Administrator

Administrator

    ባለፈው ሳምንት በደብረብርሃን ከተማ የተመረቀው ግዙፍና እጅግ ዘመናዊ የተባለው ዳሽን ቢራ ፋብሪካ፣ ጥረት ኢንዶውመንት ዱዌት - ቫሳሪ ከተባሉ ሁለት የእንግሊዝ ኩባንያዎች ጋር በእኩል 50፣ 50 የአክሲዮን ድርሻ የተቋቋመ ፋብሪካ ነው፡፡ የዛሬ 20 ዓመት የተቋቋመው ጥረት ዳሽን ቢራ ፋብሪካን ጨምሮ ተመጋጋቢ ፋብሪካዎችንና አገልግሎት ሰጪ ተቋማትን ማቋቋሙ ስኬታማ አድርጎታል ተብሏል፡፡ጥረት የዛሬ 15 ዓመት በጎንደር ከተማ ዳሽን ቢራ ፋብሪካን መሰረተ፡፡
እዚያው ጎንደር ከተማ ለቢራ ፋብሪካው ብቅል የሚያቀርብ የብቅል ፋብሪካ በባህርዳር ከተማ፣ ለቢራ ፋብሪካው የጠርሙስ ሳጥን የሚያመርት ተክራሮት የተባለ ፋብሪካ፣ በኮምቦልቻ ቆርኪ የሚያመርት ዋሊያ ቆርኪና ጣሳ ፋብሪካ አቋቋመ፡፡
ከውጭ አገር የሚገዙ ዕቃዎችን አምባሰል የንግድ ድርጀት ያቀርባል፡፡ ወደብ ላይ የደረሱ ዕቃዎችን ክሊራንስ በለሳ ያከናውናል፡፡ ዕቃዎቹን ከወደብ አንስቶ ወደ አገር ውስጥ የሚያጓጉዘውና በየፋብሪካው የሚያደርሰው ደግሞ ጥቁር አባይ የተባለው የትራንስፖርት ድርጅት ነው፡፡
 ጥቁር አባይ የዳሽን ፋብሪካ ምርቶችንም ለደንበኞች ያደርሳል ብለዋል፤ ዋና ሥራ አስፈጻሚው አቶ ታደሰ ካሳ፡፡ በክብር እንግድነት ተገኝተው ፋብሪካውን የመረቁት ጠቅላይ ሚ/ር ኃይለማርያም ደሳለኝ፤ እጅግ ዘመናዊ በሆኑ መሳሪያዎች የተደራጀው ዳሽን ቢራ ፋብሪካ የአገራችን የግል ድርጅቶች፣ ከዓለም አቀፍ ታዋቂ ድርጅቶች ጋር በመጣመር ቴክኖሎጂ ሽግግር፣ የኢንዱስትሪ አመራር እውቀትና ክህሎት ለመጎናፀፍ በሚያስችል ደረጃ ላይ መሆናቸውን ያመለክታል አርሶ አደሮችንም ምርታማ ያደርጋል ብለዋል፡፡ አቶ ኃይለማርያም፣ ፕላስቲክ፣ ቆርኪና ጠርሙስ አምራች ከሆኑና በደቡብ አማራ ክልል ከተገነቡ ተቋማት ጋር የምርት ትስስር የፈጠረ እንደሆነ ጠቅሰው፣ “ቢራ በማምረት ላይ ብቻ ሳይወሰን የአገራችንን ባህል በዓለም ደረጃ በማስተዋወቅ የአርሰናል ታዋቂ ተጫዋቾችን ሳይቀር እስክስታ ያስወረደ ቢራ ፋብሪካ ነው” በማለት ዳሽን ቢራ ፋብሪካን አሞካሽተዋል፡፡
ፋብሪካው ግብር በመክፈል አርአያ ነው ያሉት ደግሞ የአማራ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ናቸው፡፡ ዳሽን ቢራ ፋብሪካ ቤልጂየምና ቻይና ከሚገኙት የቢራ ፋብሪካዎች ቀጥሎ የዘመኑ ቴክኖሎጂ ያፈራቸው እጅግ ዘመናዊ መሳሪያዎች የተገጠሙለት ሦስተኛው ቢራ ፋብሪካ ነው ያሉት የዳሽን ደብረብርሃን ፋብሪካ ፕሮጀክት ሥራ አስኪያጅ አቶ ደሳለኝ መኮንን፤ ግንባታው ሁለት ዓመት ከመንፈቅ መውሰዱን፣ የፋብሪካው አጠቃላይ ወጪ 3 ቢሊዮን ብር መሆኑን፣ ከዚህ ውስጥ 2 ቢሊዮን ብር ለመሳሪያዎች ግዢ፣ 1 ቢሊዮን ብር ለውጭና ለአገር ውስጥ አማካሪዎች፣ ለግብአት አቅርቦትና ለሥራ ማስኬጃ መውጣቱን ተናግረዋል፡፡ ፋብሪካው፣ በ2 ሚሊዮን ሄክቶሊትር (1 ሄክቶሎትር 100 ሊትር ነው) ወደ ገበያ እንደሚገባና ትንሽ ማሻሻያ ተደርጎለት 3 ሚሊዮን ሄክቶሊትር እንደሚያመርት ጠቅሰው፣ ፋብሪካው በሙሉ አቅሙ ማምረት ሲጀምር አሁን የጎንደር ፋብሪካ ከሚያመርተው 1.5 ሚሊዮን ሄክቶ ሊትር ጋር በአጠቃላይ 4.5 ሚሊዮን ሄክቶ ሊትር ቢራ በዓመት ያመርታል ብለዋል፡፡
 አቶ ደሳለኝ፣ ፋብሪካው 40 ሺህ ኩንታል ብቅል መያዝ የሚችሉ 8 የሳይሎን፣ 4ሺህ 800 ሄክቶ ሊትር የመያዝ አቅም ያላቸው 12 የጥንስስ ጋኖች፣ ቢራው ወደ ሙሌት ከመሄዱ በፊት የሚቆይበት እያንዳንዳቸው 2 ሺህ 400 ሄክቶ ሊትር የሚይዙ 5 ታንኮች እንዳሉት ጠቅሰው፣ በሰዓት 45 ሺህ ጠርሙሶች የሚሞሉ ሁለት መስመሮች፣ (90 ሺህ) በሰዓት 100 ሊትር የሚሞላ የድራፍት መሙያ ማሽን እንዳላቸው ገልፀዋል፡፡ በግንባታ ወቅት 1200 የአካባቢው ነዋሪዎች የተለያየ የሥራ መስክ የተሳተፉ ሲሆን፣ በ245 ቋሚና በ450 ጊዜያዊ ሠራተኞች ሥራ እንደሚጀምር የፕሮጀክት ሥራ አስኪያጁ ተናግረዋል፡፡

   በአይነቱ የመጀመሪያው ነው የተባለውና ሰባት የአፍሪካ አገራት የሚካፈሉበት አፍሪካ ሰርከስ አርትስ ፌስቲቫል ከህዳር 17 እስከ 19 ቀን 2008 ዓ.ም በኦሮሞ ባህል ማዕከል ይካሄዳል፡፡
ፍካት ሰርከስ በሚያዘጋጀው በዚህ የሰርከት ፌስቲቫል ላይ ከግብፅ፣ ከኢትዮጵያ፣ ከኬንያ፣ ከማዳጋስካር፣ ከሴኔጋል፣ ከደበብ አፍሪካና ከዛምቢያ የተውጣጡና ስምንት ያህል በከፍተኛ ሁኔታ የሚንቀሳቀሱ ቡድኖች በፌስቲቫሉ ላይ የሚሳተፉ ሲሆን ከ85 በላይ የሰርከስ ባለሙያዎች ካተታቸውን አዘጋጆቹ በጣይቱ ሆቴል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቀዋል፡፡
በፌስቲቫሉ ላይ ከሰርከስ ትርኢቱ በተጨማሪ ከህዳር 21-22 ቀን 2008 ዓ.ም አውደ ርዕይ እና የልምድ ለውውጥ በአሊያንስ ኢትዮ ፍራንሲዝ እንደሚካሄድ አዘጋጆቹ ጨምረው ገልፀዋል፡፡

