Administrator

Administrator

 አዛውንቱ ፕሬዚዳንት
ሮበርት ገብርኤል ሙጋቤ እ.ኤ.አ ፌብሯሪ 21, 1924 ዓ.ም ነው የተወለዱት - በዚምባቡዌ ደቡባዊ ርሆዴዥያ ግዛት፡፡ ሮበርት ሙጋቤ አሁን 91 ዓመታቸው ሲሆን በመላው ዓለም ከሚገኙ መሪዎች ሁሉ በዕድሜ አዛውንቱ ፕሬዚዳንት ናቸው፡፡
በእናት ያደጉት ሙጋቤ
ሰዎች አምባገነን ተፈጥሮአቸውን በመመልከት ብቻ ሙጋቤ በፈላጭ ቆራጭ አባት ነው ያደጉት ብለው ሊያስቡ ይችላሉ፡፡ እውነቱ ግን ሌላ ነው። የሙጋቤ አባት አናጢ ነበሩ፡፡ ትንሹ ሙጋቤ ባልተለመደ መልኩ ሥርዓት ያለውና ጥብቅ ታዳጊ ነበር፡፡ በርግጥ አስቸጋሪ የልጅነት ጊዜ ነው ያሳለፈው፡፡ ሁለቱንም ታላላቅ ወንድሞቹን በሞት ያጣው ገና በህጻንነቱ ነበር፡፡ አባቱ በደቡብ አፍሪካ የጄሱይት ሚሽን ዘንድ ለመስራት ከቤተሰቡ ከተለዩ በኋላ ወደ ቤት አልተመለሱም፡፡ በዚህም የተነሳ መምህር የነበሩት እናቱ፣ሙጋቤንና ሦስት ወንድሞቹን ለብቻቸው ማሳደግ ነበረባቸው። ሙጋቤ ከብት በመጠበቅና ገንዘብ በሚያስገኝ የጉልበት ሥራ በመሰማራት፣ እናቱንና ቤተሰቡን እየደገፈ ነው ያደገው፡፡  
ብቸኛው የነፃነት ማግስት መሪ
ሙጋቤ እ.ኤ.አ በ1963 የብሪቲሽን ቅኝ አገዛዝ የሚታገለውን ZANU የተሰኘ የተቃውሞ ንቅናቄ መሰረቱ፡፡ በ1980 የብሪቲሽ አገዛዝ ሲያከትም የአዲሲቷ የዚምባቡዌ ሪፐብሊክ ጠ/ሚኒስትር ሆኑ። በ1987 የአገሪቱ ፕሬዚዳንት በመሆን ተመረጡ። ሙጋቤ አገሪቱ ከቅኝ አገዛዝ ነጻ ከወጣችበት ጊዜ አንስቶ ብቸኛው የዚምባቡዌ መሪ ናቸው፡፡  
ለረዥም ዓመት በወህኒ ቤት
ሙጋቤ የወግ አጥባቂውን አናሳ - ነጭ የርሆዴዥያ መንግስት የሚቃወም ንቅናቄ መሪ ነበሩ፡፡  ይሄን ተከትሎም ወህኒ ቤት ተወርውረዋል። ከ1964-1974 ለአስር ዓመት ያህልም ታስረው ነበር፡፡ በወህኒ ቤት ሳሉ ታዲያ ሥራ አልፈቱም። ሌሎች እስረኞችን የእንግሊዝኛ ቋንቋ ያስተምሩ የነበረ ከመሆኑም በላይ ከለንደን ዩኒቨርስቲ በርቀት ትምህርት ሁለት የህግ ድግሪዎችን አግኝተዋል፡፡
ከፖለቲካ በፊት መምህር
ምንም እንኳ በደቡባዊ ርሆዴዥያ ብዙ ሰዎች ከሰዋስዎ ትምህርት ባያልፉም ሙጋቤ ግን ደህና ትምህርት ለማግኘት ዕድል ቀንቷቸዋል፡፡ እስከ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ድረስ በሚሲዮናውያን የተማሩት ሙጋቤ፤በ1945 ዓ.ም ከካቱማ ቅዱስ ፍራንሲስ ዛቪዬር ኮሌጅ ተመርቀዋል፡፡ ለቀጣዮቹ 15 ዓመታትም በርሆዴዥያና በጋና ያስተማሩ ሲሆን ተጨማሪ ትምህርታቸውንም በደቡብ አፍሪካው ፎርት ሃሬ ዩኒቨርሲቲ ተከታትለዋል፡፡
ህዝባቸውን አስተምረዋል
በአምባገነኑ ሙጋቤ ላይ በርካታ ትችቶች ቢሰነዘሩም የፕሬዚዳንትነት ሥልጣን ከያዙበት ጊዜ አንስቶ የአገራቸውን የትምህርት ሥርዓት በከፍተኛ ደረጃ መቀየራቸው ግን ማንም የሚመሰክረው ሃቅ ነው፡፡ በሳቸው የአገዛዝ ዘመን ማንበብና መጻፍ የሚችለው የዚምባቡዌ ህዝብ ወደ 90 በመቶ ገደማ ደርሷል፡፡ ለዚህ ስኬት ደግሞ ትምህርት ወዳድነታቸው ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱ ይነገራል፡፡ ሙጋቤ በተለያዩ የትምህርት ዘርፎች 7 ድግሪዎችን የተቀበሉ ሲሆን ኢኮኖሚክስ፣ ትምህርት፣ አስተዳደር፣ህግና የመሳሰሉትን ያካልላል፡፡
የማንቀላፋት ልማድ ተጠናውቷቸዋል
ለበርካታ ዓመታት ዚምባቡዌን በመምራት የሚታወቁት ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ፤በተለያዩ ስብሰባዎችና ኮንፍረንሶች ላይ ሲያንቀላፉ በተደጋጋሚ በካሜራ ተይዘዋል፡፡ አንዳንዶች ይሄን የማንቀላፋት ሱሳቸውን ከዕድሜ ጋር ሲያገናኙት፣”ብዙ ስለሚያስቡ ነው” ብለው ምክንያት የሚሰጡም አሉ፡፡ ምክንያቱ ምንም ይሁን ምንም ግን እሳቸው በተለያዩ አቀማመጦች እንቅልፋቸውን መለጠጥ ይችሉበታል፡፡ አገራዊ ጉባኤ ይሁን ዓለም አቀፍ ለሳቸው ለውጥ የለውም፤ ጉባኤው እስኪጠናቀቅ ድረስ የእንቅልፍ ሱሳቸውን በቅጡ ይወጡታል፡፡
