Administrator

Administrator

    የአለማቀፉ የገንዘብ ተቋም አይኤምኤፍ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ክርስቲያን ላጋርድ፣ ኢትዮጵያዊውን ኢኮኖሚስት አቶ አበበ አእምሮን የተቋሙ የአፍሪካ ክፍል ዳይሬክተር አድርገው መሾማቸውን ተቋሙ ከትናንት በስቲያ በድረ-ገጹ ባወጣው መግለጫ አስታወቀ፡፡ ላለፉት 22 አመታት በአለማቀፉ የገንዘብ ተቋም የሰሩት አቶ አበበ አእምሮ በተቋሙ፣ በነበራቸው ቆይታ፣ ሃላፊነታቸውን በአግባቡ መወጣታቸውን የገለጸው ተቋሙ፤ በተለያዩ የስራ መደቦች ላይ ባከናወኗቸው ውጤታማ ተግባራት የካበተ ልምድ እንዳላቸውም ጠቁሟል፡፡
“አቶ አበበ በተቋሙ በነበራቸው ቆይታ አብዛኛውን ጊዜያቸውን ከአህጉሪቱ ፖሊሲ አውጪዎች ጋር በቅርበት ሲሰሩ እንደመቆየታቸው የአፍሪካን ፈተናዎች በተመለከተ ጥልቅ ግንዛቤ አላቸው፡፡ በአመራር፣ በማስተባበርና በሌሎች መስኮች ያላቸውን ብቃት በተግባር ማረጋገጣቸው ለዚህ የስራ ሃላፊነት እንዲመረጡ አድርጓቸዋል” ብለዋል የተቋሙ ማኔጂንግ ዳይሬክተር፤ ክርስቲያን ላጋርድ፡፡
አቶ አበበ አእምሮ በተቋሙ ቆይታቸው፣ የአፍሪካ ክፍል የኡጋንዳ ከፍተኛ ተወካይና የደቡብ አፍሪካ ተልዕኮ ሃላፊ ሆነው ከመስራታቸው በተጨማሪ የአህጉሪቱ የኢኮኖሚ ትንበያን ጨምሮ በኮትዲቯር፣ ጋና፣ ኬንያ፣ ቡርኪናፋሶ፣ ጊኒ፣ ላይቤሪያና ሴራሊዮን በተለያዩ የስራ መደቦች ላይ ስኬታማ ስራ ማከናወናቸውንም ተቋሙ አስታውቋል፡፡
በተቋሙ የስትራቴጂ፣ ፖሊሲና ግምገማ ክፍሎች በተለያዩ ሃላፊነቶች ላይ በነበራቸው የስራ ቆይታ የአመራር ብቃታቸውን በተግባር ያስመሰከሩት አቶ አበበ፤ በአይ ኤም ኤፍ የአውሮፓ ክፍል፣ በቱርክ፣ ፖላንድና ፖርቹጋል ለረጅም አመታት መስራታቸውንና የተለያዩ ተልዕኮዎችን በአግባቡ እንደተወጡም ገልጧል፡፡ ከሲቲ ኦፍ ለንደን ፖሊቴክኒክ ተቋም በኢኮኖሚክስ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ያገኙት ኢትዮጵያዊው የኢኮኖሚክስ ባለሙያ አቶ አበበ አእምሮ፤ ከለንደን ስኩል ኦፍ ኢኮኖሚክስ ደግሞ በኢኮኖሚክ ሂስትሪ የሁለተኛ ዲግሪያቸውን እንደተቀበሉ ተቋሙ ባወጣው መግለጫ አክሎ ገልጿል፡፡

