Administrator

Administrator

   ከዕለታት አንድ ቀን መልኩ ወደ ቁራ የሚሄድ አንድ ጥቁርና ነጭ ዥጉርጉር ወፍ በአንድ ጫካ ውስጥ ይኖር ነበረ፡፡ በእርሻ ማሳው ውስጥ የሚያማምሩ ነጫጭ እርግቦች እየተመገቡ፣ ብር ትር እያሉ ሲጫወቱ አየ፡፡ ከወፋፍርነታቸው መልካም ተመግበው እንደኖሩ ያስታውቃሉ፡፡ የገላቸውና የላባቸው ንጣት ዐይን ይስባል፡፡ ያ ዥጉርጉር የቁራ ዝርያ የሆነ ወፍ እጅግ አድርጐ ቀና፡፡
“ምነው እኔም መልኬ እንደነዚህ እርግቦች ሙሉ በሙሉ ነጭ በሆነ ምነው… ምን በድዬ ነው እኔን አምላክ አስቀያሚ ዥጉርጉር አድርጐ የፈጠረኝ?” ሲል አማረረ፡፡
ጥቂት ቆይቶ ግን አንድ መላ መጣለት፡-
“ቆይ እኔስ እንደ እርግቦቹ ለመሆን ምን ያንሰኛል? ሙሉ ለሙሉ ከእግር እስከ አናቴ ነጭ ብቀባና ከነሱ ብቀላቀልኮ እንደነሱ እበርራለሁ፤ እንደነሱም እመገባለሁ፡፡ እንደነሱም አምራለሁ” አለ፡፡
እንዳሰበው ሙሉ ነጭ ተቀባና እንደ እርግቦቹ መሰለ፡፡ ሄዶም ከእርግቦቹ ጋር ተቀላቀለ፡፡ ምንም ድምጽ ሳያሰማ፤ በሰላም ከእርግቦቹ ጋር መቀገሩን ተያይዘው፡፡ ለጥቂት ጊዜም ደስተኛ ሆነ፡፡
አንድ ቀን ግን ያልታሰበ ነገር ተከሰተ፡፡
“እስከ መቼ ዝም ብዬ እዘልቀዋለሁ፤ እኔም ከነሱ ጋር መጫወት አለብኝ፤” ብሎ በራሱ ቋንቋ ሊያናግራቸው ሞከረ፡፡
እርግቦቹ እስከ ዛሬ ሲያጭበረብራቸው እንደከረመ ነቁበት፡፡ በጋራ ይጠቀጥቁት፤ ይተከትኩት ገቡ፡፡
“አንት ወስላታ አጭበርባሪ! ያለቦታህ መጥተህ እስካሁን አታለልከን! ሂድ ድራሽህ ይጥፋ! ወገኖች ህጋ ተቀላቀል!” ብለው አባረሩት፡፡
ዥጉርጉሩ ወፈ አዝኖና ተስፋ ቆርጦ ወደ ራሱ ዝርያዎች ሄደ፡፡ ሆኖም እዚያም እንደዚህ መልኩ ነጭ የሆነ ወፍዘ ከኛ ዝርያ ውስጥ የለም፡፡ ከእኛ ጋር መኖርም ሆነ መመገብ የለበትም” ብለው አባረሩት፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ቤት - የለሽ፣ ዘመድ - የለሽዘ ብቸኛ ሆኖ ቀረ!
*   *   *
መምሰል ክፉ በሽታ ነው! ያልሆኑትን ሆኖ ለመታየት መሞከር ዕውነተኛ ማንነትን ማጣት ከመሆኑም በተጨማሪ የተነቃለታ ትልቅ ኪሣራ ያስከትላል፡፡ ወገን የሚመስሉን ወገኖችም ቢሆኑ “ከጠላትህ ውሰድኀ ወደ ዘመድህ ዞረህ ጉረስ” የሚለውን ተረት አሳምረው ያውቁታል፡፡ ይህን አለማስተዋል የማታ ማታ ዋጋ ያስከፍላል!
“መሆንህ እንጂ፣ መምሰልህ፣ ከቶ ለኔ ምን ፋይዳ አለውኀ ዓለምን ዓለም ያረጋት፣ መልክ ሳይሆን ማንነት ነው” የሚለውን ግጥም አለመዘንጋት ነው፡፡
ሀገራችን ብዙ አስመሳዮችን አስተናግዳለች፡፡ ነገም ገና ብዙ ታስተናግዳለች፡፡ የአስመስሎ ማደር ወይም አድርባይነት ጊዜያዊ ወረት ነው፡፡ ወረቱ ሲያልቅ “ጨዋታው ፈረሰ፣ ዳቦው ተቆረሰ” ማለት ግድ ይሆናል፡፡ የዚህ ዓይነት ጨዋታዎች ሲፈርሱ፤ በአፄ ኃይለሥላሴም፣ በደርግም፣ በኢህአዴግም ዘመን፣ ታዝበን አልፈናል፡፡
“ጠላትማ ምንጊዜም ጠላት ነውኀ አስቀድሞ መቅጠፍ አሾክሻኪውን ነው”
የሚለውዘ ለረዥም ጊዜ ስንሰማ የኖርነው ቀረርቶ ነው!
ሌላው ችግር ትምህርት ነው፡፡ ኩረጃና የትምህርት ጥራት እንዲህ ለያዥ ለገራዥ ያስቸግራል ብሎ ማሰብ አስገራሚ ነው፡፡ በልማት ላይ ላለች አገርዘ በብሔራዊ ደረጃ ኩረጃ ችግር ሲሆን ያሳፍራል። ምን ዓይነት ትውልድ እየቀረፅን ነው ብለን ስናስብዘ “በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ” ይሆንብቀሐል፡፡ ህብረተሰባችን ራሱ ስለ ትምህርት ጽሕለው አመለካከት እየተንሸዋረረ ነው፡፡ የት/ቤት ገንዘብ መክፈል፣ የትምህርት ቁሳቁስ መግዛት፣ ብቻውን የትምህርት ጤናማነት ማረጋገጫ አይደለም፡፡ የተማሪዎቹ ባህሪ በሚገባ መጤን አለበት፡፡ ክትትል፣ ክትትል፣ አሁንም ክትትል ያስፈልጋል!
ሌላው ችግር ጤና ነው፡፡ የህክምና ስህተቶች፣ የኮንትሮባንድ መድሀኒቶች አላግባብ መግባት፣ የሀኪሞች ስግብግብነት፣ የነርሶች ንዝህላልነት፣ የበሽተኞች መጉላላት ወዘተ… በከፍተኛ ደረጃ በሚታይበት አገር፤ ስለ ጤና ልማት ማሰብ ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ የክሊኒኮች መብዛት ለበለጠ ብዝበዛ የሚዳርግ ከሆነ ስለ ጤና ልማት ማለም  ሞኝነት ነው፡፡
በሀገርና በህዝብ ጉዳይ ምን ጊዜም ደግ ደጉን፣ ቀና ቀናውን ማሰብም ቢያንስ አዎንታዊነትና ብሩሃዊነት (Optimistic) መሆን ነው፡፡ መንገድ መስራት መልካም ልማት ነው፡፡ የትራፊክ አደጋ ከበዛ ግን የመንገዱን መሰራት አሉታዊ ያደርገዋል፡፡ ይሄን ችግር ለመፍታት ትራፊኩ ሰውዬ ጉቦ የሚበላ ከሆነ ደግሞ የመንገዱ አዎንታዊነት ይብስ አሉታዊ እየሆነ መጣ ማለት ነው፡፡ ሰንሰለታዊ ብልልት (Chain Reaction) አለበት ውስጡ፡፡ መሰረተ ልማት ውስጥ መብራትና ውሃ ተገጠመ ማለት ዋና ነገር የመሆኑን ያህል፣ መብራትም፣ ውሃም፣ ከሌለ ግን ቅርፅ ብቻ ይሆንብናል፤ ከጥቅም የተለየ ልማት የለምና፡፡ ይሄ በህዝብ ዘንድ የመንግስትን ህዝባዊነት ጥያቄ ላይ ቢጥለው በህዝብ አይፈረድም፡፡ መብራት ለምን ይጠፋል - እስኪሰለቸን ድረስ ተነግሮንም ቢሆን ማወቅ አለብን፡፡ ለሱዳንና ለጅቡቲ እየሸጥን እኛ ለምን ይቸግረናል? የሚለው ጥያቄ፣ መሬት የያዘ መልስ ቢኖረው፤ ቢያንስ “የዐባይን ልጅ ውሃ ጠማው” ከሚለው ተረት እንገላገላለን፡፡ አንዳንዴ ዝርዝር ላይ ስናተኩር ትልቁ ስዕል ይጠፋብናል (እናምታታዋለን Lose sight of the forest for the trees - ይላሉ ፈረንጆች፡፡
ደህንነታችን መደፈሩ ያሰጋናል፡፡ ሉዓላዊነታችን እንዲጠበቅ መፈለጋችን የማንደራደርበት ነው። ለማናቸውም ጥቃት፣ የምንከፍለው አፀፋ ከብሔራዊ ማንነታችን ጋር በጥኑ የተሳሰረ ነው፡፡ ዛሬም “ባለቤቱን ካልናቁ አጥሩን አይነቀንቁ” ወቅታዊ ተረት ነው፡፡ ዛሬም “ዳሩ ሲነካ መካከሉ ዳር ይሆናል” ወቅታዊ ተረት ነው፡፡ ችግሮች መቆሚያ ሊያጡ በፆም አንጀት ሆኖብን “ግዴለም፣ እንችለዋለን” እያልን ይሆናል፡፡ ነገሩ በፍስክ ሲቀጥል ግን ስጋታችን ዕጥፍ ድርብ ይሆናል፡፡ የዜጎቻችን አላግባብ መጨፍጨፍ የሚያወላዳ ምላሽን ይሻል፡፡
በምንም ሰበብ ይከሰት የዜጎቻችን እልቂት ያሳስበናል፡፡ ወደን እደለም ደግሞ እንዲህ ያለ ግልፅ ጭፍጨፋ በግላጭ አጋጥሞን ስለማያውቅ ነው! የከብቶቻችን ይዞታ የራሳችን እስከሆነ ድረስ፣ ማንም ምንም ዓይነት የባለ ይዞታን ዕምነት አለኝ ቢል ከቶም ለኛ ለውጥ አያመጣም! የእኛ ንብረት የእኛ ነውና! አሁንም ጠንቀቅ ብለን በብቃት መጠበቅ አለብን፡፡ የጎረቤት ሰላም ደፈረሰ ማለት የሁላችንም ውስጣዊ ህልውና ደፈረሰ ማለት ነው፡፡ ሰላም ለዘለዓለም ትኑር!
ዛሬ ያልተፈተሸ ብዙ ተቋማት፣ ብዙ ማህበራት፣ ሆስፒታሎች፣ ክሊኒኮች፣ ትላልቅ ሆቴሎች፣ የሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች፣ ከመንግስት መስሪያ ቤቶች ጋር ጥብቅ ቁርኝት ያላቸው ተሞዳማጅ መንግስታዊ ድርጅቶ ወዘተ እንካ በእንካ ተያይዘው ሳሉ ችግሮቻቸው በልማት ስም እየተሸፋፈነላቸው፡፡ ንፁህ መስለው በኩራት ይኖራሉ፡፡ አካሄዳቸው አገርንና ህዝብን ጎጂ መሆን አለመሆኑን በግድ መመርመር ያስፈልጋል፡፡ “ተሸፋፍነው በተኙ፣ ገልጦ የሚያይ አምላክ አለ” የሚለውን አባባል በቅጡ ጨብጦ ነገሮችን ማብጠልጠል ተገቢ ነው፡፡ “የተሰነጠቀ ቅልን ለማወቅ ውሃ ጨምርበት” ነው ነገሩ፡፡
ለክርስትና አማኞች የትንሳኤ በዓል የሞቀ የደመቀ ይሆን ዘንድ ከልብ እየተመኘን፤ የኢትዮጵያንም ትንሳኤ እንደዚሁ ይባርክልን እንላለን!!

