Administrator

Administrator

 መንግስት ተጠርጣሪዎች በመብዛታቸው አዳዲስ ፍርድ ቤቶችን እየገነባ ነው

       በቱርክ ከከሸፈው መፈንቅለ መንግስት ጋር በተያያዘ 32 ሺህ ሰዎችን ያሰረው የአገሪቱ መንግስት፣በቀጣይም ሌሎች ተጨማሪ ሰዎችን እንደሚያስር ማስታወቁን አሶሼትድ ፕሬስ ዘገበ፡፡
የአገሪቱ የፍትህ ሚኒስትር በኪር ቦዝዳግ ከኤንቲቪ የቴሌቪዥን ጣቢያ ጋር ያደረጉትን ቃለ መጠይቅ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ በሃምሌ ወር አጋማሽ ከተሞከረው መፈንቅለ መንግስት ጋር ንክኪ አላቸው በሚል የተጠረጠሩ 70 ሺህ ያህል ሰዎች ጉዳያቸው እየተጣራ እንደሚገኝ የተገለጸ ሲሆን፣ 32 ሺህ ያህሉ እንደታሰሩና በቀጣይም ሌሎች ተጨማሪ ሰዎች እንደሚታሰሩ ተነግሯል፡፡ ከመፈንቅለ መንግስቱ ጋር ንክኪ አላቸው በሚል የተጠረጠሩት ሰዎች ቁጥር ከፍተኛ ከመሆኑ ጋር በተያያዘ ምርመራውን በወቅቱ ለማጠናቀቅ አዳጋች በመሆኑ፣ የቱርክ መንግስት የተጠርጣሪዎችን ጉዳይ የሚመረምሩ አዳዲስ ፍርድ ቤቶችን እየገነባ እንደሚገኝ ሚኒስትሩ ማስታወቃቸውንም ዘገባው ገልጧል፡፡ 270 ሰዎችን ለህልፈተ ህይወት በዳረገውና ባለፈው ሃምሌ ወር አጋማሽ ላይ ተሞክሮ በከሸፈው የቱርክ መፈንቅለ መንግስት፣ ተሳትፎ አላቸው የተባሉ ከ50 ሺህ በላይ ሰዎች ከስራ ገበታቸው መባረራቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

 ከእስራኤል መስራች አባቶች አንዱ እንደሆኑ የሚነገርላቸውና አገሪቱን በፕሬዚዳንትነትና በጠቅላይ ሚኒስትርነት ያስተዳደሩት የኖቤል የሰላም ተሸላሚው ሺሞን ፔሬዝ ባደረባቸው ህመም በተወለዱ በ93 አመታቸው ባለፈው ረቡዕ ከዚህ አለም በሞት መለየታቸው ተዘግቧል፡፡
ከፍልስጤም ጋር የሰላም ድርድር እንዲደረግ ላበረከቱት አስተዋጽኦ እ.ኤ.አ በ1994 የኖቤል የሰላም ሽልማትን የተቀበሉት ፔሬዝ፣ ከሁለት ሳምንታት በፊት በልብ ህመም ተጠቅተው ቴል አቪቭ አቅራቢያ ወደሚገኝ ሆስፒታል የገቡት ፔሬዝ፣ በህክምና ሲረዱ ቆይተው ባለፈው ረቡዕ ማለዳ ማረፋቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታኒያሁ ባወጡት መግለጫ፣ በፔሬዝ ሞት የተሰማቸውን ጥልቅ ሃዘን ገልጸው፣ ፔሬዝ በእስራኤልና በአካባቢው ሰላም እንዲሰፍን እስከ እለተ ሞታቸው ያለመታከት የሰሩ ባለ ራዕይ መሪ ነበሩ ብለዋል፡፡  
የሽሞን ፔሬዝ ህልፈተ ህይወት ይፋ መደረጉን ተከትሎ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፣ ጆርጅ ደብሊው ቡሽ፣ ቢል ክሊንተን፣ ቭላድሚር ፑቲን፣ ቶኒ ብሌር፣ ፍራንኪዮስ ሆላንዴ እና ጀስቲን ትሬዱን ጨምሮ በርካታ የአለማችን አገራት የቀድሞና የወቅቱ መሪዎች የሃዘን መግለጫ ያወጡ ሲሆን፣ ፔሬዝ ሰላምን በማስፈን ረገድ ያበረከቱትን ጉልህ ሚና አድንቀዋል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ጸሃፊ ባንኪ ሙን በበኩላቸው፣ ሽሞን ፔሬዝ በእስራኤልና በመካከለኛው ምስራቅ አገራት ሰላም ለማስፈን ከፍተኛ ጥረት ያደረጉ መሪ መሆናቸውን በመግለጽ፣ የሁለትዮሽ መፍትሄን በማመንጨት የአገሪቱ ዜጎች ከፍልስጤማውያንና ከአካባቢው አገራት ጋር በሰላም እንዲኖሩ ለማስቻል የለፉ ታላቅ ሰው ነበሩ ሲሉ አሞግሰዋቸዋል፡፡
ሃማስ በአንጻሩ ረቡዕ ዕለት ባወጣው መግለጫ የፔሬዝን ህልፈተ ህይወት በደስታ እንደተቀበለው ገልጾ፣ ሰውዬው ወንጀለኛ መሆናቸውንና ፍልስጤማውያንም በግለሰቡ ሞት ጥልቅ ደስታ እንደሚሰማቸው ማስታወቁን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
እ.ኤ.አ በ1923 የተወለዱት ሽሞን ፔሬዝ፣ በ1959 ለመጀመሪያ ጊዜ ተመርጠው የእስራኤል ፓርላማ አባል መሆናቸውን ያስታወሰው የአጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘገባ፣ ከ1984 እስከ 1986 እንዲሁም ከ1995 እስከ 1996 ለሁለት ጊዜያት የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር፣ ከ2007 እስከ 2014 ደግሞ ፕሬዚዳንት በመሆን ማገልገላቸውንም አክሎ ገልጧል፡፡ የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ፣ የመከላከያና የፋይናንስ ሚኒስትር በመሆን ያገለገሉት የሽሞን ፔሪዝ የቀብር ስነስርዓት የአለማችን ታላላቅ መሪዎች በተገኙበት ትናንት በእየሩሳሌም ተፈጽሟል፡፡