   ደቡብ ሱዳን ለአመታት በእርስ በእርስ ጦርነት ስትታመስ፣ በርካታ ዜጎቿ ሲሞቱና ለስደት ሲዳረጉ፣የአገሪቱ ፕሬዚደንት ሳልቫ ኬር እና ተቀናቃኛቸው ሬክ ማቻር ግን፣በሚሊዮኖች ዶላር የሚቆጠር የህዝብ ሃብት ወደ ግል ካዝናቸው በማስገባት ቅሌት ተጠምደው እንደነበር አልጀዚራ ዘግቧል፡፡
ተቀማጭነቱ በአሜሪካ የሆነው ዘ ሴንትሪ የተባለ ተቋም በሳምንቱ መጀመሪያ ባወጣው የምርመራ ሪፖርት፣ ደቡብ ሱዳን በሁለቱ ተቀናቃኝ ሃይሎች የእርስ በእርስ ጦርነት ስትታመስ በቆየቺባቸው አመታት፣ ሳልቫ ኬርና ማቻር የህዝቡን ሃብት ሲዘርፉና በጎረቤት አገራት ባቋቋሟቸው የሪልእስቴትና ሌሎች ኩባንያዎች ጠቀም ያለ ትርፍ ሲያካብቱ ነበር ብሏል፡፡
“ዎር ክራይምስ ሹድንት ፔይ” የሚል ርዕስ ያለውና ለሁለት አመታት የዘለቀውን የተቋሙን ምርመራ መሰረት አድርጎ የተጠናከረው ሪፖርት እንደሚለው፤ሁለቱ የአገሪቱ ቀንደኛ የፖለቲካ መሪዎች በአስር ሺህ የሚቆጠሩ የአገሪቱ ዜጎችን ለሞት በዳረገው አስከፊ ጦርነት እጅግ ከፍተኛ የህዝብ ገንዘብ ወደ ግል ካዝናቸው አስገብተዋል፡፡ ሳልቫኬር ህጋዊ አመታዊ ደመወዛቸው 60 ሺህ ዶላር ቢሆንም፣ እጅግ ከፍተኛ ገንዘብ እንደሚያገኙና በአገራቸውም ሆነ በውጭ አገራት በድብቅ ታላላቅ ኩባንያዎችን እንደሚያንቀሳቅሱ ተደርሶባቸዋል። ቤተሰቦቻቸውም በአገሪቱ የነዳጅ፣ የማዕድንና የሌሎች ዘርፍ ንግድ ጠቀም ያለ ድርሻ አላቸው ብሏል- ሪፖርቱ፡፡
የቀድሞው የአገሪቱ ምክትል ፕሬዚደንት ሬክ ማቻርና ቤተሰቦቻቸውም አገሪቱ በጦርነት ስትታመስ፣የግል ሃብት በማካበት ተጠምደው ነበር የኖሩት፣ህዝቡ መከራውን ሲያይ እሳቸውና ቤተሰቦቻቸው ግን በናይሮቢ ባስገነቡት እጅግ ዘመናዊ ቤት ውስጥ የቅንጦት ኑሮን ሲመሩ ነበር ብሏል- ሪፖርቱ፡፡ 1.2 ሚሊዮን ደቡብ ሱዳናውያን በጦርነቱ ሳቢያ አገራቸውን ጥለው ሲሰደዱ፣ ሳልቫ ኬር እና ማቻር የግል ሃብት በማካበት ቅሌት ተጠምደው እንደነበር በተጨባጭ ማስረጃዎች አረጋግጫለሁ ብሏል ተቋሙ፡፡
በሺህዎች የሚቆጠሩ ደቡብ ሱዳናውያን ህጻናት የሚልሱ የሚቀምሱት አጥተው በርሃብ ሲቆራመዱ፣አራቱ የፕሬዚዳንት ሳልቫ ኬር ልጆች በናይሮቢ በሚገኝ እጅግ ውድ ትምህርት ቤት ውስጥ 10 ሺህ ዶላር እየተከፈለላቸው ተንደላቀው ይማራሉ ተብሏል፡፡ የደቡብ ሱዳን መንግስት ቃል አቀባይ በበኩላቸው፤ሪፖርቱን ረብ የለሽ ሲሉ ያጣጣሉ ሲሆን መንግስታቸው፣ ሪፖርቱን በአዘጋጀው ተቋም ላይ ህጋዊ እርምጃ ለመውሰድ ማቀዱን አስታውቀዋል፡፡

