
Administrator
ቅዱስ ሲኖዶስ፤ የተሳሳተው የትግርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም እንዳይሠራጭ አገደ
“በትግራይ በሃይማኖት ምክንያት የማይግባባ ማኅበረሰብ እየተፈጠረ ነው” /ምእመናን/
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ፣ ግድፈት አለበት በሚል በመቐለ ከተማና አካባቢዋ ሊቃውንትና ምእመናን ተቃውሞ የቀረበበት የትግርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም እንዳይሠራጭ ያገደ ሲሆን፤ አተረጓጎሙና ይዘቱ በሊቃውንት ጉባኤ እንዲመረመር አዘዘ፡፡
የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር በ2007 ዓ.ም. ያሳተመው የትግርኛ ትርጉም፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ፣ ከኢትዮጵያ ካቶሊካዊትና ወንጌላውያን ኅብረት አብያተ ክርስቲያናት በጋራ ያሳተመችው ቢኾንም፤ ትግራይን ጨምሮ በማንኛውም አህጉረ ስብከት እንዳይሠራጭ፣ ቅዱስ ሲኖዶሱ ለማኅበሩ ማስታወቁ ተገልጿል፡፡
የቋንቋ አጠቃቀም፣ አተረጓጎምና ይዘት፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ የሊቃውንት ጉባኤ እንዲመረመር ትእዛዝ የሰጠው ቅዱስ ሲኖዶሱ፣ “ውጤቱ ታይቶ ውሳኔ እስኪሰጥ ድረስ ኅትመቱ የታገደ መኾኑ እንዲታወቅ ለሚመለከተው ኹሉ ይገለጥ፤” ሲል ወስኗል፡፡
መጽሐፍ ቅዱሱ በትግርኛ ቋንቋ መተርጎሙ፣ ለኅብረተሰቡ አስፈላጊ እንደኾነ ቢታመንበትም የተዛባ መኾን እንዳልነበረበት በአቤቱታቸው የተቹት ሊቃውንቱና ምእመናኑ፤ በመላው ትግራይ መለያየትና ሁከት እየፈጠረ እንደኾነና ወደ ወረዳዎች የተበተነው የኅትመቱ ቅጅ እንዲሰበሰብ ወይም ማስተካከያ ደብዳቤ ወደ ኹሉም ወረዳዎች እንዲጻፍ፣ ካለፈው ግንቦት ጀምሮ ሲጠይቁ ቆይተዋል፤
ከ92 በመቶ በላይ የክልሉ ሕዝብ፣ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታይ በኾነበት፣ አተረጓጎሙ ለሌሎች የክርስትናው እምነቶች አስተምህሮ እንዲመችና መሠረታዊ ዶክትሪኗን በሚፃረር መልኩ መታተሙ፣ ቤተ ክርስቲያኒቱ፣ ከማኅበሩ ከምትጠቀም ይልቅ የምትጎዳበት እያመዘነ እንደመጣ ያመለክታል፤ ብለዋል፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍቱን በጥንቃቄ የሚመረምር የሊቃውንት ጉባኤ በሀገርና በአህጉረ ስብከት ደረጃ ማጠናከርና ራሱን የቻለ የዲጅታል ኅትመት ተቋም እንድታቋቁምም ጠይቀዋል፡፡
በሌላ በኩል፤ ምእመናኑ፣ በመቐለ ቅዱስ ፍሬምናጦስ አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን መንፈሳዊ ኮሌጅና በክልሉ የተለያዩ ወረዳዎች፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን የእምነት ነጻነት እየተጋፉ ነው፤ ያሏቸው የሌሎች ቤተ እምነቶችና ምልምሎቻቸው ድርጊት ሳቢያ፣ “በሃይማኖት ምክንያት የማይግባባ ማኅበረሰብ እየተፈጠረ ነው፡፡ ይህም ለቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይኾን ለአገርም አለመረጋጋት የሚፈጥር ነው፤” ብለዋል ምእመናኑ፡፡ መቐለንና አካባቢዋን ጨምሮ ኵሓ፣ ፈለገ ዳዕሮ፣ ሓውሰዋ፣ ደንጎላትና ሌሎች የደቡብ ምሥራቅ አካባቢዎች ችግሩ እንደሚታይባቸው ጠቅሰው፣ ሊወሰዱ ይገባሉ ያሏቸውን የጥንቃቄ ርምጃዎችም በአቤቱታቸው አመልክተዋል፡፡
መንፈሳዊ ኮሌጁ፣ ችግሩ ባለባቸው ደቀ መዛሙርት ላይ፣ ካለፈው 2008 ዓ.ም ጀምሮ የሚወስደውን የመለየትና የማጥራት ርምጃ አጠናክሮ እንዲቀጥል፤ በተማሪዎች ምልመላ ጥንቃቄ እንዲደረግ፤ አስተዳደሩና መምህራኑም በጥልቀት እንዲጤኑ የሚሉት፣ በመፍትሔነት ከዘረዘሯቸው ተግባራት ይገኙበታል። የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስና ሀገረ ስብከቱም፣ የሚጠበቅባቸውን እንዲወጡና ይህን አስመልክቶም በጠቅላይ ጽ/ቤቱ ቀደም ሲል የተላለፉ ውሳኔዎች ተግባራዊ እንዲደረጉላቸው ምእመናኑ ጠይቀዋል፡፡
ለኢትዮጵያ ዝቅተኛ ግምት በተሰጠበት የዓለም ሻምፒዮና
• 7.3 ሚ ዶላር የሽልማት ገንዘብ ተዘጋጅቷል፡፡
• ከ660 ሺ በላይ ትኬቶች ተሸጠው ሪከርድ ተመዝግቧል፡፡
• ብሬንዳን ፎስተርና ፖል ቴርጋት ልዩ የክብር ሽልማት ተሰጥቷቸዋል፡፡
• ቦልት፤ ሞ ፋራህ እና ጥሩነሽ የመጨረሻ ተሳትፏቸውን ያደርጋሉ፡፡
• ጥሩነሽ 6ኛዋን የወርቅ ሜዳልያ በ10ሺ ሜ እንደምታገኝ ብዙ ሲገመት፤ ለኢትዮጵያ ሌላ የወርቅ ሜዳልያ የተጠበቀው በወንዶች ማራቶን ብቻ ነው፡፡
• ገንዘቤ በ1500 ሜትር ፤ አልማዝ አያና በ5 ሺ ሜ፣ እንዲሁም ማሬ ዲባባ በማራቶን የሻምፒዮናነት ክብራቸውን ሊነጠቁ ይችላሉ፡፡ የአትሌቲክስ ዊክሊእና የትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ ትንበያዎች
