Administrator

Administrator

በሀገሪቱ በጤናው መስክ የሚታየውን የመረጃ ክፍተት ለመሙላት፣ በዘርፉ ያለውን የእርስ በርስ ግንኙነት ለማጎልበትና ለጤና አገልግሎት ተጠቃሚዎች አመቺ የመረጃ ምንጭ እንዲሆን ታስቦ የተዘጋጀው “ኢትዮ ሄልዝ ዳይሬክተሪ” የተሰኘ የጤና አገልግሎት ማውጫ ከትናንት በስቲያ ተመረቀ፡፡
በዘርፉ በአይነቱ የመጀመሪያ የሆነው ይህ የጤና አገልግሎት ማውጫ፣ በይዘቱ ምሉዕ እና ከሁለት አመት በላይ በፈጀ የመረጃ ስብሰባ የተዘጋጀ ሲሆን መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ የጤና አገልግሎት ሰጪዎችን፣ የሆስፒታሎችን፣ የመድሃኒትና የሕክምና መገልገያ መሳሪያዎች አስመጪዎችን እና ሌሎች ባለድርሻ አካላትን አድራሻ የያዘ ነው፡፡
በደብሊው ኤ ኤች አሳታሚ የተዘጋጀው የጤና አገልግሎት ማውጫው፤ ተደራሽነቱን ለማስፋት ሲባል በመጽሃፍ መልክ ከመቅረቡ በተጨማሪ በድረ ገጽ እና በሞባይል አፕሊኬሽን አማካይነት ተዘጋጅቶ ለተጠቃሚዎች መቅረቡን አዘጋጁ በተለይ ለአዲስ አድማስ ጠቁሟል፡፡  
ማውጫው በአዲስ አበባ እና በመላ የአገሪቱ ክልሎች ለሚገኙ የጤና ተቋማት በነጻ የሚሰራጭ ሲሆን  ለጤና ተቋማት የመረጃ ምንጭ በመሆን የርስ በርስ ግንኙነትን ከማጎልበት ባለፈ፣ ለጤና አገልግሎት ተጠቃሚዎችም የማንኛውም የጤና ነክ መረጃ ምንጭ በመሆን ያገለግላል፡፡
አዘገጃጀቱ ለተጠቃሚዎች ምቹ በመሆኑና መረጃዎቹ በየጤና ዘርፉ ተከፋፍለው የቀረቡ መሆናቸው፣ የጤና አገልግሎት ተጠቃሚው ህብረተሰብ እንደፍላጎቱና እንደችግሩ የሚበጀውን መረጃ በቀላሉ ለማግኘት እንደሚያስችለው አዘጋጁ ገልጸዋል።
በዝግጅቱ የኢፌዲሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር እና የመድሀኒት የምግብ እና የጤና ክብካቤ ባለስልጣንን ጨምሮ በጤናው ዘርፍ የሚሰሩ መያዶች፣ ሌሎች ባለድርሻ አካላትና በዘርፉ ለአመታት የሰሩ አንጋፋ የህክምናው ዘርፍ ባለሙያዎች፣ ተቋማትና የመንግስት አካላት የተሳተፉ ሲሆን፣ በሚቀጥሉት እትሞችም ተደራሽነቱን በስፋት ለማሳደግ እየተሰራ ነው ተብሏል።
በዘርፉ የሚታየውን የመረጃ ክፍተትን በመሙላት ረገድ ጠቀሜታው የጎላ እንደሆነ የተነገረለት የጤና አገልግሎት ማውጫው፣ የኢፌዲሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስትር ልዩ ጽ/ቤት ሃላፊ ዳይሬክተር ጀነራል፣ የጤናው ዘርፍ ባለድርሻ አካላትና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ባለፈው ሃሙስ በኢትዮጵያ ሆቴል በተዘጋጀ ፕሮግራም ላይ በይፋ ተመርቋል፡፡


Saturday, 16 May 2015 10:53

የሰዓሊያን ጥግ

(ስለ ፎቶግራፍ)

ብርሃን ባለበት ሁሉ ፎቶግራፍ ማንሳት ይቻላል፡፡
አና ጊዴስ
ጥሩ ፎቶግራፍ ማለት የቱ ጋ እንደምትቆም ማወቅ ነው፡፡
አንሴል አዳምስ
ፎቶግራፍ ማንሳት ከህይወት ጋር የሚደረግ የፍቅር ግንኙነት ነው፡፡
ቡርክ ዩዝል
አካባቢውን እስክትለቅ ድረስ ካሜራህን አትሸክፍ፡፡
ጆ ማክናሊ
ፎቶግራፍ ማንሳት አንዴ ደም ስርህ ውስጥ ከገባ እንደ በሽታ ነው፡፡
አኖን
እጄ ላይ ካሜራ ሲኖር ፍርሃት አላውቅም፡፡
አልፍሬድ አይዞንስታዴት
የሰውን ፊት በትክክል የሚያየው ማነው? ፎቶግራፍ አንሺው ነው? መስተዋቱ ነው? ወይስ ሰዓሊው?
ፓብሎ ፒካሶ
በአሜሪካ ፎቶግራፍ አንሺ የተከሰተውን የሚቀርፅ ብቻ አይደለም፤ የሚፈጥርም ጭምር እንጂ፡፡
ሱሳን ሶንታግ
ቃላትን አላምንም፤ የማምነው ምስሎችን ነው፡፡
ጊሌስ ፔሬስ
ትኩረቴን የሚስበው ፎቶግራፍ ራሱ አይደለም፡፡ እኔ የምፈልገው የተጨባጩን ዓለም አንድ ደቂቃ ማስቀረት ብቻ ነው፡፡
ሔነሪ ካርቲየር ብሪሶን
ተመልከቱ! ምሁር አይደለሁም - ምስሎችን ብቻ ነው የማነሳው፡፡
ሔልሙት ኒውተን
ድንቅ ፎቶግራፍ የስሜት ጥልቀት እንጂ የመስክ ጥልቀት አይደለም፡፡
ፒተር አዳምስ
የእኔ ተወዳጅ ፎቶግራፎች የትኞቹ ናቸው? ነገ የማነሳቸው!!
አይሞገን ከኒንግሃም
ጥሩ ፎቶግራፍ አንዲትን ቅፅበት ከማምለጥ ይገታታል፡፡
ኢዩዶራ ዌልቲ

