Administrator

Administrator

በሁለት ዓመት 250 ህሙማንን ለማሳከም አቅዷል

 “ሞት በኩላሊት ይብቃ” የተሰኘ በጐ አድራጎት ማህበር፣ ገንዘብ በማሰባሰብ በኩላሊት ህመም የሚሰቃዩና ረዳት የሌላቸውን ህሙማን ለመርዳት ማቀዱን አስታወቀ፡፡
በኩላሊት ህመምተኞች፣ በባለሙያዎችና በበጐ ፈቃደኛ መስራች አባላት የተቋቋመው ማህበሩ፤ሥራ የጀመረ ሲሆን በመጀመሪያዎቹ ሁለት ዓመታት 250 ያህል ህመምተኞችን ለማሳከም እንዳቀደ ተጠቁሟል፡፡
በነገው ዕለት መነሻውን ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል፣መድረሻውን ኢትዮ-ኩባ የወዳጅነት ሀውልት ያደረገ፣ በኩላሊት ህመም መንስኤና መፍትሔ ዙሪያ የግንዛቤ ማስጨበጫ   የእግር ጉዞ እንደሚደረግም ማህበሩ ሰሞኑን በካፒታል ሆቴል በሰጠው መግለጫ አስታውቋል፡፡
የማህበሩ መስራች አቶ ኢዮብ ተወልደ መድህን እንደገለፁት፤የፊታችን አርብ ለኩላሊት ህሙማን መርጃ የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ይካሄዳል፡፡

Saturday, 07 November 2015 09:55

የዘላለም ጥግ

(ስለ ችሮታ)
• የድሆችን ህይወት ካላሻሻልክ ችሮታ አደረግህ
አይባልም፡፡
ማኖጅ ብሃርጋቫ
• ዓለም የምትፈልገው ችሮታ ሳይሆን ፍትህ
ነው።
ሜሪ ዎልስቶንክራፍት
• ፍትህ የበለጠ የሰፈነበት ህብረተሰብ ብዙ ችሮታ
አይፈልግም፡፡
ራልፍ ናዴር
• ችሮታ፤ የእምነትና የተስፋ ውጪያዊ መገለጫ
ሊሆን ይችላል፡፡
ጆሴፍ ቢ ዊርዝሊን
• እውነተኛ ችሮታ፤ ምንም ማካካሺያ ሳያስቡ
ሌሎችን የመጥቀም ጥልቅ ፍላጐት ነው፡፡
ኢማኑኤል ስዊዲንቦርግ
• የሰዎች ባህርይ (ሰብዕና) በችሮታ የተነሳ ሊበላሽ
ይችላል፡፡
ቴዎዶር ሄርዚ
• ችሮታ እጅግ በርካታ ሃጢያቶችን ይፈጥራል፡፡
ኦስካር ዋይልድ
• ችሮታ ከቤት መጀመር አለበት፤ እዚያው
መቅረት ግን የለበትም፡፡
ፊሊፕስ ብሩክስ
• ችሮታ፤ ከልብ በፈቃደኝነት የሚሰጥ ነገር ነው፡፡
ሩሽ ሊምባው
• ስሞሽ (Kiss) ችሮታ አይደለም፡፡ ንግድንና
ችሮታን ፈጽሞ አትደባልቁ፡፡
ጆኒ ሳይሞንስ
• ግሩም ሙዚቃ፤ ታላቅ አገልግሎትና ችሮታ
የሚሆንባቸው ጊዜያት አሉ፡፡
ማይክል ሌዩኒግ
• በችሮታ ሥራ ከተሳተፍኩ በቅጡ የሥራው
አካል ለመሆን እፈልጋለሁ፡፡ ስሜ በበራሪ
ወረቀታችሁ ላይ እንዲሰፍር ብቻ አልሻም፡፡
ናንሲ ሎፔዝ
• በአሁኑ ወቅት በዓመት 30 ገደማ የችሮታ
ጨረታዎችን እያከናወንኩ ነው፡፡
ጄፍሬይ አርቼር
• ፕሬስን ለችሮታ ሥራዬ ካልሆነ በቀር ለሌላ
ለምንም ነገር ፈጽሞ ተጠቅሜበት አላውቅም፡፡
ሒዘር ሚልስ

የኢህአዴግ መልዕክቶች፡
• አሁንም ኃያል ነኝ። ከውሳኔዬ ውልፍት የለም (ሚኒስትሮችም ጭምር)።
• መሪውን የጨበጡት፣ ጠ/ሚ ኃይለማሪያም ደሳለኝ እንደሆኑ ተመልከቱ።
• በሺ የሚቆጠሩ የበታች ባለስልጣናት፣ በዘመቻ ተጠራርገው ይባረራሉ።

   በኢቢሲ የተመለከትነው የከፍተኛ ባለስልጣናት ስብሰባ፣ ትልቅ የመነጋገሪያ ርዕሰ ጉዳይ ሆኖ ሰንብቷል። ካሁን በፊት፣ ብዙ ስብሰባዎችን አይተናል፤ ብዙ ንግግሮችን ሰምተናል። የአሁኑ፣ እንዴት የብዙዎችን ትኩረት ሊስብ ቻለ? ኢህአዴግ፣ ‘የህዝብ የልብ ትርታ’ን ማዳመጥ ስለጀመረ ይሆን?
‘የሕዝብ የልብ ትርታ’ን ማዳመጥ ብቻውን፣ አሪፍ ነው ማለቴ አይደለም። የሕዝብን ስሜት ተከትሎ፣ የታክሲ ስምሪት ቁጥጥር መጀመሩ ወይም የሸቀጦች ዋጋ ተመን ለማወጅ መሞከሩ፤ ምን ትርፍ አስገኘ? የትራንስፖርት እጥረትን ከማባባስና ገበያን ከማቃወስ ያለፈ ውጤት አላመጣም። ዜጎችን ማዳመጥ ብቻ ሳይሆን፣ ሁነኛ መፍትሄ የማበጀት ብልህነትም ያስፈልጋል።
ለነገሩ፣ ኢህአዴግ፣ ብዙ ጊዜ፣ ዜጎችን አያዳምጥም። በሁለት በሦስት ዓመት ጉባኤ ሲያካሂድ፤ ወይም በየመንፈቁ፣ የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ሲሰበሰብ፣ በርካታ እቅዶችን ያወጣል፤ ውሳኔዎችን ያስተላልፋል። በቃ፤ ከዚያ በኋላ፣ ከላይ እስከ ታች፣ ውልፍት ማለት የለም። ከዚያ ውጭ የሆኑ ጉዳዮች... (ችግሮችና አቤቱታዎች) ብዙም ሰሚ አያገኙም። በሰሞኑ ስብሰባ ላይ፣ ‘ዜጎች፣ ሰሚ አጥተዋል’ እያሉ የኢህአዴግ መሪዎች ሲናገሩ አልነበር!
በእርግጥ፣ አንዳንዶቹ ችግሮች፣ ያን ያህልም ቁምነገር የሌላቸው ጊዜያዊ ጉዳዮች ሊሆኑ ይችላሉ። በእውነተኛ መረጃ ላይ ያልተመሰረቱ አቤቱታዎችና የተጋነኑ ጩኸቶችም ይኖራሉ። ነገር ግን፣ ለተጨባጭ ችግሮችና አቤቱታዎችም ቢሆኑ፣ ኢህአዴግ ፊት አይሰጥ።
ከራሱ እቅድና ውሳኔ ውጭ የሆኑ ጉዳዮች ሲመጡ፣ “እውነት ናቸው ወይስ አይደሉም? ቁምነገር ይዘዋል ወይስ አልያዙም?” ብሎ ለመመርመርና ለመመዘን፣ ፈቃደኛ አይሆንም። እንዲያውም፣ ‘አፍራሽ’ እና ‘አደናቃፊ’ ብሎ ሊፈርጃቸው ይችላል። ጭራሽ፣ የዜጎችን አቤቱታ መስማት (‘የህዝብን የልብ ትርታ ማዳመጥ’)... እንደ ድክመትና እንደ ጥፋት የሚቆጠርበት ጊዜ አለ። “አድርባይነት” በማለት ይሰይመዋል።
“አብዮታዊ ፓርቲ ነኝ” የሚለው ኢህአዴግ፤ ለውጥ ለማምጣት እታገላለሁ እንጂ፤... ከህዝብ የስሜት ነፋስ ጋር አብሮ ለመንጎድ፤ መስሎ ተመሳስሎ ለማደር፣ በዚህም ተወዳጅነትንና ዝናን ለማትረፍ የምሯሯጥ፣ “አድርባይ”ፓርቲ አይደለሁም” ይላል።    
እና፣ ‘አድርባይ’ ላለመባል፣ ምን ማድረግ ይሻላል? ዜጎችን አለማዳመጥ? ችግሮችን ላለማየት አይንን መጨፈን? አቤቱታዎችን ላለመስማት ጆሮን መድፈን? “ዜጎችን የሚያዳምጥ የመንግስት አካልና ባለስልጣን ጠፍቷል” ተብሎ የለ? (በባለስልጣናቱ ስብሰባ ላይ ማለቴ ነው)።
ተመልካችና ሰሚ ሲጠፋ፤ ተጨባጭ ችግሮች ያለ መፍትሄ እየተባባሱ፣ እውነተኛ አቤቱታዎች ወደ እሮሮ ይቀየራሉ። ያኔ፣ ችግሮች ሲባባሱ ነው፣ እሮሮዎች የሚደመጡት።
ነገር ግን፣ ኢህአዴግ፤ የህዝብን ጩኸት በማዳመጥ ብቻ አይመለስም። ጩኸቱን ይወርሰዋል። “ፍትህ ጠፋ” እያለ ዋና የእሮሮ ባለቤት ይሆናል። “ሙስና አገርን ገደለ”፣ “አገር መቀመቅ ወረደች”፣ “ኢህአዴግ በሰበሰ”... እነዚህ ሁሉ፣ ካሁን በፊት ከኢህአዴግ የሰማናቸው ምሬቶች ናቸው። ሰሞኑን እንደሰማነውም፣ “መሪዎች የሚሰሩትን አያውቁም”፤ “አላግባብ የጥቅም መረብ ዘርግተው አገሪቱን ተብትበዋታል”፤ “ከማውራት ውጭ ለውጥ አላመጣንም”፤ “ለግብር ይውጣ ህዝቡን እየጠራን፣ በአሰልቺ ስብሰባ እንዲርቀን አድርገናል”፤ “ህዝቡ ሰሚ አጥቶ በኢህአዴግ ተስፋ ቆርጧል”...
እንዲህ የኢህአዴግ መሪዎች፣ ኢህአዴግ ላይ የትችትና የወቀሳ ናዳ ሲያወርዱ፤ አገሬው ምን ይበል? የሚጨመር ትችት ከየት ይመጣል?
“አላግባብ የመሞዳሞድና የሙስና መረቦች በዘመቻ መበጣጠስ አለብን”፣ “ጠራርገን በማባረር፣ ህዝቡ ተስፋ እንዲያገኝና በኢህአዴግ ላይ እምነት እንዲያድርበት ዘመቻ ማካሄድ ይኖርብናል”፤...  
ኢህአዴግ ጉባኤ ላይ ወይም በስራ አስፈፃሚ ስብሰባ ላይ፣ እንዲህ አይነት ውሳኔ ከተላለፈና የዘመቻ እቅድ ከወጣ በኋላስ? ከዚያ በኋላማ... ወደ ቀድሞው “ሴቲንግ” ይመለሳል። በቃ፣ ሌላ ጉዳይ መስማት አይፈልግም።
“ኧረ፣ የኢህአዴግ መሪዎች በኢህአዴግ ላይ ያዘነቡት ውርጅብኝ ተጋኗል” ብሎ አስተያየት የሚሰጥ ሰው ቢመጣ እንኳ፣ ሰሚ አያገኝም። ምናልባትም፣ ‘አፍራሽ’፣ ‘ፅንፈኛ’፣ ‘አደናቃፊ’ ተብሎ ሊፈረጅ ይችላል። ጠራርጎ የማባረር ዘመቻው ላይ፣ ... እንደማንኛውም ፈጣን ዘመቻ፣ ንፁሁን ከነውረኛው፣ ቀናውን ከአጥፊው ጋር መጠረጉ የማይቀር ነው። ነገር ግን፣ ዘመቻውን በመደገፍ የሚያጨበጭብ እንጂ፣ ቅሬታ የሚያቀርብ ሰው ቦታ አይኖረውም።
በእርግጥ፣ ነውረኛውና አጥፊው፣ እሪታውን መልቀቁ አይቀርም። ግን፣ ንፁሁና ቀናው ሰራተኛም፣ አላግባብ ተባረርኩ ብሎ አቤቱታ ቢያቀርብ፣ ማንም አይሰማውም። የክልል የቢሮ ሃላፊ ወይም የወረዳ አስተዳዳሪ ይቅርና፣ ሚኒስትሮችና አንጋፋ የኢህአዴግ መሪዎችም፣ ዘመቻውን ለመተቸት ቢሞክሩ፣ ለውጥ አያመጡም። እንዲያውም፣ መረር ያለ ምላሽ ይመጣባቸዋል። ይህም ብቻ አይደለም። በቪዲዮ ተቀርፆ በቲቪ ይሰራጫል፤... ሰሞኑን በኢቲቪ እንዳየነው አይነት ማለት ነው። አለምክንያት አይመስለኝም። መልእክት ለማስተላለፍ ነው። ዘመቻው ላይ ቅሬታ ለመሰንዘር ለሚሞክሩ ሰዎች፣ ማስጠንቀቂ ነው።
ከስልጣን የሚባረር የቢሮ ሃላፊ ወይም የወረዳ አስተዳዳሪ ይቅርና፣ ሚኒስትሮችና አንጋፋ መሪዎችንም ቢሆን እንደማልምር ተመልከቱ። በቃ፤ ውሳኔ ከተላለፈና እቅድ ከወጣ በኋላ፤ ወዲህ ወዲያ ውልፍት ማለት የለም - ከታች እስከ ላይ፣ አንድ አይነት ቃል ነው የሚነገረው።  እናም፣ አንደኛው ሚኒስትር ወይም ሌላኛው አንጋፋ መሪ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከባድ ተግሳፅ ሲሰነዝሩ በቲቪ ስንመለከት፤ ኢህአዴግ ለበታች ባለስልጣናት፣ ለካድሬዎችና ለአባላት እንዲሁም ለሌላውም ዜጋ፣ ማስጠንቀቂያ እያስተላለፈ እንደሆነ መረዳት ያስፈልጋል።
ተግሳፅ የደረሰባቸው ሚኒስትሮችና መሪዎች፣ ተግሳፁን እንዴት ያስተናግዱታል? በአብዛኛው፣ በፀጋ ከመቀበል እንደ መስዋዕትነት ከመቁጠር ውጭ አማራጭ ያላቸው አይመስለኝም - “ለፓርቲዬ የምከፍለው መስዋዕትነት ነው” ሊሉም ይችላሉ። እንዲያውም፣ በኢህአዴግ መሪዎች ዘንድ በጣም የተለመደ አባባል አለ። “ፓርቲው... በሚኒስትርነት አልያም በጥበቃ ሰራተኝነት እንድሰራ ቢመድበኝ፤ ያለ ማንገራገር እሰራለሁ” ... በማለት በተደጋጋሚ ሲናገሩ ሰምተን የለ? ለፓርቲያቸው የሚያበረክቱት መስዋዕትነት ነው።
ለነገሩ፣ አይገርምም። ቢያንስ በሃሳብ ደረጃ፣ መስዋዕትነትን እንደ ቅዱስ ምግባር የማይቆጥር ኢትዮጵያዊ በጣም ጥቂት ነው። መስዋዕትነት፣ የአምልኮ ያህል በሚከበርበት አገርና ባህል ውስጥ ነው ያለነው። ለማንኛውም፣... ለአዲሱ ዘመቻ እስከጠቀመና፣ የፓርቲውን መልእክት ለማስተላለፍ እስካገለገለ ድረስ፣... በቲቪ የሚተላለፍ ስብሰባ ላይ፣ አንዱ ከፍተኛ ባለስልጣንና መሪ፣ ከባድ ተግሳፅ ቢሰነዘርበት... የመስዋዕት ተረኛ ሆኗል ማለት ነው። ያኔ፣ ከላይ እስከ ታች፣ የፓርቲ መሪና ሚኒስትር፣ የክልል ባለስልጣንና ካድሬ፣ የቀበሌ አስተዳዳሪና ተራ አባል ሁሉ፣ “መስመሩን ይይዛል፤ ሰልፉን ያሳምራል”። ይሄም አይገርምም።
“ሰልፍን ማሳመር”፣ በአገራችን ጎልቶ የሚታይ ጥንታዊ ባህል ነው። ቅንጣት የሚያፈነግጥ ሃሳብ፣ እንዳይኖር እንፈልጋለን። ለምሳሌ፣ በሃይማኖት ዙሪያ፣ “ከተለመደው ነባር ሃሳብ” ውጭ፣ ምንም አዲስ ነገር ከመጣ፣ ብዙዎችን ያስቆጣል። አንዱ ሌላውን ለማጥፋት፣ ዘመቻ ይከፈታል።
በፖለቲካም ተመሳሳይ ነው። “እኔ የምደግፈው ፓርቲ ላይ፣ አንዳች ትችት ትንፍሽ እንዳትል። አንተ የምትደግፈው ፓርቲ ላይ፣ የእውነትም ይሁን የሃሰት ውንጀላ ሳዥጎደጉድበትም፣ አፍህን ያዝ”... የሚል ስሜት የገነነበት ባህል አለብን። ሁሉንም፣ በመስመር ማሰለፍ ያምረናል። ሌላውም እንዲሁ፣ በራሱ መስመር ውስጥ ካላስገባሁ ሞቼ እገኛለሁ ይላል። እናም፣ ከመጠፋፋት ውጭ ሌላ መፍትሄ አይታየንም።
በእርግጥም፣ ለጭፍን እምነት ሳይሆን ለሳይንስ፣ ለጭፍን ስሜት ሳይሆን ለእውነታ፣ ለጭፍን ጉልበትና ለቡድን ሳይሆን፣ ለማስረጃና ለአእምሮ ዋጋ የሚሰጥ ስልጡን ባህል ብናዳብር ኖሮ፤ ችግር አይኖርም ነበር። ነፃነትንና ለእውነታ በፅናት የመቆም ስነምግባርን፤ መከራከርንና መከባበርን ያዋሃደ መፍትሄ እናገኝ ነበር። ያንን ስልጡን ባህል እስካላዳበርን ድረስ ግን፤ ብዙም አማራጭ አይኖረንም።
በየፊናው አዛዥ ናዛዥ ለመሆን የሚፈልጉ ሰዎችና ቡድኖች፣ ገናና ለመሆን ሲሻኮቱና ሲጋጩ፣ አገሬው በስርዓት አልበኝነት ይታመሳል። ወይም ደግሞ፣ ከፋም ለማም፣ አንዱ ሰው፣ አንዱ ቡድን፣ አንዱ ውሳኔና እቅድ፣ ሌሎችን ሁሉ አንበርክኮ ገናና ይሆንና፣ ከላይ እስከ ታች፣ ከጫፍ እስከ ጫፍ፣ “ስርዓት” ይሰፍናል። “የፓርቲ መመሪያ ከላይ ወደ ታች የማውረድ አሰራር”፣ “የማዕከላዊነት አሰራር” ብለው ይጠሩታል። ከማዕከል፣ አንዳች ውሳኔና እቅድ ሲወጣ፣ በዙሪያው የተዘረጋ ቅርንጫፍ በሙሉ፣ አቅጣጫውን ያስተካክላል።
ታዲያ፣ “መስመር የሚያስይዝ የማዕከላዊነት አሰራር”፣ ለውሳኔና ለእቅድ ብቻ አይደለም። መሪነትንም ይጨምራል። ጭፍን እምነትና ስሜት በበዛበት የኋላቀርነት ባህል ውስጥ፣... ያው፣... በርካታ ፊታውራሪዎችና አበጋዞች፣ ቡድኖችና ድርጅቶች፣ በየፊናቸው ገናና ለመሆን ሲሻኮቱና ሲጋጩ፣ አገር ይቀወጣል። ጥንታዊው የጎሳ አስተዳደር፣ ከእንዲህ አይነት መቋጫ የሌለው የግጭት ስርዓት አልበኝነት ያልተላቀቀ አስተዳደር ነው።
ኢትዮጵያ፣ ለሺ ዓመታት፣ በየጣልቃው ወደ ስርዓት አልበኝነት ብትንሸራተትም፣ በተወሰነ ደረጃ አገራዊ ስርዓት እስከመመስረት የደረሰ፣ ትልቅ የስልጣኔ ታሪክ የተሰራባት አገርም ናት። እናም፣ አብዛኛው ሰው፣ በርካታ አበጋዞችና ቡድኖች የሚሻኮቱበት ስርዓት አልበኝነትን አይፈልግም። እና ምን ይሻላል?
ሁለት አማራጮች አሉ። በአንድ በኩል፣ የትኛውም አበጋዝና ቡድን፣ አዛዥ ናዛዥ የማይሆንበት፣ ገናና እንዲሆንም የማይፈቀድበት፣ የእያንዳንዱ ሰው የሃሳብ ነፃነትና የምርት ባለቤትነት መብት የሚከበርበት፤ እያንዳንዱ የመንግስት ባለስልጣን በሕግ የተገደበ ሃላፊነትን ብቻ የሚያገኝበት ስልጡን ስርዓት መፍጠር ይቻላል - የሕግ የበላይነት የሰፈነበት የነፃነት ስርዓት ልንለው እንችላለን።
ለምሳሌ፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ስልጣን፣ እንዲሁም የሌሎች ሚኒስትሮች ሃላፊነት፣ ምን እንደሆነ ለማወቅ፣ የግድ የሚስጥር ተካፋይ የውስጥ አዋቂ መሆን አያስፈልግም። የሕገመንግስት አንቀፆችን ማንበብና መገንዘብ በቂ ይሆናል። ከዚያ ውጭ ውልፍት ማለት፣ አይቻልማ - የህግ የበላይነት በሰፈነበት ስልጡን ስርዓት። ይሄ አንዱ አማራጭ ነው። ነገር ግን፣ ለአእምሮና ለሳይንስ ክብር የሚሰጥ ስልጡን ባህል ካልዳበረ፣ የሕግ የበላይነት ስርዓትን መፍጠር አይቻልም።
ሌላኛው አማራጭ? ብዙ አበጋዞችና ቡድኖች፣ በየፊናቸው ገናና ለመሆን እየተጋጩ አገር በስርዓት አልበኝነት ጨለማ ከምትታመስ፣... አንዱ መሪ፣ ገናና ሆኖ ቢወጣ ይሻላል። ግን፣ ወደ ግጭት የሚያመራ ሽኩቻ እንደጠፋና አንድ መሪ ገናና ሆኖ እንደወጣ፣ እንዴት ማረጋገጥ ይቻላል? ውስጥ ለውስጥ እየተሻኮቱ ሊሆን ይችላል። “ሕገመንግስት ላይኮ፣ የእያንዳንዳቸው የሥልጣን ልክ በዝርዝር ተፅፏል” ብንል ዋጋ የለውም። በሕገመንግስት አንቀፆች ላይ መተማመን የሚቻለው፣ ስልጡን ባህልና የሕግ የበላይነት ሲስፋፋ ነው።
ካልተስፋፋስ? ያው፣ ስርዓት አልበኝነትን በመጥላት ብቻ፤... አንድ መሪ፣ ከሌሎች ሁሉ ጎልቶ እንዲወጣ እንጠብቃለን። አለበለዚያ፣ ነገሮች ሁሉ ‘አይጥሙንም’። እናም፣ ገናናነትን የሚጠቁም አጋጣሚንና ንግግርን የማየት ፍላጎት ያድርብናል። አለበለዚያ፣ በመሪነት የተቀመጠውን ሰው፣ እንደ ደካማ እንቆጥረዋለን። ለዚህም ይመስለኛል፤ ባለፉት አመታት ጠ/ሚ ኃይለማሪያም ደሳለኝ፣ አብዛኛውን ጊዜ፣ ከአነጋገራቸው ቁጥብ እና ሰከን ያሉ በመሆናቸው፣ በብዙዎች ዘንድ እንደ ደካማ የተቆጠሩት። የሚናገሩትን ሃሳብ በማገናዘብና በመመዘን፣ ጥንካሬንና ድክመትን ከመለካት ይልቅ፣ ቁጥብነትን እንደድክመት የሚቆጥር ባህል ውስጥ መሆናችን ያሳዝናል።
ከሦስት የስልጣን ዓመታት በኋላ፣ ሰሞኑን፣ ቆጣ እና ረገጥ ያለ ንግግራቸውን በቲቪ ስንመለከትስ? ወዲያውኑ ነው፣  የጠንካራ መሪ ዝና ያገኙት። በቲቪ የተሰራጨው ስብሰባ፣ የጠ/ሚ ኃይለማሪያምን ስልጣን በጉልህ የሚያሳይ መልእክት የያዘ ነው የምለውም በዚህ ምክንያት ነው።    

