Administrator

Administrator

(ወ/ሮ ሂክማ ኬይረዲን፤ የደቡብ ክልል መንግሥት ኮሙኒኬሽን ጽ/ቤት ኃላፊ)

   የችግሩ ምክንያት በዲላ የንግዱ ማኅበረሰብና የጌዴኦ ዞን ሕብረት ሥራ ዩኒየን መካከል የቦታ ይገባኛል ክርክር ነበር፡፡ ባለፉት ጊዜያት ፍ/ቤቱ አክራክሮ ውሳኔም አስተሳልፎ ወደ አፈፃፀም ሂደት ሊገባ ነበር፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ ቦታው ለዩኒየኑ ይገባል በሚል የተወሰኑ አካላት ማኅበረሰቡን አነሳስተው በንግዱ ማኅበረሰብ ላይ ጉዳት ደርሷል። የፍ/ቤቱን ውሳኔ መነሻ አድርጎ ነው ግጭቱ የተከሰተው፡፡ ከግጭቱ ጋር በተያያዘ የሰው ሕይወት ጠፍቷል፣ ንብረትም ወድሟል፡፡ 23 ሰዎች ሞተዋል፤ ቤት ንብረት የተቃጠለባቸውና የወደመባቸው አሉ፤ ጉዳቱ ሰፊ ነው፡፡
በዚሁ ሂደት መካከል ችግሩ ሲከሰት ደንግጦ ከቤቱ የወጣ፤ ቤትንብረቱ ሲቃጠል ከቤቱ የወጣ  ሰው አለ፡፡ አንዳንድ ሰዎች የብሔር ግጭት ነው ይላሉ፡፡ ግን አይደለም፡፡ ጉዳቱ የደረሰው ከአካባቢው ብሔረሰብ ውጭ ብቻ አይደለም፡፡ ከአካባቢው ተወላጅ ሕይወቱ ያለፈ አለ፡፡ ስለዚህ ከሁሉም ኢትዮጵያዊ ብለን ነው መውሰድ የሚቻለው፡፡ የንግዱ ማኅበረሰብ ውስጥም የአካባቢው ተወላጆች አሉ፡፡ ንብረታቸው የወደመው የሁሉም ነው፡፡ ስለዚህ ግጭቱ የተወሰነ ብሔረሰብ ላይ በፍፁም ያነጣጠረ አይደለም፡፡
ለተጠቂዎቹ ቀድሞ የደረሰላቸውና ሕይወታቸውን የታደገው የአካባቢው ማኅበረሰብ ነው፡፡ አንዳንዶቹ የሃይመናት ተቋማት ውስጥ ተጠልለው ነው ያመለጡት፡፡ ሌሎቹ ደግሞ በአርሶ አደሩ ጓሮ ነው የተጠለሉት፡፡ ቤቱን በማጋራት ከቤቱ በላይ ሲሆንበት የአካባቢውን ማኅበረሰብ አስተባብሮ ድንኳን በመደኮን፤ ውሃ፣ ምግብ፤ በማቅረብ ቀድሞ የደረሰላቸው የአካባቢ ማኅበረሰብ ነው፡፡ ከቤት ንብረቱ የተፈናቀለ ሰው ከ20-25ሺህ ይደርሳል፡፡ መንግሥት ችግሩ ከዞኑ አቅም በላይ መሆኑን ካረጋገጠ በኋላ የፀጥታው ኃይል ገብቶ ሰላም የመፍጠርና የማረጋጋት ሥራ ሰርቷል፡፡ በመቀጠል ደግሞ ለተፈናቀሉ የማኅበረሰብ ክፍሎች የሚያስፈልጉ ነገሮችን ከለየ በኋላ ቁሳቁሶች ገዝቶ እያሰራጨ ነው፡፡ አብዛኛው ሕዝብ ደርሶታል፤ ያልደረሳቸውም ያሉ ይመስለኛል፡፡
በመሠረቱ ችግሩ ይህን ያህል ይሆናል ተብሎ አልተጠበቀም፡፡ ሲነሳ በተደራጀ መልኩ ቀደም ብሎ የተሠራበት አይደለም፡፡ ለንግዱ ማኅበረሰብ ተወስኗል የሚል ነገር ነው ለኅብረተሰቡ ተሰራጨው። አብዛኞቹ የኅብረት ሥራ ዩኒየኑ አባላት በአርሶ አደሩ መሃከል ያሉ ናቸው ወሬውን ያሰራጩት፡፡ ውሳኔው ተላላፊ እንጂ ወደ አፈጻጸም አልተገባም፡፡ የዞኑ አመራርም በአንድ ጊዜ ችግሩ በዚህን ያህል ይሰፋል፤ ኅብረተሰቡ በአንድ ጊዜ ይህን ውሳኔ ይሰማል የሚል ግንዛቤ አልነበረውም። ጥፋቱ ከአካባቢ አካባቢ ይለያል፡፡ ዲላ በስፋት ተጎድቷል። ወናጎ ላይና ይርጋጨፌ ላይ በጣም በስፋት ጉዳት ደርሷል፡፡ ሌሎች ወረዳዎች ላይ መጠነኛና ቀላል ነበር፡፡ መነካካቱ አለ፡፡ ግን ችግሩ አጠቃላይ ነው ብሎ መውሰድ አይቻልም፡፡
በአሁኑ ወቅት ይህንን ችግር ፈጥረዋል የተባሉ የተጠረጠሩ ሰዎች ተይዘዋል፡፡ የሕግ ሂደት መጠበቅ ስላለበት እነዚህ ሰዎች ናቸው ብሎ መደምደም አይቻልም፡፡ ከኅብረተሰቡ ጋር ስለጉዳዩ ውይይት ሲደረግ እነዚህ እነዚህ ናቸው ብሎ የሰጣቸው ሰዎች አሉ፡፡ ቁጥራቸው ሊጨምርም ሊቀንስም ይችላል፡፡
ከዝግጅት ክፍሉ
የይርጋጨፌ ወረዳ አስተዳዳሪ ስለጉዳዩ ለመጠየቅ ደውለንላቸው ሞባይሉ አይሰማም፣ በቢሮ ስልክ ደውሉ ብለውን ቁጥር ሰጡን። ስንደውል አይነሳም፡፡ መልሰን ደውለን ስልኩ አይነሳም አልናቸው፡፡ ቆይ እኔ እደውላለሁ ብለው ሳይደውሉ ቀሩ፡፡ ዞኑ አስተዳዳሪ ጋ ደውለን ስለጉዳዩ ልናናግራቸው መፈለጋችንን ስንነግራቸው አሁን አልችልም ስብሰባ ላየ ነኝ አሉን፡፡

