Administrator
ዘዴ የሌለው ወፍ ቅርንጫፍ በሌለው ዛፍ ላይ ያርፋል!
ኤዞፕ ከፃፈልን ተረቶች መካከል አንዱ እንዲህ ይላል፡- ከዕለታት አንድ ቀን ብዙ ጥንቸሎች ተሰብስበው ይመካከራሉ፡፡
አንደኛ ጥንቸል - “ጐበዝ እኔ ኑሮ መሮኛል፡፡ በየአቅጣጫው ጠላት እኛ ላይ እያነጣጠረ መግቢያ መውጪያ አሳጣን፡፡ በየጊዜው መደበቅ፣ ከሰው መሸሽ በጣም ነው ያስጠላኝ” አለች፡፡
ሁለተኛዋ ጥንቸል - “እኔ ደሞ በጣም የሰለቸኝ ከውሻ መሸሽ፡፡ ድንገት ብቅ ካለ እኮ ካለእኛ ጠላት ያለው አይመስለውም፤ ክፉኛ ያባርረናል፣ ያሳድደናል” አለች፡፡
ሦስተኛዋ ጥንቸል - “እኔ ደግሞ እንደኛው የዱር አራዊት የሆኑ አውሬዎች ናቸው እረፍት የነሱኝ፡፡ ምን እንደሚበጀኝ እንጃ” አለች፡፡
እንዲህ እንዲህ እያሉ ሁሉም ብሶታቸውን ተነጋገሩ፡፡ በመጨረሻም፤ “እንዲህ ስቃይ ከሚበዛብንና በየቀኑ የሰውም፤ የውሻም፣ የአዕዋፍም፣ የዱር አውሬም ምግብ ከምንሆንና ምንም አቅም የሌለን ፍጡራን ሆነን ከምንቀር በቃ ውሃ ውስጥ ሰጥመን ብንሞት ይሻለናል” አሉ፡፡
ከዚያም ሁሉም በአንድ ድምጽ “አሰቃቂውን ህይወታችንን ላንዴም ለሁሌም እንገላገለው” በሚል በአቅራቢያቸው በሚገኝ ሰፊ ኩሬ ውስጥ ሰምጠው ሊሞቱ ሩጫቸውን ቀጠሉ፡፡
በኩሬው ዳርቻ ብዙ እንቁራሪቶች ተቀምጠው ፀሐይ ይሞቃሉ፡፡ እንቁራሪቶቹ በርካታ ጥንቸሎች ወደነሱ እየሮጡ ሲመጡ ተመለከቱና፤
“ጐበዝ፣ ጥንቸሎች ሊዘምቱብን ወደኛ እየተንደረደሩ ነው፡፡ በጊዜ ብናመልጥ ይሻለናል” ተባባሉ፡፡
ወዲያው ከኩሬው ዳርቻ ወደ ውሃው ጡብ ጡብ እያሉ በጣም ወደታች ጠልቀው ተደበቁ፡፡
ይሄኔ ከጥንቸሎቹ መካከል ብልሁ፤
“ቆይ ቆይ ቆይ” ብሎ ሁሉንም ጥንቸሎች አስቆማቸው፡፡
ሁሉም በርጋታ እሱን ለማዳመጥ ዞሩ፡፡
ጥንቸሉም፤
“አያችሁ፤ ራሳችንን ማጥፋት የለብንም፡፡ ልብ ብላችሁ ካስተዋላችሁ፣ እነዚህ እንቁራሪቶች እኛን ፈርተው ውሃ ውስጥ ገቡ፡፡ እኛንም የሚፈራን አለ ማለት ነው፡፡ እኛ ሌሎችን ፈርተን ራሳችንን እናጥፋ አልን፡፡ በዓለም ላይ ግን ሁሉም የሚፈራው አለው፡፡ ስለዚህ ሌሎች ያጠፉናል ብለን መፍራት የለብንም፡፡ እኛም የምናጠፋው አለና” ብሎ ሁሉንም መለሳቸው፡፡
***
ተስፋ ቆርጦ፣ ህይወት አበቃለት ከማለት በፊት ከእኔ የከፋም አለ ብሎ ማሰብ ትልቅ መላ ነው፡፡ ሁሉም የላይና የበታች አለው፡፡ የህይወት ሰልፍ ይህን ልብ እንድንል ያስገድደናል፡፡ ከጅምላ ውሳኔ መጠንቀቅ ደግ ነው፡፡ የተሻለው ካልተሻለው ጋር መክሮ ዘክሮ ካልተጓዘ አገር የጥቂቶች ብቻ ትሆንና ኑሮ በምሬት የተሞላ ይሆናል፡፡
የሀገራችን አሳሳቢ ጉዳዮች አያሌ ናቸው፡፡ በለውጥ ጐዳና ላይ አሳሳቢ ጉዳዮች ከበዙ ለውጡን ማዥጐርጐራቸው አይቀሬ ነው፡፡ ነባራዊ ሁኔታው በፈቀደው የሚከሰቱትን እንቅፋቶች ሁሉ ግን “ፀረ ልማት፣ ፀረ ዕድገት፣ ኪራይ ሰብሳቢነት” ወዘተ ብሎ ከመፈረጅ መጠንቀቅ ይገባል፡፡ ሩጫችን በፈጠነ መጠን “ችኩል ጅብ ቀንድ ይነክሳል”ን አለመርሳት ነው፡፡
የኦዲት ሪፖርትን በጥንቃቄ ማየት ተገቢ ነው፡፡ በመጨረሻው ሰዓት ምንጣፍ ለመግዛት ከመሯሯጥ አስቀድሞ በቅጡ ማቀድ ይሻላል፡፡ ፈሰሱ ሲበዛ ሜዳ የፈሰሰ እቅድ መኖሩን እንደሚያሳይ አንዘንጋ፡፡ በስንት ቢፒ አር፣ በስንት ግምገማ ተደግፎ ከእቅድ በላይ የተባለለት አፈፃፀም ኋላ በፈሰስ ሲመነዘር “አብዮቱ ግቡን መታ” እንደማያሰኝ እንወቅ፡፡ ሌላው አሳሳቢ ነገር የተጠርጣሪዎች መብዛት ነው፡፡ በቤት፣ በመሬት፣ በኤሌትሪክ ዕቃዎች፣ በጉምሩክ፣ በአገር ውስጥ ገቢ፣ ወዘተ እየጨመሩ ያሉ ተጠርጣሪዎች የሀገራችንን የሙስና ብዛትና ከፍተኛነት እየጠቆሙ ነው፡፡
ለዚህ ለምን አልተዘጋጀንም? ሊሠሩ የታሰቡ ነገሮች ምን መዘዝ እንደሚያመጡ ከወዲሁ ማስተዋል እንደምን ያቅታል፤ ጥፋተኝነታቸው የተነቃ ብዙ ሥራ ሲሰራ ብዙ እጅ ገንዘብ ውስጥ እንደሚገባ ጥርጥር የለውም፡፡ ሆኖም ባለሥልጣኖችሽ ሲነቃባቸው በቦሌ ሲወጡ ዝም ብሎ ማየት ተፈልጐ ነው ሳይታወቅ? ሄደው ቀሩ የሚባሉ ሰዎች ነገር ተድበስብሶ የሚታለፈው “ተገላገልነው” በሚል ስሜት ይሆንን?