  በቀዳማዊ ንጉሰ ነገስት ኃይለሥላሴ ዘመን ተሰርቶ አገልግሎት መስጠት የጀመረው አንጋፋው ብሔራዊ ቴአትር ቤት፣ የተመሰረተበትን 60ኛ ዓመት ክብረ በዓል ለማክበር ዱብ ዱብ እያለ ነው፡፡ በእርግጥ በ60 ዓመት ጉዞው ቴአትር ቤቱ ብቻውን አይደለም አንጋፋ የሆነው፡፡ በርካቶችን በጥበብ አንግሷል፡፡ ቴአትር ቤቱን በለጋ ዕድሜያቸው የተቀላቀሉ በርካታ ታዳጊዎችን፤ በጥበብ አሽቶና ሞርዶ፣ ለአንጋፋነትም  አብቅቷቸዋል፡፡  የክብር ካባ አጥልቆላቸዋል፡፡ የዝና መጎናጸፊያ ደርቦላቸዋል፡፡ አብዛኞቹ ቀደምት ተቀጣሪዎች ታዲያ ለብሔራዊ ቴአትር ያላቸው ጥልቅ ፍቅር ወደር የለሽ ነው፡፡ ፍቅር ብቻ ግን አይደለም፤ጥልቅ አክብሮትም ጭምር እንጂ፡፡ አስገራሚው ነገር፣ብዙዎቹ አርቲስቶች በቴአትር ቤቱ በትንሹ ለ30 ዓመታት ቢያገለግሉም  በገቢ ረገድ ጠብ ያለላቸው ነገር የለም፡፡ በ100 ብር ደሞዝ ተቀጥረው፣ከ30 ዓመት አገልግሎት በኋላ - 200 ብር ባልሞላች ገንዘብ ጡረታ የወጡ አሉ፡፡ ማንም ግን ብሔራዊ ቴአትርን ሲወቅስ አይሰማም፡፡ ምሬት የሚባል የለም፡፡ ፍቅር ብቻ፡፡ መወድስ ብቻ፡፡ አድናቆት ብቻ፡፡ አክብሮት ብቻ፡፡ ጥልቅ ስሜት ብቻ፡፡ ጥበባዊ መንፈስ ብቻ፡፡ ብሔራዊ ቴአትርና አርቲስቶቹ በአስማት ክር የተሰፉ ይመስላሉ፡፡ ተዓምር ነው፡፡ሰሞኑን ደግሞ ሁሉንም አርቲስቶች በቴአትር ቤቱ ውስጥ እንዲመሽጉ ያደረጋቸው አንድ ትልቅ ጉዳይ ተፈጥሯል፡፡ ብሔራዊ ቴአትር የተመሰረተበት የ60ኛ ዓመት ክብረ በዓል፡፡ እነሱም ታዲያ ልደቱን ሊያደምቁለት የጥበብ ልምምድ ላይ ናቸው፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ማህሌት ኪዳነወልድ፤የቴአትር ቤቱን  በዓል ምክንያት በማድረግ፣በብሔራዊ ቴአትር ከ30 እስከ 40 ዓመት ያገለገሉ 5 አንጋፋ አርቲስቶችን በአጭር በአጭሩ አነጋግራለች፡፡

አርቲስት አልማዝ ኃይሌ
ብሔራዊ ቴአትር መቼ ነው  የተቀጠርሽው?
የተቀጠርኩት በ1958 ዓ.ም ነው፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ጡረታ እስክወጣ ድረስ ወደ 40 ዓመታት ገደማ በብሔራዊ ቴአትር ሰርቻለሁ፡፡
ደመወዝሽ ስንት ነበር?
(ሳ….ቅ….) ስቀጠር 100 ብር ነበር፤ሲቆራረጥ 96 ብር ከ25 ሳንቲም ይደርሰኛል፡፡ ያው ጡረታ ስወጣ ግን --- 200 ብር እንኳን አልደረሰም ነበር፡፡
ብሔራዊ ቴአትርን እንዴት         ትገልጭዋለሽ?
ለኔ ትልቅ ዩኒቨርሲቲዬ ነው ዩኒቨርሲቲ እንኳን 40 ዓመት አያስተምርም፡፡ በ20 ዓመቴ ገብቼ፣ በ55 ዓመቴ ስወጣ፣ ትልቅ ልጅ ሆኜ ነው የወጣሁት፡፡ አሁንም ለበዓሉ የተለያዩ ዝግጅቶችን ለማቅረብ ልምምድ ላይ ነኝ፡፡
እስቲ የማይረሳ ገጠመኝሽን ንገሪኝ ...
ለንጉሡለጃንሆይ፣ትርኢት እያሳየን ሳለ ውስጥ ልብሴ ወደ ታች ወርዶ፣ መድረክ ላይ ስወጣ፣ ጓደኞቼ፤“አልምዬ ውስጥ ልብስሽ … ውስጥ ልብስሽ…” ያሉኝን ፈጽሞ አልረሳውም፡፡

**********
አርቲስት ወይንሸት በላቸው
ብሔራዊ ቴአትር የገባሽው መቼ ነው?
በ1959 ዓ.ም ነው፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ጡረታ እስከወጣሁበት 1992 ድረስ ለ33 ዓመታት በቴአትር ቤቱ
አገልግያለሁ፡፡አሁንም ለ60ኛ ዓመት በዓሉ ልምምድ ላይ ነኝ፡፡
ደሞዝሽ ስንት ነበር …
ስትቀጠሪ?
ስቀጠርማ … በ100 ብር ነው … ብቻ
ጡረታዬ ላይ 500 ደርሻለሁ፡፡
ብሔራዊ ቴአትር ለአንቺ ምን ትርጉም አለው?
በደስታ መስራቴና የቤቱ ፍቅር ትዝታዬ ነው፡፡ እንደ ቤቴ ነው
የማየው፡፡ ሁለተኛ ቤቴ በይው፡፡ እኔ’ንጃ ምን
ልበልሽ… ፍቅሩ በጣም ይጎዳል፡፡ ደም ስር ውስጥ ስለሚገባ ከውስጥ
አይወጣም፡፡ የማይረሳሽ ገጠመኝ…
ውይ ብዙ አሉ፤ ግን አላስታውስም፡፡

****************************
አርቲስት መራዊ ስጦት
ለስንት ዓመት ነው በብሔራዊ ቴያትር ያገለገልከው?
ከ1974 ዓ.ም ጀምሮ ለ43 ዓመታት አገልግያለሁ፡፡
27ቱን ዓመት በኦርኬስትራ ኃላፊነት ነው የሰራሁት፡፡
መጀመርያ ስትቀጠር ደሞዝህ ስንት ነበር?
እኔ በ120 ብር ነው የተቀጠርኩት ያው ግን ---- ምን ታረጊበታለሽ በ8 ብር የጣሊያን ጫማ ገዝተሸ ታደርጊያለሽ፡፡ እኔ ጡረታ ስወጣ 700 ብር ደርሼ ነበር፡፡ አሁን በኔ የኃላፊነት ቦታ ላይ የሚሰራው የ6ሺ እና የ7ሺ ብር ደሞዝተኛ ነው፡፡ ጊዜው ተቀይሯል፤ መስዋእትነቱን የከፈልነው እኛ ነን፡፡ በእርግጥ ደሞዙ በማደጉ ከሁሉም በላይ ደስተኞቹ እኛ ነን፡፡ ዛሬ ዘፋኞች በሚሊዮኖች ብር የሚደራደሩበት ጊዜ ላይ ደርሰናል፡፡
ብሔራዊ ቴአትር ለአንተ ምንህ ነው ?
ብሔራዊ ቴአትር ለኔ የጥበብ መቅደሴ ነው፡፡ ከጡረታ በኋላ እንኳን ጠዋት 2፡30 ላይ ብሔራዊ ቴያትር፣ማታ ደግሞ ማርያም አታጭኝም፡፡ ብሔራዊ ቴአትር ቤትን በጣም እወደዋለሁ፡፡ በጣም አከብረዋለሁ፡፡ መጥፎ ነገር ሳይ እበሳጫለሁ፤ጥሩ ሳይ ደስ ይለኛል፡፡ ከሁሉ በላይ ግን ቲያትር ቤቱ እንደ ናይጄሪያና ሌሎች አገራት ከ4ሺህ -5ሺህ ተመልካች የሚይዝ አዳራሽ ሰርቶ ማየትን እመኛለሁ፡፡
እስቲ በሙያህ ያለህን ትውስታ ንገረኝ?
እንግዲህ ከነበርነው 13 የኦርኬስትራ አባላት የቀረነው 5 ነን፤ አሁን 80 ዓመቴን ይዣለሁ፡፡ በሙያዬ ዓለምን ዞሬያለሁ፡፡ ብዙ ትውስታዎች አሉኝ፡፡ ከሁሉም በላይ የስራ ፍቅር ነበረኝ፤ የሰራሁት ስራ ካልተወደደ እራቴን አልበላም ነበር፡፡


*******************
አርቲስት ጌታቸው ደባልቄ

በብሔራዊ ቴያትር ለምን ያህል ጊዜ
አገለገልክ?
ከተመሰረተ ጀምሮ ጡረታ እስከወጣሁበት ጊዜ ድረስ ለ40 ዓመታት ያህል አገልግያለሁ፡፡
የደሞዝ ጉዳይ እንዴት ነበር …
መጀመሪያ ስትቀጠር?
ያው ስቀጠር በ120 ብር ነበር፤ በኋላ636 ብር ደርሼ ነው ጡረታ የወጣሁት
ብሔራዊ ቴአትርን እንዴት ትገልፀዋለህ?
እድገት ላይ ያለ ቴአትር ቤት ነው፡፡ ሌላ እድገት እንጠብቃለን፤ ሌላ ብሔራዊ
ቲያትር እንደሚሰራ ሰምተናል፡፡ እደግ ተመንደግ ነው የምለው፡፡ በኪነጥበቡ
ብዙ እድገት አይተናል፤ ማንበብ የማይችሉትን ቲያትር አስጠንተናል፤
አሁን ደግሞ በዩኒቨርሲቲ ደረጃ እስከ ሁለተኛ ዲግሪ ሲሰጥ እያየን ነው፡፡
ተመስገን ነው እንግዲህ፡፡
ከመድረክ ገጠመኝ የማይረሳህ …
ከቴያትር ቤት ተወስጄ እስር ቤት
ገብቻለሁ፡፡ መድረክ ላይ ነስሮኝ፣ ነስሩ
አልቆምም ብሎ ፕሮግራም ተቋርጧል፡፡
ኧረ ብዙ ነው… ብዙ ብ….ዙ!!