16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በለንደን ከተማ በሚገኘው ኦሎምፒክ ስታድዬም ትናንት ተጀምሯል። 205 አገራትን የሚወክሉ 2000 አትሌቶች ለ10 ቀናት በሚካፈሉበት ሻምፒዮናው 7.3 ሚሊዮን ዶላር የሽልማት ገንዘብ ተዘጋጅቷል፡፡ በሽልማቱ ዝርዝር አከፋፈል መሰረት ለወርቅ ሜዳልያ 60ሺ ዶላር፤ ለብር ሜዳልያ 30ሺ ዶላር እንዲሁም ለነሐስ ሜዳልያ 20ሺ ዶላር የሚታሰብ ሲሆን ለአራተኛ ደረጃ 15ሺ ዶላር፤ ለአምስተኛ ደረጃ 10ሺ ዶላር፤ ለስድስተኛ ደረጃ 6ሺ ዶላር፤ ለሰባተኛ ደረጃ 5ሺ ዶላር እንዲሁም ለስምንተኛ ደረጃ 4ሺ ዶላር የሚበረከት ይሆናል፡፡ በሌላ በኩል በሻምፒዮናው ላይ አዲስ የዓለም ሪከርድ ለሚያስመዘግቡ አትሌቶች የውድድሩ አብይ ስፖንሰሮች ቲዲኬ 100ሺ ዶላር እንዲሁም በተጨማሪ ቶዮታ 100ሺ ዶላር እንደሚሰጡ ታውቋል። ሻምፒዮናውን የሚያስተናግደውና የዌስትሃም ክለብ ሜዳ የሆነው የኦሎምፒክ ስታድዬም በ563 ሚሊዮን ዶላር የተገነባ ነው፡፡
ለ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና 1.04 ሚሊዮን ስታድዬም የመግቢያ ትኬቶች ለገበያ ቀርበው ከ660 ሺ በላይ የተሸጡ ሲሆን ይህም በ2009 እኤአ ላይ በበርሊኑ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ417, 156 የተመዘገበውን የትኬቶች ሽያጭ ክብረወሰን ያሻሻለ ሆኗል፡፡
በሻምፒዮናው ዋዜማ ላይ የዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር 51ኛው የኮንግረስ ጉባኤ የተካሄደ ሲሆን ከ200 በላይ አገራት ተሳትፈውበታል፡፡ በዚሁ ጉባኤ ላይ ለታዋቂው እንግሊዛዊ የረጅም ርቀት ሯጭ እና፤ የታላቁ ሩጫ ኩባንያ በእንግሊዝ መስራች ብሬንዳን ፎስተር የአይኤኤኤፍ ‹‹ጎልደን ኦርደር ኦፍ ሜሪት›› ፤ ለኬንያዊው የረጅምር ርቀት ሯጭ ፤ የዓለም አቀፉ ኦሎምፒክ ኮሚቴ አባል ፖል ቴርጋት ደግሞ የአይኤኤኤኤፍ ‹‹ፕላግ ኦርደር ኦፍ ሜሪት›› ሽልማቶች ተበርክተዋል፡፡
በዓለም ሻምፒዮና ላይ ለመጨረሻ ግዜ በመሳተፍ ልዩ ትኩረት ከሳቡት መካከል ጃማይካዊው ዩሴያን ቦልት፤ እንግሊዛዊው ሞ ፋራህ፤ እና ኢትዮጰያዊቷ ጥሩነሽ ዲባባ ዋናዎቹ ናቸው፡፡ በዓለም ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪኩ 11 የወርቅ ሜዳልያዎችን የሰበሰበው ጃማይካዊው ዩሴያን ቦልት ከለንደን የዓለም ሻምፒዮና የመጨረሻ ተሳትፎው በኋላ ጡረታ ለመውጣት መወሰኑ ሲያነጋግር ሰንብቷል፡፡
ቦልት በዓለም ሻምፒዮናው ለመጨረሻ ጊዜ በ100 ሜትር እና በ4 በ100 ሜትር ውድድሮች በመሳተፍ 2 የወርቅ ሜዳልያዎች ማግኘት ከቻለ በሻምፒዮናው ታሪክ በአጭር ርቀት 13 የወርቅ ሜዳልያዎች በመጎናፀፍ ከፍተኛውን የውጤት ክብረወሰን የሚያስመዘግብ ይሆናል፡፡ ዩሴያን ቦልት በሩጫ ዘመኑ 60 ሚሊዮን ዶላር ሃብት ያካበተ ሲሆን በውድድር ያገኛቸው ሽልማቶች እስከ 2.24 ሚሊዮን ዶላር ብቻ ነው፡፡ ዘ ቴሌግራፍ በሰራው ትንታኔ ዩሴያን ቦልት አብዛኛውን ገቢ የሚያገኘው ከስፖንሰሮቹ ሲሆን በተለይ እስከ 2025 እኤአ ከፑማ ኩባንያ ጋር በፈፀመው ውል በየዓመቱ የሚከፈለው 3.1 ሚሊዮን ዶላር ትልቁ ገቢው ነው። ጋቶርዴ፤ ሁብቦልት፤ ቨርጂን ሚዲያ፤ ቪዛ ካርድ እና ኒሳን ሞተርስ ሌሎች የአትሌቱ ስፖንሰሮች ናቸው። የዩሲያን ቦልትን የአትሌቲክስ ገቢ ቴሌግራፍ ሲያሰላ በዓለም ሻምፒዮና 728ሺ ዶላር እንዲሁም 23 ጊዜ የዳይመንድ ሊግ ውድድሮችን በማሸነፍ 210ሺ ዶላር ማግኘቱን ጠቅሶ በ2009 እኤአ በርሊን ባስተናገደችው 11ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ 2 የዓለም ሪከርዶችን በ100 ሜትር 9.58 ሰከንዶች እንዲሁም በ200 ሜትር 19.19 ሰኮንዶች ሲያስመዘግብ የወሰደው 200ሺ ዶላር የሪከርድ ቦነስ መሆኑን አመልክቷል፡፡ በሌላ በኩል የ34 ዓመቱ እንግሊዛዊ ሞ ፋራህ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የመጨረሻውን ተሳትፎ የሚያደርግ ሲሆን በሶስት ተከታታይ የዓለም ሻምፒዮናዎች በ5ሺ ሜትር እና በ10ሺ ሜትር ውድድሮች ድርብ የወርቅ ሜዳልያዎች በመሰብሰብ በታሪክ የመጀመርያው አትሌት ለመሆን አነጣጥሯል፡፡በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናው ለስድስተኛ ጊዜ የምትሳተፈው ጥሩነሽ ዲባባ 6ኛውን የወርቅ ሜዳልያ በ10ሺ ሜትር በመሳተፍ ማስመዝገቧ አዲስ የታሪክ ከፍተኛ የውጤት ክብረወሰን ሆኖ ሊጠቀስ ይችላል፡፡
በታዋቂዎቹ የአትሌቲክስ ዘጋቢ ድረገፆች ትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ እና አትሌቲክስ ዊኪሊ ድረገፆች ለ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ተዘጋጅተው የወጡ የሜዳልያ ትንበያዎች ለኢትዮጵያ ዝቅ ያለ ግምት ሰጥተዋል፡