እንደሻው እምሻው
(የሰማያዊ የፅ/ቤትና አስተዳደር ኃላፊ)

   ባለፈው ሚያዝያ 8 ቀን 2008 ዓ.ም በወጣው የጋዜጣችሁ፣የነጻ አስተያየት አምድ ላይ “ሰማያዊ ፓርቲ አደጋ ላይ ነው; በሚል ርዕስ፣ ከፓርቲያችን ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት ጋር ያደረጋችሁትን ቃለ ምልልስ አነበብኩት፡፡ ሊቀመንበሩ አንድም ጊዜ እንኳን እየመራሁት ነው የሚለውን ፓርቲ መተዳደሪያ ደንብ አንቀጽ ሳይጠቅስ፣ የፓርቲውን ተቋማት ሁሉ እንደፈለገው ሲዘልፋቸው በመታዘቤ እኔም ይህን መልስ ለመጻፍ ተገደድኩ፡፡
ፓርቲያችን ሰማያዊ ጠቅላላ ጉባኤውን በነሀሴ 16 እና 17 2007 ዓ.ም ባደረገ ወቅት በብዙ ጉዳዮች ላይ የተወያየ ሲሆን ብሔራዊ ምክር ቤቱን፣ኦዲትንና ሊቀመንበሩን መርጦ ነበር የተጠናቀቀው፡፡ በፓርቲያችን መተዳደሪያ ደንብ አንቀጽ 6፣ ንዑስ አንቀጽ 2 መሰረትም፤ እኔም ሆንኩ አሁን የስራ አስፈጻሚ አባላት የሆኑት ለብሔራዊ ምክር ቤት አባልነት ተወዳድረናል፡፡ ጠቅላላ ጉባኤውም 37 ቋሚ፣ 13 ተለዋጭ የምክር ቤት አባላትንና አምስት የኦዲትና ምርመራ ኮምሽን አባላትን ከመረጠ በኋላ፣ የምክር ቤቱ አራተኛ ዓመት መስራች ስብሰባ ጳጉሜ 1 ቀን 2007 ዓ.ም ተካሂዶ፣ አቶ ይድነቃቸው ከበደን የምክር ቤቱ ሰብሳቢ አድርጎ መረጠ፡፡ ከዛም በኋላ ከፓርቲው የጠቅላላ ጉባኤ ሰነድ ጋር ጳጉሜ 3 ቀን 2007 ዓ.ም አሁን የሰማያዊ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል የሆኑት (ያን ጊዜ የም/ቤት አባላት ነበሩ) ዝርዝራቸው ለምርጫ ቦርድ ገባ፡፡
እንግዲህ ተመልከቱ፤ሊቀመንበሩ ሁለት ገጽ ሽፋን በተሰጠው ቃለ ምልልስ፣ አንድም ጊዜ የፓርቲውን መተዳደሪያ ደንብ ጠቅሶ ለማብራራት አልሞከረም፡፡ እንደገና የም/ቤቱ አራተኛ ዓመት አንደኛ መደበኛ ስብሰባ መስከረም 9 ቀን 2008 ዓ.ም ሲደረግ ይልቃል ለስራ አስፈጻሚነት ያጫቸውን እጩዎች በም/ቤቱ እንዲጸድቅለት ሲጠይቅ፣ ከቋሚ የም/ቤት አባላት ውስጥ ስምንቱን፣ ከተለዋጭ አባላት ውስጥ ደግሞ ሁለቱን አምጥቶ ስምንቱ እጩዎች የም/ቤት ድምጽ የመስጠት መብታቸው ሳይነሳ ድምጽ እየሰጡ ሰባቱ ካለፉ በኋላ ቀሪዎቹ ባለባቸው ችግር ምክንያት ም/ቤቱ ጣላቸው፡፡ ይህ እንግዲህ የሆነው በፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ መሰረት ነው፡፡
ከዛ ተራው የፅ/ቤትና አስተዳደር ኃላፊ ሆነና ይልቃልና አዲሱ የም/ቤት ሰብሳቢ ተነጋግረው፣ በአንድ የስራ ቀን ሰብሳቢው ቢሮ መጥቶ፣“ከፅ/ቤት ኃላፊነትና ከም/ቤት አባልነት የቱን ትመርጣለህ; ብሎ ጠየቀኝ፡፡ እኔም “እዚሁ የፅ/ቤትና አስተዳደር ኃላፊ ሆኜ መቀጠል ነው የምፈልግው; በማለት ከመለስኩለት በኋላ የም/ቤት አባልነቴን ለቅቄያለሁ፡፡ እንግዲህ ይልቃል ይህን እያወቀ ነው ደንብ ሳይጠቅስ ዳር ዳሩን እየሄደ፣ የኢትዮጵያን ሕዝብና አባላትን ለማደናገር የሚሞክረው፡፡ ሌላው የፓርቲያችን መተዳደሪያ ደንብ አንቀጽ 37 የፅ/ቤትና አስተዳደር ኃላፊው ተጠሪነቱ ለም/ቤቱና ለሊቀመንበሩ ነው ይላል፡፡ ከዛ ደግሞ አንቀጽ 10/8 ደግሞ ከፓርቲው አባላት መካከል በምክር ቤት ሰብሳቢውና በሊቀመንበሩ በጋራ ተመርጦ የፅ/ቤትና አስተዳደር ኃላፊ ይሆናል ካለ በኋላ የምክር ቤት አባል ከሆነ ወንበሩን ለቆ በተለዋጭ አባል ይተካል ይላል፡፡ እንዲሁም አንቀጽ 10/13፤ የፅ/ቤት ኃላፊው በራሳቸው ፈቃድ ከለቀቁ ወይም የዲስፕሊን ጉድለት መፈጸማቸው አግባብ ባለው አካል ተረጋግጦ ከኃላፊነታቸው እንዲለቁ ሲደረግ፣ በቦታቸው በአንቀጽ 10/8 መሰረት ሌላ ሰው ይተካል ይላል፡፡
ሊቀመንበሩ ውሃ በማይቋጥር ቃለ ምልልሱ፤ አውቆ ሳይሆን የሚመራውን ፓርቲ መተዳደሪያ ደንብ ስለማያውቀው፣ ስለ እኔ ኃላፊነት ብዙ አውርቷል፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ የፅ/ቤት ኃላፊው ንብረትና ማህተም አላስረክብም ብሎ አሻፈረኝ ብሏል ይላል፤ማን ጠይቆኝ ለማንስ ላስረክብ ? እሱ እንዳደረገው ወይም እንደጻፈው ደብዳቤ፣ (“በሶስት ቀን ውስጥ ንብረት አስረክበህ ውጣ; ብሎ ነበር) ላድርግ? አላደርግም፡፡ ደንባችንም አይፈቅድም፡፡ ም/ቤቱም ሆነ ኦዲትና ምርመራ ኮምሽንም ከደንባችን አኳያ ይህን እንዳደርግ አልፈቀዱም፡፡
ይልቃል ስለ ጠቅላላ ጉባኤው፣ አራምባና ቆቦ የሚረግጥ መልስ ይሰጣል፡፡ ጉባኤው ከመድረሱ ሁለት ቀን በፊት ዮናታን ለይልቃል ድምጽ እንደሚሰጥ በፌስቡክ ገልጾ ነበር፡፡ የማይደርስ የለምና ጉባኤው ደርሶ ነሀሴ 17 ቀን 2007 ዓ.ም በተደረገው የሊቀመንበርነት ምርጫ ላይ ግን ሌሎቹ የተጠቆሙት አንወዳደርም ሲሉ፣ ዮናታን እንደ ይልቃል በግሉ እንደሚወዳደር በመግለጽ ለእጩነት ቀረበ፡፡ በሁለቱ መካከል በተደረገ የምርጫ ክርክርም፤ ዮናታን የውሸትም ቢሆን የጉባኤተኛውን ቀልብ ሳበ፡፡ በእያስጴድና በዮናስ ከድር አማካኝነት በጉባኤተኛው መካከል እየገቡ ዮናታንን እንዳትመርጡ እያሉ በመቀስቀሳቸው በውጤቱ ዮናታን 66 ድምጽ፣ ይልቃል ደግሞ 136 ድምጽ በማግኘት ምርጫውን ቢያሸንፍም በኋላ ላይ ሁለቱም ስለ ምርጫው የተሰማቸውን አስተያየት እንዲሰጡ በአስመራጭ ኮሚቴው እድል ይሰጣቸዋል፡፡ ዮናታን በሰጠው አስተያየት፤የዛሬ ሶስት ዓመት ሰላሳ ዓመት ስለሚሞላኝ ልምድ ይሆነኛል ሲል፣ ይልቃል ግን በገዛ እጄ አስጠግቼ ጉድ ሆኜ ነበር ብሏል፡፡ የጉባኤውን ፊልም በማየት ይሄን ማረጋገጥ ይቻላል፡፡ ዮናታንም በአዲሱ የይልቃል ካቢኔ የም/ቤቱን ሙሉ ድምጽ በማግኘት የሕዝብ ግንኙነቱን ስልጣን በድጋሚ ቢረከብም አንድ ወር እንኳን ሳይሰራ ከኃላፊነቱ ለቀቀ፡፡ በኋላም ለእስር በቃ፡፡
በደንባችን አንቀጽ 13 የስራ አስፈጻሚው ስልጣንና ተግባር በሚለው ላይ፣ የስራ አስፈጻሚው ተጠሪነቱ ለሊቀመንበሩና ለስራ አስፈጻሚው መሆኑን ይደነግጋል፡፡ ከአንድ እስከ 13 ያሉት ንዑስ አንቀጾች በሚያዙት መሰረትም፤ይልቃል ሊቀመንበር ስለሆነ ስራ አስፈጻሚውን ይከታተል ነበር ወይ ለሚለው መልሱን ለራሱ ትቼዋለሁ፡፡ አሁንም ሆነ በፊት የነበሩት ስራ አስፈጻሚዎች አንዳቸውም ቢሆኑ በተለይ አንቀጽ 13 ንዑስ አንቀጽ 10 በሚያዘው መሰረት፤መመሪያውን አዘጋጅቶ በስራ አስፈጻሚ ያጸደቀ የለም፡፡ ይልቃልም እንዲያዘጋጁ አይፈልግም፡፡ ይህን የሚያውቀው እሱ ብቻ ነው፡፡ ም/ቤቱም ይጨቀጭቃል፤ እሺ በማለት ይታለፋል፡፡ እኔም እንደ ኃላፊነቴ፤ በስንት ጭቅጭቅ የፅ/ቤት መመሪያ አዘጋጅቼ በስራ አስፈጻሚው ጸድቆ እየተሰራበት ነው፡፡ ሌላው ደግሞ የፋይናንስ መመሪያው ሲሆን በኃላፊው ተረቆ  በስራ አስፈጻሚው ተገምግሞ፣ በም/ቤቱ የጸደቀ ቢሆንም በመመሪያው መሰረት የገንዘብ አወጣጥ ስርዓቱ ባለመጠበቁ፣አሁን ለተፈጠረው የገንዘብ ሌብነት ምክንያት ሆኗል፡፡  
ይልቃል ከጉባኤ በፊት በሊቀመንበርነት ዘመኑ፣ በደንባችን አንቀጽ 26 መሰረት መስራት ከነበረበት ውስጥ ስንቱን ሰርቷል? በዛን ጊዜ በደንባችን ውስጥ የሌለ፣ በመመሪያ ያልተገለጸ በቃለ ጉባኤ ያልተያዘ ቢሆንም፣ የሙሉ ቀን ሰራተኛ ሆኖ የአምስት ሺህ ብር የወር ደሞዝ ተከፋይ ነበረ፡፡ ክፍያው አሁንም ድረስ ቀጥሏል፡፡ በእነዚህ ሶስት ዓመታት ውስጥ ቀኑን ሙሉ ቢሮ ሲውል ግን አንድ ነጠላ ወረቀት ፅሁፍ እንኳን ለፓርቲው አበርክቶ አያውቅም፡፡ አንቀጽ 26/6፤ በብሔራዊ ምክር ቤቱና በስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ውሳኔ መሰረት የሚወጡ ደብዳቤዎችና ሰነዶች ላይ ይፈርማል ይላል፡፡
በእርግጥም እሱን ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ ከእዚያ ውጪ እድሜ ለቴክኖሎጂ፣በሞባይሉ ጌም ሲጫወትና ሌሎች ተግባራትን ሲያከናውን ነው ጊዜውን የጨረሰው፡፡ አሁን ደግሞ የማያመጣው ሰበብ የለ፣ ከመደብደብ ብዬ ቢሮዬን ወደ ካፌዎች አዛውሬያለሁ ይለናል፡፡
ሌላው ደግሞ በእሱ በኩል ካለው ጎራ፣ ብዙ ተተኪ አመራር ሊሆኑ የሚችሉ ወጣቶች አሉ ይለናል፡፡ ለመሆኑ ይልቃል ደጋፊ እንጂ አባል የሚሆኑ ወጣቶችን በዙሪያው ያስጠጋል? አጠገቡ ያሉት እስቲ በሚጽፉት የፌስቡክ ፅሑፍ ይመዘኑ፡፡ ከይልቃል አመራር ጋር ወደፊት የሚሉና ድርጅትን ሳይሆን ግለሰብ አምላኪ፣እድሜያቸውም ከሃያ አራትና ሃያ አምስት የማይበልጡ እኮ ናቸው፡፡ በመጨረሻ ለይልቃል ጥቂት ጥያቄዎች ላቀርብለት እወዳለሁ፡- “እስቲ በዙሪያህ ሆነው ያንተን ስልጣን ይናፍቁና ይጠብቁ ከነበሩ ወጣቶች ውስጥ ምን ያህሉ ከጠቅላላ ጉባኤ በኋላ እስር ቤት ገቡ? ምን ያህሉ አገር ጥለው ተሰደዱ? ምን ያህሉን በወያኔነት ፈረጅካቸው?; ይህንን ነው መመለስ ያለበት፡፡ ቅድም እንዳልኩት፤ የፓርቲውን መተዳደሪያ ደንብ አንቀጾች በግድ ግለጽ አልለውም፡፡
 ለምን ቢባል ? እሱ ቀርቶ አሁን በስራ ላይ ያሉት የስራ አስፈጻሚ አባላት ቁጥር ሰባት መሆናቸውን እንኳን ዘንግቶ፣ስራ አስፈጻሚው በተሟላ መልኩ ስራውን እየሰራ እንደሆነ ነግሮናል፡፡ እናም አልፈርድበትም፡፡