 ከታዋቂው ማህበራዊ ድረገጽ ፌስቡክ መስራቾች አንዱ የሆነው ቢሊየነሩ ደስቲን ሞስኮቪትዝ፣ ዶናልድ ትራምፕ የአሜሪካ ቀጣዩ ፕሬዚዳንት ሆነው እንዳይመረጡ ለማድረግ የሚውል 20 ሚሊዮን ዶላር መመደቡን ፎርብስ መጽሄት ዘግቧል፡፡
ሞስኮቪትዝ እና ባለቤቱ ለዲሞክራት ፓርቲ ደጋፊ ቡድኖች 20 ሚሊዮን ዶላር በመለገስ፣ ቅስቀሳዎችን በዘመቻ መልክ እንዲያጧጡፉና ሄላሪ ክሊንተን ትራምፕን በመርታት፣ቀጣዩዋ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት እንዲሆኑ ለማስቻል ድጋፍ እንደሚያደርጉ አስታውቀዋል፡፡ ዶናልድ ትራምፕ በምርጫ አሸንፈው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ከሆኑ፣ አገሪቱ ወደ ውድቀት ማምራቷ አይቀርም፡፡ በአንጻሩ ሄላሪ ቢያሸንፉና ስልጣን ቢይዙ አገሪቱ ልእለ ሃያልነቷን አስጠብቃ ወደፊት ትጓዛለች፣ ስለዚህም ትራምፕ ወደ ዋይት ሃውስ የጀመሩትን ጉዞ ለማደናቀፍ፣እኔና ሚስቴ 20 ሚሊዮን ዶላር መድበናል ብሏል፤ሞስኮቪትዝ፡፡
ሞስኮቪትዝ ለትራምፕ ያለውን ተቃውሞ በይፋ ሲያስታውቅ ይህ የመጀመሪያ ጊዜው አይደለም ያለው ዘገባው፤ ባለፈው ሃምሌ ወር የትራምፕ መመረጥ የቴክኖሎጂ ፈጠራን አደጋ ላይ ይጥለዋል በሚል ፊርማቸውን ካሰፈሩ 145 ታዋቂ የቴክኖሎጂው ዘርፍ ባለሃብቶችና ተመራማሪዎች አንዱ  እንደነበርም አስታውሷል፡፡

   ከዕለታት አንድ ቀን በአንድ ትምህርት ቤት ውስጥ አንድ የድርሰት አስተማሪ ለተማሪዎቹ፤ “አንድ ታሪክ ፃፉ፡፡ ከዚያም ያ ታሪክ የሚሰጠንን ትምህርት ወይም ግብረገብነት ታስረዳላችሁ” ሲል ይገልጻል፡፡
ተማሪዎቹ ሁሉ የመሰላቸውን ድርሰት ይፅፋሉ፡፡ ሶስት ተማሪዎች ይመርጥና ታሪኮቻቸውን እንዲያነብቡ ይጠይቃል፡፡ የመጀመሪያዋ ልጅ፤ “አባቴ አንድ እርሻ አለው፡፡ የዶሮ እርባታም አለው፡፡ ዶሮዎቹ እንቁላል ሲፈለፍሉ ወደ ገበያ ወስደን እንቁላል እንሸጣለን፡፡ ጥሩ ገንዘብ እናገኛለን፡፡ አንድ ቀን ግን ከእርሻ ወደ ገበያ ስንሄድ መኪናችን ከሌላ መኪና ጋር ተጋጨና፣ ቅርጫት ውስጥ የነበሩት እንቁላሎች በሙሉ መሬት ላይ