- የወህኒ ቤቱ ጠባቂዎች እስረኞቹ እንዲያመልጡ ትብብር አድርገውላችዋል

    በህገ ወጥ መንገድ ድንበር ጥሰው ገብተዋል በሚል በደቡባዊ የመን በሚገኝ እስር ቤት ውስጥ ታስረው የነበሩ 1 ሺህ ህገወጥ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ባለፈው ረቡዕ ሌሊት አምልጠው መጥፋታቸውን አንድ የአገሪቱ የደህንነት ሃላፊ ማስታወቃቸውን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
በህገወጥ መንገድ ወደ የመን ገብተዋል በሚል ሻባዋ በተባለቺው የአገሪቱ ግዛት ውስጥ ታስረው ከነበሩትና ወደ አገራቸው ሊመለሱ ከተዘጋጁት 1 ሺህ 400 ያህል ኢትዮጵያውያን ስደተኞች መካከል አንድ ሺህ የሚሆኑት ባለፈው ረቡዕ ሌሊት እስር ቤቱን ሰብረው በመውጣት መጥፋታቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡
የእስር ቤቱ ጠባቂዎች ስደተኞቹ እንዲያመልጡ ትብብር እንዳደረጉላቸው ተረጋግጧል ያለው ዘገባው፤ ስደተኞቹ በተቀናበረ መንገድ ካመለጡ በኋላም በተዘጋጀላቸው መኪና በቡድን በቡድን እየሆኑ በአቅራቢያ ወደሚገኙት ማሪብ እና ባይዳ የተሰኙ ግዛቶች መሄዳቸውን አስታውቋል፡፡ የየመን መንግስት ባለፈው ወር ብቻ በህገ ወጥ መንገድ ድንበር ጥሰው ገብተዋል በሚል ከ220 በላይ አፍሪካውያን ስደተኞችን በቁጥጥር ስር በማዋል ወደ አገራቸው እንደመለሰ ያስታወሰው ዘገባው፤ከእነዚህም መካከል አብዛኞቹ ኢትዮጵያውያን እንደነበሩ ጠቁሟል፡፡

 አላስፈላጊ ብክነትን መቀነስ የሚል ዘመቻ የጀመረው የናይጀሪያ መንግስት፤ የአገሪቱ መሪ ሙሃመድ ቡሃሪ ከሚጠቀሙባቸው 11 ልዩ አውሮፕላኖች ውስጥ ሁለቱን ለመሸጥ መወሰኑን የፕሬዚዳንቱ ቃል አቀባይ ባለፈው ረቡዕ አስታወቁ።
የአገሪቱ መንግስት ፋልከን ሰቭንኤክስ እና ሃከር 4000 የሚል መጠሪያ ያላቸውን የፕሬዚዳንቱ ልዩ አውሮፕላኖችን እንደሚሸጥ የሚገልጽ ማስታወቂያ በጋዜጣ ላይ ማውጣቱን ቃል አቀባዩ ጋርባ ሼሁ መግለጻቸውን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡ መንግስት ለፕሬዚዳንታዊ በረራዎች የሚደረጉ ወጪዎችን ለመቀነስ ሁለቱን አውሮፕላኖች ለመሸጥ ከመወሰኑ ባሻገር  ከተቀሩት የፕሬዚዳንቱ አውሮፕላኖች የተወሰኑትን ለአገሪቱ አየር ሃይል እንደሚሰጥም ቃል አቀባዩ አስታውቀዋል፡፡ ናይጀሪያ በነዳጅ ዋጋ መቀነስና በውጭ ምንዛሬ እጥረት ሳቢያ የከፋ የኢኮኖሚ ድቀት ውስጥ መግባቷንና መንግስትም ይህንን ችግር ለመፍታት በማሰብ ከጀመራቸው እርምጃዎች ውስጥ፣ አላስፈላጊ ወጪዎችን መቀነስ አንዱ እንደሆነም ዘገባው ያስረዳል፡፡

 10 ሚሊዮን ሚስጥራዊ መረጃዎች እንዳሉት አስታውቋል

      የመንግስታትንና የታላላቅ ተቋማትን ጥብቅ ሚስጥሮች ፈልፍሎ በማውጣትና በማጋለጥ የሚታወቀው የዊኪሊክስ ድረገጽ መስራች ጁሊያን አሳንጄ፣ የአሜሪካን ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ የተመለከተ ጥብቅ ሚስጥር በቅርቡ ይፋ አደርጋለሁ ማለቱን ዩኤስኤ ቱዴይ ዘገበ፡፡
አሳንጄ የዊክሊክስን 10ኛ አመት የምስረታ በዓል በማስመልከት በቪዲዮ ሊንክ ባስተላለፈው ጋዜጣዊ መግለጫ፣ መጪው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ከሚከናወንበት ከህዳር ወር መጀመሪያ በፊት ከምርጫው ጋር የተያያዙ ሚስጥራዊ መረጃዎችን ለአለም ይፋ እንደሚያደርግ አስታውቋል፡፡ ዊክሊክስ ከዚህ በተጨማሪም በመጪዎቹ አስር ሳምንታት ውስጥ ከጦር መሳሪያዎች፣ ከጦርነቶች፣ ከጎግል ኩባንያና ከሌሎች ጉዳዮች ጋር የተያያዙ አዳዲስ ጥብቅ ሚስጥሮችን በየሳምንቱ እንደሚዘከዝክና ይፋ የሚያደርጋቸው 10 ሚሊዮን ያህል ጥብቅ ሚስጥራዊ መረጃዎች እንዳሉት አሳንጄ ተናግሯል፡፡
ከሰሞኑ ዊኪሊክስ ከሂላሪ ክሊንተን ጋር በተያያዘ ጥብቅ መረጃ ያወጣል ተብሎ ቢጠበቅም ምንም ነገር አለማውጣቱን የጠቆመው ዘገባው፣በሌላ በኩል አሳንጄ የሄላሪ ክሊንተንን የምርጫ ቅስቀሳ ለማደናቀፍ አሲሯል በሚል የሚናፈስበትን ሰሞንኛ መረጃ በዚሁ መግለጫው አስተባብሏል፡፡ አሳንጄ በቀረቡበት ክሶች ለስዊድን ተላልፎ እንዳይሰጥ በመስጋት፣ ከ2012 አንስቶ ለንደን ውስጥ በሚገኘው የኢኳዶር ኤምባሴ በጥገኝነት ተጠልሎ እንደሚገኝ ታውቋል፡፡

    ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ታላቅ ንጉሥ ሰፊ ግዛት እያስተዳደረ ይኖር ነበር፡፡ ዕድሜው እየገፋ  ሲሄድ ሶስቱን ልጆች በተራ ወደ አልጋው እየጠራ፣ አንድ ጥያቄ ይጠይቃቸዋል፡፡ በመጀመሪያ  ትልቁንና ጉልበተኛውን ልጁን ጠርቶ፤  ‹‹ልጄ፤ አሁን እኔ ህመምተኛ እየሆንኩ መጥቻለሁ፡፡ ስለዚህም አልጋዬን ለእናንተ መተው አለብኝ፡፡
ለመሆኑ ግዛቴን ለማስተዳደር ትችላለህ? ዝግጁ ነህ?››
ትልቁ ልጅም፤
‹‹መጠርጠሩስ! በደምብ እችላለሁ››
ንጉሡ፤
‹‹በምን ተማምነህ እንዲህ አልክ?››
ትልቁ ልጅ፤
‹‹በራሴ ስለምተማመን፡፡ ደግሞምኮ እንኳን እኔ ጎልማሳው፣ አንተም ሽማግሌው ስታስተዳድር
ነበር!›› ሲል መለሰ፡፡
‹‹እሺ ሂድ፡፡ መካከለኛውን ወንድምህን ጥራው››
መካከለኛው ወንድም ተጠርቶ መጣ፡፡
ንጉሡ፤
‹‹እንኳን ደህና መጣህ፡፡ ልጄ፤ አሁን እኔ እያረጀሁና ህመምተኛ እየሆንኩ መጥቻለሁ፡፡ ስለዚህም አልጋዬን ለናንተ ማውረስ አለብኝ፡፡ ለመሆኑ ግዛቴን ለማስተዳደር ዝግጁ ነህ?›› መካከለኛው ልጅ፤
‹‹እርግጠኛ አይደለሁም፡፡ ግን ካወረስከኝ ወንድሞቼን እያማከርኩ ለማስተዳደር እሞክራለሁ››
ንጉሥ፤
‹‹እሺ ሂድ፡፡ ታናሽ ወንድምህን ጥራው›› አለና ሸኘው፡፡
በመጨረሻ ታናሽየው ተጠርቶ ንጉሡ ፊት ቀረበ፡፡
ንጉሥ፤
‹‹ እንኳን ደህና መጣህ፡፡ ያስጠራሁህ አንድ ችግር ገጥሞኝ ነው፡፡ አየህ ልጄ፤ አሁን እኔ እያረጀሁና
ህመምተኛ እየሆንኩ መጥቻለሁ፡፡ ስለዚህም አልጋዬን ለናንተ ማውረስ አለብኝ፡፡ ለመሆኑ ግዛቴን
ለማስተዳደር ዝግጁ ነህ?›› ሲል ጠየቀው፡፡
ታናሽ ወንድምም፤
‹‹ማስተዳደር የምችል ይመስለኛል››
ንጉሥ፤
‹‹በምን ተማምነህ እንዲህ ልትል ደፈርክ?›› አለው፡፡
ታናሽ ወንድምም፤
‹‹ሦስት ዓይነት አቅም እንዳለኝ እተማመናለሁ፡፡
1ኛ/ የአንተን ምክር አዳምጣለሁ
2ኛ/ ከወንድሞቼ ጋር እመካከራለሁ
3ኛ ከአገሬው ጋር እወያያለሁ፡፡ የአገር ሽማግሌዎችን ጠርቼ ‹‹ምን ይበጃል?›› ብዬ እጠይቃለሁ፡፡
ሲል መለሰለት፡፡
ንጉሡ በጣም ተደሰተና፤
‹‹አገርና ሥልጣን የገባህ አንተ ነህ፡፡ ስለሆነም ግዛተ-መንግሥቴን መውረስ ያለብህ አንተ ነህ፡፡
ወንድሞችህን ጥራቸው›› አለው፡፡
ወንድሞቹን ሄዶ ጠራቸውና ሶስቱም ንጉሡ ፊት ቆሙ፡፡
ንጉሡም፤
‹‹አያችሁ ልጆቼ፤ ከሦስታችሁ ብልህ ሆኖ ያገኘሁት ትንሹን ወንድማችሁን ነው፡፡ የአገር አስተዳዳሪ  ብልህ መሆን አለበት፡፡ ይሄ ወንድማችሁ ብልህ በመሆኑ እኔንም አልተወ፤ እናንተንም አልተወ፤ ህዝቡንም አልተወ፡፡ እኔ ትላንት ነኝ፡፡ እናንተ ዛሬ ናችሁ፡፡ ህዝቡ ነገና ዘለዓለም ነው፡፡ ስለዚህም ሁላችንም በጊዜ ላይ ሠንሠለት ሰርተን አገርን አገር እናደርጋለን፡፡ ትንሹን ወንድማችሁን ውደዱት፡፡ ታዘዙት፡፡ ተግባብታችሁ ኑሩ!›› አላቸው፡፡
*  *  *
አገርን አገር ለማድረግ ሁላችንም መኖር አለብን፡፡ ታሪክን መርሳት የለብንም፡፡ ዛሬ ላይ ቆመንም  ነገን መገንባት እንዳለብን ማሰብ ይገባል፡፡ አገሬውን የያዘ አገርን በአግባቡ ይመራል፡፡ ከአገሬው የመከረ ከአገር መከረ ማለት ነው። ልባዊ መወያየትን መፍራት የለብንም፡፡ ሥነስርዓትን መፍራት የለብንም፡፡ አሮጌው ማለፉን አዲሱ ማሸነፉን (The new is invincible ይሏልና) ጭራሽ መዘንጋት የለብንም፡፡ መወራረስ መኖሩን፣ መለዋወጥ አይቀሬነቱን፣ ቋሚውና ቀሪ ህዝብን አገር መሆኑን ለአንድ አፍታም አለመርሳት እጅግ ይበጃል፡፡ ህዝብ ችግር ላይ ከወደቀ ሆድ እንደሚብሰው አለመዘንጋት ነው፡፡ ፕሮፌሰር ሽብሩ ተድላ፤ ‹‹በጎጃም በገንዘብ ወዳድነታቸው ብዙ ችግር ፈጥረዋል›› ያሏቸውን ራስ ኃይሉን የገለፁበት መንገድ ለእኛም ይጠቅመናል፡- (ከ‹‹ጎሬዛም ማሪያም እስከ አዲስ አበባ›› ከሚለው መጽሐፍ)
‹‹እንደሚወሳው፤ በጢስ የሚባል የግብር ሥነስርዓት ዘርግተዋል፡፡ ስለሆነም ጢስ የሚጤስበት ጎጆ ሁሉ ግብር እንዲጣልበት ተወሰነ፡፡ ገበሬው የተጣለበትን ግብር መክፈል ስላልቻለ፣ ብዙ ቤተሰቦች ቤቶቻቸውን እየለቀቁ፣ እየተዳበሉ፣ አንድ ጎጆ ውስጥ መኖር ጀመሩ፣ በዚህም ድርጊት ጢስ የሚጤስባቸው ጉጆዎች ቁጥር ቀነሰ፡፡ የተዳበሉ ቤተሰቦች፣ አንድ ቤት ቢኖሩም ቅሉ፤ ምግባቸውን የሚያበስሉ በተለያዩ ምድጃዎች ላይ ስለነበር፣ ራስ ኃይሉ ይህን ሲረዱ፣ በጉልቻ ቁጥር ላይ የተመሰረተ አዲስ ግብር ጣሉ፡፡ ባላገር ችግሩን ለማቃለል በወሰደው እርምጃ አንፃር፣ ራስ አዳዲስ ህግና ደንብ እያወጡ፤ አራሹ     ከችግሩ መላቀቅ ተሳነው፡፡
በዚህን ጊዜ አንድ አንጀቷ ያረረ፣ የተማረረች የሚከተለውን ገጠመች፡-
መሶቤን ወሰዱ፣
ድስቴንም ወሰዱ፤
ራስ የቀረዎ ትንሽ አማርኛ፣
ሆዴን በወሰዷት አርፌ እንድተኛ፡፡”
የኢኮኖሚ ችግሮች ሲያመረቅዙ ፖለቲካዊ ባህሪን ይወልዳሉና ሰብሰብ፣ ጠንቀቅ ብሎ ማየትን ይጠይቃል፡፡ (politics is the concentrated form of economics ይሏልና) የህዝብ ኢኮኖሚያዊ ምሬት ምላሽ እንደሚሻ ሁሉ በመድብለ ገፁ ፖለቲካዊ ቁጣ ሲሆንም አስቸኳይ ምላሽ መሻቱን ቢያንስ ዛሬ በይፋ አውቀናል፡፡ በይፋ ሰምተናል። ቁጣው ስርዓተ አልበኛነትን እንዳይወልድ በጊዜ የአስተዋይ መፍትሄ መስጠት ወሳኝ ነው፡፡ ከስሩ ያልተነቀለ ችግር ዳግም ማቆጥቆጡ አሌ አይባልም፡፡ የዛሬውን ተገላገልኩት ብሎ መተኛት መፍትሄ አይሆንም፡፡ ሰላም የራሱ ሂደት አለው፡፡ “ካያያዝ ይቀደዳል” የሚለውን ብሂል አንርሳ፡፡ ቀውጢ ቀውጢንና ጥላቻን እንጂ መረጋጋትን አይወልድምና ረጋ ብሎ “የረጋ ወተት ቅቤ ይወጣዋልን” ማሰብ ነው! ሁሉም
የህብረተሰብ ክፍል የነውጡ - ቀውስ ገፈት ቀማሽ ነው። ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል የደረሰው ሀዘን ሀዘንተኛ ነው፡፡ ሁላችንም፣ ለአንዲት ነብስ ማለፍ የምንቆረቆር ሁሉ ሀዘንተኞች ነን!ዛሬ እንደድሮው ዘመን “… ወይ እረሱ፣ ወይ መንኩሱ፣ ወይ ተኩሱ” አይባል ነገር 21ኛው ክፍለ
ዘመን ነው፡፡ (አገር፤ አንድ አራሽ፣ አንድ ቀዳሽ፣ አንድ ተኳሽ ያስፈልጋታል እንዲል መጽሐፍ፡፡)
ይልቁንም ሰላምን ዓላማ ማድረግ ዋና ጉዳያችን ነው፡፡ የምናርሰውና የምንቀድሰው ሰላም ሲኖር ነው፡፡ ሁከት፣ ነውጥ፣ ትርምስ፣ ዓላማ ቢስ ዘረፋ፣ ሲቀጣጠል የብዙ ህይወት፣ የብዙ ንብረት፣ የብዙ ሞራል ጥፋት ሊያስከትል እንደሚችል ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ ሁሉም “ከአያያዝ ይቀደዳል” ነው፤ መላ-ጨመቁ!
ከትውልዶች መወራረስና ከትውልድ ቅብብል የምናተርፈው፤ ካለፈው የምንማረው ምንም ይሁን
ምን አንዳች ነገር አይጠፋም፡፡ ፕሮፌሰር ሽብሩ ተድላ፤ “የቅብብሎሽ ሩጫ” በሚለው ግጥማቸው
ታላቅ ምክር ለግሰውናል፡- ከሰማን፡፡
አባቶቻችን እጅ፣ ትንታግ ተቀብለን፤
ርስ - በርስ ሽኩቻ፣ እሳቱን አዳፍነን፤
ጨለማ ውስጥ ነን፤
አትበሉ!
እጁን የዘረጋው፣ ይህ አዲሱ ትውልድ፣
ከከሰለ ችቦ፤ የቱን ብርሃን ሊወስድ፤
አትበሉ፤
መልካሙን ነው ማየት፣
ውቡን ነው መመኘት፣
ብርሃን ይከሰታል፣ ከተዳፈነ እሳት፡፡
ከአገሬው መምከር፣ ወደ ራስ ማየት፣ የሚነገረውን ማዳመጥ፣ ከአገር ሽማግሌዎች መማር፣ ልባዊ ውይይት ማድረግ፣ ጥፋትን በወግ በወጉ መዳኘት፣ ክስተቶች የምን ነፀብራቅ እንደሆኑ መመርመር፣ ብሶትን በአግባቡ መቀየድ፣ የግርግር ተጠቃሚዎችን ለይቶ ማየት፤ ደንብሮ አለማስደንበር፤ ሌላውን ለማይቀደዳል!”

