Administrator

Administrator

- ቀንደኞቹ ሙሰኞች የመንግስት ባለስልጣናት ናቸው ተብሏል
             
       ዚምባቡዌ በተለያዩ የሙስና ወንጀሎች ሳቢያ በአመት ከ1 ቢሊዮን ዶላር በላይ ገንዘብ እያጣች እንደምትገኝና ከፍተኛውን የሙስና ወንጀል የሚፈጽሙት የመንግስት ባለስልጣናትና የፖሊስ አባላት መሆናቸውን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል የተባለው አለማቀፍ ተቋም ሰሞኑን ያወጣውን ሪፖርት ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ በትምህርትና በትራንስፖርት እንዲሁም በሌሎች ዘርፎች የሚሰሩ የአገሪቱ የመንግስት ባለስልጣናት፣  የሥራ ሃላፊዎችና የፖሊስ አባላት፣ ዜጎችን በከፋ ሙስና እያሰቃዩ ይገኛሉ፡፡ በዚምባቡዌ የሙስና ተግባር ተቋማዊ እየሆነና የበለጠ እየረቀቀ መምጣቱን የጠቆመው ሪፖርቱ፤ የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በከፍተኛ ደረጃ የሚከናወኑ የሙስና ወንጀሎችን መከላከል አልቻሉም ብሏል፡፡ በዚህም የውጭ ኩባንያዎች ሙስናን በመፍራት ወደ አገሪቱ እንዳይገቡ ሆነዋል  በማለት ፕሬዚዳንት ሙጋቤን ተጠያቂ እንደሚያደርጉም ተጠቁሟል፡፡
ፕሬዚዳንት ሙጋቤ፤ ምንም እንኳን ሚኒስትሮቻቸው በሙስና ላይ እንደተሰማሩ በተደጋጋሚ ቢያምኑም አንዳቸውንም ለፍርድ ለማቅረብ አለመሞከራቸውን የሚያረጋግጡ መረጃዎች መገኘታቸውን ዘገባው ያመለክታል፡፡

   አለማቀፉ የማራቶንና የረጅም ርቀት ውድድሮች ማህበር፣ለአትሌት ኃይሌ ገብረ ስላሴ የኤአይኤምኤስን የእድሜ ዘመን ስኬት ሽልማት በመጪው ህዳር ወር መጀመሪያ ሊያበረክት መወሰኑን አስታውቋል፡፡
የማህበሩ ፕሬዚዳንት ፓኮ ቦራኦ፤ኃይሌ ለአለማችን ማራቶን ላበረከተው አስተዋጽኦ እውቅና መስጠት በመቻላቸው ኩራት እንደሚሰማቸው ገልጸው፣ የአትሌቱ ስኬት ከአፍሪካ አልፎ በመላው አለም ለሚገኙ በርካቶች የመነቃቃት ምንጭ መሆኑንና የዓላማ ጽናቱም ለተምሳሌትነት የሚበቃ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ማህበሩ ባወጣው መግለጫ፤በመጪው ህዳር ወር መጀመሪያ ላይ በግሪክ አቴንስ በሚካሄድ ሥነስርዓት ላይ ለኃይሌ የእድሜ ዘመን ሽልማቱን እንደሚያበረክት አስታውቋል፡፡ ኃይሌ ገብረ ስላሴ የማህበሩን አለማቀፍ ሽልማት ሲቀበል ይህ የመጀመሪያው እንዳልሆነ ያስታወሰው መግለጫው፣ አትሌቱ እ.ኤ.አ ከ2006 እስከ 2008 ባሉት ዓመታት የማህበሩን የዓለማችን ምርጥ አትሌት ሽልማት፣ለሶስት ተከታታይ ጊዚያት ማግኘቱንም ገልጧል፡፡ ኃይሌ ለማህበሩ ሽልማት በመመረጡ ከፍተኛ ደስታ እንደሚሰማው ገልጾ፣ በአቴንስ በሚካሄደው ስነስርዓት ላይ ተገኝቶ ሽልማቱን እንደሚቀበልና በማራቶን ማህበረሰብ ውስጥ ካሉ ጓደኞቹ ጋር አስደሳች ጊዜ እንደሚያሳልፍ ተናግሯል፡፡