  ባለፈው የሪዮ ኦሎምፒክ፣ የኬንያን ልኡካን ቡድን በመምራት ወደ ብራዚል ያቀኑት ስቴፈን አራፕ ሶይ፣ ለቡድኑ አባላት የውድድር ቆይታ ከተመደበው ገንዘብ 256 ሺህ ዶላር ዘርፈዋል በሚል ናይሮቢ በሚገኝ ፍርድ ቤት ክስ እንደተመሰረተባቸው አሶሼትድ ፕሬስ ዘገበ፡፡
የኦሎምፒክ ቡድን መሪው ወደ ብራዚል በተደረገው ጉዞ ለሚመለከታቸው የአገሪቱ የመንግስት አካላት ሳያስታውቁ ይዘውት የወጡት 234 ሺህ ዶላር የገባበት አልታወቀም፤ በተለያዩ አጋጣሚዎችም 22 ሺህ ዶላር የመንግስት ገንዘብ ዘርፈዋል የሚል ክስ እንደቀረበባቸው ዘገባው ጠቁሟል፡፡ ግለሰቡ ባለፈው ረቡዕ ናይሮቢ በሚገኘው ፍርድ ቤት ቀርበው የቀረበባቸውን ክስ ያደመጡ ሲሆን፣ የተጠቀሰውን ገንዘብ አልዘረፍኩም ሲሉ ክደው መከራከራቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ሌሎች ሁለት የኬንያ ኦሎምፒክ ቡድን ባለስልጣናትም ናይኪ ኩባንያ በስፖንሰርነት ለቡድኑ ያበረከተውን ትጥቅ ሰርቀዋል በሚል የቀረበባቸውን ክስ በእለቱ ክደው መከራከራቸውን አመልክቷል፡፡
የኬንያ የኦሎምፒክ ኮሚቴና የአትሌቲክስ ፌዴሬሽን ከፍተኛ ባለስልጣናት በሪዮ ኦሎምፒክ በሙስና እንደተጠረጠሩ ያስታወሰው ዘገባው፣ ባለፈው አመትም የአገሪቱ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት፣ ምክትል ፕሬዚዳንትና ገንዘብ ያዥ 700 ሺህ ዶላር ያህል በመዝረፋቸውና ሌሎች የሙስና ወንጀሎችን በመስራታቸው ከስራ ገበታቸው እንደተሰናበቱና ምርመራ እንደተደረገባቸው ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

   የጀርመኑ ቮልስዋገን እና የጃፓኑ ቶዮታ እየተቀያየሩ ሲመሩት በዘለቁት የዘንድሮው የአለማችን ታላላቅ የመኪና አምራች ኩባንያዎች ውድድር ከሰሞኑ ቶዮታ መሪነቱን መያዙን ፎርብስ መጽሄት ዘገበ፡፡
ቶዮታ በዘንድሮው የፈረንጆች አመት ያለፉት ስምንት ወራት ብቻ 6.69 ሚሊዮን መኪኖችን አምርቶ ለአለም ገበያ በማቅረብ መሪነቱን መያዙን የጠቆመው ዘገባው፣ በተመሳሳይ ጊዜ 6.69 ሚሊዮን መኪኖችን ለገበያ ያቀረበው የጀርመኑ ቮልስዋገን በሁለተኛነት እንደሚከተል ገልጧል፡፡
የሶስተኛነት ደረጃን ይዞ የሚገኘው የአሜሪካው ጄኔራል ሞተርስ ኩባንያ በ2016 የመጀመሪያዎቹ ስምንት ወራት 6.3 ሚሊዮን መኪኖችን አምርቶ ለአለም ገበያ ማቅረቡ ተነግሯል፡፡ ቶዮታ እና ቮልስዋገን እያንዳንዳቸው በየአመቱ 10 ሚሊዮን መኪኖችን አምርተው ለገበያ የሚያቀርቡበት አቅም ላይ እንደደረሱ ማስታወቃቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ በሁለቱ ኩባንያዎች መካከል ያለው ፉክክር መቀጠሉንና በቀሪዎቹ ወራት የመሪነቱን ስፍራ ይዞ የሚቀጥለውንና የአመቱ የዓለማችን ትልቁ የመኪና አምራች የሚሆነውን ኩባንያ ለመገመት አዳጋች እንደሆነ ገልጧል፡፡

 “ህገ-መንግስቱን በማክበር ለተተኪው ስልጣን የምለቅበት ጊዜ ላይ ነኝ”

       ላለፉት 12 አመታት ሲሼልስን የመሩት ፕሬዚዳንት ጄምስ ሚሼል ከወራት በፊት የተደረገው የአገሪቱ ህገ መንግስታዊ ማሻሻያ የስልጣን ዘመናቸው ማብቃቱን የሚያረጋግጥ ከመሆኑ ጋር በተያያዘ፣ በሁለት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ ስልጣን እንደሚለቁና ለተተኪው እንደሚያስረክቡ ማስታወቃቸውን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘገበ፡፡
የ72 አመቱ ፕሬዚዳንት ጄምስ ሚሼል ባለፈው ማክሰኞ በአገሪቱ ብሄራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያ ባደረጉት ንግግር፣ ለ12 አመታት አገሪቱን አስተዳድሬያለሁ፤ አሁን ህገ-መንግስቱን በማክበር ስልጣኔን ለተተኪው መሪ የማስረክብበት ጊዜ ነው፤ አዲሱ መሪ ሲሼልስን ወደቀጣዩ የልማት ምዕራፍ ያሸጋግራታል ብዬ አምናለሁ ሲሉ መግለጻቸውን ዘገባው አስታውቋል፡፡ ከዚህ በፊት መምህር ሆነው ያገለገሉት ፕሬዚዳንቱ፤በሚያዝያ ወር 2004 በምክትል ፕሬዚዳንትነት ወደ ስልጣን መምጣታቸውንና ከ2014 እስካሁን በፕሬዚዳንትነት እየሰሩ እንደሚገኙ የጠቆመው ዘገባው፣ ባለፈው ታህሳስ ወር ላይ በተደረገው ምርጫ አሸንፈው ለሶስተኛ የስልጣን ዘመን አገሪቱን መምራት መቀጠላቸውን ገልጧል፡፡
