Administrator

Administrator

ኢትዮጵያ አምና ወደዚያው ከላከችው ስጋ 58.8 ሚ ዶላር አግኝታለች
     የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ የኢትዮጵያ የስጋ ምርት ወደ ግዛቷ እንዳይገባ ከአንድ ሳምንት በፊት ጥላው የነበረችውን ማዕቀብ ማንሳቷን ተርኪሽ ዊክሊ ድረገጽ ትናንት ዘገበ፡፡
ከሳምንት በፊት ከኢትዮጵያ ሰባት ስጋ ላኪ ኩባንያዎች ወደ አገሪቱ ከገባው 36 ቶን የበግ ስጋ ጋር በተያያዘ የተፈጠረውን ችግር ተከትሎ አገሪቱ የኢትዮጵያ የስጋ ምርት ወደ ግዛቷ እንዳይገባ ገደብ ጥላ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ ከሚመለከታቸው የኢትዮጵያ መንግስት አካላት ጋር በመነጋገር ችግሩን መፍታት መቻሉን ገልጧል፡፡
ይህን ተከትሎም የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ የኢትዮጵያ የስጋ ምርት ወደ ግዛቷ እንዳይገባ የጣለችውን ማዕቀብ ማንሳቷንና አገሪቱ ያሳለፈችው ውሳኔ በዘርፉ የተሰማሩ ኢትዮጵያውያንን እንዳስደሰተ ዘገባው አስረድቷል፡፡
የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ የኢትዮጵያን የስጋ ምርት በስፋት በመግዛት ቀዳሚዋ አገር እንደሆነችና ኢትዮጵያ ወደ ተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ከምትልከው የምግብ ኤክስፖርት ምርት በአመት በአማካይ 30 ሚሊዮን ዶላር ገቢ እንደምታገኝም ገልጧል፡፡
ኢትዮጵያ ባለፈው አመት ወደ የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ከላከችው 11.692 ቶን የስጋ ምርት 58.8 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቷንም ዘገባው አክሎ አስታውሷል፡፡

  •         የገቢ አሰባሰቡ የአስተዳደር ጉባኤ አባላቱን አወቃቅሷል
  •         ከዕድሳት ዕጦት የሕንጻው ደኅንነት አደጋ ላይ ወድቋል

   በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የአዲስ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት፣ ለተለያዩ አገልግሎቶች ከአከራያቸው የሕንጻው ክፍሎች ከግማሽ ሚሊዮን ብር በላይ የኪራይ ክፍያ አለመሰብሰቡ ተገለጸ፤ ተከራዮች ውዝፍ ዕዳቸውን ከነመቀጫው አጠናቀው እንዲከፍሉ ጽ/ቤቱ አስጠነቀቀ፡፡
የሀገረ ስብከቱን ሕንጻ ለቢሮ፣ ለሕክምና እና ለሱቅ አገልግሎቶች ከተከራዩ ስድስት ተከራዮች ያልተሰበሰበው አጠቃላይ ክፍያ ብር 675 ሺሕ 244 ከ31 ሳንቲም ያህል እንደኾነ ጽ/ቤቱ ባለፈው ዓመት ነሐሴ ከጻፈው የማስጠንቀቂያ ደብዳቤ ለመረዳት ተችሏል፡፡ ማስጠንቀቂያው ከደረሳቸው  መካከል፣ ከሰኔ ወር 2005 ዓ.ም. ወዲህ ኪራያቸውን ሳይከፍሉ የቆዩና እስከ 360 ሺሕ ብር ከፍተኛ ውዝፍ ያለባቸው ተከራዮች እንደሚገኙበት ታውቋል፡፡ተከራዮች ደብዳቤው በደረሳቸው በሦስት ቀናት ውስጥ ውዝፍ ዕዳቸውን ከነመቀጫው ከፍለው ለጽ/ቤቱ ካላሳወቁ፣ ቢሮዎቻቸውና ሱቆቻቸው እንደሚታሸጉ የተሰጠው ማስጠንቀቂያም የሚገባውን ያህል ተግባራዊ ሳይሆን ከወር በላይ ማስቆጠሩ ተገልጧል፡፡
ኪራዩ በወቅቱ ቢሰበሰብ፣ ገንዘቡ በወቅቱ የነበረውን ዋጋ ያህል ቤተ ክርስቲያኒቱን ተጠቃሚ ያደርግ እንደነበር የሚገልጹ የሀገረ ስብከቱ ምንጮች፣ የፋይናንስና በጀት ዋና ክፍሉን ቀዳሚ ተጠያቂ አድርገዋል፡፡
ዋና ክፍሉ ከኪራዩ የሚሰበሰበውንና የቀረውን ገቢ በየጊዜው ለአስተዳደር ጉባኤው በሪፖርት በማሳወቅ፣ ክፍያው እንዳይወዘፍ ማድረግ የሚገባው ቢሆንም አለማቅረቡ ድክመቱን እንደሚያሳይ ምንጮቹ አስረድተዋል፡፡
በከፍተኛ የክፍያ ዕዳ ከሚታወቁ ተከራዮች መካከል ከአንዳንድ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ጋር ግንኙነት ያላቸው እንደሚገኙበት ምንጮቹ ጠቁመው፤ አጀንዳው በአስተዳደር ጉባኤው ስብሰባ ላይ ቀርቦ በታየበት ወቅትም “የገቢ አሰባሰቡ በዝምድና የተሸፋፈነ ነው” በሚል ሓላፊዎቹን እርስ በርስ አወቃቅሶ እንደነበር ተናግረዋል፡፡
በ2001 ዓ.ም. በወቅቱ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል አስተዳደር፣ በከፍተኛ ወጪ ተሠርቶና በቀድሞው ፓትርያርክ ተመርቆ አገልግሎት መስጠት የጀመረው ሕንጻ፣ ባለቤት አልባ እስኪሰኝ ድረስ እያፈሰሰ እንደሚገኝና አስቸኳይ ዕድሳት ካልተደረገለትም ደኅንነቱን አስጊ እንደሚያደርገው ምንጮቹ ይገልጻሉ::