*****************************

አርቲስት ሰለሞን ተካ


መቼ ነው ብሔራዊ የተቀጠርከው ?
በ1970 ነው፤ አሁንም ድረስ እየሰራሁ ነው፡፡
በስንት ብር ደሞዝ ሥራ ጀመርክ?
(ሳ…ቅ…) እንዴ --- ያኔ 100 ብር የኪስ ገንዘብ ብቻ ነበር የሚሰጠን፡፡ አሁን 2900 ብር ደርሻለሁ፡፡
ብሔራዊ ቴአትር ለአንተ ምንህ ነው?
ውይ… እኔ እንጃ፤ በቃ መንፈስ ነው ስሜት እንዴት ይገለፃል? መንፈስን ምን ብለሽ
ትገልጪዋለሽ? ለኔ ከቃል በላይ ነው፡፡
ውስጥን የማያርስ ደስታን ምን ልበልሽ?
በአፍሪካ የመጀመሪያው ቴአትር ቤት ነው፡፡ ህልሜ፤ብሔራዊ ቲአትር፣በዓለም ላይ አሉ ከተባሉ ቲያትር ቤቶች ጎን ተሰልፎ
ማየት ነው፡፡ የማይረሳህ የመድረክ ገጠመኝህ?
ሥራ እንደጀመርኩ አካባቢ፣ ያው ወጣትነትም አለ… እጩ ተዋንያን ተብዬ ተመረጥኩ፡፡ እኔ ቲያትርን ስፈልግ
ስፈልግ የምሰራው ነበር የመሰለኝ፤ በኋላም “ፍልሚያ” የሚባል ቲያትር ላይ አሽከር ሆኜ ተመረጥኩ፡፡ እኔ ሆዬ
ቤቴ ተኝቼ መጣሁና፣ ትርኢቱን ቁጭ ብዬ ማየት ጀመርኩ፡፡ በኋላ አዘጋጁ አቶተክሌ፤ “ምን ትሰራለህ እዚህ?” ሲለኝ
“መስራት ነበረብኝ እንዴ?” ብዬው፤ ደሞዝ የተቀጣሁትን አልረሳውም፡፡

የሰላም ተምሳሌቷ አን ሳን ሱ ኪ፣ ህጉ ባይፈቅድላትም አገሯን ለመምራት ቆርጣለች

   ከአስር አመታት በላይ ወታደሩ በገነነበት አገዛዝ ስር የቆየችው ማያንማር ባለፈው እሁድ ታሪካዊና የአገሪቱን መጻይ ዕጣ ፋንታ ይወስናል የተባለለትን የፓርላማ ምርጫ አካሂዳለች፡፡ ወታደሩ አገሪቱ ወደተሟላ ዲሞክራሲያዊ ስርዓት እንድትገባ ያለው ፈቃደኝነትን ይታይበታል ተብሎ የሚጠበቀው የዚህ ወሳኝ ምርጫ ጊዜያዊ ውጤት ባለፈው ረቡዕ ይፋ ተደርጓል፡፡
በምርጫ ውጤቱ መሠረትም፣ የኖቤል የሰላም ተሸላሚዋና የሰላማዊ ትግል ተምሳሌት የሆነችው አን ሳን ሱኪ ያሸነፈች ሲሆን የምትመራው ፓርቲ “ናሽናል ሊግ ኦፍ ዲሞክራሲም”፣ በስልጣን ላይ ያለውን የአገሪቱ ፕሬዚዳንት “ቴን ሴን ፓርቲ ዩኒየን ሶሊዳሪቲ ዲቨሎፕመንት” ፓርቲን በሰፊ ልዩነት እየመራ እንደሚገኝ አረጋግጧል፡፡
ምርጫ ከተደረገባቸውና ጊዜያዊ ውጤቱ ከታወቀባቸው 40 በመቶ ያህል የፓርላማ መቀመጫዎች፣ ናሽናል ሊግ ኦፍ ዲሞክራሲ 90 በመቶ ያህሉን ማሸነፉን የዘገበው ቢቢሲ፣ እስካሁን ድረስም ምርጫ ከተካሄደባቸው 491 ያህል የሁለቱ ምክር ቤቶች መቀመጫዎች 163 ያህሉን ሲያሸንፍ፣ ገዢው ፓርቲ በበኩሉ፤ 10 ያህሉን ብቻ ማሸነፉ መረጋገጡን ጠቁሟል፡፡
ከአገሪቱ ፓርላማ 664 መቀመጫዎች መካከል ሩብ ያህሉ ለጦር ሃይሉ የተተወ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፣ የአን ሳን ሱ ኪው ፓርቲ “ናሽናል ሊግ ኦፍ ዲሞክራሲ” አብላጫውን ድምጽ ይዞ አዲሱን የአገሪቱ ፕሬዚደንት መምረጥ የሚችለው ከቀሪዎቹ ወንበሮች ቢያንስ ሁለት ሶስተኛውን ወይም 329 ወንበሮችን መያዝ ሲችል ነው ብሏል፡፡
አን ሳን ሱኪ የምርጫው ውጤት ዘገየ እየተባለ መነገሩን ተከትሎ ባለፈው ማክሰኞ በስልጣን ላይ ላለው የአገሪቱ መንግስት በላኩት ደብዳቤ፣ በፖለቲካ ፓርቲዎቹ መካከል እስከ መጪው ሳምንት ድረስ ውይይት እንዲደረግና ብሄራዊ እርቅ እንዲፈጠር የጠየቁ ሲሆን፣ የፕሬዚዳንቱ ጽህፈት ቤት ዳይሬክተር ዛው ታይ፣ ፓርቲውን ላገኘው ውጤት “እንኳን ደስ አለህ” ብለው፣ መንግስት ለመወያየት ፈቃደኛ መሆኑንና ይህን መሰሉ ውይይት ሊደረግ የሚችለው ግን፣ የመጨረሻው የምርጫ ውጤት ከተገለጸ በኋላ እንደሆነ መናገራቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
በስልጣን ላይ ያለው የአገሪቱ መንግስትና አን ሳን ሱ ኪን ለአመታት በቁም እስር እንድትማቅቅ የፈረዱባት የመንግስቱ ታማኝ የጦር አበጋዞች ያወጡት ህገ መንግስት፣ አን ሳን ሱ ኪን የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ከመሆን እንደሚያግዳት የዘገበው ዘ ቴሌግራፍ በበኩሉ፣ እሷ ግን አሻንጉሊት ፕሬዚዳንት በመሾም ከበስተጀርባ ሆና አገሪቱን ለመምራት ማሰቧን አስታውቃለች፡፡
ይሄም የአገሪቱ የጦር አዛዦችን ክፉኛ አስቆጥቷል ተብሏል፡፡ የአገሪቱ ህገ መንግስት፤ ለፕሬዚዳንትነት የሚመረጠው ሰው የትዳር አጋሩ ወይም ልጆቹ የውጭ አገራት ዜግነት ያላቸው ከሆነ፣ ስልጣን መያዝ አይችልም የሚል ገደብ ማስቀመጡን ያስታወሰው ዘገባው፣ አን ሳን ሱኪ የቀድሞ ባለቤቷና ልጆቿ የእንግሊዝ ዜግነት ያላቸው ከመሆናቸው ጋር ተያይዞ፣ ፓርቲዋ ቢያሸንፍም እሷ ፕሬዚዳንት መሆን እንደማትችል ጠቁሟል፡፡
ቢቢሲ ከትናንት በስቲያ እንደዘገበው ደግሞ፣ የአገሪቱ የጦር ሃይል ሃላፊ ሚን ኡንግ ህሌንግ፤ የጦር ሃይሉ የምርጫው የመጨረሻ ውጤት መገለጹን ተከትሎ ከሚመሰረተው አዲሱ የአገሪቱ መንግስት ጋር ተባብሮ ለመስራት ፈቃደኛ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡
ለ15 አመታት ያህል በቁም እስር ላይ የቆየችውና በ2012 የፓርላማ ምርጫን ያሸነፈችው አን ሳን ሱ ኪ፣ ሰላማዊ ትግልን መርህ በማድረግ ሰብአዊ መብቶችን ለማስከበርና ዲሞክራሲን እውን ለማድረግ ባደረገችው ተምሳሌታዊ ተግባር የ1991 የአለም የኖቤል የሰላም ሽልማትን መቀበሏ ይታወሳል፡፡