ባለፈው ሚያዝያ ወር ላይ የአገሪቱ ብሄራዊ ምክር ቤት የፕሬዚዳንትና የምክትል ፕሬዚዳንትን የስልጣን ዘመን ሁለት ዙር ብቻ እንዲሆን መወሰኑ፣ ባለፈው አመት ሁለተኛ የስልጣን ዘመናቸውን የጨረሱትን ፕሬዚዳንቱን ስልጣናቸውን እንዲለቁ መነሻ እንደሆናቸውም ዘገባው አስታውቋል፡፡ ፕሬዚዳንቱን በመተካት አገሪቱን የመምራት ስልጣኑን የሚረከቡት፣ በአሁኑ ወቅት የሲሼልስ ምክትል ፕሬዚዳንት የሆኑት የ54 አመቱ ዳኒ ፋኦሬ እንደሚሆኑም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

     በአሜሪካ 80 ከመቶ የጫማ ፍላጎት የሚያሟላው የጫማ አከፋፋዮችና ቸርቻሪዎች ማኅበር (ኤፍ ዲ አር ኤ) በኢትዮጵያ የሥራ ጉብኝት ያደረገ ሲሆን ከትናንት በስቲያ በኢሲኤ አዳራሽ በቆዳ ዘርፍ ከሚመለከታቸው ኃላፊዎች ጋር ውይይት አካሂዷል፡፡
ኤፍዲአርኤ የጫማ ምርቶችን የሚገዛው ከምስራቀው ኤዥያ አገሮች ከካምቦዲያ፣ በርማ፣ ላኦስ፣ … ሲሆን ወደ ኢትዮጵያ የመጣው የሜድ ኢን ኢትዮጵያ ኩባንያ ባለቤት ወ/ሮ ቤተልሄም ጥላሁንና ኢንተርፕራዝ ፓርትነርስ ባደረጉት ያላሰለሰ ጥረት መሆኑን የኢንተርፕራይዝ ፓርትነርስ የኮሙኒኬሽን አማካሪ አቶ ዳዊት ከተማ ገልጸዋል፡፡
175 አባላት ያሉት ማኅበሩ ባለፈው ማክሰኞ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ጣቢያ ሲደርስ በውጭ ጉዳይ ሚ/ር አቀባበል የተደረገለት ሲሆን፣ 11 የታወቁ ብራንድ ያላቸው አከፋፋዮችና ቸርቻሪዎች ከፍተኛ የስራ አመራሮች ከቡድኑ ጋር መምጣታቸው ታውቋል፡፡ ቡድኑ ወደ ኢትዮጵያ የመጣው በአገሪቱ ያለውን የጫማ ሁኔታና ከኢትዮጵያ ጫማ ቢገዛ ምን ጥቅም እንደሚያገኝ ለማጥናት ሲሆን ባለፈው ረቡዕ የቆዳ አምራቾችን፣ የቆዳ ማልፊያ ፋብሪካዎችን፣ የጫማ ፋብሪካዎችን፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድን የጭነት ተርሚናል መጎብኘቱ ታውቋል፡፡
በጉብኝታቸው ወቅት ባዩት ነገር፣ በተደረገላቸው አቀባበልና መስተንግዶ መደሰታቸውን የገለጹት የኤፍ ዲ አር ኤ የመንግስትና የተቆጣሪ ጉዳዮች ዳይሬክተር ሚ/ር ቶማስ ክሮኬት ባለፈው ዓመት አሜሪካ 2.4 ቢሊዮን ጥንድ ጫማዎች ከውጭ መግዛቷን ተናግረዋል፡፡
አሜሪካኖቹ የጫማ ነጋዴዎች ኢትዮጵያን የወደዱበትን ምክንያት አቶ ዳዊት ሲገልጹ ወደ አሜሪካ ጫማ ሲገባ ትልቁ ወጪ ቀረጥ ነው፡፡ ኢትዮጵያ የአጉዋ አባል ስለሆነች ምንም ቀረጥ ሳትከፍል ታስገባለች፡፡ በከፊልና በሙሉ የሰለጠነ የሰው ኃይል ስላል ተወዳዳሪ የሆነ የጉልበት ዋጋ በኢትዮጵያ ስላለና በኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ዋጋ እጅግ በጣም ርካሽ በመሆኑ ነው ብለዋል፡፡ ኢንተርፕራዙ ከአንድ ወር በፊት በሀዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክ ያለውን የሰለጠነ የሰው ኃይል እጥረት ለመቅረፍ 60 ሺህ ሰዎች ለማሰልጠን መፈራረሙን ጠቅሰው ወደ ጫማ ኢንዱስትሪ የሚገቡ የአሜሪካ ኩባንያዎች ካሉ፣ ሊገጥማቸው የሚችለውን የሰው ኃይል እጥረት ለመቅረፍ ኢንተርፕራይዙ ዝግጁ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡
የኢትዮጵያ ቆዳ ኢንዱትሪ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሻሻለ ጥሬ ቆዳ መላክ አቁሞ እሴት እየጨመረ ያለቀለት ጫማ፣ ጓንት፣ ቀበቶ፣ የቆዳ አልባሳት፣ … ወደ ውጭ እየላከ መሆኑን የጠቀሱት አቶ ዳዊት፣ በኤፍ ዲ አር ኤ በኩል ወደ አሜሪካ ገበያ መግባት በጣም ትልቅ ዕድል ነው፡፡ ስለዚህ ሁኔታዎችን የበለጠ ማመቻቸትና ጠንክረን መስራት ይጠበቅብናል ብለዋል፡፡

     ሳምንታዊ የግል ጋዜጦች ከማተሚያ ቤት ችግር ጋር በተያያዘ ከሚወጡበት መደበኛ ቀናቸው እስከ 5 ቀን ዘግይተው እየወጡ ሲሆን ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ቤት፤ የጋዜጦችን ዘግይቶ የመውጣት ችግር ለመፍታት ጥረት በማድረግ ላይ ነኝ ብሏል። ችግሩን ለመፍታት የጋዜጣ አሳታሚዎች እስከ መስከረም 30 ቀን 2009 ዓ.ም እንዲታገሱትም ጠይቋል-ማተሚያ ቤቱ፡፡