በቅርቡ የተያዙት የናይጄሪያ አዲሱ ፕሬዚዳንት ጀነራል ሙሃማዱ ቡሃሪ ሲመተ - በዓል ላይ ነበር። እንደተለመደው እንቅልፋቸውን ሲለጥጡ በሰሃራ ሪፖርተሮች የካሜራ ዓይን ውስጥ ወድቀዋል - ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ፡፡
የክብር ድግሪዎችን ተነጥቀዋል
ሙጋቤ በተለይ በ1980ዎቹ ዓመታት ከተለያዩ ዓለም አቀፍ ዩኒቨርሲቲዎች በርካታ የክብር ድግሪዎችንና ማዕረጎችን ተቀብለው ነበር፡፡ ግን ምን ያደርጋል----በአገራቸው ከነበረው የሰብአዊ መብት ጥሰቶችና የዲሞክራሲያዊ ሂደት መጨናገፍ ጋር በተያያዘ ቢያንስ ሦስቱን ተነጥቀዋል፡፡
በጁን 2007 ዓ.ም የእንግሊዙ ኢድንበርግ ዩኒቨርሲቲ በ1984 ዓ.ም የሰጣቸውን የክብር ድግሪ ሰርዞባቸዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲው ከዓለም አቀፍ ታዋቂ ሰው ላይ የሰጠውን የክብር ድግሪ ሲነጥቅ ሙጋቤ የመጀመሪያው ነበሩ ተብሏል፡፡ በጁን 2008 ዓ.ም የማሳቹሴት ዩኒቨርሲቲ እንዲሁ በ1986 ዓ.ም የሰጣቸውን የህግ የክብር ድግሪ ነጥቋቸዋል፡፡ በሴፕቴምበር 2008 ደግሞ የሚቺጋን ዩኒቨርሲቲ በ1990 ዓ.ም የሰጣቸውን የህግ የክብር ድግሪ መልሶ ወስዶባቸዋል፡፡ ምን ይሄ ብቻ ---- በ1994 ዓ.ም ከእንግሊዟ ዳግማዊት ኤልዛቤት የተሰጣቸውን የክብር ማዕረግም በጁን 2008 ዓ.ም ተነጥቀዋል፡፡
ከሥልጣን የመውረድ ሃሳብ የላቸውም
ሮበርት ሙጋቤ ለ7 ጊዜ ያህል በምርጫ ያሸነፉ ቢሆንም ምርጫዎቹ ግን በማጭበርበርና መራጮችን በማስፈራራት የተካሄዱ እንደነበር ይነገራል፡፡ ብዙዎች “ሙጋቤ እንዴት ሥልጣን አይሰለቻቸውም?” ብለው ይጠይቁ ይሆናል፡፡ የሚገርመው ግን እሳቸው ከሥልጣን የመውረድ ሃሳቡ እንኳን የሌላቸው መሆኑ ነው፡፡ በመጪው የ2018 ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ የመወዳደር ዕቅድ እንዳላቸውም በቅርቡ አረጋግጠዋል፡፡ የዕድሜዬ መግፋት ጥንካሬዬን አልቀነሰውም ብለዋል - የ91 ዓመቱ አዛውንት ሮበርት ሙጋቤ፡፡
 መጻህፍት አሳትመዋል  
ሙጋቤ በርካታ መጻህፍትን ለንባብ ያበቁ ሲሆን ከእነሱም መካከል የሚከተሉት ይጠቀሳሉ፡-
The Third Chimurenga: Inside the Third Chimurenga (2001)
War,Peace and Development in Contemporary Africa (1987)
The Role of the University in the process of Social Transformation (1983)
Our War of Liberation (1983)

 አንዳንድ ተረት ሲደገም የበለጠ ይገባል፡፡ ምናልባት ልቡናችን ሁሌም እኩል ክፍት ስለማይሆን ሊሆን ይችላል፡፡ አንድም የበለጠ ወቅታዊ ሁኔታ አግኝቶ ሊሆን ይችላል፡፡ በሌላ አጣዳፊ ጉዳይ አዕምሮአችን ሲወጠር ጠንከርና በሰል ያለውን ጉዳይ ምን ተደጋግሞ ቢነገረን የማንሰማበት ጊዜ አለ፡፡ ውሎ አድሮ ሁኔታው ሲሻሻል ፍንትው ብሎ ይታየናል፡፡ ከአስራ አንድ ዓመት በፊት የተረትነውን ዛሬ የምንደግመው ለዚህ ነው፡፡
አንድ የሩቅ ምስራቅ ፌዘኛና ብልህ አዛውንት ነበሩ አሉ፡፡ በጣም ከሚታወቁበት ነገር አንዱ ግማሽ ህይወታቸውን ከሀገራቸው ውጪ ሲሰደዱና በምህረት ሲመለሱ የኖሩ መሆናቸው ነው፡፡
ታዲያ አንደኛው አገር አለቃ ገብረ ሀና ብዙ የሚነገሩላቸው ወጎች አሉ፡፡
አንድ ጊዜ የአገሩ ንጉሥ እኒህን አዛውንት አግንተዋቸው ሁለቱ እንደሚከተለው ያወጋሉ፡፡
ንጉሥ - እንደምን ሰነበቱ አባቴ?
አዛውንቱ - እንደ አገሬው
ንጉሥ - ከየት ነው የሚመጡት?
አዛውንት - ከፀሐይ መውጫ
ንጉሥ - ወደየት ይሄዳሉ?
አዛውንት - ወደ ፀሐይ መውጫ
ንጉሥ - እንዴት? ከፀሐይ መውጫ እየመጡ፣ ወደ ፀሐይ መውጫ ሊሄዱ ይችላሉ? ብለው በመገረም ይጠይቃሉ፡፡
አዛውንቱም - እሱ በሦስት መንገድ ይወሰናል
ንጉሥ - በምን በምን?