ወድቀው ተሰባበሩ!” አለችና ጨረሰች፡፡ አስተማሪውም፤ “ከዚህ የምናገኘው ትምህርት ምንድነው?” ሲል ጠየቀ፡፡ ልጅቷም፤ “እንቁላሎቻችንን በሙሉ አንድ ቅርጫት ውስጥ አናስቀምጥ” ስትል መለሰች።
ሁለተኛው ልጅ የሚከተለውን ታሪክ አነበበ፤ “የእኔ አባት የዶሮ እርባታ አለው፡፡ በየሳምንቱ እንቁላሎቹን ማስፈልፈያ ሳጥን (ኢንኩቤተር) ውስጥ እንከታቸዋለን፡፡ ባለፈው ሳምንት ከአሥራ ሁለቱ እንቁላሎች ስምንቱ ብቻ ጫጩት ፈለፈሉ” አለ፡፡ አስተማሪው፣ “ከዚህ ታሪክ የምናገኘው ትምህርት ምንድነው?” ሲል ጠየቀ፡፡
ልጁም፤ “እንቁላሎቻችሁ ጫጩት ከመፈልፈላቸው በፊት አትቁጠሯቸው፡፡ ጫጩቶቹን ቁጠሩ”
ሶስተኛው ልጅ፤ “አባቴ ጦርነት ውስጥ ገብቶ ያውቃል፡፡ አውሮፕላን አብራሪ ነው፡፡ አውሮፕላኑ ተመታ። በጠላት ወረዳ ከመውደቁ በፊት ግን አባቴ በፓራሹት ወረደ፡፡ አንድ ጠመንጃ፣ አንድ ጎራዴና አንድ ሳጥን
ቢራ ይዞ ነበር የወረደው፡፡ መንገድ ላይ ቢራውን ጠጣው፡፡ እንደ ክፉ አጋጣሚ መቶ የሚሆኑ
የጠላት ወታደሮች መጡበት፡፡ አንድ ሰባ የሚሆኑትን በጥይት ጣላቸው። ጥይት ጨረሰ፡፡ ጎራዴውን
መዞ ሃያ የሚሆኑትን አንገታቸውን ቀላ፡፡ የጎራዴው ስለት ተሰበረ፡፡ በባዶ እጁ የቀሩትን ጣላቸው”
ሲል ጨረሰ፡፡
አስተማሪው፤
“ከዚህ የምናገኘው ትምህርት (ግብረገብነት) ምንድነው?” አለው፡፡
ተማሪውም፤
“አባቴ ከጠጣ በኋላ አይቻልም! ያኔ ከሱ ጋር መቀለድ አደገኛ ነው” አለ፡፡
*          *        *
ከየአንዳንዱ የህይወት እንቅስቃሴ የምናገኘው ትምህርት መኖር አለበት፡፡ ዕንቁላሎቻችንን ሁሉ፤ በአንድ ቅርጫት ውስጥ አለማስቀመጥ አደጋ በመጣብን ጊዜ ሁሉንም በአንዴ እንዳናጣ ይበጀናልና ትልቅ ጠቀሜታ አለው፡፡ አንድም ደግሞ ገበያችን ላይ ብቻ በማተኮር ለግጭት መዳረግ የለብንም፡፡ በዕንቁላሎቻችን ቁጥር ልክ ሁሉ ጫጩት እናገኛለን ብለን መገመትም የዋህነት ነው፡፡ የተቀፈቀፈው ሁሉ አይወለድም!! የታሰበው ሁሉ ፍሬ ላያፈራ ይችላል። የኢንኩቤተር ሙቀት ስላለ ብቻ ሁሉም ጫጩቶች እንደፈለግናቸው አይፈለፈሉም፡፡ ግምቶቻችንም መሰረት ያላቸው ሊሆኑ ይገባል ማለት ነው፡፡ ባለፉት ወራት እስከ አዲሱ ዓመት ድረስ ተከስተው የነበሩ የእንቅስቃሴ ሁኔታዎች አንዳንድ ትምህርትና ግብረ ገብነትን አስጨብጠውን ማለፍ አለባቸው! የህዝብ ብሶት ምሬትና ያልተመለሰ ጥያቄ ከጠባብ ንፍቀ ክበብኝነት