ላለፉት አምስት አመታት በአፍሪካ ህብረት የኤርትራ ልኡክ ሆነው ያገለገሉትና ከአገሪቱ ከፍተኛ ዲፕሎማቶች አንዱ የሆኑት አምባሳደር ሞሃመድ ኢድሪስ ጃዊ፤ የኤርትራ መንግስት በዜጎቹ ላይ የሚፈጽመውን ጭቆናና የመብቶች ጥሰት በመቃወም በኢትዮጵያ ጥገኝነት መጠየቃቸውን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
ፍትህና ነጻነትን ለመጎናጸፍ ለዘመናት የታገለው የኤርትራ ህዝብ፤ በኢ-ፍትሃዊ አገዛዝ ስር እየማቀቀ ይገኛል ያሉት አምባሳደሩ፤ ይህም የኤርትራን መንግስት የጭቆና አገዛዝ በመቃወም በኢትዮጵያ ጥገኝነት ለመጠየቅ ውሳኔ ላይ እንዳደረሳቸው ተናግረዋል፡፡
በኤርትራ የነጻነት ትግል ዘመናት በትግል ያሳለፉት አምባሳደር ሞሃመድ፤ኤርትራ ነጻነቷን ከተጎናጸፈች  በኋላም በተለያዩ ከፍተኛ የስልጣን ቦታዎችና በአህጉራዊ የዲፕሎማቲክ ስራዎች ላይ ለአመታት ማገልገላቸው ተነግሯል፡፡
የመብት ተሟጋች ቡድኖችና የተለያዩ ተቋማት፣ የኤርትራ መንግስት በመብቶች ጥሰትና በአስገዳጅ የወታደራዊ አገልግሎት ዜጎቹን እያሰቃየ ነው ሲሉ አገዛዙን ቢተቹም፣ የኤርትራ መንግስት ግን የሚሰነዘሩበትን መሰል የመብቶች ጥሰት ውንጀላዎች በተደጋጋሚ እንደሚያጣጥል አስታውሷል፡፡
የኤርትራ መንግስት ባለስልጣናት በአምባሳደሩ የጥገኝነት ጥያቄ ዙሪያ ያላቸውን አስተያየት እንዲሰጡት ያደረገው ሙከራ እንዳልተሳካለት ሮይተርስ ገልጧል፡፡

የብሪጅስቶን ጎማ አምራች ኩባንያ ምርቱን ተረክበው ለሚያከፋፍሉና ለሚቸረችሩ ደንበኞቹ በመሰረታዊ ጎማ አመራረትና አጠቃቀም እንዲሁም በጎማው መለያ ባህርያት ላይ የግማሽ ቀን ስልጠና ሰጥቷል፡፡
የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረኩን ያዘጋጀው በኢትዮጵያ የብሪጅስቶን ጎማ ወኪል የሆነው ካቤ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ሲሆን በመድረኩ ላይ የብሪጅስቶን ጎማ አምራች ኩባንያ የመካከለኛው ምስራቅና አፍሪካ ተጠሪዎችና ስራ አስኪያጆች እንዲሁም የተለያዩ ሃገራት የኩባንያው ወኪሎች ተገኝተዋል፡፡
ባለፈው ማክሰኞ በሸራተን አዲስ በተካሄደው በዚህ የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረክ ላይ የኩባንያው አዲስ ምርት የሆነው “ኢኮፒያ” የተሰኘ መለያ የተሰጠው የጎማ ምርትም ተዋውቋል፡፡
መድረኩን ማዘጋጀት ያስፈለገው ብሪጅስቶን ጎማ ነጋዴዎች ስለጎማቸው መሰረታዊ እውቀት እንዲያገኙ መሆኑን የጠቆሙት በካቤ ኃ/የተ/የግ/ኩባንያ የብሪጅስቶን ጎማ የቴክኒክ ክፍል ስራ አስኪያጅ አቶ ካሊድ አህመድ፤ ኩባንያው እንዲህ ያሉ የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረኮችን ማዘጋጀቱ ደንበኞች ስለምርቶቹ ይበልጥ እውቀት እንዲያገኙና ምርጫቸው በእውቀት ላይ የተመሰረተ እንዲሆን ያደርገዋል ብለዋል፡፡
ብሪጅስቶን ጎማ ላለፉት 15 ዓመታት በኢትዮጵያ ገበያ የቆየ ሲሆን ከጊዜ ወደ ጊዜም የደንበኞቹ ቁጥር እየተበራከተና የገበያ ድርሻውን እያሰፋ እንደሚገኝ፣ በአለማቀፍ ደረጃም ተመራጭ ጎማ መሆኑን አቶ ካሊድ ተናግረዋል፡፡

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በርዝመቱ ከምስራቅ አፍሪካ ቀዳሚ የሆነውን ህንፃ በአዲስ አበባ ለማስገንባት ከቻይናው የኮንስትራክሽን ኩባንያ ጋር ስምምነት መፈራረሙን ባንኩ አስታወቀ፡፡
ሕንፃው በጋንዲ መታሰቢያ ሆስፒታልና በኢትዮጵያ ሆቴል መካከል ባለው ስፍራ የሚሰራ ሲሆን 198 ሜትር ርዝመትና 43 ወለሎች እንዲሁም 1,500 መኪኖች ማቆም የሚችል 4 ቤዝመንት ወለል እንደሚኖሩት የባንኩ የኮሙኒኬሽን ሥራ አስኪያጅ አቶ ኤፍሬም መኩሪያ ገልፀዋል፡፡
ከዋናው ሕንፃ ጎን ሁለት ባለ 5 ፎቅ ሕንፃዎች እንደሚገነቡ የጠቀሱት አቶ ኤፍሬም፤ አንዱ የኮሜርሻል ሴንተር፣ ሁለተኛው የስብሰባ ማዕከል ነው ብለዋል፡፡ ትልቁ የስብሰባ አዳራሽ 2000 ሰዎች የመያዝ አቅም ሲኖረው፣ ሌሎቹ አዳራሾች 300 ሰዎች 5 አዳራሾች ደግሞ 200 ሰዎች እንደሚይዙና የዘመኑ የቴክኖሎጂ ውጤት የሆኑ መሳሪያዎች እንደሚገጠሙላቸው ጠቁመው ግንባታው ከሜይ 2015 ጀምሮ በ4 ዓመት ውስጥ እንደሚጠናቀቅ አቶ ኤፍሬም ተናግረዋል፡፡