    የአሜሪካ መንግስት በሶማሊያ የሚንቀሳቀሰውን የሽብር ቡድን የአልሻባብን ስድስት መሪዎች የሚገኙበትን ስፍራ ለጠቆመው ሰው ወይም ተቋም፣ 27 ሚሊዮን ዶላር በዎሮታ መልክ እንደሚሰጥ ማስታወቁን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
አሜሪካ ባለፈው አመት በሰነዘረችበት የድሮን ጥቃት የገደለችውን አህመድ አብዲ ጎዳኔን በመተካት፣ ቡድኑን በዋና መሪነት በማንቀሳቀስ ላይ የሚገኘውን አቡ ኡባይዳህን በተመለከተ መረጃ ለሰጣት፣ ከፍተኛውን የ6 ሚሊዮን ዶላር ወሮታ እሰጣለሁ ማለቷን ዘገባው ገልጿል፡፡
በኬንያ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ በተከሰተውና 148 ሰዎች በሞቱበት የቡድኑ የሽብር ጥቃት ቁልፍ ሚና እንደተጫወተ የሚነገርለትን ማሃድ ካራቴ ወይም አብድራህማን ሞሃመድ ዋርሳሜ የተባለ የቡድኑ አመራር፣ የቡድኑ የምልመላና የስልጠና ሃላፊ የሆነውን ማሊም ዳኡድ፣ የፋይናንስ ጉዳዮች ሃላፊውን ሃሰን አፍጎዬን፣ በአፍሪካ ቱሪስቶች ላይ በተሰነዘሩ የቡድኑ ጥቃቶች ላይ የተሳተፈውን ማሊም ሳልማንን እንዲሁም በኬንያ አዳዲስ የቡድኑ አባላትን በመመልመል ተሳትፏል ያለችውን አህመድ ኢማን አሊን በተመለከተ መረጃ ለሚሰጣት በድምሩ 27 ሚሊዮን ዶላር እሰጣለሁ ብላለች አሜሪካ፡፡

Saturday, 14 November 2015 09:44

ስኳርና ቁጥር

* በዓለማችን በስኳር ህመም
የተያዙ ሰዎች - 387 ሚሊዮን
* በበሽታው በየዓመቱ
የሚሞቱ ሰዎች - 5 ሚሊዮን
* ከህመሙ ጋር በተያያዘ
የሚወጣ ወጪ - 550 ቢሊዮን
ዶላር
* ጤናማ የሆነ የአኗኗር ዘይቤን
በመከታተል የስኳር ህመምን
መከላከል ይቻላል - 70 በመቶ
* በ2035 እ.ኤ.አ በዓለማችን
ይኖራል ተብሎ የሚጠበቀው
የስኳር ህመምተኛ - 600
ሚሊዮን
* እ.ኤ.አ በ1985 በዓለማችን
የነበረው የስኳር ህመምተኞች -
30 ሚሊዮን
* በዓለማችን በአንደኛው
ዓይነት የስኳር ህመም ብቻ
በየዓመቱ የሚያዙ ህፃናት
ቁጥር - 70ሺ

Saturday, 14 November 2015 09:42

የፀሐፍት ጥግ

(ስለ ታሪክ)
- የምፈጥረው እያንዳንዱ ታሪክ እኔን
ይፈጥረኛል፡፡ የምፅፈው ራሴን
ለመፍጠር ነው፡፡
ኦክታቪያ ኢ.በትለር
- እውነተኛ ታሪክ የምፅፍ ከሆነ ከራሴ
ስም ነው የምጀምረው፡፡
ኬንድሪክ ላማር
- አርቲስት አይደለሁም፡፡ ካሜራዬን
እከፍትና ታሪኬን እተርካለሁ፡፡
ታይለር ፔሪ
- ህይወቴ ድንቅ ታሪክ ነው - ደስተኛና
በድርጊቶች የተሞላ፡፡
ሀንስ ክሪስቺያን አንደርሰን
- አባቴ ታሪክ መተረክ ያውቅበታል፡፡
የተለያዩ ድምፆች በማውጣት እንድስቅ
ያደርገኝ ነበር፡፡
ሊሊ ኮሊንስ
- ትልቁ ነገር ድምፅህ እንዲሰማ፣ ታሪክህ
እንዲደመጥ ማድረግ ነው፡፡
ድዋይኔ ዋዴ
- ስሜትን ሰቅዘው የሚይዙና አይረሴ
የሆኑ ገፀባህሪያትን ለመፍጠር ተግተህ
ትሰራለህ፡፡ ሆኖም የማታ ማታ ዋናው
ነገር ታሪኩ ነው፡፡
ጄምስ ዳሽነር
- በታሪክ ውስጥ ጠንካራ ሴት ገፀ ባህርይ
ስትኖር፣ ሁልጊዜ ያ ቀልቤን ይይዘዋል፡፡
ኦንግ ሊ
- አይገመቴ ሁን፡፡ እውነተኛና ቀልብ
ሳቢያ ሁን፡፡ ግሩም ታሪክ ተርክ፡፡
ጄምስ ዳሽነር
- ምንጊዜም ታሪክ ስፅፍ፣ ለወንዶችም
ለሴቶችም ማራኪ እንደሚሆን
አምናለሁ፡፡
ሱዛኔ ኮሊንስ
- ታሪክ መጀመሪያ፣ መካከልና መጨረሻ
ሊኖረው ይገባል፤ ነገር ግን የግድ በዚያ
ቅደም ተከተል መሆን የለበትም፡፡
ዣን ሉክ ጎዳርድ
- ሁሉም ገፀባህርያት ከማውቃቸው ሰዎች
የሚፈጠሩ ናቸው፡፡ ከመጀመሪያው
ንሸጣ በኋላ ግን ለታሪኩ እንዲስማሙ
አርቃቸዋለሁ፡፡
ኒኮላስ ስፓርክስ
- ይሄንን ታሪክ ከዚህ ቀደም ሰምታችሁት
ከሆነ እንዳታቆሙኝ፤ ምክንያቱም
እንደገና ልሰማው እፈልጋለሁ፡፡
ግሮቾ ማርክስ
- ሴቶች፤ ስሜት ውስጥ ጠልቆ የሚገባ
የፍቅር ታሪክ የሚወዱ ይመስለኛል፡፡
ኢ.ኤል ጄምስ