ተነስቶ አገሩን ሊያዳርስ እንደሚችል ያመላክታል፡፡ መንግሥት ውጪያዊ ሰበብ መፈለጉን (externalization) እና በሌሎች ማላከኩን (Blame-shifting) ትቶ ራሱን ወደ ውስጥ እያየ መፈተሽ እንዳለበት መገንዘብ እንደሚገባው አይተናል፡፡ ግምገማዎቹን የለበጣ እንዳያደርጋቸው ታላቅ ኃላፊነትን የሚጠይቅ ሁኔታ ውስጥ መግባቱን አስተውለናል፡፡
አመራሮች ራሳቸውን ባልለወጡ ጊዜ ባለስልጣናትን ካንድ ወንበር ሌላ ወንበር ማሸጋገር ቢሮክራሲያዊ ሽርሽር ብቻ ነው! ጥፋትን እንደማንሸራሸር ነው! “የኔ ክልል ካንተ ክልል ይሻላል” ማለትም የእኩልነትን መርህ የጣሰ አመለካከት እንደሆነ ልብ ብለናል፡፡ ህዝብ ባለቤቱ የሆነን ጉዳይ፣ “ባለቤት የሌለው እንቅስቃሴ ነው” ማለት እንቅስቃሴውን እንዳላቆመውም አስተውለናል! የመንግስትን ስልጣን ለግል ጥቅም ማዋል፣ የአዘቦት ቀን ወግ ሆኖ ሳለ፤ ለእንቅስቃሴም ወሳኝ ጨዋታ ነው ብለን ማሰብም የዋህነት መሆኑን ተገንዝበናል፡፡ ለህዝብ ጥያቄ አፋጣኝ ምላሽ አለመስጠት አንድም ዳተኝነት ሳይሆን ተዓብዮ (arrogance)፤ አንድም ደግሞ ጠባብ አመለካከት ከመያዝ (Narrow Nationalism) የሚመነጭ፣ “ሁለት ጥፉ ካገር ጥፉ”፤ ሂደት ነበር፡፡ የክልል
ጠባብነት፣ አንድ ልዩ አደጋ እንደሆነ አንርሳ!
(Provincialism እንዲሉ)፡፡ ከሁሉም በላይ በቅራኔ ውስጥ መሸብለቃችንን አንርሳ። ባንድ ወገን “የህዝቡ ጥያቄ ትክክል ነው - አፋጣኝ መልስ ይሻል” እያልን፤ በሌላ ወገን “ህገ መንግስታዊ መብት ተጥሶ ሁከትና ብጥብጥ አያስፈልግም” ብለናል፡፡ ለምን? እንዴት? እንበል ጎበዝ! ዕውነተኛ ግምገማ መሰረቱ በህዝብ ማመን ነው! ጥልቅ ተሐድሶ መሰረታዊ ለውጥ የማምጣቱ ጉዳይ ካልሆነ ከንቱ ድካም ይሆናል!
የኢትዮጵያ መልክ እንዲለወጥ የአመራሮች አስተሳሰብ በግድ መለወጥ አለበት! ለውጥ ድንገቴ ሳይሆን ሂደት ነው! ገጠመኝም አይደለም!
እንግዲህ ለውጥ እንፈልጋለን ካልን፣ ኢትዮጵያ የ1966 ዓመተ ምህረትን ዓይነት፤ “ጉልቻ ቢለዋወጥ
ወጥ አያጣፍጥም” መሪ መፈክር አይሰራም ብላ ማመን ግዷ ነው!! ያየናቸው ጉልቻዎች በቂ
ናቸውና፡፡ ጎበዝ! ከስህተት እንማር! የተሻለ ስህተት እንሥራ - አሁንም አልረፈደም - ጉዟችን ገና
ነው - ምርጥ ስህተት እንስራ!!