ሙስና ከተወራ ብዙ ጊዜ ያስቆጠረ፣ ግባራዊ ገፁ ዛሬ የታየ ነው፡፡ ፀረ -ሙስና እርምጃው አለቃና ምንዝር ሳይል የሁሉንም በር ማንኳኳት ይገባዋል፡፡
ገና የሚንኳኩ በሮች ጀርባ የሚገኙ ሙሰኞች፤ “ግጥም ሞልቶን ነበር በስልቻ ሙሉ
አንዷ ጠብ ብትል ሁሉም ዝርግፍ አሉ” ዓይነት እንደሚሆን የሚያቅ ያቀዋል፡፡
ከሀገርና ከህዝብ ጥቅም አኳያ መታየት ያለባቸው፣ ግን እንደዘበት እየታዩ የሚታለፉ አያሌ ጉዳዮች አሉ፡፡ በጥንቃቄ ጊዜ ወስዶ ከልብ ሙስናን ፈልፍሎ ማውጣት ይበል የሚባል ቢሆንም፤ አላግባብ ጊዜ መስጠትም የዚያኑ ያህል ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡ ጊዜው በረዘመ ቁጥር የወንጀሎች መደራረብ፣ የህዝብና የሀገር ጉዳት የዚያኑ ያህል ያበዛልና!
የትኩረት አቅጣጫ በአንድ ጉዳይ ዙሪያ ብቻ ሲሆን ሌሎች የተበላሹ ነገሮችን እንዳናይ ስለሚያደርግ ዕይታችን ይጠብብናል፡፡ ስለሆነም ጉዳዮች ሁሉ በአገር ዙሪያ ሲጠነጠኑ የራሳቸው ተያያዥ ድርና ማግ ይኖራቸዋልና ዘርፎቹን ሁሉ በቆቅ ዐይን አጣምሮ ማየት ይገባል፡፡ አለበለዚያ “ዘዴ የሌለው ወፍ ቅርንጫፍ በሌለው ዛፍ ላይ ያርፋል” እንደተባለው ይሆናል፡፡
“ከአድማስ ፊት” 43ኛ ዝግጅቱን ያቀርባል
በሻሸመኔ ከተማ እና አካባቢዋ ኪነጥበባት አፍቃሪዎች የተቋቋመው “ከአድማስ ፊት” የኪነጥበብ ማህበር 43ኛ ወርሃዊ ዝግጅቱን እና የተመሰረበትን አምስተኛ አመት እንደሚያከብር አስታወቀ፡፡ ነገ ከሰዓት በኋላ በከተማዋ ሁለገብ አዳራሽ በማህበሩ አባላት እና የአካባቢው ማህበረሰብ በተጨማሪ አርቲስት ሜሮን ጌትነት እና አርቲስት ዘላለም ኩራባቸው በክብር እንግድነት ይገኛሉ፡፡ በዝግጅቱ የማህበሩን የአምስት ዓመት ጉዞ የሚያሳይ ዘጋቢ ፊልም የሚቀርብ ሲሆን ሽልማት የሚያሰጥ የግጥም ውድድርም ይኖራል፡፡
የይስማዕከ ወርቁ፣ “ክቡር ድንጋይ” ልቦለድ ለገበያ ቀረበ
በየዓመቱ አዳዲስ የሥነ ጽሑፍ ሥራዎቹን የሚያስነብበን ታዋቂው ወጣት ደራሲ ይስማዕከ ወርቁ፣ ዘንድሮም “ክቡር ድንጋይ” የተሰኘ ረጅም ልቦለድ ለንባብ አቀረበ፡፡ ባለ 200 ገፁ መጽሐፍ ለገበያ የቀረበው በ45 ብር ነው፡፡ ደራሲው ከዚህ ቀደም በ100ሺ ቅጂዎች የተቸበቸበለትን ዴርቶጋዳን ጨምሮ ራማቶሐራና ተከርቸም ሌሎች የረዥም ልቦለድ ሥራዎች ለንባብ ያቀረበ ሲሆን፤ በግጥም መድበሎቹም ዝናን ማትረፉ ይታወቃል፡፡
“ምልክት” የግጥም መድበል ትናንት ተመረቀ
ነዋሪነቱ በሰሜን አሜሪካ በሆነው ገጣሚ ሳምሶን ይርሳው ጌትነት የተጻፈው ምልክት የተሰኘ የግጥም መድበል የገጣሚው ቤተሰቦችና የጥበብ አፍቃሪዎች በተገኙበት ትናንት በብሄራዊ ቤተ መዛግብት አዳራሽ ተመረቀ፡፡ከዚህ በፊት በአሜሪካ የተመረቀው የግጥም መድበሉ 100 ገጾች ያሉት ሲሆን፣ በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥኑ ግጥሞች ተካተውበታል፡፡ ለገጣሚው የመጀመሪያ ስራው እንደሆነ የተነገረለት መድበሉ በ23 ብር እየተሸጠ ይገኛል፡፡
ቤተ-እስራኤላዊቷ ድምፃዊት በእስራኤል ደምቃለች
በቅርቡ “ላይፍ ሃፕንስ” የተባለ አዲስ አልበም በእስራኤል ለገበያ ያበቃችው ቤተእስራኤላዊቷ ድምፃዊት ኤስተር ራዳ፤ በእስራኤል የሙዚቃ ኢንዱስትሪ መድመቅ ጀምራለች ተባለ፡፡ የኤስተር ራዳ አዲስ አልበም አርቲስቷ ኢትዮጵያዊ የዘር ግንዷን ሙሉ ለሙሉ የገለፀችበት ነው ያለው “ኒውስፖይንት አፍሪካ” ፤ “ላይፍ ሃፕንስ” በተባለው ዘፈኗ ዋሽንትና ማሲንቆን እንደተጠቀመች ጠቅሷል፡፡ የ28 አመቷ ድምፃዊት፤ የዘፈን ግጥም ደራሲ እና ተዋናይቷ በአዲሱ አልበሟ ውስጥ “ላይፍ ሃፕንስ” የተሰኘውን የአልበሙን መጠርያ ጨምሮ “ሞንስተርስ”፤ “ኤኒቲንግ ፎር ዩ” እና “ኩድ ኢትቢ” የተባሉ ዘፈኖችን አካትታለች፡፡ በኢትዮ ጃዝ እና በሶል የሙዚቃ ስልቶች የተሰሩት የድምፃዊቷ ዘፈኖች በእስራኤላውያኖቹ እውቅ የሙዚቃ ባለሙያዎች ኩቲ እና ሳቦ የተቀናበሩ እንደሆኑ ለማወቅ ተችሏል፡፡