ከ1 ሳምንት በፊት ተሻሽሎ የተሰራጨው የትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ እንዲሁም የአትሌቲክስ ዊክሊ የወርቅ፤ የብርና የነሐስ ሜዳልያዎች ዝርዝር ግምት እንዲሁም ያለፉት 15 የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች የውጤት ታሪክ፤ የውድድር ፕሮግራሞች እና ኢትዮጵያን የሚወክሉ አትሌቶች ከዚህ በታች ቀርበዋል፡፡
በ800 ሜትር
ለኢትዮጵያ የተሰጠ የሜዳልያ ግምት የለም
ባለፉት 15 ሻምፒዮናዎች (1 የወርቅ ሜዳልያ በወንዶች)
በ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ኢትዮጵያን በመወከል የሚሳተፉት አትሌቶች ሐብታም አለሙ፤ ኮሬ ቶላ ፤ ማህሌት ሙሉጌታ(በሴቶች) እንዲሁም መሃመድ አማን (በወንዶች) ናቸው፡፡ ለኢትዮጵያ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ800 ሜትር ብቸኛው ውጤት በወንዶች የመጀመርያውን የወርቅ ሜዳልያ ድል በ2013 እኤአ ላይ በሞስኮ ያስመዘገበው መሃመድ አማን ነው፡፡ አትሌቲክስ ዊኪሊ በሰራው ትንብያ በወንዶች ምድብ የወርቅ ሜዳልያው ለኬንያዊው ኢማኑዌል ኮሪር፤ የብር ሜዳልያው ለቦትስዋናው ኒጄል አሞስ እንዲሁም የነሐስ ሜዳልያው ለኬንያው ኪፕዮጌ ቤት የተገመተ ሲሆን በሴቶች ምድስብ ደግሞ የወርቅ ሜዳልያው ለደቡብ አፍሪካዋ ካስተር ሴማንያ፤ የብር ሜዳልያው ለብሩንዲዋ ፍራንኪሶ ኒኮሻ እንዲሁም የነሐስ ሜዳልያው ለአሜሪካዋ አጄ ዊልሰን ተሰጥቷል፡፡
ትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ ለሴቶች የሰራው ትንበያ ከአትሌቲክስ ዊክሊ ጋር የተመሳሰለ ሲሆን በወንዶች ግን የወርቅ ሜዳልያው ለቦትስዋናው ኒጄል አሞስ፤ የብር ሜዳልያው ለኢማኑዌል ኮሪር እንዲሁም የነሐስ ሜዳልያው ለኬንያው ኪፕዮጌ ቤት ነው የተገመተው፡፡
በ1500 ሜትር
የዓለም ሻምፒዮንና የዓለም ሪከርድ ባለቤት ገንዘቤ የነሐስ ሜዳልያ ተገምቶላታል
ባለፉት 15 ሻምፒዮናዎች በሴቶች 1 የወርቅ ሜዳልያ ፤ በወንዶች 1 የብር ሜዳልያ
በ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ኢትዮጵያን በመወከል የሚሳተፉት አትሌቶች በሴቶች ገንዘቤ ዲባባ (ሻምፒዮን)፤ ጉዳፍ ፀጋዬ፤ በሱ ሳዶና ፋንቱ ወርቁ ሲሆኑ በወንዶች ደግሞ አማን ወጤ፤ ሳሙኤል ተፈራና ተሬሳ ቶሎሳ ናቸው፡፡ ለኢትዮጵያ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ1500 ሜትር ብቸኛውን የወርቅ ሜዳልያ በ2015 እኤአ በቤጂንግ ያስመዘገበችው በሴቶች ገንዘቤ ዲባባ ናት፡፡ በወንዶች ደግሞ ብቸኛውን ውጤት በ2009 እኤአ በርሊን ላይ ደረሰ መኮንን በብር ሜዳልያ አስመዝግቦታል፡፡ አትሌቲክስ ዊኪሊና ትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ በሰሩት ትንበያ የሜዳልያ ውጤቶቹን በወንዶች ምድብ ለኬንያውያን ሙሉለሙሉ ሰጥተዋል። በሴቶች ደግሞ የወርቅ ሜዳልያውን ለኬንያዊቷ ፌዝ ኪፕዮጌ፤ የብር ሜዳልያውን ለባህሬኗ ትውልደ ኢትዮጵያዊት ሲፋን ሃሰን እንዲሁምየነሐስ ሜዳልያውን ለገንዘቤ ዲባባ አትሌቲክስ ዊክሊ ሲገምት ትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ ደግሞ የወርቅ ሜዳልያውን ለባህሬኗ ሲፋን ሃሰን ሰጥቶ የብር ሜዳልያውን ለኬንያው ፌዝ ኪፕዮጌ በመገመት ገንዘቤ ዲባባን ለነሐስ ሜዳልያ ጠብቋታል፡፡
በ3ሺ ሜ. መሰናክል
ለኢትዮጵያ የተሰጠ የሜዳልያ ግምት የለም
ባለፉት 15 ሻምፒዮናዎች በሴቶች 1 የብር 1 የነሐስ ሜዳልያዎች
በ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ኢትዮጵያን በመወከል የሚሳተፉት አትሌቶች በሴቶች ሶፍያ አሰፋ፤ እቴነሽ ዲሮና ብርቱካን ፈንቴ ሲሆኑ በወንዶች ደግሞ ጌትነት ዋሴ፤ ታፈሰ ሰቦቃና ተስፋዬ ድሪባ ናቸው፡፡ ለኢትዮጵያ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ3ሺ ሜትር መሰናክል በሁለቱም ፆታዎች የወርቅ የሜዳልያ ውጤት ተመዝግቦ አያውቅም፡፡ በ2013 እኤአ በሞስኮ ሲካሄድ በሴቶች የብር እና የነሐስ ሜዳልያዎች ተገኝተዋል፡፡ አትሌቲክስ ዊክሊና ትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ በሁለቱም ፆታዎች የሜዳልያ ግምቱን ለኬንያውያን ሰጥተዋል፡፡
በ5ሺ ሜትር
በሴቶች ሪከርድ ሊሰበር እንደሚችል፤ የወርቅ ሜዳልያው በኬንያ እንደሚነጠቅ ቢገመትም፤ የኢትዮጵያ አትሌቶች ከ1 እስከ 3 ተጠብቋል፡፡
በወንዶች ትልቁ ግምት ለሙክታር ኢድሪስ የተሰጠው የብር ሜዳልያ ነው፡፡
ባለፉት 15 ሻምፒዮናዎች በሴቶች 5 የወርቅ ፤ 1 የብርና 8 የነሐስ ሜዳልያዎች በወንዶች 1 የወርቅ፤ 3 የብርና 3 የነሐስ ሜዳልያዎች