Saturday, 14 November 2015 09:38

አንዲት ክፉ ቀን በካዛንቺስ

    ነገሩ ወዲህ ነው፡፡ ከአንድ ጓደኛዬ ጋር ካዛንቺስ አካባቢ ተቀጣጥረን ስለ ስራ ጉዳይ ለመናጋገር ቦታ ስንመርጥ፣“ፈተና ስለደረሰብኝ የጋራ ጓደኛችን ቤት እያነበብኩ ልጠብቅህ” አለኝና ስልኩ ተዘጋ፡፡ ይህ የጓደኛችን ቤት ታዲያ ካዛንቺስ በአሁኑ ጊዜ በልማት ምክንያት ከፈረሱት ከአድዋና ኦሜድላ ሆቴል በስተጀርባ የሚገኝ ነው፡፡  በዚህ ሰፊ ግቢ ውስጥ ብዙ የቀበሌም ሆነ የግል ቤቶች የሚገኙ ሲሆን አብዛኛዎቹ ለጫት መቃሚያና ሺሻ  ማጨሻ ቤትነት ያገለግላሉ፡፡
 እኔም በዚያች ክፉ ቀን ከጓደኛዬ ጋር ወደ ተቀጣጠርንበት ቤት ስደርስ፣አንድ ሁለት ተጨማሪ ሰዎች ባሉበት ፍራሽ አንጥፈው ግማሹ እየቃመ ሲያነብ ፣ግማሹ ካርታ ይዞ ነበር፡፡ በመሰረቱ ቤቱ የጓደኛችን በመሆኑ ከምናውቀው ሰው ውጪ ገንዘብ አስከፍሎ ጫት የሚያስቅም አይደለም፡፡ ሌሎቹ ቤቶች ግን ገንዘብ አስከፍለው የሚሰሩ ናቸው፡፡ለወትሮው ታዲያ ጫት መሸጥ እንጂ ማስቃም ክልክል ነው የሚል የንግድ ጽ/ቤት መመሪያና ደንብ አንግበው፣ ወደ ግቢው ጎራ የሚሉ የደንብ ማስከበር ሰራተኞች አልፎ አልፎም የፖሊስ ሀይሎች አይጠፉም፡፡ ታዲያ ባለ ጫት ቤቶቹ እቃቸው እየተወሰደባቸው ስለተቸገሩ፣በድንገት ከተፍ የሚሉ ወራሪ ደንብ ማስከበሮችን ለመከላከል ወሬ አቀባይ ዘብ፣ በር ፊት ለፊት እንዲቀመጥ ያደርጋሉ፡፡ ወሬ አቀባዩ ልጅ፤ “መጡ... በሩን ዝጋው” ካለ  ያለ ቅድመ ሁኔታ በሩን.... ድርግም፣ መብራቱን.... ድርግም፣ ሞባይልን ድርግም ..... ሁሉን  ድርግም አድርጎ ---- የውጭውን ሁኔታ በጆሮ ማዳመጥ ብቻ፡፡
የደንብ ማስከበር ሰራተኞቹ እያሰለሱ ወደ ግቢው ብቅ ቢሉም ተጠቃሚንና  ባለቤቶችን ከማደናበር በቀር ምንም አይነት ዘላቂ መፍትሄ ማምጣት አልቻሉም፡፡ ነገር ግን “መጡ! በር ዝጉ” ጨዋታ እያሰለቻቸው ሲመጣ፣ በዚያች ክፉ ቀን አንድ መላ ዘይደው መጡ፡፡ አንዱ የሲቪል ልብስ በመልበስ ተጠቃሚ መስሎ ቤት ውስጥ ዘው አለና፣ የማጨሻ እቃዎቹን ወስዶ፣ የፖሊስ ድጋፍ ለመፈለግ ወደ ውጭ ወጥቶ እስኪመለስ፣ በሮች በሙሉ ተዘጋግተዋል፡፡ ፖሊሶቹ ከደንብ ማስከበሮቹ ጋር ሆነው በር ቢያንኳኩም ምላሽ ስላጡ፣ “በር ክፈቱ ካልሆነ ቤቱን እናሽጋለን” የሚል ትእዛዝ አስተላለፉ፡፡ ነጋዴዎቹ ደግሞ በሲቪል ደንብ ማስከበር እቃ በመወሰዱ ቢደናገጡም፣ በር መክፈቱን ግን ተጨማሪ እቃ የሚያስወስድባቸው በመሆኑ “አያዋጣም” በማለት “ውስጥ የነበረው ሰው ወጥቶ በሩን ዘግቶ ሄዷል” ብለው መለሱ፡፡ በዚህ መሀል በተፈጠረው ክርክርና አተካራ ነገሮች እየተካረሩ መጡና ፖሊሶች “በሩን ካልከፈታችሁ በሃይል ሰብረን እንገባለን“ ማለት ጀመሩ፡፡ በሶስቱም ቤቶች ውስጥ ተቆልፎባቸው የተቀመጡ ሰዎች አሉ፡፡ “ውስጥ ያላችሁ ሰዎች፤በሩን አስከፍቱ፤አሽገነው ከሄድን መውጫ አይኖራችሁም” ማለት ጀመሩ፡፡ ውስጥ ያሉት ሰዎች ደግሞ በፍርሀት ተውጠዋል፡፡ ፖሊስ ቢያስረንስ፣ በአደባባይ እቃ አስይዘው ቢያሰልፉንስ፣ በቪድዮ ቀርጸው በሚዲያ ቢያሳዩንስ ---- በማለት በስጋት ቢርበደበዱም ከዝምታ በስተቀር ምንም ምላሽ የሰጠ አልነበረም፡፡
ታዲያ ፖሊሶች ሀይል ጨምረው የአንደኛው ቤትን በር ገንጥለው ገቡና ውስጥ በድንጋጤ ተውጠው የነበሩ ተጠቃሚዎች ላይ የዱላ መአት ያዘንቡባቸው ጀመር፡፡ ትንሽ ትልቅ የለ መቀጥቀጥ ሆነ፡፡ አንዱ ፖሊስ፣ ሴቷን አስተናጋጅ   በጫማ ሆዷ ላይ ሲረግጣት፣”ኽረ በእናትህ ነፍሰ ጡር ነኝ” ብላ ነው የተረፈችው፡፡
በተለይ አንድ አስር አለቃ ፖሊስ፤ፍጹም ስሜታዊ ሆኖ ጫማ ለማድረግ፣ ሽንት ለመሽናት ፍቃድ ሲጠየቅ ሁሉ ምላሹ፣በዱላ አናት እየበሳ ቁጭ እንዲሉ ማድረግ ሆነ፡፡ “ፍቃድ መጠየቅ አይቻልም ወይ?” ብለህ ጥያቄ ካቀረብክማ አለቀልህ፡፡  በቆመጥ፣ በእርግጫ ያጣድፍሃል፡፡ ዋይ! ዋይ! ቢባል ሰሚ የሚልም፡፡ ወደ ሁለተኛው ቤት ጎራ አሉና አሁንም በሩን በሀይል ገንጥለው በተመሳሳይ ሁኔታ ቅጥቀጣውን ገፉበት፡፡
ከሁለቱ ቤቶች የተገኙትን ተጠቃሚዎች መታወቂያ ሰበሰቡና እያዋከቡና እያዳፉ በመኪና ጭነው ወሰዷቸው፡፡ ወደ ቂርቆስ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ፡፡ ፖሊስ ጣቢያ ውስጥ የነበረው ሁኔታ አዝናኝም አሳዛኝም ሁኔታ ነበረው፡፡ አዝናኙ ሁኔታ አግዳሚ ወንበር ላይ ያስቀምጡህና የወጣ የገባ ሰው እያየህ እንዲዝናናብህ ያደርጉሃል፡፡ ለሌላ ጉዳዩ ባጠገብህ የሚያልፍ ፖሊስ ከየት እንደመጣህ ይጠይቅህና፤ “ከጫት ቤት” ስትላቸው፣ እንደ አሽሙረኛ ክፉ ጎረቤት እያሽሟጠጠ እየተሳለቀብህ ይሄዳል፡፡
አሳዛኙ ሁኔታ ደግሞ ይሄን ይመስላል፡፡ ከቤት ውስጥ ከተገኙት ተጠቃሚዎች ውስጥ አንዱ ዱላና ቅጥቀጣ ሲበረክትበት፣ “በህግ አምላክ አትምታኝ” ማለት ጀመረ፡፡ ያው ሞገደኛ አስር አለቃ፣ “ብትመታ ምን ታመጣለህ?”  “እናትክን...“. ብሎ መሳደቡን ቀጠለ፡፡” ተቀጥቃጩም “እናቴን አትስደብ፤እኔን ስደበኝ በህግ አምላክ” ይላል፡፡ አሁንም “እናትክን ብሎ” መራገጡን ገፋበት፡፡ በዚህ መሃል ታዲያ “እንደው የሚደበደብ ሰው ያለህ!” እያለ አምላኩን ሲለማመን የነበረ የሚመስል ፖሊስ፤ ተንደርድሮ መጥቶ ተደርቦ ይረግጠው ገባ፡፡ ይሄ “የመምታት ሱስ  ካልሆነ በቀር ምን ሊባል ይችላል?” ለእኔ ግልጽ አልነበረም፡፡ ለነገሩ ነብስ ያጠፋ ሰው ፖሊስ ጣቢያ ገብቶ እጅ የሚሰጥበት ምክንያት እኮ የሟች ወገኖች እንዳይገሉት መንግስት ከለላ እንዲሰጠው ነው፡፡ ፖሊስ ጣቢያ ውስጥ የህግ ከለላ ይሰጣል እንጂ ህግ ተላልፏል ተብሎ የተጠረጠረ ሁሉ ይቀጠቀጣል እንዴ? ህገ መንግስታዊ የሰብአዊ መብትስ? ዜጎች ፖሊስ ሲያዩ ሰላምና መረጋጋት ሊሰማቸው ይገባል እንጂ ፖሊስ ሲያዩ ሽብር፣ ፖሊስ ሲያዩ እንደሰረቀ ሰው መደናበር ውስጥ መግባት የለባቸውም፡፡