አለማቀፉ የማራቶንና የረጅም ርቀት ውድድሮች ማህበር፣የበርሊን ማራቶንን ጨምሮ በአለማችን 110 አገራትና አካባቢዎች የሚካሄዱ እጅግ ዝነኛና ግምባር ቀደም አለማቀፍ የሩጫ ውድድሮችን በአባልነት መያዙ ታውቋል፡፡

“ለደህንነታችን ዋስትና የሚሰጠን አካል የለም” ባለሀብቶች
- “ቢሻን ጋሪ ሎጅ” ላይ በደረሰው ዘረፋና ቃጠሎ ፖሊስ ጥቃቱ እንዳይደርስ ከመከላከል ተቆጥቧል
- ፖሊስ ጣቢያዎች፣ ፍርድ ቤቶች፣ ማዘጋጃ ቤቶችና የመንግስት ተቋማት ወድመዋል

በኢሬቻ በዓል አከባበር ወቅት የተከሰተውን የበርካቶች ህልፈተ ህይወት ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች በተቀሰቀሰው ተቃውሞና አመፅ እያደረሰ ያለው የንብረት ውድመት ከመንግስት ጥበቃና ቁጥጥር ውጪ እየሆነ ነው፡፡
ባለፈው ሳምንት በክልሉ የተለያዩ ስፍራዎች በተቀሰቀሰው ተቃውሞና አመፅ በቢሊዮን ብሮች የሚቆጠር ንብረት ወድሟል ተብሏል፡፡
ሰሞኑን በቡራዩ፣ በሰበታ፣ በአዋሽ መልካሳ፣ በአርሲ ነገሌ፣ በአለምገና እና ሌሎች የኦሮሚያ ክልሎች በተቀሰቀሰው ተቃውሞ፣ በሚሊዮኖች በሚቆጠር ገንዘብ የተቋቋሙ ፋብሪካዎች፣ የህዝብና የጭነት ማመላለሻ መኪኖች፣ የመንግስት ተቋማት፣ ፖሊስ ጣቢያዎችና የአበባ እርሻዎች ሙሉ በሙሉ ወድመዋል፡፡
በላንጋኖ አካባቢ በ100ሺ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ በተገነባው ቢሻን ጋሪ ሎጅ ባለፈው እሮብ በደረሰበት ዘረፋና ቃጠሎ ሙሉ በሙሉ ለማጥፋትም ሆነ ንብረቱን ከአደጋ ለመከላከል የተደረገ ሙከራ አለመኖሩ ተስፋ እንዳስቆረጣቸው የድርጅቱ ባለቤት አቶ ዑመር ባገርሽ ትናንት ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ላይ ተናግረዋል፡፡
ሎጁ ላለፉት 17 ዓመታት የአካባቢ ጥበቃን ባማከለ መንገድ ለውጪ አገርና ለአገር ወስጥ ቱሪስቶች አገልግሎት በመስጠት ላይ እንደነበር የገለፁት ባለሀብቱ፤ ‹‹ምንም በማናውቀውና ፈፅሞ ባልገመትነው ሁኔታ በሎጁ ላይ በተፈፀመው ዘረፋና የቃጠሎ አደጋ ከፍተኛ ሀዘን ተሰምቶናል ብለዋል፡፡ የድርጅቱ ኦፕሬሽን ክፍል ሃላፊ አቶ ዘለዓለም ቤኩማ በወቅቱ ስለተፈጠረው ሁኔታ ሲገልፁ፤ “ማንነታቸውን የማናውቃቸው በርከት ያሉ ወጣቶች እየጨፈሩ ወደ ግቢው ለመግባት ያደረጉትን ተደጋጋሚ ሙከራ በአካባቢው ሽማግሌዎች ልመናና ውትወታ ለመከላከል ሞክረናል፡፡ ሁኔታው እየተባባሰና የሰዎቹም ቁጥር እየጨመረ ሲሄድ ለአሩሲ ነጌሌ ፖሊስ ጣቢያ ደውለን፣ አሣወቅን” ያገኘነው