የኤስተር ቤተሰቦች እ.ኤ.አ በ1983 ዓ.ም በተከሰተው ረሃብ ሳቢያ ኢትዮጵያን ለቅቀው ወደ እስራኤል የተሰደዱ ሲሆኑ ኤስተር የተወለደችው ቤተሰቦቿ እስራኤል ገብተው ኪራያት ኡባ በተባለ ስፍራ መኖር ከጀመሩ ከአንድ አመት በኋላ ነው፡፡ ኤስተር እና ቤተሰቧ 10ኛ ዓመቷን እስክትይዝ ድረስ በሄብሮን ዳርቻ የኖሩ ሲሆን እድሜዋ ለእስራኤል የውትድርና አገልግሎት ሲደርስ ወደ ውትድርናው ገብታ እግረመንገዷን እዚያው በነበረ የሚሊታሪ ባንድ ድምፃዊ በመሆን ሰርታለች፡፡
ቤተእስራዔላዊ ብትሆንም በፀጉረ-ልውጥነቷ ብዙ አሳዛኝ ገጠመኞችን በወጣትነቷ ያሳለፈችው ኤስተር፤የሚሰማትን የመገለል ስሜት በሙዚቃዋ ስትከላከልና ስትዋጋ እንደኖረች አልደበቀችም፡፡ የውትድርና አገልግሎቷን ከጨረሰች በኋላ ኑሯዋን በቴል አቪቭ በማድረግም ወደ ትወና ሙያ እንደገባች ትናገራለች፡፡ በተዋናይነቷ የቴሌቭዥን ፊልሞች የሰራችው ኤስተር፤ ከአራት በላይ የሙሉ ጊዜ ፊልሞች ላይ መተወኗንና “ስቲል ዎኪንግ” እና “ዘ ሩቫቤል” የተባሉት ሁለት ፊልሞች በእስራኤል ፊልም አፍቃሪያን ዘንድ ተወዳጅነት ያተረፉ መሆናቸውን ገልፃለች፡፡
ወሎ ውስጥ በ1ቢ ብር ወጪ ሆስፒታል ሊገነባ ነው
በአንድ ቢሊዮን ብር ወጪ በደሴ ከተማ ውስጥ ይገነባል ለተባለው የወሎ ተርሸሪ ኬርና ቲቺንግ ሆስፒታል ግንባታ የሚውል ገቢ የማሰባሰብ ሥራ በይፋ ተጀመረ፡፡ ለሆስፒታሉ ማሰሪያ የሚሆን ገቢ የማሰባሰቡ ሥራ ባለፈው ረቡዕ በሸራተን አዲስ በይፋ በተከፈተበት ወቅት እንደተገለፀው፤ ሆስፒታሉ በብሔራዊ ደረጃ ከፍተኛ የህክምና ተቋም እንዲሆን ከማድረጉ በተጨማሪ የስልጠናና የምርምር ማዕከል ይሆናል፡፡ ከ750 በላይ አልጋዎች ይኖሩታል ለተባለው ለዚህ ሆስፒታል ግንባታ፤ የወሎ ተወላጆች የሆኑ ባለሀብቶችና በውጭ አገር የሚኖሩ የአካባቢው ተወላጆች ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደርጋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅም በዚሁ ወቅት ተገልጿል፡፡
የኢፌዲሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የትምህርት ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንንን ጨምሮ የክልሉ ተወላጆች የሆኑ ታላላቅ የመንግስት ባለስልጣናት በተገኙበት በሸራተን አዲስ በተካሄደው ፕሮግራም ላይ እንደተገለፀው፤ በመጪው ዓመት የሆስፒታሉ ግንባታ የገቢ ማሰባሰቢያ ዓመት እንዲሆን እቅድ ተይዟል፡፡ የደሴ ከተማ አስተዳደር ጢጣ በተባለው ሥፍራ ለሆስፒታሉ ግንባታ የሚውል 40 ሄክታር መሬት የሰጠ ሲሆን የሆስፒታሉ የመሰረት ድንጋይም ህዳር 16 ቀን 2004 ዓ.ም የኢፌዲሪ ምክትል ጠቅላይ ሚ/ር እና የትምህርት ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን፣ የአማራ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ አያሌው ጐበዜና የፕሮጀክቱ የበላይ ጠባቂ ሼክ አሊ መሐመድ ሁሴን አልአሙዲ በተገኙበት መቀመጡ የሚታወስ ነው፡፡
ፈርጅ ያለው ነጠላ አሰርቼ መልክ የሌለው ሰው ይለብሳል
ከነአያ አንበሶ በታች ያሉት የዱር አራዊት ሁሉ ተሰብስበው ትልቅ ግብዣ ተደረገና ዳንሱ፣ ጭፈራው፣ ዳንኪራው ቀለጠ! ደራ!