“ጮሃ የማታውቅ ወፍ እለቁ እለቁ ትላለች” - ሀገርኛ ተረት
አንዳንድ ታሪክ ሲውል ሲያድር እንደ ተረት ይወራል፡፡ ኢሮብ ትግራይ ውስጥ የምትገኝ አንዲት ወረዳ ናት፡፡ ተራራማ መልክዐ - ምድር ያላት ስትሆን ኢሮብ የሚባል ብሔረሰብ ይኖርባታል፡፡ የነደጃች ሱባጋዲስ (ማሸነፍን አበልፃጊ እንደማለት ነው) አገር ናት፡፡
በዚች አገር የሚታወቀው አንድ የነዋሪው ልማዳዊና ባህላዊ ጠባይ፣ መቻል፣ መታገሥና ሁሉን እኩል ማስተናገድ ነው፡፡ ህንፃም ልጅ ቢሆን፡፡ በሠርግ ወቅት የሚታደል ማንኛውም ነገር እንኳ ለልጅም እኩል ይደርሳል፡፡ ከተማይቱ ለጦርነት አመቺ ከሆኑት እንደ አሲምባ ተራራ እና አይጋ (ሻቢያ በጣም የተመታበት ቦታ) አሊቴና (ዳውሃን) ዓይነት ቦታዎች አካባቢ በመሆንዋ የደርግ ጦር፣ የኢዲዩ ጦር፣ የኢህአፓ ጦር፣ የህወሓት ጦር፣ አንዳንዴም የህዝባዊ ግንባር ጦር ወዘተ ኃይሎች እንደመተላለፊያ በየጊዜው እየመጡ ይሰፍሩባት ነበር ይባላል፡፡
ህዝቡ እነዚህን ኃይሎች በአግባቡ፣ ሳያጋጭና ሳያጣላ፤ አንዱን በፊት ለፊት አንዱን በጀርባ/ በጓሮ አስተናግዶ ኮሽ ሳይልበት ይሸኛቸዋል፡፡ ለኢሮብ ውይይት ዋና ባህል ነው፡፡ ህዝቡ የአገር ሽማግሌ ይኖረዋል፡፡ የእድር ዳኛ፣ የማህበር መሪ፣ የጎበዝ አለቃ ወዘተ እንደሚባለው ዓይነት የበሰሉ፣ ብልህነት የተዋጣላቸውና ህዝቡ እህ ብሎ የሚያዳምጣቸው አባት (አቦይ) ይኖሩታል፡፡
በአንድ ወቅት በዚሁ በኢሮብ አካባቢ ከፖለቲካ ንቅናቄ ድርጅቶች አንዱ ይመጣል፡፡ ህዝቡን ሰብስቦ እንደተለመደው ሰበካ ያደርጋል፡፡ ህዝብን ወክለው አቦይ ንግግር ያደርጋሉ፡፡ ጥያቄም ይጠይቃሉ፡፡
የንቅናቄ ቡድኑ አባላት በአቦይ ንቃትና አንደበተ ርቱዕነት ይደመማሉ፡፡ አቦይን በንቅናቄው ፖለቲካ ቢያጠምቋቸው የኢሮብ ህዝብ ላይ ትልቅ የፖለቲካ ተፅዕኖ ሊፈጥሩ እንደሚችሉ ገመቱ፡፡
ስለዚህም፤ አቦይን ለአሥራ አምስት ቀናት ወስደው የፖለቲካ ፕሮግራማቸውን ቢያስተዋውቋቸው ትልቅ ሥራ እንደሚሰሩላቸው ወሰኑ፡፡ አቦይን ይዘዋቸው ሄዱ፡፡ አቦይ ውይይቱን ተካፈሉ፡፡ ግምገማውን አዳመጡ፡፡ ትምህርቱን ቀመሱ፡፡
“አቦይ እየገባዎት ነው?” ይላል አንዱ ካድሬ፡፡
“አሳምሬ” ይላሉ አቦይ፡፡
ሌላው ሰበካውንና ገለፃውን ይጨርስና፣
“እህስ አቦይ! እየተከታተሉ ነው ትምህርቱን?”
“እንዴታ!” ይላሉ አቦይ፡፡
ሌላው ይቀጥላል፡፡
“አቦይ ዓላማችን ገባዎት?”
“አዎን”
“ፕሮግራማችን በዝርዝር ፍንትው ብሎ ታየዎት?”
“እጅግ! እጅግ!” ይላሉ፡፡
የአሥራ አምስቱ ቀን የአቦይ ንቃት ፕሮግራም አለቀ፡፡ ከዚያ አለቃው ካድሬ፤
“ይበሉ እንግዲህ አቦይ፣ ወደ ኢሮብ ጎሣ ይሂዱና እስካሁን የተማሩትን ያስተምሩ” አሉ፡፡
አቦይ አመስግነው ወደ ኢሮብ ተመለሱ፡፡
የኢሮብ ህዝብ ተሰብስቦ ጠበቃቸውና፤
“እሺ አቦይ ምን ተምረው መጡ?” አላቸው
አቦይም እንዲህ መለሱ፣
“ይገርማችኋል ወገኖቼ፣ የተማርኩት ስለዲሞክራሲ ነው፡፡ እናም በጣም ያስደሰተኝ ነገር በዲሞክራሲ ዝም ማለትም ይቻላል!” ብለው አጠቃለሉ፡፡
*       *      *
ብልህ ህዝብ ብልህ ዘመን ይሰራል፤ ይላሉ አበው፡፡ የተነሳበትን ቦታና ሁኔታ የማያውቅ ህዝብ የት እንድደደረሰ ለመገንዘብም ልብና ልቡና ያንሰዋል፡፡ የህዝብን ዐይን ይገልጣሉ፣ ያንቀሳቅሱታል የሚባሉ ማህበራት፣ ድርጅቶችና ፓርቲዎች፣ የነቁ፣ የተቡ፣ ሥነ - ምግባር የተላበሱና ከሁሉም በላይ አርቀው ማስተዋል የሚችሉ ሊሆኑ ይገባል። ታግለው የሚያታግሉ፣ ነቅተው የሚያነቁና የተደራጀ ህዝብ የሚከተላቸው መሆንም አለባቸው፡፡ ሥርዓትን መውለድ፣ ሥርዓታዊ አስተዳደርን ማበልፀግ አለባቸው፡፡ ገብረ ህይወት ባይከዳኝ ያሉትን እዚህ ላይ መጥቀስ አግባብነት አለው፡-
“አዕምሮ የሌለው ህዝብ ሥርዓት የለውም፡፡ ሥርዓት የሌለው ህዝብም የደለደለ ኃይል የለውም፡፡ የኃይል ምንጭ ሥርዓት ነው እንጂ የሠራዊት ብዛት አይደለም፡፡ ሥርዓት ከሌለው ሰፊ መንግስት ይልቅ ትንሽ ከተማ ሞያ ትሰራለች፡፡”