በ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ኢትዮጵያን በመወከል የሚሳተፉት አትሌቶች በሴቶች ሻምፒዮናነቷን ለማጠበቅ የምትሰለፈው አልማዝ አያና፤ ገንዘቤ ዲባባ፤ ሰንበሬ ተፈሪና ለተሰንበት ግደይ ሲሆኑ በወንዶች ደግሞ ሙክታር እድሪስ፤ ሰለሞን ባረጋ፤ ዮሚፍ ቀጄልቻና በዳይመንድ ሊግ አሸናፊነቱ በቀጥታ መሳተፍ የሚችለው ሃጎስ ገ/ህይወት ናቸው፡፡ በዚህ ርቀት 16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ አዲስ የዓለም ሪከርድ ሊመዘገብ እንደሚችል በርካታ ዘገባዎች ይጠቅሳሉ፡፡ በተለይ ኢትዮጵያውያኑ ሴት አትሌቶች ገንዘቤ ዲባባ እና አልማዝ አያና ከመሳተፋቸው ጋር ተያይዞ ነው፡፡ በ5ሺ ሜትር ሴቶች ፍፁም የበላይነት ያላት ኢትዮጵያ ባለፉት ሁለት የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች የወርቅ ሜዳልያዎችን መውሰድ የቻለች ሲሆን በተሳትፎ ታሪኳ ከወንዶች እጅግ የላቀ ውጤት አላት፡፡ በ15 የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች በሴቶች 5 የወርቅ ፤ 1 የብርና 8 የነሐስ ሜዳልያዎችን ሰብስባለች። በ1999 እና በ2001 እኤአ ላይ በተደረጉት ሁለት ተከታታይ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች አየለች ወርቁ ሁለት የነሐስ ሜዳልያዎችን በማግኘት ፈርቀዳጅ ነበረች፡፡ ከዚያም በ2003 እኤአ ጥሩነሽ ዲባባ የወርቅ፤ በ2005 እኤአ ጥሩነሽ ዲባባ የወርቅ፣ መሰረት ደፋር የብር እንዲሁም እጅጋየሁ ዲባባ የነሐስ፤ በ2007 እኤአ መሰረት ደፋር የወርቅ፤ በ2009 እና በ2011 እኤአ መሰረት ደፋር ሁለት የነሐስ ሜዳልያዎች፤ በ2013 እኤአ ላይ መሰረት ደፋር የወርቅ እንዲሁም አልማዝ አያና የነሐስ ሜዳልያዎች፤ በ2015 እኤአ ደግሞ አልማዝ አያና የወርቅ ሰንበሬ ተፈሪ የነሐስ ሜዳልያዎችን ማግኘት ችለዋል። በወንዶች 5ሺ ሜትር በሻምፒዮናው ታሪክ ከአንድ ጊዜ በላይ የወርቅ ሜዳልያው ለማግኘት ለኢትዮጵያ ለማግኘት ሳይቻል ቆይቷል፡፡ የመጀመርያው የሜዳልያ ውጤት የተመዘገበው በ1991 እኤአ ላይ በፊጣ ባይሳ በተገኘው የብር ሜዳልያ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ በ1993 እኤአ ላይ ሃይሌ ገብረስላሴ የብርና ፊጣ ባይሳ የነሐስ፤ በ2001 እኤአ ላይ ሚሊዮን ወልዴ የብር፤ በ2003 እኤአ ላይ ቀነኒሳ በቀለ የነሐስ፤ በ2005 እኤአ ላይ ስለሺ ስህን የብር፤ በ2009 እኤአ ላይ ቀነኒሳ በቀለ የወርቅ እንዲሁም በ2011 እኤአ ላይ ደጀን ገብረመስቀል እንዲሁም በ2013 እኤአ ደጀን ገብረመስቀል የነሐስ ሜዳልያዎች፤ በ2015 እኤአ ደግሞ ሐጎስ ገብረህይወት የብር ወስደዋል፡፡ በአጠቃላይ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ5ሺ ሜትር ወንዶች ለኢትዮጵያ ያስመዘገቡት በወንዶች 1 የወርቅ፤ 3 የብርና 3 የነሐስ ሜዳልያዎች ብቻ ናቸው፡፡
አትሌቲክስ ዊከሊና ትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ በሰሯቸው የሜዳልያ ትንበያዎች በሁለቱም ፆታዎች ተመሳሳይ ሆነዋል፡፡ በሴቶች የወርቅ ሜዳልያውን ኬንያዊቷ ሄለን ኦቡሪ እንደምትወስድ ገምቶ የብር ሜዳልያውን ለገንዘቤ ዲባባ የነኘስ ሜዳልያውን ደግሞ ለአልማዝ አያና ሲሰጥ፤ በወንዶች ደግሞ የወርቅ ሜዳልያው ለሞ ፋራህ፤ የብር ሜልያው ለሙክታር ኢድሪስ እንዲሁም የነሐስ ሜዳልያ ለአሜሪካው ፖል ቼሌሞ እንደሚጠበቅ አመልክተዋል፡፡
በ10ሺ ሜትር
የአልማዝና የጥሩነሽ ፍጥጫ እንዲሁም ብቸኛው የወርቅ ሜዳልያ ለኢትዮጵያ በሴቶች ተጠብቋል፡፡
ባለፉት 15 ሻምፒዮናዎች በሴቶች 6 የወርቅ፣ 6 የብርና 4 የነሐስ ሜዳልያዎች በወንዶች 9 የወርቅ፣ 4 የብርና 5 የነሐስ ሜዳልያዎች
በ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ኢትዮጵያን በመወከል የሚሳተፉት አትሌቶች በሴቶች የዓለም ሪከርድ የያዘችውና የኦሎምፒክ ሻምፒዮኗ አልማዝ አያና፤ የምንግዜም የረጅም ርቀት ምርጥ ሯጭ ጥሩነሽ ዲባባ እና ደራ ዲዳ ሲሆኑ በወንዶች አባዲ ሃዲስ፤ ጀማል ይመርና አንዱአምላክ በልሁ ናቸው፡፡
በርግጥ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዋንኛው የኢትዮጵያ የበላይነት በ10ሺ ሜትር እንደሆነ የሚታወቅ ነው፡፡ ከ1983 እኤአ ጀምሮ በተካሄዱ 15 የዓለም ሻምፒዮናዎች ኢትዮጵያ 9 የወርቅ ሜዳልያ በወንዶች እንዲሁም 5 የወርቅ ሜዳልያ በሴቶች በማግኘት ተሳክቶላታል፡፡ በዓለም ሻምፒዮና ላይ በ10ሺ ሜትር ወንዶች የመጀመርያው የሜዳልያ ድል የተመዘገበው በ1993 እኤአ በኃይሌ ገብረስላሴ በተገኘው የወርቅ ሜዳልያ ነበር፡፡ ከዚያም በኋላ በ1995፣ በ1997 እና በ1999 እኤአ ላይ ሶስት የወርቅ ሜዳልያዎችን አከታትሎ የተጎናፀፈውም ራሱ ኃይሌ ገብረስላሴ ነበር፡፡ በ1999 እኤአ ላይ አሰፋ መዝገቡ ተጨማሪ የብር ሜዳልያ ወስዷል፡፡ በ2001 እኤአ ላይ አሰፋ መዝገቡ የብርና ኃይሌ ገብረስላሴ የነሐስ፤ በ2003 እኤአ ቀነኒሳ በቀለ የወርቅ፣ ኃይሌ ገብረስላሴ የብርና ስለሺ ስህን