በምግብ ዝግጅት ባለሙያዋ አዝመራ ካሳሁን የተፃፈውና ከ6 ወር ህፃን፣ ት/ቤት እስከ ሚቋጠር የልጆች ምግብ አዘገጃጀት ያስተምራል የተባለው “ከቤት እስከ ት/ቤት” የተሰኘ የህፃናት ምግብ አዘገጃጀት መፅሐፍ ዛሬ በካሌብ ሆቴል ከረፋዱ 4፡00 ጀምሮ ይመረቃል፡፡
በ51 ገፆች የተቀነበበውና በ50 ብር ለገበያ የቀረበው መፅሀፉ፤ የትኛውም ወላጅ በአካባቢው በቀላሉ በሚገኙ የምግብ ጥሬ ዕቃዎች ለልጆቹ እንዴትና በምን ሁኔታ ምግብ በማዘጋጀት መመገብና ጤናማ ማድረግ እንደሚችል ያሳያል ተብሏል፡፡በምርቃት ስነ - ስርዓቱ ላይ ወላጆች፣ የት/ቤቶች ባለቤቶች ህፃናት ላይ የሚሰሩ ድርጅቶችና በርካታ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እንደሚገኙ የመፅሀፉ አዘጋጅ ወ/ሮ አዝመራ ካሳሁን ተናግረዋል፡፡

 አብርሀም ግዛው ኢንተርቴይመንትና የፕሬስ ስራዎች፣ ከጄቲቪ ጋር በመተባበር ‹‹መስቀልና ባህላዊ አከባበሩ›› የተሰኘ ልዩ የመዝናኛ ፕሮግራም ማዘጋጀቱን ገለጸ፡፡
ፕሮግራሙ በካፒታል ሆቴል ነገ የሚቀረጽ ሲሆን የአገር ሽማግሌዎች ምርቃት፣ የእርድ ስነ-ስርዓት፣ የደመራ ማብራት ስነ- ስርዓት፣ ባህላዊና ዘመናዊ የሙዚቃ ዝግጅቶች፣ ባህላዊ የጉራጌ አለባበስ የፋሺን ትርኢትና ሌሎች ዝግጅቶች እንደሚካሄዱ ለማወቅ ተችሏል፡፡ በፕሮግራሙ ላይ ታዋቂ ሰዎች ገጠመኞቻቸውን ለታዳሚው የሚያካፍሉ ሲሆን በጉራጌ ማህበረሰብ ለመስቀል በዓል የሚደረገው ቅድመ ዝግጅት ለዕይታ ይቀርባል ተብሏል፡፡ በመዝናኛ ፕሮግራሙ ላይ ታዋቂ ሰዎች፣ አርቲስቶች፣ የሚዲያ ባለሙያዎችና ጥሪ የተደረገላቸው የመንግስት የስራ ሃላፊዎች እንደሚታደሙ አዘጋጁ ጋዜጠኛ አብርሃም ግዛው ጨምሮ ገልጿል፡

ሚዩዚክ ሜይዴይ፤ ከኢትዮጲስ ኮሌጅ ጋር በመተባበር፣ ነገ ከቀኑ 8፡00 ጀምሮ በብሄራዊ ቤተ-መፃህፍትና ቤተ መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ፣ ‹‹ምስክርነት›› በተሰኘው የሻምበል ተስፋዬ ርስቴ መፅሐፍ ላይ ውይይት ያካሂዳል፡፡ ለውይይቱ የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት የ‹‹ጅቡቲ›› መፅሐፍ ደራሲ የሆኑት ዶ/ር በለጠ በላቸው ሲሆኑ፣ማንኛውም ፍላጎት ያለው ሰው በውይይቱ ላይ እንዲሳተፍ ሚዩዚክ ሜይዴይ ጋብዟል፡፡

   ከወራት በፊት የአሲድ ጥቃት ለደረሰባት ወጣት መሰረት ንጉሴ ህክምና የሚውል ገቢ ማሰባሰቢያ የሙዚቃ ድግስ ጀክሮስ አካባቢ በሚገኘው ጋላኒ ኮፊ ውስጥ ከቀኑ 8 ሰዓት እስከ 12 ሰዓት እንደሚካሄድ አዘጋጁ ሴታዊት ንቅናቄ ገለፀ፡፡ በመዚቃ ድግሱ ላይ ፀደንያ ገ/ማርቆስ፣ ማርታ ታደሰና ቼሊና የሚያቀነቅኑ ሲሆን በድግሱ ላይ ለመታደም መግቢያ በነፃ እንደሆነ ታውቋል፡፡ ከሙዚቃ ድግሱ በተጨማሪ የስዕልና የፎቶግራፍ ሽያጭ የሚካሄድ ሲሆን ገቢው ሙሉ በሙሉ ለተጎጂዋ እንደሚሆን ከሴታዊት ንቅናቄ መስራቾች አንዷ የሆኑት  ዶ/ር ስሂን ተፈራ ገልጸዋል፡፡ በዝግጅቱ ላይ በጥቃት መከላከል ላይ የሚሰሩ የድርጅት ተወካዮች፣ የመንግስት ሃላፊዎች፣የኪነ-ጥበብ ባለሙያዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እንደሚገኙ የተገለጸ ሲሆን ተጎጂዋ በቦታው ተገኝታ ንግግር እንደምታደርግም ታውቋል፡፡ ማንኛውም ጉዳዩ ይመለከተኛል የሚል አካል በፕሮግራሙ ላይ ተገኝቶ፣ለተጠቂዋ ወገናዊነቱን እንዲያሳይ አዘጋጆቹ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