ሥርዓታዊ አስተዳደር ሲባል፣ ከሁሉም በላይ ገዢም ተገዢም የሚዳኙበትና የሚያከብሩት ደንብ ማለት ነው፡፡
ህዝብን የማያዳምጥ ፓርቲም ሆነ መንግስት ዕድሜ አይኖረውም፡፡ እኔ ያልኩት ብቻ ነው ትክክል ማለትም ብዙ መንገድ አያስኬድም፡፡
ፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴ እንዲህ ይሉናል፡- “እንደ ኢትዮጵያ ላሉ ደሀና ደካማ ሀገሮች ትልቁ አደጋ እንዲህ ያለ መንግስት ዘፈኔን ካልዘፈናችሁ፣ እስክስታዬን ካልወረዳችሁ እያለ ክብራቸውን ከመንካትም አልፎ ማለቅያ ወደ ሌለው ጦርነትና ውጥረት ውስጥ እንዳያስገባቸው ነው፡፡ በአሜሪካ ዳፋ ኢትዮጵያ ከዐረቦችና ሙስሊሞች ጋር ተጣላች ማለት፤ ከውጪም ከውስጥም በእሳት ስትለበለብ ኖረች ማለት ነውን፡፡ (ምን ዓለምን? የት ደረስን? ወዴትስ እያመራን ይሆን?)
ትውልዶች ያለሙት ዒላማ በየለውጡ ኩርባ (turning point) መመርመር አለበት፡፡ ምን ምን የሰመረ ነገር ታየ? ምን አጋጣሚ ተሳተ? ምን ምን ሥተት ተሰራ? ምን ላይ ፈር ቀደድን? ምን ላይ ባቡሩ ሐዲዱን ሳተ? ማለት ይገባል፡፡
የሄድንበት መንገድ አንዱ ችግር ቃልና አፈፃፀም አለመጣጣማቸው ነው፡፡ “በተለይ መብትን በተመለከተ፡፡ በሕገ - መንግሥት የተረጋገጡ መብቶች በተግባር ሲሻሩ ይታያሉ፡፡” ይላሉ ፀሐፍት በተደጋጋሚ፤ ስለ አፈፃፀም ችግር ሲያወጉ፡፡
ማንም ይፈፅመው ማን፤ ከየትኛውም ሀረግ ጋር ይጠላለፍ፤ ሙስናን መዋጋት ሌላው ግዴታችን ነው፡፡ እነ እገሌ ካሉበት ሙስናውን ማጋለጥ አደገኛ ነው እያሉ ገሸሽ ማለት ይሄው እዚህ አድርሶናል፡፡
“ኢትዮጵያ አንዴ በመደብ ስትመራ፣ አንዴ በብሔረሰብ ስትመራ ቆይታ፣ ወደፊት እጣ ፈንታዋ ከነዚህ ሁሉ የከፋው የሃይማኖት ጦርነት እንዳይሆን የብዙ ተመልካቾች ሥጋት ነው!” ይላሉ ፀሐፍት፡፡ የሃይማኖትን አያያዝ ማወቅ ዋና ነገር መሆኑ ብቻ ሳይሆን ከጀርባው ያሉትንም ኃያላን ነቅቶ ማየት እጅግ ወሳኝ ነገር ነው፡፡ ጠንቀቅ እንበል፡፡
የሀገራችን ሌላው አስገራሚ ነገር ህዝብ ያደነቀውና ሆይ ሆይ ያለለት ታጋይ (ልክም ይሁን አይሁን) ሲገል ቆይቶ አንድ እክል ከገጠመው እንዳልነበር መረሳቱ ነው፡፡ ያላንተ ማናለን ሲባል የነበረ ታጋይ፣ መሪ ወይም ንቁ ሰው፤ ሲታሰር ወይም ካገር ሲወጣ ከአዕምሮአችን ጨርሶ ለመውጣት ሁለት ሳምንት አይፈጅበትም፤ ፈፅሞ ይረሳል፡፡ ያውም ምን አቅብጦት እዛ ነገር ውስጥ ገባ? ተብሎ ካልተተቸ ነው! ይሄ እንግዲህ ከዓመታት በፊት የተሰውለትን ሳይጨምር ነው!
ሌላው በእስከዛሬው መንገዳችን ያየነው ጉዳይ፣ የጠቅላይ ገዢነት አመለካከት ነው፡፡ በዝግ ባህላችን ላይ ይሄ ሲታከልበት “በደምባራ በቅሎ፣ ቃጭል ጨምሮ ነው!” ከዚህ ይሰውረን!
ፕሮፌሰር ባህሩ በዚያው ፅሑፋቸው፤ “ሁሉን አውቃለሁ ከማለት የሌሎችንም ሀሳብ ለማዳመጥ ዝግጁ መሆን፣ ሁሉንም ጠቅልዬ ልያዝ ከማለት ለመጋራት መዘጋጀት፣ ከሁሉም በላይ በስሙ የምንገዳደልበት ሰፊ ህዝብ የሚበጀውን አሳምሮ እንደሚያውቅ ተገንዝበን ከሱ መሬት የቆነጠጠ እውቀት ለመማር ዝግጁ መሆን ይኖርብናል፡፡” … በኢኮኖሚውም ረገድ፡፡ “የተማረ የሰው ኃይላችንን ተንከባክቦ መያዝ፣ ለግሉ ክፍለ ኢኮኖሚ ሰፊ ዕድል መስጠት የዕድገታችን መሰረት ነው… ከእርሻ ኢኮኖሚ ያገኘነው ቋሚ ድህነትንና ተደጋጋሚ ረሀብን ብቻ ነው፡፡ የትም ያላደረሰንን በጥቃቅን የገበሬ ማሳዎች ላይ የተመሰረተውን የእርሻ ኢኮኖሚ ትተን ወደ ኢንዱስትሪያል ኢኮኖሚ በፍጥነት የምንሸጋገርበትን ስልት ስናወጣ ነው የምናድገው” ይሉናል፡፡ የሰብዓዊ መብቶችም ሆኑ የዲሞክራሲ መብቶች በልካችን እንዲሰፉ የታሰበ እለት “መላው ቀለጠ!” “ገደደ!” ማለት ብቻ ነው የሚተርፈን፡፡ የመናገርና ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት የምንታገልለት፣ ሳናሰልስ የምንጮህለት፣ መቼም ወደ ኋላ የማንልበት ጉዳይ ቢሆንም፣ የማይጥመን ነገር ካለ፣ የአቦይን በሳል አስተሳሰብም እንጋራለን “በዲሞክራሲ ዝም ማለትም ይቻላል!” እንላለን፡፡  