አዛውንት - አንደኛ በማንነትዎ ነው፡፡ ማለትም ፀሐይ ልትጠልቅብኝ ነው ብለው የሚያስቡ ከሆነ ወደ ፀሐይ መውጫ እንደሚሄዱ ያምናሉ፡፡ ሁለተኛ/በአነሳስዎ ማለትም መንገድ የጀመሩት በጨለማ ከሆነ መድረሻዎ ሲነጋጋ ስለሚሆን ወደ ፀሐይ መውጫ ሄዱ ማለት ነው፡፡ መንጋቱ አይቀርምና፡፡ ሦስተኛው/ወሳኝ ነገር የአቅጣጫና የእንቅስቃሴ ግንዛቤዎ ነው፡፡ እንዴት ቢባል ዘወር ብለው ፀሐይን ቢመለከቷት እየተከተለችኝ ነው? እያሳደደችኝ ነው? ብለው መጠየቅዎ አይቀርም፡፡” አሉና አስረዷቸው፡፡
በሌላ ጊዜ ደግሞ እንደዚሁ እኒያ አዛውንት ንጉሡ ፊት ይቀርባሉ፡፡
ንጉሡ፡- ምነው ጢምዎ እንደዚህ ረዘመ - ሲሉ ይጠይቋቸዋል፡፡
አዛውንቱም - የአገር ነገር ከብዶት - ሲሉ ይመልሳሉ፡፡
ቀጥሎም ንጉሡ፡- እስከ ዛሬ ካጋጠሙዎት መሪዎች የትኛውን ያደንቃሉ?- ብለው ይጠይቋቸዋል፡፡
አዛውንቱም - ዐይኔን ሳልታወር በፊት ሊመራኝ የቻለውን ነው - ብለው ይመልሳሉ፡፡
ቆይተው ከስደት ሲመለሱ ንጉሡ ያስጠሯቸውና፤
የውጪ አገር ኑሮዎንና የ፣.አገር ውስጥ ኑሮዎትን ሲያወዳድሩት የቱን ወደዱት - ሲሉ ይጠይቋቸዋል፡፡
አዛውንቱ - እሱማ እንደቆምኩበት ቦታ ይለያያል፡፡ እዚህ ስሆን ያንን እወደዋለሁ፡፡ እዚያ ስቆም ደግሞ ይሄንን እወድደዋለሁ፡፡
ከርመው ከርመው፣ ደግሞ ከስደት ሲመለሱ፤
ንጉሡ፡- ከስደት ምን ይዘህ ወደ አገርህ ተመለስህ? - ሲሉ ይጠይቋቸዋል፡፡
አዛውንቱም - ንጉሥ ሆይ፤ ዱሮ ይዤ የወጣሁትን ችግር ይዤ ነው የተመለስኩት፡፡ ማንም የነካብኝ የለም፡፡ …አሉ ይባላል፡፡
*          *        *
  የስደት ቦቃ የለውም፡፡ በኢኮኖሚም ይሁን በፖለቲካ፣ ወይም በማናቸውም ማህበራዊ ችግር፤ ምንም ዓይነት ስም ብንሰጠው፣ አንዴ ከሀገር ከወጣን ስደተኞች ነን፡፡ ስለዚህም የስደትን ገፈት መቅመሳችን አይቀሬ ነው፡፡
“ከአገሩ የወጣ አገሩ እስኪመለስ
ቢጭኑት አህያ ቢለጉሙት ፈረስ”
       *    *     *
“ወይ አዲስ አበባ ወይ አራዳ ሆይ
አገርም እንደሰው ይናፍቃል ወይ”
        *   *  *  
“እረ ሰው እረ ሰው
ዐይኔን ሰው ራበው”
እኒህንና ሌሎችም በቅኔ ባኮ ውስጥ ያሉ ግጥሞች፣ የዚያው የስደት አባዜ አስረጆች ናቸው፡፡ ሁሉም ውስጣቸው የስደት ምሬት ቃና አላቸው፡፡ እነዚህ ላይ ዶናልድ ትራምፕ ሲጨመርባቸው፤ በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ ይሆናል፡፡ ከላይ በተረቱ ውስጥ እንዳየነው፤ “ዱሮ ይዤ የወጣሁትን ችግር ይዤ ነው የተመለስኩት” እንደተባለው ነው፡፡ ስደት የማንነት ጠላት ነው፡፡ ብዙ ነገሮችን ያስረሳል፡፡ የራሱ አጉይ - መነፅር አለውና አመለካከትን ያንጋድዳል፡፡ ጥንቃቄ ካልተደረገበት፣ ጠባይንም ያስለውጣል፡፡ “ዞሮ ዞሮ ከቤት፣ ኖሮ ኖሮ ከመሬት” መግባት አሌ አይሉት ሀቅ ነውና፣ ለዘመድ አዝማድ፣ ለወዳጅና ለሀገር ቁም ነገር ልሥራ ማለት ብልህነት ነው፡፡ ከራስ አልፎ ለወገን ማሰብ፣ ለወገን መትረፍ፣ ልብና ልቦና ላለው ሁሉ ታላቅ ተግባር ነው፡፡ በጎ አድራጎትን ማሰብ አያሌ ህፃናትን ለመታደግ በር ከፋች ነው፡፡ ለአያሌ እናቶች መድህን ነው፡፡ የርሀብን ስፋት፣ የድርቅን ብዛት ነግ - ሠርክ ብናወራው ሰቆቃው ውስጥ ላለው ህዝብ ዳቦ አይሆነውም፡፡ ድህነት ሲያወሩት ቢውሉ፣ ያው ውሃ ወቀጣ ነው፡፡ እንደ ዋና ገብተው ካላዩት አይማሩትም፡፡ ውስጡ ሙስና እያለ፣ ውስጡ ፀረ-ዲሞክራሲነት እያለ፣ ውስጡ ኢ-ፍትሀዊነት እያጠጠ፣ ድህነትን ተረት እናደርጋለን ማለት የአፍ ወግ ብቻ ይሆናል፡፡ ፀሐፌ - ተውኔቱ፤ ድህነት በአፍ አይገባም ያለውን አለመዘንጋት ነው፡፡
ሀገራችን የጀግኖች ሀገር ለመሆኗ ዛሬ ብዙ ምስክር መቁጠር አያሻም፡፡ አድዋ ማግስት ላይ ቆሞ ይህን መጠየቅ የዋህነት ነው፡፡ ይልቁንም የትናንቱን ጀግንነት ለአሁኑ ትውልድ እንዴት እናስጨብጠው ነው ጥያቄው፡፡ ከዘመናዊነት ጋር የትናንቱን ጀግንነት እንዴት እናዋህደው ነው ጉዳዩ፡፡ ባህሉን ያልረሳና ከዓለም ጋርም እኩል የሚራመድ ጀግና ትውልድ እንዴት እንፍጠር ማለት ግዴታችን ነው፡፡ አጓጉል ትውልድ የአባቱን መቃብር ይንድ” እንዳይሆን ምን ዘዴ እንዘይድ እንበል፡፡ ከአንገት በላይ ሳይሆን ከአንጀቱ የሀገርን ጉዳይ የሚያይ ትውልድ እንዴት እናፍራ? ባህሉንና ግብረ ገብነቱን፣ ትምህርቱን አጥብቆና ጠንቅቆ፤ አውቆ እንዲጓዝ ምን ይደረግ? ካልኩ ካለፈው ራስ - ወዳድነት እንዴት እናላቀው? ያለፈ ታሪኩ ባለታላቅ ዝና፣ ነገው ግን ኦና (with glorious past but no future እንዲሉ ፈረንጆቹ) እንዳይሆን ምን እናድርግ? ወጣት የነብር ጣት በማለት ብቻ ወኔ አይጠመቅም፡፡ መራር ሀሞት ከመሬት አይበቅልም፡፡ በተግባራዊ ግንዛቤው፣ ንቃቱ፣ ብቃቱ እና ሽንጥን ገትሮ መንቀሳቀሱ፣ መኖሩን ቀርቦ መመርመር፣ ከሌለም ቀርቦ ማስተማር ያስፈልጋል፡፡ ለሀገሩ መኖሩን ማረጋገጥ ያስፈልጋል! ስለወጣቱ እኩል እሳቤ ካልኖረንና፤ እኛ ራሳችንም የጋራ ቤት እንዳለን ሳናስተውል መቻቻል ጠፍቶብን ከተናቆርን፤ የምናወርሰውም ያንኑ በቂምና በሸር የተሞላ ሀገር ነው፡፡ ያንኑ አፈ - ቅቤ ልቤ - ጩቤ ሥርዓት ነው፡፡ አንዱ ሲያልፍለት ሌላው ለመመቅኘት እንቅልፍ የሚያጣበትን ህይወት ነው፡፡ ዕድሜ ልካችንን፤ “ደስ አይበላችሁ ባለ ምጣዶች፣ ልንጋግረው ያሰብነውን አገነፋነው” እየተባባልን አንዘልቀውም! ቆም ብለን እናስብ!