የነሐስ፤ በ2005 እኤአ ላይ ቀነኒሳ በቀለ የወርቅ እና ስለሺ ስህን የብር፤ በ2009 እኤአ ቀነኒሳ የወርቅ እንዲሁም በ2011 እኤአ ላይ ኢብራሂም ጄይላን የወርቅ እና ኢማና መርጋ የነሐስ ሜዳልያዎችን እንዲሁም በ2013 እኤአ ኢማና መርጋ የነሐስ ሜዳልያ በመሰብሰብ የኢትዮጵያን የበላይነት ለረጅም ጊዜ አስጠብቀዋል፡፡ በአጠቃላይ ኢትዮጵያ በዓለም ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪኳ በ10 ሺ ሜትር በወንዶች 9 የወርቅ፣ 4 የብርና 5 የነሐስ ሜዳልያዎችን ሰብስባለች ማለት ነው፡፡ በ2013 እኤአ እና በ2015 እኤአ በሁለት የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች የወርቅ ሜዳልያዎቹን ከኢትዮጵያ የነጠቀው ሞፋራህ ነው፡፡ በሌላ በኩል በ10ሺ ሜትር ሴቶች በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የኢትዮጵያ የመጀመርያው የሜዳልያ ድል የተመዘገበው በ1995 እኤአ ደራርቱ ቱሉ በተጎናፀፈችው የብር ሜዳልያ ነበር፡፡ በ1999 እኤአ ላይ ጌጤ ዋሚ የወርቅ፤ በ2001 እኤአ ደራርቱ ቱሉ የወርቅ፣ ብርሃኔ አደሬ የብር እና ጌጤ ዋሚ የነሐስ፤ በ2003 እኤአ ብርሃኔ አደሬ የወርቅ እና ወርቅነሽ ኪዳኔ የብር፤ በ2005 እኤአ ጥሩነሽ ዲባባ የወርቅ፣ ብርሃኔ አደሬ የብር እና እጅጋየሁ ዲባባ የነሐስ፤ በ2007 እኤአ ጥሩነሽ ዲባባ የወርቅ፤ በ2009እኤአ መሰለች መልካሙ የብርና ዉዴ አያሌው የነሐስ ሜዳልያዎች አግኝተዋል፡፡ በአጠቃላይ ኢትዮጵያ በዓለም ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪኳ በ10 ሺ ሜትር ከ4 አመት በፊት ምንም አይነት የሜዳልያ ውጤት ባይኖራትም በ2013 እኤአ ላይ ጥሩነሽ ዲባባ የወርቅ ሜዳልያ በመውሰድ ክብሩን መልሳለች፡፡ በላይነሕ ኦልጅራ ደግሞ ነሐስ ወስዳ ነበር፡፡ ይሁንና በ2015 እኤአ ኬንያ የወርቅ ሜዳልያ ነጥቃለች፡፡የብር ሜዳልያ የወሰደችው ደግሚ ገለቴ ቡርቃ ነበረች፡፡ በአጠቃላይ ባለፉት 15 የዓለም ሻምፒዮናዎች በሴቶች 10ሺ ሜትር 6 የወርቅ፣ 6 የብርና 4 የነሐስ ሜዳልያዎችን አግኝታለች፡፡
አትሌቲክስ ዊክሊ በሰራው ትንበያ በወንዶች የወርቅ ሜዳልያ ለሞ ፋራህ፤ የብር ሜዳልያው ለጄፍሪ ኪዋሪር እንዲሁም የነሐስ ሜዳልያው ለአባዲ ሃዲስ ሲገመት በሴቶች የወርቅ ሜዳልያው ለጥሩነሽ ዲባባ፤ የብር ሜዳልያው ለአልማዝ አያና እንዲሁም የነሐስ ሜዳልያው ለማትሰለፈው ገለቴ ቡርቃ ተጠብቋል፡፡ትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ በበኩሉ በወንዶች የወርቅ ሜዳልያውን በተመሳሳይ ለሞ ፋራህ ሰጥቶ የብር ሜዳልያውን ለአባዲ ሃዲስ እንዲሁም የነሐስ ሜዳልያውን ለኬንያው ቤዳን ሙቹሪ ሲጠብቅ በሴቶች ደግሞ የወርቅና የብር ሜዳልያውን ጥሩነሽ ዲባባ እና አልማዝ አያና እንደሚያሸንፉ በመገመት የነሐስ ሜዳልያውን ለኬንያዋ አሊስ ንዋንዋ ሰጥቷታል፡፡
በማራቶን
በሴቶች ለኢትዮጵያ ከወርቅ ውጭ፤ የብርና የነሐስ ሜዳሊያ
ለታምራት ቶላ የወርቅ ሜዳሊያ ድል ብዙ ግምት አለ
ባለፉት 15 ሻምፒዮናዎች በሴቶች 1 የወርቅና 1 የነሐስ ሜዳልያዎች በወንዶች 1 የወርቅ 2 የብርና 3 የነሐስ ሜዳልያዎች
በ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ኢትዮጵያን በመወከል የሚሳተፉት አትሌቶች በሴቶች ማሬ ዲባባ (ሻምፒዮን)፤ ብርሃኔ ዲባባ፤ ሹሬ ደምሴና አሰለፈች መርጋ ሲሆኑ በወንዶች ደግሞ ታምራት ቶላ፤ ፀጋዬ መኮንንና የማነ ፀጋዬ ናቸው፡፡
ኢትዮጵያ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪኳ በማራቶን ውድድር በሁለቱም ፆታዎች ሁለት የወርቅ ሜዳልያዎች ብቻ አስመዝግባለች፡፡ በወንዶች ማራቶን ኢትዮጵያ የመጀመርያ የሜዳልያ ድሏን በመጀመርያው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ1983 እኤአ ላይ ያገኘችው ከበደ ባልቻ ባስመዘገበው የብር ሜዳልያ ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ በ2001 እኤአ ላይ ገዛሐኝ አበራ ብቸኛውን የወርቅ ሜዳልያ ድል አስመዘግቧል። በ2009 እኤአ በፀጋዬ ከበደ ፤በ2011 እኤአ በፈይሳ ሌሊሳ ሁለት የነሐስ ሜዳልያዎች፤ በ2013 እኤአ ሌሊሳ ዴሲሳ የብር ሜዳልያ እንዲሁም በ2015 በየማነ ፀጋዬ የነሐስ ሜዳልያ ተገኝቷል ፡፡በሴቶች ማራቶን ኢትዮጵያ በዓለም ሻምፒዮናው የመጀመርያ የሜዳልያ ድል በ2009 እኤአ ላይ አሰለፈች መርጊያ ያስመዘገበችው የነሐስ ሜዳልያ ሲሆን በ2015 እኤአ ላይ ማሬ ዲባባ የወርቅ ሜዳልያ ወስዳለች፡፡