የአለም የጤና ድርጅት ባወጣው መረጃ በአለማችን ላይ እድሜያቸው ከ15-49 የሆነ 340/ ሚሊዮን
ሰዎች በመራቢያ አካላት ኢንፌክሽን እንዲሁም በተለያዩ የአባላዘር በሽታዎች እንደሚያዙ ቁሟል። ይህ የመራቢያ አካላት ኢንፌክሽን እንደኛ ባሉ ታዳጊ ሀገራት ትልቁን ቁጥር የሚሸፍን የስነተዋልዶ ጤና ችግር እንደሆነም በተለያየ ግዜ የሚወጡ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡የመራቢያ አካላት ልክ እንደ ሌሎች የሰውነት ክፍሎቻችን ሁሉ በተለያየ ግዜ እና አጋጣሚ ተለያዩ በሽታዎች ሊጠቁ ይችላሉ፡፡ በተለያየ ምክንያት የሚፈጠሩ ኢንፌክሽኖች ወይም በህክምናው ሳይንስ RTIs (Reproductive tract infections)  ለዚህ ተጠቃሽ ናቸው፡፡ዛሬው ፅሁፋችን በእነዚህ በመራቢያ አካላት ላይ በሚከሰቱ ኢንፌክሽኖች እንዲሁም የአባላዘር ሽታዎች ዙሪያ ባለሙያ አነጋግረን ያገኘነውን ምላሽ እንዲህ ልናስነብባችሁ ወደናል፡- ለዛሬ ያነጋገርናቸው ባለሙያ ዶክተር መብራቱ ጀንበር ይባላሉ፡፡ ዶክተር መብራቱ በብራስ የእናቶች እና ህፃናት ሆስፒታል የማህፀንና ፅንስ ሀኪም ናቸው። የምናወራው በመራቢያ አካላት ላይ
በሚከሰቱ ኢንፌክሽኖች ዙሪያ ነውና በአጠቃላይ የስነተዋልዶ አካላት ስንል የትኛውን የሰውነት ክፍል የሚያጠቃልል ነው? ብለን በቅድሚያ ላነሳንላቸው ጥያቄ የሚከተለውን ማብራሪያ ሰጥተውናል፡፡
“...የስነተዋዶ አካል ስንል በሴት በኩል የሴት ብልትን እና የማህፀን ክፍሎችን ባጠቃላይ እንዲሁም ልጅ  ከተወለደ በኋላ ወተት በማመንጨት የሚያገለግሎ ጡቶችንም ይጨምራል፡፡ በወንድ በኩል ደግሞ የወንድ ልጅ ብልት አለ የዘርፍሬዎች እንዲሁም ሌሎች ሆርሞን በማመንጨት የሚያገለግሉ እጢዎች አሉ፡፡ እነዚህ በሙሉ ከስነተዋልዶ ጋር  ቀጥተኛ የሆነ ግንኙነት ያላቸው የሰውነታችን ክፍሎች ናቸው፡፡” የስነተዋልዶ አካላትን የሚያጠቁ ኢንፌክሽኖች በብዛትም ሆነ በአይነት እጅግ በርካታ ሲሆኑ በእነዚህ የሰውነት ክፍሎች ላይ በሚፈጠር ባክቴሪያ መንስኤነት የሚከሰቱ እና በግብረስጋ ግንኙት አማካኝነት የሚተላለፉ የአባላዘር በሽታዎች በሚል በሁለት እንደሚከፈሉ ባለሙያው ይናገራሉ፡፡ “...የስነተዋልዶ አካላትን የሚያጠቁ የኢንፌክሽን አይነቶች በጣም ብዙ ናቸው ነገር ግን በዋናነት በሁለት ከፍለን ልናያቸው እንችላለን፡፡ አንደኛው በጥገኛ ህዋስ ወይም ባክቴሪያ አማካኝነት የሚመጣ ሲሆን ሌላኛው ደግሞ በግብረስጋ ግንኙነት የሚተላለፉ የበሽታ አይነቶች ወይንም sexually  transmitted infections ተብለው የሚጠሩት ናቸው፡፡”ምንም እንኳን ሁሉም አይነት ኢንፌክሽኖች የተለያየ የጤና ችግር የሚያስከትሉ ቢሆንም ትልቁ ትኩረት መሰጠት ያለበት በግብረስጋ ግንኙት አማካኝነት ሊተላለፉ የሚችሉት የበሽታ አይነቶች ላይ ነው ይላሉ ዶክተር መብራቱ፡፡ ለዚህም በምክንያትነት የሚያነሱት እነዚህኞቹ የኢንፌክሽን አይነቶች ብዙውን የህብረተሰብ ክፍል የሚያጠቁ እና በግብረስጋ ግንኙነት አማካኝነት ተላላፊ መሆናቸውን ነው፡፡ ስለዚህም ይላሉ ዶክተር፡-
“..ስለዚህ sexually transmitted infections  ወይንም በግብረስጋ ግንኙነት አማካኝነት ሊተላለፉ የሚችሉ የበሽታ አይነቶች የትኞቹ ናቸው? እንዴትስ መከላከል ይቻላል? በሚሉት ጉዳዮች ላይ ትኩረት ሰጥቶ መስራት እና በህብረተሰቡ ዘንድ ግንዛቤ መፍጠር ያስፈልጋል፡፡”አንዳንዶቹ የኢንፌክሽን አይነቶች ከማህፀን ውጨኛው ክፍል አንስቶ በተለያዩ የማህፀን ክፍሎች ላይ ሊዛመቱ የሚችሉ ሲሆን በማህፀን ውጫዊ ክፍል ላይ ብቻ ተከስተው በህክምና ክትትል ወዲያው ሊጠፉ የሚችሉም አሉ፡፡  “...vulval area ወይንም ደግሞ የብልት የውጨኛውን ክፍል ሊያጠቁ የሚችሉ ወይም ቆዳው ላይ ብቻ የሚወጡ አንዳንድ ኢንፌክሽኖች አሉ፡፡ ነገር ግን ከእነዚህ የውጪውን አካል ከሚያጠቁ ኢንፌክሽኖች መካከል የውስጠኛውን ክፍልም ሊያጠቁ የሚችሉ ይኖራሉ፡፡ ለምሳሌ ፈንገስ የምንለው የውጪውን ክፍል ከማሳከኩ እና ከማቅላቱ በተጨማሪ የውስጠኛው ክፍል ላይም ከፍተኛ የሆነ የማሳከክ ስሜት ያመጣል፡፡ በተጨማሪም ነጭ የሆነ አይብ የመሰለ ፍርፍር የሚል አይነት ፈሳሽ ይኖረዋል፡፡ ይህ በብዛት የሚከሰት የፓራሳይት አይነት ሲሆን በተለይ በእርግዝና ሰአት በጣም ይበዛል፡፡     በተቃራኒው ደግሞ በውስጠኛው የማህፀን ክፍል ላይ የሚከሰቱ የኢንፌክሽን