 ድርቁን ተከትሎ አስከፊ ረሀብ ሊከሰት እንደሚችል ተመድ አስጠንቅቋል
               መንግሥት የእርዳታ ጥሪ ቢያቀርብም እስካሁን ምላሽ አላገኘም
               እስከ 15 ሺህ ብር ይሸጡ የነበሩ ከብቶች፣ 500 ብር ድረስ እየተሸጡ ነው
                              
    በኦሮሚያና በሶማሌ ክልል የድርቅ አደጋ በመቶ ሺዎች የሚገመቱ ሰዎችን ያፈናቀለ ሲሆን ከሩብ ሚሊዮን በላይ ህፃናት ትምህርታቸውን እንዲያቋርጡ ውጪ ማድረጉንም የተባበሩት መንግስታት የእርዳታና የሰብአዊ ድጋፍ ድርጅት (UNOCHA) ሰሞኑን ባወጣው ሪፖርቱ አስታውቋል፡፡
በሌላ በኩል በድርቅ ከተጎዱ አካባቢዎች አንዱ በሆነው የኦሮሚያ ክልል፣ ቦረና ዞን ያሉ አርሶ አደሮች በህይወት የተረፉ ከብቶቻቸውን በርካሽ ዋጋ እየሸጡ መሆኑን ምንጮች ለአዲስ አድማስ ጠቁመዋል፡፡
ድርቅ ባጠቃቸው የቦረና አካባቢዎች በጉዳዩ ላይ ጥናት በማድረግ ላይ የሚገኙ ባለሙያዎች እንደሚሉት፤ በደህናው ጊዜ እስከ 15 ሺህ ብር ይሸጡ የነበሩ በሬዎች፤ በአሁን ወቅት ከ500 እስከ 1 ሺህ ብር ድረስ እየተሸጡ ሲሆን ከ500 እስከ 1 ሺህ 500 ብር ይሸጡ የነበሩ በጎችና ፍየሎች ደግሞ በ80 እና በ90 ብር እየተሸጡ ነው ተብሏል፡፡
ከብቶቹ በአብዛኛው በአካላዊ ቁመናቸው የተጎዱ በመሆኑ፣ ፈላጊ ስለሌላቸው አርብቶ አደሮቹ በርካሽ ዋጋ ለመሸጥ መገደዳቸውን ባለሙያዎቹ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡፡፡
የከብቶች ሞትም እንደቀጠለ መሆኑን የጠቆሙት አጥኚዎች በተለይ የመጠጥ ውሃ ችግሩ ተባብሶ መቀጠሉን ገልፀው፤ መንግስት በቦቴ ውሃ እያቀረበ ቢሆንም በበቂ መጠን አለመሆኑን አመልክተዋል፡፡
ወቅታዊ ሪፖርቱን ሰሞኑን ይፋ ያደረገው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በበኩሉ፤ በተለይ በኦሮሚያና በሶማሌ ክልል የሚሊዮኖችን ህይወት አደጋ ላይ ለጣለው ድርቅ መንግስትና የእርዳታ ለጋሽ ተቋማት ውሃና ምግብ በማቅረብ እየተረባረቡ ቢሆንም ከአደጋው አስከፊነት አንፃር በቂ አይደለም ብሏል፡፡
በድርቁ ምክንያት 228 ሺህ ህፃናት ትምህርት ማቋረጣቸውን ይፋ ያደረገው ሪፖርቱ፤ ከእነዚህ ውስጥ 183 ሺህ 090 የሶማሌ ክልል ህፃናት ሲሆኑ 44 ሺህ 571 የሚሆኑት ደግሞ የኦሮሚያ ክልል መሆናቸውን ጠቁሟል፡፡ በሁለቱ ክልሎች ማለትም በኦሮሚያ በድርቁ ምክንያት 141 ት/ቤቶች፣ በሶማሌ ክልል 437 ት/ቤቶች በድምሩ 578 ትምህርት ቤቶች መዘጋታቸውን ሪፖርቱ አስታውቋል፡፡
ምግብና ውሃ ፍለጋ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ አባወራዎች ከቀዬአቸው መፈናቀላቸውን የጠቆመው የተመድ የእርዳታና ሰብአዊ ድጋፍ ድርጅት ሪፖርቱ፤ ከተፈናቀሉት ውስጥ 163 ሺህ ያህሉ ለትምህርት የደረሱ ህፃናት መሆናቸውን አመልክቷል፡፡ እነዚህን ተፈናቃይ ህፃናት ለ75 ቀናት ሊመመገብ 5.9 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልግም ተገልጿል፡፡
በእርዳታ አሰጣት ደንብ ለአንድ ሰው በቀን ውስጥ 5 ሊትር ውሃ መቅረብ ያለበት ቢሆንም በአሁን ወቅት ለአንድ ሰው በቀን እየቀረበ ያለው በአማካይ 2.1 ሊትር ውሃ መሆኑን የተመድ ሪፖርት ጠቁሞ፤ የውሃ ክፍፍሉም ፍትሃዊ አለመሆኑንና ከወረዳ ወረዳ እንደሚለያይ አስታውቋል፡፡
በአጠቃላይ ለ5.6 ሚሊዮን የተረጂዎች 1 ቢሊዮን ዶላር የሚጠጋ እርዳታ እንደሚያስፈልግና ይህ እርዳታ በአፋጣኝ ካልተገኘ ሁኔታው ወደ አስከፊ ረሃብ ሊቀየር እንደሚችል አሳስቧል፡፡
ተመድ መንግስት ከለጋሽ ድርጅቶች ጋር በመሆን የእርዳታ ርብርብ እያደረጉ ነው ቢልም መንግስት በበኩሉ፤ ለድርቁ አደጋ የእርዳታ ጥሪ ቢያቀርብም እስካሁን ምላሽ አለማግኘቱን አስታውቋል፡፡
በሌላ በኩል የተባበሩት መንግስታት ድርጅት አፍሪካን በተመለከተ ባወጣው ሪፖርቱ፣ ኢትዮጵያን ጨምሮ በድርቅ በተጎዱ፣ ከሠሃራ በታች ባሉ የአፍሪካ ሃገራት፣ በአሁኑ ወቅት ከ20 ሚሊዮን በላይ ሰዎች አስቸኳይ የእርዳታ ርብርብ እንደሚፈልጉ አስታውቆ፤ አለማቀፉ ማህበረሠብ እጁን እንዲዘረጋ ጥሪውን አስተላልፏል፡፡