 የታሪክ ፀሐፊ ጋዜጠኛና ዲፕሎማቱ አምባሳደር ዘውዴ ረታ ባለፈው ረቡዕ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል፡፡ አምባሳደር ዘውዴ ረታ በተለይ “የኤርትራ ጉዳይ”፣ “የተፈሪ መኮንን ረጅም የስልጣን ጉዞ” እና “የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግሥት” የሚሉ የታሪክ መፅሃፍትን ፅፈዋል፡፡
በአዲስ አበባ ኦርማ ጋራዥ አካባቢ ነሐሴ 7 ቀን 1927 ዓ.ም የተወለዱት አምባሳደር ዘውዴ፤ እንግሊዝ ሎንደን ከተማ ዕረፍት ላይ እንዳሉ በድንገት በገጠማቸው ህመም ህይወታቸው ማለፉ ታውቋል፡፡አምባሳደር ዘውዴ በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግሥት በሬድዮ በቤተ መንግሥት ዜና አቅራቢነት የሰሩ ሲሆን፣ በቱኒዚያና በሌሎች ሀገሮች በአምባሳደርነትና በሌሎች የመንግሥት ኃላፊነቶች ላይም ሰርተዋል፡፡አምባሳደር ዘውዴ ረታ በቅርቡ በኤግዚቢሽን ማዕከል በተዘጋጀው “ንባብ ለህይወት” የመፅሃፍ አውደ ርዕይና ሸያጭ ላይ “የአመቱ የንባብ ለህይወት” የወርቅ ብዕር ተሸላሚ የነበሩ ሲሆን “የ2006 የበጐ ሰው” ተሸላሚም ነበሩ፡፡

  ፊልሞች ደህንነታቸው ተጠብቆ ለተመልካች ለማድረስ የሚያስችልና የፊልም ስርቆቶችን ያስቀራል የተባለ አዲስ ቴክኖሎጂ ስራ ላይ ዋለ፡፡
አቢስውድ በተባለ ድርጅት ስራ ላይ የዋለው  አዲስ ቴክኖሎጂ፤ ፊልሞች በአንድ ጊዜ ከአንድ የማሰራጫ ስፍራ ወደተለያዩ ሲኒማ ቤቶች እንዲሰራጩ የሚያደርግና የፊልሙን ደህንነት በአስተማማኝ ሁኔታ የሚጠብቅ ነው፡፡
 ድርጅቱ በፊልሞች ላይ የራሱን የይለፍ ኮድ በማድረግ ፊልሞች ያለ ባለቤቱ ፈቃድ እንዳይታዩ ቴክኖሎጂው ይከላከላል ተብሏል፡፡ድርጅቱ ከፊልም ስራዎች ተቀብሎ በየሲኒማ ቤቱ እንዲታዩ ለሚያደርጋቸው ሲኒማዎች ሁሉ ዋስትና የሚሰጥ ሲሆን ፊልሞቹ በምንም መንገድ ያለባለቤቱ ፈቃድ ለተመልካች ቢደርሱ ተጠያቂ የሚሆንበትን አሰራር ተግባራዊ የሚያደርግ ነው፡፡
 ድርጅቱ ፊልሞች በክልል ከተሞችም በተመሳሳይ ቀንና ሰዓት እንዲታዩ ለማድረግ የሚችል ሲሆን በቀጣይ ከአገር ውጭ ፊልሞች የሚታዩበትን አሰራር ተግባራዊ ለማድረግ እቅድ እንዳለው ተገልጿል፡፡

