Administrator

Administrator

ከዕለታት አንድ ቀን በአንድ ዓመት በዓል ወቅት፣ አንድ አባት ልጁን ይዞ ወደ አንድ ሆቴል ቤት ጎራ ይላል፡፡ ለልጁ ለስላሳ ለሱ ነጭ አረቄ አዞ መጠጣት ይጀምራል፡፡ ያን አረቄ በላይ በላዩ ሲጨማምርበት ወደ ሞቅታው ተጠጋ፡፡
አረቄውን ልትቀዱለት የምትመላለሰው ቆንጆ ሴት እየተሞናደለችና ሽንጧን እያተራመሰች ስትመላለስበት ዐይኑ ከሱዋ አልላቀቅ አለ፡፡
“አንቺም ጠጪ፣ ለኔም አምጪ” ማለት ጀመረ፡፡ ቆንጆይቱም መጎንጨት ጀመረች፡፡ ሞቅ አላቸው ሁለቱም፡፡ ተጠቃቀሱና ተራ በተራ ወደ ጓዳ ገቡ፡፡
ይህ ሁሉ ሲሆን ልጅየው ለስላሳውን ትንሽ በትንሽ እየጠጣ ሲያስተውል ቆይቷል፡፡ አባቱ ሳይመለስ ብዙ የቆየ ስለመሰለው፣ ወደሄደበት አቅጣጫ ሄደ፡፡ አንድ ክፍል ውስጥ ተኝተዋል ለካ! ደንግጦ ቶሎ ወደ ቦታው ተመልሶ ተቀመጠ፡፡
አባትዬው ተመለሰ፡፡ አንድ ደግሞ ሂሳብ ከፈለና ወጡ፡፡
ቤት ደርሰው የሚበላ ቀርቦ በልተው እንደጨረሱ ጨዋታ መጣ፡፡
እናት - “እሺ ዙረታችሁ እንዴት ነበር?” አለች ወደ ልጁ እያየች፡፡
ልጁም - “መጀመሪያ ወደ ሆቴል ሄድን”
እናት - “እሺ?”
ልጅ - “አባዬ አረቄ አዘዘ፡፡ ለእኔ ለስላሳ ሰጠኝ”
እናት - “ከዛስ?”
ልጅ - “ከዛማ አባዬ ደጋገመ”
አባት - “በቃህ እንግዲህ! ወሬ አታብዛ”
እናት - “ተወው እንጂ ይንገረኝ”
ልጅ - “ከዛ የምታስተናግደንን ሴትዮ ጋበዛት”
እናት - ጉጉቷ ጨመረ፡፡ “እሺ ከዛስ?”
ልጅ - “ከዛ ሴትዮዋ ወደ ጓዳ ሄደች”
አባት - “አንተ ልጅ! ሁለተኛ ሽርሽር አልወስድህም!”
እናት - “ተወው ይጨርስልኝ!”
ልጅ - “ከዛ አባዬም ወደ ውስጥ ገባ”
እናት  - በችኮላ፤ “እሺ? ከዛስ?”
ልጅ - “አባዬ ሲቆይብኝ የት ሄደ ብዬ ወደዛ ሄድኩ”
እናት - “ከዛስ?”
ልጅ - “ከዛ አይቼ ተመለስኩ”
እናት - “ምን አየህ?”
ልጅ - አመነታ!
እናት ሁኔታው ገብቷት - “አይዞህ ንገረኝ”
ልጅ፤ እናቱንም አባቱንም አየና፤
“ያየሁትማ አንቺና ዘበኛችን እንደምትተኙት ዓይነት ነው!” አለ፡፡  
*           *          *
የሌላውን ዐይን ጉድፍ ለማሳየት ከመጣጣር የራስን ጉድፍ አስቀድሞ ማየት፣ አስቀድሞ ማውጣት ታላቅ ብልህነት ነው፡፡ ሁሉም ለስህተት በሚጋለጥበት ሁኔታ ውስጥ እያሉ አንዱ ባንዱ ላይ ጣቱን ቢቀስር ውጤቱ ሲቀሳሰሩ መዋል ነው፡፡ በንጉሡ ዘመን የወጣ አንድ ካርቱን ስዕል ባሳየው ምስል፣ ባለስልጣናት ወይም ሚኒስትሮች በትልቅ የኮንፈረንስ ጠረጴዛ ዙሪያ ተቀምጠዋል፡፡ እያንዳንዳቸው፣ አንዱ ባንዱ ላይ በሌባ ጣቱ ይጠቁማል፡፡ ማንም በማንም ላይ ጣቱን ሳይቀስር የሚታይ የለም፡፡ ሁሉም ጥፋተኛ ነው እንደማለት ነው፡፡ ግምገማዎች ምን ያህል ሀቀኛ ናቸው? ስህተትን ለማረም የሚያስችል ምን ያህል ቅን ልቦና አለ? የተገመገሙት ሁሉ እርምጃ ይወሰድባቸዋልን? ያንንስ ማን ይቆጣጠራል? ግምገማ ከእከክልኝ ልከክልህ ነፃ ነውን? ከየአንዳንዱ ግምገማ ምን ያህል ተምረናል? የሚገመገምና የማይገመገም፣ ይነኬና አይነኬ ሰው የለምን? ግምገማ ራሱ መገምገም የለበትምን? ባለፈው ዘመን የኮሚቴ መብዛት ትልቅ ችግር ሆኖ ተሰበሰቡና አሉ፤ ይህንኑ የሚያጠና ኮሚቴ አቋቁመው ተለያዩ! ሀገራችን አባዜዋ ብዙ ነው፡፡ አንድ ተገምጋሚ፤ ስለሀገራችን የስድስት መስመር የህዝብ መዝሙር ፃፍ ተብሎ አሥር ገፅ ያህል የዓላማ ፅሁፍ ተሰጠው፡፡ ቢለው ቢለው ያን ሁሉ ዓላማ በስድስት መስመር ማጠናቀቅ እንደማይመች ታወቀውና፤
“እንኳን ስድስት መስመር፣ መቶም አይበቃሽ እንደው በደፈናው፣ ዕንቆቅልሽ ነሽ    !”ብሎ ደመደመ ይባላል፡፡
በግምገማ ንፍቀ - ክበብ ዋና ጉዳይ የሚሆነው አዎንታዊነት (Positivism) ነው፡፡ በአዎንታዊነት ውስጥ ተስፋ አለ፡፡ በአሉታዊነት ውስጥ ጨለምተኝነት ነው ያለው፡፡ ሰውን ማነፅ አገርን ማልማት ነው፡፡ ሙያን ማክበር ሙያተኛን ማበልፀግ ነው! ይህም አዎንታዊነት ነው፡፡ መንገድ መሥራት ባለሙያ ይፈልጋል፡፡ ሀዲድ መዘርጋት ባለሙያ ይፈልጋል፡፡ ባቡር ማስኬድ ባለሙያ ይፈልጋል፡፡ በባቡር መሄድ ደግሞ ስልጣኔ ይፈልጋል፡፡ የባቡሩን መነሻና መድረሻ ደግሞ መረጃ ጆሮ ነው የሚፈልገው፡፡ አዎንታዊነት ውስጥ ሟርትን እንዳንከት መጠንቀቅ ያንድ የሰለጠነ ህዝብ ብልህነት ነው፡፡ ብዙ የሰራን እያስመሰልን ውስጡ ውስብስብ መክተት አሉታዊነት ነው! አገር ገንዘብ ይኖራት ዘንድ ሁለት ሶስት ያለው ቢላ መጠቀምም አሉታዊነት ነው፡፡ አገር አቀናለሁ ብሎ ደፋ - ቀና የሚለው ዜጋ፣ በንፁህ ስሜት፣ በቀና ልቦና ሲወድቅ ሲነሳ፤ ሌላው ወገን በአጭር - አቋራጭ (Short-cut)፣ አየር ባየር ከባለሥልጣን በመመሳጠር፣ በቀጭን ቢሮክራሲያዊ ትዕዛዝ ወዘተ… ሀብቱን ሲያከማችና ፎቁን ሰማይ ሲያስነካ ማየት ዘግናኝ ነው! ጉዳይ አስፈፃሚ የሆነ ባለዘመድ (መንገድ አዋቂ) ከባለ ጉዳዩ በላይ የሚያገኝበት አገር ውስጥ ለአስተዋይ ሰው ከኮሜዲው ትራጀዲው ማየሉ አይገርምም፡፡ በየቀኑ ነገር የባሰበት ዜጋ፤ “ደረቁ ከበደኝ እያልኩ፣ እርጥብ ትጨምርበታለች” የሚለው ለዚህ ነው! ከዚህ ያውጣን!!