 በተጠናቀቀው የፈረንጆች አመት 2016 ብቻ በአዲስ አበባ ከተማ ከ30 ሚ. ዶላር በላይ የተጣራ ሃብት ያላቸው 20 አዳዲስ እጅግ ባለጸጋ ሚሊየነሮች መፈጠራቸውን “ናይት ፍራንክ” የተባለ አለማቀፍ የሃብት ጥናትና አማካሪ ተቋም ሰሞኑን ባወጣው የ2017 አለማቀፍ የሃብት ስርጭት አመታዊ ሪፖርት አስታውቋል፡፡ ተቀማጭነቱ በእንግሊዝ የሆነው ተቋሙ፤ በ89 የአለማችን አገራት ውስጥ በሚገኙ 125 ከተሞች ላይ ያደረገውን ጥናት መሰረት በማድረግ፣ ለ11ኛ ጊዜ ባወጣው ሪፖርቱ፤ በአዲስ አበባ ከ30 ሚሊዮን ዶላር በላይ የተጣራ ሃብት ያላቸው አዳዲስ ሚሊየነሮች ቁጥር ከአንድ አመት በፊት ከነበረው በ10 በመቶ በማደግ፣ በ2016 አመት 20 መድረሱን የጠቆመ ሲሆን፣ ይህ ቁጥር በመጪዎቹ ዘጠኝ አመታት በእጥፍ በማደግ 40 ይደርሳል ተብሎ እንደሚገመት አስታውቋል፡፡  
በአዲስ አበባ ባለፈው የፈረንጆች አመት 2016፣ ከ1 ሚሊዮን ዶላር በላይ የተጣራ ሃብት ያላቸው ሰዎች ቁጥር 800 መድረሱን የገለጸው ሪፖርቱ፣ ከ10 ሚሊዮን ዶላር በላይ የተጣራ ሃብት ያላቸው ሚሊየነሮች ቁጥር ደግሞ 40 ደርሷል ብሏል፡፡
ሪፖርቱ በአፍሪካ አህጉር በመጪዎቹ ዘጠኝ አመታት ከፍተኛ የሚሊየነሮች ቁጥር እድገት ይመዘገብባቸዋል ብሎ የጠቀሳቸው አገራት፡- ኢትዮጵያ፣ ሞሪሽየስ፣ ታንዛኒያ፣ ኡጋንዳ፣ ኬንያ እና ሩዋንዳ ሲሆኑ፣ በመላው አለም ከ30 ሚሊዮን ዶላር በላይ የተጣራ ሃብት ያላቸው ሰዎች ቁጥር በዘጠኝ አመታት ጊዜ ውስጥ በ43 በመቶ ያድጋል ተብሎ እንደሚጠበቅም ገልጧል፡፡
ባለፈው የፈረንጆች አመት 2016 በመላው አለም ከ30 ሚሊዮን ዶላር በላይ የተጣራ ሃብት ያላቸው 6 ሺህ 340 አዳዲስ ሚሊየነሮች መፈጠራቸውን የጠቆመው ሪፖርቱ፣ ይህን ያህል የሃብት መጠን ያላቸው የአለማችን ሚሊየነሮች አጠቃላይ ቁጥር 193 ሺህ 490 መድረሱንም አክሎ ገልጧል፡፡
በሚሊየነሮች ቁጥር ከአለማችን አገራት ከፍተኛውን ጭማሪ ታስመዘግባለች ተብላ የምትጠበቀው ቬትናም ስትሆን፣ በአገሪቱ ከ30 ሚሊዮን ዶላር በላይ የተጣራ ሃብት ያላቸው ዜጎች ቁጥር በዘጠኝ አመታት ጊዜ ውስጥ በ170 በመቶ ያድጋል ተብሎ እንደሚገመትም ተነግሯል፡፡

Monday, 27 February 2017 08:14

የቢዝነስ ጥግ

- የእውነተኛ ሥራ ፈጣሪ የህይወት ዓላማ ዓለምን መለወጥ ነው፡፡
  ቢል ድራይቶን
- የንግድ ሥራ ፈጣሪ ከሆንክ፣ ከተለመደው ወጣ ብለህ ማሰብ አለብህ፡፡
  ዋይኔ ሮጀርስ
- ልጄ አሁን “ሥራ ፈጣሪ” ነው፡፡ ሥራ ከሌለህ እንደዚያ ነው የሚሉህ፡፡
  ቴድ ተርነር
- ሦስት ጊዜ የንግድ ሥራ ፈጥሬአለሁ፡፡ ሦስት ኩባንያዎችንም መስርቼአለሁ፡፡
  ማርክ አንድሬሰን
- ሁሉም ሰው ሥራ ፈጣሪ ሊሆን ይችላል፤ ሀብታም ሥራ ፈጣሪዎች የሚሆኑት ግን በጣም ጥቂቶቹ ናቸው፡፡
  ሮበርት ኪዩሳኪ
- ዛሬ በንግድ ሥራ ፈጣሪነት ዘርፍ ብዙ አማራጮች አሉ፡፡
  ኢክላስ ዜንስትሮም
- ከራሴ ጋር እንዲህ ስል ተማከርኩ፡- “የንግድ ሥራ ፈጠራን እያስተማርኩ ነው፤ ስለዚህ ራሴ የንግድ ስራ ፈጣሪ መሆን አለብኝ”
  ዳን ሼችትማን
- ዶናልድ ትራምፕ የንግድ ሥራ ፈጣሪ ነው፡፡
  ስቲቭ ባኖን
- የንግድ ሥራ ፈጣሪ መሆን ከባድ ነው፡፡ በጣም በጣም ከባድ፡፡
  ዴቪድ ኤስ.ሮዝ
- የንግድ ሥራ ፈጠራ፤ በአስቸጋሪ ኢኮኖሚ ውስጥ ህይወታችንን የምንቆጣጠርበት መንገድ ነው፡፡
  ሎርል ግሬይነር
- ሥራ ፈጣሪዎች በሳምንት 40 ሰዓት መስራትን ለማስቀረት፣ በሳምንት 80 ሰዓት ለመስራት ፈቃደኞች ናቸው፡፡
  ሎሪ ግሬይነር
- የንግድ ሥራ ፈጠራ፤ ለችግሮች አትራፊ መፍትሄዎች የመፈለግ ጥበብ ነው፡፡
  ብሪያን ትሬሲ

የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ም/ቤት “ኮንዲዩሲቭ ኢንቫይሮመንት ፎር ኢንሃንስድ ኤክስፖርት ፐርፎርማንስ) በሚል መሪ ቃል ያዘጋጀው 21ኛ ዓለም አቀፍ የንግድ ትርዒት ከትናንት በስቲያ ተከፈተ፡፡
አገር ውስጥ ያሉ የንግድ ሰዎችን ከውጭ አገር አቻዎቻቸው ጋር የንግድ ትስስር እንዲፈጥሩ፣ ንግድና ኢንቨስትመንትን ለማስተዋወቅና የአባላቱን አቅም ለማሳደግ የሚሰራው የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ም/ቤት ባዘጋጀው 21ኛው የንግድ ትርዒት፤ 100 የውጭ አገራትና 80 የአገር ውስጥ በአጠቃላይ 180 ድርጅቶች የሚሳተፉ ሲሆን ከውጭ ኩባንያዎች 50 ያህሉ ከኢጣሊያ የመጡ እንደሆነ ታውቋል፡፡
ከየካቲት 16 እስከ 22 ቀን 2009  በሚቆየው የንግድ ትርዒት፤ ከ27 የውጭ አገራት፣ ኢጣሊያ፣ ሕንድ፣ ኢንዶኔዢያ፣ ሱዳን፣ ዱባይ … እንዲሁም ከአገር ውስጥ የተውጣጡ… 180 ኩባንያዎች በአገልግሎት፣ በንግድ፣ በማኑፋክቸሪንግ በትርዒቱ የሚሳተፉ ሲሆን የኢጣሊያ ኩባንያዎች ከአገር ውስጥ ባለሀብቶች ጋር ተቀናጅቶ የመስራት ፍላጎት እንዳላቸው የም/ቤቱ የውጭ ግንኙነትና የሚዲያ ሥራ አስኪያጅ አቶ ካሳሁን ማሞ ገልጿል፡፡
