Administrator

Administrator

ከዕለታት አንድ ቀን፣ባልና ሚስት የገና በዓል ፌሽታ ወዳለበት አንድ አደባባይ በመኪና ይሄዳሉ፡፡
“የዘንድሮን ገና በደመቀ ሁኔታ ነው የምናከብረው” አለ ባል፡፡
“እንደሱ እንዳናደርግ እኔ ትላንት የገና ወጪ ስጠኝ ብልህ፣ እንደልማድህ ‹እሱን ለእኔ ተይው› አልከኝ” አለች ሚስት፡፡
“የልጆቹን ፍላጎት አንተ አታውቅም” ብልህ፣ “እንዴት? አባታቸው አይደለሁም?!” ብለህ ትቆጣለህ፡፡ አሁንም የገበያውን ነገር ካወቅኸው ገላገልከኝ”
ጥቂት መንገድ እንደሄዱ፣ አንድ የትራፊክ መብራት ጋ ይደርሳሉ፡፡ ባል ቀይ መብራቱን ጥሶ ይሄዳል፡፡
ትራፊክ ፊሽካ ይነፋል፡፡
ሹፌር ያቆማል፡፡
ለሚስቱ፤
“የዓመት ባል ገንዘብ ፈልጎ ነው እንጂ እኔ ምንም አላጠፋሁም!” ይላታል፡፡
“ቀይ መብራት ዘለህ መጥተህ፣‹እንዴት አላጠፋሁም› ትላለህ?”
“የአንቺን አላምንም፤ትራፊኩ የሚለኝን ልስማ!”
ትራፊኩ መጣ፡፡ ሹፌር መስተዋቱን ዝቅ አደረገ፡፡
ትራፊክ - “መንጃ ፍቃድ?”
መንጃ ፍቃዱን ጠየቀ፡፡
ሹፌር አሳየውና፤ “ምን አጠፋሁ ጌታዬ”
ትራፊክ፤ “ቀይ መብራት ጥሰዋል”
ሹፌር ፤“በጭራሽ አልጣስኩም!”
በመካከል ሚስት ትገባና፤
“እኔ ተው እያልኩት ነው የጣሰው፡፡ ግን ችግሩ እዚህ አገር፣ሰዎች ዶክተር ስለሆኑ የፈለጉትን ማድረግ የሚችሉ ይመስላቸዋል፡፡
ባል፤“ዝም በይ! አፍሽን ዝጊ! … እሺ ትራፊክ ይቅርታ አድርግልኝ”
ትራፊክ፤ “ጥፋትዎ ያ ብቻ አልነበረም፡፡ 30 ኪ.ሜ በሰዓት በሚነዳበት መንገድ፣50 ኪ.ሜ በሰዓት በመንዳትዎ ይጠየቃሉ፡፡”
ሚስት፤
“እኔ ቀስ ብለህ ንዳ ብዬው እምቢ ብሎኝ ነው - ነግሬዋለሁ!”
ባል፤ “አንቺ ሴትዮ፤አፍሺን ዝጊ ብያለሁ!!”
ትራፊኩም፤ “እመቤት፤ሁልጊዜ እንደዚህ ነው የምትወያዩት?”
ሚስት፤
“ኧረ ጌታዬ፤ሌላ ጊዜ ጨዋ ነው፡፡ እንዲህ ሲጠጣ ብቻ ነው እንደዚህ የሚናገረኝ!”
ትራፊክ፤
“አሃ!!”
*   *   *
 አውቃለሁ፣ በቅቻለሁ ብሎ ሁሉ እኔ እንዳልኩት መሆን አለበት የማለት ግትርነት ደግ አይደለም፡፡ የየትኛውም ሙያ ባለቤት እንሁን፡፡ ከህግ በላይ አይደለንም፡፡ በሙያ ክህሎት አገኘን ማለት ከሀገርና ከሀገሬው በላይ ሆንን ማለት አይደለም፡፡ ዝርዝር ጉዳዮች ለዐቢዩ ህግ ተገዢ መሆናቸውን በፍፁም መዘንጋት የለብንም፡፡ የትራፊክ ህግን ማክበር ከሙያችን በላይ የሆነውን ያህል፤ ለትራፊኩ የእኛን ሙያ ማክበር፣ ከሙያው በላይ መከበር እንዳለበት፣ አሊያም እኩል የሙያ አክብሮት ሊኖር እንደሚገባው መገንዘብ እንዳለበት ሊያስተውል ተገቢ ነው፡፡