 “መርካቶ ሰፈሬ” በሚለው የመጀመሪያ አልበሙ ተወዳጅነትን ያተረፈው ድምፃዊው አብዱ ኪያር፤ “ጥቁር አንበሳ” በሚል ስያሜ አራትኛ አልበሙን ሰሞኑን ለአድማጭ አድርሷል፡፡ የአልበሙን መጠሪያ ጨምሮ 11 ዘፈኖች የተካተቱበት የሙዚቃ አልበሙ፤ በአሸብር ማሞ የተቀናበረ ሲሆን ዋሽንግተን ዲሲ በሚገኘው ዜማ ስቱዲዮ ውስጥ እንደታተመ በአልበሙ ሽፋን ላይ ተገልጿል፡፡ በግጥምና በዜማ ድምፃዊውን ጨምሮ በርካታ ባለሙያዎች የተሳተፉ ሲሆን ታዋቂው ሙዚቀኛ ፈለቀ ሀይሉ በሳክስፎን አጅቦታል፡፡ ዘፈኖቹ በፍቅር፣ በአንድነት፣ በትውስታና ሌሎች ማህበራዊ ጉዳዮች ዙሪያ እንደሚያጠነጥኑም ለማወቅ ተችሏል፡፡

 ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ ከኢትዮጵስ ኮሌጅ ጋር በመተባበር፣ ነገ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ በብሔራዊ ቤተ መፃሕፍትና ቤተ መዛግብት ኤጀንሲ በ “አንቀፅ 39” መጽሐፍ ላይ ውይይት እንደሚያካሂድ ገለፀ፡፡ የመጽሐፉ ደራሲ አቶ ውብሸት ሙላት፤ ለውይይቱ መነሻ ሃሳብ እንደሚያቀርቡ የጠቆመው ሚዩዚክ ሜይዴይ፤ የመጽሐፍት አፍቃሪያን በውይይቱ ላይ እንዲታደሙ ጋብዟል፡፡

በወጣት ቴዎድሮስ አበራ የተደረሰው “ሀገርህን ጥላት ልጄ እና ሌሎች ልቦለዳዊ ትረካዎች” ሰሞኑን ለንባብ በቅቷል፡፡ መጽሐፉ አራት ታሪካዊ ልቦለዶችን ያካተተ ሲሆን በሃገርና ፖለቲካ እንዲሁም ባለፈውና በመጪው ትውልድ ዙሪያ ይሞግታል ተብሏል፡፡ በ214 ገፆች የተመጠነው መጽሐፉ፤ በ50 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

Saturday, 03 October 2015 10:39

የኪነት ጥግ

  (ስለ አርትኦት)
ህይወቴ አርትኦት (editing) ይፈልጋል፡፡
ምርት ሳህል
አርትኦት ያስጠላኛል፡፡ መፃፍ ደስ ይለኛል፤ ፅሁፌን መላልሶ ማንበብ፣ መከለስ ግን አልወድም፡፡
ባሪ ሃናህ
አርትኦት እወዳለሁ፡፡ ከፊልም ስራ የምወደው አንዱ  ክፍል ነው፡፡
ስቲቨን ስፒልበርግ
አርትኦት ለብቻ የሚሰሩት ዓይነት ሥራ ነው፡፡
ጆ ዳንቴ
ከምፅፋቸው እያንዳንዱ አራት ቃላት ውስጥ ሦስቱን እሰርዛለሁ፡፡
ኒኮላስ ቦይሉዩ
መሰረዝ መደለዝ የፈጠራ ምልክት ነው፡፡
ሜላኒ ሰርክል
የሚሰርዝ እጅ ብቻ ነው እውነተኛውን ነገር መፃፍ የሚችለው፡፡
ሜይስተር ጆሃን ኢክሃርት
ማንም ደራሲ ያለመታተምን የሚጠላውን ያህል አርትኦትን አይጠላም፡፡
ጄ.ራስል ላይንስ
ሌሎች በአንድ ሙሉ መፅሐፍ ያሉትን ነገር በአስር ዓ.ነገሮች መግለፅ ምኞቴ ነው፡፡
ፍሬድሪክ ኒቼ
ይሄን ደብዳቤ ያስረዘምኩት ለማሳጠር ጊዜ ስላልነበረኝ ነው፡፡
ብሌይዝ ፓስካል
ብዙ ድግግሞሽ፣ መላልሶ በማንበብና በአርትኦት ሊወገድ ይችላል፡፡
ዊሊያም ሳፋየር
ተገቢ ያልሆኑ ቃላትን አስወግድ፡፡
ዊሊያም ስትራንክ ጄአር
ባዶ ገፅን ልትከልሰው አትችልም፡፡
ሊኦናርድ ዎልፍ
በኪነጥበብ ቁጥብነት ሁልጊዜ ውበት ነው፡፡

