Administrator

Administrator

 ዶ/ር መሸሻ ሸዋረጋ
(የCCRDA ዋና ዳይሬክተር)
ዓመቱ በግል ህይወቴ የተለየ ነገር ባላይበትም፣ የማማርረው አይደለም፡፡ የምመራው CCRDA የልማት ድርጅቶችን የሚያስተባብር እንደመሆኑ፣ በእቅድ ከያዛቸው አብዛኞቹን አሳክቷል፡፡ ያው እንደሚታወቀው፣ እኛ የበጀት ዓመቱን የምንቆጥረው፣በፈረንጆቹ የዘመን ቀመር ነው፡፡ እስካሁን ባለው የስራ ግምገማ፣ ድርጅቱ ካቀደው 80 በመቶውን አሳክቷል፡፡
በግል ህይወቴ፤ ልጄ የ10ኛ ክፍል ብሄራዊ ፈተና ወስዳ፣ በጥሩ ውጤት ወደ መሰናዶ ልትገባ ነው፡፡ ባለቤቴም በእቅዷ መሰረት ሁለተኛ ዲግሪዋን እየሰራች ነው፤ጥሩ ነው፡፡
 በ2009 የማቅደው ፤ስራዬ ህዝብን ከማገልገል ጋር የተያያዘ ስለሆነ፣ እስከ ዛሬ ከምሰራው በተሻለ ሁኔታ በመስራት የተሻለ ውጤት ማስመዝገብ ነው፡፡ ምኞቴ ደግሞ አገራችን ላይ በተለያዩ አቅጣጫዎች የተነሱት ግጭቶችና አለመግባባቶች ተፈትተው፣ አገራችን ላይ ሰላም  ሰፍኖ ማየት ነው፤ ምክንያቱም ያለ ሰላም ልማት የለም፣ እንደ ልብ ወጥቶ መግባት የለም፡፡ አሁን በአገራችን ያለው ሁኔታ እንደ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ያሰጋኛል፤ ያሳስበኛል፡፡ በአዲስ ዓመት ይሄ ሁሉ ችግር ተቀርፎ፤ ሰው ያለ ስጋት ወጥቶ የሚገባበት አገር እንድትሆን እመኛለሁ፡፡ ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ፤ መልካም አዲስ ዓመት እንዲሆንለት እመኛለሁ፡፡

Sunday, 11 September 2016 00:00

አይጥ በበላ ዳዋ ተመታ!