በቤተሰብ ህግም የባል ሙያ መከበሩ እንዳለ ሆኖ፣ ሚስት የምትለውን አለማዳመጥ ወይም መናቅ ኪሳራ ነው!!
ይህ ነገር በበዓል ሰሞን በጣም ግዘፍ ይነሳል! መደማመጥ በበዓል ሰሞን ምንዛሪው ብዙ ነው። በአንድ ወገን ባህል አለ፡፡ በሌላ ወገን ዘመናዊ ስሜት አለ፡፡ ለምሳሌ፣ በአውሮፓውያን የልደት ዛፍ (X-mas Tree) እና በእኛ ቄጤማና ነጭ አረቄ ስሜት መካከል እንደምንገነዘበው፡፡ በልጆቻችን ላይ የሚፈጠረው ስሜት፣ በወላጆቻችን ላይ የሚደረተው ስሜት፣ ማንም ስለ ምንም ማብራሪ ሳይሰጥ፣ በዘፈቀደ መከበሩና እንደፈረደብን ሳንወያይበት፣ በተድላና በደስታ ማለፋችን፤ የአልፋ - ኦሜጋ ሕግ መሆኑ ግራ ያጋባል፡፡
ባህልን መጠበቅ ግድ ነው፡፡ ባህልን መከለስ ምርጫ ነው፡፡ የሁለቱን ልዩነት ማወቅና ማስተዋል፣ ኃላፊነት የሚሰማው ዜጋ ግዴታ ነው!
የገና በዓልን ስናስብ የክርስቶስን ልደት እናስብ፡፡ የእኛን “ልደት”ን ግን በፍፁም፣ መርሳት የለብንም። በየቀኑ መወለድ፣ በየዕለቱ ማደግ መቼም ያስተዋልነው ጉዳይ ነው፡፡ የየዕለት ውልደታችን ውጤት እገና ዘንድ እሚደርሰው፣ የዓመት ውሎአችንን ጠቅልሎ ነው፡፡ ስለዚህም ከተወለድን አይቀር በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊና ባህላዊ መንፈሱ የተሟላ ልደት ይሆንልን ዘንድ እንመኝ! “ከሰማያተ - ሰማያት ወርጄ፣ ከድንግል ማሪያም ተወልጄ አድንሃለሁ” የሚለውን አስታውሶ፣ በስፋት መጠቀም ነው፡፡ “ሳያዩ የሚያምኑ ብፁዓን ናቸው!” ማለትም ያባት ነው፡፡
በየወቅቱ መወለድ የአዳጊ ልጅ ባህሪ ነው፡፡ እያንዳንዷን እድገት ሳይታክቱ መመርመር ታላቅ ዕድል ነው፡፡ ለመወለድ ሰብዓ ሰገሎችን ሳንጠብቅ፣ ለየራሳችን ስራ፣ ጥረት፣ ትግል፣ ዕምነት ቦታ መስጠት አገርንና ህዝብን ያሳብባል፡፡ በየዕለቱ ሁላችንም አራስ ነን፡፡ ነገ ግን ወጣት፣ ጎልማሳና አዋቂ እንሆናለን፡፡ በሁሉም ገፅታችን አገራችን ትፈልገናለች!!
የለውጥ አቅም ከለመድነው መፋታት ነው፡፡ ከለመድነው መላቀቅ፣ የአዲስ አዕምሮ ቅያስ ይፈልጋል፡፡ ቅያሱ መንገድ የት እንደሚያደርሰን ለማወቅ፣ የእንቅፋቶቹን ምንነት፣ የእኛን ምርጫና ግባችንን ማወቅ፣ የእኛን ቀጣይ - ዘዴ መቀየስ፤ የለውጥ ሙከራ ባይሳካ ደግሞ መዘጋጀት ዋና መሆኑን … ማስተዋል ብልህነት ነው፡፡ ያም ሲለመድ ደግሞ እንደ ህይወት ይኖራል፡፡ “ልማድ ሲሰለጥን ተፈጥሮ ይሆናል” የሚለው አባባል ግንዛቤ ውስጥ ይገባል የሚባለው ይሄኔ ነው!! ሁሉንም በቀናው ሂደት ይባርክልን፡፡ ራሳችንን ከአደጋ እንጠብቅ!
መልካም የገና በዓል
 ለክርስትና ዕምነት ተከታዮች!!

በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የአዕምሮ ህክምና ክፍል ተባባሪ ፕሮፌሰርና የትምህርት ክፍሉ ሃላፊ በሆኑት ዶ/ር ዳዊት ወንድምአገኝ ተፅፎ፣ ባለፈው ሳምንት ለንባብ የበቃው ‹‹አለመኖር›› የተሰኘ መፅሐፍ፤ ዛሬ ከቀኑ 9፡00 ጀምሮ ቦሌ ሩዋንዳ በሚገኘው ባታ የባህል ምግብ አዳራሽ እንደሚመረቅ የፕሮግራሙ አዘጋጅ ክላስ ፕላስ ኤቨንት አስታውቋል፡፡
በምርቃት ሥነስርዓቱ ላይ መፅሐፉ ለውይይት የሚቀርብ ሲሆን የአዕምሮ ሀኪሙ ዶ/ር መስፍን አርአያ፣ የፍልስፍና ምሁሩ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ፣ ደራሲና ጋዜጠኛ ቴዎድሮስ ተ/አረጋይና ወ/ሮ ሶሎሜ ታደሰ በመጽሐፉ ላይ ጥናታዊ ጽሁፍ እንደሚያቀርቡ ይጠበቃል፡፡  

Saturday, 31 December 2016 11:37

የፍቅር ጥግ

 (ስለ ቤተሰብ)

 · በዓለም ላይ ትልቁ ነገር ቤተሰብና ፍቅር ነው፡፡
    ጆን ውድን
· የእኔ ጥንካሬና ድክምቴ፤ ቤተሰቤ ነው፡፡
    አይሽዋርያ ራይ ባችቻን
· ህፃናት የገነት መግቢያ ቁልፎች ናቸው፡፡
    ኤሪክ ሆፈር
· ቤተሰብ ከተፈጥሮ ድንቅ ስራዎች አንዱ ነው፡፡
    ጆርጅ ሳንታያና
· ህፃናት ንስሮች፤ በቤተሰባቸው ክንፍ ፈጽሞ ሊበሩ አይችሉም፡፡
    ሊዩ ያንግ
· የእኔ ምክር፡- ዛሬ ለአንዲት ሰከንድ ቤተሰብህን አመስግን፡፡
     ጄና ሞራስካ
· የሴቶች ተፈጥሮአዊ ሚና የቤተሰብ ምሰሶ መሆን ነው፡፡
     ግሬስ ኬሊ
· ቤተሰብ የሥልጣኔ መሰረት ነው፡፡
     ዊል ዱራንት
· በቤተሰቤ ውስጥ ከትውልድ ወደ ትውልድ፣ ከሰባት ትውልድ በላይ፣ ለ200 ዓመታት ሲተላለፍ የቆየ አንድ ነገር ቢኖር - ተስፋ አለመቁረጥ ነው፡፡ ለሽንፈት እጅ አለመስጠት፡፡ በዚያ መንገድ ነው የምንኖረው፡፡
      ኒክ ዋሌንዳ
· የነበረኝን በሙሉ ሰጥቼአለሁ፡፡ አሁን ከቤተሰቤ ጋር ጥሩ ጊዜ ማሳለፍ እፈልጋለሁ፡፡
       ዲያጎ ማራዶና
· በጣም ሃይማኖተኛ የሆነ ቤተሰብ ውስጥ ነው ያደግሁት፡፡ በ5 ዓመቴ ቁራን በቀላሉ አቀራ ነበር፡፡
       አክህማድ ካድይሮቭ
· ቤተሰቤ አስቂኝ እንደነበር ተገንዝቤአለሁ፤ ምክንያቱም ማንም ሰው ከቤታችን መውጣት አይፈልግም ነበር፡፡
       አንቶኒ አንደርሰን
· በእኛ ቤተሰብ፣ ለአባቴ መልስ ከሰጠሁ፣ ችግር ውስጥ እወድቃለሁ፡፡
      ጆል ኮርትኔይ
· ቤተሰብህን አትመርጥም፡፡ ከእግዚአብሔር የሚቸርህ ስጦታ ነው፡፡
      ዴዝሞንድ ቱቱ
· ቤተሰብ የህይወት መሰረት ነው፡፡ የዘላለም ደስታ ቁልፍም ጭምር፡፡
      ሌ.ቶም ፔሪ

Saturday, 31 December 2016 11:41

የፀሀፍት ጥግ

 - ማንም ሰው እስኪሞት ድረስ ግለ ታሪኩን መፃፍ ያለበት አይመስለኝም፡፡
      ሳሙኤል ጎልድዊን
- የገጣሚ ግለ ታሪኩ ግጥሙ ነው፡፡ የቀረው ሁሉ የግርጌ ማስታወሻ ነው፡፡
      ዬቬጌኒ ዩቭቱሼንኮ
- ‹ህይወቴ› ግለታሪኬ አይደለም፤ ሙዚቃ ነው፡፡
      ሜሪ ጄ. ብሊግ
- ከባለቤቱ ይሁንታ ያላገኘ ግለ ታሪክ እየፃፍኩ ነው።
     ስቲቨን ራይት
- መፅሐፍ አንድም ግለ ታሪክ ነ ው፣ አ ሊያም ረዥም ልብወለድ ነው፡፡
     አይምሬ ኬርቴስዝ
- የወንድ ፊት ግለ ታሪኩ ነው፡ የሴት ፊት የልብ ወለድ ስራዋ ነው፡፡
     ኦስካር ዋይልድ
- የህይወት ታሪክህ ሲፃፍ ብዕሩን ማንም እንዲይዘው አትፍቀድ፡፡
     ሬቤል ትሪቨር
- ይሄ ግለ ታሪኬ አይደለም፡፡ የእስካሁኑን ጉዞዬን ብቻ የሚናገር ነው፡፡
     ሪቱ ቤሪ
- የህይወት ጉዞ አይገመቴ ነው፤ ማንም አስቀድሞ ግለ ታሪኩን ሊፅፍ አይችልም፡፡
     አብርሃም ጆሹዋ ሄሼል
- የህይወት ታሪክህን ስትፅፍ፣ እያንዳንዱ ገፅ ማንም ሰምቶት የማያውቀው ጉዳይ ማካተት አለበት፡፡
     ኤልያስ ካኔቲ