“አዲስ አድማስ” ን ጨምሮ ቅዳሜ ለአንባቢያን መድረስ የነበረባቸው ጋዜጦች እሁድ መውጣት የጀመሩ ሲሆን የእሁድ ሳምንታዊ ጋዜጦች እስከ 4 እና 5 ቀናት እየዘገዩ እንደሚወጡ የገለፁት አሳታሚዎች፤ መዘግየቱ ከማስታወቂያ ደንበኞቻቸው ጋር ቅራኔ ውስጥ እየከተታቸው መሆኑን ጠቁመው ለአንባቢያን በጊዜና በሰአቱ መድረስ ያለባቸው መረጃዎችም እየዘገዩ መቸገራቸውን ተናግረዋል፡፡
የብርሃንና ሰላም ማተሚያ ቤት ስራ አስኪያጅ አቶ ተካ አባዲ፤ ጋዜጦች ለምን በዕለታቸው እንደማይወጡ ከአዲስ አድማስ ለቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ፤ ‹‹ማተሚያ ቤቱ በ22 ሚሊዮን ብር የገዛውና በሰአት እስከ 20 ሺህ ኮፒ ጋዜጦች የማተም አቅም ያለው ዘመናዊ ማሽን የቴክኒክ እክል ስለገጠመው ነው›› ብለዋል፡፡
ችግሩን በአጭር ጊዜ ለመፍታት ድርጅቱ ጥረት እያደረገ መሆኑን የገለጹት አቶ ተካ፤ ማሽኑ ወደ ሀገር ውስጥ ከገባ ከ1 ዓመት በላይ ቢሆነውም ባለሙያዎች ማሽኑን የማንቀሳቀስ እውቀታቸው በቂ ባለመሆኑ ተጨማሪ ስልጠና እንዲወስዱ እየተደረገ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
ማሽኑ አሁን ላጋጠመው ችግርም መለዋወጫው ሀገር ውስጥ ሊገኝ ባለመቻሉ ከውጭ ለማስመጣት ጥረት እየተደረገ በመሆኑ፣ መለዋወጫው እንደተገኘ ችግሩ ይቀረፋል ብለዋል - ሥራ አስኪያጁ፡፡
“አዲሱ ማሽን ቴክኖሎጂው በጣም ውስብስብ በመሆኑ፣ ባለሙያዎቻችን በቀላሉ ሊረዱት አልቻሉም” የሚሉት አቶ ተካ፤ ከዚህ በፊት ማተሚያ ቤቱ ችግሩን ለመፍታት የገባው ተደጋጋሚ ቃል ያልተፈፀመው ማሽኑና የድርጅቱ ባለሙያዎች ሊጣጣሙ ባለመቻላቸው ነው ብለዋል፡፡
የማሽኑን ሙሉ አቅም ለመጠቀም የባለሙያ ብቃት ያስፈልጋል ያሉት ስራ አስኪያጁ፤ ከዚህ ቀደም 4 ሠራተኞች ህንድ ሀገር ሰልጥነው የተመለሱ ቢሆንም ከማሽኑ ጋር በቅጡ መተዋወቅና መግባባት እንዳልቻሉ አስረድተዋል፡፡ በየጊዜው ለባለሙያዎች ተደጋጋሚ ስልጠና ቢሰጥም ውጤት አልተገኘም ይላሉ - አቶ ተካ፡፡
በሁለት ዓመት ውስጥ 11 ማሽኖች ተገዝተው የማተሚያ ቤቱን አቅም ማሳደጋቸውን የሚገልፁት ሥራ አስኪያጁ፤ ‹‹ለጋዜጦች ያስመጣነው ሁለት ማሽን ነው፤ እነ ‹‹አዲስ ዘመን›› እና ‹‹ሄራልድ›› የሚታተሙበት በአግባቡ እየሰራ ስለሆነ እክል አይገጥማቸውም፤ ችግሩ ያለው ሌሎች ጋዜጦች በሚታተሙበት ማሽን ላይ ነው›› ብለዋል፡፡
በዚህ ዓመት ተጨማሪ ማሽኖች በመግዛት የማተሚያ ቤቱን አቅም በማሳደግ በዘላቂነት ችግሩን እንደሚፈታም አቶ ተካ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል። አቶ ተካ አባይ፤ የማተሚያ ቤቱ ሥራ አስኪያጅ ሆነው እንደመጡ፤ የህትመት ሙያ ማሰልጠኛ ት/ቤት እንደሚከፈትና ጋዜጦች ፈፅሞ መዘግየት እንደማይገጥማቸው፤ ከገጠማቸውም የሚደርስባቸውን ኪሳራ ማተሚያ ቤቱ እንደሚከፍል ቃል ገብተው የነበረ ቢሆንም እስካሁን ተፈፃሚ አልሆነም፡፡


     ኖርዝ ኢስት ኢንቨስትመንት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲና ከብሔራዊ ቤተ መዛግብትና ቤተ መጻሕፍት ኤጀንሲ ጋር በመተባበር በየዓመቱ የሚካሄድ ‹‹ሆሄ የኢትዮጵያ የሥነ ጽሁፍ ሽልማት›› ፕሮግራም ማዘጋጀቱን አስታወቀ፡፡
የሽልማት ዝግጅቱ ዓላማ በሀገራችን የንባብ ባህል እንዲጎለብት ማስቻል፣ በየዓመቱ የሚታተሙ መጽሐፍትን እንዲተዋወቁና የተሻሉት ደግሞ በተሸላሚነት እውቅና እንዲያገኙ እንዲሁም በልጆች ንባብ ላይ የተለየ ትኩረት በማድረግ ድጋፍ መስጠት ነው፡፡
የፈጠራ ፅሁፍ ስራዎቻቸውን ላበረከቱ ደራሲያንና ጸሐፍት እውቅና ከመስጠት ባለፈ የንባብ ባህል እንዲስፋፋ፣ በተፃፉ መፅሃፍት ላይ ህብረተሰቡ እንዲወያይባቸው ሁኔታዎችን የሚያመቻቹ የንባብ ክበባት እንዲፈጠሩ እንዲሁም በየጊዜው የሚታተሙ መፅሀፍት ላይ ሂስና ትንታኔ በመስጠት ለመላው ህብረተሰብ የንባብ ትሩፋቶችን በማጋራት ለሚሰሩ ሀያሲያን የሽልማት ፕሮግራሙ እውቅና የሚሰጥ ይሆናል፡፡
“ሆሄ የስነፅሁፍ ሽልማት” ፕሮግራም በዋነኛነት ሶስት የውድድር ዘርፎች የሚኖሩት ሲሆን እነዚህም የረጅም ልብ ወለድ መጻህፍት፣ የስነ ግጥም መድበሎችና የልጆች መጻህፍት ናቸው። ተወዳዳሪ መፃህፍት በዳኞች ኮሚቴ አማካይነት በተዘጋጀላቸው መስፈርቶች መሰረት የሚመዘኑ ሲሆን ውድድሩ በዳኞች ኮሚቴ ከሚሰጠው ውጤት በተጨማሪ በአንባቢያን ነፃ የስልክ መልእክትና በድረ ገፅ ኦን ላይን ከአንባቢያን የሚሰጠው ድምፅ ተደምሮ አጠቃላይ ውጤቱ የሚታወቅ ይሆናል፡፡