    አዲስ አድማስ ሚያዝያ 8 ቀን 2008 ዓ.ም፤“የካቴድራሉ ካህናትና ሠራተኞች፤ ለታላቁ ሕዳሴ ግድብ ያዋጣነው ከ400ሺ ብር በላይ ገንዘብ የገባበትን አናውቅም፤አሉ” በሚል ያወጣው ዘገባ የተሳሳተ ነው ሲል አስተዳደሩ አስተባበለ፡፡
የካቴድራሉ ካህናትና ልዩ ልዩ ሠራተኞች ሚያዝያ 7 ቀን 2003 ዓ.ም. ባካሔዱት ስብሰባ፤በስድስት ወር ተከፍሎ የሚያልቅ የአንድ ወር ደመወዛቸውን ለታላቁ የሕዳሴ ግድብ ግንባታ ለመስጠት መወሰናቸውን በማስተባበያው ያስታወሰው አስተዳደሩ፤በውሳኔው መሠረት “ከደብራችን ሙሉ ካህናት የተዋጣው ገንዘብ 117 ሺ 549 ብር እንጂ በዘገባው እንደተጠቀሰው፣400 ሺ ብር አይደለም፤” ብሏል፡፡
የተሰበሰበውም ገንዘብ የክፍያ ሰርተፊኬት ተዘጋጅቶለት፣በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አዲስ አበባ ቅርንጫፍ ለታላቁ የሕዳሴ ግድብ ገቢ መደረጉንና ለዚኽም የማረጋገጫ ሰነድ መሰጠቱን ካቴድራሉ ገልጿል፡፡ ካህናቱ የቦንድ ሰርተፊኬቱን የሚያገኙበትንም መንገድ በተመለከተ፣“ቤተ ክርስቲያኒቱ ከግድቡ ጽ/ቤት ጋር እየተከታተለች ነው፤” ብሏል - ካቴድራሉ በማስተባበያው፡፡
ሚያዝያ 8 በወጣው ዘገባ የተጠቀሰው 400ሺ ብር ከካህናቱና ከሠራተኞቹ ተሰብስቦ እንደኾነ የካቴድራሉ አስተዳዳሪ መልአከ ሰላም አባ መንግሥተ ኣብ ገብረ እግዚአብሔር ከአዲስ አድማስ ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ፤“ያ ገንዘብ ተሰብስቧል፤ከእኔ ጀምሮ ተቆርጧል፤ሒሳብ ሹሙና ቁጥጥሩ ናቸው ገንዘቡን ተቀብለው ገቢ ያደረጉት” ማለታቸው ይታወሳል፡፡
በተመሳሳይ ዘገባ ላይ ለህዳሴው ግድብ ከሠራተኛው የተሰበሰበው ገንዘብ ገቢ የተደረገው በንግድ ባንክ ሥላሴ ቅርንጫፍ እንደነበር የተናገሩት የወቅቱ የካቴድራሉ ሒሳብ ሹም እማሆይ እኅተ ማርያም ገብረ ሥላሴ፤ያንን ያሉት በስሕተት መኾኑን አምነው፣ በማስተባበያው የአዲስ አበባ ቅርንጫፍ ተብሎ የተጠቀሰው ትክክል እንደኾነ አረጋግጠዋል፡፡  ሒሳብ ሹሟ ወደ ባንክ የገባው ገንዘብ ምን ያህል እንደነበር በወቅቱ ተጠይቀው፣ መጠኑን እንደማያስታውሱት መናገራቸው አይዘነጋም።


ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ሐኪም በሽተኛውን ሊጠይቅ ወደ በሽተኛው ክፍል ይሄዳል፡፡
ሐኪም፡
“እንደምናደርክ ወዳጄ?”
በሽተኛ፡
“ደህና ዶክተር፤ አንተስ ደህና አደርክ?”
ሐኪም፤
“እኔ ደህና አድሬአለሁ፡፡ ለመሆኑ ህመምህ እንዴት ነው?”
“በጣም ያልበኛል እንጂ ደህና ነኝ”
ሐኪም፤
“ይሄ ጥሩ የመዳን ምልክት ነው፤ አይዞህ” አለውና ሄደ፡፡
በሶስተኛው ቀን ሐኪሙ ደግሞ በሽተኛውን ሊያይ መጣ፡፡
ሐኪም፤
“እንዴት አደርክ ወዳጄ?”
በሽተኛ፤
“ደህና ነኝ፡፡ እንደምነህ ዶክተር?”
ሐኪም፤
“እህ፤ ዛሬስ ህመምህ እንዴት ነው?” አለው፡፡
በሽተኛውም፤
“በጣም ደህና ነኝ ዶክተር፡፡ ግን ህመሙ ያመጣብኝ አዲስ ጠባይ ደግሞ፤ ማታ ማታ ያንቀጠቅጠኛል”
ሐኪም፤
“ኦ እሱም ጥሩ የመዳን ምልክት ነው! አይዞህ” አለውና ትከሻውን መታ መታ አድርጎት ሄደ፡፡
ሐኪሙ በሶስተኛው ቀን መጣና፤
“እህስ ዛሬስ ህመምህ እንዴት ነው?”
በሽተኛ፤
“ደህና ነኝ፣ ግን አሁን ደግሞ ትኩሳት ለቀቀብኝ”
ሐኪም፣
“እሱም፣ ጥሩ የመዳን ምልክት ነው፡፡ አይዞህ” ብሎት ሄደ፡፡
በመጨረሻ ሐኪሙ ለአራተኛ ጊዜ መጥቶ፤
“እህስ ወዳጄ ዛሬስ እንደምንድነህ? በጣም ተሻለህ አይደል?” ብሎ ጠይቆ እንደተለመደው “ጥሩ ምልክት ነው” ብሎት ሄደ፡፡ ከዚህ በኋላ አንድ ዘመዱ በሽተኛውን ሊጠይቀው መጣና፣
“እህስ ወንድሜ እንዴት ከርመሃል?” ሲል ጠየቀው፡፡
በሽተኛውም፤
“ኧረ ባክህ ተወኝ ወንድሜ፤ ‹ጥሩ ምልክት› በዝቶብኝ ልሞትልህ ነው” አለው፡፡
*           *           *
“ወፍራም ውሻ አለ ሲሉት ይሞታል” ይላሉ አበው፡፡ የምንሄድበት ቦታ፣ የምንረግጠውን ምድር ሁሉ፣ “ቅዱስ፣ ቅዱስ” እያልን ካሞካሸነው እንከኑን ለማየት ዐይናችን ይታወራል፡፡ መልካም ነው፣ ጥሩ ምልክት ነው ማለት ለአዎንታዊ ተስፈኝነቱ (Optimism) ትልቅ ፀጋ ነው። ሙገሣው ብቻውን ከሆነና ተግባር ላይ ከለገምን በ “ጥሩ ምልክት” እንሞታለን፡፡ ስለ ሀገር ደግ አለማውራት ደግ አይደለም፡፡ ደግ ደጉን ብቻ ማውራትና ለክፉ ክፉው ዐይንንም ጆሮንም መዝጋት ግን፤ ሁኔታው ድንገት የሚያፋጥጠን ደረጃ ላይ ከደረሰ መደነባበርን ያስከትላል፡፡ አለመዘጋጀት እርግማን ነው፡፡ መረጃው ደርሶን ለመዘጋጀት አለመቻል፤ የእርግማን እርግማን ነው፡፡ አለመዘጋጀታችን ያደረሰውን ጥፋት አይተን እጅን - አጣጥፎ መቀመጥን ከመረጥን ደግሞ ከመኖር ወደ አለመኖር መለወጥ ነው፡፡ ዛሬ ሀገራችንን፣ በተጓዘችው የለውጥ መጠን ስናሰላት፤ በፖለቲካውና በዲፕሎማሲው መስክ፣ በተለይ በጎረቤት አገሮች አኳያ ስናጤናት፣ ጤናማና የበሰለ መንገድ ዘልቃለች ብንል ሀሰት አይሆንም፡፡ የራሷን ሳታስነካ፣ የሌላውን ሳትነካ ተራምዳለች ማለት አይደለም፡፡ ይሄ “ማታ የምትበላውን  ጧት አሳስቀው” በሚለው በበርናርድ ሻው ዲፕሎማሲያዊ ምፀት ሳናስበው ነው፡፡ ድንበራችንን ማስከበር፣ ጠረፋችንን መጠበቅ የዋዛ አጀንዳ አይደለም፡፡ “ባለቤቱን ካልናቁ አጥሩን አይነቀንቁ፡፡ የሚለው መሪ ብሂል፤ የዳር ድንበራችንን ነገር በውል ያፀኸይልናል፡፡ ከወረራ እስከ ተራ ሽፍታ ዘረፋ፤ በድን በርም መጣ በውስጥ ቡርቦራ፣ በአገር የመጣ ነገር ምጣት ነው፡፡ ሰሞኑን የደረሰው ሁሉ አሳዛኝ፣ አረመኔአዊ ጭፍጨፋነቱ አሌ ባይባልም፤ ሉዓላዊነትን በዘዴ ማስከበርም ጥበብንና ብልሃትን የግድ ይላል፡፡ የሞቱት ወገኖቻችን ናቸው፡፡ የታገቱት ወገኖቻችን ናቸው፡፡ በዚህም ተባለ በዚያ የዋሃንን መጨፍጨፍ አረመኔአዊነት ነው፡፡ የህዝባችን፣ የሀገራችን ዕንባ ረግፎላቸዋል፡፡ ማዕከላዊ መንግስት እያለ አረመኔያዊ ተግባር ምላሽ አልባ አይሆንም፡፡ ለዘለቄታው መንቃት ደግ ነው፡፡ ሆኖም የአጎራባች አገሮችን ታሪካዊ ዝምድና ውሉን እንዳይስት መላ መላ ማለት መሰረታዊ ፍሬ ነገር ነው፡፡ የዳር ድንበራችን ጉዳይ የአንድ አቅጣጫ ነገር አይደለም፡፡ ሀገራችን በዙሪያዋ ካሉት ጎረቤት አገሮች አንፃር ሀብት ጠገብ ናት፡፡ ምናልባትም የንፍቀ - ክበቡን የሰላም ኃላፊነት ብትወሰድ አይገርምም፡፡ የአፍሪካ ህብረትና የተባበሩት መንግሥታት ወካይ ድርጅቶች መናኸሪያ ናት፡፡ የመካከለኛውን ምሥራቅ ቀጠና አሻግሮ ለማየት ዓይነተኛ ማማ ናት፡፡ የታሪክና የቅርስ አገር ናት፡፡ በጂኦግራፊያዊ አቀማመጧ ብዙዎች ከጥንት እስከ ዛሬ የሚጎመጇት ተፈጥሮአዊ ስትራቴጂን የታደለች አገር ናት፡፡ በራሷ የግል ውስጣዊና ውጪአዊ ሁኔታ መልካም መደላድል ላይ አላረፈች እንደሆነ እንጂ በዳር - ድንበሯ እንኳ አትደራደርም!! ይህን የማያውቁ አካላት አንዳች የድፍረት እርምጃ እንውሰድ ቢሉ፤ “ውሻ በእግር መምታት፣ እንካ ሥጋ ብላ ማለት” የሚባለውን የአበው ተረት መዘንጋት ነው!!