  - 20 ሺህ ዶላር ያህል እንደሚያወጣ ተገምቷል
    በዘንድሮው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ሪፐብሊካንን ወክለው በመወዳደር ላይ የሚገኙትን አነጋጋሪው ዕጩ የዶናልድ ትራምፕ እርቃን ተክለ ሰውነት የሚያሳየው ሃውልት ለጨረታ ሊቀርብ ነው ሲል ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
እንደ ሰውዬው አነጋጋሪ የሆነውና ዘ ኢምፐረር ሃዝ ኖ ቦልስ የሚል ስያሜ የተሰጠው ይህ ሃውልት፣ በመጪው ጥቅምት ወር አጋማሽ ላይ ጁሊንስ በተባለ አጫራች ኩባንያ አማካይነት በሎሳንጀለስ ለጨረታ እንደሚቀርብ የጠቆመው ዘገባው፤ሃውልቱ እስከ 20 ሺህ ዶላር ሊሸጥ እንደሚችል መገመቱን አስታውቋል፡፡
ኢንዲክላይን የተባለው የስነጥበብ ኩባንያ ንብረት የሆነውና የዶናልድ ትራምፕን ያልተሟላ ተክለ-ሰውነት በማሳየት በሰውየው ወንድነት ላይ ይሳለቃል የተባለው ሃውልት ተሸጦ ከሚገኘው ገቢ የተወሰነው ለስደተኞች መብቶች ለሚሟገት አንድ ግብረ ሰናይ ተቋም እንደሚለገስ ታውቋል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ዶናልድ ትራምፕ ላይ የሚሳለቁ ሌሎች አምስት ሃውልቶች ከዚህ ቀደምም በአሜሪካ የተለያዩ አካባቢዎች ተሰርተው ለእይታ እንደበቁ ዘገባው አስታውሷል፡፡

- በአገሪቱ የአህዮች ዋጋ በ3 እጥፍ አድጓል
      በኒጀር አህዮችን ወደ ውጭ ገበያ የሚልኩ የንግድ ተቋማት መበራከታቸውንና የአገሪቱ አህዮች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ መመናመኑን ተከትሎ የኒጀር መንግስት ባለስልጣናት የአህያ ኤክስፖርትን የሚከለክል ህግ ማውጣታቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የአገሪቱ የንግድ ተቋማት ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው አህዮችን ወደ ሌሎች አገራት በመላክ ከፍተኛ ትርፍ እያገኙ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፤ የአገሪቱ አህዮች በብዛት የሚላኩት ወደ እስያ አገራት መሆኑንና ቀዳሚውን ስፍራ የምትይዘውም ቻይና እንደሆነች ገልጧል፡፡ ባለፈው አመት ለውጭ ገበያ የቀረቡ የኒጀር አህዮች ብዛት 27 ሺህ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፤ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ብቻም ከ80 ሺህ በላይ የአገሪቱ አህዮች ወደተለያዩ የአለማችን አገራት መላካቸውን ጠቁሟል፡፡
አህያ በተለይ በአገሪቱ የገጠር አካባቢ ማህበረሰብ ዋነኛ የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪ መሆኑን የጠቆመው ዘገባው፤ የኒጀር መንግስት ባለስልጣናትም አህዮችን በብዛት ለውጭ ገበያ ማቅረቡ በዚሁ ከቀጠለ አስጊ ሁኔታ ይፈጠራል በሚል የውጭ ንግዱን የሚከለክል ህግ ማውጣታቸውን አመልክቷል፡፡ የውጭ ንግዱ መስፋፋቱን ተከትሎ ባለፉት ጥቂት ወራት ብቻ በአገሪቱ የአህዮች ዋጋ በሶስት እጥፍ ያደገ ሲሆን በኒጀር አንድ አህያ እስከ 150 ዶላር ዋጋ እንደሚያወጣ ዘገባው አስታውቋል፡፡