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አንበሳ እና አንድ ድብ በየፊናቸው ለአደን ወጥው ድንገት መንገድ ላይ የወደቀ ግልገል ያገኛሉ፡፡
አንበሳ፤
“እኔ ነኝ ቀድሜ የደረስኩት፡፡ ስለዚህ ይሄ ግልገል የእኔ ሊሆን ይገባል፡፡” አለ፡፡
ድብ፤
“አንተ ገና መድረስህ ነው፡፡ እኔ ቀደም ብዬ ነው የደረስት፡፡ ስለሆነም ቀድሞ የደረሰ ያገኘውን ዕድል ቀድሞ ይወስዳል” አለ፡፡
አንበሳ፤
“እንደዚህ ልታታልል የፈለግህ ከሆነማ፣ ጉልበት ያለው በኃይሉ የሚወስድበት ሁኔታ ተፈጠረ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ይዋጣልን!” አለ፡፡
ድቡም፤
“በሕግ የማታምን ከሆነ፤ የሚያዋጣው ጉልበት ይሆናል፡፡ እስከ ዛሬ የጫካ ንጉሥ እየተባልክ ስትፈራ፣ ስታስፈራራ፣ ኖረሃል፡፡ አሁን ግን አንድ ግልገል ላይ እንኳ ፍትሐዊ ክፍፍል ለማድረግ በጡንቻ ካልሆነ አይሆንም ስትል እየተሰማህ ነው፡፡ በጡንቻህ ክፉኛ የተማመንክ ይመስለኛል፡፡ ጡንቻ ግን ሁልጊዜ አያበላም፡፡ በል እንጋጠምና ይለይልን፡፡ ፍርሃት ዱሮ ቀረ!” አለው፡፡
አንበሳው አመነታ፡፡ ከድብ ጋር ትግል ገጥሞ አያውቅም፡፡ አሁንም ማስፈራራቱን መቀጠል ያዋጣኛል ብሎ፣
 “ህይወትህን አትፈልገውም እንዴ?” ሲል ጠየቀው፡፡
ድቡም፤
“ህይወት የሚያስፈልግህ ማንንም ሳትፈራ በነፃነት የምትኖርበት ከሆነ ነው፡፡ ስለዚህ ተዋጥቶልን ዕውነተኛው ኃይለኛ ሊለይ ይገባል!” አለ ፍርጥም ብሎ፡፡
 አንበሳ፤ድቡ እንዳልፈራው ገባውና፡፡ ወደ ትግሉ የግዱን ገባ፡፡ ተናነቁ፡፡ ተያያዙ፡፡ ትግሉ ቀጠለ፡፡ አንዴ አንበሳ ከላይ ሲሆን፤ ሌላ ጊዜ ድቡ አንበሳን ገልብጦ ከላይ ሲሆን፤ ሲገለባበጡ ብዙ ሰዓት አለፈ፡፡ ሆኖም አልተሸናነፉም፡፡ አልለየላቸውም፡፡ ቀስ በቀስ ግን አቅማቸው እየደከመ ሄደ፡፡ ምንም መታገል የማይችሉበት ደረጃ ደረሱ፡፡ ክንዳቸው ዛለ፡፡ ጉልበታቸው ላመ፡፡ መታገሉን ትተው ተኙ፡፡
ይህ ሁሉ ሲሆን ዳር ሆኖ ያስተውል የነበረ ቀበሮ፤ የሁለቱንም አቅል አልባ መሆን ተገንዝቦ ግልገሏን ይዞ መጭ አለ፡፡
ሁለቱም ዐይናቸው እያየ የቋመጡላትን ግልገል አጡ፡፡
ድቡም፤
“አየህ አያ አንበሳ፤ ግባችንን ልናሳካ እንችል የነበረው በእኩልነት ብናምንም፣ስለ ጡንቻችን ባናስብ ነበረ፡፡ ይሄው ውጤቱና ጥቅሙ ዳር ቆሞ ላስተዋለን ቀበሮ ሆነ!” አለው፡፡
*        *      *
በጡንቻ መተማመን በታሪክ እንዳላዋጣ ሁሉ፤ ዛሬም አያዋጣም፡፡ ውሎ አድሮ የድካም ጊዜ መምጣቱን ፈላስፎች ይናገራሉ፡፡ The endpoint is fatigue ይሉታል፡፡ የአሜሪካ የጦር ጠበብት፤የኢትዮጵያና የኤርትራ ጦርነት ሁለቱም ወገኖች ሲደክማቸው ይፈፀማል አሉ ይባላል፡፡
ገጣሚ ደበበ ሰይፉ፤ እራሴን በላሁት በሚለው ግጥሙ፣ በስብሰባ ብዛት ሰውነቱ ዝሎ፣ ተቆራርጦ ያለቀን ሰው ነው ያመላከተው (Symbolize) ስብሰባዎች ልባዊ ከሆኑ ራስን ለማየት ጠቃሚ ይሆናሉ፡፡ ራስን መገምገምና ራስን ወደ ውስጥ ማየት፣ትክክለኛ መፍትሄ ለመሻት ዓይነተኛ ዘዴ ነው፡፡ ሆኖም ህዝብን በሚያሳምን መንገድ ከሆነ ነው፡፡ በአሁኑ ሰዓት መንግሥት ራሱን መፈተሹ አስፈላጊ ብቻ ሳይሆን ግዴታም ጭምር ሆኗል፡፡ ህሊናዊና ነባራዊ ሁኔታዎች ተመቻችተዋል ይላል፤የዱሮው ፖለቲከኛ ቭላዲሚር ሌኒን፡፡ ሁለት እርምጃ ወደ ፊት፣ አንድ እርምጃ ወደ ኋላም መባሉን አንዘንጋ፡፡ ወፎች በጮሁ ዛፉ አይነቃነቅም፤ የሚለውንም የቻይናዎች ተረት ልብ እንላለን፡፡ “ግመሎች ይሄዳሉ ውሾቹ ይጮሃሉም›› ስንባል ኖረናል፡፡ ‹‹በኢህአዴግ ካመነ ዘበኛም ሚኒስትር ይሆናል›› ከሚለው ብሂል ተነስተን፣ሚኒስትር ለመሆን ኢህአዴግ መሆን አያስፈልግም የሚል እሳቤ ጋ መድረስ አንድ መልካም ምሥራች ነው! ምናልባትም የተራንስፎርሜሽን ምልክት ነው!
‹‹ራሳችንን እንፈትሽ!›› በተግባር እንዲታይ ከፈለግን፣አስፈታሽ ያስፈልገናል፡፡ ‹‹አገር ሁሉ ኪራይ ሰብሳቢ ነው›› ካልን እንግሊዞች እንደሚሉት፤ Who guards the guards ጋ ልንደርስ ነው፡፡ ጠባቂዎቹን ማን ይጠብቃቸዋል እንደ ማለት ነው፡፡ ‹‹በስብሰናል፤ ተቸክለናል!›› የሚል ሰው መጥፋቱ አንዱ መሠረታዊ ችግራችን ነው፡፡
‹‹አለ አንዳንድ ነገር
በዚህ ቢሉት በዚያ፣ ከመሆን የማይቀር”
--- ይሉናል ከበደ ሚካኤል፡፡ የማይቀረውን እንቀበለው እንደማለት ነው፡፡
‹‹አይደለም እንዴ?
ዋሸሁ እንዴ?!››
ብለን እንደ ዘፋኙ የማናልፋቸው አያሌ አጀንዳዎች አሉን፡፡ ከዋሸን ዋሽተናል፡፡ ካጠፋን አጥፍተናል-ተጠያቂዎች ነን!! ‹‹ኤጭ አይባል የአገር ጉዳይ!›› ይለናል፤ፀጋዬ ገብረመድህን፡፡ የአገር ጉዳይ መሸዋወጃ መድረክ አይሆንም! አንድ አንደበተ- ርቱዕ ሰው፤‹‹መንግሥት ተቃዋሚዎችን በገንዘብ ልግዛ ቢልም የማይችልበት ደረጃ ደርሷል›› አሉ ይባላል፡፡ ያለ ተቃዋሚ ኃይል እኛ የለንም፤ሲባል የነበረውን ልብ ይሏል!
ዛሬ አገራችን መጠንቀቅ ያለባት ብርቱ ጉዳይ፤አንዱ ባጠፋ ሌላው እንዳይመታ ማስተዋል ነው፡፡ ይሄ ክልል ለሌላ ክልል ተጠያቂነት ሰበብ መሆን የለበትም! ‹‹በእነሞር ዳፋ ቸሃ ተደፋ›› የሚለው አስተሳሰብ መወገዝ አለበት፡፡ ‹‹አይጥ በበላ ዳዋ ተመታ››ን ከልብ ካጤንነው መፍትሔያችንም ፍትሐዊ የመሆን ዕድሉ የሰፋ ይሆናል፡፡ አዲሱ ዓመት ይሄን ዕድል ያጎናፅፈን ዘንድ እንፀልይ! የመጨረሻውን የ2008 ቅዳሜ ዛሬ እንሰናበተው!
መልካም አዲስ ዓመት!!
አዲሱ ዘመን፤
አዲስ ስርዓት፤ አዲስ ራዕይ ያሳየን!!

“ግጭቱ ይበርዳል፤ ያልፋል የሚል ተስፋ አለኝ”
የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፣እንደ ወትሮው ሁሉ በወቅታዊ የአገሪቱ ችግሮችና መፍትሄው ዙሪያ አንጋፋ ፖለቲከኞችን፣ ምሁራንን፣የሃይማኖት መሪዎችንና የአገር ሽማግሌዎችን አነጋግሯል፡፡ የውይይት መድረኩ ዓላማ፣በወቅታዊ የፖለቲካ ችግሮች ዙሪያ ሃሳቦችን በማንሸራሸር መፍትሄ ማፈላለግና መጠቆም ነው፡፡ እግረ-መንገዱንም እርስበርስ እንድንማማር ዕድል ይሰጠናል፡፡ በአገራችን ለተከሰተው ወቅታዊ የፖለቲካ ቀውስ ሁነኛ መፍትሄ አለን የምትሉ፣ሃሳባችሁን በጽሁፍ
(ኢሜይል)፣በስልክ ወይም በአካል (ቢሮ) ብታደርሱን ለማስተናገድ ዝግጁ ነን፡፡