      አዲስ አድማስ ጋዜጣ ባለፈው ቅዳሜ ጥቅምት 20 ባወጣው እትሙ፤ ‹‹ህልምና ኑሮ ሲምታታ እንዲህ ነው - ከእውነት ዓለም ጋር የተላተመው የጤና ኢንሹራንስ!›› በሚል ርዕስ ዮሐንስ ሰ. የተባሉ ጸሃፊ አንድ ጽሁፍ ለንባብ አቅርበው ነበር፡፡ ጸሃፊው የጤና ኢንሹራንስ ጉዳይ አብከንክኗቸው፣ ተግባራዊነቱ ላይ ጽልመትና ጥላቻ የጋረደበት ትችታቸውን ቢሰነዝሩም ጉዳዩን እንደ ጉዳይ ማንሳታቸው በራሱ ሊያስመሰግናቸው ይገባልና በቅድምያ ላነሱት ርዕሰ ጉዳይ ልባዊ ምስጋናችንን በኤጀንሲው ስም ማቅረብ እንፈልጋለን፡፡
እኛ እንደምንገምተው፣ አዲስ አድማስ ጋዜጣ ነገሮችን በመረጃ አስደግፎ ለአንባቢ እውቀት የሚያስጨብጥ ጋዜጣ ነው፡፡ ሆኖም ዮሐንስ ሰ. (መረጃ ለማግኘት መሯሯጡ ዳገት ሆኖባቸው ነው መሰል) በወፍ በረር ስለ ጤና ኢንሹራንስ በሰሙት ወሬ ተደግፈው የጻፉት ጽሁፍ ትክክል ባለመሆኑ ይህን ጽሁፍ ለማዘጋጀት ተገደናል፡፡
በበቂ መረጃ ላይ ያልተመሰረተ ጽሁፍ፣ ጸሃፊውንም ሆነ አንባቢውን ማምታታቱ አይቀርም። ዮሐንስ ሰ. ስለ ጤና ኢንሹራንስ ለመጻፍ ሲነሱ በቂ መረጃ ይዘው ስላልነበረ የጽሁፋቸውን ርዕስ ‹‹ህልምና ኑሮ ሲምታታ እንዲህ ነው!!›› ብለው ለመጀመር ተገደዋል፡፡ ሃቁን  ለመናገር ከእውነት ዓለም ጋር የተላተመው የጤና ኢንሹራንስ ሳይሆን መረጃን በበቂ ሁኔታ ባለማሰባሰብ ከገሃዱ ጋር የተላተሙት ራሳቸው ለመሆናቸው ታሪክ ቀመስ ልብ ወለድ የሚመስል የፈጠራ ስራቸው ፍንትው አድርጎ ያሳያል፡፡
ጸሃፊው በመግቢያቸው ‹‹የቤተሰብዎን ጤንነት (ጥርስ ከማስተከል በቀር…) ሁሉም አይነት ምርመራ፣ህክምናና መድሃኒት ያገኛሉ - ነጻ ወይም ደግሞ 25 ብር ባልበለጠ የወር መዋጮ፡፡ ይህን ይመስላል መንግስት የጀመረው አስደናቂ የጤና ኢንሹራንስ›› በሚል የጤና ኢንሹራንሱ ምናባዊ የህልም ዓለም እንደሆነ ስላቅ አዘል አስተያየታቸውን ሰንዝረዋል፡፡
ጸሃፊው በምናባዊ ዓለም ውስጥ ሆነው በመጻፋቸው መንግስት ሃገሪቱ ውስጥ ለመተግበር ያቀደው የጤና መድህን ሁለት አይነት መሆኑን እንኳን ከሚያውቁ ሰዎች ለመጠየቅ ዕድል አልነበራቸውም። ዮሐንስ ሰ. ያልተገነዘቡት በማህበራዊ የጤና መድህን ስርዓትና በማህበረሰብ አቀፍ የጤና መድህን መካከል ያለውን ልዩነት ነው። የማህበራዊ የጤና መድህን ማለት በመደበኛው ክፍለ-ኢኮኖሚ ለተሰማሩ (ደመወዝ ተከፋይ የሆኑ ሠራተኞች) 3%  ከደሞዛቸው  መዋጮ በማድረግ፣አሰሪያቸውም ተመሳሳይ ፐርሰንት እያዋጣላቸው ዜጎች ያልተጠበቀ ድንገተኛ ህመም ሲገጥማቸው ከኪስ የሚወጣ የገንዘብ ክፍያ ሳይኖር የህክምና አገልግሎት የሚያገኙበት የጤና መድህን ሥርዓት ነው፡፡ ይኸኛውን የመድህን ስርዓት መንግስት ገና በሃገሪቱ ተግባራዊ አላደረገውም።  በመጪው ጥር ወር ለመጀመር ቅድመ ዝግጅቱ በመጠናቀቅ ላይ ነው፡፡ እዚህ ጋ ጸሃፊው ባልተጀመረ ነገር አስተያየት መስጠታቸው ትዝብት ላይ ሳይጥላቸው አልቀረም።
ሁለተኛው የጤና መድህን ስርዓት ደግሞ የማህበረሰብ አቀፍ የጤና መድህን የሚባለውና መደበኛ ከሆነው ክፍለ-ኢኮኖሚ ውጭ በተለይም በግብርና ላይ ለተሰማሩ ዜጎች የሚያገለግልና ቀድሞ በሚደረግ አነስተኛ መዋጮ ዓመቱን ሙሉ ያልተጠበቀ ህመም ሲከሰት የህክምና አገልግሎት የሚያገኙበት ነው፡፡ ይሄም ቢሆን በአባላት መዋጮ ብቻ የሚደረግ ሳይሆን እስከ 25 % በሚደርስ የመንግስት ድጎማ የተደገፈ ነው፡፡ ይህ የመድህን ስርዓትም ቢሆን ገና በሙከራ ደረጃ ላይ ያለና በሚታዩ ድክመቶች ዕርማት እየተወሰደ የማስፋፍያ ስራ የሚሰራበት ነው፡፡
እዚህ ጋ ጸሃፊውን ዮሃንስ ሰ.ን ለመጠየቅ የምንፈልገው ለመተቸት የፈለጉት ገና ያልተጀመረውን የማህበራዊ የጤና መድህንን ነው ወይንስ በሙከራ ትግበራ ላይ የሚገኘውን የማህበረሰብ አቀፍ የጤና መድህን ስርዓትን?...
በጽልመት ከታጀበው ጽሁፋቸው ለመረዳት እንደሞከርነው ጸሃፊው ‹‹የህልም ዓለም!›› በማለት ለመንቀፍ የሞከሩት የመድህን ስርዓት፤ ገና በሙከራ ትግበራ ላይ የሚገኘውን የማህበረሰብ አቀፍ የጤና መድህን ስርዓትን ይመስለናል፡፡ በእርግጥ የጸሃፊው ትኩረት በዚህ መድህን ስርዓት ላይ ከሆነ ሥለ መድህን ሥርዓቱ ምንም አይነት ግንዛቤ የላቸውምና ስለ ሂደቱ ጥቂት ማውጋቱ ለአንባቢ ትክክለኛውን መረጃ ከማቀበል ባሻገር ጸሃፊው ለሌላ ጊዜ ተመሳሳይ ስህተት እንዳይደግሙ አጋዥ እርምጃ ይሆናል፡፡
የማህበረሰብ አቀፍ ጤና መድህን ኢትዮጵያ ውስጥ የሙከራ ትግበራውን የጀመረው ከዛሬ አራት አመት በፊት በአማራ፣በትግራይ፣ በኦሮምያና በደቡብ  ብሄር፣ብሄረሰቦችና ህዝቦች ክልልላዊ መንግስታት  በሰኔ ወር 2003 ዓ.ም ነበር - በ 13 ወረዳዎች ፡፡  በእነኚህ ወረዳዎች የተጀመረው የሙከራ ትግበራ፤ ጠንካራና ደካማ ጎን እየታየ በተደረገ የማስፋፍያ ሥራ በአሁን ሰአት ይህ የሙከራ ትግበራ ወደ 198  ወረዳዎች አድጓል፡፡
ይህ ሁሉ ሲሆን ሂደቱ ከችግር የጸዳ ነበር ብለን ወገባችንን ይዘን አንሞግትም፡፡ የተወሰኑ ችግሮች እንደነበሩ መንግስትም ሆነ ሥራው የሚመለከታቸው አስፈጻሚ አካላት በትክክል ይረዳሉ፡፡ ግን ደግሞ እንኳን እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እንዲሁም መልክዐ - ምድራዊ ችግሮች ባሉባት ሀገር አዲስ የሆነን ነገር  መሞከር ቀርቶ በረቀቀ ቴክኖሎጂ የሚታገዘው የናሳ ስፔስ ሺፕም ከስህተት የጸዳ ሊሆን እንደማይችል ለሁላችንም ግልጽ ይመስለናል፡፡
የሙከራ ትግበራው ያመጣውን ውጤት ከመዘርዘራችን በፊት የጤና መድህን ሥርዓትን በሃገራችን ለመተግበር ለምን አስፈለገ? የሚለውን መመለሱ ተገቢ ይመስለናል፡፡ ጸሃፊ ዮሃንስ ሰ. እንዳሉት ‹‹የህልም ዓለም ›› ለመፍጠር መንግስት በከንቱ ጊዜውንና ገንዘቡን ለማባከን ወይንስ የዓለም ጤና ድርጅት ባስቀመጠው መስፈርት የሃገሪቱን የጤና ስርዓት ሌሎች ሃገሮች ወደሚከተሉት አቅጣጫ ለመምራት?
የጤና አገልግሎትን ማግኘት የሰው ልጅ ሰብዓዊ መብት ነው፡፡ ይህ መብት እንዲከበር ደግሞ ሦስት ነገሮችን በሚዛናዊነት ሳይነጣጠሉ ማስኬድ ያስፈልጋል፡፡ አንደኛ ሃብታም ከደሃ ሳይለይ ዜጎች ህመም ሲገጥማቸው አገልግሎት የሚያገኙበት መብት (Equity)፣ ሁለተኛ ዜጎች ጥራት ያለው የህክምና አገልግሎት የሚያገኙበት የጤና አገልግሎት ( Quality Health Services )፤ ሦስተኛ አገልግሎቱን በጥራት መስጠት የሚያስችል የጤና ፋይናንስ ( Health Financing )፡፡ እነኚህ ሦስት ነገሮች የጤና አገልግሎት ለሚሰጡ አካላት አንድም ሦስትም ነገሮች ናቸው፡፡
እነኚህን ሦስት ነገሮች ማንጸርያ አድርገን የሃገራችንን የጤና አገልግሎት ስንቃኝ፣ መንግስት ለሁሉም ዜጎች ጤናን ለማዳረስ ጠንክሮ የመስራት ኃላፊነት አለበት፡፡ ይህን ለመፈጸም የጤና አገልግሎት በሁሉም ክልሎችና ወረዳዎች ተደራሽ እንዲሆን እየሰራ ይገኛል፡፡ ጥራት ያለው የጤና አገልግሎት ለመስጠት ደግሞ የጤና ተቋማትን በብዛት ከመገንባት ባሻገር በዘርፉ የተማረ የሰው ሃይል በማፍራት ላይ ይገኛል፡፡ ሦስተኛዉና ዋናው የጤና አገልግሎቱ የሚመራበት ፋይናንስ ነው፡፡
የኢትዮጵያን የጤና ፋይናንስ  ስንመለከት፣ 50 በመቶ የሚደጎመው ለጋሽ ሃገራት በሚሰጡን ድጋፍ ነው፡፡ ( አያድርገውና ይህ እርዳታ ድንገት ቀጥ ቢል ምን ያህል ምስቅልቅል እንደሚፈጠር መገመት አይከብድም)፡፡  የጤናው ዘርፍ የፋይናንስ ምንጭ ከሆኑት ውስጥ አንዱ ከመንግስት ካዝና የሚገኘው ሲሆን በአሁኑ ወቅት ለጤና ዘርፍ ከሚውለው ጠቅላላ ወጪ 16 በመቶ  የሚሆነውን  ብቻ የሚሸፍን ነው፡፡ ቀሪው ደግሞ የጤና ተቋማት የጤና አገልግሎት በመስጠት ከሚያገኙት ገቢ የሚገኝ ነው።
በእርዳታ ላይ የተደገፈ የጤና ፋይናንስ ይዞ እስከመቼ? … እስከመቼ በልመና ዜጎቻችን ይታከሙ?.... ለጋሾቻችን ፊት ያዞሩብንና እርዳታቸውን ያቆሙ ቀን ምን ይዋጠን?... መልሱ ቀላል ነው፡፡ ተጨማሪ የጤና ፋይናንስ አቅም መፍጠር!! ይህን ለማድረግ ደግሞ አዲስ የጤና ፋይናንስ ስርዓት ለሃገሪቱ ማስተዋወቅ - የጤና መድህን ስርዓትን፡፡
በዓለም ላይ የጤና መድህን ስርዓት ከእድርና ከዕቁብ ቅርጽ ተላቆ  አሁን ያለውን መልክ ለመያዝ ወደ 700 ዓመታት በፈጀ ሂደት ውስጥ እንዳለፈ ታሪክ ያወሳል፡፡ ዘመናዊው የጤና መድህን አባት ግን  ቻንስለር ኦቶቫን ቢስማርክ የተሰኘው የጀርመን ቻንስለር እንደሆነና  እ.ኤ.አ. በ1883 ዓ.ም ያወጣው ህግ መነሻ መሆኑን ድርሳናት ያስረዳሉ፡፡
በቢስማርክ አርቃቂነት የተጀመረው የጤና ኢንሹራንስ፣ የተለያየ ቅርጽ ይዞ አተገባበሩም ከሃገራት፣ሀገራት እየተለያየ ዓለምን አዳረሰ፡፡ ዛሬ በተለያየ መልኩ የጤና ኢንሹራንስን ተግባራዊ ለማድረግ የማይፍጨረጨር ሃገር የለም ማለት ይቻላል፡፡ የአፍሪካ ሀገሮችን ሁኔታ በምንመለከትበት ጊዜ ብዙዎቹ የምስራቅና የምዕራብ አፍሪካ ሀገሮች ከቅኝ ግዛት ነፃ እንደወጡ ይከተሉት የነበረውን የጤና አገልግሎትበማሻሻል የጤና አገልግሎትን በፍትሀዊነት ለዜጎቻቸው ለማዳረስ የተለያዩ የጤና መድህን ዓይነቶችን በመንድፍ ተግባራዊ አድርገዋል። በዚህ ረገድ ከሚጠቀሱት ሀገሮች መካከል ሩዋንዳ፤ ሴኔጋል፤ማሊ፤ኡጋንዳ፤ታንዛንያና፤ጋና ይገኙበታል። ሩዋንዳ የጤና መድህን ስልትን በመከተል እ.ኤ.አ እስከ 2007 ድረስ ከ9.5 ሚሊዮን ህዝቧ ውስጥ 5.7 ሚሊዮን የሚሆነውን በማህበረሰብ አቀፍ ጤና መድህን በማካተት ከፍተኛ ውጤት አስመዝግባለች።
ሃገራችን ኢትዮጵያም  የጤና መድህን ሥርዓት ተግባራዊ ለማድረግ በሙከራ ደረጃ የማህበረሰብ አቀፍ የጤና መድህንን በሙከራ ደረጃ በአራት ክልሎች በ198 ወረዳዎች በመተግበር ላይ ትገኛለች። ይህም በመሆኑ በሀብታሙና በድሀው እንዲሁም ከፍተኛ የጤንነት ችግር ያለበት የጤንነት ችግር ብዙም በሌለበት መካከል መረዳዳትና፣ መደጋገፍ እንዲፈጠርና  ፍትሃዊ የጤና አገልግሎት  እንዲሰፍን ምክንያት እየሆነ መምጣቱ  ታይቷል ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የሙከራ ትግበራው  ዜጎች የጤና አገልግሎት በሚሹበት ወቅት የሚያስፈልገውን ከፍተኛ ክፍያ በመቀነስ አባላትና ቤተሰቦቻቸው ህመም ባጋጠማቸው ወቅት ህክምና እንዲያገኙ የሚያበረታታና የጤና አገልግሎት አጠቃቀምን እንዲጨምር የሚያደርግ ነው፡፡
ከዚህ ረገድ ካየነው የማህበረሰብ አቀፍ የጤና መድህን የሙከራ ትግበራ የተካሄደባቸው ወረዳዎች ካልተካሄደባቸው ጋር ሲነጻጸሩ የማህበረሰቡ የጤና አጠቃቀም ላይ መድህኑ ያመጣውን ለውጥ መገንዘብ ይቻላል፡፡ ገለልተኛ በሆነ አማካሪ የተሰራውና ባለፈው ግንቦት ወር ለህትመት የበቃው የግምገማ ጥናት እንደሚያስረዳው የጤና መድህኑ በተተገበረባቸው ወረዳዎች የጤና አጠቃቀም ድግግሞሽ0.7 አድጓል፡፡ ይህም በሃገር አቀፍ ካለው አማካይ የጤና አጠቃቀም ( 0.34) አንጻር ሲታይ ትልቅ እድገት ነው፡፡
በአባላት ረገድም ካየነው እስከ ባለፈው ሰኔ 30 ቀን 2007 ዓ.ም በአራቱም ክልሎች 1,344,055 ቤተሰቦች ወይም 6,504,146 ሰዎች አባል ሲሆኑ 2,214,557 ሰዎች ህክምና አግኝተው ወጪያቸው በመድህኑ ተሸፍኗል፡፡
እንግዲህ ይሄን ነው ጸሃፊ ዮሐንስ ሰ. ‹‹ የህልም ዓለም!›› በማለት ሊያጥላሉት የሞከሩት፡፡ አራት ዓመት ሙሉ የሚከሰቱ ድክመቶችን በማረም የጤና መድህኑን የሙከራ ትግበራ ከ 13 ወረዳ ወደ 198 ማድረስ ትግስትና እልህ አስጨራሽ ትግል እንጂ የ‹‹ህልም ዓለም›› የወለደው ቅዠት አለመሆኑን ያገኘነውና ያስመዘገብነው ውጤት ይመሰክራል፡፡
በስተመጨረሻ ዮሐንስ ሰም ሆኑ ሥለ ጤና መድህኑ የተሳሳተ አቋም ያላቸው ሰዎች እንዲገነዘቡልን የምንፈልገው ሃቅ፣ የሚሰጡን አስተያየት እንድንሻሻል ታስቦ ከሆነ ድክመታችንን በማረም የተሻለ የጤና ስርዓት በሃገራችን እንዲሰፍን ሌት ተቀን እንጥራለን፡፡ ህብረተሰቡ በጤና መድህን ሥርዓት ላይ ያለውን ግንዛቤ ከፍ ለማድረግ በጋራ ለመስራት እንዲሁም መረጃ ለመለገስ በራችን ምንጊዜም ክፍት ነው፡፡ ይሄ ሳይሆን ቀርቶ በተሳሳተ መረጃ ህዝብን ለማደናገር መሞከርና ሥራን ማደናቀፍ ግን ወንጀል ነውና ተጠያቂ ሊያደርግም ይችላል፡፡
በተረፈ በመጪዎቹ አምስት አመታት ውስጥ የማህበረሰብ አቀፍ የጤና መድህንን በመላ ሃገሪቱ ለመተግበር መንግስት እንደሚሰራ ልናረጋግጥልዎ እንወዳለን፡፡ እርስዎም ‹‹ከህልም ዓለም ›› ትችትዎ ወጥተው እውነቱን ለማየትና ሃቁን ለመጻፍ እንደሚበቁ ሙሉ እምነት አለን፡፡
ከኢትዮጵያ የጤና መድህን
ኮሚኒኬሽንና ሞቢላይዜሽን ዳይሬክቶሬት