    በአሁኑ ወቅት እጅግ አሳሳቢ እየሆነ ለመጣው የኩላሊት ህመም መፍትሄ ይሆናል በሚል በዘውዲቱ ሆስፒታል ግቢ ውስጥ በመገንባት ላይ ለሚገኘው የህክምናና የዕጥበት ማዕከል የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ወጣቶች ፎረም ተካሄደ፡፡ ትናንት በግሎባል ሆቴል በተካሄደው በዚህ ፕሮግራም ላይ ለማዕከሉ ግንባታ የሚረዳ ገቢ ለማሰባሰብ በማህበረሰቡ ላይ በጎ ተፅዕኖ የሚፈጥሩ የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች፣ ታዋቂ ሰዎች፣ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎችና የመንግስት ባለስልጣናት ተገኝተዋል፡፡

 የአርቲስት ሰብለ ተፈራ( እማማ ጨቤ) የቀብር ስነስርዓት በመንበረ ፀባኦት ቅድስት ስላሴ ቤተክርስቲያን የውጭጉዳይ ሚኒስቴር ዶር ቴዎድሮስ አድሃኖም ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት ታዋቂ ግለሰቦች  አድናቂዎቿ በተገኙበት የቀብር ስነስርዓቷ ተፈፀመ፡፡
ለወዳጅ ዘመዶቿ እንዲሁም አድናቂውቾ መፅናናትን እንመኛለን፡፡

Friday, 11 September 2015 10:18

የፀሐፍት ጥግ

  (ስለ ሳንሱር)
ማንኛውንም ዓይነት ሳንሱር አበክሬ እቃወማለሁ፡፡
ዶን ጆንሰን
ባኮሪያ ምንም መንግሥታዊ ሳንሱር የለም፡፡
ቦንግ ጁን-ሆ
ሳንሱር ልክ እንደ ችሮታ ከቤት መጀመር አለበት፡፡ ነገር ግን ከችሮታ በተለየ መልኩ እዚያው ማዎም ይኖርበታል፡፡
ክላሬ ቡዝ ሉሴ
ለዕድገት የመጀመሪያው አስፈላጊ ሁኔታ የሳንሱር መወገድ ነው፡፡
ጆርጅ በርናርድ ሾው
በብዙ የዓለም ክፍሎች ስላለው ሳንሱር እጨነቃለሁ፡፡
ጂማ ዋልስ
ዓለም ዘላለማዊ የሚላቸው መፃህፍት የራሳቸውን ውርደት የሚያጋልጡ ናቸው፡፡
ኦስካር ዋይልድ
ሰውን ዝም ስላሰኘኸው ለወጥከው ማለት አይደለም፡፡
ጆን ሞርሌይ
መፃህፍት ታግደው አይቀሩም ሃሳች ዘብጥያ አይወርዱም፡፡
አልፍሬድ ዊትኔይ ግሪስዎልድ
ምንጊዜም መፃህፍት ሲቃጠሉ ሰዎችም በመጨረሻ መቃጠላቸው አይቀርም፡፡
ሁንሪክ ሄይን
ብዙ ጊዜ ሳንሱር አድራጊው ከመድረሱ በፊት ራሳችንን ሳንሱር እናደርጋለን፡፡
ስፓይክ ሊ-
ማንንም ለማስደሰት ብዬ ራሴን ፈፅሞ ሳንሱር አላደርግም፡፡
ናታሊያ ኪልስ
የሰዎችን ህልም ሳንሱር ማድረግ አትችልም፡፡
ሮቢን ሂችኮክ
ዘፋኙን እንጂ ዘፈኑን መከርቸም አትችልም፡፡
ሃሪ ቤላፎንቴ