ግርማ ወ/ጊዮርጊስ (የቀድሞ ፕሬዚዳንት)
ወጣቶች ንብረት ማቃጠላቸው በጣም መጥፎ ነገር ነው፡፡ በሚዲያ ሲነገር እንደሰማሁት፤ መንግስት ያሉበትን ችግሮች አርሞ፣ለውጥ ለማድረግ እየጣረ መሆኑን አስታውቋል፡፡
ከዚህ አንፃር ጥያቄዎች መልስ አግኝተው ግጭቱ ይበርዳል፤ያልፋል የሚል ሀሳብ ነው ያለኝ፡፡ መካሪ የማጣትም ሊሆን ይችላል፡፡ በመሸበርና በማሸበር ውስጥ ብዙ ጥቅም የለም፡፡ ጥቅም የሚኖረው ሁሉም ነገር በሰላም ሲሆን ብቻ ነው፡፡ ወጣቶቹ ይሄን ነገር ለማድረግ ያሰቡበትን ከጀርባ ያለ ምክንያት አናውቅም፡፡ ብናውቅም የምናየው ነገር ደስ አይልም፡፡ ስለዚህ እነዚህ ወጣቶች ተመክረው ወደየትምህርት ቤታቸው ይመለሳሉ፤ወደየስራቸው ይሄዳሉ የሚል እምነት አለኝ፡፡
መንግስት የሚችለውን ሁሉ እያደረገ ይመስለኛል፡፡ ጠ/ሚ ኃይለማሪያም፤ወጣቱን ሰብስበው አነጋግረዋል፡፡ ነገሮችን በጉልበት ከማድረግና በመግደል ከመመለስ፣በማስተማር ማስታገስና መመለሱ ነው የሚሻለው፡፡
ለመንግስትም ጥሩ የሚሆነው ይህ ነው፡፡ የሚገርመው የኢትዮጵያ ህዝብ በፈጣን የእድገት ደረጃ ላይ ነው ያለው፡፡ 35 ዩኒቨርሲቲ የተመሰረተበትና ድንቁርና እየጠፋ ስልጣኔ የመጣበት ጊዜ ነው፡፡ ድህነትም እንዲህ የሚጠፋ ይሆናል፤ እየጠፋም ነው፡፡ ወጣቶች አንዳንድ አነቃናቂ አግኝተው፣የሚያስቸግሩትን ሃሳብ ማስለወጥና በጥሩ መንገድ እንዲሄዱ ማድረግ ከተቻለ አዲሱ ዓመት ጥሩ ይሆናል፡፡

===================================

“ማንኛውም አለመግባባት በውይይት መፈታት አለበት”

ብጹዕ ካርዲናል ብርሃነየሱስ (የኢትዮጵያ ካቶሊካዊያን ጳጳሳት ጉባዔ ፕሬዚደንት)

ባሳለፍነው ዓመት በአገራችን አንዳንድ ቦታዎች የታዩ ውስጣዊ ግጭቶች እንደነበሩ ይታወቃል፡፡ ሆኖም እነዚህ ሁኔታዎች ጥፋትና የማህበረሰብ ስሜት ማፋለስ እንዳያስከትሉብን፣ በሰከነ መንፈስ ነገሮች የሚፈቱበት መንገድ እንዲደረግ፣ ቤተክርስቲያን አጥብቃ ትማጸናለች፡፡ ቤተክርስቲያን በሰው ህይወትና በአገር ንብረት ላይ በደረሰው ጥፋት በጣም ታዝናለች፡፡
መንግስት ባለበት የማስተዳደር ኃላፊነት፣ መሰረቱን የጠበቀ ማህበረሰብ ለመፍጠር በጋራ በመወያየት፣ የግንዛቤ ትምህርቶች በመስጠት፣በጥበብና በማስተዋል በዚህ አዲስ አመት ተግቶ እንዲሰራ፣የአገሪቱንም እድገትና ደህንነት እንዲያስጠብቅ አደራ ትላለች፡፡ ሁላችንም እንደየእምነታችን ክፉውን ከምንወዳት አገራችን እንዲያርቅልን በጸሎት እንትጋ፡፡ መላው የአገራችን ሕዝቦች፤በመካከላችን የሚነሳውን ማንኛውንም አለመግባባት በሰከነ መንፈስ፣ በውይይት የመፍታት ባህል እንዲያዳብሩ፣ በታላቅ በአክብሮት እንጠይቃለን፡፡