እርግጥ ነው ሱስ አስያዥ ነገሮች በማህበረሰቡ ላይ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና  ስነልቦናዊ ቀውስ ይፈጥራሉ፡፡ ወደፊት ሀገር ተረካቢ ተተኪ ትውልድ በሱስ የሚጠመድ ከሆነ ወንጀል፣ አስገድዶ መድፈር፣ ራስን ማጥፋት፣ እብደት ወዘተ ሊከሰት ይችላል፡፡ አደንዛዥ እፅ በመጠቀም ምክንያት ከሚፈጠረው ችግር ውስጥ ይሄ እጅግ ቁንጽል ችግር ይመስለኛል፡፡ የስነልቦና ባለሙያዎች ከሱስ ጋር ተዛማጅ የሆኑ ችግሮችን በተመለከተ ብዙ ሊሉ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን የእኔ ጥያቄ በሀገሪቱ እንኳን ጫት መቃም ሊያውቁ ቀርቶ “ጫት ማለት ምን ማለት እንደሆነ?” የማያውቁ የሀገሪቱ ክልል ከተሞች፣ በጫት ቤቶችና ሺሻ ቤቶች ተጥለቅልቀዋል፡፡ ለማመን በሚከብድ ፍጥነት ጫት መቃም ስልጣኔ፣ የዘመናዊነት መገለጫ ሆኗል፡፡
ፖሊስና ደንብ አስከባሪዎች “ከመቼውም ጊዜ በላይ የተጠናከረ ክትትል አድርገን ጫትና ሺሻ ቤቶችን እያሸግን ነው”፤ “ማጨሻ እቃዎች ሰብስበን አቃጥለናል” ይላሉ፡፡ በተቃራኒው ግን በተለይ ባለፉት አስር አመታት ውስጥ በአይነትም ሆነ በይዘት የተሻሻሉ ጫት ቤቶች በርክተዋል፣ የጫት ዓይነቶች በጥራት ጨምረዋል፡፡ የጫት ዋጋ የዛሬ አስር አመት ከነበረበት እጥፍ ሆኗል፡፡ ታዲያ ዋጋ እየጨመረ የመንግስት ቁጥጥር እየተጠናከረ፣የጫት ቃሚ ቁጥር ለምን ይጨምራል? ይባስ ብሎ በወር እስከ 30 ሺ ብር ድረስ ኪራይ እየከፈሉ፣ ሰፋፊ ግቢዎችን ተከራይተው አገልግሎት እየሰጡ ነው፡፡ ችግሩ የት ነው ያለው? ችግሩን ሳናውቅ መፍትሄ በመሰለን ነገር ላይ ብቻ ተመስርተን እየዳከርን ይመስለኛል፡፡ ፓራዶክስ (አያ አዎ) ነገር ነው፡፡
እኔ አንድ መፍትሄ ይታየኛል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት ችግሩ እጅግ ስር የሰደደ መሆኑን በይፋ አምኖ፣ መፍትሄውን ለማመላከት እንዲረዳ ጥናት ማካሄድና የችግሩን ስፋትና ጥልቀት መገንዘብ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባ ነገር ነው፡፡ በመቀጠልም ችግሩን ለመቅረፍ ሁሉን አቀፍ ስራዎች መሰራት ቢገባቸውም ህገወጥ ጫት ቤቶችን ለመቆጣጠር ግን የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ወይም የከተሞች አስተዳደር ምክር ቤቶች አዲስ አዋጅ ወይም ደንብ ማውጣት አለባቸው፡፡ ችግሩ መኖሩን መንግስትም፣ ህዝብም ሁሉም የሚመለከታቸው አካላት ከተገነዘቡ ችግሩ የለም ብሎ መከራከር ይቆማል ማለት ነው፡፡
 አብዛኛው የህብረተሰብ ክፍል ችግሩ አንገብጋቢ ደረጃ ላይ ደርሷል ይላል፡፡ መንግስት በበኩሉ፤ ስለ ችግሩ በግልጽ አያወራም፤ይልቁንም ውስጥ ውስጡን የአስቃሚዎችን እቃዎች በመውረስና ቅጣት በማስከፈል፣ ሰልችቷቸው ስራውን እንዲያቆሙ ለማድረግ ቆርጦ ተነስቷል፡፡ ብዙ ባይሳካለትም፡፡
መሆን ይገባዋል ብዬ የማምነው፤ “ችግሩ አለ?” አዎ! ስለዚህ ለችግሩ እውቅና በመስጠት እንደማናችውም ስራ የንግድ ዘርፍ ወጥቶለት መቃሚያ ቤት ከፍቶ ለመስራት ህጋዊ ፍቃድ መስጠት፣ በሚሰጠው ፍቃድ ውስጥ ግን ዝርዝር ጉዳዮችን በማካተት፣ ለምሳሌ ከ18 ዓመት በታች የሆኑ ወጣቶችን ሲያስቅሙ ቢገኙ ንግድ ፍቃዳቸው እንዲቀማ ማድረግ፣ በገንዘብም በእስራትም እንዲቀጡ ህግ ማበጀት፡፡ ባለቤቱ፤ ተጠቃሚዎች በቤቱ ውስጥ ለሀገር ደህንነት ስጋት የሆኑ ስራዎች ሲሰሩ ቢያገኝ ወይም ቢሰማ ለፖሊስ ማሳወቅ እንዳለበት ግዴታ ማስገባት፡፡ ይህን ባያደርግ ግን ለሚፈጠረው ማናቸውም ችግሮች በሃላፊነት እንደሚጠየቅ ማሳመን ወዘተ እንዲካተቱ ማድረግ፡፡
ስለዚህ መንግስትና ህዝብ የወደፊት ተተኪ  ትውልድ ጤናማ እንዲሆንና አደንዛዥ እጽ ውስጥ እንዳይዘፈቅ ለሚያደርጉት ትግል፣ ከዚህ ቀደም ችግር አባባሽ የነበሩት ጫት አስቃሚዎች፣ የመፍትሄ አካል እንዲሆኑ መንገድ አመቻቸ ማለት ነው፡፡ በምእራባውያን መንግስታት ዘንድ ያሉት ህጎች ይዘታቸው ይህን ይመስላል፡፡ ለምሳሌ አንድ ባለ ሱፐርማርኬት 18 ዓመት ላልሞላው ወጣት ሲጋራ ቢሸጥለትና ወጣቱ ሲጋራ ሲያጨስ ፖሊስ ይዞት 18 ዓመት ያልሞላው መሆኑን ካረጋገጠ፣ የሸጠለት ባለ ሱቅ ወይም የሰጠው ግለሰብ በህግ ይጠየቃል፡፡ በመሆኑም ባለ ሱቁ፣ ገዢው ወጣት 18 ዓመት ያልሞላው ሊሆን ይችላል ብሎ ከተጠራጠረ መታወቂያውን ይጠይቃል፡፡ ተጠቃሚው መታወቂያ የለኝም ካለ አለመሸጥ እንጂ ሌላ አማራጭ የለውም፡፡
በህግ እንዳይዘዋወሩ፣ እንዳይጠቀሙ፣ እንዳያስጠቅሙ ክልከላ ያልተደረገባቸውን ጫት፤ ሲጋራና ሺሻ መጠቀም ወንጀል ካልሆነና፣ አንድ ለአቅመ አዳም የደረሰ ወንድ ወይም ለአቅመ ሄዋን የደረሰች ሴት፤ የምትፈጽመውን ድርጊት ጥቅምና ጉዳቱን ተገንዝበው የሚያደርጉት በመሆኑ፣ ሌላ ምክንያት ከሌለ በስተቀር ዜጎች የመጠቀም መብታቸው ሊከለከል አይገባም፡፡ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበረሰባዊ፣ የጤናና የስነልቦና ችግሮች ያስከትላል ከተባለ፣ማስተማርና ግንዛቤ የመጨመር ስራዎችን አጠናክሮ መቀጠል ያስፈልጋል፡፡
በካዛንቺሱ ገጠመኜ ተከድኖ ይብሰል ብለን የተውነው ችግር ቀላል እንዳልሆነ ለእኔ ተሰምቶኛል፡፡ ለዚህም ነው ያለኝን ሃሳብ ያካፈልኩት፡፡ መንግስት የዜጎችን መብት የመጠበቅ፣ ያለመናድ፣ ያለመደፍጠጥ ግዴታ አለበት፡፡ በአንዳንድ ሥነምግባር የጎደላቸው ፖሊሶች ስሜታዊነትና ግልፍተኝነት ምክንያት የዜጎች ሰብአዊና ሲቪል መብቶች ሲጣሱ ዝም ብሎ ማየት ተገቢ አይመስለኝም፡፡ ዜጎች እንዲህ መሰሉ የመብት ጥሰት በአንዳንድ ፖሊሶች ሲደርስባቸው አቤት የሚሉበትን ቦታም ማወቅ ይኖርባቸዋል፡፡ በተለይ እኔ እንደታዘብኩት ዓይነት የመብት ጥሰት በፖሊስ ጣቢያ ሲፈጸም ብዙዎች ግራ ሊጋቡ ይችላሉና ይታሰብበት፡፡