      ያለፈው የስራ ዘመናችን መጠነኛ ነበር፡፡ የስራ እንቅስቃሴዎቹ ደህና ናቸው፡፡ ያለፉት አመታት ላይ አጥልቶ የነበረው የስራዎች መጓተት በዚህኛውም ላይ አጥልቶ ነበረ፡፡ በዚህ ምክንያት እንቅስቃሴያችን መጠነኛ ነበር፡፡
በቀጣይ አመት ግን ብሩህ ተስፋ እናያለን፡፡ በኢህአዴግ ጉባኤ ላይ እንደተገለፀው፤የመልካም አስተዳደር ችግር ተቀርፎ፣ ለሀገር ውስጥ ባለሀብቶች የማጠናከሪያ ድጋፍ እየተደረገ ይሄዳል የሚል እምነት አለን፡፡ የሪል እስቴት ግዢና ሽያጭ ህግም ይፀድቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ እሱም በሪል እስቴት ላይ አዎንታዊ አስተዋፅኦ ይኖረው ይሆናል፡፡ በአጠቃላይ መጪው ጊዜ ብሩህ ነው ብሎ ማሰብ ይቻላል፡፡ ለኢትዮጵያ ህዝብም ሰላም፣ ጤናና፣ ፍቅር ይብዛለት!

    ያለፈው ዓመት ጥሩ የሚባሉ ስራዎችን የሰራሁበት ዓመት ነው፡፡ ሁለት ልጓሞቼን (ወርቅ በወርቅና፣ ሄሮሺማን) በቪሲዲ፣በዲቪዲ ለተመልካች ያቀረብኩበት ዓመት ነበር፡፡ የህዳሴውን ዋንጫም ይዘን ኢትዮጵያን የዞርኩበት ዓመት ነው፡፡ ዘመናዊ  ሲኒማ ቤትና የስፖርት ላውንጅ ግንባታም የጀመርኩበት ዓመት ነው፡፡ በብዙ መልኩ ለኔ ስኬታማ ዓመት ነበር፡፡
ቦሌ አካባቢ ያስገነባሁት ሲኒማ ቤት፣በአዲሱ ዓመት ሥራ ይጀምራል፡፡ መደበኛ ስራዎቹ እንደተጠበቁ ሆነው ሌላ አዲስ ፊልም የመስራት እቅድም አለኝ፡፡

   አንጋፋዋ ድምፃዊት አስቴር አወቀና ማዲንጎ አፈወርቅ ለአዲስ ዓመት ዋዜማ ዛሬ ምሽት  በጊዮን ሆቴል የሙዚቃ ኮንሰርት ያቀርባሉ፡፡ ከቀኑ 10፡30 ላይ የኮንሰርቱ መግቢያ በሮች እንደሚከፈቱ አዘጋጆቹ ገልፀዋል፡፡
የዝግጅቱ አስተባባሪ አቶ እዩኤል ልዑልሰገድ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፤በኮንሰርቱ ላይ ድንገተኛ (surprise) እንግዳ የሚኖር ሲሆን እንግዳው 2 ወይም 3 ዘፈኖችን ያቀነቅናል፡፡ አስቴር በዋዜማው ኮንሰርት 25 ዘፈኖችን የምታቀርብ ሲሆን ማዲንጎ 8 ወይም 9 ዘፈኖችን እንደሚያቀርብ ተገልጿል፡፡
የ2008 አዲስ ዓመትን ለመቀበል ከሌሊቱ 6 ሰዓት ላይ የርችት ተኩስ ሥነስርዓት ይካሄዳል ተብሏል፡፡ የVIP አቀማመጡ ከመድረኩ ፊት ለፊት መደረጉን የገለፁት አዘጋጆቹ፤ቲኬቶቹ ኤሌክትሮኒክ ስለሆኑ ግፍያ አይኖርም ብለዋል፡፡  