ምላሽ ግን ተስፋ የሚያስቆርጥ ነው ብለዋል፡፡ እኛ ወደ እናንተ መምጣት አንችልም፤ ጉዳዩን እዛው በሽምግልና ለመፍታት ሞክሩ ነው ያሉን ሲሉ ገልፀዋል - አቶ ዘልዓለም፡፡  “ሁኔታው ከአቅማችን በላይ ስለነበር፣ ዓይናችን እያየ ሎጁን እሳት ለኮሱበት፡፡ በአሁኑ ወቅትም ሎጁ ሙሉ በሙሉ ወድሟል፡፡ በሰው ህይወት ላይ ግን የደረሰ አደጋ የለም›› ብለዋል፡፡ በዚህ ዘረፋና ቃጠሎ ከ50 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት ንብረት እንደወደመባቸውም የሎጁ ባለቤት አቶ ዑመር ባገርሸ ተናግረዋል፡፡
‹‹ደህንነታችን ባልተረጋገጠበትና ፖሊስ ሊደርስልን በማይችልበት ሁኔታ ውስጥ እንሆናለን ብለን ፈፅሞ አልጠረጠርንም፡፡ የደረሰብን ጉዳት እጅግ አሳዛኝና ተስፋ አስቆራጭ ነው›› ብለዋል፡፡
ባለፈው ረቡዕ በኦሮሚያ ክልል አዋሽ መልካሳ በተቀሰቀሰ አመፅ በአካባቢው በሚገኘው ብስራት የጠጠር ማምረቻ ድርጅት ላይ የተከሰተው ቃጠሎም ከ23 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገዙ አዳዲስ ማሽኖች ወድመዋል ተብሏል፡፡
ውድመቱ በደረሰባቸው አንዳንድ አካባቢዎች ተዘዋውረን ያነጋገርናቸው ባለሃብቶች፤ በአሁኑ ወቅት በከፍተኛ ሥጋት ላይ እንደሚገኙና በማንኛውም ጊዜና ሰዓት በንብረታቸውም ሆነ በህይወታቸው ላይ አደጋ ሊከሰት እንደሚችል ገልፀው፤ ለደህንነታችን ዋስትና የሚሰጠንና አደጋ ቢደርስብን ፈጥኖ የሚደርስልን አካል የለም ብለዋል፡፡ ሁኔታው ከመንግስት ቁጥጥር ውጪ እየሆነ መምጣቱ ከፍተኛ ሥጋት አሳድሮብናል ሲሉም ተናግረዋል፡፡
በዝዋይ ከተማ ውስጥ በአበባ እርሻ ልማት ላይ የተሰማሩ አንድ ባለሃብት ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፤ በአካባቢው በተቀሰቀሰው ተቃውሞና አመፅ ሳቢያ በንብረት ላይ እየደረሰ ያለው ውድመት እጅግ እንዳሳሰባቸው ጠቁመው፤ ዋስትና በሌለበትና ምን እንደሚከሰት መገመት በማይቻልበት ሁኔታ ውስጥ መሆን እጅግ አስፈሪ ነው ብለዋል፡፡
በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ አካባቢዎች እየተባባሰ በሄደው ተቃውሞና አመፅ በርካታ ፖሊስ ጣቢያዎች፣ ፍርድ ቤቶች፣ ማዘጋጃ ቤቶች፣ የመንግስት ሴክተር መ/ቤቶች የመንግስትና የግለሰቦች ተሽከርካሪዎች በእሳት ወድመዋል፡፡ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት፤ በሳምንቱ ውስጥ በርካታ የመንግስትና የግል ንብረቶች ወድመዋል፡፡ በሰበታ ከተማ ብቻ የኤሌክትሪክ ኬብል ማምረቻ፣ የጨርቃ ጨርቅና የፕላስቲክ ፋብሪካዎችን ጨምሮ 11 ልዩ ልዩ ፋብሪካዎች የተቃጠሉ ሲሆን ከ62 በላይ አውቶብሶችና ሌሎች ተሽከርካሪዎች በቃጠሎው ሙሉ በሙሉ ወድመዋል፡፡  