አትሌቲክስ ዊክሊ በሰራው ትንበያ በወንዶች ማራቶን የኬንያ ዋንጂሩ የወርቅ ሜዳልያውን እንደሚወስድ ተገምቶ ታምራት ቶላ የብር ሜዳልያ እንዲሁም ፀጋዬ መኮንን የነሐስ ሜዳልያዎች እንደሚያገኙ የተጠበቀ ሲሆን በሴቶች ኤድና ኪፕላጋት ከኬንያ የወርቅ ሜዳልያውን እንደምታሸንፍ እንዲሁም ብርሃኔ ዲባባ እና ማሬ ዲባባ የብርና የነሐስሜዳልያዎች ተገምቶላቸዋል። በትራክ ኤንድ ፊልድ ኒውስ ትንበያ ደግሞ በሴቶች ምድብ ለባህሬኗ ዩሪስ ጅፕኪሪዊ የወርቅ ሜዳልያ፤ ለኢትዮጵየዊቷ ማሬ ዲባባ የብር ሜዳልያ እንዲሁል ለኬንያዋ ኤድና ኪፕላጋት የነሐስ ሜዳልያ ሲሰጥ በወንዶች ምድብ የወርቅ ሜዳልያው ለታምራት ቶላ፤ የብር ሜዳልያው ለዳንኤል ዋንጂሩ እንዲሁም የነሐስ ሜዳልያው ለፀጋዬ መኮንን ተገምተዋል፡፡
ባህር ዛፍን ከእንጦጦ ተራራ ለማስወገድ፣ 130 ሺ ሀገር በቀል ችግኞች ይተከላሉ
የባህር ዛፍ ተክልን ከእንጦጦ ተራራ ላይ በማስወገድ በሀገር በቀል ዛፎች ለመተካት እስከ 2012 ዓ.ም የሚቆይ እቅድ የተያዘ ሲሆን ዘንድሮም ከ130 ሺህ በላይ የሀገር በቀል ዛፍ ችግኞች ይተካላሉ ተብሏል፡፡
ከዚሁ ፕሮጀክት ጋር በተያያዘ የኢትዮ ቴሌኮም እና የቻይናው የቴሌኮም ኩባንያ ዜድቲኢ ሰራተኞች ከትናንት በስቲያ በተራራው ላይ 200 ያህል ሀገር በቀል ዛፎችን የተከሉ ሲሆን ይህን ተግባርም ላለፉት 4 ዓመታት ሲተገብሩት እንደቆዩ ተገልጿል፡፡ በ4 ዓመታት ከተከሉት መካከል 80 በመቶው መፅደቁም ተገልጿል፡፡
የእንጦጦ ተራራ በአብዛኛው በባህር ዛፍ ተክል ተሸፍኖ እንደነበር ለአዲስ አድማስ ያስረዱት የጉለሌ ክፍለ ከተማ የብዝሃ ህይወት ጥበቃ ባለሙያ አቶ ደጀኔ ሙሉጌታ፤ ከ9 ዓመት በፊት ይፋ በተደረገው ባህር ዛፍን በሀገር በቀል የመተካት እቅድ አብዛኛው የተራራው ክፍል ከባህር ዛፍ ነፃ መደረጉን አስታውቀዋል፡፡ እስከ 2012 ዓ.ም ሙሉ ለሙሉ ተራራውን ከባህር ዛፍ ነፃ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡
የባህር ዛፍ ቅጠር ሲረግፍ በቶሎ ወደ አፈርነት የመቀየር ባህሪ የሌለው በመሆኑ፣ በብዝሃ ህይወት ላይ ጉዳት እንደሚያስከትል በመረጋገጡ ነው እንዲወገድ የተፈለገው ተብሏል፡፡ በተራራው ላይ የተለያዩ ተቋማት ሀገር በቀል ችግኞችን የሚተክሉት ይሄን ዓላማ ለማሳካት ሲሆን ከተቋማቱ ውስጥም ዜድቲኢ ተጠቃሽ መሆኑን አቶ ደጀኔ ተናግረዋል፡፡
በ7 ኪ.ግ ወርቅ የተሰራው ኮምፒውተር፣ በ1 ሚ. ዶላር ለገበያ ቀርቧል
ፕራይም ኮምፒውተር የተባለውና ተቀማጭነቱ በስዊዘርላንድ የሆነው ኩባንያ፤ ከደምበኞቹ የሚቀርቡለትን የተቀናጡ ምርቶች ጥያቄ ለመመለስ በማቀድ ያመረተውን በ18 ካራት ወርቅ የተሰራ አዲስ አይነት ዴስክቶፕ ኮምፒውተር ባሳለፍነው ሳምንት በ1 ሚሊዮን ዶላር፣ በተባበሩት አረብ ኤሜሬትስ ለገበያ ማቅረቡ ተዘግቧል፡፡
ሰባት ኪሎ ግራም በሚመዝን ንጹህ ወርቅ የተሰራው ይህ በአይነቱ ልዩ የሆነ ኮምፒውተር፤አምስት ቴራ ባይት ሃርድ ድራይቭ እንዳለው የዘገበው አይፒቲኔት፣ በተለያዩ ኦፐሬቲንግ ሲስተሞች እንደሚሰራና ከአምስት አመት ዋስትና ጋር ለሽያጭ መቅረቡንም አመልክቷል፡፡
ኩባንያው ፕራይም ጎልድ የሚል ስያሜ የሰጠውንና በተወሰነ መጠን አምርቶ ለገበያ ያቀረበውን ይህን ኮምፒውተር፤ በቀጣይም ባልተለመደ ሁኔታ አሻሽሎ ለማዘመን እቅድ መያዙን የጠቆመው ዘገባው፤ ከእነዚህ ማሻሻያዎች መካከልም የኮምፒውተሩን የማብሪያና ማጥፊያ ቁልፍ፣ እጅግ ውድ ዋጋ ባለው የከበረ ድንጋይ መስራት እንደሚገኝበት አስረድቷል፡፡
በዱባይ ከዚህ ቀደምም ከወርቅ የተሰሩ የአፕልና የብላክቤሪ ምርቶች ለገበያ ቀርበው እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ በጁሜራህ የሚገኘው እና በአገሪቱ እጅግ ዝነኛው እንደሆነ በሚነገርለት ቡርጂ አል አረብ ሆቴል፣ ደምበኞቹ በቆይታቸው የሚጠቀሙበትን ባለ24 ካራት ወርቅ አይፖድ፣ በነጻ እንደሚሰጥም አመልክቷል፡፡
ጆርጅ ክሉኒ፣ 3ሺህ ሶርያውያን ስደተኛ ህጻናትን ሊያስተምር ነው
ታዋቂው የሆሊውድ የፊልም ተዋናይ ጆርጅ ክሉኒ እና ባለቤቱ አማል ክሉኒ በሊባኖስ የሚገኙ 3ሺህ ሶርያውያን ሰደተኛ ህጻናትን ሙሉ ወጪ በመሸፈን ትምህርታቸውን እንዲከታተሉ የሚያስችል የበጎ ምግባር ፕሮጀክት ተግባራዊ ሊያደርጉ ነው ሲል አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
ጆርጅ ክሉኒና ባለቤቱ በጋራ ባቋቋሙት ፋውንዴሽን፣ ከጎግል ኩባንያ ጋር በፈጸሙት የጋራ ስምምነት፣ ሶርያውያኑን ስደተኛ ህጻናት ወደ ትምህርት ቤት ለማስገባት፣ ከ2.25 ሚሊዮን ዶላር በላይ በጀት በመመደብ እቅዳቸውን እውን ለማድረግ እየተንቀሳቀሱ እንደሚገኙ ዘገባው አመልክቷል፡፡ የስደተኞች ትምህርት ፕሮጀክቱ፣ ህጻናቱ በሰባት ትምህርት ቤቶች ጥራቱን የጠበቀ ትምህርት እንዲያገኙ የሚያስችል መሆኑም ተነግሯል፡፡
በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ የአገሪቱ ስደተኛ ህጸናት ከትምህርት ገበታቸው ውጭ መሆናቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ በሊባኖስ ከ1 ሚሊዮን በላይ ሶርያውያን ስደተኞች እንደሚኖሩና ከእነዚህም መካከል 500 ሺህ ያህሉ ህጻናት እንደሆኑም አመልክቷል፡፡
“አርግዞ” የተወለደው ህንዳዊ ጨቅላ፣ አለምን አስደንቋል