ከደናሾቹ መካከል ጥንቸል ተነስታ፤
“ዝም ብለን ከምንደንስ እንወዳደርና ምርጥ ዳንሰኛው ይለይ!” አለችና ሃሳብ አቀረበች፡፡
በሃሳቡዋ ሁሉም ተስማሙና ጭፈራው ቀጠለ፡፡ ሁሉም በተራ በተራ ወደ መድረክ እየወጣ ችሎታውን አሳየ፡፡
በመጨረሻ ዳኞች ተሰይመው ውጤት ተነገረ፡፡ በውጤቱ መሰረት አንደኛ - ዝንጀሮ፣ ሁለተኛ ቀበሮ፣ ሶስተኛ - ጦጣ ሆኑ፡፡
ዝንጀሮ መመረጡን በማስመልከት መድረክ ላይ ወጥቶ ተጨማሪ ዳንስ በማሳየት ታዳሚዎቹን አራዊት አዝናና፡፡ ንግግርም አደረገ፡፡
አራዊቱ በጣም በመደሰት ንጉሣችን ይሁን ብለው ወሰኑ፡፡
በዝንጀሮ ንጉሥ መሆን ቀበሮና ጦጣ ቅናት እርር ድብን አደረጋቸው፡፡ ስለዚህ መዶለት ጀመሩ፡፡
ጦጣ፤ “አያ ቀበሮ መቼም ከዳኝነት ስተት ነው እንጂ ዝንጀሮ ከእኛ በልጦ አይመስለኝም፡፡ አንተስ ምን ይመስልሃል?”
ቀበሮም፤
“እኔም እንዳንቺው ነው የማስበው፡፡ የዘመድ ሥራ ነው የተሰራው፡፡ ግን አንዴ ሆኗል ምን ይደረጋል?”
ጦጣ፤ “አንዴ ሆኗል ብለንማ መተው የለብንም”
ቀበሮ፤ “ምን እናደርጋለን ታዲያ?”
ጦጣ፤ “እኔ ወጥመድ ላዘጋጅ፡፡ አንተ እንደምንም ብለህ ወጥመዱጋ አምጣልኝ” አለችው፡፡ “ወጥመድ ላይ ሥጋ አድርጌ እጠብቃችኋለሁ፡፡ አንተ ዝንጀሮን ትጋብዘዋለህ”
ቀበሮ በሃሳቡ ተስማምቶ ዝንጀሮን ሊያመጣው ሄደ፡፡
ዝንጀሮ በአዲስ የሹመት ስሜት እንደሰከረ፤ እየተጐማለለ ይመጣል፡፡
“ይህን የመሰለ ሙዳ ሥጋ አስቀምጬልሃለሁ” አለው ወደ ሥጋው እያሳየው፡፡
ዝንጀሮም፤ “አንተስ? ለምን አልበላኸውም?” ይሄን የመሰለ ሙዳ እንዴት ዝም አልከው?” አለው፡፡
ቀበሮ፤ “ውድ ዝንጀሮ ሆይ! ለንግሥናህ ክብር ይሆን ዘንድ ብዬ ያዘጋጀሁት ነውና ስጦታዬን ተቀበለኝ?” አለው እጅ በመንሳት፡፡
ዝንጀሮ “ስጦታህን ተቀብያለሁ፤” ብሎ ወደወጥመዱ ዘው አለ፡፡ እዚያው ታስሮ ተቀረቀረ!!
ተናደደ!! በምሬትና በቁጭት በደም ፍላት ተናገረ፤
“ለዚህ አደጋ ልትዳርገኝ ነው ለካ ያመጣኸኝ? አንት ሰይጣን! ለንዲህ ያለ ወጥመድ ነበር ለካ ስታባብለኝ የነበረው? አረመኔ!” አለው፡፡
ቀበሮም፤ እየሳቀ፤
“ጌታዬ ዝንጀሮ ሆይ! የአራዊት ንጉሥ ነኝ እያልክ፤ ግን እቺን ቀላል አደጋ እንኳን ማለፍ አልቻልክም!” ይሄ የመጀመሪያ ትምህርት ይሁንህ ብሎ ጥሎት ሄደ፡፡
***
“ሹመት ያዳብር” የሚለውን ምርቃት የሀገራችን ህዝብ ጠንቅቆ ያቃል፡፡ በልቡ ግን “አደራዬን ተቀበል” የሚል ጠንካራ ማስጠንቀቂያና ጠንካራ መልዕክት ልኮ ማስገንዘቡ ነው፡፡ ካልሆነ አደራ በላ ትሆናለህ!