 የዘመን መለወጫ በዓልን ምክንያት በማድረግ የአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት ከፖሊስ ኦርኬስትራ የሙዚቃ ባንድ ጋር በመተባበር በነገው ዕለት ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ ልዩ የዓውዳመት የመዝናኛ ፕሮግራም ማዘጋጀቷን አስታውቋል፡፡ በእለቱ አጫጭር ድራማዎችን ጨምሮ ዘመናዊና ባህላዊ ዘፈኖች ከነውዝዋዜያቸው ይቀርባሉ፡፡ ፕሮግራሙን ከቀኑ 8፡00 ሰዓት እስከ 11፡30 በ30 ብር መግቢያ መታደም እንደሚቻል አዘጋጆች ተናግረዋል፡፡

 “የአባባ ተስፋዬ ተረቶች የስዕል አውደ ርዕይ” ባለፈው ማክሰኞ በብሔራዊ ቴአትር አርት ጋለሪ ተከፍቶ ለ4 ቀናት ክፍት ሆኖ የቆየ ሲሆን በዛሬው ዕለት ይጠናቀቃል፡፡ አውደ ርዕዩን መርቀው የከፈቱት አባባ ተስፋዬ፤በኔክስት ጄነሬሽን የበጎ አድራጎት ማህበር ህፃናትና ወጣቶች የተዘጋጀላቸው በሙካሽ የተጌጠ ካባ ተበርክቶላቸዋል፡፡ “በዓለም ላይ ብዙ አገራትን አይቻለሁ፤ሰርቶ ለመኖር እንደ ኢትዮጵያ የተመቸ አገር አላየሁም” ያሉት አባባ ተስፋዬ፤“አገራችሁንም ሥራንም ውደዱ፤እኔ አርቲስት ሆኜ እየሰራሁ  ሻሸመኔ ላይ በግብርና ሥራም ተሰማርቼ ነበር፡፡ ከግብርናው ባገኘሁት ትርፍም የራሴን ቤት ሰርቻለሁ፤መኪናም ገዝቻለሁ” በማለት የሥራን ጥቅም አስረድተዋል፡፡
በመክፈቻው ላይ ንግግር ያደረገው ዲያቆን ዳንኤል ክብረት በበኩሉ፤“እኛ ዛሬ ላይ የደረስነው በቀደመው ትውልድ ታግዘንና ተረድተን ነው፡፡ ይህንን ውለታ ታሳቢ በማድረግ አባባ ተስፋዬን የሚዘክር መድረክ መሰናዳቱ መስፋፋትና መቀጠል አለበት” ብሏል፡፡
በአባባ ተስፋዬ ሳህሉ መኖሪያ ቤት ይዞታ ላይ ሊሰራ የታቀደው ቴአትር ቤትና የባህል ማዕከል ጋለሪ ህንጻ ዲዛይን በዕለቱ ቀርቦም ገለፃ ተሰጥቶበታል፡፡

 በብሩክ ከድር የተዘጋጀው “የአረቦች ፀደይ” የተሰኘ መፅሃፍ በትላንትናው ዕለት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ፋካልቲ፣ የፕሮፌሰር እሸቱ ጮሌ መታሰቢያ አዳራሽ ተመርቋል፡፡
መፅሀፉ እ.ኤ.አ ከ2010 ጀምሮ በመካከለኛው ምስራቅ የተከሰተውና እስካሁንም ሙሉ በሙሉ ያልተጠናቀቀው ንቅናቄ ያስከተለውን ዘርፈ ብዙ ምስቅልቅልና ሁለንተናዊ ገፅታውን ይዳስሳል፡፡
በ253 ገፆች በተቀነበበው “የአረቦች ፀደይ” መፅሃፍ ላይ አጭር ውይይት እንደተካሄደም ታውቋል፡፡