 - ወንድማቸው ራኡል ካስትሮ በኮሙኒስት ፓርቲ መሪነቱ ይቀጥላል

    ኩባን በመምራት ላይ የሚገኘው ወንድማቸው ራኡል ካስትሮ በኮሙኒስት ፓርቲ መሪነቱ እንደሚቀጥል ባለፈው ማክሰኞ መገለጹን ተከትሎ፣ የቀድሞው የአገሪቱ አብዮታዊ መሪ ፊደል ካስትሮ፣ ለፓርቲው አባላት ባደረጉት ንግግር፣ መሞቻዬ ደርሷል፣ ተግታችሁ የኔን ሃሳቦች ተግባራዊ ማድረጋችሁን ቀጥሉ ሲሉ መልዕክታቸውን ማስተላለፋቸውን አሶሼትድ ፕሬስ ዘገበ፡፡
ለአመታት ከአደባባይ ርቀው የቆዩት ካስትሮ ለፓርቲያቸው አባላት ባደረጉት ንግግር፣ በቅርቡ 90 አመት ይሞላኛል፤ ወደማይቀርበት ሞት የምሄድበት ጊዜም ተቃርቧል፤ እንግዲህ በርቱና የኩባን ኮሙኒስቶች ሃሳቦች ህያው ሆነው እንዲቀጥሉ የተቻላችሁን ሁሉ አድርጉ ብለዋል፡፡
ከ55 አመታት በፊት አንስቶ አገሪቱን በመምራት ላይ የሚገኘውን የኩባ ኮሙኒስት ፓርቲ ያቋቋሙት ፊደል ካስትሮ ባጋጠማቸው የጤና እክል  በ2008 ስልጣናቸውን መልቀቃቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ፊደል ካስትሮ ያደረጉት ንግግር ፓርቲው በአዲሱ ትውልድም ከስልጣኑ እንዳይለቅ ለማሳሰብ የታለመ ነው መባሉንም ገልጧል፡፡

 በህንድ ለሁለት ተከታታይ አመታት የዝናብ እጥረት መከሰቱንና የሙቀት መጠን በከፍተኛ ሁኔታ መጨመሩን ተከትሎ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች የተከሰተው ድርቅ ከ330 ሚሊዮን በላይ ዜጎችን ተጠቂ እንዳደረገ የአገሪቱ መንግስት ማስታወቁን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
በአብዛኞቹ የአገሪቱ አካባቢዎች የሙቀት መጠኑ ከ40 ዲግሪ ሴንቲግሬድ በላይ ሆኗል ያሉት የአገሪቱ ባለስልጣናት፣ የውሃ እጥረትና ሌሎች ችግሮች ተጠቂ የሆኑት የአገሪቱ ዜጎች ቁጥር በቀጣይም ይጨምራል ተብሎ እንደሚጠበቅ መናገራቸው ተዘግቧል፡፡
በአገሪቱ  ላለፉት ሁለት ተከታታይ አመታት የዝናብ እጥረት መከሰቱን የጠቆመው ዘገባው፣ ይህም ከፍተኛ የውሃ እጥረት መፍጠሩንና ተላላፊ በሽታዎች በርካታ ዜጎችን ለህልፈተ ህይወት እየዳረጉ እንደሚገኙና ድርቁ፣ የአገሪቱን ሩብ ያህል ግዛት በሚሸፍኑ 256 አውራጃዎች መስፋፋቱን ገልጧል፡፡
በአንዳንድ አካባቢዎች ትምህርት ቤቶች መዘጋታቸውና የዕለት ከዕለት እንቅስቃሴዎች መስተጓጎላቸው የተነገረ ሲሆን፣ በዝናብ እጥረት ሳቢያ ላለፉት ሁለት አመታት ምርታማነት መቀነስ መታየቱ በቀጣይ የከፋ ርሃብ ሊያስከትል ይችላል የሚል ስጋት መፍጠሩንም ዘገባው አስረድቷል፡፡
የአገሪቱ መንግስት ለዜጎች ውሃ ከማቅረብ ባለፈ፣ ከድርቁ ጋር ተያይዞ የተከሰቱ ችግሮችን ለመቅረፍ እየተረባረበ እንደሚገኝም ተነግሯል፡፡

  - ገዢው ፓርቲ የጀመረውን ልማት እንዲቀጥል እንፈልጋለን ብለዋል
     በመጪው ነሃሴ ወር አገር አቀፍ ምርጫ ለማካሄድ በመዘጋጀት ላይ ባለቺው ዛምቢያ የሚንቀሳቀሱ 13 ተቃዋሚ ፓርቲዎች በምርጫው ገዢው ፓርቲ ወክለው ለሚወዳደሩት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ኤድጋር ሉንጉ ድምጻቸውን እንደሚሰጡ መግለጻቸውን ኒውስዊክ ዘገበ፡፡
በተናጠል ይንቀሳቀሱ የነበሩት 13 አነስተኛ የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ናሽናል ኦፖዚሽን አሊያንስ በሚል ጥምረት ፈጥረው በጋራ እየሰሩ እንደሚገኙ ያስታወሰው ዘገባው፣ ጥምረቱ ሰሞኑን በሰጠው መግለጫ በመጪው ምርጫ ለፕሬዚዳንቱ ድምጹን እንደሚሰጥ አስታውቋል፡፡
የጥምረቱ አባላት የሆኑ የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችም፣ ጥምረቱ በምርጫው ተሳትፎ የምክር ቤት አባል በመሆን ከገዢው ፓርቲ ጋር ተስማምቶ የፖለቲካ እንቅስቃሴውን እንደሚቀጥል ጠቁመው፣ የአባል ፓርቲዎቹ የግል መርሆዎች ግን ተጠብቀው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል፡፡
ኤድዊን ሳካላ የተባሉት የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ጥምረቱ ገዢው ፓርቲ የጀመራቸውን የልማት ፕሮጀክቶች ተፈጻሚ ማድረጉን እንደሚደግፍ በመጠቆም፣ በመሆኑም ለፓርቲው መሪ የምርጫ ድምጹን እንደሚሰጥ አቋም መያዙን ተናግረዋል፡፡