Saturday, 31 December 2016 11:32

የዘላለም ጥግ

 (ዝነኞች በመሞቻቸው ሰዓትየተናገሩት)

- “ወዳጆች ያጨብጭቡ፤ ኮሜዲው አልቋል”
    ሉድዊግ ቫን ቤትሆቨን (ሙዚቃ ቀማሪ)
- “እየሞትኩ ነው፡፡ ለረዥም ጊዜ ሻምፓኝ አልጠጣሁም”
   አንቶን ፓቭሎቪች ቼክኾቭ (ፀሐፊ)
- “ትክክለኛውን ነገር ለመስራት ተጣጥሬአለሁ”
   ግሮቨር ክሌቪላንድ (የአሜሪካ ፕሬዚዳንት)
- “መብራቱን አብሩት፤ በጨለማ ወደ ቤቴ መሄድ አልፈልግም”
    ኦ ኼንሪ (ደራሲ)
- “መብራቱን አጥፉት”
    ቴዎዶር ሩስቬልት (የአሜሪካ ፕሬዚዳንት)
- “ኢየሱስን አየዋለሁ፤ ኢየሱስን ለማየት እሻለሁ”
    ዊትኒ ሂዩስተን (ድምፃዊት)
- “መሞት አልፈልግም” (ሞታ ከመገኘቷ ከ2 ሰዓት በፊት በስልክ የተናገረችው)
    ኤሚ ዋይንሃውስ (ድምፃዊት)
- “ለማንበብ ወደ መታጠቢያ ክፍል እየሄድኩ ነው”
    አልቪስ ፕሪስሊ (ሙዚቀኛ)
- “አያችሁ፤ እንዲህ ነው የምትሞቱት”
    ኮኮ ቻኔል (ፋሽን ዲዛይነር)
- “ለእኔ ጠጡልኝ”
    ፓብሎ ፒካሶ (ሰዓሊ)
- “ዛሬ ማታ በደንብ እተኛለሁ››
    ሔነሪ ፎርድ (የአውቶሞቢል አምራች)
- “ብቻዬን ተዉኝ፡፡ ደህና ነኝ!”
     ባሪ ዋይት (ዘፋኝ)
- “ነገ ፀሐይ ስትወጣ እዚህ አልገኝም”
    ኖስትራዳመስ (ሀኪምና የክዋክብት ተመራማሪ)
- “ከሞት በስተቀር ምንም አልፈልግም”
     ጄን ኦዩስተን (ደራሲ)
- “ሰዓቴ የት ነው ያለው?”
    ሳልቫዶር ዳሊ (ሰዓሊ፣ ፀሐፊና ፊልም ሰሪ)

Saturday, 31 December 2016 11:31

አስገራሚ እውነታዎች!!!