የንግድ ትርዒቱን በክብር እንግድነት መርቀው የከፈቱት የንግድ ሚ/ር ዴኤታው አቶ አሰድ ዚያድ ሲሆኑ የንግድ ም/ቤቱ የቦርድ አባላት፣ አምባሳደሮችና የዲፕሎማቲክ አባላት፣ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል፡፡
ንግድ ም/ቤቱ በቅርቡ ዓለም አቀፍ የእርሻና ምግብ ትርዒት በሚያዝያ፣ የማኑፋክቸሪንግና ቴክኖሎጂ ኤግዚቢሽን በሰኔ እንደሚያካሂድ ታውቋል፡፡ እንዲሁም የንግድ ም/ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አበባው መኮንን ደረጃውን የጠበቀ ዘመናዊ ኤግዚቢሽን ማዕከል ለመገንባት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከ‹‹ፋይራ ባርሴሎና›› ጋር መስማማቱን አስታውቀዋል፡፡   

• እንደኢትዮጵያ ባሉ ታዳጊ አገሮች በሆስፒታል ውስጥ ከሚሞቱ እናቶች በሚወሰደው መረጃ መሰረት እስከ 20% የሚሆነው የእናቶች ሞት በደም መርጋት በሽታ ነው።
 ዶ/ር ሙህዲን አብዶ
የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት
ደም በሰውነት ውስጥ ትልቅ ተግባር ያለው ተፈጥሮ ነው። ደም በሰውነት ውስጥ በሕይወት ዘመን ሁሉ ካለምንም ችግር መመላለስ መቻል አለበት። ነገር ግን ጉዳት በሚደርስበት ገዜ ከሰውነት ውጭ እንይፈስ እና ተጎጂው ከጉዳት እንዳይወድቅ እራሱን ማዳን መቻል አለበት። ይህም የደም ስሩ በተቆረጠበት በኩል ካለአግባብ እንዳይፈስ በአካባቢው በመርጋት እና የተከፈተውን የደም ስር በመዝጋት ነው። ስለዚህም የደም መርጋት ጤናማ እና ሕይወት አድን ተፈጥሮአዊ ሂደት ነው። ነገር ግን ባልተፈለገ ሁኔታ ማለትም ከልብ ሕመም፣ ስትሮክ እና ከመድሀኒት ጋር በተያያዘ በሚደርስ ችግር የደም መርጋት ከተከሰተ ጠቃሚነቱ ቀርቶ ጎጂ ይሆናል።
በሰውነት ውስጥ የደም መርጋት ተከሰተ ሊባል የሚችለው የሚከተሉት ሁኔታዎች ሲስተዋሉ ነው።
• የደም ዝውውሩ በትክክለኛው መንገድ መሆን ሲገባው ነገር ግን ሲገታ፣
• በደም ውስጥ የደም መርጋትን አጋጣሚ የሚጨምሩ ነገሮች በሚጨምሩበት ጊዜ፣
• በደም ስር ውስጥ ያሉ ተፈጥሮአዊ አካላት በሚጎዱበት ወይንም አደጋ በሚደርስባቸው ጊዜ፣ ነው።
ከዚህ ውጭ ግን በተለያዩ ባእድ አካላት ሰውነት ሲመታ ወይንም ሲቆረጥ የሚኖረውን ደም መፍሰስ ለማስቆም የሚረዳው ደም መርጋት እንደችግር ሳይሆን እንደነፍስ አድን ይቆጠራል። ምክንያቱም በዚያ በተቆረጠው የደም ስር ጫፍ ላይ ተከስቶ የደም ፍሰቱን ስለሚገታ ነው። ነገር ግን ደም የሚያቀጥን መድሀኒት የሚወስዱ ሰዎች ከሌሎች በተለየ በአደጋ ጊዜ የደም ስራቸው በራሱ የሚያደርገውን የደም መርጋት ሂደት ሊያስተጉዋጉልበት ይችላል። የደም መርጋትን ሊያመጡ የሚችሉ ከሚባሉት ውስጥ የደም ግፊት፣ ኮሎስትሮል፣የልብ ሕመም፣የስኩዋር ሕመም፣ማጨስ እና በቤተሰብ ውስጥ የደም መርጋት ሕመም የነበረ ከሆነ ተጠቃሾች ናቸው። ከልብ ሕመም፣ስትሮክ እና ከደም ስሮች መዘጋጋት ጋር የሚያያዘውን የደም መርጋትን ለመከላከል የደም ግፊትን የስኩዋር ሕመምን እና ኮለስትሮልን መቆጣጠር ተገቢ ነው።
አንዲት ሴት በእርግዝና ላይ እና በወሊድ ወቅት ሊያጋጥሙዋት ከሚችሉ የጤና እክሎች አንዱ የደም መርጋት ነው። በዚህ ወቅት የደም መርጋት በሽታ እንዲከሰት የሚያደርጉ የተለያዩ አጋጣሚዎች በመኖራቸው ከፍተኛ ጥንቃቄ ሊደረግ ይገባል። በእርግዝና ጊዜ የሚከሰተው የደም መርጋት ጽንሱን አደጋ ላይ የመጣል አዝማሚያው ከፍተኛ ነው። እንደመረጃዎቹ ጥቆማ ለዚህ ደረጃ የሚያደርስበት ምክንያትም የደም መርጋቱ በእንግዴ ልጅ ውስጥ ስለሚፈጠር ወደልጁ የሚሄደውን የደም ፍሰት ሊዘጋ ስለሚችል ነው።
• በእርግዝና ጊዜ ሰውነት በራሱ ደም እንዳይፈስ ለመከላከል ሲል የሚያዘጋጃቸው የደም መርጋት ተፈጥሮአዊ ሂደቶች ይጨምራሉ።
• እርግዝናው ጊዜውን እየጨመረ በሚመጣበት ጊዜ ጽንሱ በማደጉ ምክንያት በሚፈጠረው ጭነት ምክንያት ደም መልስ የሚባለው አካል በትክክል ስራውን እንዳይሰራ የሚሆንበት አጋጣሚ ይኖራል።
• በእርግዝና ወቅት በምጥ ሰአት ወይንም በውርጃ ጊዜ በተለይም ደግሞ ከወሊድ በሁዋላ በተለይም በመጀመሪያዎቹ ሁለት ሳምንታት ውስጥ በከፍተኛ ሁኔታ የደም መርጋት ሂደቱን የሚያባብሱ ነገሮች አሉ። በተለይም...