 - ኤርትራ በከፋ የፕሬስ ነጻነት አለምን ትመራለች
                - ኢትዮጵያ የ142ኛ ደረጃን ይዛለች

      ሪፖርተርስ ዊዝአውት ቦርደርስ የተባለው አለማቀፍ የፕሬስ መብቶች ተሟጋች ተቋም ባለፈው ረቡዕ ይፋ ባደረገው የ2016 የአለማችን የፕሬስ ነጻነት አመልካች ሪፖርት፣ የፕሬስ ነጻነት አፈና በአለማቀፍ ደረጃ መባባሱንና ጋዜጠኞች በሙያቸው ሳቢያ እስራትን ጨምሮ የተለያዩ ጥቃቶች እንደሚደርስባቸው አስታወቀ፡፡
ተቋሙ በአለማችን 180 አገራት ላይ በሰራው ጥናት፣ መንግስታት ለጋዜጠኞች ያላቸው ፍራቻ እየጨመረ በመምጣቱ በ2015 በነጻው ፕሬስ ላይ ልዩ ልዩ ጫናዎችን ሲያደርጉ እንደነበርና ጋዜጠኞች ነጻ ሆነው ዘገባዎችን ለመስራት በርካታ እንቅፋቶች ይገጥሟቸው እንደነበር ማረጋገጡን ገልጧል፡፡
የሚዲያ ነጻነት፣ ግልጽነት፣ የህግ የበላይነትና ሌሎች መስፈርቶችን በመጠቀም ተቋሙ የሰራው አመታዊ ሪፖርት በ2016 የአለማችን የፕሬስ ነጻነት ደረጃ ቀዳሚውን ስፍራ የያዘቺው ፊንላንድ መሆኗን ጠቁሞ፣ ኒዘርላንድስና ኖርዌይ ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃ መያዛቸውን አስታውቋል፡፡
የከፋ የፕሬስ ነጻነት ያለባትና ከአለማችን አገራት በመስኩ የመጨረሻውን ደረጃ የያዘቺው ኤርትራ ናት ያለው ተቋሙ፣ ሰሜን ኮርያ እንደምትከተላት ጠቁሞ፣ ኢትዮጵያ ከአለማችን 180 አገራት የ142ኛነት ደረጃን መያዟንም ሪፖርቱ ገልጧል፡፡
በሁሉም የአለማችን አካባቢዎች የፕሬስ ነጻነት እየቀነሰ መጥቷል ያለው ተቋሙ፣ በተለይ ደግሞ በደቡብ አሜሪካ አገራት ያለው ሁኔታ አሳሳቢ መሆኑን ጠቁሞ፣ በአመቱ የፕሬስ ነጻነት በከፍተኛ ሁኔታ እያሽቆለቆለ የመጣባቸው የአለማችን አገራት ቱርክና ግብጽ መሆናቸውን አብራርቷል፡፡

Saturday, 23 April 2016 10:30

ትናንት ዛሬን ሲበድለው

የዮርዳኖስ ጉዕሽ ልቡሰ ጥላ ሲነበብ
ዕዝራ አብደላ
[ደራሲዋ፥ ዮርዳኖስ ጉዕሽ]