Saturday, 03 October 2015 10:38

የዝነኞች ጥግ

ሌላውን መምሰል የለባችሁም፤ ማንነታችሁን ውደዱት፡፡
ሊ ሚሼል
ገንዘብ ማሳደዱን ትታችሁ፣ ከልባችሁ የምትወዱትን ነገር ማሳደድ ጀምሩ፡፡
Tony hsieh
ግብ፤ ቀነ-ገደብ የተቀመጠለት ህልም ነው፡፡
ናፖሊዮን ሂል
ሥራችሁን ለማሻሻል ከፈለጋችሁ የማይቻለውን ለመስራት ሞክሩ፡፡
ብሪያን ትሬሲ
መሞከራችሁን እስክታቆሙ ድረስ ተሸናፊዎች አይደላችሁም፡፡
ማይክ ዲትካ
እንደ ቢራቢሮ ተንሳፈፉ፤ እንደ ንብ ተናደፉ፡፡
ሙሃመድ አሊ
የምንቀጥረው በዓለም ላይ ምርጥ ነገሮችን ለመስራት የሚፈልጉ ሰዎችን ነው፡፡
ስቲቭ ጆብስ
ማለም ከቻላችሁ መስራት አያቅታችሁም፡፡
ዋልት ዲዝኒ
ተመሳሳይ ስኬቶችን መድገም አልወድም፤ ወደ ሌሎች ነገሮች ደግሞ መሻገር እሻለሁ፡፡
ዋልት ዲዝኒ
አመለካከት፤ ትልቅ ልዩነት የሚፈጥር ትንሽ ነገር ነው፡፡
ዊንስተን ቸርችል
እግራችሁን በትክክለኛው ቦታ ማኖራችሁን አረጋግጡ፤ ከዚያ ሳትበገሩ ቁሙ፡፡
አብርሃም ሊንከን
በሌላው ሰው ደመና ላይ ቀስተደመና ለመሆን ጣሩ፡፡
ማያ አንጄሎ

     በአፍሪካም ሆነ በኢትዮጵያ በቴኳንዶ ሙያ ኮሪያ ድረስ ሄዶ ቴኳንዶ የተማረ ብቸኛው አፍሪካዊ ኢትዮጵያዊ ብቸኛው የማስተር ማዕረግ ያለው አሰልጣኝ ነው - ማስተር አብዲ ከድር፡፡ ባለፈው ነሐሴ ወር በቡልጋሪያ ሶፊያ ዓለም አቀፉ-የቴኳንዶ ፌዴሬሽን (ITF) የተመሰረተበትን 60ኛ ዓመት ሲያከብር ለሙያው ላበረከተው የላቀ አስተዋፅኦ የወርቅ ሽልማት ተበርክቶለታል”” የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ በህይወቱና በቴኳLዶ ሙያው ዙሪያ ከማስተር አብዲ ከድር ጋር ተከታዩን ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡

    አንድ ሰው በቴኳንዶ ምን ደረጃ ላይ ሲደርስ ነው “ማስተር” የሚለውን ማዕረግ የሚያገኘው?
በዓለም አቀፍ ደረጃ በዘርፉ ማስተር ለመባል የራሱ እርከን አለው፡፡ አንድ የቴኳንዶ ተማሪ ትምህርቱን ሲጀምር ከቢጫ ቀበቶ እስከ ጥቁር ቀበቶ ድረስ የራሱ ሂደቶች አሉት፡፡ ከጥቁር ቀበቶ በኋላ ፈርስት ዳን፣ ሰከንድ ዳን፣ ፎርዝ ዳን፣ እያለ ሲክዝ ዳን (6ኛ ዳን) ላይ ሲደርስ ኢንተርናሽናል ኢንስትራክተር የሚል ማዕረግ ያገኛል፡፡ ሰባተኛ ዳን ላይ ሲደርስ ማስተር የሚለውን ማዕረግ ያገኛል ማለት ነው፡፡ እኔም በዚሁ ሂደት ውስጥ አልፌ ነው ማስተር የሚለውን ማዕረግ ያገኘሁት፡፡
በቴኳንዶ ሙያ ለምን ያህል ጊዜ ሰራህ?
ላለፉት 40 ዓመታት ህይወቴ ከቴኳንዶ ጋር ተቆራኝቶ ነው ያለው፡፡ አላህ ከፈቀደ ወደፊትም በሚሰጠኝ ዕድሜ በዚሁ ሙያ እቀጥላለሁ፡፡
በእነዚህ 40 ዓመታት ውስጥ በሙያው ያደረግሃቸውን አጠቃላይ እንቅስቃሴዎች እስኪ አስረዳኝ…
በዚህ አርባ ዓመት ውስጥ ራሴ ከመማር አልፌ በኢትዮጵያና በአፍሪካ እንዲሁም በሌላው የዓለም ክፍል እየተዘዋወርኩ አስተምሬአለሁ፡፡ ኮሪያ ድረስ ሄጄ በከፍተኛ ማዕረግ የተማርኩ የመጀመሪያው አፍሪካዊና ኢትዮጵያዊ ነኝ፡፡ በሙያው ያሳለፍኩት ውጣ ውረድ ከፍተኛ ነው፤ በተለይም በደርግ ጊዜ ፈተናው ከባድ ነበር፡፡ ዘርፉ እንዳሁኑ በመንግስት እውቅና ተሰጥቶት በይፋ ሊሰራ ቀርቶ እኛም እየተደበቅን ነበር የምንሰራው፡፡ ያ ሁሉ አልፎ በአሁኑ ሰዓት አገራችን በአሶሴሽን ደረጃ ተቋቁሞ የዓለም አቀፉ የቴኳንዶ ፌዴሬሽን አባል ለመሆን በቅተናል፤ እስካሁን ልጆች በማስተማር ክለቦችን በማቋቋም፣ አሶሴሽኑን ወደ ከፍተኛ ደረጃ ለማሸጋገር ጥረት ሳደርግ ቆይቻለሁ፡፡ በአፍሪካም ሆነ በኢትዮጵያ ብቸኛው 7ኛ ዳን ያለኝ ነኝ፤ በዚህ በጣም ደስ ይለኛል፡፡
ከ7ኛ ዳን ወይም ማስተር ከሚለው ማዕረግ በላይስ ሌላ ማዕረግ አለ? ካለስ ወደዚያ ደረጃ ለማደግ ምን አይነት እንቅስቃሴ እያደረግህ ትገኛለህ?
በጣም ጥሩ! ከ7ኛ ዳን ቀጥሎ ያለው 8ኛ ዳን ነው፡፡ ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ 7ኛ ዳን ላይ ሲደረስ “ማስተር” እንደሚባል ሁሉ፣ 8ኛ ዳን ላይ ሲደረስ “ሲኒየር ማስተር” የተሰኘ ማዕረግ ይሰጣል፡፡ እኔም አላህ ፈቃዱ ሆኖ ከደረስኩ (እንደምደርስ ተስፋ አለኝ) ከስድስት ወራት በኋላ 8ኛ ዳን በማግኘት ደረጃዬን ወደ ሲኒየር ማስተርነት አሳድጋለሁ፡፡
ወደቴኳንዶ እንዴት ነው የገባኸው?
ቴኳንዶን የጀመርኩት ገና የአምስት ዓመት ልጅ ሆኜ ነው፡፡ እንዴት ጀመርክ ላልሺው ከአባቴ የወረስኩት ነው፡፡ አባቴ የቴኳንዶ ባለሙያ ነበር፡፡ እንግዲህ የአላህ ስጦታ ሆኖ እድሜዬን ሙሉ በስፖርቱ አሳልፌያለሁ፡፡ ከሁለት ሳምንት በኋላ በሚቀጥለው ጥቅምት 1 60ኛ ዓመቴን አከብራለሁ፡፡ ከአምስት ዓመቴ ጀምሮ ከስፖርቱ ጋር ነኝ፤ እንደነገርኩሽ በከፍተኛ ደረጃ እየሰራሁ እየተማርኩ፣ በዓለምና በአፍሪካ እየተዘዋወርኩ 40 ዓመታትን አሳልፌያለሁ ማለት ነው፡፡
አሁን 60 ዓመትህ ነው ማለት ነው፤ ግን የ30 ዓመት ወጣት ነው የምትመስለው…