 (የራስ ተሞክሮ)

      ስለ አጭር ልብ ወለድ መፃፍ ፈለግሁኝ፡፡ ስለ አጭር ልብ ወለድ ከመፃፍ፣ አጭር ልብወለድ መፃፍ ይቀለኛል፡፡ መጀመሪያ ያነበብኩትን አጭር ልብ ወለድ ከማስታወስ፣ መጀመሪያ የፃፍኩትን አጭር ልብ ወለድ ማስታወስ ይቀለኛል፡፡
አዲስ ነገር የምፈልግበት ጊዜ ነበር፡፡ የተወሰኑ የእንግሊዝኛ አጭር ልብ ወለዶች ለመፃፍ ሞክሬ፣ግን እኔ እንደምፈልጋቸው አልሆኑልኝም፡፡ ያነበብኳቸው መፅሐፍት እየጎተቱ ያስቸግሩኛል፡፡ ደግሞ ፀሐፊ/ደራሲ እሆናለሁ ብዬ ቆርጫለሁኝ፡፡ የቀድሞ ስራዬን ለዚህ ድፍረት ስል ትቼዋለሁ፡፡ አስታውሳለሁኝ በጣም የትግል ጊዜ ነበር፡፡ የጥርጣሬ ጊዜ ነበር፡፡ “ነኝ ወይንስ አይደለሁም? መፃፍ እችላለሁ ወይንስ አልችልም?” … ሁሉም ነገር ጥርጣሬ ብቻ ነበር፡፡ ግን እርግጠኝነትም አለ፡፡ እርግጠኛ ባልሆን እርግጠኛ የነበረውን ስራዬን አልተውም፡፡
“It’s a shot in the dark” እንደሚለው ነው ቡካውስኪ፡፡ … “ወርውር የእጅህን ዘገር/የህሊናህን ዘር/ ይዘኸው እንዳትቀር” የሚለው የደበበ ሰይፉ ቁራጭ ግጥምን እንደ አዝማች እደጋግማለሁ፡፡ ቤተሰቦቼ ፈርተውኛል፡፡ ተጠራጥረውኛል፡፡ አባቴ አንድ ቀን አስቀምጦ መከረኝ፡፡ ስለ ብዙ ደራሲዎች ህይወት ዘረዘረልኝ፡፡ ብዙዎች ደራሲ እንሆናለን ብለው ባክነው ነው የሚቀሩት ------ they end up being bums … ምናምን ሲለኝ ትዝ ይለኛል። ግን ማስፈራሪያው ቢያስፈራራኝም፣ ህይወቴ ትርጉም የሚኖረው ሳልፈራ ከቀጠልኩ ብቻ ነው ብዬ ገገምኩኝ፡፡
ቤተሰቤ በአጠቃላይ በንባብ ባህል ውስጥ የሚመላለስ ቢሆንም … የሌሎችን ልፋት በድርሰት መልክ ማንበብ እንጂ … ደራሲ ሆኖ አስነብባለሁ የሚል አቋምን ለማስተናገድ ዝግጁ አልነበረም፡፡ “ሞክር እና እየው” በሚል ተዉኝ፡፡
የፅሁፍ አለም አስፈሪው ጨለማ በመኝታ ቤቴ ውስጥ ቢሰፍንም … መፅሐፍ ገልጬ ሳነብ መጠነኛ ብርሐን እፈጥራለሁ፡፡ የሆነ ሀሳብ ብልጭ ሲል ለመፃፍ ስታገል፣ ጥርጣሬዬ ለጊዜውም ቢሆን ይወገዳል፡፡ ትግል ነው፡፡ ተስፋ መቁረጥ እንዳይኖር ግን ከጧት እስከ ማታ በትግል ውስጥ እደበቃለሁኝ።
የጥንቱ የስራ ዓለም ጓደኞቼን ራቅኋቸው። የድሮው አለም ለፅሁፍ ግብአት እንዲሆነኝ እንጂ እንድኖርበት አልፈልግም ብዬ ወስኛለሁ፡፡ አዲስ ድልድይ ለመስራት የድሮውን አፈረስኩት፡፡  እንድፅፍ ሲያበረታታኝ የነበረ አንድ ፈላስፋ ወዳጅ ነበረኝ፡፡ ፀሐፊ ሆኖ እኔ እንድፅፍ ሲገፋፋኝ በነበረ ጊዜ፣ እኔ ደብዳቤ እንኳን መፃፍ የማልደፍር ሰው ነበርኩኝ፡፡ ጓዜን ጠቅልዬ ወደ ፅሁፍ ስገባ፣ ፀሐፊ የነበረው ጓዴ መፅሐፍን ማምለክ አቁሞ፣ ብር ማምለክ መጀመሩን በይፋ አስታወቀኝ፡፡ እምነቴን እንዳይበክለው ካፈረስኩት ድልድይ ጋር እሱንም አስወገድኩት፡፡