o ከምጥ ጋር በተያያዘ የደም ስሮች መጎዳት፣
o በኦፕራሲዮን መውለድ፣
o የሰውነት ውፍረት፣
o ተገቢውን አካላዊ እንቅስቃሴ ካለማድረግ ...ወዘተ ጋር በተያያዘ ወላድዋ የደም መርጋት ሕመም ሊገጥማት ይችላል።
• የደም መርጋት ምልክት ደም መርጋቱ እንደተከሰተበት የስውነት ክፍል ወይንም አርተሪ እና ቬይን በተባሉ የደም ክፍሎች ይለያያል። ስለዚህም የልብ ሕመም ወይንም መጠነኛ ስትሮክ ሊያጋጥም ይችላል። የደም መርጋትን ሊያስከትሉ የሚችሉ ምክንያቶች ተብለው ከሚጠቀ ሱት መካከል ውፍረት፣እንቅስቃሴ አለማድረግ፣መተኛት የመሳሰሉት ይገኙበታል። አንዲት ሴት በተለይም በኢትዮጵያ ስትወልድ ከሚደረግላት እንክብካቤ መካከል ምግብ ከለመደችው መጠንና አይነት በላይ መስጠት እና ለእረፍት መተኛት እንዳለባት ታዋቂ ነው።ይህ ግን በባለሙያዎች ዘንድ ተቀባይነት የለውም።
• .....እንደጥሩ ልማዳዊ ድርጊት ተደርገው ከሚወሰዱ መካከል ሴቶች ሲወልዱ የሚደረግላቸው እንክብካቤ ይገኝበታል። ነገር ግን የእንክብንቤው መንገዱ ልብ ሊባል የሚገባው ነው። የወለደች ሴት መታረስ አለባት ከሚል አስተሳሰብ ብዙ እንድትተኛ ቅባት ያላቸውን ምግቦች ከመጠን በላይ እንድትመገብ ይደረጋል። በተለይም መኝታው እንደእረፍት የሚቆጠርበት መንገድ ትክክል አለመሆኑን መረዳት ይገባል። እረፍት ማለት መኝታ አይደለም። ማረፍ ማለት ሰውነት እንዳይንቀሳቀስ በማድረግ ለተለያዩ በሽታዎች እንዲጋለጥ ማድረግ ተብሎ ሊተረጎም አይገባም። ማረፍ ማለት ቀደም ሲል ከነበረው አስጨናቂ ነገር አእምሮን ገለል አድርጎ ጥሩ ጥሩ ነገር እያሰቡ አዲስ ስላገኙት ነገር በተለይም ስለወለዱት ልጅ ምቹ ነገርን እያሰቡ ቀድሞ ከነበረው ውጥረት የበዛበት የኑሮ እንቅስቃሴ እራስን ገለል አድርጎ በመጠኑ እየተንቀሳቀሱ ለተወሰነ ጊዜ እራስን ማደስ ተብሎ ቢታሰብ ይበጃል። ከወለዱ በሁዋላ መተኛት የሚለው እጅግ ጎጂ የሆነና የተሳሳተ አስተሳሰብ መሆኑን ሁሉም ቢረዳው መልካም ነው። ስለዚህ አንዲት ሴት ከወለደች በሁዋላ ለተወሰነ ጊዜ እረፍት አድርጋ በየአንድ እና ሁለት ሰአቱ ልዩነት ለአስራ አምስት እና ሰላሳ ደቂቃ ያህል ከአልጋ እየተነሳች ብዙ ሳትርቅ ከክፍል ክፍል ዞር ዞር ማለት እና አቅሙዋም በጨመረ ጊዜ በደንብ በቤቷ ውስጥ ወዲያ ወዲህ ማለት ይጠበቅባታል። ወደምግቡ ሁኔታ ስንመለስም... በወለዱ ጊዜ የሚመገቡት ምግቦች ስብ እና ጣፋጭ የበዛባቸው እንዲሆኑ አይመከርም። ይልቁንም በፈሳሽ መልክ የተዘጋጁ ምግቦችን እንዲሁም መጠጦችን እየወሰዱ በወለዱ ጊዜ የሚሰሩ የአካል እንቅስቃሴዎችን በየደረጃው በባለሙያ ምክር መስራት ሊከሰት የሚችለውን የደም መርጋት ሊያስቀር ይችላል። በተለይም ኦፕራሲዮን ሆነው የወለዱ ሴቶች ከቁስሉ ጋር በተያያዘ የተለያዩ ምክንያቶችን ለራሳቸው እየፈጠሩ ፍርሀት ሰለሚያድርባቸው እራሳቸውን ከእንቅስቃሴ ሊገድቡ ስለሚችሉ የደም መርጋት ክስተቱን ሊያባብሱ ይችላሉ። ስለዚህ ማንኛዋም ወላድ የመጀመሪያዎቹን ስምንት ሰአታት ካረፈች በሁዋላ በየደረጃው የሰውነት ክፍሉዋን ማንቀሳቀስ ይጠበቅባታል.....