የማልደብቅሽ ነገር ስፖርቱ በራሱ ለአሁኑ የሰውነት አቋሜ የራሱን ሚና ተጫውቷል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ እጅግ የማከብራት፣ የምወዳትና የማፈቅራት ሰላም የሆነች ሚስት አላህ ሰጥቶኛል፤ በኑሮዬ ደስተኛ ነኝ፡፡ ፈጣሪ፤ ሚስት የምትሰራው ከግራ ጎን ነው ይላል አይደል፤ የኔ ሚስት ግን ከሁሉም ጎኔ ነው የተሰራችው፡፡ እህቴም፣ ሚስቴም፣ እናቴም፣ አማካሪዬም… ብቻ ሁሉም ነገሬ ናት፡፡ ከእሷ የማገኘው ድጋፍ፣ እንክብካቤና ፍቅርም በራሱ ከእድሜዬ በታች ወጣት መስዬ ኧረ እንዲያውም ሆኜ እንድታይ ከፍተኛውን ቦታ ይይዛል፡፡
በትዳር ምን ያህል ጊዜ ቆያችሁ? ልጆችስ አፍርታችኋል?
ላለፉት 31 ዓመታት አብረን በትዳር እየኖር ነው፡፡ በእድሜ ከእኔ በጣም ታንሳለች፤ ገንዬን አሳድጌያታለሁ ማለት ይቻላል፡፡ ልጆች አልወለድንም፤ ወደተለያዩ የውጭ አገራት ሄደን ምርመራ አድርገን፣ መውለድ ትችላላችሁ ተብለናል፡፡ አንድ ቀን ልጅ እንደሚኖረን ተስፋ አለን፡፡ ሆኖም በአሁን ሰዓት የልጅ ጉዳይ በኑሯችን ውስጥ እንደ እንከን ተጠቅሶ አያውቅም፡፡ በዙሪያችን ያሉ የማስተምራቸው ልጆች ሁሉ ልጆቼ ናቸው፡፡ አንድም ቀን በዚህ ቅር ተሰኝቼ፣ በትዳሬና በፍቅሬ ላይ እንቅፋት ሆኖብኝ አያውቅም፡፡ ገኒ ለእኔ ልጄም ጭምር ናት፤ እንዴት እድለኛ እንደሆንኩ አልነግርሽም፡፡
እስኪ ቡልጋሪያ ላይ ባለፈው ነሐሴ ወር ስላገኘኸው ሽልማት ንገረኝ…
ባለፈው ኦገስት በተካሄደው የኢንተርናሽናል የቴኳንዶ ፌደሬሽን 60ኛ ዓመት የምስረታ በዓል ላይ በዓለም አቀፍ ደረጃ በቴኳንዶ ከፍተኛ እንቅስቃሴና አስተዋፅኦ ያበረከቱ 60 ሰዎች ተሸልመው ነበር፡፡ በዚህ ሽልማት ዝግጅት ላይ ተሳታፊ ብሆንም እንደምሸለምና እጩ እንደነበርኩ ግን አላውቅም ነበር፡፡ የኢትዮ ዮናይትድ ቴኳንዶ አሶሴሽን ፕሬዚዳንት እንደመሆኔ፣ 60ኛ ዓመት በዓሉን ለማክበር ወደ ቡልጋሪያ ሶፊያ ከተማ ሄጄ ነበር፡፡ ሽልማቱ ሲካሄድ ግን ብቸኛው አፍሪካ ኢትዮጵያዊ የወርቅ ሜዳሊያ ተሸላሚ መሆኔን ድንገት ሰማሁኝ፡፡ ይሄ እንግዲህ ለኢትዮጵያም ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካም ትልቅ ሽልማትና ኩራት ነው ማለት ይቻላል፡፡ ምክንያቱም ለዚህ ሽልማት ወደ 180 ያህል የዓለም አገራት ተሳታፊ ሆነውበት፣ ከነዚህ ሁሉ አገራት ነው ብቸኛው አፍሪካ ኢትዮጵያዊ የወርቅ ተሸላሚ የሆንኩት፡፡ ፈረንጆቹ ተሳሳቱ የምለው ሽልማቱን ለሚስቴ ለገነት ሀብተማሪያም ባለመስጠታቸው ብቻ ነው፡፡
እንዴት ማለት?
እኔ በጣም ተደባዳቢ፣ አስቸጋሪ ባህሪ የነበረኝና የማልረባ ሰው ነበርኩ፤ እርሷ ናት ለዚህ ማንነት ያበቃችኝ፤ የለወጠችኝ፡፡ በዚያ ላይ እርሷ የኦርቶዶክስ እምነት ተከታይ ስትሆን እኔ ሙስሊም ነኝ፡፡ የእርሷን ፆም እፆማለሁ፤ የእኔን ፆም ትፆማለች፡፡ የመቻቻል የመፋቀር ተምሳሌቶችም ነን፡፡ አንተ ትብስ አንቺ ትብሽ ተባብለን ነው ከ30 ዓመት በላይ የዘለቅነው፡፡ የእርሷ ድጋፍና ፍቅር ገና ለብዙ ሽልማቶች ያበቃኛል፡፡ አንድ ነገር ልንገርሽ፤ 35ኛ የጋብቻ በዓላችን ላይ እንደገና ሰርግ ደግሰን ለመጋባትና ትዳራችንን ለማደስ እቅድ ይዘናል፤ አላህ ይርዳን፡፡