================================================

‹‹ኢህአዴግ ብቻውን የችግሩ መፍትሄ ሊሆን አይችልም››

አቶ ገብሩ አስራት
(የቀድሞ አንጋፋ ታጋይ)
የአሁኑ ተቃውሞና ግጭት ባህሪ መንግስት እንደሚለው፣በመልካም አስተዳደር እጦት ብቻ የመጣ አይደለም፡፡ መልካም አስተዳደር ከሃገራችን በርካታ ችግሮች አንዱ ነው፡፡ የተቃውሞ  መነሻ ግን በሰልፎችም ላይ እንደተንጸባረቀው፤የነፃነት፣ የፍትና፣ የዲሞክራሲ እጦት ነው፡፡ ከዚያም ሲያልፍ የኢኮኖሚ ፍትሃዊ ተጠቃሚነትና የመሬት ዘረፋና የሃብት ክፍፍል፣ የወጣቱ ስራ አጥ መሆን ተደማምሮ ያስነሣው ነው፡፡ ባለፈው አመት የተደረገው ምርጫም የውሸት እንደነበር ያመለክት ነው፡፡ ህዝቡ በግልፅ ነግሮአቸዋል፡፡ እኛ አልመረጥናችሁም፣ በማስፈራራት የተደረገ ምርጫ ነው ብሏቸዋል፡፡
በአጠቃላይ በሃገራችን ያለው ፖለቲካ ከመሠረቱ ኢህአዴግ በሚከተለው አቅጣጫ የተሳሳተ ሲሆን ዲሞክራሲን የሚያፍን፤ ያፀደቀውን ህገ መንግስት እንኳ ሳይቀር የማያከብር፣ የህግ የበላይነት፣ ነፃነት፣ ፍትህ የሌለበት ሃገር መሆኑ ነው መነሻው። ዴሞክራሲና ነፃነት በሌለበት፤ ሚዲያዎች፣ ተቃዋሚ ፓርቲዎች፣ የሲቪክ ማህበራት በነፃነት ተንቀሣቅሰው፣የህዝብ ድምፅ መሆን አይችሉም፡፡ ይህ የተጠራቀመ ብሶትን ይወልዳል፡፡ እነዚህ በነፃነት ተደራጅተው ሚዛኑን ሲጠብቁ እንጂ “እኔ ብቻ ነኝ የማውቅልህ” የሚል መንግስት ባለበት፤ሙስና፣ ብልሹ አስተዳደር የሚባሉት መፈጠራቸው አይቀርም፡፡
ኢህአዴግ ላለፉት 25 ዓመታት በራሱ ፍላጎትና መንገድ ብቻ የሚንቀሳቀስ እንጂ በሀገሪቱ ያሉ ባለድርሻዎችን ይዞ መንቀሳቀስ የሚችል ፓርቲ አለመሆኑን አሳይቷል፡፡ እንደ እኔ፤ችግር ፈጣሪው መልሶ ራሱ፣ የችግሩ መፍትሄ ሊሆን አይችልም። ኢህአዴግ፤ የአገር ሽማግሌዎችን፣ ተቃዋሚዎችንና ባለድርሻዎችን ሳያካትት እታደሳለሁ ቢል ጭራሽ የሚሆን አይደለም። መፍትሄም አያመጣም፡፡ እንደውም ዋና የመፍትሄ አቅጣጫ ያደረጉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወጥተው ለፀጥታ ኃይሎች የሰጡት ስልጣን ነው፡፡ በግልፅ ያልታወጀ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ነው ያወጁት፡፡ ለችግሮች ፖለቲካዊ መፍትሄ ከመሻት ይልቅ በኃይል ለመፍታት የተዘጋጁበት ሁኔታ ታይቷል፡፡
በሀገራችን በኃይል የሚመጣ መፍትሄ እንደሌለ ብዙ ጊዜ ተሞክሮ ተረጋግጧል፡፡ በግጭቶች በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ሞተው፣መንግስት ኃላፊነት ተሰምቶት ለማጣራት እንኳ አልፈለገም፡፡ ይሄን ሁሉ ገድሎና አስሮ የመፍትሄው ባለቤት ነን ማለት አያስኬድም፡፡ አሁን እየተሄደበት ያለው አቅጣጫ ችግሩን እንደሚፈታም አያመላክትም፡፡ የሚሰጡት ማብራሪያም ሆነ መግለጫ የሚታወቀውን ከመድገም በስተቀር አዲስ ነገር የለውም። ለችግሩ ምክንያት የሆኑት ራሳቸው ሆነው በኢህአዴግ የፖለቲካ ተቋም እንፈታዋለን ማለታቸው የማይሞከር ነው፡፡ በዚህች ሀገር ያገባናል የሚሉ በውጭም በሀገር ውስጥም ያሉ አካላት በመወያየት መፍትሄ እስካላመጡ ድረስ አሁን ኢህአዴግ በሚለው መንገድ የችግሩን 1 በመቶ እንኳ መፍታት አይቻልም፡፡  
እኔ እንደ ፖለቲከኛ መፍትሄው በአንድ ፓርቲ እጅ ብቻ አይደለም እላለሁ፡፡ በዚህች ሀገር የአስተሳሰብ ብዝሃነት አለ፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎች በዚያው ልክ አሉ። ስለዚህ አንድ ገዥ ፓርቲ የፖለቲካ መፍትሄ ይሰጣል የሚል እምነት የለኝም፡፡ መፍትሄው መነጋገር ነው። ለተነሱት ጥያቄዎች መልስ መስጠት ብቻ ሳይሆን ከሁሉም ባለድርሻዎች ጋር ቁጭ ብሎ መወያየት ያስፈልጋል፡፡ የችግሩ ምንጭ የሆነው ፓርቲ ብቻውን መፍትሄ ማምጣት አይችልም፡፡ ስለዚህ ህዝቡ እያቀረበ ያለውን ችግር ረጋ ብሎ አይቶ፣ የአጭር ጊዜና የረጅም ጊዜ መፍትሄ ማስቀመጥ ያስፈልጋል፡፡ ለአጭር ጊዜ መፍትሄ ግድያ ማቆም፣ የታሰሩ ፖለቲከኞችን መፍታት፣ ለተጎዱት ካሳ መስጠት ይሄ የአቭር ጊዜ መፍትሄ ነው፡፡ በረጅም ጊዜ መፍሄት ግን ዲሞክራሲ፣ ፍትህ የሚነግስበት ስርአት መቋቋም አለበት፡፡ የአጭር ጊዜውን መፍትሄ እየተገበሩ ዘላቂው መፍትሄ የሚመጣበትን ሁኔታ መፍጠር አለብን።  
 ===================================

‹‹መንግስት የሌሎችን ሀሳብ መስማት አለበት››
ጠበቃ አመሀ መኮንን

በ2008 ዓ.ም በኑሮዬና በግሌ ብዙ የማማርርበት ነገር አልገጠመኝም፤እንደ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ራሴን ካለኝ ሁኔታ ጋር አጣጥሜ ለመኖር ሞክሬያለሁ፡፡ ነገር ግን በስራዬ በኩል ዓመቱ በጣም የፈተና ነበር ማለት እችላለሁ፡፡ ከስራዬ ጋር በተያያዘ ደግሞ በቀጥታ እኔ ከያዝኳቸው ጉዳዮች ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ ከአገሪቱ የሰብአዊ መብት አያያዝ፣ ከማረሚያ ቤት የእስረኞች አያያዝና ተያያዥ ጉዳዮች አንፃር አመቱን ስመለከተው፣ እጅግ በጣም አስቸጋሪ ጊዜ ነበር፡፡ በተለይ ሁላችንንም የሚያግባባን፣ቀደም ብሎ በኦሮሚያ ከዚያም በአማራ ክልል ለተነሱት የመብት ጥያቄዎች መንግስት ምላሽ የሰጠበት መንገድ በጣም አሳሳቢ መሆኑ ነው፡፡ በተለይ የፀጥታ ሀይሉ ንፁሀን ላይ ጥይት የመተኮስና መግደል ጉዳይ፣ መንግስት የመጨረሻ ሳይሆን የመጀመሪያ አማራጭ አድርጎ መውሰዱ በጣም ይረብሻል፡፡ አዲሱ አመት መግቢያ ላይ ቆመን ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት የደረሰው አሰቃቂ አደጋና እየተሰማ ያለው ነገር ዓመቱን ሲበዛ ፈታኝ ያደርገዋል። በአጠቃላይ ከሙያዬና ከስራዬ አንፃር 2008 እጅግ የፈተና ዓመት ነው፡፡
በአዲሱ ዓመት እንደ ሰው ተስፋ አድርጋለሁ፡፡ በመንግስት በኩል፤ የሌሎችን ሀሳብ ለመስማት ዝግጁ እንዲሆን እመኛለሁ፡፡ ከመንግስት የተለየ ሀሳብ ያላቸውን እንደ 2008ቱ፣በሀይል ሳይሆን በውይይት የሚፈታበት እድል እንደሚኖር ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ይሄ እንግዲህ ተስፋ ነው፡፡ የህዝቡን ጥያቄ በተመለከተ መንግስት እድገቱ የፈጠረው ነው፤የሚል አከራካሪ ምላሽ እየሰጠ ነው። የሚገርመው አሁን ምላሽ እየተሰጠ ያለበት መንገድ፤ ከ25 ዓመት በፊት ምላሽ ሲሰጥ የነበረበት መንገድ ነው፡፡ የህዝብ ጥያቄ በየጊዜው እንደሚነሳ እየታመነ፣ ለጥያቄው ተመጣጣኝ የሆነ ወቅታዊ ምላሽ መዘጋጀት ነበረበት፡፡ ይህን ግን እያየን አይደለም፡፡ በአዲስ ዓመት የፀጥታ ሀይሉ ንፁሀን ላይ መተኮስን መደበኛ ስራ አድርጎ የማይቀጥልበት እንደሚሆን በጥብቅ እመኛለሁ። የህዝብን ጥያቄ መንግስት በአግባቡ መመለስ አለበት። እንግዲህ ሰው ነኝና፣ምኞትና ተስፋ ነው፡፡ ለሁሉም መልካም አዲስ አመት እመኛለሁ!!