• ሶስት ግለሰቦች ተጠያቂዎች ሆነዋል፡፡ የስራ አስፈፃሚው አቶ ዮሴፍ ተስፋዬ ከሃላፊነት
ሲታገዱ ሁለቱ ሰራተኞች የጽሕፈት ቤት ኃላፊው ዘሪሁን ቢያድግልኝና፣ የአይቲ
ባለሙያዋ ዘውድነሽ ይርዳው ደግሞ ተባርረዋል፡፡
• ከስራ አስፈፃሚው አባላት አንዱ ይቅርታ ሲጠይቁ፤ ፕሬዝዳንቱና ሌሎቹ አመንትተዋል
• ጠቅላላ ጉባዔ እንደማይጠራም ተገልጿል፡፡

    በኢትዮጵያ ሴቶች እግር ኳስ  ላይ የፌዴሬሽን አስተዳደር ባደረሰው ከባድ ጥፋት ዙርያ በትናንትና እለት በኢንተርኮንትኔንታል የተሰጠው መግለጫ በቂና ተገቢ ምላሾች  ሳይሰጡት ቀረ፡፡ የሴቶች እግር ኳስ ባለድርሻ አካላት፤ የስፖርት ቤተሰቡ፤ የሚዲያ አካላትና ሌሎች ባለሙያዎች በሉሲዎች የውድድር ተሳትፎና የወፊት አቅጣጫዎች ላደረሱ ጥፋቶች አጠቃላይ አስተዳደሩ ተጠያቂ መሆን እንደሚገባውና በይፋ ይቅርታ መጠየቅ እንዳለበት ሲያሳስቡ ቢሰነብቱም መግለጫውን የሰጡት የፌደሬሽኑ አመራሮች ለደረሱት ጥፋቶች ሶስት ግለሰቦችን ተጠያቂዎች አድርገው በርካታ ጉዳዮችን አድበስብሰው አልፈዋል፡፡
ትናንት በኢንተርኮንትኔንታል ሆቴል በተካሄደው ጋዜጣው መግለጫ 4 የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ የስራ አስፈፃሚ አባላት ተገኝተዋል፡፡ እነሱም ፕሬዝዳንቱ አቶ ጁነዲን ባሻ፤ እንዲሁም ሌሎች የስራ አስፈፃሚው አባላት ኢንጅነር ጆን ቼቤ፤ አቶ አበበ ገላጋይ፤ አቶ ልዑልሰገድ በጋሻው እና አቶ አሊ ሚራህ ነበሩ፡፡ በጋዜጣዊ መግለጫው ስራ አስፈፃሚዎቹ ሉሲዎች ከአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ ውድድር ውጭ የሆኑባቸውን ጥፋቶች የፈፀሙት 3 ግለሰቦች መሆናቸውን እንዳረጋገጡ ሲገልፁ አንደኛው የስራ አስፈፃሚ አባል እንደሆኑና፤ ሁለቱ የፌደሬሽኑ ሰራተኞች ናቸውን አስታውቀዋል፡፡
የመጀመርያው ጥፋተኛ  ተብለው ከሃላፊነታቸው የታገዱት የስራ አስፈፃሚው ኮሚቴ  አባል የነበሩት አቶ ዮሴፍ ተስፋዬ ናቸው፡፡ አቶ ዮሴፍ በመግለጫ ላይ ተገኝተው ለሚዲያ ቃላቸውን እንዲሰጡ እድል ተሰጥቷቸው እንደነበር ውሳኔውን ያሳለፉት የስራ አስፈፃሚ አባላት ገልፀዋል፡፡ መረጃዎች እንዳመለከቱት ግን ይህ እድል እንደተነፈጋቸውና ከስራ ካገዳችሁኝ ሃላፊነቱን እለቃለሁ ማለታቸውን ጠቁመዋል፡፡ በሌላ በኩል ለእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ከካፍ የተላኩትን የውድድር ተሳትፎ ማረጋገጫ 4 ደብዳቤዎች በአግባቡ ባለመመልከታቸው ሁለት የፌዴሬሽን ተቀጣሪዎች ተጠቃቂ ተደርገዋል፡፡ ሁለቱ ሰራተኞች ለአፍሪካ እግር ኳስ ፌዴሬሽን  በተገቢው ጊዜ ምላሾችን ባለመስጠታቸው፤ ከሚመለከታቸው ጋር በቅርበት ባለመስራታቸውና ስለ ውድድር የተሳትፎ ማረጋገጫ ማሳወቅ ቢኖርባቸውም ግድየለሽነት በማሳየታቸው ከስራቸው እንዲባረሩ ተወስኖባቸዋል፡፡ የመጀመርያው የፅህፈት ቤቱ ሃላፊ አቶ ዘሪሁን ቢያድግልኝ ሲሆኑ ፌደሬሽኑ እንዳሰናበታቸው ከማሳወቁ በፊት የስራ መልቀቂያ አስገብተው ነበር ተብሏል፡፡ ሌላዋ ተጠያቂ ሆና ከስራዋ እንድትሰናበት የተወሰነባት ደግሞ ለረጅም ዓመታት በእግር ኳስ ፌደሬሽኑ የቀድሞ የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ ሆና በርካታ ስራዎች ስታከናውን የነበረችው የፌደሬሽኑ የአይቲ ዲፓርትመንት ሃላፊ ዘውድነሽ ይርዳው ናት፡፡ ዘውድነሽ በደረሰው ጥፋት ከካፍ በቀጥታ ይደርሷት የነበሩትን ደብዳቤዎች በግድየለሽነት ተመልክታለች፤ የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ ሳይሆን የመላው አፍሪካ ጨዋታዎች ተሳትፎን የሚመለከት ደብዳቤ ነው በሚል አዘናግታለች በሚል ጥፋተኛ መደረጓን በመግለጫ ላይ የነበሩት የስራ ሃላፊዎች አብራርተዋል፡፡
ከ1፡30 በላይ በፈጀው ጋዜጣዊው መግለጫ ላይ ከ30 በላይ የስፖርት ሚዲያዎች ተገኝተው ነበር፡፡ የፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ  መድረኩ ለሁሉም ጥያቄዎች ዕድል መስጠት የማይቻበት መሆኑን በተደጋጋሚ በመግለፅ፤ የምናካሂደው ጋዜጣዊ መግለጫ እንጂ ስብሰባ አይደለም በማለት ሲናገሩ ነበር፡፡ በአጠቃላይ ጋዜጣዊ መግለጫው በርካታ ጥያቄዎች ያልተመለሱበት፤ በርካታ አሳሳቢ አጀንዳዎች ማብራርያ ሳይሰጥባቸው የተድበሰበሱበት በስፖርት ሚዲያውና በፌዴሬሽኑ የሥራ ኃላፊዎች መካከል የተለያዩ ውዝግቦች የ የተንፀባረቁበትና አለመደማመጥ የሰፈነበት  ነበር፡፡
በመግለጫው ላይ ከተገኙ የሥራ አስፈጻሚ አባላት ኢ/ር ጆን ቼቤ ብቻ በይፋ ይቅርታ ቢጠይቁም የፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ እና አብረዋቸው መግለጫ ላይ የነበሩት ሦስት የሥራ አስፈጻሚ አባላት  ይቅርታ ለመጠየቅ እንዳዳገታቸው ለመታዘብ ተችሏል፡፡ አንድ ሁለት ሰው ባጠፋው ሁሉም መወንጀል የለበትም፤ የሚል አቋማቸውንም አስታውቀዋል፡፡
በጋዜጣዊ መግለጫ ላይ የተገኙት የስፖርት ሚዲያዎች ፌደሬሽኑ ለደረሱት ጥፋቶች በይፋ ይቅርታ እየተጠየቀ ነው አይደለም በሚልም ግራ መጋባታቸውን በተለያየ መንገድ ቢገልፁም፤ የፌዴሬሽኑ ኃላፊዎች ይህን አስመልክቶ ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ፤ በቂ ማጣራት እና ምርመራ አድርጎ መግለጫ ከመስጠት በላይ ምንም ማድረግ እንደማይችሉ ፤ ጥፋተኞችን ከስራ በማገድ እንዲሁም ቀጣይ አቅጣጫዎቹን ለመወሰን ምክክር በማድረግ የተከተልናቸው እርምጃዎችን መገንዘብ አለባችሁ ከዚህ በላይ ይቅርታ ለማለት ያዳግተናል ብለዋል፡፡
ከጋዜጣዊ መግለጫው በፊት ባለፈው ሰሞን ክለቦች አቋማቸውን ያሳወቁባቸውን ደብዳቤዎችን ማሰራጨታቸው የሚታወስ ነበር፡፡ የደደቢት እግር ኳስ ክለብ በጉዳዩ ላይ አፈጣኝ ማብራርያ እንደሚያስፈልግ ሲያሳስብ የቡና ስፖርት ማህበር ደግሞ አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራ ጠይቋል፡፡  የቅዱስ ጊዮርጊስ ህዝብ ግንኙነት እንደ ክለብ ወደ ውድድር የየምንገባበት ለብሔራዊ ቡድን አስተዋፅኦ ማድረግ ቢሆንም በእቅዳችን መሰረት ስኬታማ ካልሆንን ተጫዋቾቻችን ሀገር አለመወከላቸው ያሳዝነናል ብሎ ሲያስታውቅ የቅድስተ ማርያም ኮሌጅ፤ የዳሸን ክለቦችም በደረሰው ጥፋት ያደረባቸውን ቁጭት ከገለፁት መካከል ይገኙበታል፡፡ በጋዜጣዊ መግለጫው  ከተነሱት ጥያቄዎች መካከል ከላይ የተዘረዘሩትን የክለቦች አቋሞች በተመለከተ የፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ ምላሾችን ሲሰጡ  ቡድን መስርተው እና በጀት መድበው ከሚሰሩ ክለቦችና ኃላፊዎቻቸው ጋር በቀጥታ ግንኙነት እያደረግን ለመግባባት  የምንችልባቸውን ሁኔታዎች እንፈጥራለን ብለው፤ ጠቅላላ ጉባኤ መጥራት የማያስፈልግ ይሆናል ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ከዚሁ ጋር በማያያዝ ሌላው የፌዴሬሽኑ የሥራ አስፈፃሚ አባል አቶ አበበ ገላጋይ በበኩላቸው ጠቅላላ ጉባኤ መጥራት የሚቻለው በመተዳደሪያ ደንቡ መሰረት እንደሆነ ገልጸው አንድ ወይም ሁለት ክለብ ስለጠየቀ ሳይሆን ከጠቅላላ ጉባኤው አካላት ሁለት ሦስተኛው እንዲጠራ ከወሰኑ ብቻ ሊፈፀም የሚችል መሆኑን ሊያስገነዝቡ ሞክረዋል፡፡
በሌላ በኩል የስፖርት ሚዲያው በመግለጫው ካነሳቸው ጉዳዮች ዋንኛው በአጠቃላይ በስልጣን ላይ ያለው የእግር ኳስ ፌዴሬሽን በሴቶች እግር ኳስ በቂ ትኩረት አልሰጠም የሚለው ነበር፡፡ አሁን የታገዱት የቀድሞው የሥራ አስፈጻሚ አባል አቶ ዮሴፍ ተስፋዬ ፌደሬሽኑን በመወከል፤ በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን የሴቶች ልማት ኮሚቴ አባልነት መመደባቸው፤ በአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ተሳትፎ ዙሪያ ከአራት ጊዜ በላይ ደብዳቤ ተልኮ በቂ ትኩረትና ምላሽ አለመሰጠቱ፤ በአጠቃላይ በፌዴሬሽኑ አመራር ውስጥ ሴቶች አለመኖራቸው ለደረሱት ጥፋቶች አስተዋፅኦ ማድረጋቸውን የዳሰሱ ሃሳቦች በሁሉም ጥያቄዎች ተንፀባርቀዋል፡፡
በእነዚህ ሁኔታዎች ላይ ፕሬዚዳንቱ አቶ ጁነዲን ባሻና ሌሎቹ የስራ አስፈፃሚ አባላት በሰጧቸው ማብራሪያዎች በጥቅሉ ለሴቶች እግር ኳስ በቂ ትኩረት አልተሰጠም መባሉን አልተቀበሉትም፡፡ በአገሪቱ እግር ኳስ ታሪክ በሀ-20 ደረጃ ብሔራዊ ቡድን ተቋቁሞ እስከ ዓለም ዋንጫ ዋዜማ በማጣሪያ ውድድሮች መጓዝ መቻሉ፤ በሀ-17  በአገር ውስጥ ውድድሮች መካሄዳቸውና በአህጉራዊ ውድድር ተሳትፎ እንዲኖር መደረጉን የጠቀሱት የፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት፤ በዋናው ሴቶች ብሄራዊ ቡድን ደግሞ የዋና እና  ረዳት አሰልጣኞች  ኃላፊነት ላይ ሴቶች መሾማቸው እንዲሁም የደመወዝ መሻሻሎች መደረጋቸው እንደውጤት መታየት አለበት ሲሉ አስተባብለዋል፡፡ ይሁንና ካለፈው ሰሞን አስተዳደራዊ ጥፋት በኋላ ክለቦች በሴቶች እግር ኳስ ለመስራት ያላቸው ፍላጎት መቀነሱ፤ አንዳንድ ክለቦች ከወዲሁ ቡድኖቻቸውን እያፈረሱ መሆናቸውን፤ በጉዳዩ ላይ ጠበጠቅላላ ጉባኤ እንምከርበት የሚሉት ጥያቄዎች በቂ ምላሽ ሳይገኝባቸው  ተድበስብሰዋል፡፡
የእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንት በጋዜጣዊ መግለጫ ላይ አስተዳደራቸው የፈፀመውን ጥፋት በሦስት የተለያዩ ኃላፊዎች ላይ ብቻ በመጫን ለማለፍ መሞከራቸውና በይፋ ይቅርታ እንዲጠይቁ በተደጋጋሚ የቀረበላቸውን ጥያቄ አልወደዱትም፡፡ ፌዴሬሽኑ አስተዳደራዊ ስህተት መሰራቱን በጋራ ጋዜጣዊ መግለጫ ከሰጠበት እና ጥፋት በፈፀሙት ሦስት ኃላፊዎቹ ላይ እርምጃ ከወሰደ በቂ ይሆናል ብለው ተሟግተዋል፡፡
ስልጣኑን በገዛ ፍቃዱ መልቀቅ እንደሌለበት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ባንፀባረቀው አቋም ያረጋገጠው የፌዴሬሽኑ ሥራ አመራር ከክለቦች ጋር በምን አይነት ሁኔታ እንደሚመካከር የወጣቶቹ ሉሲዎች ቡድን እስከ ዓለም ዋንጫ የመጨረሻ ማጣሪያ በመጓዝ ላሳየው ጀግንነት ምን አይነት ማበረታቻና ማፅናኛ ለማድረግ ማሰቡን ሳይገልጽ ነው ያለፈው፡፡ ፕሬዚዳንቱ በተሰጣቸው ኃላፊነት የፌዴሬሽኑ ሥራዎች በትክክል መከናወናቸውን ማረጋገጥ፤ የሥራ አስፈጻሚውን አባላት የማስተባበር የመምራት የመቆጣጠር ድርሻ ቢኖርባቸውም ይህን አለመፈፀማቸው በአንደኛ ደረጃ ተጠያቂ ሆነውበት ከሥልጣን መልቀቅ እንደነበረባቸው የስፖርት ሚዲያው ሊያመለክት ሞክሯል፡፡ ይሁንና ጋዜጣዊ መግለጫውን የሰጠው የፌዴሬሽኑ የሥራ አመራር በአጠቃላይ ያስተዳደር ችግር እንዳለበት ሥልጣን ልቀቁ ከማለት መዋቅሩ የሚስተካከልበትን ሁኔታ መመልከት አለብን በሚለው ማስተባበያቸው አቶ ጁነዲን ባሻ ሌሎቹ የስራ አስፈፃሚ አባላት  መግለጫውን አገባደውታል፡፡

    የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ፣ ከካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ጋር ያለን ልዩነት “ጠባብ ነው” ማለታቸው እያነጋገረ ነው፡፡ፓትርያርኩ ይህን የተናገሩት ባለፈው ሳምንት በዓዲግራት ሀገረ ስብከት ተገኝተው የደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያንን በመረቁበት ወቅት ሲሆን በሥነ ሥርዓቱ ላይ የትግራይ ክልል ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ተስፋ ሥላሴ መገኘታቸውን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ድረ ገጽ ዘግቧል፡፡
ፓትርያርኩ አቡነ ማትያስ፣ “ከካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ጋር  ያለንን ጠባብ የሃይማኖት ልዩነት ጠብቀን፣ በዜግነታችንና በክርስቶስ ልጅነታችን በዋና ዋና የልማት ሥራዎች ዙሪያ በጋራ በመሥራት፣ ለክርስቶስም ለሰው ልጅም ደስታን የሚሰጥ አገልግሎት ማበርከት  ይጠበቅብናል፤” ብለዋል - ድረ ገጹ እንደዘገበው፡፡ይሁንና የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንና የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ያላቸው የእምነትና የሥርዓት አስተምህሮ ልዩነት መሠረታዊ መሆኑን የጠቀሱ አስተያየት ሰጪዎች፣ ፓትርያርኩ ሃይማኖታዊ ልዩነቱ ጠባብ እንደሆነ ተናግረዋል ተብሎ በሰፈረው ዘገባ ግር መሰኘታቸውን ጠቁመዋል፡፡