በአለማችን 200 ጨቅላዎች፣ የመንታቸውን ጽንስ አርግዘው ተወልደዋል
ነገሩ በሳይንስ ፊክሽን ፊልም አልያም በልቦለድ ካልሆነ በገሃዱ አለም የሚከሰት ነው ብሎ ለማመን ቢያዳግትም፤ የእንግሊዙ ሚረር ግን በእርግጥም የሆነ ነው ይለዋል - ከሰሞኑ በህንድ የተከሰተውን አስደንጋጭ ክስተት፡፡
ዘገባው እንዳለው፤ የመውለጃ ቀኗ ሲቃረብ ከፍተኛ የህመም ስሜት የተሰማትና ለቅድመ ወሊድ ምርመራ ወደ አንድ ሃኪም ቤት ያመራችው የ19 አመቷ ህንዳዊት፤ መንታ ወንድሙን ያረገዘ ጨቅላ በቀዶ ህክምና ተገላግላለች፡፡
ጨቅላው 7 ሴንቲ ሜትር ያለውና ሙሉ የራስ ቅል፣ እጆች እና እግሮች ያሉትን መንታ ወንድሙን አርግዞ መወለዱን የጠቆመው ዘገባው፤ በተደረገለት ቀዶ ህክምና ጽንሱ እንደወጣለትና እሱም ሆነ እናቱ በመልካም ጤንነት ላይ እንደሚገኙ አመልክቷል፡፡
በመላው አለም እስካሁን ድረስ 200 ያህል ተመሳሳይ ክስተቶች መፈጠራቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ ይህ ክስተት ከአምስት ሚሊዮን ወሊዶች በአንዱ ብቻ የመከሰት እድል እንዳለው ሃኪሞች መናገራቸውን አስረድቷል፡፡
500 ቱርካውያን በመፈንቅለ መንግስቱ ተከስሰው ፍ/ ቤት ቀረቡ
ፍርድ ቤቱ፣ በወህኒ ቤት ቅጽር ግቢ ውስጥ የተቋቋመ ነው
ባለፈው አመት በተሞከረውና በከሸፈው የቱርክ መፈንቅለ መንግስት ሴራ፣ እጃቸው አለበት ተብለው የተከሰሱ 500 ያህል ቱርካውያን ባለፈው ማክሰኞ በአገሪቱ እጅግ ግዙፉ እንደሆነ በሚነገርለትና በወህኒ ቤት ውስጥ በተቋቋመው ፍርድ ቤት መቅረባቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ተከሳሾቹ የአገሪቱን ፕሬዚዳንት ጠይብ ኤርዶጋንን ለመግደልና የከሸፈው መፈንቅለ መንግስት ሙከራ አካል የነበረውንና ከአንካራ አቅራቢያ ከሚገኝ የአየር ሃይል ጣቢያ የተነሱ የጦር ጀቶች የአገሪቱን ፓርላማ የደበደቡበትን ጥቃት በማስተባበርና በማቀናጀት ወንጀል ተጠርጥረው መታሰራቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡
ከተከሳሾቹ መካከል የቀድሞው የአገሪቱ የአየር ሃይል ዋና አዛዥ አኪን ኦዝቱክር እንደሚገኙበት የጠቆመው ዘገባው፤ አገር በመክዳትና በሽብርተኝነት የተከሰሱት ግለሰቡ፣ የቀረቡባቸውን ክሶች ተቃውመው መከራከራቸውን ገልጧል፡፡
ከ1 ሺህ በላይ በሚሆኑ ወታደሮች ታጅቦ በጥብቅ ክትትል የተከናወነው ችሎት፣ ወደተከናወነበት ግዙፍ ፍርድ ቤት የቀረቡት ተከሳሾች፣ የተከሰሱባቸው የወንጀል አይነቶች የተለያዩ ቢሆኑም፣ አብዛኞቹ ጥፋተኛ ሆነው ከተገኙ በእድሜ ልክ እስራት ሊቀጡ እንደሚችሉ መነገሩን ዘገባው አመልክቷል፡፡
የተከሳሾቹን ጉዳይ በመመርመር ላይ የሚገኘው ፍርድ ቤቱ፤ በአገሪቱ ግዙፉ እንደሆነና 1 ሺህ 558 ሰዎችን ማስተናገድ የሚችል እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፤ ሲኒካን ውስጥ በሚገኝ ትልቅ ወህኒ ቤት ቅጽር ግቢ ውስጥ የሚገኘው ፍርድ ቤቱ፣ ከመፈንቅለ መንግስት ጋር የተያያዙ ክሶችን ለማስተናገድ ብቻ ታስቦ በቱርክ መንግስት መቋቋሙንም አስረድቷል፡፡
የጠይብ ኤርዶጋን መንግስት ከከሸፈው መፈንቅለ መንግስት ጋር በተያያዘ ለእስር የዳረጋቸው ዜጎቹ ቁጥር ከ50 ሺህ በላይ እንደሚሆን የጠቆመው ዘገባው፤ የጅምላ እስር እና ከስራ የማባረር እርምጃው፣የአውሮፓ ህብረትን ጨምሮ ከበርካታ አካላት ተቃውሞ እንዳጋጠመውም አስታውሷል፡፡
የቀድሞ የማላዊ መሪ፤ በ100 ሚሊዮኖች ዶላር ሙስና ይፈለጋሉ
ማላዊን ለአራት አመታት ያስተዳደሩት የቀድሞ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ጆይስ ባንዳ፣ በመቶ ሚሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር ተመዝብሮበታል በተባለ የሙስና ወንጀል ተጠርጥረው በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ የእስር ትዕዛዝ የወጣባቸው ሲሆን በአሜሪካ የሚገኙት ባንዳ ግን “ወንጀሉን አልፈጸምኩም፣ ወደ አገሬ ተመልሼ ንጽህናዬን አረጋግጣለሁ” ብለዋል፡፡
በእሳቸው የስልጣን ዘመን ተሰራ ከተባለው ሙስና ጋር በተያያዘ ፕሬዚዳንቷን ጨምሮ 70 የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት፣ ነጋዴዎችና የመንግስት ሰራተኞች መከሰሳቸውን የዘገበው አልጀዚራ፤ በ2014 በምርጫ መሸነፋቸውን ተከትሎ ወደ አሜሪካ በማቅናት፣ በአንድ የልማት ተቋም ውስጥ በመስራት ላይ የሚገኙት ጆይስ ባንዳ ግን፤ በስልጣን ዘመኔ እንዲህ ያለ አስጸያፊ ተግባር አልፈጸምኩም ሲሉ ውንጀላውን ማጣጣላቸውን አመልክቷል፡፡
በአሁነ ወቅት ለስራ ጉዳይ ባመሩበት ደቡብ አፍሪካ የሚገኙት ጆይስ ባንዳ፤ የአገሪቱ ፖሊስ የእስር ማዘዣ እንዳወጣባቸው መስማታቸውን ተከትሎ፣ ለሮይተርስ በስልክ በሰጡት መግለጫ፣ በስልጣን ዘመናቸው ሙስናን በትጋት የታገሉና የመጀመሪያውን የጸረ ሙስና ኮሚሽን ያቋቋሙ፣ የመጀመሪያዋ የአገሪቱ መሪ እሳቸው መሆናቸውን በመጥቀስ፣ ወደ አገሬ ተመልሼ የሚመጣውን ሁሉ ለመጋፈጥ ዝግጁ ነኝ፤ ምንም የሚያስጠይቀኝ ነገር ስላልሰራሁ የሚያስፈራኝ ነገር የለም ብለዋል፡፡