አደራ! ሲባል፤ የመብራት የውሃዬን ነገር አደራ ማለቱ ነው፡፡
አደራ! ሲባል፤ የትምህርትን ነገር ጠንቅቀህ ምራ ማለት ነው፡፡ ውስጡን በደምብ መርምር ማለት ነው፡፡
አደራ ሲባል፤ የኢንዱስትሪውን ሂደት፤ የትራንስፖርቱን (የባቡሩን፣ የመኪናውን፣ የአየሩንና የእግሩን ጉዞ) ነገር በቅጡ በቅጡ ያዙት ማለት ነው፡፡ የአካባቢ ጥበቃውንና የሳይንስና ቴክኖሎጂው ጉዳይ ዕውነተኛ አሠራር፣ ብስለትና ከዓለም ጋር የሚሄድ እንዲሆን ማድረግ ዋና ነገር ነው ማለት ነው፡፡
አደራ! ሲባል በተለይ የገቢዎችን ነገር፣ እከሌ ከእከሌ ሳትሉ ኢወገናዊ በሆነ ዐይን በማየት፤ የታረመ፣ የተቀጣ፣ ከስህተቱ የተማረ አካሄድ እንድትሄዱ ማለት ነው፡፡
አደራ ሲባል በአጭሩና በጥብቁ ቋንቋ
“አደራ - በላ አትሁኑ” ማለት ነው፡፡
በተለምዶ እኛ አገር “ባለፈው ሥርዓት” የሚል ፈሊጥ አለ፡፡ “ያለፈው ሹም ጥፋተኛ ነበር፣ ደካማ ነበር እኔ ግን አንደኛ ነኝ…” ዓይነት አንድምታ ያለው ነው ያለፈው ሹም የበደላችሁን እኔ እክሳለሁ! እንደማለትም አለበት፡፡ ይህን እንጠንቀቅ፡፡
የተሻሪም የተሿሚም ሂደት ተያያዥ ሥርዓት ነውና ሰንሰለቱ ተመጋጋቢ ነው፡፡ እንጂ የወረደው ጠፊ፣ የተሾመው ነዋሪ ነው ማለት አይደለም፡፡ በቅንነት፣ በሰብዓዊነት፣ በለሀገር አሳቢነት ካላየነው፤ ሁሉም ነገር ከመወነጃጀል አይወጣም፡፡ በተሰበሰበ ቀልብ፣ በሙያ ክህሎትና በዲሞክራሲያዊ አረማመድ ነው ፍሬያማ ለመሆን የሚቻለው፡፡ ያንን ካልተከተልን “ንጉሥ ነኝ እያልክ ይቺን ቀላል አደጋ እንኳን ለማለፍ አቃተህ” እንባባላለን፡፡
ጐባጣውን የምናቃናው፣ ጐዶሎውን የምንሞላውና የምናስተካክለው፤
መዋቅር የምናጠናክረው፣ እዚህጋ ተሳስተናል እንተራረም የምንባባለው፤ ለሀገር ይበጃል፣ ብለን ነው፡፡ የሾምነውና ያስቀምጥነው ሰው ተስተካክሎ የተበጀውን ሥርዓት ለግል ጥቅሙ ካዋለ፤ አደራውን ከበላ፣ አድሎኛ ከሆነ፣ በመጨረሻም ያለውን ሁኔታ ከመጠበቅ አልፎ በማሻሻል፤ ለውጥ ካላመጣ፣ የወላይትኛው ተረት እንደሚለው፤ “ፈርጅ ያለው ነጠላ አሰርቼ፤ መልክ የሌለው ሰው ይለብሳል” ሆነ ማለት ነውና ከወዲሁ እንጠንቀቅ፡፡ “ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል”ን እንዋጋ!
“ሸክላ ሲሰበር ገል ይሆናል፡፡ መኳንንትም ሲሻሩ ህዝብ ናቸው” የሚለውንም አንዘንጋ!