የውድድሩ አሸናፊዎች የዋንጫና የገንዘብ ሽልማት የሚያገኙ ሲሆን በተጨማሪም በአለም አቀፍ የኪነ ጥበብ ጉባኤዎች ላይ የመሳተፍ እድል እንዲያገኙ ይደረጋል። በሽልማት ፕሮግራሙ በንባብ ባህል፣ በመጻሕፍት አቅርቦት፣ በትምህርት ቤቶች የንባብ ክበባት ዙሪያ የሚዘጋጁ አውደ ጥናቶችና የኪነ ጥበብ ምሽቶች የሽልማት ፕሮግራሙ አካል ይሆናሉ፡፡ የሽልማቱ መርሀ ግብር ከመስከረም 15 ጀምሮ ተወዳዳሪ መፅሐፍት ምዝገባ የተጀመረ ሲሆን መጋቢት 2 ቀን 2009 ዓ.ም የመዝጊያ ፕሮግራም ይካሄዳል፡፡


ከዕለታት አንድ ቀን የሩሲያ መሪ የነበረው ስታሊን፣አንድ አዳራሽ ውስጥ ጋዜጣዊ መግለጫ ሊሰጥ እየተዘጋጀ ነበር፤ አሉ፡፡
‹‹ጓድ ስታሊን መግለጫውን ለመስጠት ዝግጁ ነዎት?›› አለ ጋዜጠኛው፡፡
‹‹አዎን መቀጠል እንችላለን›› ሲል መለሰ ስታሊን፡፡
‹‹ጓድ ስታሊን፤ ግምገማን በተመለከተ በከተማችን የሚወራ አንድ ነገር አለ፡፡ ይኸውም አንድ የአገራችን ባለሥልጣን ሶስት ሰራተኞችን ሥራ ያዛል፡፡ ሥራውም፤ አንደኛው ሰራተኛ ጉድጓድ ይቆፍራል፡፡ ሁለተኛው የዛፍ ችግኝ ይተክላል፡፡ ሶስተኛው አፈር ይሞላል፡፡ አሁን ሥራ ሲሰሩ የሚታዩት ግን ሁለት ብቻ ናቸው፡፡ ቆፋሪውና አፈር ሞይው፡፡ ‹‹ምንም ሥራ እየሠራችሁ እኮ አይደለም፡፡” ብሎ አንድ መንገደኛ ሀሳብ ሰጣቸው፡፡ ‹‹እኛ ምን እናድርግ፤ ዛፍ ተካዩ ታምሜ ነው ብሎ ቀረ!” አሉና መለሱ፡፡
“ጓድ ስታሊን፤ስለዚህ ሁኔታ ምን ይላሉ?››
ጓድ ስታሊንም፤ ‹‹ሁለቱ ሠራተኞች ትክክል ናቸው፡፡ እነሱ ኃላፊነታቸውን ተወጥተዋል›› አለ፡፡
‹‹ግን’ኮ ምንም ዛፍ አልተተከለም?›› አለ ጋዜጠኛው፡፡
‹‹መጥቶ ዛፍ ያልተከለ ሰው በኋላ ይገመገማታል፡፡ ቆፋሪውና ደፋኙ ግን በሚገባ ሥራቸውን ተወጥተዋል፡፡ እንዲያውም መሾም አለባቸው!›› ብሎ ወሰነ፤ስታሊን፡፡
ይህ በዚህ እንዳለ ጋዜጣዊ መግለጫው የሚሰማበት አዳራሽ ውስጥ አንድ ሰው አስነጠሰ፡፡ ስታሊን ማስታወሻ ማንበቡን ትቶ፤ ቀና አለና፡- ‹‹አሁን ያስነጠሰው ማን ነው?›› ሲል ጠየቀ፡፡ ማንም መልስ አልሰጠም፡፡ ፀጥ ፀጥ ሆነ፡፡
‹‹ማነው ያስነጠሰው ተናገሩ?››
አሁንም መልስ የለም፡፡
ስታሊን ወደ ግል ጠባቂዎቹ ዞሮ፤
‹‹ከአዳራሹ የመጨረሻ ረድፍ የተቀመጡትን ሰዎች አስወጡና ረሽኑልኝ!›› አለ፡፡
ጠባቂዎቹ የታዘዙትን ፈፀሙ፡፡
ስታሊን፤‹‹አሁንስ አታወጡም?” አለ፡፡
 ሰው ፀጥ አለ፡፡ ስታሊን ወደ ጠባቂዎቹ ዞሮ፤
“ከኋለኛው መስመር አንድ ረድፍ አውጥታችሁ ረሽኑ›› አለና አዘዘ፡፡
 ትዕዛዙ ተፈፀመ፡፡
ለሶስተኛ ጊዜ፤“አሁንስ ያስነጠሰውን ሰው አታወጡም?” ሲል ጠየቀ፡፡
ይሄኔ አንድ ሰው እጁን አውጥቶ፤
“እኔ ነኝ ያስነጠስኩት” አለ፡፡
ስታሊንም፤ “ይማርህ!” አለ፡፡
ያስነጠሰውም ሰው “ያኑርህ!” አለው፡፡
*             *          *
መሪዎች አምባገነን ሲሆኑ ጭካኔያቸውም የዚያኑ ያህል ጣራ ይነካል፡፡ ማን አለብኝ ይላሉ፡፡ ለመሪዎች ፍላጎት ሲባል የብዙ ንጹህ ሰዎች ህይወት ይጠፋል፡፡ በ “ይማርህ” እና በ “ያኑርህ” መካከል ደም ሊፈስ ይችላል። ምንም ህይወት አላግባብ ሲያልፍ ሊቆጨን ሊያንገበግበን ይገባል፡፡ ተጠያቂነትም ሊኖር ግድ ነው፡፡ አያሌ ተድበስብሰው የቀሩና ተጠያቂም ያልተጠየቀባቸው፤ ከንቱ ሆነውም የቀሩ ጥያቄዎችና ነብሶች ነበሩ፡፡ ሳይመለሱ የቀሩ ጥያቄዎች ያመረቅዛሉ፡፡ አድረው ውለው ዳግመኛ ብቅ ይላሉ፡፡ ኦቴሎን እናስታውስ፡-
“ገንዘቤን የሰረቀኝ ሰው፣ ወሰደ እንበል ከንቱ ነገር
የእኔም፣ የእሱም፣ የዚያም ነበር
ግና ስሜን የሰረቀኝ
የማያከብረውን ወስዶ፣ እኔን በግልፅ አደኸየኝ!”
የሚለውን የሼክስፒርን አባባል ማስተዋል ይበጃል፡፡ ከሼክስፒር ስራዎች እጅግ ተደናቂ አባባል ተገኝቷል ከተባለ “መሆን ወይም አለመሆን” የሚለው ቀዳሚ ስፍራ ይይዛል፡፡ ቁጭትን፣ ፀፀትን፣ በቀልንና በተለይ የቁርጠኝነት ውሳኔ ላይ ለመድረስ የሚቀርብን የሞት - የሽረት ጥያቄ የሚያመላክት በመሆኑ፣ዝንተ ዓለም ችግር ባለበት አገር ውስጥ ሁሉ ሲጠቀስ ይኖራል፡፡ (እንደ ታሪኩ አካሄድ መሪው ገፀ ባህሪ ሐምሌት፤ አባቱ በአጎቱ ተገድሎበት፣ የአባቱ አልጋ ተወረሰ፡፡) የዚህ ቁጭት ነው የ“መሆን አለመሆን” መሰረት፡፡ ስለ አብነቱ ይጠቀስ። እነሆ፡-
“መሆን ወይስ አለመሆን፣ እዚሁ ላይ ነው ችግሩ
የዕድል የፈተና አለንጋ፣ ሲወናጨፍ ወስፈንጥሩ
በሀሳብ ግርፊያ መሰቅየቱን፣ ችሎ ታፍኖ ማደሩ
ወይስ የፈተናውን ማዕበል፣ ተጋፍጦ ጦሩን ከጦሩ
ተጋትሮ ወግቶ ድል መምታት፣ እስኪነቀል ከነሥሩ
የቱ ነው የሰው ልጅ ክብሩ ?….”