አይነቶችም  አሉ፡፡ ለምሳሌ የግብረ ስጋ ግንኙነት በመልካም ሁኔታ እንዲካሄድ ሊያደርጉ የሚችሉ እርጥበት የሚያወጡ እጢዎች መውጫ በር ላይ የሚፈጠሩ የኢንፌክሽን አይነቶች አሉ። በዚህም ምክንያት የፈሳሽ መውጫ ቀዳዳው ይጠባል ወይም ይዘጋል፡፡ ይህም በብልት አካባቢ እብጠት ለሚያመጣው Bartholin’s cyst ወይም Bartholinitis  ለሚባለው ኢንፌክሽን መፈጠር ምክንያት ይሆናል፡፡”ሌሎች በቫይረስ አማካኝነት  የሚተላለፉ የኢንፌክሽን አይነቶችን ሲያብራሩም፡-  “ሌሎች ልክ እንደ chancroid, wart  ወይም ደግሞ papillomavirus  ወይም ኪንታሮት በመባል የሚጠራው አይነት  በቫይረስ አማካኝነት የሚተላለፉ  ኢንፌክሽኖች አሉ፡፡ እንዲሁም ደግሞ Herpes zoster  ወይም ደግሞ Herpes simplex የሚባል አለ፡፡ ይህም በቫይረስ የሚተላለፍ ሲሆን የብልት ውጨኛውን አካባቢ ያቆስላል፡፡” በባክቴሪያ አማካኝነት ከሚከሰቱት ይልቅ በግብረስጋ ግንኙነት አማካኛነት የሚመጡት ኢንፌክሽኖች  በይበልጥ ወንዶችን ያጠቃሉ ይላሉ ዶክተር መብራቱ፡፡
“...በወንዶች ላይ ባክቴሪያል ኢንፌክሽን የተለመደ አይደለም፡፡ ነገር ግን ወንዶች በግብረስጋ አማካኝነት በሚተላለፉ የኢንፌክሽን አይነቶች በብዛት ሲጠቁ ይስተዋላል፡፡ በተለይ Gonorrhea እና syphilis,  የምንላቸው የአባላዘር በሽታዎች ዋነኞቹ ናቸው። በተጨማሪም ከርክር ወይም chancroid, wart  እንዲሁም ደግሞ papillomavirus     የምንላቸውም ሊከሰቱ ይችላሉ፡፡”በፈረንጆቹ 2008 በናይጄሪያ የተደረገ አንድ ጥናት የግብረ ስጋ ግንኙነት እንዲሁም ደካማ የሆነ የንፅህና አጠባበቅ 44.6% የሚሆነውን የበሽታው መተላለፊያ መንገድ እንደሚይዝ ጠቁሟል፡፡“...መተላለፊያ መንገዱ አብዛኛውን ግዜ የሰውነት አቅም መድከም ነው፡፡ በተጨማሪም ከፍተኛ የጣፋጭ ይዘት ያላቸው ምግቦች ወይም መጠጦች ማዘውተር እና አብዝቶ መጠቀም በሽታው የሚኖረውን ተጋላጭነት ሊጨምር ይችላል፡፡ እንዲሁም አዘውትረው ብልታቸውን የሚታጠቡ ሴቶች ይህ ችግር ሊያጋጥማቸው ይችላል። የብልት ተፈጥሯዊ እርጥበት ታጥቦ መወገድ የለበትም
ምክንያቱም ብልት የእራሱ የሆነ በሽታ ተከላካይ ፈሳሽ አለው፡፡ ይህ መከላከያ ደግሞ አላስፈላጊ
ፓራሳይቶችን ያጠፋል፡፡ ስለዚህ የብልት አካባቢ ቢያንስ በቀን ሁለት ግዜ ጠዋትና ማታ ከታጠበ በቂ ነው፡፡ ሌሎቹ የኢንፌክሽን አይነቶች ደግሞ ቀደም ሲል እንደ ገለፅኩት በግብረስጋ ግንኙነት አማካኝነት የሚተላለፉ     ናቸው፡፡ ለዚህም እንደ Gonorrhea, syphilis, Trichomoniasis እንዲሁም papillomavirus የመሳሰሉትን መጥቀስ ይቻላ፡፡” አብዛኞቹ በባክቴሪያ አማካኝነት የሚመጡት ኢንፌክሽኖች ከግል ንፅህና ጉድለት ወይም ተገቢውን የንፅህና አጠባበቅ ባለመከተል የሚከሰቱ መሆናቸውንም ጨምረው ይገልፃሉ፡-
“ከሰገራ ጋር የሚወጡ በጣም አጥቂ የሆኑ ህዋሳቶች አሉ በጣም በብዛት የሚገኘው Escherichia coli  ወይም E. coli  የምንለው  የባክቴሪያ አይነት ነው፡፡ ይህ ባክቴሪያ በማህፀን አካባቢ ሲገኝ የማህፀን ኢንፌክሽን እንዲሁም የሽንት መተላለፊያ ቱቦ ኢንፌክሽኖችን ያመጣል፡፡ ስለዚህ በተቻለ መጠን የግል ንፅህና አጠባበቅ ስልቱን ማወቅ ያስፈልጋል ወይም ደግሞ የጤና ባለሙያ ጋር በመሄድ እንዴት ባደርግ ነው እነዚህን ኢንፌክሽኖች መከላከል የምችለው የሚለውን በተመለከተ የምክር አገልግሎት መቀበሉ በጣም ጥሩ ይሆናል፡፡” የዚህ አይነት የስነ ተዋልዶ ጤና ችግሮች ተገቢው ህክምና ካልተደረገላቸው ለመሀንነት፣ ከመሀፀን ውጪ ለሚፈጠር እርግዝና ብሎም ለኤች አይቪ ቫይረስ የማጋለጥ እድላቸው ከፍተኛ ነው፡፡ ችግሩ እየተባባሰ ከሄደም ለሞት መዳረጋቸው አይቀሬ ነው ብለዋል ዶ/ር መብራቱ ጀምበር፡፡ “...እነዚህ ኢንፌክሽኖች እስከ ሞት ደረጃም ሊያደርሱ ይችላሉ፡፡ ምክንያቱም ኢንፌክሽኑ ሀይለኛ እየሆነ በሄደ ቁጥር ወደ ሌሎች የሰውነታችን ክፍሎች መዛመቱ አይቀርም፡፡ ሌላው ያልጠቀስነው ደግሞ ኤችአይቪም ነው፡፡ ኤች አይቪም እንደዚሁ በግብረስጋ ግንኙነት ነው።  ምንም እንኳን የግብረስጋ ግንኙነት ብቻ የመተላለፊያ መንገዱ ባይሆንም በግብረስጋ ግንኙነት የመተላለፍ ሀይሉ ከፍተኛ ነው፡፡ ስለዚህ ችግሩ እየጠና ሲሄድ     ህክምና በወቅቱ ካልተገኘ የመሞት አጋጣሚም ይኖራል።”