“`ውበትሽ ከሌሎች ይለያል። ውስጥ ውስጡን እየሰረሰረ የሚገባ ነገር አለሽ` ብሎ ዓይኖቹን በመነፅሩ ውስጥ ተከለብኝ። እዩት እንግዲህ አፉን ሲከፍት፤ ምናለ ስለውበት ምንም አስተያየት ሳይሰጥ እንደወደድኩት ብቆይ።”
[መልካም ግርማ -ገፀባህሪ-፥ ገፅ 52-53]
--ክፍል 2 --
ደራሲዋ በቋንቋ ብስለቷ አትታማም፤ የቃላት እጥረት አይፈትናትም። ሆኖም ለውበት ለዘይቤው አእምሯችን ውስጥ የሚፈካ ዐረፍተ ነገር ያጣራታል። አልፎ አልፎ ለምልክት ያክል ይንጠባጠባሉ። ለምሳሌ ሚልኪ እህት ወንድሞቿ አገልለዋት የተቆጨችበት ገለጣ ከምናባችን ይነዝራል።“በእናቴ ወሬ ጠልተውኛል ... ምናልባት እኔ የረገጥኳትን ፈንጂ የረገጡ ዕለት ይረዱኛል፤ አዝነው ያለቅሱልኛል።”ጊዜና ገጠመኝ ግለሰብን ያበስላል ከማለት የላቀ ነው። ወይም በእውቀት መረቧን ዘርግታ ያጠመደችው ቀጭን ወጣት አብረው አድረው በማግስቱ ትክ ብላ ስታጤነው የተጋባባት ስሜት። “ይሄ ልጅ ግሩም ፍጥረት ነው፤ ካለምንም ጥያቄ ነፍስን ይቀርባል። ከእኔ ገላ ጋር ይናበባል። ከርቤ፥ ናርዶስ ... ከገላው ይረጫል።” ትናንት ምሽት ተዋውቄው ለምን በአንድ ሌሊት አወላልቄ ገላዬን መዘመዝኩለት የመሰለ ተራነት አላፈናትም፤  በአካል መጣጣም፥ ለቁስ ሳይሆን ለስሜት መርበትበት፥ እና ለውበት ጊዜን ቆርሶ መለገስ ያጋባባትን ብርቅ ደስታ እንዴት ትግለጠው?
ደራሲ ዮርዳኖስ ትንፋሽ አላጠራትም፤ የህይወትን ውጣ ውረድ፥ የሴትን እንግልት፥ የኅላዌ ፍጥጫ ድርጊቱ እሳቦቱ በጥሬው ከቧጠጠን፥ በዘይቤ ጥፍሮቹን ማሾል ለምን ያስፈልገዋል ባይ ናት። “እንደ ለመድናቸው ድርሰቶች በቃላት ውበት ላይ፥ በዓረፍተ ነገር ቅንብር ላይ አልተጨነቀም። ትኩረቱ በጥልቁ አእምሮ ላይ ነው።” ብላለች ስለ ልቦለዷ። መቼም የሴት እንባ፥ የፈካና የነተበ ፈገግታዋ፥ ጥንካሬና ውበት፥ ተስፋና ስጋት ብሎም ሥነልቦናዊና ማኅበራዊ መዘዝ ሲታሰበን የበአሉ ግርማ ሉሊት ድቅን ትላለች። ለአምስት አሰርታት  ያልፈዘዘችበት አንድ ምክንያት በደራሲው የቋንቋ ምትሀት ለዘልአለም መፈጠሯ ነው። ልቡሰ ጥላ ዳግም ቋንቋው ተላልጦ ተከትፎ ቢታተም ጥበባዊ ደረጃው በበለጠ ያደናግዛል። ሆኖም አጻጻፏ ተራ አይደለም፤ ቋንቋዋ አይቸክም። ልቦለዷ ከመዋቅር አንፃር ዘመም እንዳይል የበጇት አራት አላባዊያን አሉ።
አንድ፥ ገፀባህሪያት ሲወያዩ ይመስጣሉ።
“ሃይ አብረን ብንጠጣ ምን ይመስልሃል?”
“ብቻውን የሚጠጣ ወንድን የምትጋብዝ ሴት!” ... በለበጣ የሰጠኝ መልስ።
“በል ዛሬ የእድልህ ቀን ነው። ብቻውን የሚጠጣ ወንድን የምትጋብዝ ገጠመችህ።” ሳይጋብዘኝ ከግራው ካለው ክፍት ወንበር ላይ ተቀመጥኩ። እኔን ለማየት እንዲመቸው ፊቱን ከነመጠጡ ወዳለሁበት ዞረ። [ገፅ፥ 98-99]
የተማረች፥ ደሞዝተኛ ወጣት ነፍሷን ለመቀሸር፥ ብቻዋን ሙዚቃ እያደመጠች ከስሜት ጭጋግ ለመላቀቅ ከቡና ቤት መጠጥ አዛ ቁጭ ብላለች። የሆነ ጥግ የተቀመጠ ወንድ ማረካት። ባህላችን ዛሬም እቺን የመሰለች እንስት እንደ ጋጠወጥ ይገላምጣታል። ስር የሰደድ ተራ አመለካከት የምትፃረር ዘመነኛ ሄዋን፥ የፈቀደችውን ስትናገርና ስትፈፅም ወንዱ ግር ብሎት ይበረግጋል። ይህን የመሰለ በውይይት የደመቀ ሁለት-ሶስት ክስተት ደራሲዋ ልቦለዱ ውስጥ ቀብራለች። ሴትና ወንድ ቦታ የመለዋወጥ አባዜ፥ ቢቀር ቢቀር እንስቷ ለተባዕት የተፈቀደውን በፆታዋ ምክንያት እንዳትነፈግ፥ የመኖር እልህ የልቦለዱ አንድ ጭብጥ ነው።
ሁለት፥  ግጭት። (አንድ ምሳሌ) ሚልኪ ትዳር ምርር ብሏት ከቤት ለመጥፋት ሞክራ አልተሳካላትም፤ ባሏም ችግሯን ለመገንዘብ ከሚያወያያት ሊቀጣት ብድግ አለ።
መላኩ ቀበቶውን ከወገቡ መዠረጠው።
“እና አሁን አንተ ልትገርፈኝ ነው?” ንቀት መላ አካሌን ወረረኝ። ቀበቶውን በድጋሚ ሲያወናጭፍ ፊቴን አገኘው። ቆዳዬ የተገፈፈ መሰለኝ። ግን አላለቅስም። እንባዬን አፍስሼ ለዚህ ደደብ እርካታ አልሰጥም። ... ቀበቶውን ደጋግሞ እላዬ ላይ አሳረፈው። ...
ተወረወርኩ። ከሶፋው ላይ አንገቱን አነቅኩት። ቀበቶውን አስለቀቅሁት። መሬት ላይ ተንፈራፍሬ ቀበቶውን በእጄ ላይ አስገባሁኝ። ቆምኩ፤ ቀበቶውን እንደማረኩ። አወናጨፍኩ ቀበቶውን።
“አንተ የወንድ አውደልዳይ አልጫ! ከቤቴ አርፌ በተቀመጥኩ ትገለኝ? አንገቴን ደፍቼ ስለተገዛሁ ታጐድፈኝ?” ቀበቶውን ሰነዘርኩ አንገቱ ላይ። ... አቀመስኩት ጀርባው ላይ።
ቀበቶውን ያዘው፤ ከቀበቶዬ ጋር ሳበኝ። ሶፋው ላይ ደፋኝ። የሞት ሞቴን ታግዬ ከእምነበረድ የተሰራውን የአበባ ባዝ አነሳሁት። ወረወርኩት። ጥሩ አልሞ ተኳሽ እንደሆንኩ አላውቅም ነበር። አናቱን መሀል ለመሀል ለሁለት ተረከኩት። ጩኸቱን አቀለጠው። [ገፅ፥ 146]
ይህ ግጭት ለሴራው ማድመቂያ ሳይሆን ደራሲዋ የሴት በደል ዝምታና ማቀርቀር እንደማይፈታው፥ ራስን ለማስጣል መወራጨት እንዲሚበጅም የተጠቀመችበት ተምሳሌታዊ ድርጊት ነው። ብዙ ጊዜ ውጭ እያደረ ሲፈቅድ ብቻ ወደ ጐጆው እየተመለሰ ለሰባት አመታት ሚስቱን አንገላታት፤ አቀርቅራ ቆዝማለች። የሥነልቦና፥ የአካልና የርዕይ መነጠቅ ስቃይ ተፈራርቆባት ነው መደባደብ ብቸኛ ደመነፍሳዊ ምርጫ የሆናት። መግቢያና ተገን የመቀማት እልህ የፈጠረው ምላሽ ነው።
ሶስት፥ እሳቦት። ገፀባህሪያት ከራሳቸው ሲወያዩ አልያም በአንድ ነገር ተመስጠው ሲያውጠነጥኑ ለተራም ሆነ ለአንኳር ጉዳይ በየገፁ ጥያቄ ይጫራሉ።
“አሁን በቀን ሶስቴ በልቶ ማደር በህይወት አለሁ ያስብላል? ፈጣሪንስ `ቁርሴን፥ ምሳዬን እራቴን ስላበላኸኝ አመስግናለሁ!` ለመባል ይገባዋል? እግዜርስ ቢሆን ዓይን የለውም? የፈጠረው ሰው ስንት ነገር መፍጠር የሚችል ወርቅ ጭንቅላቱን ለመብላት፥ ተኝቶ ለመነሳት እና ከእጁ፥ ከነፍሱ መንጭቆ ብር በማካበቱ ብቻ `ተመስገን` እያለው ሲኖር እሱስ ምን ይሰመዋል?
እኔ ግን ፈጣሪዬን `ለምን በእኔና በህዝቤ ላይ ተነሳህ? ለምን አዕምሯችንን ንፍጥ በመሰለ የኑሮ ትርኪምርኪ አነተብከው?` እያልኩ ሁሌ እጨቀጭቀዋለሁ። መልሱን የሰጠኝ ቀን ምናልባት አመስግነው ይሆናል። እስከዚያው ግን ስራው ያውጣው።
እናቴን አስታወስኳት፤ ፈጣሪዋን እንዳመሰገነች ሳትጠይቀው ከዚች አለም እልም አለች። አሁን ለምን ይሆን ካልጠፋ ሰው እሷን `ነይ ብሎ` የወሰዳት? [ገፅ፥ 32-33]
