድርጅቶች ለመሳተፍ ሰነድ ወስደዋል፡፡ እስካሁን ባለን መረጃ አራት ድርጅቶች ናቸው ጨረታውን ያስገቡት፡፡ ከአራቱ አንዱ የእኛ ሀበሻ ዊክሊ ነው፡፡ ቴክኒካሊ ጥሩ እንደሆነ ሰምተናል፡፡ ጨረታው የተሰረዘው በፋይናንስ አቅም የተሻለ ድርጅት አልተገኘም በሚል ነው፡፡ አሁን ጨረታው በድጋሚ ወጥቷል፡፡ ማንም እንዳላሸነፈ ባለስልጣኑ በጋዜጣዊ መግለጫው አስታውቋል፡፡ ስለዚህ ለሁለተኛ ጊዜ ጨረታውን ከ15 ቀን በኋላ እናስገባለን፡፡
ባለትዳርና የአንዲት ሴት ልጅ አባት ነህ፡፡ ትዳር ምን ይመስላል?
ባለቤቴ በጣም ጐበዝ፤ቀልጣፋና ጠንካራ ሴት ናት፡፡ ስራውን ከእኔ እኩል ትሰራለች፡፡ በስራ ላይ ጭቅጭቁ፣ የሀሳብ ፍጭቱ አለ፡፡ ቤታችን ስንገባ የምንዋደድ ባልና ሚስቶች ነን፡፡ ኤንጂል አዶኒክ የተባለች ቆንጆ ሴት ልጅ ወልደናል፤በጣም ደስተኞች ነን፡፡ እንደ ጓደኞችም እንደ ሥራ ባልደረቦችም ነን፡፡

የቲማቲም ምርቶችን በማጥቃት ከፍተኛ ውድመት ያደርሳሉ ለተባሉ በሽታዎች፣ ኢትዮጵያውያን ተመራማሪዎች  አዲስ መድሃኒት በምርምር ማግኘታቸውን ገለፁ፡፡
“ኬንት ፓወር” የሚል ስያሜ የተሰጠው ይኸው መድሃኒት፤ በቲማቲም ተክል ላይ ጉዳት የሚያደርሱ ባክቴሪያና ፈንገሶችን የሚያጠፋና ምርቱ በቫይረስ እንዳይጠቃ የሚከላከል እንደሆነ ተመራማሪዎቹ ተገኘ ዘለቀና ታደሰ ገ/ኪሮስ ሰሞኑን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተናግረዋል፡፡
በአገሪቱ በተለያዩ ወቅቶች በቲማቲም ምርቶች ላይ በሚያጋጥሙ ልዩ ልዩ በሽታዎች ሳቢያ ምርቱ ስለሚቀንስ በበቂ መጠን ለገበያ ሊቀርብ አለመቻሉን የሚናገሩት ተመራማሪዎቹ፤  በምርቱ ላይ የሚደርሰውን ችግር ለመቅረፍ የሚረዳና አምራቹም በለፋው መጠን አምርቶ ለተጠቃሚው ምርቱን በበቂ መጠን የሚያቀርብበትን ሁኔታ ለማመቻቸት አስበው ወደ ምርምር መግባታቸውን ገልፀዋል፡፡ ሁለቱ ተማራማሪዎች፤ ከሁለት ዓመታት እልህ አስጨራሽ የምርምር ጥረትና ትጋት በኋላ ነው የቲማቲም በሽታዎችን ማጥፋትና መከላከል የሚችል መድሃኒት ማግኘታቸውን ይፋ ያደረጉት፡፡
በተመራማሪዎቹ የተገኘው ኬንት ፓወር የተሰኘው ይኸው መድሃኒት፤ ቀደም ሲል ከነበረውና አርሶ አደሩ ከሚጠቀመው ፀረ-ተባይ መድሃኒቶች በዋጋው በእጅጉ ያነሰና በአገልግሎቱ የተሻለ መሆኑን ታውቋል፡፡ በአንድ የቲማቲም ምርት ዘመን፣ በስድስት ሄክታር መሬት ላይ የተዘራውን የቲማቲም ምርት ከበሽታ ለመከላከል ከውጪ የሚገባውን መድሃኒት የሚጠቀም አርሶ አደር ከ63ሺህ ብር በላይ ወጪ ማድረግ ይጠበቅበታል ያሉት ተማራማሪዎቹ፤ አዲሱን “ኬንት ፓወር” ግን በስድስት ሺህ ብር ብቻ ገዝተው፣ በበሽታ ያልተጠቃና በመድሃኒት ያልተበከለ ንፁህ የቲማቲም ምርት ማግኘት እንደሚችሉ ገልፀዋል፡፡ ተመራማሪዎቹ ይህንኑ የምርምር ግኝታቸውን አስመልክቶ ከኢትዮጵያ አዕምሮአዊ ንብረት ጽ/ቤት ሰርተፍኬት ያገኙ ሲሆን በምርምር ያገኙትን መድሃኒት ለአርሶ አደሩ በስፋት ለማድረስ የሚችሉበትን መንገድ በማመቻቸት ላይ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡
የምርምር ውጤታቸውን በፋብሪካ ደረጃ እያመረቱ ለተጠቃሚው ለማድረስ 23 ሚሊዮን ብር እንደሚያስፈልግና ለፋብሪካው ግንባታ የሚሆን የቦታ ጥናት ማድረጋቸውንም ተመራማሪዎቹ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ጠቁመዋል፡፡