- የሞቱ ዜጎች ጉዳይ በገለልተኛ አካል ይጣራ፤ የመብት ጥሰቶችን የፈጸሙ በህግ ይጠየቁ ብለዋል

   የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በቅርቡ በአማራና ኦሮምያ ክልሎች ከተቀሰቀሱ ተቃውሞዎች ጋር በተያያዘ የታሰሩ ዜጎችን ያለምንም ቅድመ ሁኔታ በአፋጣኝ እንዲፈታ በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ግፊት እንዲያደርግ በሰብዓዊ መብቶች ዙሪያ የሚሰሩ 15 የተለያዩ ታዋቂ አለማቀፍ እና ብሄራዊ ተቋማት ጠየቁ፡፡
ተቋማቱ ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት በላኩት የጋራ ደብዳቤ፣ ምክር ቤቱ በቀጣዩ ሳምንት በሚያካሂደው አመታዊ ጉባኤው በኢትዮጵያ እየተባባሰ የመጣውን የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ቀዳሚ አጀንዳው እንዲያደርግና ጉዳዩን በተመለከተ መግለጫ እንዲያወጣ ጠይቀዋል፡፡
መንግስት ከተቃውሞው ጋር በተያያዘ የታሰሩ ጋዜጠኞች፣ የሰብዓዊ መብቶች ተከራካሪዎች፣ የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮችና አባላትና ተቃዋሚዎችን ያለምንም ቅድመ ሁኔ በአፋጣኝ እንዲፈታ እንዲሁም የጸጥታ ሃይሎች በሁለቱም ክልሎች ሆነ በሌሎች የአገሪቱ አካባቢዎች በተቃዋሚዎች ላይ ያልተመጣጠነና ተገቢ ያልሆነ የሃይል ጥቃት መፈጸማቸውን እንዲያስቆም ግፊት እንዲያደርግም ምክር ቤቱን ጠይቀዋል፡፡
መንግስት ከተቃውሞው ጋር በተያያዘ የተገደሉና የሰባዓዊ መብቶች ጥሰቶች የደረሱባቸው ዜጎች ጉዳይ በአለማቀፍ ገለልተኛ ተቋማት እንዲጣራ እንዲፈቅድ፣ የመብት ጥሰቶችን የፈጸሙ አካላት በህግ እንዲጠየቁ እንዲያደርግና ህገ መንግስቱን፣ አለማቀፋዊና አህጉራዊ የሰብዓዊና የፖለቲካዊ መብቶች ህግጋትና ስምምነቶችን እንዲያከብር ለማስቻል ምክር ቤቱ ጫና እንዲያሳድርም ጠይቀዋል፡፡
ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት ከትናንት በስቲያ የጋራ ጥያቄያቸውን ካቀረቡት ከእነዚህ 15 ተቋማት መካከል፣ አምነስቲ ኢንተርናሽናል፣ ፍሪደም ሃውስ፣ ሂውማን ራይትስ ዎች፣ ሪፖርተርስ ዊዛውት ቦርደርስና ወርልድ ኦርጋናይዜሽን አጌንስት ቶርቸር ይገኙበታል፡፡




- ፕሬዚዳንቱ ቡድኑን ለመደምሰስ ያቀዱት ከ8 ወራት በፊት ነበር

    የናይጄሪያ የጦር ሃይል ከፍተኛ መሪ ሜጀር ጄኔራል ላኪ ኢራቦር፣ ጦራቸው በአገሪቱ ሰሜን ምስራቃዊ አካባቢዎች የሚገኙትንና በአሸባሪው ቡድን ቦኮ ሃራም የተያዙትን ጠንካራ ይዞታዎች በቁጥጥር ስር በማዋል ቡድኑን በሳምንታት ጊዜ ውስጥ ሙሉ ለሙሉ እንደሚደመስስ ማስታወቃቸውን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
ላለፉት ሰባት አመታት በአገሪቱ የከፉ የሽብር ጥቃቶችን ሲፈጽምና ልጃገረዶችን ሲጠልፍ የቆየውን ቦኮ ሃራም፣ ሙሉ ለሙሉ የመደምሰስ ግብ ይዞ የሚንቀሳቀሰውን ጦር የሚመሩት ሜጀር ጄኔራል ላኪ ኢራቦር ባለፈው ረቡዕ በሰጡት መግለጫ፣ቡድኑ በሳምንታት ጊዜ ውስጥ ሙሉ ለሙሉ ይደመሰሳል ብለዋል፡፡ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ሙሃሙድ ቡሃሪ እስካለፈው ታህሳስ ወር ቦኮ ሃራምን እንዲደመስስ ለጦር ሃይላቸው ያስቀመጡት ቀነ ገደብ ካለፈ 8 ወራት መቆጠራቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤የጦሩ መሪ ሜጀር ጄኔራል ላኪ ኢራቦር በሰጡት መግለጫ፣ ቦኮ ሃራምን ለመደምሰስ የቀረው የሳምንታት ጊዜ ብቻ እንደሆነ በእርግጠኝነት ተናግረዋል፡፡
የሽብር ቡድኑ በአሁኑ ወቅት ሶስት ያህል ጠንካራ ይዞታዎችን በቁጥጥር ስር አድርጎ እንደሚገኝ የገለጹት ላኪ ኢራቦር፣ የጦር ሃይላቸው በሚወስደው የማያዳግም እርምጃ ቡድኑ ሙሉ ለሙሉ እንደሚደመሰስ ገልጸው፣ በሽብር ቡድኑ ላይ የሚፈጸመው ጥቃት ከአጎራባች አገራት የጦር ሃይሎች ጋር በተቀናጀ መልኩ እንደሚከናወን አስታውቀዋል፡፡
ቦኮ ሃራም እ.ኤ.አ ከ2009 አንስቶ በናይጀሪያ፣ ቻድ፣ ኒጀርና ካሜሩን በፈጸማቸው አሰቃቂ የሽብር ጥቃቶች ሳቢያ ከ15 ሺህ በላይ ሰዎች መገደላቸውንና 2.3 ሚሊዮን ያህል የአገራቱ ዜጎች እንደተፈናቀሉም ዘገባው አክሎ አስታውሷል፡፡