 (ከዝነኞች ህይወት)
ዝነኛው የፊልም ተዋናይ ጃኪ ቻን፤ በ1954 (እ.ኤ.አ) ከድሃ ጥንዶች ነው የተወለደው፡፡ ወላጆቹ ያጡ የነጡ ድሃ ስለነበሩ ለሆስፒታል የሚከፍሉት ገንዘብ አጥተው ልጃቸውን (ጃኪ ቻንን) ለመሸጥ ሁሉ ዳድተው ነበር፡፡ በመጨረሻ ግን ተግተው ሰሩና ለሆስፒታሉ ክፍያ በቂ  ገንዘብ አገኙ፡፡ ዛሬ ጃኪ ቻን የሆሊውድ ተከፋይ ነው፡፡  
ታዋቂው አሜሪካዊ ኮሜዲያን ጂም ኬሪ፤ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን አቋርጦ የወጣው በ16 ዓመቱ ነበር፡፡ ለምን? ትኩረቱን ኮሜዲ ላይ አድርጎ ለመሥራት፡፡  
“Rocky” የተሰኘውን የፊልም ስክሪፕት የጻፈው ዝነኛው ተዋናይ ሲልቪስተር ስታሎን ነበር- ራሱ። ነገር ግን ስክሪፕቱን ሲጽፍ የሚኖርበት ቤት እንኳን አልነበረውም፡፡ ስክሪፕቱን ከመሸጡ ከአንድ ሳምንት በፊት በጣም ተቸግሮ ውሻውን በ50 ዶላር ሸጧት ነበር፡፡ በኋላ ግን መልሶ ገዛት - በ3ሺ ዶላር!! ገንዘብ ከየት ፈሰሰለት? ከስክሪፕት ሽያጩ ነዋ!!
የፊልም ተዋናዩ ሳን ዊሊያም ስኮት፤ ሴቶች ሲያፍርና ሲሽኮረመም አይጣል ነበር፡፡ እንስቶች በአካባቢው ካሉ በጭንቀት ላብ በላብ ይሆናል። በዚህም የተነሳ 30 ዓመት እስኪሞላው ድረስ የሴት ጓደኛ ወይም ፍቅረኛ አልነበረውም፡፡
የፊልም ተዋናዩ ጃክ ኒኮልሰን፤ ዓይናፋርነት አይነካካውም፡፡ ከልጅነቱ ጀምሮ ያሳደጉት  አያቶቹ ነበሩ፡፡ እሱ ግን እውነተኛ ወላጆቹ እንደሆኑ ነበር የሚያውቀው፡፡ እ.ኤ.አ በ1973 ዓ.ም ከ”ታይም” መፅሄት ጋዜጠኛ የሰማው መረጃ ዱብዕዳ ነው የሆነበት፡፡  “እህቱ” እንደነበረች የሚያውቃት ጁን፤ እውነተኛ እናቱ ሆና ተገኘች። በ37 ዓመት ዕድሜው!! ክፋቱ ደግሞ ይሄን እውነት ከመስማቱ በፊት እናቱም ሴት አያቱም ሞተዋል፡፡  
ጄምስ ቦንድን ሆኖ የሚተውነው የፊልም ባለሙያው ዳንኤል ክሬይግ፤ በትወናው ከፍተኛ ዝናና ተወዳጅነት፣ እንዲሁም በሽበሽ ገንዘብ አግኝቷል፡፡ ይሄ ብቻ ግን አይደለም፡፡ በፊልሙ ላይ ሲተውን የሚያሽከረክራትን Aston Martin የተሰኘች አውቶሞቢል የሚያመርተው ፋብሪካ፤ የህይወት ዘመን ስጦታ (መብት) አሽሮታል፡፡ በማንኛውም ጊዜ ደስ ያለውን መኪና (አስቶን ማርቲን ጨምሮ) አስነስቶ መፈትለክ ነው - በቀሪው ህይወቱ ሁሉ፡፡
“ሚስተር ቢን”ን ሆኖ የሚተውነው እንግሊዛዊው ኮሜዲያን ሮዋን አትኪንሰን፤ እንደ አሜሪካዊው ኮሜዲያን ጂም ኬሪ በ16 ዓመቱ ትምህርት አላቋረጠም፡፡ እንደውም ወደ ትወና የገባው በኤሌክትሪካል ኢንጂነሪንግ የማስተርስ ዲግሪውን ከተቀበለ በኋላ ነው-  ከእንግሊዙ ኒውካስትል ዩኒቨርሲቲ፡፡  

 ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ቀበሮ፣ በአንድ ገበሬ ግቢ እየመጣችና የሚያረባቸውን ዶሮዎች እየሰረቀች በጣም ታስቸግራለች፡፡
ገበሬው ለፍቶ ለፍቶ ለቀበሮ መቀለብ ሲሆንበት፣ ከሚስቱ ጋር ለመማከር ይወስንና፤
‹‹ሰማሽ ወይ ውዴ?››
‹‹አቤት ጌታዬ››
‹‹የዚችን የቀበሮ ነገር ምን ብናደርግ ይሻላል?››
‹እኔም ግራ- እየገባኝ ምን እናድርግ ልልህ ነበርኮ››
‹‹አንቺ ምን አሳብ አለሽ?››
‹‹እኔማ ሠፈሩን እንረብሻለን ብዬ ፈርቼ ነው እንጂ፤ መሳሪያ እያለህ አንድ ቀበሮ መግደል ምን ችግር ነበረው?››
‹‹አይ ያሉትን ይበሉ እንጂ ዕውነትም ጠመንጃዬን ወልውዬ አድፍጩ ብጠብቃት አታመልጠኝም›› አለ ፍርጥም ብሎ፡፡
‹‹ግን  እንዲህ ብናረግስ?››
‹‹ምን?››
‹‹ለሰፈሩ አለቃ ብናሳውቅ? ሰውም ጥይት ሲሰማ እንዳይሸበር፣ ለሊቀ መንበሩ ብንነግር?››
‹‹ደግ ሀሳብ አመጣሽ፡፡ አሁኑኑ እነግረዋለሁ፡፡›› አለና ወደ ሊቀ መንበሩ ቢሮ ሄደ፡፡
ሊቀመንበሩ ግን ሀሳቡን አልተቀበለውም፡፡ ይልቁንም፤
‹‹ለምን በወጥመድ አትይዛትም?›› ሲል ጠየቀው፤
‹‹ወጥመድ የለኝም››
‹‹እኔ እሰጥሃለሁ፡፡››
በዚሁ በወጥመዱ ሀሳብ ተስማሙና፣ በገብሬው ወጥመዱን ተረከበ፡፡
ማታም ቀበሮዋ መግቢያ ላይ ወጥመዱን አስቀመጠና መጠበቅ ጀመረ፡፡ ወጥመዱን ያልጠረጠረችው ቀበሮ ዘው ብላ ገባች፡፡ ተያዘች፡፡
ገበሬው በጣም ተደሰተ፡፡ በምን እንደሚቀጣ ያሰላሰለ ጀመር፡፡ በመጨረሻ…
‹‹እንዲያ ስትጫወትብኝ… እንደከረመች በፍፁም አልምራትም›› አለ፡፡
ከዚያም ጭራዋ ላይ ጭድ አሰረና እሳት ለቀቀባት፡፡ ከወጥመዱ አውጥቶም ወረወራት። ቀበሮም ቃጠሎው ሲበዛባት… በአቅራቢያው ወደሚገኘው የገበሬው የበቆሎ እርሻ ገባች፡፡ በቆሎው የደረሰ አዝመራ ነው፡፡ በእሳት ተያያዘ፡፡ ሙሉ በሙሉ ነደደ፡፡
*   *   *
ቂም በቀል የሁለት-ወገን-ስለት አለው፤ ይላሉ ፈረንጆች፡፡ ለሌላው የሳሉት ሰይፍ ወደ ራስ ሊመጣ እንደሚችል ማስተዋል ጥበበኝነት ነው፡፡ ክፋት ማቆሚያ የለውም፡፡ የጥፋተኝነት ስሜቱም አዕምሮን ከመነቆር አይገላገልም፡፡ ‹‹ዳባ ራሱን ስለት ድጉሡን›› ማለት ነው- በአማርኛ አገራዊ እነጋገር፡፡ በሀገራችን የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ዛሬ አንገብጋቢ እሳት ሆኗል- (Burning Issue እንዲሉ) በመልካም አስተዳደር ጉድለት፣ በሥልጣን መባለግ፣ የሀገርንና የህዝብን ጥቅም ለራስ ማዋል፣ ፖለቲካን የግል ንብረት በማድረግ ማስፈራሪያና ‹‹እኔ ብቻ ነኝ አድራጊ ፈጣሪ›› ማለት ወዘተ እጅግ ጎጂ ባህል ሆነው ከርመዋል፡፡ ያደረጉት ነገር በተጨባጭ ስህተት መሆኑ ታውቆ ለፍርድ ይቅረቡ የተባሉ አሉ፡፡ ይበል የተባለ እርምጃ መሆኑን የማይስማማ ያለ አይመስለንም፡፡ ሆኖም ዕውነቱን ፈልፍሎ የማውጣት ሥራ፣ ያለ ምንም ወገንተኝነት ህሊናዊ ንፅህናን የመጠበቁ ኃላፊነት እና የግብረ-አበሮችን ሰንሰለት መርምሮ፣ ፈለጉን የማግኘትን የመበጠስ ዕልህ - አስጨራሽ ጉዞ ሳያሰልሱ የመጓዝን ሂደት ከወዲሁ አስቦና አስልቶ መንቀሳቀስ ወሳኝ ነው። ጅምሮች በአጭር እንዳይቀጩ ከመርማሪ ፖሊስ እስከ ፍትህ አካላት የተባበረ ቅኝት ያስፈልጋቸዋል። ዲሞክራሲ ላጲስ አይደለም፤ ተጋጋዥ እንጂ ተጠፋፊ አይደሉም፡፡ ፖለቲካ የኢኮኖሚ ዕምቅ መገለጫ (Concentrated Expression) እንጂ ሌላ ላንቃ አይደለም፡፡ ሀቀኝነት ሳይኖር ፍትሃዊነት መጎናፀፍ አይቻልም፡፡ ለማኅበራዊ ምስቅልቅልነት መፍትሄው የመንግስትና ህዝብ ተቀራርቦ ሀገራዊ መተሳሰብን መፍጠር እንጂ ‹‹መንግስት ነኝና ልፈራ ይገባኛል›› የሚል አመለካከትና ጉልበታዊ ተግባር አይደለም፡፡ በመንግስት ውስጥ ያሉና ህዝብን በመበደል የሚኩራሩ ወገኖች ጊዜያዊ ድል እንጂ ዘላቂ ወንበር አይኖራቸውም፡፡ ያም ሆኖ እኒህንም አካላት ለፍርድ ሲቀርቡ ያለአድልዎ ዳኝነት የሚሰጥ አካል ሊኖር ይገባል። ህጋዊ ፍርድ በሀቅ ላይ የተመረኮዘ እስከሆነ ድረስ የመልካም አስተዳደር አለመጓደልን የሚያፈካ ብርሀን አለ ማለትን ማመን እንጀምራለን፡፡
የመልካም አስተዳደር ጉዳይ፣ በመልካም አስተዳደር ጉድለት እንዳይጨናገፍ ብርቱ ጥረት ያስፈልጋል፡፡ ሀገራችን የሰው አስተሳሰብ ልማት ያሻታል፡፡ ጠቃሚ የሆነ ነው የምንለውን የመዋቅር ለውጥ ለማምጣት፣ እስከ ቻርተር ማሻሻል ስንዘልቅ ዞሮ ዞሮ ወሳኙ ሁነኛ የሰው ኃይል መሆኑን አንርሳ! ተለውጧል ተሻሽሏል ማለት ብቻ ሳይሆን ከዕውነታው ያልራቀ መፍትሄ መሆኑን ማረጋገጥ ቁልፍ ነገር ነው!
በማናቸውም ግለሰብ ፣ በግል ኢንቬስተሮች፣ በቢሮክራሲ አባላት በንግዱ ማህበረሰብ፣ በሲቪክ ማህበረሰብ አባላት ወዘተ ላይ የምንሰነዝራቸውን ሂሶች፣ ውንጀላዎችና ፍረጃዎች ስናስብ፣ እኛስ ራሳችንን እንዴት እንገመግማለን? እንዴት እንፈርጃለን? እንዴትስ ስህተታችንን እናምናለን? የሚለውን ወሳኝ ጉዳይ ልብ - እንበል! ለዚህ የሚበጀን ዘዴ “ንስሓ ከኃጢአት፣ ውኃ ከእድፍ ያፀዳል!” የሚለውን ምሳሌ ለሊት ተቀን ማሰብ እና ስራ ላይ ማዋል ነው!