የቀድሞዋ የማላዊ ፕሬዚዳንት ጆይስ ባንዳ፣ በደቡብ አፍሪካ እያከናወኑት የሚገኙትን የበጎ ምግባር ተልዕኮ እንዳጠናቀቁ፣ ወደ አገራቸው በመመለስ፣ የፍርድ ቤት ምርመራ ሂደቱን እንደሚከታተሉ ይጠበቃል ተብሏል፡፡
አሜሪካ ስደተኞችን በዲቪ ዕጣ ሳይሆን በችሎታ ለመቀበል አስባለች
አዲሱ አሰራር የህጋዊ ስደተኞችን ቁጥር በግማሽ ይቀንሳል ተብሏል
ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ፣ ባለፈው ረቡዕ በይፋ ድጋፋቸውን የሰጡት አዲሱ የአገሪቱ የህጋዊ ስደተኞች አቀባበል ስርዓት ረቂቅ አዋጅ፣ የሴኔት ድጋፍ አግኝቶ የሚጸድቅ ከሆነ፣ አሜሪካ የዲቪ ሎተሪ ዕድለኞችን ከመላ አለም መሰብሰቧን ትታ፣ በተለያዩ መስፈርቶች የላቀ ውጤትና ችሎታ እንዳላቸው የተረጋገጡ፣ የተመረጡ ስደተኞችን ብቻ በመቀበል የመኖሪያ ፈቃድ መስጠት እንደምትጀምር ተዘግቧል፡፡
ኤንቢሲኒውስ ከትናንት በስቲያ እንደዘገበው፣ ዕድልን ሳይሆን ችሎታን መሰረት ያደረገ የስደተኞች አቀባበልን ተግባራዊ ለማደረግ ታስቦ የተዘጋጀው ረቂቅ አዋጅ፤ በየአመቱ በህጋዊነት ወደ አሜሪካ የሚገቡ የተለያዩ የአለማችን አገራት ስደተኞችን ቁጥር በመጪዎቹ አስር አመታት ጊዜ ውስጥ በግማሽ ሊቀንስ ይችላል ተብሏል፡፡
አዲሱ አዋጅ በሴኔት ጽድቆ እንደ ህግ በስራ ላይ የሚውል ከሆነ፣ ስደተኞችን የምትቀበለውና የመኖሪያ ፍቃድ የምትሰጠው በዕጣ እና በኮታ ወይም በዘመድ አዝማድ መጠራራት ሳይሆን የተለያዩ መስፈርቶች ተጠቅማ እየገመገመች ነው ያለው ዘገባው፤ከእነዚህ መስፈርቶች መካከልም የስደተኞቹ የእንግሊዝኛ ቋንቋ ችሎታ፣ የትምህርት ደረጃና ዕድሜ እንደሚገኙበት አመልክቷል፡፡
ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን በቅጡ መደገፍ የሚያስችላቸውን አካላዊ ብቃት መያዝና፣ በኢኮኖሚው ውስጥ የራሱን አስተዋጽኦ የሚያበረክት ክህሎት ባለቤት መሆንም፣ በህጋዊነት ወደ አሜሪካ የሚገቡ የተለያዩ አገራት ስደተኞች፣ ከሚገመገሙባቸውና የመኖሪያ ፈቃድ ከሚያገኙባቸው ሌሎች መስፈርቶች መካከል ይጠቀሳሉ።
ሲኤንኤን በበኩሉ፤ ስደተኞችን ለመቀበልና የመኖሪያ ፈቃድ ለመስጠት መስፈርት የሚደረጉ መመዘኛዎችን በተመለከተ ከትናንት በስቲያ ባወጣው ዝርዝር ዘገባ፣ ዕድሜው ከ26 እስከ 30 የሆነ፣ የሌሎች አገራት የመጀመሪያ ወይም የዶክትሬት ዲግሪ ያለው እና የእንግሊዝኛ ችሎታው እጅግ ከፍተኛ የሆነ ስደተኛ፣ ወደ አሜሪካ የመግባትና የመኖሪያ ፈቃድ የማግኘት እድሉ እጅግ ከፍተኛ እንደሚሆን ጠቁሟል፡፡
የኦሎምፒክ ሜዳይ ባለቤቶች ወይም የኖቤል ሽልማት ተሸላሚዎች የሆኑ የሌሎች አገራት ስደተኞችም፣ ከሌሎች በተለየ ወደ አሜሪካ የመግባትና የመኖሪያ ፈቃድ የማግኘት እድላቸው ከፍ ያለ እንደሚሆንም ዘገባው ገልጧል፡፡
በየአመቱ የመኖሪያ ፈቃድ የሚሰጣቸውን ስደተኞች ቁጥር 50 ሺህ ለማድረስ ያለመውና ባለፈው የካቲት ወር ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ ተሰምቶ ሲያወዛግብ የነበረው ረቂቅ አዋጁ፤ፕሬዚዳንት ትራምፕ ባለፈው ረቡዕ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ በእጅጉ እንደሚደግፉትና ለተግባራዊነቱ እንደሚሰሩ በይፋ ማስታወቃቸውን ተከትሎ፣ እንደገና የውዝግብና የውይይት አጀንዳ መሆን መጀመሩንም ዘገባው ጠቁሟል፡፡
ናሽናል ኢሚግሬሽን ፎረም የተባለው የአገሪቱ ቡድን በበኩሉ፤ በመጪዎቹ 3 አመታት ጊዜ ውስጥ የ7.5 ሚሊዮን ሰራተኞች ዕጥረት እንደሚገጥማት በተነገረላት አሜሪካ፤ከፍተኛ የሰራተኛ የሰው ሃይል ምንጭ የሆነውን የህጋዊ ስደተኞች ፍሰት የሚገታውን ይህን አዋጅ ማጽደቅ፣የአገሪቱን ኢኮኖሚ ክፉኛ የሚጎዳ አደገኛ እርምጃ ነው ማለቱን ኒውዮርክ ታይምስ ዘግቧል። ረቂቅ አዋጁ ከፖለቲካና ኢኮኖሚ ተንታኞች ከፍተኛ ትችት እየተሰነዘረበት ነው ያለው ዘገባው፤ ረቂቅ አዋጁ እንደታሰበው በምክር ቤት ጸድቆ ስራ ላይ የመዋል ዕድሉ እጅግ ጠባብ ነው እየተባለ እንደሚገኝም አመልክቷል፡፡
“የልብ ሽበት እና ሌሎችም” መፅሀፍ ለንባብ በቃ
ከፈረንሳይኛና ከሌሎች ቋንቋዎች ወደ አማርኛ የተመለሱ ከ20 በላይ አጫጭር ልቦለድ ታሪኮችን ያካተተው “የልብ ሽበትና ሌሎችም” የተሰኘ መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ በተርጓሚና ደራሲ ሀይላይ ገብረ እግዚአብሔር የተተረጎመው ይሄው መፅሐፍ ያካተታቸው ታሪኮች ከዚህ ቀደም በአዲስ አድማስ ጋዜጣና በተለያዩ መፅሄቶች ላይ የወጡና አዳዲስ ታሪኮችም ተጨምረውበት ለንባብ የበቃ መሆኑን ተርጓሚው ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡ በ2015 ገፆች የተመጠነው መፅሐፉ፤ በ68 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