ታዋቂው የቴክኖሎጂ ምርቶች አምራች ኩባንያ አፕል፤ በአየርላንድ በሚያደርገው የንግድ እንቅስቃሴ በህገ-ወጥ መንገድ ሳይከፍለው የቀረውን የ14.5 ቢ ዶላር የግብር ዕዳ እንዲከፍል በአውሮፓ ህብረት አጣሪ ቡድን እንደተወሰነበት ስካይ ኒውስ ዘገበ፡፡
ህብረቱ ለ3 አመታት ከዘለቀ ምርመራ በኋላ በኩባንያው ላይ ይህንን ክብረ ወሰን ያስመዘገበ የተባለ የግብር ቅጣት የጣለው አየርላንድ ለኩባንያው ያልተገባ የግብር ጥቅማ ጥቅሞችን በህገ ወጥ መንገድ መስጠቷን በማረጋገጡ ነው ተብሏል። አፕልና የአየርላንድ መንግስት ህብረቱ ያሳለፈውን ውሳኔ በመቃወም ይግባኝ እንደሚጠይቁ የገለጹ ሲሆን፣ ውሳኔው የኩባንያዎቼን ስኬት ለማደናቀፍ እየሰራ ነው ስትል ህብረቱን ስትከስ የቆየቺውን አሜሪካን ክፉኛ ያስቆጣል ብሏል - ዘገባው፡፡
 አየርላንድ የአሜሪካ ኩባንያዎች በስፋት ተሰማርተው ትርፋማ ለመሆን የሚያስችል ስራ እንዲሰሩ የከፈተቺው እድል ለውዝግቡ መነሻ እንደሆነ ዘገባው አስታውሷል፡፡


                       - ከአልባግዳዲ ቀጥሎ የቡድኑ ሁለተኛው ቁልፍ ሰው ነበር
      የሽብርተኛው ቡድን አይሲስ ቃል አቀባይ በመሆን ሲሰራ የቆየውና በቡድኑ የአስተዳደር መዋቅር ሁለተኛው ቁልፍ ሰው እንደሆነ የሚነገርለት አቡ ሞሃመድ አል አድናኒ፤ ሶርያ ውስጥ መገደሉን ቡድኑ ባለፈው ማክሰኞ ባወጣው መግለጫ አስታወቀ፡፡
አይሲስ ግድያውን በተመለከተ ባወጣው መግለጫ፣ አል አድናኒ ሶርያ ውስጥ በምትገኘው አሌፖ አካባቢ የሚካሄዱ ወታደራዊ እንቅስቃሴዎችን በሚቆጣጠርበት ወቅት ለህልፈት መዳረጉን ይግለጽ እንጂ፣ የሞቱን ሰበብ በተመለከተ በይፋ ያለው ነገር እንደሌለ ሲኤንኤን ዘግቧል፡፡ የሽብር ቡድኑ የአል አድናኒን የሞት መንስኤ ባይናገርም፣ የከፍተኛ አመራሩን ሞት ለመበቀል ቁርጠኛ አቋም መያዙን እንዳስታወቀ የጠቆመው ዘገባው፤ የአሜሪካ የመከላከያ ሚኒስቴር አንድ ከፍተኛ ባለስልጣን፣አል አድናኒ በአልባብ ከተማ በተፈጸመበት የአየር ላይ ጥቃት መገደሉን ባለፈው ረቡዕ ማስታወቃቸውን ጠቅሷል፡፡
አል አድናኒ በሽብር ቡድኑ ታሪክ የተገደለ ከፍተኛው ባለስልጣን ነው ያለው ዘገባው፤ግለሰቡ የአይሲስ መሪ የሆነውን አቡበከር አልባግዳዲን ይተካል ተብሎ የሚጠበቅ ቁልፍ ሰው እንደነበር ጠቁሟል፡፡ ሟቹ የአይሲስ ቀንደኛ መሪ አል አድናኒ፤ የሽብር ቡድኑ አጠቃላይ እንቅስቃሴ መሃንዲስ እንደነበር የጠቆመው ዘገባው፤ከቡድኑ መሪ አቡበከር አል ባግዳዲ ያልተናነሰ ቁልፍ ሚና ሲጫወት እንደነበርና ቡድኑን ለመደምሰስ በተደረጉ ዘመቻዎች በተሳተፉ የተለያዩ አገራት ላይ ጥቃት እንዲፈጸም ትዕዛዝ ያስተላለፈውም እሱ እንደነበር ገልጧል፡፡
እ.ኤ.አ በ1977 ሶርያ ውስጥ የተወለደው አቡ ሞሃመድ አል አድናኒ፣ የሽብር ቡድኑ ከቡድንነት አልፎ ራሱን የቻለ እስላማዊ  መንግስት አቋቁሞ የመምራት አላማ ይዞ እንደሚንቀሳቀስ በይፋ ያስታወቀ የመጀመሪያው ሰው እንደሆነም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