በእውቀት የምትኖርበት ማኅበረሰብ የነቀዘ እየመሰላት፥ የኑሮ ከንቱነት እንደብል ወኔዋን በአንድ ወቅት ስለአነተበው ራሷን ለመግደል ሞክራ ነበር። ይህ ከሰው እስከ እግዜር የተወጠረ የኅላዌ ጭንቀት ተባዕት በሴት (የእናቷ ታሪክ) ያደረሰው በደል ታክሎበት ውስጧ የተላወሱ ጥያቄዎች የጥሞና መልስ ይሻሉ። ለሰው ባዶነት፥ ብሎም የምር ሳይሆን በመንሳፈፍ ዕድሜውን እየተረተረ ለተኮፈሰ ፍጡር፥ ... እግዜርን መነዝነዝ የመሰለ እሳቦትም እንደ ማፈንገጥ ነው።
በግለሰብ የዕለት እንቅስቃሴ ሆነ የስሜት ፍላጐት መልካም ስለፍቅር ያጤነችው አያሌ እንስትን ይጐረብጣል።
“እኔ በህይወቴ ውስጥ ሁሌም ወንድ እንዲኖር እፈልጋለሁ። ማለት ሴሰኝነት ምናምን ሳይሆን ፍቅር ሲይዘኝ በህይወት የምር መኖሬ ይሰማኛል። ልቤ ከበሮ ይመታል፤ ጥርሴ አስሬ መስተዋት ፊት ይፈግጋል። ፀጉሬ በሳምንት አንዴ ይተኮሳል። ዘፈን ከከንፈሬ ይለቀቃል። ፍቅር የእኔን ባዶነት ይሞላል። ስለዚህ ከሥራ በኋላ ፍቅር በየቦታው ይፈለጋል።
     እኔ እኮ ፍቅርን እንደሰው `ሙሽራዬ` ተብዬ ተድሬ ከእናቴ ቤት ወደ ባሌ ቤት ለመግባት፥ ወይ ልጆች ወልዶ ዓይኔን በዓይኔ ለማየት አይደለም የምፈልገው። `የእናት ቤት ማደጊያ እንጂ መጦሪያ እንዳልሆነ` ድሮ እናቴ ስለነገረችኝ ቤት ለመከራየት አቅም አዳብሪያለሁ። ግን ብቸኝነትን በጣም እፈራለሁ። እኔ ፍቅር ለመተንፈስ፥ መኖሬን ለማወቅ ነው የምፈልገው።” [ገፅ፥ 41-42]
“ፍቅር ሲይዘኝ በህይወት የምር መኖሬ ይሰማኛል” ቀላል ጉዳይ አይደለም። ልጅነቷን የቦረቦራት ብቻነት፥ እናቷም ጭምር የገፈተሯት ህፃን ሆና ማደግ፥ እውስጧ ያደባው የአለመፈለግ ስጋት በደመነፍስም ቢሆን የሆነ የወንድ ጠባብ ጥግ እንኳን ለመውረስ መዘመዛት። ጐጆ እስከ መቀለስ ባይሆንም፥ ከዳር ከጠርዙም ቢሆን የተባዕት የልብ ትርታ የሚሾርበት የሆነ የኅላዌ ምሽግ ያስፈልጋታል። ለህይወት መፍካት ሆነ መጠውለግ፥ ትንሽ-ትልቅ ብሎ የጉዳይ ድንበር መከለል ሳይሆን ሁለቱም ሴትን ሊኮሰኩሳት ይችላል።
አራተኛው እና ልቦለዱ ሳይሰለች -ቢድግሙትም- እንዲነበብ ያደረገው የአተራረክ አትኩረት ማለትም የአንፃር ምርጫ ነው። ሶስቱም የተማሩ ወጣት ሴቶች ተራ በተራ ያወጋሉ። በአንደኛ ደረጃ አንፃር `እኔ` እየተባለ ሲተረክ ከአንባቢ ጋር ቅርበት ይፈጥራል። የሶስቱም አኗኗር ህልምና እሳቦት የተለያየ በመሆኑ ድግግሞሽ አይደለም። የዩኒቨርስቲ ተማሪ ሳሉ ነው የተዋወቁት። በእውቀትና መልካም ተመርቀው ራሳቸውን ችለዋል። ሚልኪ ሳይሳካላት ቀርቶ ትዳር መስርታ ልጅ ወልዳለች። የሴትን ህይወት ጥንቃቄና ድፍረት ከሶስት አቅጣጫ ተተክሮበታል። የትረካውን ፍስት የሚገድብ የሁነቶች መጐማመድ አንባቢን ያደናግራል።
እያንዳንዷ ገፀባህሪ በሶስት አራት ገፅ ብቻ ህይወቷን ስትተርክ በፈረቃ ስለሆነ፥ በተለይ የመልካምና የበእውቀት ቤትና ልጅነት ያደናግራል። ሶስቱ የትረካ አቅጣጫ እንደተጠበቁ ሆነው በቁርጭራጭ ሳይሆን እስከ ጥግ ቢያወጉ ይመረጣል፤ ምክንያቱም ሶስቱም ስለ አንድ ጉዳይ አያወጉም፤ የየግል እንቅስቃሴያቸውን ነው የሚተርኩት። ዮርዳኖስ፥ ዳግም ልታሳትመው ካሰበች ሶስቱ ገፀባህሪያት እስከሚገናኙበት ክስተት ምዕራፎችን መገጣጠም ይኖርባታል። እንድታቅማማ የሚገፋፋት ለምሳሌ በእውቀት ስታወጋ ድንገት የሚልኪ ስም ቢጠቀስ፥ አዳም ረታ እንደአደረገው በግርጌ ማስታወሻ ከአርታኢው ተብሎ ስለሚልኪ ይጦቀማል።
ደራሲዋ ለልቦለዷ “ልቡሰ ጥላ” የሚል ርዕስ ብትጠቀምም ምን እንደሆነ አታብራራም። ይህን ቃል መጀመሪያ የተጠቀመው በ “አድፍርስ” ልቦለዱ ዳኛቸው ወርቁ ነበር። ርዕሱ ግራ የገባው በድረገፅ መፅሃፉን የሚሸጠው imaginary shadow ብሎታል፤  ምናባዊ ጥላ እንደማለት። እንደ ዳኛቸው አጠቃቀም ቃሉ ለ subconcious  ታህተ-ንቃት ያደላል። “`ልቡስ ጥላ` ለአደፍርስ ገፀባህሪይ መያዣ መጨበጫ የሌለው ምስቅልቅል ሁኔታ ነው። ከአእምሮ ክፍሎች በአነስተኛው ልዩ ልዩ ነገሮች ማየትና ማውጠንጠን ከጀመርንበት ጊዜ አንስቶ የሚጠራቀም ነው።” ከኑሮ  ከንባብ ከባህል ልብ ሳንለው አእምሯችን ውስጥ እየቃረምነው የሚዘቅጥ ተግባራችንን ሊጫን የሚችል ጥርቅም ነው።
የዮርዳኖስ ልቦለድ አንድ ጭብጥ፥ ከልጅነት ጀምሮ ከውስጠ አእምሮ ያደባው ጥርቅም የዛሬ እኛነታችንን መበደል መቻሉ ተተኩሮበታል። ህይወትን ለማወክና ለማመሳቀል አቅም አለው። ሚልኪ የአባቷ ግፍ የእናቷ መሽቆጠቆጥ ከአእምሮዋ ተቀብሮ ለራሷም ለእናቷም እንግልት እንደ መበቀል ባሏን ገድላ ተገላገላለች።
መልካም፥ እናቷ ከተለያየ ወንድ ስትዝናና፥ አባቷ በቅናት ሲበግን፥ እሷም እንደ ትርፍ ተቆጥራ መገፍተሯ፥ ዛሬ ብቻዋን መሆን እያሰጋት፥ከሆነ የወንድ ጉያ ውስጥ ለመወሸቅ አበቃት። በእውቀት እናቷን ጠይም ልዕልት ብላ ነው የምትጠራት። በአስራ ስድስት አመቷ ለአዛውንት ተድራ ለሰባት ዓመታት በአካልም በሥነልቦናም ከማቀቀች በኋላ፥ ወጣት ሳለች ከወንድ ሸሽታ ደስታን ተነፍጋ አልፋለች። ዛሬ በእውቀት ለእናቷም ጭምር እድሜዋን እያጣጠመች፥ የፈቀደችውን እያደረገች ከማኅበረሰቡ ተላትማ ትኖራለች። ምናልባት ደራሲዋ ይህ ልቦለዷ “... ከድርጊት እና ከንግግር ጀርባ ወዳለው ጥልቅ አለም ይወስደናል።” ስትል ያው ልቡሰ ጥላችንን እንደ መቦርቦር ነው። ለሌላው ተሸፋፍነን የምንቀርብ ብንሆንም ለራሳችን ግን ዥንጉርጉር ነን እንደ ማለት።
ስር የሰደደ ለእንስት የተፀናወተንን ንቀት፥ ይህ ልቦለድ ለመጋፈጥ ሞክሯል። የመረጠችውን ህይወት እየወለወለች፥ በራሷ ብቻ ተማምና ያማራትን እየላጠች፥ በግልፅ የምትናገርና የምታውጠነጥን  አዲስ ሴት ገፀባህሪ ተመልምላለች። ጥንትም አርስጣጣሊስ እንዳወጀው “The female is female by virute of a certain lack of qualities.” እንስት፥ እንስት የሆነችው የአይነት የጥራት ፀጋ ስለሚጐድላት ነው። ብዙ ሰው የሚያምነው “A woman is an imperfect man” በሚለው ነው። ሴት ያልተሟላ ጐደሎ ወንድ ናት እንደ ማለት። በአገራችንም አሁንም ድረስ የወረስነው ለሄዋን ዝቅተኛ አመለካከት ከኢ-ንቁ አእምሮ እያደፈጠ አንደበታችንና ልባችን እኩል አይነዝሩም። “የሴት እውቀትና የዶሮ ሩጫ፥ከአውድማ አያልፍም”  ብሎ እንስትን ለሚገላምጥ ማኅበረሰብ፥ የዮርዳኖስ ጉዕሽ ልቦለድ ፈታኝ ነው።
የፆታ ጥያቄ ሳይሆን ሴትና ሰው፥ ለበጐም ለክፉም የማይሰነጣጠቁ ውስብስብ ኅላዌ ናቸው። ታድያ ዝምታዋ እየዳደረ ብትዘገይም፥ ዮርዳኖስ ለምን ተጨማሪ አዲስ ልቦለድ ነፈገችን?