“አዲስ ጉዳይ” መጽሔት የዓለም አቀፍ ጋዜጠኞች ማዕከል ሽልማት አሸናፊ ሆነ
“አዲስ ጉዳይ” መጽሔት በታፈኑ ዕውነቶች አምድ ላይ ለንባብ ባበቃው “ቀናት የሚታደጓቸው እድሜ ልኮች” የሚል ተንታኝ ሃተታ (ፊቸር ስቶሪ) የዓለም አቀፉን የጋዜጠኞች ማዕከል (ICFJ) የሁለተኛ ደረጃ ቀዳሚ ሽልማት አሸነፈ፡፡ ማዕከሉ ከአፍሪካ የጤና ጋዜጠኞች ማህበር እና ከአረብ ሚዲያ ፎረም ጋር በመተባበር ባዘጋጀው በክትባት ጉዳይ ላይ የሚያተኩር የዘገባ ውድድር ላይ 200 የእስያ፣ የአፍሪካና ስድስት የባህረሰላጤው አገራት ሚዲያዎች እንደተሳተፉ ታውቋል፡፡
መጽሔቱ በኢትዮጵያ የክትባት ተደራሽነት አናሳ መሆኑን አስመልክቶ የሰራው ተንታኝ ሃተታ፤ ከመላው አፍሪካ፣ ከእስያና ከባህረሰላጤው ሀገራት ሚዲያዎች ጋር ተወዳድሮ ነው ያሸነፈው፡፡
ከ14 ሀገራት በተውጣጡ በሙያው አንቱ በተባሉ ጋዜጠኞች በተዋቀረው ኮሚቴ በተሰጠው ዳኝነት ከ200 ዘገባዎች ውስጥ የአዲስ ጉዳይ “ቀናት የሚታደጓቸው እድሜ ልኮች” ከሁለተኛ ደረጃ ተሸላሚዎች የአንደኝነት ደረጃን ለማግኘት ችሏል፡፡
“ኢትዮጵያን ወክለን መወዳደራችንና ማሸነፋችን ዝግጅት ክፍሉን በጣም አስደስቶታል፡፡ በተለይም በአሁኑ ወቅት አዲስ ጉዳይን በአዲስ መልክ ለአንባቢያን ለማቅረብና በይዘቱ ላይ መጠነኛ ማሻሻያ አድርገን በባለሙያዎች የሚሰራ መጽሔት ለማድረግ ከልዩ ልዩ ዘርፎች ባለሙያዎችን እና አማካሪዎችን ቀጥረን እየተንቀሳቀስን ባለንበት ወቅት ይህ ውጤት መገኘቱ ሞራላችንን ገንብቶታል፡፡ ለበለጠ ስራም አነሳስቶናል” ብሏል የመጽሔቱ ዋና አዘጋጅ አቶ ዮሐንስ ካሳሁን፡፡
የውድድሩ ዋና አላማ በክትባት ማጣት ሳቢያ በየዓመቱ ህይወታቸውን የሚያጡ ህጻናትን ቁጥር ለመቀነስና ለከፍተኛ የአካል ጉዳት የሚዳረጉ ዜጐችን ጤና መታገድ የሚያስችል እውቀት መፍጠር ሲሆን የመጽሔቱ ዘገባ ኢትዮጵያ ያለችበትን ወቅታዊ ሁኔታ በማሳየት ህብረተሰቡ ግንዛቤ እንዲኖረውና መንግስትም ክፍተቶቹን እንዲደፍን መረጃ የሚያስጨብጥ ነው ተብሏል፡፡
ቢሮውን ዋሽንግተን ዲሲ ያደረገው የአለምአቀፉ ጋዜጠኞች ማህበር ፕሬዚዳንት ጆይስ ባርናታን አሸናፊዎቹ ይፋ በተደረጉበት ስነስርዓት ላይ እንደተናገሩት፤ “አሸናፊዎች ያቀረቧቸው ስራዎች እንደ ፖሊዮ ያሉ ከፍተኛ ጉዳት አድራሽ የሆኑ ነገር ግን በቀላሉ መከላከል የሚቻሉ በሽታዎችን መቋቋምና ማሸነፍ የሚቻልባቸውን መንገዶች ያመላከቱ ትምህርት ሰጪ ዘገባዎች ናቸው፡፡ ለህዝባቸው እና ለጤና ባለሙያዎቻቸው እንቅፋትን አስወግደው ስኬትን የሚያገኙባቸውን መንገዶችም የጠቆሙ ናቸው” ብለዋል፡፡
በውድድሩ አንደኛ የወጡት የናይጀሪያ “ቲቪሲ ኒውስ” ቴሌቪዥን ጣቢያ፣ የፓኪስታኑ “ኒውስ ዋን” ቴሌቪዥን ጣቢያ፣ የኮትዲቩዋሩ “አቬኑ 225 ኒውስ ሳይት” ድረገጽ እና የተባበሩት አረብ ኢምሬቶች “ፊላንትሮፒ ኤጅ ማጋዚን” ሲሆኑ ጽሑፎቹ አንደኛ የወጡት ሚዲያዎቻቸው ሰፊ ተደራሽነት ያላቸው የቴሌቪዥን ኔትወርኮች በመሆናቸውና በኢንተርኔት ቴክኖሎጂ በታገዘ ስርጭታቸው አህጉራዊ ሽፋን በመፍጠራቸው መሆኑን የውድድሩ አዘጋጆቹ ተናግረዋል፡፡ ዋና አዘጋጁ አቶ ዮሐንስ እንዳለው፤ አዲስ ጉዳይ መጽሔት ከነዚህ ታዋቂ አህጉራዊ ሚዲያዎች ጋር ተወዳድሮ በ2ተኛ ደረጃ ተሸላሚነት ከተመረጡት የዩጋንዳው “ኤንቲቪ”፣ የፓኪስታኑ “ሳውዝ ኤሺያን ሜጋዚን”፣ እና የሳውዲአረቢያው “ሳውዲ ኒውስፔፐር ቱዴይ” ጋር የላቀ ውጤት በማስመዝገብ አንደኛ ደረጃ አግኝቷል፡፡ ይህ ውጤትም ኢትዮጵያውያን ሚዲያዎች በቴክኖሎጂ ቢታገዙና መልቲሚዲያ ቢሆኑ አህጉራዊ ተደራሽነትና ከየትኛውም አገር ጋር የሚፎካከር ሥራ መሥራት እንደሚችሉ ያመላከተ ነው፡፡
ደደቢት የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ‹መለስ ዋንጫ›ን ተቀዳጀ