በቀድሞው አንድነት ፓርቲ ውስጥ ጉልህ ሚና በነበራቸው አቶ አበበ አካሉ የተፃፈው ‹‹የቤልሆር ሹመኞች›› የተሰኘ ፖለቲካዊ ልብወለድ መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ መፅሐፉ በምድር ላይ ያለውን ነባራዊ ሁኔታ እንዲሁም የሰማዩን ኑሮ የሚያስቃኝ ነው ተብሏል፡፡ በ256 ገጾች የተመጠነው መፅሀፉ ለአገር ውስጥ በ81 ብር፣ለውጭ አገራት በ20 ዶላር ገበያ ላይ ቀርቧል፡፡ የቀድሞው አንድነት ፓርቲ አፈጉባኤ.፣በኋላም የሰማያዊ ፓርቲ የውጭ ግንኙነት ሀላፊ የነበሩት ደራሲው፤ቀደም ሲል “የሲኦል ፍርደኞች ቁ-1” የተሰኘ መጽሃፍ ለንባብ ማብቃታቸው የሚታወስ ሲሆን ‹‹ጉዞ ወደ ሲኦል ፍርደኞች ቁጥር 3›› ለማሳተም በዝግጅት ላይ መሆናቸውንም  ገልፀዋል፡፡

- ቀንደኞቹ ሙሰኞች የመንግስት ባለስልጣናት ናቸው ተብሏል
             
       ዚምባቡዌ በተለያዩ የሙስና ወንጀሎች ሳቢያ በአመት ከ1 ቢሊዮን ዶላር በላይ ገንዘብ እያጣች እንደምትገኝና ከፍተኛውን የሙስና ወንጀል የሚፈጽሙት የመንግስት ባለስልጣናትና የፖሊስ አባላት መሆናቸውን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል የተባለው አለማቀፍ ተቋም ሰሞኑን ያወጣውን ሪፖርት ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ በትምህርትና በትራንስፖርት እንዲሁም በሌሎች ዘርፎች የሚሰሩ የአገሪቱ የመንግስት ባለስልጣናት፣  የሥራ ሃላፊዎችና የፖሊስ አባላት፣ ዜጎችን በከፋ ሙስና እያሰቃዩ ይገኛሉ፡፡ በዚምባቡዌ የሙስና ተግባር ተቋማዊ እየሆነና የበለጠ እየረቀቀ መምጣቱን የጠቆመው ሪፖርቱ፤ የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በከፍተኛ ደረጃ የሚከናወኑ የሙስና ወንጀሎችን መከላከል አልቻሉም ብሏል፡፡ በዚህም የውጭ ኩባንያዎች ሙስናን በመፍራት ወደ አገሪቱ እንዳይገቡ ሆነዋል  በማለት ፕሬዚዳንት ሙጋቤን ተጠያቂ እንደሚያደርጉም ተጠቁሟል፡፡
ፕሬዚዳንት ሙጋቤ፤ ምንም እንኳን ሚኒስትሮቻቸው በሙስና ላይ እንደተሰማሩ በተደጋጋሚ ቢያምኑም አንዳቸውንም ለፍርድ ለማቅረብ አለመሞከራቸውን የሚያረጋግጡ መረጃዎች መገኘታቸውን ዘገባው ያመለክታል፡፡