Monday, 11 May 2015 09:02

የፍቅር ጥግ

ከሁሉም ጣፋጩ ድምፅ ያፈቀርናት ሴት ድምፅ ነው፡፡
ዣን ዲላ ብሩዬር
የመጀመሪያ ዕይታዬ የሚያርፈው በልብሽ ላይ ነው፡፡
ጆሃን ኤፍ ሲ ሺለር
አበባ ያለ ፀሐይ ብርሃን እንደማያብበው ሁሉ፣ ሰውም ያለ ፍቅር መኖር አይችልም፡፡
ማክስ ሙለር
ለዓለም አንድ ሰው ነሽ፤ ለእኔ ግን ዓለሜ ነሽ፡፡
ያልታወቀ ደራሲ
አፍቅሪኝ፤ ያኔ ዓለም በሙሉ የእኔ ትሆናለች።
ዴቪድ ሪድ
አንድ ቃል ከህይወት ሸክምና ስቃይ ነፃ ያወጣናል፡፡ ያ ቃል “ፍቅር” ነው፡፡
ሶቅራጦስ
ህይወትን ውደዳት፤ ህይወት መልሳ ትወድሃለች፡፡ ሰዎችን ውደዳ    ቸው፤ እነሱም መልሰው

ይወዱሃል፡፡
አርተር ሩቢንስቴይን
መሳሳም ጨዋማ ውሃ እንደ መጠጣት ነው። በጠጣህ ቁጥር ጥምህ ይጨምራል፡፡
የቻይናውያን አባባል
ስሞሽ (Kissing) የፍቅር ፊርማ አይደለምን?
ሔነሪ ፊንክ
ደስተኛ ትዳር ያፈቀርነውን ስናገባ ይጀምራል፤ ያገባነውን ስናፈቅር ደግሞ ያብባል፡፡
ቶም ሙሌን
የደስታን ሙሉ ጣዕም ለማግኘት፣  የምታካፍሉት ሰው ሊኖራችሁ ይገባል፡፡
ማርክ ትዌይን
በጣቶቻችሁ መካከል ያሉት ክፍት ቦታዎች የተፈጠሩት በሌሎች ጣቶች እንዲሞሉ ነው፡፡
ማንነቱ ያልታወቀ ፀሐፊ
በህይወት ውስጥ አንድ ደስታ ብቻ ነው ያለው፡፡ ይኸውም ማፍቀርና መፈቀር ነው፡፡
ጆርጅ ሳንድስ
መውደድን የምንማረው በመውደድ ብቻ ነው፡፡
አይሪስ ሙርዶክ
ፍቅር ሰዎችን ይፈውሳል - ሰጪውንም ተቀባዩንም፡፡
ካርል ኤ. ሜኒንገር
ጥላቻ በጥላቻ አይሻርም፤ በፍቅር ብቻ እንጂ፡፡ ይሄ ዘላለማዊ ህግ ነው፡፡
ቡድሃ
በፍቅር ለሚወድቁ ሰዎች ስበት ተጠያቂ አይደለም፡፡
አልበርት አንስታይን
ፍቅር ህይወት ነው፡፡ ፍቅር ካመለጠህ፣ ህይወትም ያመልጥሃል፡፡
ሊዮ ቡስካግልያ