የሰሜን ኮርያ መንግስት፤ ከአገሪቱ ከፍተኛ ሚኒስትሮች አንዱ የነበሩትንና  በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የትምህርት ዘርፍ ሃላፊ ሆነው ሲሰሩ የቆዩትን ኪም ዩንግ ጂንን፣ባለፈው ወር ገድሏል ስትል ደቡብ ኮርያ መናገሯን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ሚኒስትሩ ባለፈው የካቲት ወር ላይም ተገድለዋል ተብሎ ተወርቶ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፤ይሄም ሆኖ ግን ከቀናት በኋላ በፓርቲው ምክር ቤት ስብሰባ ላይ ሲካፈሉ መታየታቸውን ጠቁሞ ይሄኛው የደቡብ ኮርያ መረጃም አጠራጣሪ ሊሆን እንደሚችል ገልጧል፡፡
ሰሜን ኮርያ ተገደሉ የተባሉትን ሚኒስትር በተመለከተ እስካሁን ያለቺው ነገር እንደሌለ የጠቆመው ዘገባው፣ የአገሪቱ መንግስት በቅርቡ የሚኒስትሩን ቦታ ተክቶ የሚሰራ ሌላ ሚኒስትር ከሾመ የመሞታቸው ነገር እርግጥ ሊሆን ይችላል መባሉን አመልክቷል፡፡
የሰሜን ኮርያ መንግስት ከዚህ ቀደምም ከፍተኛ ባለስልጣናቱንና ሚኒስትሮችን በድብቅና በይፋ በወሰዳቸው እርምጃዎች መግደሉን ዘገባው አስታውሷል፡፡