     ከኤዞፕ ተረቶች አንዱ እንዲህ ይላል፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ የሀብታም ጌታ አገልጋይ፤ ከቤት ጠፍቶ ወደ ዱር ይሄዳል። እዚያም አንድ ባዶ ዋሻ ያገኝና እዚያው ለመኖር ይወስናል፡፡ ሆኖም ገና አንድም ቀን ሳያድር የዚሁ ዋሻ ባለቤት የሆነው አያ አንበሶ ከች ይላል፡፡ አገልጋዩ ሰው በጣመ ደነገጠ፡፡ “አለቀልኝ!” ብሎ ተስፋ በመቁረጥ ካሁን አሁን ዘሎ ደቆሰኝ እያለ ይጠባበቅ ጀመር፡፡ ሆኖ አያ አንበሶ ዘሎ ሰውዬው ላይ ሳይወጣ ቀረ፡፡ ሰውዬው ደርቆ ተገርሞ ያስተውለዋል፡፡
ይልቁንም ማጥቃቱን ትቶ ያባበጠ መዳፉን ወደ አየር ከፍ አድርጐ እያቃሰተ አሳየው። ሰውዬው ትኩር ብሎ ሲያይ አንዳች የሚያክል እሾክ ተሰቅስቆበታል፡፡ ስለዚህ ቀስ ብሎ እየሳበ ነቀለለት፡፡ የቆሰለውንም አሠረለት፡፡ በአጭር ጊዜ ውስጥ ቁስሉ ሙሉ በሙሉ ዳነለት፡፡
አያ አንበሶ ምሥጋናው ወሰን የሌለው ሆነ፡፡ ስለሆነም ሰውዬውን ጓደኛ አደረገው፡፡ ዋሻውም ቤታቸው ሆነ፡፡
ጊዜ እየረዘመ ሲሄድ ግን ሰውዬው ወደ ዘመዶቹ መሄድ ፈለገ፡፡ አያ አንበሶን ተሰናብቶ ወደናፈቃቸው ወዳጅ ዘመዶቹ ሄደ፡፡ ከሰው ጋር ሲቀላቀል ግን አንዳንድ ሰዎች ከጌታው ጠፍቶ መሄዱን አስታውሰው እጁን በገመድ አስረው ወስደው ለጌታው አስረከቡት፡፡
ጌታውም ለሌሎች መቀመጣጫ ይሆን ዘንድ በአደባባይ የትርዒት ሸንጐ ላይ ለአውሬዎች እንዲጣልና ህዝብ እንዲያየው አዘዘ፡፡ በዚያ የፍልሚያ ቀን አውሬዎች ሰውዬው ላይ ተለቀቁበት፡፡ ከነዚህ አውሬዎች መካከል አንድ ግዙፍ አንበሳ ይታያል፡፡ ያ አገልጋይ ሜዳው ላይ ተጥሎባቸዋል፡፡
ግዙፉ አንበሳ ቀድሞ ወደ ሰውዬው አመራ፡፡ “ደቆሰው በቃ!” ሰባበረው በቃ!” ይላል ህዝቡ፡፡
የሆነው ግን የተገላቢጦሽ ነው፡፡ አንበሳው ሰውዬው እግር ሥር አጐንብሶ በፍፁም አክብሮትና ፍቅር ይተሻሸው ገባ! ደስተኝነቱ ፊቱ ይ ያበራል!ይህ አንበሳ የጥንቱ የዋሻ ጓደኛው አያ አንበሶ ነው!
ተመልካቹ ሁሉ፤ “ሰውዬው ምህረት ሊደረግለት ይገባል!” እያለ ጮኸ!
የከተማው ከንቲባ ከአውሬ የዚህ ዓይነት ምሥጋናና ደግነት በማየታቸው ተደስተው፣
“ሁለቱም በነፃ ይለቀቁ” ብለው አወጁ!
*   *   *
ከአንበሳ መዳፍ እሾክ የመንቀል ያህል ደግነት ለመሥራት መጣር ትምህርትነቱ ኃያል ነው፡፡ አንበሳና ሰው የመቀራረብና አብሮ የመኖር ደረጃ ሲደርስ፣ ሰውና ሰውማ ማንም ይሁን ማን ተስማምቶ መኖር ሊያቅተው አይገባም፡፡ መቻቻል በቁም ትርጉሙ ስንወስደው የማይስማሙ ወይም የሚቃረኑ ኃይሎች፣ ቡድኖች ወይም ግለሰቦች መኖራቸውን ያሳያል፡፡ ምንም ያህል ተፃራሪ ቢሆኑ የሀገር ጉዳይን
አማክለው ካዩት፤ የጋራ መድረክ አያጡም፡፡ ባለሙያውና ፖለቲከኛው የጋራ ቦታ ሊኖራቸው ይገባል፡፡ ፖለቲከኛውና ፖለቲከኛው (የተለያየ ፓርቲ አባል ቢሆኑም) የጋራ መቻቻያ ሊኖራቸው ግድ ነው፡፡ ከመቀራረብ መደፋፈር መወለድ የለበትም፡፡ ተባብሮ አብሮ መሥራት እንጂ ምሁሩን ማግለል ሊያስከትል የሚችለውን ችግር ግምት ውስጥ ማስገባት በዓለም ታሪክ የታዩትን ታላላቅ ስህተቶች
ከመፈፀም ያድነናል! ለጠብ አለመቸኮል ተገቢ ነው፡፡ “ወዳጅና ወዳጅ የተጣሉ እንደሆን መታረቅም አይቀር፣ እንደ ጥንቱም አይሆን” የሚለውን ግጥምም አለመዘንጋት ነው!
ገሀድ ዕውነት በአደባባይ ሲወራ ለመስማት አብዛኛው ህዝብ ይናፍቃል፡፡ ብዙ ከመፈንደቅና ያለልክ የሀዘን ማቅ ከመልበስ ይሰውረን!
አንዳንድ ምሁራን የለውጥ እርምጃ (ተሃድሶ) (Reformism) ወደ አብዮት ያመራል ይላሉ፡፡ አንዳንዶች ደግሞ “አብዮት እንዳይፈጠር ታኮ ይሆናል” ይላሉ፡፡ እንደየአገሩ ልዩ ባህሪ ግብዓቶቹ ወሳኝነት አላቸው የሚሉት ወገኖች ደግሞ እንደየሁኔታው ሁለቱን አካሄዶች
ያሞግሷቸዋል ወይም ይሽሯቸዋል፡፡ ዞሮ ዞሮ ፀሐፊው ሀንቲንግተን እንደሚለው፤ ከተሀድሶ እርምጃ ጋር የሚያያይዙት የአብዮት ችግሮች አንድም የምሁር መገለል፣ አንድም የገበሬ መከፋት ናቸው፡፡ በሀገራችን የአቀባባይ ከበርቴዎችና የቢሮክራሲ ደላሎች አደጋ ብዙ ሊሸሸግ ቢሞከርም ዛሬ አደባባይ መውጣቱ ዘግይተንም ቢሆን ዐይናችንን መግለጣችንን ይጠቁማል፡፡ እንግዲህ ኔትዎርኮቹን ሁሉ መፈተሽ ነው
ቀሪው ጐዳና! ስብሰባዎቻችን የተሞሉት “ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮህ” በሚለው ስላቅ ከሆነ መንፈሳቸው አስቂኝ ይሆናል፡፡ ሙሰኛው የፀረ ሙስና ተናጋሪ ሲሆን ምፀቱ አስገራሚ ነው፡፡ የትላንቱን ታሪክ ከዛሬው ሁኔታ የሚያላትመው ደስኳሪ ከውይይት ይልቅ ድንፋታን የሙጥኝ ሲል፤ “ይቺ አገር ወዴት እየሄደች ነው?” ብሎ መሸሞር ግድ ይሆናል፡፡ ሀቅ አይነቀን፡፡ ግልጽነት አይመመን፡፡ ወገናዊነትን፣
ዘረኝነትን፣ ፅንፈኝነትን፣ ትምክህተኝነትን እናስወግድ ካልን ከልብ እናስወግድ!
በዱሮው ዘመን፤ “ጉዟችን ረዥም፣ ትግላችን መራራ” ይባል ነበር፡፡ መንፈሱ ለየቅል ቢሆንም፤ የአሁኑም ዘመን ትግል መራራና ረዥም መሆኑ አልቀረም፡፡ “ለዳገት የጫንከው ሜዳ ላይ እንዳይደክም፣ ማልዶ መነሳት!” የሚባለው ለዚህ ነው፡፡ 