• እርግዝናና መውለድ የደም መርጋትን ከሚያባብሱ ነገሮች መካከል ናቸው። የደም መርጋት ችግር በሕይወት ዘመኑዋ አንድ ጊዜ ማለትም በእርግዝና ወይም ወሊድ ወቅት ብቻ የተከሰተባት ሴት እና በሌሎች የጤና ሁኔታዎች ወይንም በዘር ምክንያት ችግሩ የተሰከተባት ሴት በእኩል አይን አይታዩም። ስለዚህ ከእርግዝናው ወይንም ከመውለድ ጋር በተያያዘ ብቻ የደም መርጋት ሕመም የገጠማት ሴት ለዚህ ሕመም የዳረጉዋት ምክንያቶች ከተስተካከሉና ሕክምናውን በተገቢው መንገድ ወስዳ ለሚቀጥለው እርግዝና ብቁ መሆንዋን ሐኪም ካረጋገጠላት የሚቀጥለውን ልጅ ብዙም ሳትቆይ ማርገዝ ትችላለች። የደም መርጋት ችግር በተለያዩ ምክንያቶች እና በዘር የወረሱ ወይንም በተደ ጋጋሚ የሚከሰትባት እናት ከሆነች ግን በቀላሉ ወደ እርግዝናው እንድትገባ አይፈቀድም። ተከታታይ የሆነ የህክምና ክትትል አድርጋ የደም መርጋቱ ችግር በከፍተኛ ሁኔታ መወገዱ ሲረጋገጥ እና ሐኪሞች ሲወስኑላት ግን ልጅ መውለድ ትችላለች። (ዶ/ር ሙሁዲን አብዶ - የጽንስና ማህጸን ሕክምና)
• በአጠቃላይ ግን በደም መርጋቱ ምክንያት የሚደርሰውን ጉዳት የታማሚው የጤንነት ሁኔታ ፣የደም መርጋቱ የተከሰተበት ቦታ እና በምን ያህል ፍጥነት ሕክምና እንዳገኘ የመሳሰሉት ሁኔታዎች ደረጃውን ይለያዩታል። ብዙ ሰዎች በተለይም በእግራቸው ላይ የደም መርጋት ሕመም እንደደረሰባቸው ላያውቁ ይችላሉ። ምናልባትም ምልክቱ በግልጽ የማይታይ ሆኖ ወይንም ችላ ተብሎ ሊሆን ይችላል። በዚህም የተነሳ ወደ 25% የሚሆኑ ታማሚዎች የደም ቡዋንቡዋቸው በደም መርጋት ስለሚዘጋ በድንገት ይሞታሉ።
• የደረት ሕመም፣ የሆድ እቃ የላይኛው ክፍል ሕመም፣ ክንድ፣አንገት ወይንም መንጋጋ አካባቢ ሕመምና ስቃይ፣የምግብ አለመፈጨት፣ የትንፋሽ ማጠር፣ላብ ማላብ፣የማቅለሽለሽ ወይንም የማስመለስ እና የመሳሰሉት ሕመሞች ሲከሰቱ በፍጥነት ወደህክምና መሔድ ይገባል። ነገር ግን እነዚህ ምልክቶች ታዩ ማለት ሁልጊዜ የደም መርጋት ምልክቶች ናቸው ማለት አይደለም።

    የአዘርባጃኑ ፕሬዚዳንት ኢሃም አሊየቭ የትዳር አጋራቸውን መህሪባንን ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት አድርገው መሾማቸውን ባለፈው ማክሰኞ በይፋ ማስታወቃቸውን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
   ፕሬዚዳንቱ የ52 አመት ዕድሜ ያላቸውን ባለቤታቸውን በአገሪቱ የስልጣን እርከን ሁለተኛ ደረጃን በሚይዘውና ባለፈው መስከረም ወር ላይ በጸደቀው አዲሱ የተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንትነት ቦታ ላይ ማስቀመጣቸው ብዙዎችን እያነጋገረ እንደሚገን የገለጸው ዘገባው፣ ዘገባው ገልጧል፡፡ ባለፈው መስከረም ወር
ላይ በተከናወነው ህዝበ ውሳኔ በአገሪቱ የህገ መንግስት አንቀጾች ላይ ማሻሻያ መደረጉን ያስታወሰው ዘገባው፣
የፕሬዚዳንቱን የስልጣን ዘመን ከአመስት አመታት ወደ ሰባት አመታት ማሳደጉ፣ ከ14 አመታት በፊት የአባታቸውን ቦታ ተክተው አገሪቱን መምራት የጀመሩት ፕሬዚዳንት አሊየቭ ከስልጣን ላለመውረድ የያዙት አቋም መገለጫ ነው በሚል መተቸቱንም አክሎ ገልጧል፡፡
   በምክትል ፕሬዚዳንትነት የተሾሙት መህሪባን በህክምና ሙያ ከዩኒቨርሲቲ መመረቃቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ከዚህ ቀደም በህግ አውጭነት መስራታቸውንና የአንድ በጎ አድራጎት ድርጅት ሃላፊ ሆነው ማገልገላቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡
    ገና የ19 አመት ወጣት ሳሉ ከፕሬዚዳንት ኢሃም አሊየቭ ጋር ትዳር የመሰረቱት መህሪባን፣ በረጅም አመታት የትዳር ቆይታቸው ሁለት ሶቶች እና አንድ ወንድ ልጅ ማፍራታቸውን ዘገባው አክሎ ገለጧል፡፡

     ደቡብ ኮርያ በሞባይል ኢንተርኔት አገልግሎት ፍጥነት ከአለማችን አገራት የመጀመሪያውን ደረጃ መያዟን ኦፕንሲግናል የተባለው የቴሌኮም መረጃ ተቋም ሰሞኑን ያወጣውን የጥናት ውጤት ጠቅሶ ሲቢሲ ኒውስ ዘግቧል። ተቋሙ በ87 የአለማችን የተለያዩ አገራት የ2016 የፈረንጆች አመት የሞባይል ኢንተርኔት አገልግሎት ፍጥነት ዙሪያ ባደረገው ጥናት፣ ከአለም አንደኛ ደረጃን በያዘቺው ደቡብ ኮርያ የሞባይል ኢንተርኔት ፍጥነት በሰከንድ 37.54 ሜጋ ባይት እንደሚደርስ አስታውቋል፡፡
በሰከንድ 34.77 ሜጋ ባይት ፍጥነት ያለባት ኖርዌይ በሞባይል ኢንተርኔት አገልግሎት ፍጥነት ሁለተኛ ደረጃን መያዟን የጠቆመው ዘገባው፣ ሃንጋሪ በ31.04 ሜጋ ባይት በሰከንድ ፍጥነት ሶስተኛ ደረጃ ላይ መቀመጧን እንዲሁም ሲንጋፖር እና አውስትራሊያ በቅደም ተከተላቸው አራተኛና አምስተኛ ደረጃን መያዛቸውን ገልጧል፡፡
በጥናቱ ከተካተቱት የአፍሪካ አገራት በሞባይል ኢንተርኔት ፍጥነት አንደኛ ደረጃን የያዘቺው ደቡብ አፍሪካ ስትሆን፣ በሰከንድ 9.93 ሜጋ ባይት ፍጥነት ያላት አገሪቱ ከአለማችን አገራት ደግሞ የ48ኛ ደረጃን ይዛለች ተብሏል፡፡

     የናዚው መሪ አዶልፍ ሂትለር በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች እንዲገደሉ ትዕዛዝ አስተላልፈውበታል የተባለው ተንቀሳቃሽ ስልክ፣ በአሜሪካ ሜሪላንድ ውስጥ በተካሄደ ጨረታ 195 ሺህ ፓውንድ መሸጡ ተዘግቧል፡፡
የሂትለር የጥፋት ሞባይል ተብሎ የሚጠራውና ከ70 አመታት በላይ ዕድሜ እንዳለው የተነገረለት ይሄው ቀይ ቀለም ያለው ስልክ፣ በስተጀርባው የሂትለር ስም፣ የንስር ምስል እና የስዋስቲካ ምክልት እንዳለበት የዘገበው ቢቢሲ፣ ስሙ ያልተገለጸ ተጫራች በስልክ ባቀረበው የመወዳደሪያ ዋጋ አሸንፎ እንደገዛው ገልጧል፡፡
ብርጋዴር ጄኔራል ራልፍ ራይነር የተባሉ እንግሊዛዊ የጦር መሪ እ.ኤ.አ በ1945 በርሊን ውስጥ የሚገኘውን የሂትለር ምሽግ በጎበኙበት ወቅት፣ ይሄው ታሪካዊ ስልክ ከሩስያ የጦር መኮንኖች በስጦታ መልክ እንደተበረከተላቸውም ዘገባው አስታውሷል፡፡