የአገር ጉዳዮች እልህ መጋባት ድረስ ሲደርሱ፣ የአደጋ ቀይ መብራት መብራቱን መገንዘብ ያባት ነው። ኢትዮጵያ የአገር ሽማግሌ ትፈልጋለች፡፡ ችግራቸውን ራሳቸው የሚፈቱ፣ ቀናውን መንገድ የሚያዩ፣ እሾና አሜኬላውን ለይተው የሚያስወግዱ፤ ልባምና ሆደ ሰፊ ሰዎች ያሿታል፡፡ ከማንም የማይወግኑ፣ የማንም ተፅዕኖ የሌለባቸው፣ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ልጄ ነው የሚሉ፣ ችግሩ ችግሬ ነው የሚሉና አስተዋይ የአገር ሽማግሌዎች አገርን ከአገር ለማቀራረብ፣ “መልካም ምላስ ፍቅርንና ሰላምን ትወልዳለች” በማለት መላ የሚመቱ፤ ሀቀኛ ልጆች ያስፈልጋሉ፡፡ እኒህን ሽማግሌዎች ለማዳመጥ የሚያስፈልገው አንድ ነገር ብቻ ነው - ከቀድሞው አስተሳሰባችን መላቀቅ፤ መፋታት! (Breaking with old ideas) ይህ ደግሞ ከግትርነት፣ ከማን አለብኝነት፣ “እስከ ዛሬ የለፋሁት ምን ይሆናል?” ከማለት፣ ወንበርን እንደ ግል - ንብረት ከማየት አስተሳሰብ መላቀቅን በግድ ይጠይቃል፡፡ ዋጋ ያስከፍላል፡፡ ይህን ሁሉ የማደርገው ለሀገር አንድነት፣ ለሀገር እኩልነት፣ ለሀገር ሰላም ስል ነው፣ ማለትን ይጠይቃል፡፡
ያልተሄደበትን መንገድ (The road less travelled እንዲሉ) መሞከር በጎ ነው፡፡ የተለመደውን መዝሙርና ዘፈን ቢያንስ መቀነስ፣ ቀስ በቀስም መተው የወቅቱ ጥያቄ ነው (order of the day እንዲሉ፡፡) የአገር ሽማግሌዎች በተስኪያን ሳሚ፣ መስጊድ ፀላይ ናቸውና ለሰላም ቅርብ ናቸው፡፡ የራሳቸውን መፍትሄ ለመሻት ቅርብ ዘዴ አጥተው አያውቁም፡፡ ግብረ ገብነት እንጂ የጥናት መመሪያ አይፈልጉም፡፡ ባህልን የመጠበቅ ልማዳዊ አቅም አላቸው፡፡ የሀገራቸው ጣራም፣ ግድግዳም፣ ወለልም ራሳቸው ናቸው፡፡ የሲቪል ማህበረሰብ እናቱም፣ አባቱም የሀገር ሽማግሌዎች ናቸው (“Civic society” እንደ ማለት ነው) የሀገር ሽማግሌዎች ወገን መቀያየሪያ አይደሉም፡፡
“ጓደኞቼ አሁን በያዝኩት አካሄድ ከቀጠልኩ ውጤቴ ውድቀት ነው አሉኝ፡፡ ስለዚህ አንድ ነገር ማድረግ እንዳለብኝ አሰብኩ፡፡ ከቤቴ ወጥቼ ሄድኩና አዲስ ጓደኛ ቀየርኩ፡፡ ይሄ ጓደኛ ትወድቃለህ አይለኝም፡፡”  
የሚለው የአበው ፖለቲከኞች አነጋገር፣ ከግብዝነት እንድንላቀቅ ትልቅ ትምህርት ይሰጠናል፡፡ መውደቃችን እየታወቀን “አይዞህ አትወድቅም” የሚለን ቲፎዞ ለመፈለግ መሯሯጥ ግብዝነት ነው፤ነው የሚለን ትምህርቱ፡፡ ከዚህ ይሰውረን! ትልቁ ጉዳይ ትራንስፎርሜሽን ሊኖር የሚገባው በየአንዳንዳችን ጭንቅላት ውስጥ መሆኑ ነው። ያ ደግሞ በየቅንነታችን መጠን እንጂ በግምገማ የሚለካ አይደለም - የባህል አብዮት ነውና! በሌለ ነገር መፎከር የቁርጡ ቀን ሲመጣ በአደባባይ እርቃናችንን ያወጣናል፡፡ “የምትበላውን አጥታ የከሳች፣ እኔ ቀጭኗ ልጅ፣ ብላ ፎከረች!” የሚለው ተረት፣የዚህን ውስጠ - ሚስጥር ይነግረናል፡፡ “ያመነ የተጠመቀ የዘላለም ህይወት አለው” ይለናል መጽሐፉ፡፡






     ባለፉት 2 ሳምንታት በኡጋንዳ አስተናጋጅነት በተካሄደው የ2016 የሴካፋ ሴቶች ሻምፒዮና የፍፃሜ ጨዋታ ታንዛኒያ  2ለ1 ኬንያን በመርታት የዋንጫው አሸናፊ ሆናለች፡፡ በሻምፒዮናው በአፍሪካ ዋንጫ ሴካፋን በመወከል የምትሳተፈው ኬንያ በ2ኛ ደረጃ ስታጠናቅቅ፤ ኢትዮጵያ 3ኛ ደረጃ እንዲሁም አዘጋጇ ኡጋንዳ 4ኛ ደረጃዎችን አግኝተዋል፡፡ የኪሊማንጃሮ ንግስቶች የሚባሉት የታንዛኒያ ሴቶች ብሄራዊ ቡድን ዋንጫውን ለማሸነፍ የበቁት በሚያስደንቅ የቡድን ጥንካሬ እና ሁሉንም ጨዋታዎች በማሸነፍ ነው፡፡ በሻምፒዮናው የኡጋንዳዋ  ሃሳኒ ናሳና በ6 ጎሎች ኮከብ ግብ አግቢ ሆና ስትጨርስ የሉሲዎቹ አጥቂ ሎዛ አበራ በ5 ጎሎች ሁለተኛ ደረጃ አግኝታለች። የኢትዮጵያ ሴቶች ብሄራዊ ቡድንን በዋና አምበልነት የመራችው ብርቱካን ገብረክርስቶስ ኮከብ ተጨዋች እንደነበረች ታውቋል። ሁለተኛ ደረጃ ያገኘችው ኬንያ  ዞኑን በመወከል ከ2 ወራት በኋላ ካሜሮን ላይ በሚካሄደው የ2016 የአፍሪካ ሴቶች እግር ኳስ ዋንጫ የምትሳተፍ ሲሆን፤ በሴካፋ ሴቶች ሻምፒዮና የነበራት ተሳትፎ ለአፍሪካ ዋንጫው ጠቃሚ ዝግጅት እንደሚሆንላት ተገልጿል፡፡ በሌላ በኩል የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን በቀጣይ የሴካፋ ሴቶች ሻምፒዮናን ቢያስተናግድ በአገሪቱ ለሚካሄደው የሴቶች እግር ኳስ ከፍተኛ መነቃቃት እንደሚፈጥር አስተያየቶች ተሰጥተዋል፡፡