 ታዋቂው የማህበራዊ ድረገጽ ትዊተር ባለፈው አመት ብቻ ሽብርተኝነትን የሚያስፋፉ መልዕክቶችን አሰራጭተዋል ያላቸውን የ360 ሺህ የትዊተር ተጠቃሚዎች አካውንቶችን በመዝጋት ከአገልግሎት ውጭ ማድረጉን ስካይ ኒውስ ዘገበ፡፡ እነዚሁ አካውንቶች ሽብርተኝነትን የሚያስፋፉ መልዕክቶችን በማስተላለፍና ግለሰቦችን በማስፈራራት ተግባር ላይ ተሰማርተው በመገኘታቸው እንዲዘጉ መደረጉን ያስታወቀው ኩባንያው፤ከእነዚህም መካከል 235 ሺህ የሚሆኑት ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ እንደተዘጉ ገልጧል፡፡
ተቀማጭነቱን በሳን ፍራንሲስኮ ያደረገው ትዊተር የሚተዳደርበት ፖሊሲ፣ ሽብርተኝነትን ማስፋፋትን እንደማይፈቅድ ገልጾ፣ በቀጣይም በተመሳሳይ ህገወጥ ተግባራት ላይ የተሰማሩ ተጠቃሚዎቹን እየተከታተለ አካውንታቸውን እንደሚዘጋ አስታውቋል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ቀበሮ ጉሮሮው ውስጥ አጥን ተቀርቅሮበት በጣም ሲሰቃይ ዋለ፡፡ ወደማታ ላይ አንዲት ረዝም ኩምቢ ያላት ወፍ አገኘና እንዲህ አላት፡-
“ወፊት ሆይ”
“አቤት” አለች ባለ ኩምቢዋ ወፍ፡፡
“አንድ ነገር ልለምንሽ?”
“የምችለው ከሆነ ምን ቸገረኝ”
“የምትችይው ነገር ነው፡፡ በዚያ ላይ ለውለታሽ ዋጋሽን እከፍላለሁ”
“ምን ትከፍለኛለህ?”
“የፈለግሺውን፡፡ ብቻ ከአቅሜ በላይ አይሁን”
“እሺ፡፡ እንግዲያው እኔን የሚያሳድዱኝ ጠላቶች አሉኝ፡፡ እነሱን አሳደህ ታጠቃልኛለህ?”
“ይሄማ በጣም ቀላል ነው፡፡ ብቻ አንቺ የምጠይቅሽን ፈፅሚልኝ”
“ምንድን ነው እንዳረግልህ የፈለግኸው?” ብላ ጠየቀችው፡፡
“ጉሮሮዬ ውስጥ አጥንት ተቀርቅሮ እያሰቃየኝ ነው፡፡ ስለዚህ ኩምቢሽን አፌ ውስጥ አስገብተሸ እንደ ምንም ብለሽ አውጪልኝ” አላት፡፡
“ይሄ ለእኔ ቀላል ነው፡፡ ፊትህን ወደ ብርሃን መልስና አፍህን በደምብ ክፈተው” አለችው፡፡
ወፊቱ ኩምቢዋን እጉሮሮው ድረስ አስገብታ አጥንቱን ጎትታ አወጣችለት፡፡ እፎይ አለ ቀበሮው፡፡
ከዚያም ወፊቱ፤ “በል እንደተዋዋልነውና ቃል እንደገባህልኝ ወደ ጠላቶቼ ልውሰድህና ተበቀልልኝ” አለችው፡፡ ቀበሮም ቃሉን አጠፈና፤
“ቀበሮ አፍ ውስጥ ገብቼ በሰላም ወጥቻለሁ፤ ብለሽ በኩራት መናገርሽ ይበቃሻል፡፡ ከፊቴ ጥፊ!” አለና አባረራት፡፡ ወፊቱም አቅራቢያዋ ወዳለው ዛፍ ላይ ወጣችና፤
“ሌላ አጥንት ጉሮሮህ ላይ የማይቀረቀር እንዳይመስልህ፡፡ ያኔ ምን እንደሚውጥህ እናያለን” አለችው፡፡ ከአካባቢው በርራ ጠፋች፡፡
*             *          *
በአንድ አገር ሶሺዮ-ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ሂደት ውስጥ አንዱ ትልቅ ቁምነገር ለህዝብ ቃል መግባት ነው፡፡ ይህን ቁምነገር የሚያረክሰው ደግሞ የገቡትን ቃል ማጠፍ ነው፡፡ የገቡትን ቃል ማጠፍ ዕምነትን ያጠፋል፡፡ ዕምነተ-ጎዶሎ አመራር ደግሞ በጄ ብሎ መንግሥትን አምኖ የሚገዛ ህዝብ እንዳይኖር ያደርጋል፡፡ ሰላምን ያደፈርሳል፡፡ ጥርጣሬንና እየተገላመጡ መኖርን ያገዝፋል፡፡ መረጋጋት እንዳይኖር ያደርጋል፡፡ ከሀገር መሰደድን ያበዛል፡፡ ማንም ማንንም የማያምንበት፣ ነፃነቱን የሚጠራጠርበት፣ እኩልነቱን የማይቀበልበት፣ የሕግን የበላይነት በወጉ የማይረዳበት፣ ለምንም ነገር ብቃት እንዳለው የማይተማመንበት፣ አልፎ ተርፎም ኢትዮጵያዊነቱን ለጥያቄ የሚዳርግበት ሁኔታ ውስጥ እንዲገባ ሊገደድ የሚችልበት ደረጃ ሊደርስ ይችላል። ስለዚህም ልንፈፅም የምንችለውን ቃል ብቻ በአደባባይ መናገር ብልህነት ነው፡፡ መንገዶች ሁሉ ሁሌ አልጋ ባልጋ ላይሆኑ እንደሚችሉ እንገንዘብ፡፡ መንገዶች ሁሉ ሁሌ ወደ ሮማ አይወስዱም፡፡ ሁሌም “የአፈፃፀም ችግር ነው” እያልን እንደማንዘልቅ እናስብ፡፡ ይልቁንም እቅዳችንን እንፈትሽ፡፡ ራሳችንን ወደ ውስጥ እንይ። እርስ በርሳችን ምን ያህል እንተማመናለን፤ ብለን እንጠይቅ፡፡ ስንወሻሽ እንጠያየቅ፡፡ በችግር ላይ ችግር ለምን ይደራረብብናል? ብለን እንጠይቅ፡፡ ቀውስ በተፈጠረ ቁጥር ወደ ኃይል መሄድ ከትርፉ ኪሳራው የሚያመዝን ሁነት መሆኑን እንይ፡፡ ከቶውንም ኃይል ከቀውስ ወደቀ ውስ ሊከተን እንደሚችል ልብ እንበልና ልብ እንግዛ፡፡ “መካር የሌለው ንጉሥ፣ ያለ አንድ ቀን አይነግሥ” የሚለውን ተረት እናስታውስ። “እንደ ንጉሡ አጎንብሱ” የሚለው ተረትም ሁልጊዜ አያበላም፡፡ ጊዜው ያለፈበት ነውና፡፡ ይልቁንም ሐምሌት የሚለንን ከአንጀታችን እናዳምጥ፡-
“በንጉሥ ፍርፋሪ የፋፋን ትል
አሣ አገኘችና፤ ቅርጥፍ
አሣ-አጥማጅ፣ እሷን ቅርጥፍ!
ሆድን ሞልቶ እንደስልቻ
በልቶ ለመበላት ብቻ!!”
ከሀገራችን የችግር ቁንጮዎች አንዱ አድር - ባይነት ነው፡፡ የጥንቱ የጧቱ ወዳጃችን ሌኒን፤ ‹‹The Pendulum of Opportunism never stops Oscillating›› ይላል፡፡ የአድር-ባይነት ፔንዱለም ዥዋዥዌውን አይተውም፤ እንደ ማለት ነው፡፡ አድር-ባይነት፣ ብቃት የጎደላቸው ሰዎች የኑሮ ዘዴ ነው። አጉል መካሪ ሀገር ያጠፋል፡፡ አድር - ባዮች አጉል መካሪ ናቸው፡፡ የራሳቸውን ጥቅም ለማካበት ሲሉ የማይፈነቅሉት ድንጋይ የለምና፡፡ ልታይ ልታይ ያበዛሉ፡፡ አደባባይ ይደፍራሉ፡፡ በአደባባይ ቃል መግባት አይፈሩም፡፡ ልሳናቸው ስል ነው፡ በሀገር ተቆቋሪነት ስም የማይዘላብዱት ነገር የለም! እንደ እስስት መልካቸውን ይለዋውጣሉ፡፡ በሠርግ ላይ ዘፈን አውጪ፣ በልቅሶ ቤት ሙሾ አውራጅ ናቸው! ሁሉንም የሚያደርጉት ለግል ጥቅማቸው ነው፡፡ ስለሆነም የሙስና ፈታውራሪ ናቸው፡፡ ሆኖም ደግሞ ሙሰኞችን ሲኮንኑ ይሰማሉ፡፡ የግምገማ መሪ ተዋንያን ናቸው፡፡ አልባሳት የመቀያየር ክህሎት አላቸው፡፡ ከነዚህ ያልተጠነቀቀ አመራር ወይም መሪ ለአደጋ የተጋለጠ ነው፡፡ ተንሸራታችና አንሸራታች ናቸውና፡፡ አፋቸው እንጂ ግብራቸው እኩይ ነውና!
‹‹አጓጉል ምላስ ብቻ ናት
ማሞካሸት የማይደክማት፤
ቀን አዝላ ማታ እምታወርድ
ንፉግን ልመና እምትሰድ!››
ይለናል ጋጣሚ ፀጋዬ ገብረመድህን፡፡ ይህን ልብ ማለት ይበጃል፡፡ ሌላው የሀገራችን ቁንጮ ችግር፤ ብሶትና ምሬትን ቸል ማለት ነው፡፡ ውስጥ ውስጡን የሚቀጣጠል እሳት አንድ ቀን የማይጠፋ ቋያ ይሆናል፡፡
‹‹ከጥንት ጀምሮ እኛ እንደምናውቀው
ሲነድ ሲቃጠል የሚስቅ እሳት ነው
ነገሩ አልሆን ብሎ ሁኔታው ሲጠጥር
ጠጣሩ እንዲላላ፣ የላላውን  ወጥር!››
ዛሬም ያው በረከተ-መርገም ነው! የህዝብን ብሶት እናዳምጥ፡፡ ችግርን ፊት ለፊት መጋፈጥና ተነጋግሮ፣ ተመካክሮ መፍታት እንጂ መሸፋፈኑ፤ ‹‹አለባብሰው ቢያርሱ በአረም ይመለሱ›› የሚለውን የአበው ብሂል መዘንጋት ነው፡፡ ‹‹እንደ ድመት አሥራ ሶስት ነብስ ነው ያለን!›› ማለት አያዋጣም፡፡
‹‹እኛ አድገናል ሌሎች ችግር ገጥሟቸዋል›› ማለትም ብዙ አያራምድም፡፡ ያለው›› ‹‹አለባብሰው ቢያርሱ..›› ነው፡፡ ህዝብ እየተቃወም ነው ሲባል፤ ‹‹በእነ እገሌ ምክንያት ነው› ማለትም ያው ‹‹አለባብሰው ቢያርሱ…›› ነው፡፡ የተቃውሞዎች ሁሉ ማጠንጠኛ ‹‹የመልካም አስተዳደር ችግር ነው›› ማለትም ያነው ‹‹አለባብሰው ቢያርሱ…›› ነው፡፡ የአባዬን እከክ ወደ እምዬ ልክክ (Blame-shifting) ያው ‹‹አለባብሰው ቢያርሱ…›› ነው፡፡ የሕግ የበላይነት በአፍ ቀላል ቢሆንም፣ በተግባር ግን እየተፈፀመ አለመሆኑን አለማመንም ‹‹አለባብሰው ቢያርሱ በአረም ይመለሱ›› ነው፡፡ ከሁሉም ይሰውረን! አዲሱ ዓመት አዲስ አድማስ ያሳየን! ልብና ልቦና ይስጠን!!