   አለማቀፉ የማራቶንና የረጅም ርቀት ውድድሮች ማህበር፣ለአትሌት ኃይሌ ገብረ ስላሴ የኤአይኤምኤስን የእድሜ ዘመን ስኬት ሽልማት በመጪው ህዳር ወር መጀመሪያ ሊያበረክት መወሰኑን አስታውቋል፡፡
የማህበሩ ፕሬዚዳንት ፓኮ ቦራኦ፤ኃይሌ ለአለማችን ማራቶን ላበረከተው አስተዋጽኦ እውቅና መስጠት በመቻላቸው ኩራት እንደሚሰማቸው ገልጸው፣ የአትሌቱ ስኬት ከአፍሪካ አልፎ በመላው አለም ለሚገኙ በርካቶች የመነቃቃት ምንጭ መሆኑንና የዓላማ ጽናቱም ለተምሳሌትነት የሚበቃ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ማህበሩ ባወጣው መግለጫ፤በመጪው ህዳር ወር መጀመሪያ ላይ በግሪክ አቴንስ በሚካሄድ ሥነስርዓት ላይ ለኃይሌ የእድሜ ዘመን ሽልማቱን እንደሚያበረክት አስታውቋል፡፡ ኃይሌ ገብረ ስላሴ የማህበሩን አለማቀፍ ሽልማት ሲቀበል ይህ የመጀመሪያው እንዳልሆነ ያስታወሰው መግለጫው፣ አትሌቱ እ.ኤ.አ ከ2006 እስከ 2008 ባሉት ዓመታት የማህበሩን የዓለማችን ምርጥ አትሌት ሽልማት፣ለሶስት ተከታታይ ጊዚያት ማግኘቱንም ገልጧል፡፡ ኃይሌ ለማህበሩ ሽልማት በመመረጡ ከፍተኛ ደስታ እንደሚሰማው ገልጾ፣ በአቴንስ በሚካሄደው ስነስርዓት ላይ ተገኝቶ ሽልማቱን እንደሚቀበልና በማራቶን ማህበረሰብ ውስጥ ካሉ ጓደኞቹ ጋር አስደሳች ጊዜ እንደሚያሳልፍ ተናግሯል፡፡
አለማቀፉ የማራቶንና የረጅም ርቀት ውድድሮች ማህበር፣የበርሊን ማራቶንን ጨምሮ በአለማችን 110 አገራትና አካባቢዎች የሚካሄዱ እጅግ ዝነኛና ግምባር ቀደም አለማቀፍ የሩጫ ውድድሮችን በአባልነት መያዙ ታውቋል፡፡

“ለደህንነታችን ዋስትና የሚሰጠን አካል የለም” ባለሀብቶች
- “ቢሻን ጋሪ ሎጅ” ላይ በደረሰው ዘረፋና ቃጠሎ ፖሊስ ጥቃቱ እንዳይደርስ ከመከላከል ተቆጥቧል
- ፖሊስ ጣቢያዎች፣ ፍርድ ቤቶች፣ ማዘጋጃ ቤቶችና የመንግስት ተቋማት ወድመዋል

በኢሬቻ በዓል አከባበር ወቅት የተከሰተውን የበርካቶች ህልፈተ ህይወት ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች በተቀሰቀሰው ተቃውሞና አመፅ እያደረሰ ያለው የንብረት ውድመት ከመንግስት ጥበቃና ቁጥጥር ውጪ እየሆነ ነው፡፡
ባለፈው ሳምንት በክልሉ የተለያዩ ስፍራዎች በተቀሰቀሰው ተቃውሞና አመፅ በቢሊዮን ብሮች የሚቆጠር ንብረት ወድሟል ተብሏል፡፡
ሰሞኑን በቡራዩ፣ በሰበታ፣ በአዋሽ መልካሳ፣ በአርሲ ነገሌ፣ በአለምገና እና ሌሎች የኦሮሚያ ክልሎች በተቀሰቀሰው ተቃውሞ፣ በሚሊዮኖች በሚቆጠር ገንዘብ የተቋቋሙ ፋብሪካዎች፣ የህዝብና የጭነት ማመላለሻ መኪኖች፣ የመንግስት ተቋማት፣ ፖሊስ ጣቢያዎችና የአበባ እርሻዎች ሙሉ በሙሉ ወድመዋል፡፡
በላንጋኖ አካባቢ በ100ሺ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ በተገነባው ቢሻን ጋሪ ሎጅ ባለፈው እሮብ በደረሰበት ዘረፋና ቃጠሎ ሙሉ በሙሉ ለማጥፋትም ሆነ ንብረቱን ከአደጋ ለመከላከል የተደረገ ሙከራ አለመኖሩ ተስፋ እንዳስቆረጣቸው የድርጅቱ ባለቤት አቶ ዑመር ባገርሽ ትናንት ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ላይ ተናግረዋል፡፡
ሎጁ ላለፉት 17 ዓመታት የአካባቢ ጥበቃን ባማከለ መንገድ ለውጪ አገርና ለአገር ወስጥ ቱሪስቶች አገልግሎት በመስጠት ላይ እንደነበር የገለፁት ባለሀብቱ፤ ‹‹ምንም በማናውቀውና ፈፅሞ ባልገመትነው ሁኔታ በሎጁ ላይ በተፈፀመው ዘረፋና የቃጠሎ አደጋ ከፍተኛ ሀዘን ተሰምቶናል ብለዋል፡፡ የድርጅቱ ኦፕሬሽን ክፍል ሃላፊ አቶ ዘለዓለም ቤኩማ በወቅቱ ስለተፈጠረው ሁኔታ ሲገልፁ፤ “ማንነታቸውን የማናውቃቸው በርከት ያሉ ወጣቶች እየጨፈሩ ወደ ግቢው ለመግባት ያደረጉትን ተደጋጋሚ ሙከራ በአካባቢው ሽማግሌዎች ልመናና ውትወታ ለመከላከል ሞክረናል፡፡ ሁኔታው እየተባባሰና የሰዎቹም ቁጥር እየጨመረ ሲሄድ ለአሩሲ ነጌሌ ፖሊስ ጣቢያ ደውለን፣ አሣወቅን” ያገኘነው ምላሽ ግን ተስፋ የሚያስቆርጥ ነው ብለዋል፡፡ እኛ ወደ እናንተ መምጣት አንችልም፤ ጉዳዩን እዛው በሽምግልና ለመፍታት ሞክሩ ነው ያሉን ሲሉ ገልፀዋል - አቶ ዘልዓለም፡፡  “ሁኔታው ከአቅማችን በላይ ስለነበር፣ ዓይናችን እያየ ሎጁን እሳት ለኮሱበት፡፡ በአሁኑ ወቅትም ሎጁ ሙሉ በሙሉ ወድሟል፡፡ በሰው ህይወት ላይ ግን የደረሰ አደጋ የለም›› ብለዋል፡፡ በዚህ ዘረፋና ቃጠሎ ከ50 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት ንብረት እንደወደመባቸውም የሎጁ ባለቤት አቶ ዑመር ባገርሸ ተናግረዋል፡፡
‹‹ደህንነታችን ባልተረጋገጠበትና ፖሊስ ሊደርስልን በማይችልበት ሁኔታ ውስጥ እንሆናለን ብለን ፈፅሞ አልጠረጠርንም፡፡ የደረሰብን ጉዳት እጅግ አሳዛኝና ተስፋ አስቆራጭ ነው›› ብለዋል፡፡
ባለፈው ረቡዕ በኦሮሚያ ክልል አዋሽ መልካሳ በተቀሰቀሰ አመፅ በአካባቢው በሚገኘው ብስራት የጠጠር ማምረቻ ድርጅት ላይ የተከሰተው ቃጠሎም ከ23 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገዙ አዳዲስ ማሽኖች ወድመዋል ተብሏል፡፡
ውድመቱ በደረሰባቸው አንዳንድ አካባቢዎች ተዘዋውረን ያነጋገርናቸው ባለሃብቶች፤ በአሁኑ ወቅት በከፍተኛ ሥጋት ላይ እንደሚገኙና በማንኛውም ጊዜና ሰዓት በንብረታቸውም ሆነ በህይወታቸው ላይ አደጋ ሊከሰት እንደሚችል ገልፀው፤ ለደህንነታችን ዋስትና የሚሰጠንና አደጋ ቢደርስብን ፈጥኖ የሚደርስልን አካል የለም ብለዋል፡፡ ሁኔታው ከመንግስት ቁጥጥር ውጪ እየሆነ መምጣቱ ከፍተኛ ሥጋት አሳድሮብናል ሲሉም ተናግረዋል፡፡
በዝዋይ ከተማ ውስጥ በአበባ እርሻ ልማት ላይ የተሰማሩ አንድ ባለሃብት ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፤ በአካባቢው በተቀሰቀሰው ተቃውሞና አመፅ ሳቢያ በንብረት ላይ እየደረሰ ያለው ውድመት እጅግ እንዳሳሰባቸው ጠቁመው፤ ዋስትና በሌለበትና ምን እንደሚከሰት መገመት በማይቻልበት ሁኔታ ውስጥ መሆን እጅግ አስፈሪ ነው ብለዋል፡፡
በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ አካባቢዎች እየተባባሰ በሄደው ተቃውሞና አመፅ በርካታ ፖሊስ ጣቢያዎች፣ ፍርድ ቤቶች፣ ማዘጋጃ ቤቶች፣ የመንግስት ሴክተር መ/ቤቶች የመንግስትና የግለሰቦች ተሽከርካሪዎች በእሳት ወድመዋል፡፡ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት፤ በሳምንቱ ውስጥ በርካታ የመንግስትና የግል ንብረቶች ወድመዋል፡፡ በሰበታ ከተማ ብቻ የኤሌክትሪክ ኬብል ማምረቻ፣ የጨርቃ ጨርቅና የፕላስቲክ ፋብሪካዎችን ጨምሮ 11 ልዩ ልዩ ፋብሪካዎች የተቃጠሉ ሲሆን ከ62 በላይ አውቶብሶችና ሌሎች ተሽከርካሪዎች በቃጠሎው ሙሉ በሙሉ ወድመዋል፡፡  