“ዲሞክራሲያዊ ውይይት ከሌለ አገሪቱ እንደአገር አትቀጥልም”

    ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ፤ “ከጋዜጠኞች የሚሰነዘርብኝን ትችት አልፈራም፤ ነጻ ሚዲያ ለዲሞክራሲ ግንባታው ሂደትና ለልማት እጅግ ወሳኝ ነገር ነው” ሲሉ መናገራቸውን ቢቢሲ ትናንት ዘገበ፡፡
“ፍጹም እንዳልሆንን እናውቃለን፤ በመሆኑም ከማንኛውም ጋዜጠኛ የሚቀርብብንን ትችት ለመቀበል ዝግጁ ነን” ብለዋል፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከቢቢሲ የአፍሪካ አገልግሎት አዘጋጅ ሜሪ ሃርፐር ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፡፡
“በዚህች አገር ውስጥ የማህበራዊ ሚዲያውን የመረጃ ፍሰት በዕለት ተዕለት እንቅስቃሴው በስፋት የሚጠቀም ንቁና ወጣት የህብረተሰብ ክፍል እንደመኖሩ፣ ዲሞክራሲያዊ የሃሳብ ልውውጥና ውይይት በሌለበት ሁኔታ አገሪቱ እንደ አገር መቀጠል አትችልም፡፡ ከዚህ አንጻር በትክክለኛው ጎዳና ላይ እንገኛለን ብለን እናምናለን” ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም፡፡
ባለፈው አመት ታስረው የነበሩት አንዳንድ ጦማርያንና ጋዜጠኞች፣ “እውነተኛ” ጋዜጠኞች” አልነበሩም፤ ታሳሪዎቹ ከሽብርተኛ ድርጅት ጋር ግንኙነት የነበራቸው ናቸው ያሉት ጠ/ሚኒስትሩ፤ የታሰሩትም በሙያቸው ሳይሆን መንግስትን ለመናድ ከሚፈልጉ ቡድኖች ጋር ግንኙነት እንዳላቸው የሚያሳይ ማስረጃ በመገኘቱ ነው ማለታቸውን የቢቢሲ ዘገባ ያስረዳል፡፡
“ጋዜጠኞች በዚህች አገር ውስጥ የሚሰሩትን ስራና የተከበረውን የጋዜጠኝነት ሙያ ማምታታት እንደሌለብን ግልጽ ሊሆንልን ይገባል”

ሲሉም አክለዋል ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም፡፡

ቡድኑ በቀጣዩ ኦሎምፒክ ማጣሪያም አይሳተፍም

    የኢትዮጵያ ሴቶች እግር ኳስ ብሔራዊ ቡድን ሉሲ፣ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ለሚመለከተው አካል መላክ የነበረበትን የተሳትፎ ማረጋገጫ ደብዳቤ ባለመላኩ በሰራው ጥፋት ሳቢያ፣ በካሜሩን አስተናጋጅነት ከሚካሄደው የ2016 የአፍሪካ ዋንጫ ቅድመ ማጣሪያ ውድድር ውጭ ሆኗል፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን፣ የውድድር ተሳትፎ ማረጋገጫ ደብዳቤውን ባለመላኩ ሳቢያ ብሄራዊ ቡድኑ
ከቅድመ ማጣሪያ የምድብ ድልድል ውጭ መደረጉን የተነገረ ሲሆን፣ ከዚህ በተጨማሪም ቡድኑ በዚሁ የፌዴሬሽኑ ጥፋት ምክንያት ከ2016ቱ የሪዮ ዴ ጄኔሮ ኦሎምፒክ ማጣሪያ ውጭ መሆኑንም ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡
ባለፈው ማክሰኞ ካይሮ በሚገኘው የካፍ ዋና ጽህፈት ቤት በተከናወነው የቅድመ ማጣሪያ ውድድር የምድብ ድልድል እጣ አወጣጥ ስነስርዓት ውስጥ ሉሲዎቹ አለመካተታቸውን ያስታወሱት ምንጮች፣ ፌዴሬሽኑ ከሚመለከተው አካል ጋር ተጻጽፎ ቡድኑን ወደ ውድድር ለመመለስ ማቀዱንና የፌዴሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ ትናንት ወደ ግብፅ በማቅናት፣ በበጀት ምክንያት በውድድሩ
በማይሳተፉ አገራት ቡድኖች ምትክ ብሄራዊ ቡድኑ መሳተፍ የሚችልበትን ዕድል ለማመቻቸት እንዳሰቡም ጠቁመዋል፡፡ፌዴሬሽኑ ባለፈው የአለም ዋንጫ ማጣሪያ ውድድር ተሳትፎ በነበረው የወንዶች ብሄራዊ ቡድን መመዝገብ የነበረበትን የምንያህል ተሾመ ቢጫ ካርዶች ችላ በማለቱ ሳቢያ በተፈጠረ ችግር ከፍተኛ የህዝብ ተቃውሞ ገጥሞት እንደነበር ይታወሳል፡፡

ከእንግሊዝ በተለይ ለአዲስ አድማስ)

“‘የሚያቅትህ ነገር የለም!...‘ እየተባልኩ ነው ያደግሁት...” - ደራሲ ስዩም ገ/ ህይወት


ከ12 አመታት በፊት ለንባብ የበቃው “ሚክሎል - የመቻል ሚዛን” በበርካታ አንባብያን ዘንድ ከፍተኛ አድናቆት የተቸረው የረጅም ልቦለድ
መጽሃፍ ነው፡፡ የመጽሃፉ ደራሲ ስዩም ገብረ ህይወት፣ በዚሁ መጽሃፍ ላይ ቀጣዩን “ሚክሎል - የማቃት አንጀት” ለንባብ እንደሚያበቃ ቢገልጽም፣
መጽሐፉ ለረጅም አመታት ለህትመት ሳይበቃ መቆየቱ፣ በርካታ አንባቢያን ዘንድ መልስ ያልተገኘለት ጥያቄ ሆኖ ቆይቷል፡፡ደራሲ ስዩም ገ/ ህይወት
ከአስር አመታት በላይ ድምጹን አጥፍቶ መቆየቱ ያሳሰባቸው አድናቂዎቹ፣ በቅርቡ በማህበራዊ ድረ ገጾች በኩል ደራሲውን የማፈላለግ ዘመቻ
መጀመራቸው ይታወቃል፡፡ ጋዜጠኛ አንተነህ ይግዛው፤ለደራሲ ስዩም ገብረ ህይወት በግል ህይወቱ፣ በመጀመሪያው ልብወለድ መጽሐፉና ተያያዥ
ጉዳዮች ዙሪያ፣ በኢሜይል ላቀረበለት ጥያቄዎች፣ የሰጣቸውን ምላሾች የመጀመሪያ ክፍል እንዲህ አጠናቅረነዋል፡፡