 ባለፉት 9 ወራት ብቻ 71 ያህል ዝነኞች ሞተዋል

      የመጨረሻዋ ቀን ላይ በሚገኘው የፈረንጆች አመት 2016፣ ባልተለመደ ሁኔታ ከፖለቲካ እስከ ስፖርት፣ ከፊልም እስከ ሙዚቃ በየሙያ መስኩ እውቅናን ያተረፉ በርካታ ዝነኞችና ታዋቂ ሰዎች ከዚህ አለም በሞት የተሰናበቱበት መሆኑ ተነግሯል፡፡
ሲኤንኤን በአለማቀፍ ደረጃ የተሰራ የጥናት ውጤት ጠቅሶ ሰሞኑን እንደዘገበው፣ እስካለፈው ጥቅምት ወር ድረስ በነበሩት የአመቱ 9 ወራት ብቻ፣ በተለያዩ የሙያ መስኮች ስማቸውን በአለም መድረክ ላይ ማስጠራት የቻሉ ከ71 በላይ የዓለማችን ታዋቂ ሰዎችና ዝነኞች ከዚህ አለም በሞት ተለይተዋል፡፡ ከስፖርቱ አለም ብንጀምር፣ እድሜ የማያዝላቸው፣ ህመም የማይረታቸው ከሚመስሉ ጠንካራ እጆቹ በሚወነጨፉ ቡጢዎቹ ብዙዎችን ያደባየው የአለም የከባድ ሚዛን ሻምፒዮናው መሃመድ አሊ፣ ባለፈው ሀምሌ ወር መጀመሪያ ላይ ነበር በተወለደ በ74 አመቱ ይህቺን ዓለም በሞት የተሰናበተው፡፡
ወደ ፖለቲካው ጎራ ስንል ደግሞ፣ አለማችን በአመቱ ካጣቻቸው ታላላቅ ሰዎች መካከል አንዱ የሆኑትን የቀድሞውን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ጸሃፊ ግብጻዊውን ቡትሮስ ቡትሮስ ጋሊን እናገኛለን። ቡትሮስ ጋሊ በወርሃ የካቲት ነበር በ93 ዓመታቸው በሞት የተለዩት፡፡ አለማችን በዓመቱ ካጣቻቸው ሌሎች ፖለቲከኞች መካከልም የኖቤል የሰላም ተሸላሚውን ሺሞን ፔሬዝን እናገኛለን፡፡ እስራኤልን በፕሬዚዳንትነትና በጠቅላይ ሚኒስትርነት ያስተዳደሩት ፔሬዝ፣ ባለፈው መስከረም ወር መጨረሻ ላይ ነበር በ93 ዓመታቸው ይህቺን አለም በሞት የተሰናበቱት፡፡
መስከረም ላይ ፔሬዝን የወሰደ ጨካኝ ሞት፣ በህዳር ዞሮ መጣና ሌላ የፖለቲካው መስክ ገናና ይዞ ሄደ፡፡ ኮሙኒስት ኩባን ለግማሽ ምዕተ አመት ያህል ያስተዳደሩት ፊደል ካስትሮ ሩዝ፤ በ90 አመታቸው ወደማይቀርበት መሄዳቸው ተሰማ፡፡ ከሙዚቃው መስክ ከተሰሙት አስደንጋጭ መርዶዎች መካከል ከሰሞኑ የተደመጠው የጆርጅ ማይክል ሞት አንዱ ነበር፡፡ ታዋቂው ድምጻዊ ጆርጅ ማይክል፣ በፈረንጆች የገና እለት ከዚህ አለም በሞት የመለየቱ መርዶ ተሰምቷል፡፡ በካንሰር ሲሰቃይ የቆየው እንግሊዛዊው የሮክ አቀንቃኝ ዴቪድ ቦዌም በዚሁ ጦሰኛ አመት ነበር በ69 ዓመቱ ይህቺን አለም በሞት የተሰናበተው፡፡
አመቱ ሊጠናቀቅ ጥቂት ቀናት በቀረበት ሁኔታ አለምን በድንጋጤ ክው ያደረገ ሌላ የመዝናኛው መስክ መርዶ ከሰሞኑ ተሰምቷል፡፡ በ”ስታር ዎርስ” ፊልም ላይ በመተወን የዓለምን ቀልብ ገዝታ የዘለቀቺው የፊልም ተዋናይትና ደራሲ ኬሪ ፊሸር፣ ባለፈው ሰኞ በልብ ድካም ህመም በ60 አመቷ አለምን ተሰናብታለች፡፡