 (የራስ ተሞክሮ)

      ስለ አጭር ልብ ወለድ መፃፍ ፈለግሁኝ፡፡ ስለ አጭር ልብ ወለድ ከመፃፍ፣ አጭር ልብወለድ መፃፍ ይቀለኛል፡፡ መጀመሪያ ያነበብኩትን አጭር ልብ ወለድ ከማስታወስ፣ መጀመሪያ የፃፍኩትን አጭር ልብ ወለድ ማስታወስ ይቀለኛል፡፡
አዲስ ነገር የምፈልግበት ጊዜ ነበር፡፡ የተወሰኑ የእንግሊዝኛ አጭር ልብ ወለዶች ለመፃፍ ሞክሬ፣ግን እኔ እንደምፈልጋቸው አልሆኑልኝም፡፡ ያነበብኳቸው መፅሐፍት እየጎተቱ ያስቸግሩኛል፡፡ ደግሞ ፀሐፊ/ደራሲ እሆናለሁ ብዬ ቆርጫለሁኝ፡፡ የቀድሞ ስራዬን ለዚህ ድፍረት ስል ትቼዋለሁ፡፡ አስታውሳለሁኝ በጣም የትግል ጊዜ ነበር፡፡ የጥርጣሬ ጊዜ ነበር፡፡ “ነኝ ወይንስ አይደለሁም? መፃፍ እችላለሁ ወይንስ አልችልም?” … ሁሉም ነገር ጥርጣሬ ብቻ ነበር፡፡ ግን እርግጠኝነትም አለ፡፡ እርግጠኛ ባልሆን እርግጠኛ የነበረውን ስራዬን አልተውም፡፡
“It’s a shot in the dark” እንደሚለው ነው ቡካውስኪ፡፡ … “ወርውር የእጅህን ዘገር/የህሊናህን ዘር/ ይዘኸው እንዳትቀር” የሚለው የደበበ ሰይፉ ቁራጭ ግጥምን እንደ አዝማች እደጋግማለሁ፡፡ ቤተሰቦቼ ፈርተውኛል፡፡ ተጠራጥረውኛል፡፡ አባቴ አንድ ቀን አስቀምጦ መከረኝ፡፡ ስለ ብዙ ደራሲዎች ህይወት ዘረዘረልኝ፡፡ ብዙዎች ደራሲ እንሆናለን ብለው ባክነው ነው የሚቀሩት ------ they end up being bums … ምናምን ሲለኝ ትዝ ይለኛል። ግን ማስፈራሪያው ቢያስፈራራኝም፣ ህይወቴ ትርጉም የሚኖረው ሳልፈራ ከቀጠልኩ ብቻ ነው ብዬ ገገምኩኝ፡፡
ቤተሰቤ በአጠቃላይ በንባብ ባህል ውስጥ የሚመላለስ ቢሆንም … የሌሎችን ልፋት በድርሰት መልክ ማንበብ እንጂ … ደራሲ ሆኖ አስነብባለሁ የሚል አቋምን ለማስተናገድ ዝግጁ አልነበረም፡፡ “ሞክር እና እየው” በሚል ተዉኝ፡፡
የፅሁፍ አለም አስፈሪው ጨለማ በመኝታ ቤቴ ውስጥ ቢሰፍንም … መፅሐፍ ገልጬ ሳነብ መጠነኛ ብርሐን እፈጥራለሁ፡፡ የሆነ ሀሳብ ብልጭ ሲል ለመፃፍ ስታገል፣ ጥርጣሬዬ ለጊዜውም ቢሆን ይወገዳል፡፡ ትግል ነው፡፡ ተስፋ መቁረጥ እንዳይኖር ግን ከጧት እስከ ማታ በትግል ውስጥ እደበቃለሁኝ።
የጥንቱ የስራ ዓለም ጓደኞቼን ራቅኋቸው። የድሮው አለም ለፅሁፍ ግብአት እንዲሆነኝ እንጂ እንድኖርበት አልፈልግም ብዬ ወስኛለሁ፡፡ አዲስ ድልድይ ለመስራት የድሮውን አፈረስኩት፡፡  እንድፅፍ ሲያበረታታኝ የነበረ አንድ ፈላስፋ ወዳጅ ነበረኝ፡፡ ፀሐፊ ሆኖ እኔ እንድፅፍ ሲገፋፋኝ በነበረ ጊዜ፣ እኔ ደብዳቤ እንኳን መፃፍ የማልደፍር ሰው ነበርኩኝ፡፡ ጓዜን ጠቅልዬ ወደ ፅሁፍ ስገባ፣ ፀሐፊ የነበረው ጓዴ መፅሐፍን ማምለክ አቁሞ፣ ብር ማምለክ መጀመሩን በይፋ አስታወቀኝ፡፡ እምነቴን እንዳይበክለው ካፈረስኩት ድልድይ ጋር እሱንም አስወገድኩት፡፡
በህይወቴ እንደዚያ ያነበብኩበት ዘመን የለም። ሌላ አማራጭም አልነበረኝም፡፡ የማላነብ ከሆነ መፃፍ ነበረብኝ፡፡ የማልፅፍ ከሆነ ስለ ፀሐፊዎች ህይወት ማወቅ ነበር ፍላጎቴ፡፡ የጃክ ለንደንን አጭር ልብ ወለዶች ከመውደድ ወደ መጥላት ገባሁኝ። ከአጭር ልብ ወለዱ ይልቅ “ማርቲን ኤደን” የተባለውን ብቸኛውን ረጅም ድርሰቱን ሳነብ ብዙ ፅናትን ፈጠረልኝ፡፡ “ማርቲን ኤደን” የአንድ ደራሲ ታሪክ ነው፡፡ ተነባቢ ለመሆን የሚያደርገውን ውጣ ውረድ፣ ከህይወቱ ጋር ቀይጦ የሚተርክ መፅሐፍ ነበር፡፡ ልክ ለእኔ የተፃፈ ድርሰት እስኪመስለኝ ተዋጥኩበት፡፡