ውልደትና እድገት
ድርና ማጌ ወሎ ነው። “ሃድራው የሚደምቀው ተደራርበው ሲተኙ” እየተባለ የተዘፈነለት ባቲ ገንደድዩ፣ የአባቴ አገር ነው። “እኒህ አምባሰሎች አበላል ያውቃሉ በጤፍ እንጀራ ላይ ሳማ አርጉ ይላሉ” የተባለለት አምባሰል ደሞ የእናቴ አገር ነው። እኔ ግን ባቲ ተወልጄ፣ ያኔ የቃሉ ወረዳዋና ከተማ በነበረችው ሐርቡ ነው ያደግሁት። አስታውሳለሁ ገና የስምንት ዓመት ልጅ እያለሁ፣ ከቤታችን በር አጠገብ ባለው ወደ ሰሜን በሚሄደው ጎዳና ዳር ቆሜ፣ ወደማታ ላይ የሚያልፉትን አውቶቡሶች ማየት ደስ ይለኝ ነበር። አንዳንዶቹ አሥመራ፣ አንዳንዶቹ መቀሌ የሚል የተለጠፈባቸው ነበሩ። “እኔ ግን ሳድግ የምኖረው መቀሌ ነው” እል ነበር፤ ሁልጊዜ። ምን ታይቶኝ ነበር ማለት ነው? መቀሌን ማየት ይቅርና ስለሱ ሲወራ እንኳን ሰምቼ አላቅም።
 የትምህርት ሂደት
የአንደኛ ደረጃ ትምህርቴን ሐርቡና ቢስቲማ በምትባለው አምባሰል ባለች ትንሽ ከተማ ነው የተማርኩት። ሰባተኛ ክፍል ብቻ ባቲ ተማርኩ እንጂ የቀረው የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን የጨረስኩት የቃሉ አውራጃ ዋና ከተማ በሆነችው ኮምበልቻ ነው። ከዛ እድሜዬ በኋላ ከወሎ ጋር እንደተለያየን ቀረን። መጀመሪያ አዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ተመድቤ ከሄድኩበት ጊዜ አንስቶ በቋሚነት ለመኖር ተመልሼ አላውቅም። የሐርቡ ልጅነት መንፈሴ ግን የትም ልሂድ የትም፣ ቋሚ መኖሪያው እስካሁን ሐርቡ ነው። ከአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ላይብራሪ ሳይንስ በሚባል ሙያ በዲፕሎማ እንደተመረቅሁ፣የተመደብኩበት መስሪያ ቤት አንድ ስህተት ሰራ። አሁን ሳስበው ለካ ስህተትም ትክክል የሚሆንበት ጊዜ አለ እላለሁ። ያ መስሪያ ቤት  ስሜን ብቻ በማየት የሰሜን ተወላጅ ነው ብሎ በማመኑ፣ መቀሌ መድቦ ላከኝ። ለካ የራሴ ቃል ጥሪ ነው መስሪያ ቤቱን ያሳሳተው። ምን ይሄ ብቻ -  ያን ስህተት ትክክል የሚያደርገው ጉድ መች ታየና።
መፈጸም የነበረበት ስህተት ---  
አሁን ባለትዳርና የአራት ልጆች አባት ነኝ። የመሆኔ ብርታት፣የነፍሴ ብርሃን፣ የራዕየ ምርኩዝ የሆነችው ውዷ ባለቤቴ ባትኖር ኖሮ የኔ ማንነት ባዶ ነበር። ሚክሎልን ያነበበ ሁሉ በስም ያውቃታል። ሚክሎል የተወለደው ከኔ የሁነት አብራክ ብቻ ሳይሆን ከሷምዝንታለም የማይላላ፣ የማያረገርግ የድጋፍ ምሶሶ ነው። ያለ ምሶሶ ጎጆ ሊቆም ይችላል? በብርቱ ሴት ጠጣር መንፈስያልተደገፈ የወንድ ህይውት፣ በሸንበቆ ተራዳ የቆመ ጊዜያዊ ድንኳን ነው።
ትዳር ሳልይዝ፣ሶስት ዓመት ኖሬ መቀሌን ለቅቄ ሄድኩ። ሁለት ዓመት አዲስ አበባ ከኖርኩ በኋላ እንደገና ዩንቨርስቲ ገባሁ። ከዱሮው ሞያዬ ላይ የኢንፎርሜሽንና ኮምፒውተር ሳይንስ ተጨምሮበት በዲግሪ ተመረቅሁ። በጣም የሚገርመው ነገር ግን የመቀሌ አዙሪትሊለቀኝ አልቻለም። በከፍተኛ ትምህርት ኮሚሽን ተወዳድሬ አለፍኩና አሁንም ዳግመኛ መቀሌ ተላኩ። የመቀሌ ዩንቨርስቲን ለማቋቋም ከየትምህርት ተቋሙ ተመርጠው ከተመደቡት በጣት የሚቆጠሩት የአካዳሚክ ሰራተኞች አንዱ ሆንኩ። እንግዲህ የመሆኔ መረብ ሊይዝ የሚፈልገው ዓሳ፣ እዛው መቀሌ ስለነበር ይሆናል፡፡
በመቀሌ ዩንቨርስቲ የመጀመሪያውን ላይብረሪና የኮምፒውተር ማዕከል አቋቋምኩ። የመጀመሪያውም የኮምፒዩተር ስልጠና አደራጅና አስተማሪም እኔው ነበርኩ።መቀሌ ዩንቨርስቲ ሥራ እንደጀመርን ብዙም አልቆየንም። ከሁለት ጓደኞቼ ጋር እየተጨዋወትን፣ በግቢው ውስጥ እንንጎራደዳለን። ፀሃፊዎች ለመቅጠር ማስታወቂያ ወጥቶ ነበርና ማመልከቻ ለማስገባት የሚጎርፈው ግቢውን እጥለቅልቆታል። ከፊት ለፊታችን ከሚመጡትሶስት ወጣት ሴቶች መሃለኛዋ ላይ ዓይኔ ድንገት አረፈ። በህይወቴ ተሰምቶኝ የማያውቅ ልዩ ንዝረት ሁለንተናዬን ናጠው። ልቤ አምልጦ አለት ላይ እንደወደቀ እንቁላል ጧ ብሎ የፈረጠ መሰለኝ። ልጅቷ እስከመቼውም የማይጠፋ የሚመስል እሳተጎመራ አስነስታ፣ሄደች። ደግሜ ላያትም አልቻልኩም። ተፈልጋ የምትገኝበትም መንገድ የለም።  ህመሜን ተሸክሜ ቀረሁ። እንደ ካሜራ፣ ያ ድንገት ከፊቴ ላይ ፏ ብሎ የጠፋው ብርሃን፣ አሁንም እሁንም እየተመላለሰ ይጎበኘኝ ነበር። እሸሸዋለሁ ይከተለኛል። እንዲሁ ሲያንገላታኝ አንድሁለት ሰሞን እንዳለፈ፣ አንድ ቀን ድንገት ወደ ቢሮዬ ስልክ ተደወለ። ከአስተዳደር ነበር። ከሚቀጠሩት ሶስት ፀሃፊዎች አንዷ፣ ለኔ የሥራ ክፍል መሆኑን አውቅ ነበር። አስተዳዳሪው ሦስቱ መመረጣቸውን ገልጾልኝ፣ ለኔ የተቀጠረችውን እገሌ ትባላለች ብሎ ስሟን ነገረኝ። ስሟን በልቤ እየደጋገምኩ  ወደ አስተዳደር መሄድ ጀመርኩ። ልቤ ግን ስሟን መሸከም የከበደው ይመስል ምቱ ጨመረ። “ደሞ ይሄ ምን እሚሉት በሽታ ነው ለማያውቁት ሰው። ኧረ ተው! ኧረ ተው! አንተ ልብ አበዛኸው!” አልኩት።
ሦስቱ የተመረጡት ፀሃፊዎች ያሉበት ክፍል ደርሼ፣ ዓይኔን ወደ ውስጥ ወርወር ሳደርግ፣ ልቤም ተፈትልኮ ተወረወረና በእርግጡን እንቦጭ ብሎ ፈረጠ። እንዴት አድርጎ መልሶ እቦታው እንደተመለሰ አላውቅም። ከሶስቱ አንዷ ያቺው ልጅ እራሷ ነበረች። ጉልበቴእየተብረከረከና ከንፈሮቼ እየተንቀጠቀጡ፣ “መብራት አበራ የምትባለው የትዋ ነች?” አልኩኝ፤ ዓይኖቼን ከዓይኗ ላይ ሳልነቅል። ይባስ ብሎ ይቺው ልጅ እራሷ “እኔ ነኝ” እለችኝ። እርፍ! እሞት እንደሁ ጉዱን አየዋለሁ። ለካ ያቺ ልጅ የሁነቴ አሻራ መረብ አጥምዷትየነበረችው መብራት አበራ ነበረች።
ያቺ የነፍሴ ብርሃን መብራት አበራ (እኔ መብርህቴ እያልኩ ነው የምጠራት) ወደውጭ ለመሄድ እያደረገችው የነበረውን ዝግጅት ሰርዛ፣ መቀሌን ለቀን አዲስ አበባ በመግባት በሠርግ ተጋባን። የመሆኔ ብርታት፣ የራዕዬ ምርኩዝ ሆና፣ ሚክሎል መፅሐፍን አብረን ወለድን። ሦስት ወንድ ልጆችም ወለደችልኝ።
“የፍቅር መታሰቢያችን - ታይታኒክ” - በመቀሌ ዩኒቨርሲቲ
በጣም የሚገርመው ከ22 ዓመታት በኋላ ሦስቱን ልጆቻችንን ይዘን (ሚክሎል፣ ኖባ እና ካሌብን) መቀሌ ቤተሰብ ለመጠየቅ ከእንግሊዝ አገር እንደሄድን፣ ያኔ የቅርብ ጓደኛችን የነበረው የዩንቨርስቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር ክንደያ ገ/ሕይወት ዩንቨርስቲውን እንድንጎበኝጋበዘን። ያኔ ሲጀምር 42 ተማሪ ብቻ እንዳልተቀበለ ሁሉ ዛሬ ከ30 ሺ ተማሪ በላይ የሚያስተናግድበት አቅም ላይ ደርሷል። ደስ አለን። ግና በጣም ደስ የሚያሰኝም ያሳቀንም፣ ልጆቻችንንም እጅግ በጣም አድርጎ ያስገረመው ነገር የመጣው በኋላ ነበር።
ዶ/ር ክንደያ፤ ግቢውን እያስጎበኘን እያለ፣ ቀጥ አድርጎ ወደ አንድ ልዩ ቦታ ወሰደን። ያቺ ልዩ ቦታ መብርህቴን ለመጀመሪያጊዜ ያየሁባት፣ ከመጀመሪያው ያስተዳደር ህንፃ ፊት ለፊት የነበረች ነጥብ ናት። ሌላው እጅግ በጣም ጉድ የሚያሰኘውን ነገር የተናገረው ወዲያውኑ ነበር። እሱና የሥራ ባልደረቦቹ እየሳቁ፤ “ይቺን ሃውልት ያሰራነው ለናንተ ፍቅር መታሰቢያ ነው” አሉን። እኛም እጃቸው የሚጠቁመውን ስንከተል፣ በመርከብ ቅርፅ በኮንክሪት የተሰራች ትንሽ ጀልባ የምትመስል ሃውልት ዓየን። እኛም ልጆቻችንም ፍንድቅ ብለን የሳቅነውግን “ታይታኒክ” ተብላ ተሰይማለች ሲሉን ነበር። አይገርምም!
የድሮው ቢሯችን የነበረበት ህንፃም እስካሁን ድረስ አለ። “የኔ ቢሮ እዚህ፣ የናታችሁ ቢሮ ደሞ እዚህ ነበር” ብዬ ለልጆቼ ቢሮዎቹን እያሳየኋቸው ሳለ፣ ቀልደኛው ትንሹ ካሌብ ስዩም ፈገግ አለና በእንግሊዘኛ “ስለዚህ እናቴ ገና እዚህ መስራት እንደጀመረች ያለ ምክንያት ወደቢሮዋ መመላለስ ጀምረህ ነበር ማለት ነው!” ብሎ ሁላችንንም አሳቀን። ከዩንቨርስቲው ባልደረቦች አንዱ እየሳቀ፤ “ያኔ ያለምክንያት ቢሆንም አሁን ሲታይ ግን ለካ ለጥሩ ምክንያት ነበር የሚመላለሰው ያስብላል” አለ።
 ልምድ ያካበትኩበት ብሪትሽ  ካውንስል
እኔ ብዙውን የሥራ ዘመኔን ለብሪትሽ ካውንስል ኢትዮጵያ ነው የሠራሁት። አራት ዓመት ሙሉ የፕሮጄክት ማኔጀር ሆኜ ስሰራ፣ መላኢትዮጵያን ልቅም አድርጌ ለማየት ዕድል አግኝቻለሁ። ከዚያም ቀጥሎ የብሪቲሽ ካውንስል ኢትዮጵያ ቤተመጻህፍትናኢንፎርሜሽን አገልግሎት ዋና ሥራ አስኪያጅ ሆኜ አገልግያልሁ። በስሬ እስከ 25 ፕሮፌሽናል ሠራተኞች ነበሩ። በዚህ የሰባት ዓመት የሥራ ዘመን፣ እጅግ በርካታ የማኔጅመንትና ፕሮጄክት ማኔጅመንት ሥልጠናዎችን በአውሮፓ፣በአፍሪካና በኤስያ እየተዘዋወርኩ ወስጃለሁ፡፡ እጅግ በጣም በርካታ ፕሮጀክቶችን ነድፌአለሁም ፣ የሥራ ፕሮግራማቸውንም መርቻለሁ።በብሪትሽ ካውንስል ቆይታዬ ከሠራኋቸው ብዙ ነገሮች አንድ ሁለቱን ልጥቀስ። በኢትዮጵያ የመጀመሪያዎቹን ቴሌሴንተሮች (ኢንተርኔት ካፌና ኮምፒውተር ማዕከል) ያቋቋመው ፕሮጄክት ሃሳብ፣ንድፍና ትግበራም የኔው የአእምሮ ውጤት ነው። እኒህ የመጀመሪያዎቹማዕከሎች የተቋቋሙት በወሊሶ፣ በደብረብርሃን፣በጎንደርና በአክሱም ከተሞች ነበር። በኢትዮጵያ ውስጥ ያኔ የነበሩትን ሁሉንም ዩንቨርስቲዎች፣ ኮሌጆች፣ መምህራን ማሰልጠኛ ተቋማት፣ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች፣ ሆስፒታሎችና ጤና ጣቢያዎችን በኢንፎርሜሽን ቁሳቁስ፣መጽሐፍትና ሥልጠና ይረዳ የነበረውን እጅግ በጣም ሰፊ ፕሮጀክት በሃላፊነት መርቻለሁ። የኢንፎርሜሽን ማኔጅመንትና ፕሮጀክት ማኔጅመንት ኮርሶችን በማዘጋጀትና በማስተማርም አገልግያለሁ።
የሥራ ልምዴ በእንግሊዝ -----
በፊት የነበረኝን የማኔጅመንትና የፕሮጄክት ማኔጅመንት ዕውቀትና ልምድ በመጠቀም፣ እዚህ እንግሊዝ አገር ባለሁበት ክፍለ ሀገር (ዮርክሻየር) ለክፍለ ሃገሩ ስደተኞች ጉዳይ አስተዳደር መ/ቤት የፖሊሲና ሕዝብ ግንኙነት ሃላፊ በመሆን አገልግያለሁ።  ዋና ስራዬ ግን፣ በእንግሊዝኛ የሚታተም ወርሃዊ ጋዜጣ ማዘጋጀት፣ የማኔጅመንት ኮርሶችን ማዘጋጀትና መምራት፣ ዌብ ሳይት ማኔጅ ማድረግ፣ ኢንፎርሜሽን ማሰራጨት፣ ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ ጥናትና ምርምር ማካሄድን ይጨምር ነበር።
ጉግሳና ስዩም ምንና ምን ናቸው?
የሚክሎልጉግሳ ሙሉ በሙሉ ሃሳብ ወለድ ገጸባህሪይ ነው። እኔንም ሆነ ሌላ ማንንም ሰው አይወክልም። መጀመሪያ ስዩም ና ጉግሳ የማይመሳሰሉበትን ብናነሳ አይሻልም? አንባቢዎቼም ይሄንን ልብ ብለው እንዲረዱልኝ እፈልጋለሁ። ካልሆነማ እኔም በየአእምሮአቸው ጓዳሲንጀላጀል የሚኖር ዘባተሎው ጉግሳ ቀዌ ሆኜ መቅረቴ ነው።
ጉግሳኮ በየስብሰባው “ያዝ እንግዲህ” እያለ ታዳሚን ሲያሰለች ነው የሚውለው። እኔ ግን እሱ በተገኘበት ስብሰባ ሁሉ እግሬ የረገጠ ቢሆንም አንድ ቀን እንኳን ትንፍሽ ብዬ አላውቅም። ሲነሳ ሲወድቅ የነበረውን የዩኒቨርስቲ ተማሪ ስሜት ማዕበል ልብ ዬ መታዘብነበር ስራዬ። በልቤ ጓዳ ውስጥ ግን ልብ ያላልኩት የጉግሳ ሽል እየተፈራገጠ ሊሆን ይችላል። የማቀው ነገር የለኝም።ጉግሳ ሁሌ አለባበሱ የተንጀላጀለ፣ ያን ድንኳን የሚያህል ጃኬቱን እያንጓፈፈ ባለፈ ቁጥር በአካባቢው የነበረ ሁሉ “ይሄ ጅልአንፎ ቀውስ መጣ እንግዲህ” እያለ እሚጠቋቆምበት ነበር። ስዩም ግን ከረባት ከአንገቱ፣ ሱፍ ከትከሻው ወርዶ የማያውቅ፣ ዘወትር ሽክ እንዳለየሚታይ የዘመናዊ (አውሮፓዊ) ቢሮ ፕሮፌሽናል ማኔጀር ነበር።ጉግሳኮ ሴቶች ሲፈልጉት አይገባውም። መቼስ ጉዳዩ ነበረና ለሴት። እነ ፀደኒያና እነ ሶስና እንዴት ነበር በድንዝዝነቱ ልባቸው እርር ይል የነበረው። ስዩምም ለሴቶች እንደጉግሳ ነበር ብል እውነት አሁን የሚያውቁኝ ሁሉ ልባቸው ፍርስ እስኪል አይስቁም ትላላችሁ።
ጉግሳ የሐርቡ ልጅ ሆኖ ሲያድግ እንጂ አዲስ አበባ ከገባ በኋላ የነበረው ሁሉ ትምህርቱም፣ ድርጊቱም፣ ውሎውም የራሱ ብቻ ነው፡፡ ከስዩምጋር ምንም ግንኙነት የለውም። ስዩምኮ ሥነ-ጽሁፍ የሚባል ነገር ተምሮ አያውቅም።እሺ አሁን ደሞ ጉግሳና ስዩምን የሚያመሳስላቸው ምንድነው የሚለውን እንይ። የጉግሳ አስተዳደግና የጉግሳ አባት ባህሪና ታሪክ የራሱ የስዩም አባት ባህሪና ታሪክ ቀጥተኛ ነፀብራቅ ነው። ጉግሳ  የስዩምን ማንነት ኮርጆ ተወለደ እንጂ ስዩም የጉግሳን ማንነት ኮርጆ አልተወለደም። ለካ መኮረጅ የምጠላው ገና ከመወለዴ በፊት ነበር።
እንግዲህ ልብወለድ ያልሆነውን ፤ እውነቱን (ያልተኮረጀውን) ስዩም፣ የሐርቡን ልጅ አስተዳደግ እንዲህ እንዲህ አድርገን ዳሰስ ልናደርገው እንችላለን።
አባቴ “ትንሽ ነገር አታስብ” እያሉ ነው ያሳደጉኝ  