በህይወቴ እንደዚያ ያነበብኩበት ዘመን የለም። ሌላ አማራጭም አልነበረኝም፡፡ የማላነብ ከሆነ መፃፍ ነበረብኝ፡፡ የማልፅፍ ከሆነ ስለ ፀሐፊዎች ህይወት ማወቅ ነበር ፍላጎቴ፡፡ የጃክ ለንደንን አጭር ልብ ወለዶች ከመውደድ ወደ መጥላት ገባሁኝ። ከአጭር ልብ ወለዱ ይልቅ “ማርቲን ኤደን” የተባለውን ብቸኛውን ረጅም ድርሰቱን ሳነብ ብዙ ፅናትን ፈጠረልኝ፡፡ “ማርቲን ኤደን” የአንድ ደራሲ ታሪክ ነው፡፡ ተነባቢ ለመሆን የሚያደርገውን ውጣ ውረድ፣ ከህይወቱ ጋር ቀይጦ የሚተርክ መፅሐፍ ነበር፡፡ ልክ ለእኔ የተፃፈ ድርሰት እስኪመስለኝ ተዋጥኩበት፡፡
የጃክ ለንደን አጫጭር ልብ ወለዶችን የጠላሁበት ምክኒያት ለአንባቢ እንጂ ለደራሲ የሚሆኑ ስላልነበሩ ነው፡፡ በህይወት ስቃይና በተፈጥሮ ጭካኔ ስር ስለሚፍጨረጨሩ ሰዎች ገድል ነው  የሚተርኩት። የህይወት ተሞክሮው በጉዞ ገድሎችና በአደገኛ የህይወት ጠርዝ ላይ ተፈትኖ የኖረ ሰው የሚፅፋቸው ታሪኮች ናቸው። የእሱ ታሪክን እንደ አንባቢ ሆኜ ሳየው፣ ነፍስን ሰቅዞ የሚይዝ የአድቬንቸር ፊልም ነው፡፡ ግን የእኔን አለም አይወክልም፡፡ የእኔ አለም ከመኝታ ቤቴና ከመፅሐፍቴ የበለጠ ገድል የሌለበት ነው። ተጉዤ አላውቅም፡፡ ጀብድ ፈፅሜም አላውቅም። ለነገሩ የመጓዝም ፍላጎት አልነበረኝም፡፡ እኔ የጉዞ ማስታወሻ ፀሐፊ መሆን እጣ ፈንታዬ አይደለም ብዬ ደምድሜያለሁ፡፡ ስለዚህ ጃክ ለንደንን ጠላሁት። ሪያሊዝም የሚፅፉትንም ጠላሁዋቸው፡፡ አዲስ አማራጭ መፈለግ ነበረብኝ፡፡ ስለ ተራ ሰዎች መፃፍ እችላለሁ፡፡ የማውቃቸው ሰዎች ከተራም የበለጠ የወል ናቸው፡፡ የሚያወሩትን፣ የሚያስቡትን፣ የሚኖሩትን ----- ልፅፈው ይቅርና ልብ ብዬ ሳያቸው እንኳን ነፍሴ ትፀየፋለች፡፡
አቅጣጫ ማግኘት ነበረብኝ፡፡ የራሴን ድምፅ መፍጠር ነበረብኝ፡፡ ጭንቁ የሚቻል አይደለም። ጭንቅ ውስጥ እንደነበርኩ ግን የሚገባኝ አሁን ወደ ኋላ ተመልሼ ሳስታውስ ነው፡፡ ደግነቱ በወቅቱ ለእኔም አይታወቀኝም ነበር፡፡ ኪሎ ስቀንስም ልብ አልልም፡፡ ያኔ ኤችአይቪ የሚፈራበት ዘመን ነበር፡፡ ግን አይታወቀኝም፡፡ …. ማማጥ ብቻ ነበር ሥራዬ፡፡
ይሄ ጽሁፍ ልብ ወለድ ይመስላል አይደል። ወደ ኋላ ተመልሰን በድጋሚ ህይወታችንን ከተመለከትነው እኮ ታሪካችን በራሱ ጊዜ ልብ ወለድ ሆኖ ይገኛል፡፡