የጃክ ለንደን አጫጭር ልብ ወለዶችን የጠላሁበት ምክኒያት ለአንባቢ እንጂ ለደራሲ የሚሆኑ ስላልነበሩ ነው፡፡ በህይወት ስቃይና በተፈጥሮ ጭካኔ ስር ስለሚፍጨረጨሩ ሰዎች ገድል ነው  የሚተርኩት። የህይወት ተሞክሮው በጉዞ ገድሎችና በአደገኛ የህይወት ጠርዝ ላይ ተፈትኖ የኖረ ሰው የሚፅፋቸው ታሪኮች ናቸው። የእሱ ታሪክን እንደ አንባቢ ሆኜ ሳየው፣ ነፍስን ሰቅዞ የሚይዝ የአድቬንቸር ፊልም ነው፡፡ ግን የእኔን አለም አይወክልም፡፡ የእኔ አለም ከመኝታ ቤቴና ከመፅሐፍቴ የበለጠ ገድል የሌለበት ነው። ተጉዤ አላውቅም፡፡ ጀብድ ፈፅሜም አላውቅም። ለነገሩ የመጓዝም ፍላጎት አልነበረኝም፡፡ እኔ የጉዞ ማስታወሻ ፀሐፊ መሆን እጣ ፈንታዬ አይደለም ብዬ ደምድሜያለሁ፡፡ ስለዚህ ጃክ ለንደንን ጠላሁት። ሪያሊዝም የሚፅፉትንም ጠላሁዋቸው፡፡ አዲስ አማራጭ መፈለግ ነበረብኝ፡፡ ስለ ተራ ሰዎች መፃፍ እችላለሁ፡፡ የማውቃቸው ሰዎች ከተራም የበለጠ የወል ናቸው፡፡ የሚያወሩትን፣ የሚያስቡትን፣ የሚኖሩትን ----- ልፅፈው ይቅርና ልብ ብዬ ሳያቸው እንኳን ነፍሴ ትፀየፋለች፡፡
አቅጣጫ ማግኘት ነበረብኝ፡፡ የራሴን ድምፅ መፍጠር ነበረብኝ፡፡ ጭንቁ የሚቻል አይደለም። ጭንቅ ውስጥ እንደነበርኩ ግን የሚገባኝ አሁን ወደ ኋላ ተመልሼ ሳስታውስ ነው፡፡ ደግነቱ በወቅቱ ለእኔም አይታወቀኝም ነበር፡፡ ኪሎ ስቀንስም ልብ አልልም፡፡ ያኔ ኤችአይቪ የሚፈራበት ዘመን ነበር፡፡ ግን አይታወቀኝም፡፡ …. ማማጥ ብቻ ነበር ሥራዬ፡፡
ይሄ ጽሁፍ ልብ ወለድ ይመስላል አይደል። ወደ ኋላ ተመልሰን በድጋሚ ህይወታችንን ከተመለከትነው እኮ ታሪካችን በራሱ ጊዜ ልብ ወለድ ሆኖ ይገኛል፡፡
አንድ ዓመት በዚህ ሁኔታ ውስጥ ቆየሁኝ፡፡ እህቴ የገዛችልኝ ሙሉ እሽግ የወረቀት ጥራዝ በመፃፍ አለቀ። ብዙ እፅፋለሁ ግን የነጠረው ውጤት ጥቂት ነው፡፡ ክረምት መውጫው ላይ አልሰር ያዘኝ፡፡ ጨጓራዬ ደማ፡፡ ደም አስታወከኝ … ራሴን ስቼ ሆስፒታል ገባሁኝ፡፡ ደም አዋጥተው ሰጡኝ፡፡ ያው ድኜ ወጣሁ፡፡ ምናልባት የሰጡኝ ደም እንደሆነ ባላውቅም … ከሆስፒታል ወጥቼ ሳገግም፣ ከመስከረም ፀሐይ ጋር አዲስ የምናብ አቅም በውስጤ ሲበራ ድንገት ይሰማኝ ጀመር፡፡
ከመስከረሙ ፀሐይ ጋር አንድ ቀደም ሲል ሰው ያስተዋወቀኝን ጋዜጠኛ በመንገድ ላይ ባጋጣሚ አገኘሁት፡፡ ቤቱ ወስዶ አብረን ቃምን፡፡ እንደኔው የሚፅፍ ሰው … እና ከፅሁፉ ጋር ለመሞት የቆረጠ አምሳያዬን ለመጀመሪያ ጊዜ አገኘሁኝ፡፡ ጋዜጠኛው ዘና ያለ ነው … በአላማና ግብ የተወጠረ አይደለም። ታላቅ ደራሲ በአንዴ ካልሆንኩ ብዬ፣ በጭንቀት አልሰር መያዝ የዋህነት መሆኑን ተገነዘብኩኝ፡፡ ሁሉም ነገር ቀስ በቀስ የሚመጣ ነው፡፡
በሦስት ወር ታላቅ ድርሰት ካልፃፍኩ ብሎ ነገር የለም፡፡ ጋዜጠኛው ቤት ሌሎች ሁለት ልጆች አይጠፉም፡፡ አንዱ ገጣሚ ነው፤ ሌላኛው … እንደ ሀያሲ፣ እንደ ባህታዊም ያደርገዋል፡፡ ለብቻ ከሚደረግ ትግል ይልቅ የማህበሩ ይቀላል፡፡ መናበብም ይኖራል። የባህሪይ ብቻ ሳይሆን የወረቀትም መናበብ፡፡ እስከዚያ ጊዜ ድረስ በእንግሊዝኛ እንጂ በአማርኛ ፅፌ አላውቅም፡፡
“አማርኛ ወንዝ የማያሻግር ቋንቋ ነው” ብለን ከቀድሞው ፈላስፋ (በኋላ ነጋዴ) ጓዴ ጋር እንፎክር ነበር፡፡ እንደ አዲስ እምነቴን ለማደስ፣ አማርኛን ማንበብ ያዝኩኝ፡፡ ንባቤ ለዘመናት ሳይሆን አቅሜን ምዘና ነበር፡፡ የአዳም ረታ “ማህሌት”ን … እና በፋሲል ይትባረክ የተተረጎመውን የዶስቶይቪስኪ “የስርቻው ስር መጣጥፍ”ን ከሌላው ለይቼ ወደድኳቸው፡፡ ሁለቱንም የማምለክ ፍላጎት ግን ባልታወቀ ምክኒያት አልነበረኝም፡፡
የመጀመሪያ የአማርኛ መጣጥፍ ፅፌ፣ ለማህበሩ አባላት አስነበብኳቸው፡፡ ገጣሚው መጣጥፉን መውደድ ብቻ ሳይሆን ከዚያ ላይ እየጠቀሰ፣ በወሬ መሀል እንደ ማስረጃ ሲያነሳሳው፣ ያ የድሮው ፍርሐቴ የልብ ልብ ተሰማው፡፡ ከዚያ በኋላ መጣጥፍ መፃፍ ላይ በረታሁኝ፡፡ መፃፍና ለእነዛ መሰሎቼ አስነብቤ ጭበጨባን ማግኘት እንጂ ሌላ ግብ ለጊዜው አልታየኝም፡፡
ለጋዜጣ ለምን አትሰጥም? የሚል ግፊት የመጣውም ከዚሁ ቡድን ነው፡፡ ጋዜጦች አጭር ልብ ወለድ እንደሚያስተናግዱና ‹‹አዲስ አድማስ›› ተብሎ የሚጠራ ጋዜጣ፣ የርቅቀት ጫፍ መሆኑ ሁሉም በጊዜው ይስማማበት ነበር፡፡ ከቡድኑ መሀል ባይሆንም አንድ ጓደኛቸው፣ ሳይንስ አምድ ላይ ስለ ‹‹አክሊሉ ለማ›› ጽፎ እንደተስተናገደለት፣ ልጁን እንደ ጀግና ክበው ነገሩኝ፡፡