በአብዛኛው የባላንባራስ ልጅ እየተባልኩ ነበር የምታወቀው፤ በዛችው በሐርቡ ከተማ ሳድግ። አባቴ ባላንባራስ ገ/ሕይወት ሽማግሌ ከሆኑ በኋላ ነበር የወለዱኝ። ባላንባራስ ገ/ሕይወት ገና በጉርምስናቸው ነበር ከወላጆቻቸው ጋር ከሚኖሩበት ባቲ አካባቢ ካለ ገጠርመንደር በመጥፋት ወደ አስመራ የተሰደዱት። ከጣሊያን ወረራ በፊት ገና ዱሮ ነው ይባላል ይሄ የሆነው። ባላንባራስ ገብረሕይወት በጉርምስናቸው አገር ቤት እያሉ  ሰፈር ከሰፈር በሚደረገው ውጊያ የወንድ አውራ ነበሩ። በዛም የተነሳ ዑመር አባስበር የሚል ስምወጥቶላቸው ነበር። ይህን ያልወደዱላቸውና ስሞታው ያሰለቻቸው አባታቸው ሸህ አሊ ያሲን፤ እረግምሃለሁ እያሉ ስላስቸገሯቸው ነው ጥሎ ለመጥፋት ወስነው የተሰደዱት።
አስመራ ከተማ የትሪቦሊ (ትሪፖሊ) ዘማች ወታደር ሲመለምል ለነበረው ጣሊያንም ያን መለሎ፣ዠርጋዳ፣ወጠምሻ ዑመር አሊ ማግኘት ትልቅ ሲሳይ ነበር። ወጣቱ ዑመር አባስበር ዘወትር የሚናፍቀውን የወንድ ቦታ አግኝቶ፣ “ሸጋው ትርቡሊ” እየተባለ የሚዘፈንለትንሠራዊት ተቀላቀለ። ቦርድ ወጥቶ ወደ ጣሊያን እስኪመለስም ድረስ ወደ ስምንት አመት በየአረብ በረሃው ሲዋጋ ቆየ። ከዛም በኋላ ለዚያኑ ያህልጊዜ በጣሊያን አገር የዘመናዊ እርሻና አትክልት አዘማመር ሙያ ሲማርና ሲሰራ ቆይቷል። ወደ ኢትዮጵያ ተመልሶ፣ በአሥመራናመቀሌ ከተሞች ለብዙ ጊዜ እንደኖረ ይናገራል።
ገና ወዲያው መቀሌ እንደደረሰም ነው ያኔ የትግራይ ንጉስ ከነበሩት ከራስ ስዩም መንገሻ (የአፄ ዮሐንስ የልጅ ልጅ) ጋር የተዋወቀው። አብሮአቸው እንዲሰራም ሲጋብዙት ተስማምቶ በአስተርጉዋሚነት ከቤተመንግስታቸው መስራት ገና ከመጀመሩ ነበር ክርስትና ያነሱት።ዑመር አሊ ቀረና ገ/ሕይወት ካሳ የሚል አዲስ ስም አወጡለት። ‘ባላንባራስ’ የሚል ማዕረግም ሰጡት።
ባላንባራስ ገ/ሕይወት እድሜያቸው ገፋ ካለ በኋላ ነበር ወደ ትውልድ አገራቸው ባቲ ተመልሰው ሚስት አግብተው ልጅ መውለድ የጀመሩት። እስከዛ ድረስ መሃን ነኝ ብለው ይገምቱ የነበሩት ሰውዬ፣ አከታትለው ሦስት ልጅ ወለዱ። ሶስተኛ የተወለደውን ወንድ ልጅ በራስ ስዩም ስም ጠሩት። የስዩም ገ/ሕይወት ነፍስ፣ የህልውና ፊደሏን መቁጠር ጀመረች። አድጋም ከመብራት ህልውና ጋር ተሳሰረች። መብራት የማን ልጅ እንደሆነች ታቃላችሁ? የመብራት አባት አስር አለቃ አበራ ወልዱ የራሳቸው የራስ ስዩም ልጅ የሆኑት የራስ መንገሻ ስዩም ዋና አጃቢ ነበሩ። ታዲያ ይሄን ምን ትሉታላችሁ? ባላንባራስና ስዩምን ወደ መቀሌ ምን ጎተታቸው? አጋጣሚ ወይስ የህልውና አብሮነት አሻራ አዙሪት?
ስዩም ገ/ሕይወት ከእናቱ ተለይቶ ማደግ የጀመረው ገና የስምንት ወር ልጅ እያለ ነበር (በህመም ምክንያት) ። ባላንባራስም በአንቀልባ እያዘሉ፣ ወደ ስራቸው ቦታ ይዘውት ይሄዱና የፍየል ወተት የተሞላ ጡጦውን እያስታቀፉ ከዛፍ ጥላ ስር ደልድለው ያስተኙት ነበር። እዛበርሃ መሃል። ባላንባራስ ያኔ  ዱብቲ ተንድሆ አዋሽ ወንዝ ዳር የጥጥ እርሻ መሬት በማልማት ሥራ ላይ ተሰማርተው ነበር።
አባትም እናትም ሆነው ያሳደጉኝ ባላንባራስ ገ/ሕይወት፤ ገና ሦስት ዓመት ሳልሞላ የፍየል ሃሞት ያጠጡኝ እንደነበረ በደንብ አስታውሳለሁ። ፍየል ባረዱ ቁጥር የሃሞቱን ከረጢት ከሆድቃው መዝው ያወጡና “ናልኝ እስቲ ወዲህ የኔ አንበሳ... አንተነህ የወንዶች ወንድጀግና.... በል ያዝና ግጥም አድርጋት” እያሉ ይሰጡኝ ነበር። ታላቄ የነበሩት ወንድሜና እህቴ ከጎን ቆመው ያዩኛል። “እዩት እዩት የኔን ልጅ ፊቱ ትንሽ እንኳን ጨምደድ አይልም” ይላሉ ባላንባራስ። እኔም አንድ ጊዜ ጀግና የወንዶች ወንድ ተብሎ የተሰጠኝን ስም ላለመነጠቅ፣ ፊቴ ዘና እንዳለ ጭልጥ አደርጋታለሁ። በወንድነት ኩራትም እህትና ወንድሜን ጀነን ፈጠጥ ብዬ አያቸዋለሁ።
“ትንሽ ነገር አታስቡ” እያሉ ነው ያሳደጉኝ ባላንባራስ። “ትንሽ ነገር ማሰብ ትንሽ ያደርጋል። የኔልጅ ትልቅ ነህ። የሚያቅትህ ነገር የለም!!” ይሉኝ ነበር በየአጋጣሚው።ባላንባራስ የሚዝረከረክ ሰው አይወዱም። “ሰው ማለት ሁሉ ነገሩ ስትር ያለ ነው። ይሄ ልብሱን እንኳን በአግባቡ መሰተር ያቃተው ሰው፣ ምን የተሰተረ ህይወት ሊኖረው ይችላል።” ሲሉ እየሰማሁ ነው ያደግኩት።
ገና የአስራ ስድስት ዓመት ልጅ ሳለሁ ነው የሐርቡ ከተማ ወጣቶች ሊቀመንበር ሆኜ የተመረጥኩት። እንዴት እሳት የላሰ ምላስ እንደነበረኝ አስታውሳለሁ። ያኔ ነበር ሸዋየ እብዲቱ ‘የልጅ ሹም’ ትለኝ የነበረው። “አይ የልጅ ሹም..... የልጅ ሹምና የህዳር ጉም አንድ ነው”ትለኝ ነበር ባየችኝ ቁጥር። አስታውሳለሁ-- ጓደኞቼ ሁሉ የመንግስት ሠራተኞች ነበሩ፤ ካድሬ፣የግብርና ሚ/ር ሠራተኞች፣ አስተማሪዎች።
ከጥበብ ጋር ትውውቅ
በዛው እድሜዬ በወረዳው የታውቅሁ ሰዓሊ ነበርኩ። የመስከረም ሁለት ዓመታዊ በዓል ሲመጣ፣ አንደኛ ሆኖ የሚመረጠው አብዮታዊ ግጥም የኔ ነበር። ሰው ጢም አለበት አደባባይ ወደ መድረክ ወጥቼ አሸናፊ ግጥሜን ሳነብ ኩራቴ ወደር የለውም ነበር። የባላንባራስማ ኩራት ምኑ ተወርቶ። “ እንዴት ያለ ልጅ ነው ያለዎት አቦ አላህ ያሳድግልዎት” እያለ ሰው አድናቆቱን ሲገልፅላቸው፣ “ድሮስ የኔ ልጅ ምን ያቅተውና” ይሉ ነበር በኩራት ጀነን ብለው። በተመሳሳይ ጊዜ ነው በሐርቡ ከተማ የመጀመሪያውን ቤተመጽሐፍት ያቋቋምኩትና እዛው የመጀመሪያው አስነባቢ ላይብረሪያን ሆኜ መስራት የጀመርኩት። ትዝ ይለኛል እነዚያን ትርጉም የሩስያ ልብወለድ መጻሕፍት እንዴት አድርጌ እየተንሰፈሰፍኩ አነባቸው እንደነበረ።
እሚገርም እኮ ነው።  በጣም ከመጓጓቴ የተነሳ የነቻርልስ ዲክንስና ዶስቶይቪስኪ ትልልቅ የእንግሊዘኛ ልብወለድ መፃሕፍት ለመረዳት እታገል ነበር። ከእንግሊዘኛ ጋር የነበረን ፍጥጫ ትዝ ይለኛል። “እኔ ደግሞ ትሞታታለህ እንጂ አልገባህ” ይለኝ ነበር አያ እንግሊዘኛ።
እረስቼው....... ለካ በኪነትም ሃርሞኒካ ተጫዋቹ እኔው ነበርኩ።
እና ይሄውላችሁ ጉግሳ እንዳለ የኮረጀው  የሐርቡው ልጅ ስዩም፣ ልብወለድ ያልሆነው ታሪክ ይህን ይመስላል።
 “የቃሉ ሰው ቃል ማንጠር ይወዳል”
የቃሉ ሰው ከሆንክ ከቃሉ ጋር የሚኖርህ ፍቅር በእንዶድ ቢያጥቡት የሚለቅ አይደለም።የቃሉ ሰው ቃል ማንጠር ይወዳል። ተራው ሰው እንደ ዋዛ ጣል እሚያደርገው ነገር አባባል ሆኖ ይቀራል። ስነፅሁፍ ተፃፈም አልተፃፈም ያው ቃል ማንጠር ከሆነ ስነጽሁፍ የጀመረኝ ገና እኔ አድጌ ሳልጀምረው ነበር። ገና ብዕር ይዤ ልጻፍህ ሳልለው በፊት ነበር፣በልጅነቴ ቃል በገፍ የሚነጠርበትን ገበያ ሁሉ ማዘውተር የጀመርኩት። ከነ ሰይድዋ ሙሄ መች መለየት እወድ ነበር፡፡ እኔም ጅና የጠገበ ሸመሌን ይዤ በየለፍጀሌው (የሠርግ ዋዜማ ዘፈን ምሽት)፣ በየሠርጉ ሆታ፣ በአረፋው ጭፈራ እየታደምኩ፣ ያን የቃሉ ቃል እሸትእየዠመገግኩ ስቅመው፣ ያቺ ትንሽ ነፍሴ እንዴት ውስጧ ጥግብ እያለ ትመለስ እንደነበር ትዝ ይለኛል። የነ ሸህ ሁሴን ማሃዲ፣ የነሸህ ሙሃመድ አወልን መንዙማ ስሰማማ እንኳን ያኔ አሁንም ቢሆን ቀልቤን ይዞት ጥፍት ይላል። የነፍሴን ክሮች ልብን በሰመመን ጣቶችደበስበስ እያደረገ በሚያስተኛ የንዝረት ቅኝት ያርገበግባቸዋል። የእናቶቻችን ቡና እየጠጡ የሚፈለፍሉት የወግ እሸትስ የት ይረሳል።ቃልን በጽሁፍ የማንጠሩንም ስራ የጀመርኩት በዛውን ዘመን ነው። ለአብዮት በዓሉ፣ ለኪነቱ ማድመቂያ የሚሆኑ ግጥሞች እሞነጫጭር ነበር። አዎ እንዲያውም አንድ ነገር ትዝ አለኝ። እሱ ተጣፈው የሴትን ልጅ ልብ በአንድ ጊዜ ትኩስ ምጣድ ላይ እንዳረፈ ቅቤ ቅልጥነው የሚያደርገው ይባልለት የነበረ የፍቅር ደብዳቤም እፅፍ ነበር፤ለራሴ ሳይሆን ለሌሎች ጓደኞቼ። እኔማ አይናፋር ነበርኩ። አስታውሳለሁ አንድ ቀን ለጓደኛዬ የፃፍኩለት የፍቅር ደብዳቤ አምጥቶብኝ የነበረው መዘዝ። ደብዳቤው የተፃፈላት ልጅ ልክደብዳቤውን እንዳነበበች፣ እሱን ትታ ለምን እኔኑ ወዳ እርፍ አትልም መሰላችሁ። ጓደኛዬ መቼም ምን ቢማር ቢራቀቅ እንዲህ ያለ ደብዳቤ በህልሙም ሆነ በእውኑ ሊጥፍ እንደማይችል ለካ ልቧ ነግሯት ነበር።ሕይወት’ኮ ቅኔ ነች፤ ወርቁን ሳይሆን ሰሙን ብቻ እየኖርነው ሆኖ እንጂ።
 ቃሉና ቃሉ (አገሩ) እንዲህ በማይላቀቅ የፍቅር ቃልኪዳን ተሳስረው መኖራቸውን ሳስበው ግርም ይለኛል!
ሚክሎል -  ከጽንሱ እስከ ውልደቱ
ሚክሎል የተፀነሰው የሁነቴ አሻራ አካል ሆኖ ነው፣ እኔ ልብ ባልለውም።
መጀመሪያውኑ ከዘሩ ውስጥ ያልነበረ ነገር በኋላ የዛፍ ቅጠል፣ አበባና ፍሬ ሆኖ ሊታይ አይችልም። ቃለሚክሎል ከልቤ ውስጥ ሆኖ ኩኩሉሉ ሲል መሰማት የጀመረው ግን በኋላ ጊዜ የዩንቨርስቲ ተማሪ እያለሁ ተነስቶ የነበረውን የፖለቲካ ነውጥ ካሸተተ በኋላ ነበር።የዛን ጊዜ የዩኒቨርስቲ ተማሪ ትርምስን አባዜ በልቤ ውስጥ፣  የብላቴ ወታደር ማሠልጠኛ ጣቢያ ህይወቱን በፅሁፍ ልቅም እያደረግኩ እዘግብ ነበር - አንድ ቀን ወደ መፅሐፍ እቀይረዋለሁ በሚል ምኞት።ከዚህ ሁሉ በጣም ጠንካራ የሚመስሉኝ ግን እነዚህ ሁለት ምክንያቶች ናቸው። አንደኛው ከእውነት ስሪት ምንነት ጥያቄ ጋር ሁልጊዜ እንደተፋጠጠ የሚኖረው አእምሮዬ ነው። ገና ከልጅነቴ ጀምሮ እውነት እንደቡና ቁርስ ቂጣ ተቆራርሳ ልትኖር አይገባትም ይልየነበረው ልቤ ቂም አግቷል። “አንድ ፈጣሪ ከሆነ ያለው ለምን ብዙ እውነት ይኖራል። ብዙ እምነት ማለት’ኮ ብዙ እውነት ማለት ነው። እውነትማ አንድ ብቻ ትንፋሽ ነው እንጂ መሆን ያለበት። ፖለቲካ እንጂ እውነት እንዴት በጎራ ተከፋፍሎ ያዙኝ ልቀቁኝ እያለ፣በበላይነት ነግሶ ለመውጣት ይፋለማል። እውነትማ ገለልተኛ ገላጋይ ዳኛ እንጂ ጎራ የለየ አዋጊ ሊሆን አይገባውም። እውነት የጥያቄና መልስ አንድነቱን ጨርሶ፣ ሙሉነቱን ያለ የነበረ አንድ ትንፋሽ ካልሆነማ፣ መጀመሪያውኑስ እንዴት ሊፈጥረን ቻለ። የጥያቄና መልስእድሜውን ጨርሶ እንደ አለቀ እውነት ያልተቋጠረ፣ እስቲ የትኛው ትንተና፣ የትኛው ንድፈ-ሃሳብ ነው ወደ ድርጊት ተቀይሮ መፍጠር የቻለ።” ከዚህ ጥያቄጋ ግብግብ የሚገጥም መጽሐፍ የመጻፍ ህልሜ፣ ዘወር በል ብለውም ዘወር የማይል የመንፈሴ አውራጅና ማገር ሆኖይኖር ነበር።እውነቴን አይደለምን’ዴ? እውነት ያልሆነችውን ስንሆን እንከፋፈላለን፣ እርስ-በርስ እንገዳደላለን፣እውነት የሆነችውን ስንሆን ግን አንድ እንሆናለን፣እንፋቀራለን፤
ከራስም ከማህበረሰብም ጋር። ታዲያ መሆን ማለት ሌላ ምን ትርጉም አለው? የእራስን እውነትእንደ አንድ ያለቀ የህልውና ትርጉም ፈልጎ ከማግኘት ውጭ!ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ የሚገርም ነው። አንድም ቀን ባነበብኩት መጽሐፍ  እርካታ የማታውቀው ውስጠ ነፍሴ፣ ‘አንተ ልታነብ የምትፈልገውን ዓይነት መጽሐፍ መጻፍ አለብህ’ እያለች ሁልጊዜ ትሞግተኝ ነበር። አሁንም አልረካችም። ‘ሚክሎል፤የመቻል ሚዛን’ መጀመሪያህ፣እንጂ መጨረሻህ አይደለም ትለኛለች፤ እስካሁን።
ሚክሎል እና አንባቢው
ሚክሎል የመቻል ሚዛን በመጀመሪያ ህትመቱ አንባቢዎችን የመድረስ ችግር ነበረበት። የታተመው ቅጂ ብዛት ውስን፣ የስርጭቱ አያያዝ በአግባቡ ያልተደረገ ነበር። ምንም የማስተዋወቅም ሥራ አልተሰራለትም ነበር። እንደምንም ከብዙ ጊዜ በኋላም ቢሆን እጃቸውከገባው አንባቢዎችውስጥ፤ ‘ይሄ ሁልጊዜ ላነበው እፈልገው የነበረ፣ ሁሉን ነገር በአንድ ላይ አሰናድቶ የያዘ፣ መቼም ተሰርቶ የማያውቅ ሥራ ነው’ እያሉ እስካሁን አድናቆትና ከበሬታቸውን የሚገልፁልኝ ብዙ ናቸው። “ይሄ በጣም ከባድ መጽሐፍ ስለሆነ እኔ የምወደው ዓይነትአይደለም” የሚሉም አይብዙ እንጂ አሉ።
 ሚክሎል ላይ ያበቃል --?
ሚክሎል የመቻል ሚዛንን ያሳተምኩት በራሴ ገንዘብ ነበር። ከላይ እንደገለፅኩት፣ ስርጭቱ በጣም ብዙ ችግር ስለነበረበት የወጣውን ወጪ እንኳን መመለስ አልቻለም። ‘የማቃት አንጀት’ አብዛኛው ሥራው አልቆ የነበረ ቢሆንም እንደገና መጽሐፍ ማሳተም፣የሚታሰብ አልነበረም። ምንም እንኳን ምናቤ እጅግ በጣም ከፍ ያለ ቢሆንም በአጠቃላይ በሃገራችን ከነበረው ተጨባጭ እውነታ አንፃር፣ መጽሐፍ ተጽፎ ሊኖር እንደማይቻል ስረዳ፣ ብዕሬ፤”ምነው ገና ብዙ ለመውለድ ዱብ ዱብ ከማለቴ ወደ ኪስህ ከተትከኝ”  ስትለኝ  ሰምቼ፣እንዳልሰማሁ ዘጋኋት፤ ተውኳት። ‘ምናልባት አንድ ቀን ይሆናል..... አሁን ግን አልሆነም’ እያልኩ በልቤ የማቃት አንጀትን ረቂቅ ይዤ፣ ከነቤተሰቤ አገር ለቅቄ ወጣሁ። አሁን አስራ አራት ዓመት አልፎ፣ ከስንት ፍለጋ በኋላ አድነው የያዙኝ አድናቂዎቼ ጩኸት ቀሰቀሰኝ።ጠፍቷል ተብሎ ተስፋ የተቆረጠበት፣ሁለተኛውክፍል ‘የማቃት አንጀት’ ረቂቅም ከጓሮ አሮጌ ዕቃ ማጠራቀሚያ ጋራዥ ውስጥ አቧራ ለብሶ ተገኘ።