“ልጆች ባሉበት ሁሉ ምግብ ይኑር” በሚል መሪ ቃል፤ ዘላቂ የት/ቤት ምገባ ፕሮግራም ሲያካሂድ የቆየው የኢትዮጵያ ስኩል ሚል ኢንሼቲቭ (ኢ.ስ.ሚ.ኢ)፤ ተግባሩን ወደ አቅም ግንባታ ስራ ለማሸጋገር እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ገልፆ፣ ማዕከሉን ሰቆጣ ለማድረግ ከዋግህምራ ዞን መስተዳደር ጋር በመጪው ማክሰኞ ስምምነት እንደሚፈራረም አስታውቋል፡፡
ህፃናት ተማሪዎችን በየትምሀርት ቤታቸው ሲመግብ የቆየው ማዕከሉ፤ ት/ሚኒስቴር በመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤቶች ተመሳሳይ የምገባ ፕሮግራም መጀመሩን ተከትሎ ቀደም ሲል ድርጅቱ ለምገባ ሲጠቀምባቸው የነበሩ ማዕከላቱን ለሰርቶ ማሳያነት እንዲያገለግሉ በማድረግ፣ ፊቱን ወደ አቅም ግንባታ ማዞሩን ገልጿል፡፡
በዋግምሀራ  ዞን በተከሰተው ድርቅ ሳቢያ አካባቢው ይበልጥ ድጋፍ የሚያስፈልገው  ቢሆንም ረሀብን ማሸነፍ እንደሚቻል የተረጋገጠበት አካባቢ በመሆኑ፣ ዞኑ ለመጪዎቹ 3 ዓመታት የኢ.ስ.ሚ.ኢ የስራ ማዕከል ሆኖ የሚዘልቅበትን ስምምነት እንደሚፈረም ታውቋል፡፡


የኢትዮጵያ የፅንስና ማህፀን ሃኪሞች ማህበር 25ኛ ዓመቱን ያከብራል

የአፍሪካ ፅንስና የማህፀን ሐኪሞች ፌዴሬሽን ጉባዔ፣ በመጪው የካቲት ወር በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ሊካሄድ ነው፡፡  ‹‹ዘላቂ የልማት ግቦች በአፍሪካ የስነ ተዋልዶ ጤና፣ ዕድሎችና ተግዳሮቶች›› ‹‹በሚል መሪ ሃሳብ በሚካሄደው በዚሁ አህጉር አቀፍ ጉባኤ ላይ የተለያዩ ጥናታዊ ፅሁፎች ይቀርባሉ፡፡
የአፍሪካ የፅንስና ማህፀን ሐኪሞች ፌዴሬሽን መስራችና አባል የሆነው የኢትዮጵያ ፅንስና ማህፀን ሃኪሞች ማህበር (ኢሶግ)፤ የተመሰረተበትን 25ኛ ዓመት በአሉን ያከብራል፡፡ ይህንኑ የማህበሩን የብር ኢዮቤልዩ በዓልና አህጉር አቀፍ ጉባዔውን እስመልክቶ ማህበሩ በነገው ዕለት በሒልተን ሆቴል ጋዜጣዊ መግለጫ እንደሚሰጥ ማህበሩ ለአዲስ አድማስ የላከው መረጃ ያመለክታል፡፡ በዚሁ ዕለትም የማህበሩ አባላት የሆኑ የህክምና ባለሙያዎች ደም እንደሚለግሱ ታውቋል፡፡