አጭር ልብ ወለድ በአማርኛ ለመፃፍ ገና ሩቅ መሆኔ ይገባኛል፡፡ ጅማቴን ለማጠንከር ስል የእንግሊዝኛ ልብ ወለዶችን ወደ አማርኛ መተርጎም ጀመርኩኝ፡፡ ትርጉም ራሱን የቻለ ውበት እንዳለው የገባኝ፤ በተመስጦ ስተረጉም ውዬ፣ ከሀያ ገፅ በላይ ፅፌ እንቅልፍ የሚገላግለኝ ጊዜ ስለነበር ነው፡፡ በእጄ ብዙ ልብ ወለድ ቢኖሩኝም- በአልፍሬድ ሂችኮክ ብራድ ስር የሚታተሙ ‹ሚስትሪ ማጋዚን› ላይ የወጡ ብዙ የፍርሀት  ታሪኮችን ወደ አማርኛ ማዞር ያዝኩኝ፡፡
ለ“አዲስ አድማስ” ልብ ወለድ ከመስጠቴ በፊት በጋዜጣው ላይ የወጡትን አጭር ልብ ወለዶች  ደርድሬ በማንበብ ራሴን አዘጋጀሁ፡፡ የፀሐፊዎቹን ስም አልይዝም፡፡ ትኩረቴ የልብ ወለዱ አቅም ላይ ብቻ ነበር፡፡ ለአቅመ “አዲስ አድማስ” እስክደርስ… ተመሳሳይ ይዘት ያለው ‹‹ኔሽን›› የሚባል ጋዜጣ ትኩረቴ ውስጥ ገባ፡፡ “ኔሽን” ላይ ‹‹ሉቂያኖስ››  በሚል ስም የሚፅፈውን ልጅ የእይታ አዲስነት ማድነቅ ጀመርኩኝ፡፡ ልጅ በእውቀቱ ስዩም ስለመሆኑ በጊዜው ምንም መረጃ  አልነበረኝም፡፡
የተረጎምኩትን ልብ ወለድ በአዲስ ሉክ በጥንቃቄ ገልብጬ፣ ወደ ጋዜጣው የዝግጅት ክፍል ሄድኩኝ፡፡… “ማርቲን ኤደን” በሚል ርዕስ፣ ጃክ ለንደን ጻፈው ያልኩት ወጥ ልብወለድ ላይ ደራሲ ለመሆን አሳሩን የሚበላው ገፀ ባህርይ፤ ፅሁፉን ለጋዜጣ ሲያስገባና “rejection slip” ሲሰጠው ነው መፅሐፉ የሚተርከው፡፡ እኔም የማርቲን ኤደን እጣ ፈንታ ይገጥመኛል ብዬ ደምድሜ ነበር ፅሁፌን ያስገባሁት። መቶ ጊዜ ለመመላለስ ዝግጁ ነበርኩኝ፡፡
ግን የሰጠሁት የትርጉም አጭር ልብ ወለድ በተመሳሳይ ሳምንት ጋዜጣው ላይ ወጣ፡፡ ማመን አልቻልኩም፡፡ በውስጤ የነበረውን ኩራት የማጋራው ሰው  ናፈቀኝ፡፡ በአንድ ጊዜ ሁሉንም ሰው ማግኘት ፈለኩኝ፡፡ ገንዘብ ግን አልነበረኝም። ጋዜጣዬን ይዤ ተቀመጥኩኝ፡፡ እገልጠዋለሁ። አነበዋለሁ፡፡ ስሜ ከፅሁፉ በላይ አለ፡፡ ለልብ ወለዱ የካርቱን ስዕል ተስሎለታል፡፡ ትንግርት ሆነብኝ፡፡ በቀጣዩ ሳምንት የአጭር ልብ ወለድ እሩምታ በጋዜጣው ዝግጅት ክፍል ለቀቅሁኝ፡፡ ግን ያስገባሁት አልወጣም፡፡ ተስፋ አልቆረጥኩም፡፡ የማርቲን ኤደን ዕጣ ፈንታ በእኔ የመጀመሪያ ስኬት ተሽሯል፡፡
ምናልባት ወጥ ልብ ወለድ ይሆናል የሚፈልጉት በሚል መፃፍ ጀመርኩኝ፡፡ ግን መፃፍ ስጀምር… የልብ ወለዶቹ አቅጣጫ አዲስነት፣ በጋዜጣ ከማውጣት ስኬት በላይ ይማርከኝ ጀመር፡፡… የጥበብ ጓደኞቼም ሙከራዎቼን ክበው/ከምረው በራስ መተማመን አሳበጡኝ፡፡ በአንድ ሳምንት ውስጥ ሁለት አጭር ልብ ወለድና አንድ መጣጥፍ መፃፍ አለብኝ ብዬ ወሰንኩኝ፡፡ አንዳንዴ ግን ከውሳኔዬ በላይ የምጽፍበትም ጊዜ ነበር፡፡….
ይህ አመት ለእኔ ድምፄን ያገኘሁበት አመት ነው ብዬ ስለማስበው…. ትቶብኝ የሄደው ብርሀናማ ትዝታ ተራ ቦታ የሚሰጠው አይደለም፡፡ ግን ይኼ አመት እኔ የድርሰት ድምፄን ያገኘሁበት ነበር ብልም… በሀገሪቷ ታሪክ ግን አስገራሚ ቁጥር ያለው ህዝብ ድምፁን ለምርጫ ለመጀመሪያ ጊዜ ሰጥቶ የተነጠቀበት ተብሎ የሚታወስ ታሪካዊ አመት ነው። ዓመቱ 1997 ነበር፡፡  
የፖለቲካ ውዝግቡ ሳይረብሸኝ መሰረታዊ ብዬ የማስባቸውን የልብ ወለድ ንድፎች የፃፍኩበት ወቅት ነበር፡፡ 97 ለመላው ኢትዮጵያ ሌላ ትዝታ ቢኖረውም፤ ለእኔ ግን ‹‹የንፋስ ህልም እና ሌሎች የምናብ ታሪኮች›› የሚለውን ከ97 አምስት አመታት በኋላ ያሳተምኩትን መፅሐፍ ጥንስስ ያቦካሁበት ልዩ አመት ነበር፡፡
ታዲያ አሁን ይኼንን ታሪክ ለምን ልብ ወለድ አስመስዬ ፃፍኩት? ለብልሃቴ ብዬ ነው፡፡ ‹‹የንፋስ ህልም›› በድጋሚ ታትሞ ገበያ ላይ ለመውጣት ዝግጅቱ ጦፏል፡፡ ይሄን መረጃ ለናንተ ለውድ አንባብያን ለመጠቆም የዘየድኩት መላ ነው፡፡ መፅሐፉን ማንበብ ከመፅሐፉ ጀርባ ያለውን ታሪክ አይነግርም፡፡
(በፊልም The making of the film እንደሚሉት መሰለኝ) እኔ ግን ‹‹የንፋስ ህልም›› አፃፃፍን ከፅሁፉ ነጥሎ መደበቅ ንፉግነት ስለመሰለኝ እነሆ ብያለሁኝ። መጽሐፉ እስኪወጣም መዳረሻ ይሆናችኋለሁ፡፡