በሴካፋ ሴቶች ሻምፒዮናው ሉሲዎቹ በምድብ 2 ከሩዋንዳ እና ከታንዛኒያ ጋር ተደልድለው ነበር፡፡ በመጀመርያ ጨዋታቸው በሎዛ አበራ ሁለት ጎሎች እና በመስከረም ኮንካ አንድ ተጨማሪ ግብ ሩዋንዳን 3ለ2 አሸነፉ፡፡ በሁለተኛ ጨዋታቸው ደግሞ ከታንዛኒያ ጋር 0ለ0 አቻ በመለያየት በምድባቸው  4 ነጥብ እና አንድ  የግብ ክፍያ ካስመዘገቡ በኋላ በእጣ ሁለተኛ ደረጃ አግኝተው ወደ ግማሽ ፍፃሜ አልፈዋል፡፡ በግማሽ ፍፃሜው  የተገናኙት  ከኬንያ አቻቸው ጋር የነበረ ሲሆን 3ለ2 ተሸንፈው ለዋንጫ ፍልሚያው ሳይደርሱ ቀርተዋል፡፡ በዚህ ጨዋታ ሁለቱንም ጎሎች ያገባችው ሎዛ አበራ ነበረች፡፡ ለደረጃ ጨዋታ የተገናኙት ደግሞ ከአዘጋጇ አገር ኡጋንዳ ጋር  ሲሆን 4ለ1 በሆነ ሰፊ ውጤት በማሸነፍ የሴካፋ ሻምፒዮና ተሳትፏቸውን በ3ኛ ደረጃ ማጠናቀቅ ችለዋል፡፡ በዚህ ጨዋታ  ረሂማ ዘርጋው 3 ጎሎች በማስቆጠር ሃትሪክ ስትሰራ 1ኛውን ጎል ያገባችው ደግሞ ሎዛ አበራ ነበረች፡፡ ሉሲዎቹ ለዋንጫ ቅድሚያ ግምት ቢሰጣቸው በግማሽ ፍፃሜ በኬንያ አቻቸው በገጠማቸው መራር ሽንፈት ሳይሳካላቸው ቀርቷል፡፡  በአጠቃላይ በሴካፋ ሴቶች ሻምፒዮናው ከምድብ አንስቶ እስከ ደረጃ ጨዋታው  4 ጨዋታዎች አድርገው ሁለቱን ሲያሸንፉ በአንድ አቻ ወጥተው በአንድ ጨዋታ ደግሞ ተሸንፈዋል፡፡ በተጋጣሚዎቻቸው ላይ  9 ጎሎች አስመዝግበው 6 ጎሎች ደግሞ አስተናግደዋል፡፡
ኡጋንዳ ስፖንሰር የሌለውን ሲኒዬር ቻሌንጅ ካፕ ሻምፒዮና ማስተናገዷን ያደነቁት የሴካፋ ምክር ቤት ዋና ፀሃፊ ኒኮላስ ሙንሶኜ ናቸው፡፡ ሻምፒዮናው በሴቶች እግር ኳስ  አብዛኛዎቹ የዞኑ አባል አገራት የሚገኙበትን ደካማ  ደረጃ  እንደሚቀይር ሲገልፁም፤ ለአፍሪካ ዋንጫና ሌሎች ኢንተርናሽናል ውድድሮች የሚደረጉ ዝግጅቶችን የሚያግዝ መሆኑን  አመልክተዋል። በሌላ በኩል ሻምፒዮናው በሴቶች እግር ኳስ ላይ የሊግ ውድድሮች ለሚያካሂዱት እና በተለያዩ የእድሜ ደረጃዎች በመስራት ላይ ለሚገኙት የምስራቅ አፍሪካ አገራት ከፍተኛ መነቃቃት እንደሚፈጥርም የሴካፋ ዋና ፀሃፊ አስገንዝበው ፤ በአፍሪካ ዋንጫ ላይ የዞኑ አገራት ተሳትፎ ማደግ እንዳለበት ሲናገሩ የሴካፋ ሴቶች ሻምፒዮናው ይህን የዞኑን ብሄራዊ ቡድኖች ተሳትፎ ለማጠናከር ያለው አስተዋፅኦ ከፍተኛ ነው ብለዋል፡፡ በሴካፋ የሴቶች ሻምፒዮናው ለዋንጫ ከተፋለሙት ታንዛኒያ እና ኬንያ ባሻገር ሁሉም ተሳታፊዎች በተለይ ኢትዮጵያ እና ኡጋንዳ ጥሩ ደረጃ ላይ እንደሚገኙ ታዝበናል የሚሉት ዋና ፀሃፊው በሚቀጥሉት የአፍሪካ ዋንጫዎች ከዞኑ ሁለት እና ሶስት አገራት መሳተፍ የሚችሉ ከሆነ  እድገት መኖሩን ያመለክታል ብለዋል፡፡ በአፍሪካ ሴቶች ዋንጫ ትልቁ የተሳትፎና የውጤት ክብረወሰኖች የተመዘገቡት  ሶስት ጊዜ በ2002፤2006 እና 2012 እኤአ ላይ መሳተፍ በቻለችው ኢትዮጵያ ሲሆን ሉሲዎቹ በ2006 እኤአ ላይ በአፍሪካ ዋንጫው ባገኙት አራተኛ ደረጃ የዞኑን ከፍተኛ ውጤት ነበራቸው፡፡ ታንዛኒያ በ2010 እኤአ ላይ ሴካፋን በመወከል በአፍሪካ ዋንጫው የተሳተፈች ሲሆን ለኬንያ የ2016 የአፍሪካ ሴቶችዋንጫ የመጀመርያው ይሆናል። ካሜሮን ለምታስተናግደው የ2016 የሴቶች አፍሪካ ዋንጫው የምድብ ድልድሉ ሰሞኑን የታወቀ ሲሆን ኬንያ በምድብ ሁለት ከናይጄርያ፤ ጋና እና ማሊ ጋር ስትደለደል በሌላ በኩል በምድብ 1 ካሜሮን፤ ግብፅ፤ ደቡብ አፍሪካና ዚምባቡዌ እንደሚገኙ ተገልጿል፡፡
ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ፌደሬሽኖች ማህበር ፊፋ ከ2014 ጀምሮ እስከ 2018  እኤአ በመላው ዓለም በሴቶች እግር ኳስ ተግባራዊ የሚሆን የእድገት ፕሮግራም በመንደፍ ሲንቀሳቀስ ቆይቷል፡፡  ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር አባል አገራቱ  የሴቶች እግር ኳስን በማሳደግ እንዲሰሩ የባለሙያ ክትትል ማድረግ፤ የአቅም ግንባታ ስልጠና በመስጠት፤ የገንዘብ ድጋፍ በማበርከትንና የፕሮሞሽን ተግባራትን በማከናወን እያገዛቸው ይገኛል፡፡  ፊፋ በዚህ የሴቶች እግር ኳስ የእድገት ፕሮግራሙ  በሁሉም የእድሜ ደረጃዎች አገር አቀፍ፤ ክፍለ አህጉራዊ እና አህጉራዊ ውድድሮች እንዲካሄዱ ድጋፍ የሚያደርግ ሲሆን በስሩ ያሉ 209 አባል አገራት ለተግባራዊነቱ የስራ እቅዶችና ስትራቴጂዎች ነድፈው እንዲያቀርቡ በመጠየቅ የሚሰራበትን ሁኔታ እስከ 2018 እኤአ የሚቀጥልበት ይሆናል፡፡  ከዚህ ጋር ተያይዞ ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር የሴቶች እግር ኳስ የእድገት ፕሮግራሙን በ2014 እኤአ ላይ ተግባራዊ ማድረግ ከመጀመሩ በፊት የሰራው ጥናት ነበር፡፡ ከአባል አገራቱ መካከል  177 የእግር ኳስ ፌደሬሽኖች በጥናቱ ላይ የተካተቱ ነበሩ፡፡ በዚህ የዓለም ሴቶች እግር ኳስ አጠቃላይ ጥናት ላይ የተሳተፉት 177 ፌደሬሽኖች በዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር በሴቶች እግር ኳስ ላይ በሚያደርጓቸው እንቅስቃሴዎች ዙርያ ላቀረበላቸው ጥያቄዎች 85 በመቶ ምላሽ ሰጥተዋል። በየአባል አገራቱ የሴቶች እግር ኳስ እድገትን የሚፈታተኑ ሁኔታዎች ተብለው በጥናቱ ከተጠቀሱት መካከል የሊግ ውድድሮች አለመሻሻል፤ አስተዳደራዊ ድክመቶች፤ የባለድርሻ አካላት በቅንጅት አለመስራት፤ በስፖርቱ የሴቶች ተሳትፎ ማነስ፤ ደካማ ኢንቨስትመንት፤ በአጠቃላይ የግንዛቤ ማነስ እና