ኮሪያ ሄዶ ከፍተኛ የቴኳንዶ ትምህርት በመማር የመጀመሪያው አፍሪካዊ ኢትዮጵያዊ ነህ፡፡ ከኮሪያ ውጭ የት የት ተምረሃል?
ከዚያ በኋላ ያልሄድኩበትና ኮርስ ያልወሰድኩበት የዓለም ክፍል የለም፡፡ ለምሳሌ ጀርመን፤ እንግሊዝ፣ ስውዲንና ሌሎችም አገሮች ሄጄ በዘርፉ አሉ የተባሉ ኮርሶችን በመውሰድ እውቀቴን አዳብሬያለሁ፡፡ ሌላው ህንድ አገር በሚገኝ አንድ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ፊዚካል ኢጁኬሽን ተምሬአለሁ፡፡
በአሁኑ ወቅት ቴኳንዶ በኢትዮጵያ ውስጥ ያለበት ደረጃ ምን ይመስላል?
ዘርፉ በደርግ ጊዜ የነበረበትን ሁኔታ ነግሬሻለሁ፤ በመንግስት አካላትና በተፈቀደላቸው ወገኖች ብቻ በገደብ የሚሰጥ ትምህርት ነበር፡፡ ቴኳንዶ በአሁኑ ሰዓት ጥሩ እውቅና አለው፡፡ ከመንግስትም በኩል እገዛ ይደረጋል፤ ነገር ግን እገዛው በቂ አይደለም፡፡ ሆኖም ኢትዮጵያ በአፍሪካ ደረጃ በቴኳንዶ ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ በማርሻል አርት በከፍተኛ ደረጃ ላይ ናት፡፡ በአዲስ አበባ ብቻ ሳይሆን በክልሎችም በከፍተኛ ሁኔታ እየተስፋፋ ይገኛል፡፡
በኢትዮጵያ ዩናይትድ ቴኳንዶ አሶሴሽን ስር ምን ያህል ተማሪዎች አሉ?
በአሶሴሽናችን ስር ብቻ 37 ሺህ ሰልጣኞች ይገኛሉ፡፡ ወደ 200 ያህል ክለቦችም እናስተዳድራለን፡፡
እስኪ ስለቴኳንዶ ሳይንስና ዲሲፕሊን በአጭሩ ንገረኝ…
በአጠቃላይ ቴኳንዶ ማለት ህይወት ነው፤ ሰዎች ስለቴኳንዶ ሲያስቡ እግርና እጅ ማወናጨፍ ብቻ ነው ብለው ካሰቡ በጣም ተሳስተዋል፡፡ ነገር ግን ሰው ከእግርና እጅ እንቅስቃሴ በፊት በመልካም ስነ ምግባርና ጥሩ ሰብዕና ጭንቅላቱ ይገነባል፡፡ ታጋሽ፣ ሰው አክባሪ፣ ማህበራዊ ኑሮ አዋቂ፣ በጎ አድራጊ… በአጠቃላይ የጥሩ ስብዕና ባለቤት እንዲሆን ተደርጎ ይቀረፃል፡፡ ከዚህ በኋላ ነው ወደ አካላዊ እንቅስቃሴ የሚገባው፡፡ ከላይ ከተጠቀሱት የስብዕና መሰረቶች ውጭ ሆኖ የቴኳንዶ ባለሙያ ነኝ የሚል ካለ፣ ጨርሶ የቴኳንዶን ሳይንስም ሆነ ዲሲፕሊን አያውቀውም ማለት ነው፡፡ ቴኳንዶ ማለት እጅ እግርና አዕምሮ የተቀናጁበት ጥበብ ማለት ነው፡፡ ቴኳንዶ፡- ሰላም፣ ፍቅር አንድነት ነው፡፡ እነዚህ ናቸው በቴኳንዶ ውስጥ ያሉት መሰረታዊ ነገሮች፡፡
በአገራችን በተለይም በመዲናችን በተለያዩ ቦታዎች በርካታ የቴኳንዶ ማሰልጠኛዎች ይገኛሉ፡፡ እነዚህን ማሰልጠኛዎች ቃኝተሃቸው ታውቃለህ? ማሰልጠኛዎቹ ምን ያህል ትክክለኛውን የቴኳንዶ ስልጠና እየሰጡ ነው ትላለህ?
 የቴኳንዶ ትምህርት የሚያልቅ አይደለም፡፡ በሂደቱ ውስጥ ብዙ ስህተቶች ሊፈጠሩ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን በሂደትም ይስተካከላሉ፡፡ እነዚህ ትምህርት ቤቶች ዋነኛ ዓላማቸው መልካም ዜጋን ማፍራት ነው፡፡ አብዛኛዎቹ ከሞላ ጎደል ትምህርቱን እየሰጡ ይገኛሉ፤ በዚያው መጠን ግን ችግር ያለባቸው የሉም ማለት አይቻልም፡፡ ግን በሂደት ሊቀረፉ ይችላሉ የሚል ግምት አለኝ፡፡ አሁን በየቦታው ለዘርፉ ፈቃድ እየተሰጠ ነው፤ በዚያው መጠን ያሉባቸውን ችግሮች እንዲቀርፉ ማስጠንቀቂያዎችም ይሰጣሉ፡፡