የደደቢት የእግር ኳስ ክለብ የ2005 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ‹መለስ ዋንጫ› አሸናፊ መሆኑን አረጋገጠ፡፡ የውድድር ዘመኑ ሊጠናቀቅ የሁለት ሳምንት ጨዋታ እየቀረው ደደቢት ሻምፒዮን መሆኑን ያረጋገጠው ባደረጋቸው 24 ጨዋታዎች 17 አሸንፎ፤ በአራቱ አቻ ተለያይቶ እና በ3 ተሸንፎ 55 ነጥብ እና 35 የግብ ክፍያ በማስመዝገብ ነው፡፡ ደደቢት በአንድ ጨዋታ በአማካይ የሚያገባው 2.39 ጎሎች ሲሆን ይህም በሜዳው 2.91 ጎሎች ከሜዳው ውጭ ደግሞ በ1.92 ጎሎች የሚመነዘር ነው፡፡ ባደረጋቸው 24 ጨዋታዎች በተጋጣሚዎቹ ላይ 59 ጎሎች አስቆጥሮ 24 ጎሎችን ያስተናገደው ክለቡ ጎል ማግባት ያቃተው በ1 ጨዋታ ብቻ ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮንነቱም በ2014 በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ የሚሳተፍ ይሆናል፡፡
የደደቢት እግር ኳስ ክለብ መሥራችና ፕሬዚዳንት ኮሎኔል አወል አብዱራሂም ለስፖርት አድማስ እንደገለፁት ክለቡ የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን የሆነው ዕቅዱና አላማውን መሠረት አድርጐ በመንቀሳቀሱ ነው ብለው፤ በተገኘው ውጤት የትኩረት አቅጣጫው ለአገሪቱ እግር ኳስ ሙሉ አስተዋጽኦ ማበርከት መሆኑን አስመስክሮበታል ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ክለቡ በ2002 ዓ.ም ፕሪምየር ሊጉን ለመጀመሪያ ጊዜ ሲቀላቀል ለብሔራዊ ቡድን አንድ ተጨዋች ብቻ ማስመረጡን ያስታወሱት ፕሬዝዳንቱ፤ ከአራት የውድድር ዘመን በኋላ ግን በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በተሳተፈው ብሔራዊ ቡድን 8 ቋሚ ተሰላፊዎችን ከማስመረጡ በላይ ከአፍሪካ ዋንጫውም በኋላ ከክለቡ 11 ተጨዋቾች ተመልምለው 9ቱ በቋሚነት ተሰላፊነት ማስመረጥ መቻሉ ዓለማውን ያንፀባረቀ ነው ሲሉ አስረድተዋል፡፡
ደደቢት ፕሪሚዬር ሊግን መሳተፍ በጀመረ በ4ኛ የውድድር ዘመኑ ላይ የመጀመሪያውን የሻምፒዮንነት ክብር መጐናፀፉ በክለቡ ታሪክ አበይት ምዕራፍ የሚከፍት ነው ያሉት የክለቡ ፕሬዝዳንት ኮሎኔል አብዱራሂም፤ዘንድሮ ውድድሩ ለክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ መታሰቢያነት ተዘጋጅቶ ደደቢት ዋንጫውን መውሰዱ ልዩ ታሪክ እና ትርጉም ሰጥቶታል ብለዋል፡፡ ለዚህ ውጤት መገኘት ከክለቡ ባለድርሻ አካላት ባሻገር ለኢትዮጵያ እግር ኳስ እድገት ሞተር ሆነው ወሳኝ ሚና በመጫወት፤ የክለቡን ሞራል በመገንባትና የሚሰራን በማነሳሳት መመስገን ያለባቸው እግር ኳስ አፍቃሪያን ናቸው፤ በማለትም ኮሎኔል አወል ለስፖርት ቤተሰቡ ያላቸውን አድናቆት ገልፀዋል፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ማኅበር ለደደቢት የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮናነት የእንኳን ደስ ያላችሁ መልዕክት ወዲያውኑ በማድረስ የፈፀመው ተግባር በጣም እንደማረካቸው የሚናገሩት ኮሎኔል አብዱራሂም ከከፍተኛ ፉክክር በኋላ ለአሸናፊው ወገን አድናቆት መስጠት በአርአያነት ሊታይ የሚገባው ነው፤ ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ከአመት ወደ አመት የፉክክር ደረጃው እያደገ መጥቷል የሚሉት ኮሎኔል አወል አብዱራሂም፤ ክለቦች ለመሸናነፍ በጥሩ ፉክክር መወዳደራቸው፣ በደረጃ ሰንጠረዥ ላይ ተቀራራቢ ነጥቦች መስተዋላቸው እንደሚበረታታ አስገንዝበው በየመካከሉ ኢንተርናሽናል ውድድሮች በዝተው በውድድር ፕሮግራሞች ላይ በሚፈጠሩ መዛባቶች ከሚያመጡት የመቀዛቀዝ ችግር በስተቀር ጠንካራና ፈታኝ የውድድር ዘመን አሳልፈናል ብለዋል፡፡ ከ4 የውድድር ዘመን በፊት ደደቢት ፕሪሚዬር ሊጉን ለመጀመርያ ጊዜ ሲቀላቀል ባልተጠበቀ ሁኔታ ከባድ ፉክክር በማሳየት የፕሪሚዬር ሊጉን የመጀመርያ ዙር በመሪነት ቢያጠናቅቅም የውድድር ዘመኑን በ2ኛ ደረጃ ነበር የጨረሰው፡፡ በዚሁ የውድድር ዘመን ግን ክለቡ በኢትዮጵያ የክለቦች ውድድር ከፍተኛ ደረጃ ባለው የጥሎ ማለፍ ውድድር ሻምፒዮን ለመሆን በቅቷል፡፡ ካች አምና በኮንፌደሬሽን ካፕ እየተወዳደረ በመጀመርያ ዙር ማጣርያ ከውድድር የተሰናበተው ክለቡ በፕሪሚዬር ሊጉ ደግሞ ከቡና እና ጊዮርጊስ በመቀጠል በሶስተኛ ደረጃ አጠናቅቋል፡፡ አምና በፕሪሚዬር ሊጉ ለ3ኛ ጊዜ ተሳትፎ በሁለተኛ ደረጃ ያጠናቀቀው ደደቢት በአፍሪካ ክለቦች ኮንፌደሬሽን ካፕ የመሳተፍ እድል አግኝቶ እስከ ሁለተኛ ዙር የመልስ ጨዋታ በመጓዝ ተስፋ ሰጭ ውጤት አሳይቷል፡፡
የብሔራዊ ባንክ ክበብ ሠራተኞች በደል እንደሚፈፀምባቸው ተናገሩ
የብሔራዊ ባንክ ክበብ ሠራተኞች በደል እንደሚፈፀምባቸው ተናገሩ የብሔራዊ ባንክ ክበብ አስተዳደር፣ በሠራተኞቹ ላይ በደል እንደሚፈፅምና ያለ ህግና ማስጠንቀቂያ ከሥራ እንደሚያባርር በደል ደረሰብን ያሉ የክበቡ ሠራተኞች ገለፁ፡፡ የባንኩ የሠራተኞች ክበብ ከባንኩ ሠራተኞች በተጨማሪ ለውጭ ተጠቃሚዎች አገልግሎት በመስጠት እንዲሁም የሠርግ ፕሮግራሞችን በማዘጋጀት ላለፉት 20 ዓመታት ሲሠራ የቆየ ሲሆን በክበቡ ውስጥ በተለያዩ ሙያዎች ተቀጥረው በቋሚነት ሲያገለግሉ የቆዩ 92 ሠራተኞች ለረዥም ዓመታት ዕድገትና የደሞዝ ጭማሪ አግኝተው እንደማያውቁ ምንጮች ይናገራሉ፡፡ የአመት እረፍት፣ የህመም ወይም የወሊድ ፈቃድ የሚባል ነገር ያልተለመደና እንደ መብትም እንደማይቆጠር ነው በቅርቡ ከስራቸው የተባረሩ የክበቡ ነባር ሠራተኞች የገለፁት፡፡
ሠራተኞቹ በህመምና በሐዘን ምክንያት ከሥራቸው ሲቀሩ በጥበቃ ሠራተኞች ወደ ውስጥ እንዳይገቡ እንደሚከለከሉና በሥራ ላይ እያሉ ለሚደርስባቸው አደጋና የአካል ጉዳት ምንም ዓይነት ህክምና እንደማያገኙ ተናግረዋል፡፡ በሥራ ላይ እያለች እግሯ ላይ ቢላ ወድቆ በደረሰባት ጉዳት ለከፍተኛ ህመም የተዳረገችው የክበቡ ሠራተኛ፤ ከጉዳቷ ጋር በተገናኘ የሥራ ገበታዋ ላይ ባለመገኘቷ ደሞዟ እንደተቆረጠባት ሠራተኞቹ ይናገራሉ፡፡ ሌለው የክበቡ ሠራተኛም ፔርሙዝ ይዞ ደረጃ ላይ ሲወጣ ተንሸራቶ በመውደቁ እግሩ ቢሰበርም የሰበረውን ፔርሙዝ ሂሣብ እንዲከፍል ተደርጐ ከሥራ መሰናበቱን እነዚህ ሠራተኞች ይገልፃሉ፡፡ በክበቡ ውስጥ ለ15 ዓመታት በወጥ ቤት ኃላፊነት የሰሩትና ከህግና ስርዓት ውጭ ያለ ማስጠንቀቂያ የተባረሩት አቶ ቀፀላ ተሾመ፤ የበዓላት ቀናትን ጨምሮ የተለያዩ የትርፍ ጊዜ ሥራዎችን ቢሠሩም የሚያገኙት የትርፍ ሰዓት ክፍያ በሰዓት 3 ብር ብቻ እንደነበር ተናግረዋል፡፡
ያለ አንዳች ማስጠንቀቂያ ከሥራ ገበታቸው ላይ እንዲታገዱ ከተደረጉ በኋላም ወደ ውስጥ ገብተው ዕቃቸውን ለማውጣት እንኳን መከልከላቸውን የገለፁት አቶ ቀፀላ፤ ቀሪ ደመወዛቸውን ለመውሰድ ወደ መ/ቤታቸው ቢሔዱም ወደ ውስጥ መግባት እንደማይችሉ ተነግሮዋቸዉ፣ ገንዘብ ከፋይዋ ውጪ ድረስ ወጥታ እንደከፈለቻቸው ተናግረዋል፡፡ ከአቶ ቀፀላ ተሾመ ጋር ከሥራ ከታገዱት ሠራተኞች መካከል ወ/ሮ ሰላም አማኑኤል እና ወ/ሮ መሠረት ደምሴ በበኩላቸው፤ የክበቡ አስተዳደር ለሠራተኛው ደንታ የሌለውና የሠራተኛውን መብት ለማክበር ፈፅሞ የማይፈልግ መሆኑን ጠቁመው፤ መብቱን የጠየቀ ሠራተኛ እጣ ፋንታው ከሥራ መታገድ ብቻ እንደሆነ ተናግረዋል። በክበቡ ውስጥ ለሃያ ዓመት የሠሩ ሠራተኞች ቢኖሩም ሁሉም ሠራተኛ ቋሚ አይደለም እየተባለ ኃላፊዎች በፈለጉት ጊዜና ሰዓት ከሥራው ሊያፈቅናሉት እንደሚችሉ ስለሚያስፈራሩ መብታቸውን ለማክበር ወደ ፍርድ ቤት የሚሄዱ ሠራተኞች አለመኖራቸው፣ ለሃላፊዎቹ የልብ ልብ ሰጥቶ እንደፈለጉ እንዲገዙን አድርጓቸዋል ብለዋል - ተበዳዮቹ፡፡ የሠራተኞቹን ቅሬታ አስመልክቶ ምላሽ እንዲሰጡን የክበቡን የሥራ ኃላፊዎች ለማግኘት ባደረግነው ጥረት ከብዙ እንግልት በኋላ የክበቡ ሥራ አስኪያጅ አቶ ታደሰ መሰረትን ብናገኝም ጥያቄዎችን ማቅረብ ከመጀመራችን “ሥራችንን እያወካችሁ ነው” በማለት በጥበቃ ሠራተኞች ከቢሮአቸው ተገደን እንድንወጣ አድርገዋል፡፡