Monday, 11 May 2015 08:55

መርዶ ባደባባይ

በአገራችን ባህል እኛ የምናውቀው፡-
    በሌሊት ነበረ ሰው ለቅሶ ‘ሚያረዳው,
    ተረጂው ሳይሰማ፣ በምስጢር ተይዞ ጎረቤት መክሮበት
    ለዚሁ እሚመጥን አንጋፋ ተመርጦ ዕድር ያመነበት፤
    በሥርዓት ነበር፣ ሰው መርዶ እሚረዳው
    ሃዘንተኛም ሰምቶ በወጉ ነበረ እርሙን የሚያወጣው፡፡
        ዛሬ ወግ ተሸሮ፣ ባህል ተሸርሽሮ
        ሉላዊነት (ግሎባላይዜሽን) ገኖ በዕድገት ተስፈንጥሮ
        እርም ባደባባይ ኦን-ላይን አወጣን
        የሟቾችን ሲቃ በፌስ ቡክ እያየን፡፡
        በዕድገት ኋላ ቀርተን፣ በመከራ ቀድመን
        በዘመን ተሳቀን፣ ዓለም ተሳልቆብን
        እንደ ሰው ተፈጥረን፣ አጉል ሞት እየሞትን
        በጉደኛው ዘመን እንደጉድ እየኖርን
        ይሄው ለዚህ በቃን! ይኸው ለዚህ ደረስን!!
    የጉድ ቀን አይመሽም፣ ፍርጃ እቤት አይውልም
    መከራ ሲመክር አስተዋይ አዕምሮ ቀና ልብ የለውም፣
    አገር መርዶ አረዳች፣ አገር እርም አወጣች በጠራራ ፀሐይ
    ሰቆቃ ዘነበ … በረዶ ወረደ … በአገሬ ሰማይ ላይ
    ህዝቡ ደረት ጣለ፣ ሳር ቅጠሉ አዘነ በእንባ ተጥለቅልቆ
    ሀዘን ቅጡን አጣ፤ ከል ለበሰ አገር ባንዲራ አዘቅዝቆ
    ድህነት በፊናው፣ ያሰበው ሞላለት ኮራ ግዳይ ጥሎ
    በወገን ደም ግብር የሱ ቆሌ ረካ፣ የእኛ ፅዋ ጎድሎ፡፡
***
    “ድህነት ወንጀል አይደለም” ይላል አዳሜ እንደዋዛ
    ከወንጀል-ወንጀልም እንጂ ጣጣ መዘዙ የበዛ፡፡
    ማጣት የሃጢያት ሥር ነው፣ የገዛ እርምን ያበላል
    የሰው ፊት የቋያ እሳት ነው፣ ከሩቁ ይለበልባል
    “ችግር በቅቤ ያስበላል”፣ ይሉት የአበሻ ጅል ተረት
    የስላቅ የፌዝ - መርፌ ነው፣ የነፍስ ግርዛት ሸለፈት
    አጅሬ ችግር ዱር አውሬ እንኳንስ ቅቤ ሊያበላ
    አየነው ለጉድ ተፈጥረን፣ በካራ አንገት ሲያስቀላ፡፡
    የድህነትን ጅብ ሸሽቶ - ቢወጣ ካገር ተሰዶ
    ጥርሶቹን ስሎ ጠበቀው፣ አይምሬው የባህር ዘንዶ፡፡
    ምስካየ ሕዙናን ነበርን፣ ለተሰደዱት አለኝታ
    ለሰቅጣጭ “የርድ” ሞት በቃን፣ አቤቱ የማታ ማታ!
    ፅናቱን ይስጥሽ አገሬ፣ ይከብዳል መርዶው የልጅ ሞት
        በተለይ እጅሽ አጥሮበት
        ሪቅሽ እየራቀበት
        ሌማትሽ ሲራቆትበት…
        የኑሮ ሚዛን ተዛብቶ
        በቀየሽ ልጅነት ጎልቶ …
    … ቢጨንቀው ስደትን መርጦ …
    ሲኳትን በረሃ አቋርጦ …
    በባዕድ ቀላድ ቀላውጦ …
    ተስፋውን ሊወልድ አምጦ!
    ካቀደው ሳይደርስ ምኞቱ
    በሰደፍ ሲቀላ አንገቱ
        ይከብዳል ለእናት ስሱ አንጀት
        ይዳብስሽ አምላክ በምህረት!
    ፅናቱን ይስጥሽ ኢትዮጵያ! ያድንሽ ከዳግም ውርደት
    በብልፅግና ፅደቂ! ገሃነም ይውረድ ድህነት!
    ገናናነትሽ ይመለስ - አይታይ ክብርሽ ኮስሶ
        ጥቃት አንገት ያስደፋል!
        ማጣት አንገት ያስቀላል!
        ይመራል ልክ እንደ ኮሶ!
    የሐዘን ማቅሽ ይቀደድ! ያቁምሽ በፈውሱ ማማ
    ሙሾ ወረዳው አብቅቶ - ህዳሴሽ በዓለም ይስማ!!
ደመቀ ወልዴ
22/08/2007 (በሊቢያ በሥደት ሳሉ
አይኤስአይኤስ በተባለ ቡድን በግፍ ለታረዱ ወገኖቻችን)

ድር ቢያብር አንበሳ ያስር፡፡
የኢትዮጵያውያን አባባል
ብዙ እጆች ሥራን ያቀላሉ፡፡
የታንዛንያውያን አባባል
ሁለት ጉንዳኖች አንድ አንበጣን ለመጐተት አያንሱም
የታንዛንያውያን አባባል
አንድ አምባር ለብቻው አይንሿሿም፡፡
የኮንጐአውያን አባባል
አንድ እንጨት ይጨሳል እንጂ አይነድም፡፡
የአፍሪካውያን አባባል
በፍጥነት ለመጓዝ ከፈለግህ ብቻህን ሂድ፤ ሩቅ ለመጓዝ ከፈለግህ በህብረት ሂድ፡፡
የአፍሪካውያን አባባል
ቤተሰብ እንደዛፍ ነው፤ ይጐብጣል እንጂ አይሰበርም
የዩቴ አባባል
የቅርብ ወዳጅ የቅርብ ጠላት ይሆናል፡፡
የአፍሪካውያን አባባል
ጓደኛ ማጣት ከመደህየት እኩል ነው፡፡
የታንዛንያውያን አባባል
ለከብቶችም እንኳን ወጣትነት ውበት ነው።
የግብፃውያን አባባል
ቁንጅና ተሸጦ አይበላም፡፡
የናይጄሪያውያን አባባል
ቡናና ፍቅር የሚጣፍጠው በትኩሱ ነው፡፡
የኢትዮጵያውያን አባባል
ፍቅር ባለበት ጨለማ የለም፡፡
የቡሩንዲያውያን አባባል
ከአንተ የሚበልጥ እግር ያላት ሴት አታግባ።
የሞዛምቢካውያን አባባል
ትዕግስት ሁሉንም ችግሮች የሚፈታ ቁልፍ ነው፡፡
የሱዳናውያን አባባል
ስለሮጡ ብቻ ይደረሳል ማለት አይደለም፡፡
የስዋሂሊ አባባል
ትዕግስት ድንጋይ ያበስላል፡፡
የአፍሪካውያን አባባል