ቴኳንዶ በጥበብና በዲሲፕሊን ካልተሰራ፣ ጋንግስተሮችን የምናፈራበትና ፈቃድ የሌለው መሳሪያ የምናስታጥቅበት ይሆናል፡፡ ቴኳንዶ ደግሞ ጋንግስተሮችን የምናፈራበት ሳይሆን ጋንግስተሮችን የምናጠፋበት ነው መሆን ያለበት፡
ቴኳንዶ በከፍተኛ የትምህርት ተቋም ደረጃ ስለሚሰጥበት ሁኔታ የታሰበ ነገር አለ?
ትምህርቱ በመንግስት በኩል በመምህራን ኮሌጅ ደረጃ እየተሰጠ ነው፡፡
 ዩኒቨርሲቲ ውስጥም እንደ አርት ትምህርት እየተሰጠ ነው፡፡ ወደፊት ራሱን የቻለ ዩኒቨርሲቲ እንዲኖረው ከውጭዎቹ ጋር በመነጋገር ላይ ነን፡፡ ይህ የሚሳካ ይመስለኛል፡፡
በርከት ያሉ የቴኳንዶ ማሰልጠኛ ተቋማት እንዳሉህ ሰምቻለሁ፡፡ ምን ያህል ናቸው? የት የት ነው የሚገኙት?
በርካታ ተቋማት አሉኝ፡፡ ለምሳሌ አፍሪካ ህብረት ውስጥ፣ ኢሲኤ፣ ጁቬንቱስ ጣሊያን ክለብ ውስጥ፣ ሳር ቤት አዳምስ ፓቪሊዮን ህንፃ እንዲሁም፣ ፍፁም በላይ ሆቴል ውስጥ የማሰልጠኛ ተቋማት አሉኝ፡፡
በኢትዮ ዮናይትድ ቴኳንዶ አሶሴሽን ስር ደግሞ እንደ ፕሬዚደንትነቴ በስሬ ወደ 200 ያህል ክለቦች ይገኛሉ፡፡ እነዚህን እኔ ነኝ የምመራቸው፡፡
እነዚህ ክለቦች ተምረው ከፍተኛ ደረጃ ሲደርሱ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያሉትን ቀበቶዎች (ዳኖች) ፈርሜ ከውጭ የማስመጣቸው እኔ ነኝ፡፡ ዳኖቹ የሚመጡት ከዋና ጽ/ቤታችን ከኦስትሪያ ቪዬና ነው፡፡
እስኪ ማርሻል አርት በሚባሉት እነካራቴ ጁዶ፣ ውሹ ቴኳንዶና ሌሎችም ስፖርቶች መካከል ስላለው አንድነትና ልዩነት በአጭሩ ንገረኝ?
ማርሻል አርቶች በኢንተርናሽናልና በወርልድ ቴኳንዶዎች የተከፋፈሉ ናቸው፡፡ የሚገርመው የነዚህ ማርሻል አርቶች ልዩነት የእንቅስቃሴ ልዩነት ነው፡፡ ውሹ የቻይና ስፖርት ሲሆን በብዛት በአክሮባትና ሰውነትን እንደልብ በማዘዝ (Flexibility) ላይ የሚያተኩር ነው፡፡ በብዛት ታይገር ስታይል፣ ስኔክ ስታይል በማለት በእንስሳት እንቅስቃሴ ይከፋፍሏቸዋል፡፡ ካራቴ የምንለው የጃፓንና የፈረንሳይ ስፖርት ነው፡፡ ጃፓኖች እንቅስቃሴውን ልዩ አድርገው ስለቀመሩት ከቴኳንዶ ትንሽ ይለያል፡፡ ጁዶ ደግሞ በመያዝና በመጣል እንደ ትግል አይነት ስፖርት ሲሆን ብዙ ጊዜ ወታደሮች የሚያዘወትሩት ነው፡፡
በመጨረሻ የምታክለው ይኖርሃል?
የሚገርመውና ልጨምርልሽ የምፈልገው እስከዛሬ በኦሎምፒክ ውስጥ ወርልድ ቴኳንዶ ነበር ለውድድር የሚቀርበው፡፡
አሁን ግን በ2016 ሪዮ ዲጄነሪዮ በሚካሄደው 31ኛው ኦሎምፒክ ላይ ኢንተርናሽናል ቴኳንዶ ከወርልድ ቴኳንዶ ጋር በጋራ ለውድድር ይቀርባል፡
በዚህም ውድድር ላይ ኢትዮጵያውያን አገራቸውን ወክለው የሚቀርቡ በመሆኑ በጣም ደስተኞች ነን፡፡ ለኢትዮጵያም ሆነ ለአፍሪካ ትልቅ የምስራች ነውና እንኳን ደስ አላችሁ ለማለት እንወዳለን፡፡