የሚዲያ ትኩረት ቀዝቃዛ መሆን ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡ በ2014 እኤአ ላይ ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር ይፋ ባደረገው ይህ ጥናት በመላው ዓለም በእግር ኳስ ስፖርት ከ30 ሚሊዮን በላይ ሴቶች በተጨዋችነት እና በሌሎች ሙያዎች የሚሳተፉ መሆኑን ይገልፃል፡፡ በፊፋ የተመዘገቡት ሴት እግር ኳስ ተጨዋቾች ብዛት ከ4.8 ሚሊዮን በላይ እንዲሁም  በታዳጊ ፕሮጀክቶች የታቀፉት ደግሞ  እስከ 1.2 ሚሊዮን እንደሚገመቱ አመልክቷል። በጥናቱ የተሳተፉት 177 የእግር ኳስ ፌደሬሽኖች በአጠቃላይ በሴቶች እግር ኳስ እንቅስቃሴያቸው በዓመት እስከ 157 ሚሊዮን ዶላር በጀት ያወጣሉ፡፡ በየፌደሬሽኖቹ በእግር ኳስ አስተዳደርና ልዩ ልዩ ሃላፊነቶች የሴቶች ተሳትፎ 23 በመቶ፤  የሴቶች ዋና ብሄራዊ ቡድን ያላቸው 80 በመቶ፤ የወጣቶች ቡድን ያላቸው 50 በመቶ፤ የሊግ ውድድሮችን የሚያካሂዱ 78 በመቶ መሆናቸው ተረጋግጧል፡፡ በሌላ በኩል በእግር ኳስ ፌደሬሽኖቻቸው ስራ አስኪያጅ ኮሚቴዎች የሴቶች ተሳትፎ 8 በመቶ ፤ የሴት አሰልጣኞች 7 በመቶ እንዲሁም የሴት ዳኞች ተሳትፎ 10 በመቶ ብቻ እንደሆነም ጥናቱ አመልክቷል፡፡
የሴካፋ ምክር ቤት በዞኑ የወጣቶች እና የሴቶች እግር ኳስ ላይ ለመስራት የአምስት ዓመታት ስትራቴጂ በመቀየስ መንቀሳቀስ የጀመረው በ2014 እኤአ ፊፋ ባካሄደው 64ኛው ጠቅላላ ጉባኤ በተወሰነው ፕሮግራም መነሻነት  ነው፡፡ በመካከለኛውና ምስራቅ አፍሪካ ያሉ 12 አገራትን በአባልነት ያቀፈው የሴካፋ ምክር ቤት ፊፋ በነደፈው ፕሮግራም እና አቅጣጫ ለመስራት ስትራቴጂውን ነድፎ ቢንቀሳቀስም ውድድሮችን ለማዘጋጀት የአባል አገራቱ ፍላጎት ማነስ እና የስፖንሰሮች እጥረት እየተፈታተነው ይገኛል፡፡ በ2015 እኤአ የሴካፋ ሲኒዬርስ ቻሌንጅ ካፕ በኢትዮጵያ መስተናገዱ የሚታወስ ቢሆንም በቀጣይ ውድድሩን የሚያዘጋጅ አገር ጠፍቶ 2016 ላይ ላይካሄድ እንደሚችል ስጋት ተፈጥሮ ነበር።  ከዋናው የሴካፋ ሲኒዬር ቻሌንጅ ካፕ ባሻገር የምስራቅ አፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮና ካጋሜ ካፕ ፤ የሀ17 የሀ20 የእግር ኳስ  ሻምፒዮናዎችን ለማካሄድ በነበሩት እቅዶችም ሲቸገር ቆይቷል።  ይህ ሁኔታም በዞኑ የእግር ኳስ አስተዳደር ላይ ንትርኮችን እየፈጠረ ሲሆን፤ ዋንኛው ማስረጃም ምክርቤቱን በዋና ፀሃፊነት እና በተለያዩ የስራ ድርሻዎች ለ15 ዓመታት ሲያገለግሉ የቆዩት ኬንያዊው ኒኮላስ ሙንሶኜ ተጠያቂ ተደርገው ከሃላፊነታቸው ለማንሳት ዘመቻ በሩዋንዳ ፊት አውራሪነት መጀመሩ ይጠቀሳል። የሴካፋ ምክር ቤት አንዳንድ አባል አገራት ውድድሮችን ማካሄድ አስቸጋሪ እየሆነ መምጣቱ እና ስፖንሰሮችን ማቆየት አለመቻሉን  እንደ አስተዳደራዊ ድክመት በመቁጠር ዋና ፀሃፊውን  ኒኮላስ ሙንሶኜ እንዲባረሩ እየጠየቁም ነበር፡፡  ኒኮላስ ሙንሶኜ ከሴካፋ ምክር ቤት ከተሰናበቱ በኬንያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ፕሬዝዳንትነት ለመስራት ፍላጎት እንዳላቸው በአፀፋዊ ምላሻቸው ያስታወቁ ሲሆን ምናልባትም በኡጋንዳ አስተናጋጅነት የሴካፋ ሴቶች ሲኒዬርስ ቻሌንጅ ካፕ በተሳካ ሁኔታ መካሄዱ ህልውናቸውን እንደሚወስን እየተገለፀ ነበር፡፡ በኡጋንዳ አስተናጋጅነት ከሰላሳ ዓመታት በኋላ የሴቶች ሻምፒዮናው በስኬት መከናወኑን ተከትሎ  ግን የሴካፋ     ምክር ቤት አንዳንድ ውድድሮችን እነማን እንደሚያስተናግዱ  በይፋ አስታውቋል፡፡ዋና ፀሃፊው ኒኮላስ ሙንሶኜ ሰሞኑን በኡጋንዳዋ ከተማ ጂንጃ በሰጡት መግለጫ ኬንያ የ ሴካፋ ሲኒዬርስ ቻሌንጅ ካፕ እና የክለቦች ሻምፒዮና የሆነው ካጋሜ ካፕ በማከታተል እንድታስተናግድ መመረጧን እንዲሁም ኡጋንዳ የሀ17 ኻምፒዮናውን እንደምታዘጋጅ አስታውቀዋል፡፡ ኬንያ ሁለቱን ውድድሮች ለማዘጋጀት በምታደርገው ጥረት የሴካፋ ምክር ቤት ሙሉ ድጋፍ እንደሚኖርቃል የገቡት ዋና ፀሃፊው የውድድሮቹ መካሄጃ ሳምንታት በቅርብ ጊዜ ይወሰናሉ ብለዋል፡፡ የሁለቱ የሴካፋ ውድድሮች መቀራረብ በተለይ በብሄራዊ ቡድን እና በክለብ አሰልጣኞች በተጨዋቾች አስፈላጊነት ዙርያ ቅራኔዎችን እንደሚፈጥር የተሰጋም ሲሆን በተለይ ከአፍሪካ ሌሎች ውድድሮች ጋር የጨዋታ መደራረብ መኖሩ እያከራከረ ነው፡፡  የሴካፋ ሲኒዬር ቻሌንጅ ካፕ ሱዳን እንዲሁም የሴካፋ ክለቦች ሻምፒዮና ካጋሜ ካፕን ሱዳን ለማስተናገድ ተመርጠው እድሉን ሰርዘዋል፡፡ በ2016 የሴካፋ ሴቶች ሻምፒዮና ስኬታማ መስተንግዶ የነራት ኡጋንዳ በ2017 ደግሞ የዞኑን የሀ17 ውድድር እንደምታስተናግድም ይጠበቃል፡፡ ቀጣዩ የሴካፋ ሴቶች ሻምፒዮናን ማን እንደሚያዘጋጅ የተገለፀ ባይሆንም የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ይህን እድል ለመጠቀም መንቀሳቀስ ይኖርበታል፡፡