“እኔ በቁሜ ብሸለምም ሽልማቱ ለሌሉት ባልደረቦቼም ነው” (አርቲስት ዙፋን)

“ቆንጆ ቆንጆ ሴቶች ፈልጉ” ተብሎ ነው፤ተመርጬ የተቀጠርኩት
· ተወዛዋዥነት ለዘመናት ተንቆ የኖረ ሙያ ነው ትላለች

  የ50 ዓመት የኪነ ጥበብ ጉዞሽ እንደሚዘከር ቀደም ብሎ መረጃ ነበረሽ? በሰማሽ ወቅት ምን አልሽ? የአንጋፋ አርቲስቶችን የረዥም ዘመን የኪነጥበብ አገልግሎት መዘከር የተለመደ ይመስላል፡፡ ትክክል ነኝ?
የተሰማኝን ነገር እንኳን ልነግርሽ አልችልም፡፡ እግዚአብሄር እራሱ ሲፈቅድ ነው ሁሉም የሚሆነው፡፡ እኔ በቁሜ እያለሁ ይሄ በመደረጉ ከምነግርሽ በላይ ደስ ብሎኛል (በስሜት  እያለቀሰች) ምክንያቱም የውዝዋዜ ሙያ እንደ ሙያ፣ ሙያተኛውም እንደ ሙያተኛ ሳይቆጠር ዘመናት አልፈዋል፡፡ መጀመሪያ የ50ኛ ዓመት በዓሉ ሊከበር የነበረው መስከረም 27 ነበር፡፡ በመንግስት ስብሰባዎች ምክንያት ወደ ጥቅምት ሁለት ተዛወረ፤ ከዛ በኋላ እንደገና ወደ ጥቅምት 11 ተዛውሮ፣ እናትና ልጁ ሲፈቅዱ (ክርስቶስንና ማሪያምን ማለቷ ነው) ያው በዚህ ቀን በልዩ ሁኔታ ተከበረ፡፡ በዚህ አጋጣሚ ባህልና ቱሪዝምን ላመሰግን እወዳለሁ፡፡ የብሔራዊ ቴአትር የባህል ማዕከል ሰራተኛ የሆነችውን ወ/ሮ ብርሃንንም አመሰግናታለሁ፤ ብዙ ደክማለች ለዚህ በዓል፡፡ ድካምና መሰላቸት ሳይሰማት ለዚህ ክብር አብቅታኛለች፡፡ ለዚህ ክብረ - በዓል ብዙ የለፉትን ሌሎችንም ሁሉ በጣም አመሰግናለሁ፡፡
የውዝዋዜ ሙያና ሙያተኛው በተለየ ሁኔታ የማይከበሩበት ምክንያት ምን ነበር ?…
እኔ እንግዲህ መንታ አርግዤ እንደተገላገልኩ የምቆጥርባቸው ሁለት ነገሮች አሉኝ፡፡ ሙያውና ሙያተኛው እንደሙያተኛ አለመቆጠራቸውና ክብር አለማግኘታቸው አንዱ ያረገዝኩት ሃሳብ የነበረ ሲሆን ሁለተኛው የምንሰራው ብሔራዊ ቴአትር ይሁን እንጂ እኛ ተወዛዋዦች  የመንግስት አልነበርንም፡፡ ስለዚህ የጡረታ መብት አልነበረንም፡፡ ከዚያ ሰላማዊ ሰልፍ ወጥተን፣ የማዘጋጃ ቤት አንድ አርቲስት ህይወቱ አልፎ፣ ስንቱ በሳንጃ ተወግቶ ነው ጡረታችንን ያስከበርነው፡፡ ለ4 ወር ታስረን ሁሉ ነበር፡፡ በደምና በህይወት የተገነባ መብት ነው፡፡ የተወዛዋዡን ጉዳይ በተመለከተ ምንም ክብር አልነበረም፡፡ ቴአትር የሰራ፣ ዘፈን የዘፈነ፣ አሁን ዘመን ያመጣውን ፊልም የሰራ ጭምር ሲሸለም ታያለሽ፡፡ የኛን ሙያ ስታይና ስታስቢው ያሳለፍነው መከራ ይከብዳል፡፡ ከእኛ በፊት የነበሩ የዘርፉ ባለሙያዎች፤ በትንሽ ብር ደሞዝ ሀብት ንብረት ሳያምራቸው፣ ለሙያው ፍቅር ሲሰሩና መስዋዕትነት ሲከፍሉ ኖረዋል፡፡ ቀጣዮቹ እኛ ነን፤ ከኛም በኋላ የመጡ አሉ፡፡ ስለዚህ በተሰጠሽ ሙያ ተተኪን ታስተምሪያለሽ፤ ታሰለጥኛለሽ፤ ራስሽም ታገለግያለሽ፡፡ ለምን ብትይ… ያለፉት ለእኛ አስተምረዋል አገልግለዋል፡፡ በሌላ በኩል ተወዛዋዥ የሚሰራው ውዝዋዜ ብቻ አይደለም፡፡ ሁለገብ ነው፤ ቴአትርም ዘመናዊና ባህላዊ ውዝዋዜም… ብቻ ብዙ ነገር ይሰራል፡፡ ይህን ሁሉ የሚሰራው ሙያተኛ ግን አንድም ቀን ስሙ ሲጠራና ሲወደስ አትሰሚም፤ ሲሸለምም አታይም፡፡ ውዝዋዜ የዕድሜ፣ የጉልበትና የወጣትነት ስራ ነው፡፡ ለምን ስሙ አይነሳም? ለምን አይሸለምም? የሙዚቃ ማህበራት፣ የቲያትር ማህበራት፣ የፊልም ሰሪዎች ማህበራት አሉ፤ የውዝዋዜ ግን የለውም፡፡
እነዚህ ሁሉ ነገሮች ይቆጩሽ ነበር?
በጣም ይቆጨኝ ነበር… በጣም! እኔ እንደሚታወቀው፤ ለሚዲያም ቅርብ አይደለሁም፤ ግን አንድ ቀን እድል ገጥሞኝ ይህን ቁጭት እንደምናገረው እርግጠኛ ነበርኩ፡፡ ይሄው እግዚአብሔር ፈቅዶ፣ 50ኛ ዓመት ክብረ በዓሉ ሲከበር በደንብ ተናገርኩት፡፡ አንደኛ በእንዲህ መልኩ በውዝዋዜ ጥበብ 50 ዓመት ሰርታለች ተብዬ፣ ክብረ በዓሉ መዘጋጀቱ አንዱን አረገዝኩ ያልኩሽን ሃሳብ እንደመገላገል ነው፡፡ ሽልማቱ፣ ክብረ በዓሉና ዝግጅቱ የእኔ ብቻ ሳይሆን ከዚህ በፊት በዘርፉ ብዙ ሰርተው፣ ምንም ክብርና ሞገስ ሳያገኙ ላለፉት ሁሉ ነው፡፡ አንድ ሰው ግጥም ይጽፋል፣ ሌላው ዜማ ሊደርስ ይችላል፡፡ አቀናባሪው ሙዚቃውን ያቀናብራል፡፡ ከዚያ በኋላ ተወዛዋዡ መድረክ ላይ ይውረገረግበታል፡፡ እነዚህ ሁሉ ተቀናጅተው ነው አድማጭ ተመልካችን በቁጥጥር ስር የሚያውሉት፡፡ እንደ ጆሮ ሁሉ አይንም እኮ ሙዚቃን ማየት ይፈልጋል፡፡ ቪሲዲ የሚሰራው ለዚህ አይደለም እንዴ? ውዝዋዜ ለሙዚቃ የጀርባ አጥንት እኮ ነው፡፡
ከዚህ በፊት የተሸለሙ ተወዛዋዦች የሉም?
እርግጥ ባህልና ቱሪዝም እንዲሁም የኢትዮጵያ የባህል ማዕከል ይህን ሲያደርጉ የመጀመሪያቸው አይደለም፡፡ ለአርቲስት መርአዊ ስጦት፣ ለአርቲስት ደስታ ገብሬም ሲዘጋጅላቸው ነበርኩኝ፡፡ ነገር ግን ደስታ ገብሬ ማለት የኢትዮጵያን ብሔር ብሔረሰቦች ባህልና ውዝዋዜ በአሜሪካ፣ አውሮፓ፣ በአፍሪካና በክልል ስታስተዋውቅ ዘመኗን የጨረሰች ናት፡፡ ወዲህ ደግሞ ስትጨፍር አይን የምታፈዝ፣ አጥንት አላት የላትም እየተባለ የምታከራክር ትልቅ ባለሙያ፡፡ ከዚህ አንጻር አንደኛ በህይወት እያለች ባለመሸለሟ፣ ሁለተኛ ደግሞ በዝግጅቱ ቀን ብዙ ሰው ባለመምጣቱ በጣም ቅር ተሰኝቼ ነበር፡፡ አንድ ሰው ከሞተ በኋላ አበባ ማስቀመጥ፤ ወዲህ ወዲያ ማለት ጥቅም የለውም፡፡ እንደኔ በቁሙ ያለ ሰው፤ እንዲህ አይነት ክብር ሲደረግለት ግን እጅግ ያስደስታል፡፡
ያንቺ የ50ኛ ዓመት ክብረ በዓል ምን ይመስል ነበር? …
ከጅምሩ ልጆቼና የልጆቼ ጓደኞች ቀኑ ደርሶ ዝግጅቱ ሲጧጧፍ፣ እኔ በሌሊት ፀጉር ቤት ሄጄ ፀጉሬን ተሰርቼ ስመጣ፣ በራሴ መኪና እንደምሄድ ነበር የማውቀው፡፡ ልጆቼም የራሳቸው መኪና አላቸው፡፡ እናም በእናንተ ታጅቤ ስለምሄድ፣ መኪናችሁን አዘጋጁ፤ አገር ልብስም አዘጋጁና ልበሱ ብያቸው ነበር፡፡ ከፀጉር ቤት እንደመጣሁ ትንሿ ልጄ፤ “ማሚዬ፤ ዛሬ እኔ ነኝ ፕሮቶኮል፤ ተረጋጊ” አለችኝ፡፡  
ወደ ብሔራዊ የመጣሽው ግን በራስሽ መኪና ሳይሆን በሽንጠ ረጅም ሊሞዚን ነበር-----
ልክ ነው ልነግርሽ ነው፡፡ ከዚያ በቃ ገባሁ፤ ለበስኩና “በሉ እንዳናረፍድ እንውጣ” ስላቸው፣ “ቆይ ማሚ ትንሽ እንቆይ፤ ከዝግጅቱም ቦታ እየደወሉ ነው፤ እኛም በስልክ እየተገናኘን ነው” ይሉኛል፡፡ ልክ ወደ ውጭ ስወጣ፣ የ “ዋዜማ” ድራማ ካሜራ ማንን አየሁት፡፡ እንዴ እዚህ ምን ይሰራል ብዬ ገረመኝ፡፡ “ለምን እዚህ መጣህ ሳሚ?” አልኩት “ማሚዬ፤ ካንቺ ጋር ከቤትሽ ጀምሮ አብሬ መሄድ ፈልጌ ነው” አለኝ፡፡ እኔ አዳራሽ እንዲመጣ ነበር የጠራሁት፡፡ ለካ ከልጄ ጋር ተነጋግረው ኖሯል፡፡ ስወጣ ፎቶ እንዲያነሳኝ ተጠርቶ ነው፡፡ ከዚያ ለባብሼ ጨርሼ ስወጣ፣ ያን ሊሞዚን ተገትሮ አየሁት እልሻለሁ፡፡ ልጆቼና ቤተሰቦቼ ናቸው ሰርፕራይዝ ያደረጉኝ፡፡ ልጆቼ፣ ቤተሰቤና የልጆቼ ጓደኞች፤ በአበባ የታጀበውን ሊሞዚን ከበው እልልል ይባላል፡፡ በጣም ነው ያለቀስኩት! (አሁንም እያለቀሰች)
በደስታ ስሜት ----?
አዎ! አንደኛ ይህን ሁሉ ሳያዩ ያለፉ ተወዛዋዥ አስተማሪዎቼን አስቤ አለቀስኩ፡፡ እኔ የደረስኩበት አልደረሱም፤ ቢያንስ በህይወት ቢኖሩ ጡረታ ይወጡ ነበር፡፡ ለሙያው እየተሰጠ ያለውን ክብር ያዩ ነበር፡፡ በእነዚህ ምክንያቶች እንዲሁም ቤተሰቤና ልጆቼ ባደረጉት ነገርም በጣም ተደሰትኩኝ፡፡ ከዚያ እንባዬን መቆጣጠር አልቻልኩም፡፡ ማልቀስ ሲያንሰኝ ነው፡፡ በብሔራዊ ቴአትር፣ የአገር ፍቅር--- የባንዲራ ፍቅር------ የብሔር ብሔረሰብ ፍቅር… ያስተማሩን፣ ከአገራችን ወጥተን በዚያው እንዳንቀር፣ አገራችንን እንድንወድ ያደረጉን አንጋፋዎቹ አልፈዋል፤ ይህንን አላዩትም (አሁንም ለቅሶ…) እኔ በህይወት ቆሜ ብሸለምም ሽልማቱ የእነሱም ነው፡፡ በህይወት እያሉ በየጓዳው ተረስተው የቀሩ፣ በውጭም በስደት ህይወታቸውን የሚገፉ፣ ለሙያው መስዋዕትነት የከፈሉ ብዙ አሉ፤ ሽልማቱ የእነሱም ጭምር ነው፡፡