Saturday, 23 April 2016 10:28

የዘላለም ጥግ

- ጥበብ አንድም ስርቆት ነው አሊያም አብዮት ነው።
ፓውል ጋውጉዪን
- የነፃነት ፍቅር ሌሎችን ማፍቀር ነው፤ የሥልጣን
ፍቅር ራሳችንን ማፍቀር ነው፡፡
ዊልያም ሃዝሊት
- ተንበርክከህ ከመኖር ቆመህ መሞት የተሻለ ነው፡፡
ዶሎሬስ ኢባሩሪ
- ኪነ - ህንፃ ቦታን እንዴት ማባከን እንደሚቻል
የማሳያ ጥበብ ነው፡፡
ፊሊፕ ጆንሰን
- ማውራትና አንደበተ - ርቱዕነት አንድ አይደሉም፤
መናገርና በቅጡ መናገር ሁለት የተለያዩ ነገሮች
ናቸው፡፡
ቤን ጆንሰን
- ጋዜጠኝነት ባዶ ቦታን የመሙላት ፈተናን
የመወጣት ችሎታ ነው፡፡
ሬቤካ
- ሰዎች ስለ ሥዕል እኔ የማውቀውን ያህል ቢያውቁ
ኖሮ ስዕሎቼን ፈፅሞ አይገዙኝም ነበር፡፡
ኢድዊን ላንድሲር
- ቀዝቃዛውን ጦርነት ያስቆመው ሰው ነበር … የጦር
መሳሪያ ወይም ቴክኖሎጂ፣ የጦር ሰራዊት ወይም
ዘመቻ አልነበረም፡፡ በቃ ሰው ነው፡፡
ጆን ሊካሬ
- ሰዎች ካልተቸገሩ በቀር ምንም ጥሩ ነገር
አይሰሩም፡፡
ኒኮሎ ማኪያቬሊ
- ሌሎችን የሚያስተዳድር ሰው በመጀመሪያ የራሱ
ጌታ መሆን አለበት፡፡
ፊሊፕ ማሲንገር
- ደስተኛ መሆን አለመሆንህን ራስህን ጠይቅ፤
ከዚያም ደስተኛ መሆንህን ታቆማለህ፡፡
ጆን ስተዋርት ሚል
- እያንዳንዱ ትውልድ በአባቶቹ ላይ ያምፅና
ከአያቶቹ ጋር ወዳጅነት ይፈጥራል፡፡
ሌዊስ ሙምፎርድ