ሽልማትሽ ምን ነበር?
ብዙ ነገር ተሸልሜያለሁ፤ ወርቅ፣ ብርና የተለያዩ ነገሮችን ተሸልሜያለሁ፡፡ ከ “ዋዜማ” ድራማ አዘጋጆችና ተዋንያን፣ እንደ አዋርድ የሚሰጥ ሽልማት ተበርክቶልኛል፡፡ ከተለያዩ አርቲስቶችም በርካታ ሽልማት አግኝቻለሁ፡፡ ከሽልማቱ ይበልጥ የሚያኮራው ደግሞ እያንዳንዱ ሰው፤ ስለኔ የሚያወራውና የሚሰጠው ምስክርነት ነበር፡፡ “አልጋነሽ ማለት ይህቺ ናት፤ እሷ ማለት እንዲህ ናት---” ተብሎ በቁምሽ ስትሰሚ፤ከዚህ በላይ ደስታ የለም፡፡ ይህ ክብረ በዓል ተከታዮቻችንን ያበረታታል፤ ለሙያቸው ፍቅር እንዲኖራቸው ያደርጋል፡፡
ከብሔራዊ ቴአትር ጡረታ የወጣሽው መቼ ነው?
ጡረታ የወጣሁት 2001 ዓ.ም አካባቢ ነው፡፡ አሁን በግሌ ብዙ ስራዎችን በመስራት ላይ እገኛለሁ፡፡
በመሃል ግን ውጭ ቆይተሽ መጥተሻል፡፡ የሄድሽው ለስራ ነበር ወይስ ለእረፍት?
ጡረታ እንደወጣሁ አሜሪካ ሄጄ፣ ሁለት ዓመት ቆይቼ ነው የተመለስኩት፡፡ እንደተመለስኩም፤ በየሻሽ ወርቅ በየነ የተዘጋጀ “ደመነፍስ” የሚባል ቴአትር አስተባብር ነበር፡፡ እስከ ዛሬዋ ቀን ድረስ እየሰራሁ ነው ያለሁት፤እግዚብሔር ይመስገን፡፡
በአሁኑ ወቅት “ቃቄ ወርዲዮት”፣ “ዋዜማ” ---- ላይ እሰራለሁ፡፡ ይኼው ለብሔራዊ ቴአትር 60ኛ ዓመት ክብረ በዓል ዝግጅትም እየሰራን ነው፡፡ እኔ ጡረታ ብወጣም ከቤቱ አልወጣሁም፡፡ ብሔራዊ ቴአትር፤ ለእኔ አባቴም እናቴም፣ለእዚህ ሁሉ ያበቃኝ ስለሆነ ከዚህ መራቅ አልፈልግም፡፡ ከታላቆቼም ከታናሾቼም… በቤቱ ካሉ የአስተዳደር ሰራተኞችም ጋር ተዋድጄ ነው የምኖረው፡፡
እስኪ ወደ ኋላ ልመልስሽ ----- ትውልድና እድገትሽ የት ነው?
ተወልጄ ያደግሁት ጎጃም ውስጥ ነው፡፡ በጣም ትንሽ ሆኜ ነው አዲስ አበባ የመጣሁት፡፡ እዚሁ ነው ያደግኩት፡፡ የጎጃም ተወላጅ ሆኖ አዲስ አበባ የሚኖር ሰው አግብቶ በልጅነቴ ይዞኝ መጣ፡፡ ያው እንደሚታወቀው፣ በዛን ዘመን ልጅ ሆነሽ ትዳሪያለሽ፤ ለአቅመ ሄዋን እስክትደርሺ ባልሽ ጋ ታድጊያለሽ፤ እኔም በዚህ መልኩ አግብቼ ሊያስተምረኝ አመጣኝ፤ አልተመቸኝም፤ ወደ አገሬ ተመለስኩኝ፡፡ ከዚያ ብዙ ሳልቆይ አክስቴ አዲስ አበባ አመጣችኝ ግን የሚያስተምረኝ አልተገኘም፡፡ ከዚያ ወደ ብሄራዊ ቴአትር መጣሁና ተቀጠርኩኝ፡፡ ዋናው ነገር በአሁኑ ሰዓት ደስ የሚለኝ፤ እኔ ያላገኘሁትንና የተቆጨሁበትን ትምህርት፤ በወንድሞቼ፣ በልጆቼ፣ በዘመዶቼ ተወጥቼዋለሁ፡፡ አሁን ያስተማርኳቸው ፕሮፌሰር፣ ዶክተር ወንድሞች አሉኝ፡፡ ልጆቼንም አስተምሬያለሁ፤ ሁሉም በጥሩ ሁኔታ ላይ ነው የሚገኙት፡፡
ብሔራዊ ቴአትር እንዴት ተቀጠርሽ?
ያን ጊዜ የባህልም የዘመናዊም ተወዛዋዥ እንዲኖራቸው አርቲስት አውላቸው ደጀኔ ጥያቄ አቀረቡ፡፡ በባህሉ በኩል የራሳቸው ተወዛዋዦች እንዲኖራቸው ሲፈቀድላቸውም “ቆንጆ ቆንጆ ሴቶች ፈልጉ” ተብሎ፤ተፈልጌ ነው ተመርጬ የተቀጠርኩት፡፡
ያው መልክሽም ቁመትሽም የሰጠ ሆኖ ተገኘሽ?    እንዴታ! መልክና ቁመና፣ ቅጥነት ጭምር መስፈርት ነበር፡፡ በወቅቱ ስንፈተን ደግሞ ዝም ብሎ ፈተና እንዳይመስልሽ፡፡ እስከ ላይ እስከ ጭንሽ ድረስ ልብስሽን ገልበሽ፣ አንዲት ጠባሳ በሰውነትሽ ላይ ካለ፣ አታልፊም፡፡ ፈታኙ በወቅቱ አርቲስት ጌታቸው ደባልቄ ነበር፡፡ ጠባሳው ብቻ ሳይሆን አቋቋምሽም ይታያል፤እግርሽ ቀጥ ያለ መሆን አለበት፤ወልገድ ሸፈፍ ካልሽ አለቀልሽ፡፡
 የበረራ አስተናጋጆች  እንደሚመለመሉት ማለት ነው?
እንደዚያ ነው! ከባድ ነበር ፈተናው፡፡ ከዚያ ስድስት ልጆች ተመረጥን፡፡ የሚገርምሽ ስድስታችንም በህይወት አለን፡፡
እስኪ እነማን እንደነበራችሁ ----- የሌሎቹን ስም ንገሪኝ?
አልማዝ ሀይሌ (ማሚ)፣ አሰለፈች በቀለ፣ ወይንሸት በላቸው፣ አበበች ገ/ሚካኤል፣ አሰለፈች  ገሰሰ፣ አልጋነሽ ታሪኩ ነን፡፡ ፍቅርተ ጌታሁን ሰባተኛ ናት፡፡ አሰለፈች ገሰሰና አሰለፈች በቀለ ውጭ ነው የሚኖሩት፤ ሌሎቻችን እዚሁ አለን፡፡ አሁን ለብሔራዊ ቴአትር 60ኛ ዓመት፣ ወገባችንን ስናውረገርግ ለማየት ያብቃሽ እንግዲህ፡፡
ብሔራዊ ቴአትር በስንት ዓመትሽ ነበር የተቀጠርሽው?
ምናልባት 16 ዓመት ቢሆነኝ ነው፤ በጣም ልጅ ነበርኩኝ፡፡
ውዝዋዜ ያቆምሽው መቼ ነው?
ለ24 ዓመት በውዝዋዜ ከሰራሁ በኋላ ነው ያቆምኩት፡፡ ለምን አቆምሽ ብትይ…በድሮ ጠቅላይ ግዛት፣ በአሁኑ ክ/ሀገር ስትሄጂ፣ ውዝዋዜም ቴአትርም ይዘሽ ሄደሽ ነው የምትሰሪው፡፡ ስለዚህ ባህል ትሰሪያለሽ፤ መሀል ላይ ቴአትር ትሰሪና ከዚያ በባህል ትዘጊያለሽ፡፡ ወይም ባህልና ዘመናዊ፣ ከቴአትር ጋር ይዘሽ ትሄጂና በዘመናዊ ዳንስ ትዘጊያለሽ… እንዲህ ነበር የሚሰራው፡፡ ከኢትዮጵያ ውጭ የብሄር ብሄረሰቦችን ስራ እንሰራለን፤ ፈረንጅ ቋንቋችንን ስለማያውቀው፣ማይም የሚሰራበትም ጊዜ አለ፡፡
በዚህን ወቅት መጀመሪያ የውብሸት ወርቃለማሁ ድርሰት የሆነውን “አንድ ለሶስት” ድራማ ሰርቻለሁ፤ “ሀሁ በስድስት ወር” ላይ የለማኝ ገፀ ባህሪ፣ “እናታለም ጠኑ” የጉሊት ሽንኩርት ነጋዴ፣ “ሀኒባል” ላይ ወታደር፣ “ቴዎድሮስ” ላይ የንግስቲቱ ገረድ ሆኜ ------ ተጫውቻለሁ፡፡ ከዚህ በኋላ በመዋቅር ዝውውር ወደ ቴአትር ክበብ ገባሁ፡፡
በማስተባበር ደረጃ እነ “ደመነፍስ”ን አስተባብሬያለሁ፡፡ በ “ገመና” አንድ ላይም የቃልኪዳን አክስት ሆኜ ሰርቻለሁ፡፡ አሁን “ዋዜማ” ድራማ ላይ ታማሚዋ ጥሩዬን ሆኜ እየሰራሁ ነው፡፡ ገና ያልታየ “የኔ ዘመን” ፊልም ላይ እየተወንኩ ነው፤ በቅርቡ ተጠናቅቆ ይመረቃል፡፡ “ይግባኝ” ላይም ዳኛ ሆኜ ሰርቻለሁ፡፡
እኔ የምለው ----“ይግባኝ”፣ “የባላገር ፍቅር”፣ “በእንቅልፍ ልብ“፣ “ዋናው ተቆጣጣሪ”፣ የተሰኙት ቴአትሮች ላይ የተወንሽው ወደ ቴአትር ክፍል ከተዛወርሽ በኋላ ነው?
ልክ ነው ግን አሁን ጠፋብኝ እንጂ በማስተባበርም በመተወንም ብዙ ሰርቻለሁ፡፡ “ስሌት” ፊልም ላይም ተውኛለሁ፡፡
ብሔራዊ ቴአትር ውስጥ መኪና የገዛሽ የመጀመሪያዋ አርቲስት አንቺ ነሽ ይባላል፡፡ ይሄ እውነት ነው?
ልክ ነው፤ በ1966 መስከረም 19 ቀን ነው መኪናዬ ከሞኤንኮ የወጣው፤አዝዤ ነው ያስመጣሁት፡፡ በደርግ ጊዜ እሱ መኪና ነዳጅ ይበላል ተብሎ እንዲገባ አይፈቀድም ነበር፤ ላለፉት 40 ዓመታት ነድቼዋለሁ፡፡ አሁን 41ኛ ዓመቱን ይዟል፤እሱ ቀለም እንዲቀባ ጋራዥ ገብቷል፡፡ አሁን ልጆቹ ለልደቴ ኮሮላ መኪና ገዝተውልኝ ነው የምነዳው፡፡ ከብሔራዊ ቴአትር የመጀመሪያ መኪና ገዢ ብሆንም ከሃገር ፍቅር አሰለፈች አሽኔና ዘነበች ታደሰ (ጭራ ቀረሽ) ቀድመውኝ ገዝተው ነበር፡፡
ስንት ልጆች አሉሽ?
ሶስት ሴቶች ልጆች አሉኝ፡፡ በጥሩ ሁኔታ ነው ያሳደግኋቸው፡፡ አንዷ ዲፕሎማና ዲግሪዋን ይዛ የራሷን ስራ ትሰራለች፡፡ አንዷ አግብታ፣ አንድ ልጅ ወልዳለች፤ ሆስተስ ናት፡፡ አንዷም አግብታ አሜሪካ ነው የምትኖረው፡፡ በዚህ ሁኔታ ላይ ይገኛሉ፡፡



    ከ2000 በላይ የጠቅላላ እውቀት ጥያቄና መልሶችን የያዘውና በድጋሚ ተሻሽሎ የታተመው “ምን ያህል ያውቃሉ” የተሰኘ መፅሐፍ ለ6ኛ ጊዜ ታትሞ ለንባብ በቃ፡፡ በቁምነገር መፅሔት ባለቤትና ስራ አስኪያጅ በጋዜጠኛ ታምራት ኃይሉ የተሰናዳው የጠቅላላ እውቀት መፅሀፍ፤ በቴክኖሎጂ፣ በኢኮኖሚ፣ በስነ-ፅሁፍ፣ በህክምና፣ በህግ፣ በታሪክ፣ በጠፈር፣ በቱሪዝም፣ በስፖርትና በሌሎች በርካታ ጉዳዮች ላይ እንደሚያተኩር ለማወቅ ተችሏል፡፡
 መፅሀፉ ለታዳጊም ሆነ ለአዋቂዎች እድሜ ሳይገድብ እውቀትን ለማስፋፋት ይረዳል የተባለ ሲሆን በየጊዜው እየተሻሻለና አዳዲስ ነገሮችን እያካተተ እንደሚሄድ ታውቋል፡፡መፅሀፉ በ193 ገፆች ተቀንብቦ፣ በ48 ብር ከ65 ሳንቲም ለገበያ ቀርቧል፡፡