አንድ ዓመት በዚህ ሁኔታ ውስጥ ቆየሁኝ፡፡ እህቴ የገዛችልኝ ሙሉ እሽግ የወረቀት ጥራዝ በመፃፍ አለቀ። ብዙ እፅፋለሁ ግን የነጠረው ውጤት ጥቂት ነው፡፡ ክረምት መውጫው ላይ አልሰር ያዘኝ፡፡ ጨጓራዬ ደማ፡፡ ደም አስታወከኝ … ራሴን ስቼ ሆስፒታል ገባሁኝ፡፡ ደም አዋጥተው ሰጡኝ፡፡ ያው ድኜ ወጣሁ፡፡ ምናልባት የሰጡኝ ደም እንደሆነ ባላውቅም … ከሆስፒታል ወጥቼ ሳገግም፣ ከመስከረም ፀሐይ ጋር አዲስ የምናብ አቅም በውስጤ ሲበራ ድንገት ይሰማኝ ጀመር፡፡
ከመስከረሙ ፀሐይ ጋር አንድ ቀደም ሲል ሰው ያስተዋወቀኝን ጋዜጠኛ በመንገድ ላይ ባጋጣሚ አገኘሁት፡፡ ቤቱ ወስዶ አብረን ቃምን፡፡ እንደኔው የሚፅፍ ሰው … እና ከፅሁፉ ጋር ለመሞት የቆረጠ አምሳያዬን ለመጀመሪያ ጊዜ አገኘሁኝ፡፡ ጋዜጠኛው ዘና ያለ ነው … በአላማና ግብ የተወጠረ አይደለም። ታላቅ ደራሲ በአንዴ ካልሆንኩ ብዬ፣ በጭንቀት አልሰር መያዝ የዋህነት መሆኑን ተገነዘብኩኝ፡፡ ሁሉም ነገር ቀስ በቀስ የሚመጣ ነው፡፡
በሦስት ወር ታላቅ ድርሰት ካልፃፍኩ ብሎ ነገር የለም፡፡ ጋዜጠኛው ቤት ሌሎች ሁለት ልጆች አይጠፉም፡፡ አንዱ ገጣሚ ነው፤ ሌላኛው … እንደ ሀያሲ፣ እንደ ባህታዊም ያደርገዋል፡፡ ለብቻ ከሚደረግ ትግል ይልቅ የማህበሩ ይቀላል፡፡ መናበብም ይኖራል። የባህሪይ ብቻ ሳይሆን የወረቀትም መናበብ፡፡ እስከዚያ ጊዜ ድረስ በእንግሊዝኛ እንጂ በአማርኛ ፅፌ አላውቅም፡፡
“አማርኛ ወንዝ የማያሻግር ቋንቋ ነው” ብለን ከቀድሞው ፈላስፋ (በኋላ ነጋዴ) ጓዴ ጋር እንፎክር ነበር፡፡ እንደ አዲስ እምነቴን ለማደስ፣ አማርኛን ማንበብ ያዝኩኝ፡፡ ንባቤ ለዘመናት ሳይሆን አቅሜን ምዘና ነበር፡፡ የአዳም ረታ “ማህሌት”ን … እና በፋሲል ይትባረክ የተተረጎመውን የዶስቶይቪስኪ “የስርቻው ስር መጣጥፍ”ን ከሌላው ለይቼ ወደድኳቸው፡፡ ሁለቱንም የማምለክ ፍላጎት ግን ባልታወቀ ምክኒያት አልነበረኝም፡፡
የመጀመሪያ የአማርኛ መጣጥፍ ፅፌ፣ ለማህበሩ አባላት አስነበብኳቸው፡፡ ገጣሚው መጣጥፉን መውደድ ብቻ ሳይሆን ከዚያ ላይ እየጠቀሰ፣ በወሬ መሀል እንደ ማስረጃ ሲያነሳሳው፣ ያ የድሮው ፍርሐቴ የልብ ልብ ተሰማው፡፡ ከዚያ በኋላ መጣጥፍ መፃፍ ላይ በረታሁኝ፡፡ መፃፍና ለእነዛ መሰሎቼ አስነብቤ ጭበጨባን ማግኘት እንጂ ሌላ ግብ ለጊዜው አልታየኝም፡፡
ለጋዜጣ ለምን አትሰጥም? የሚል ግፊት የመጣውም ከዚሁ ቡድን ነው፡፡ ጋዜጦች አጭር ልብ ወለድ እንደሚያስተናግዱና ‹‹አዲስ አድማስ›› ተብሎ የሚጠራ ጋዜጣ፣ የርቅቀት ጫፍ መሆኑ ሁሉም በጊዜው ይስማማበት ነበር፡፡ ከቡድኑ መሀል ባይሆንም አንድ ጓደኛቸው፣ ሳይንስ አምድ ላይ ስለ ‹‹አክሊሉ ለማ›› ጽፎ እንደተስተናገደለት፣ ልጁን እንደ ጀግና ክበው ነገሩኝ፡፡
አጭር ልብ ወለድ በአማርኛ ለመፃፍ ገና ሩቅ መሆኔ ይገባኛል፡፡ ጅማቴን ለማጠንከር ስል የእንግሊዝኛ ልብ ወለዶችን ወደ አማርኛ መተርጎም ጀመርኩኝ፡፡ ትርጉም ራሱን የቻለ ውበት እንዳለው የገባኝ፤ በተመስጦ ስተረጉም ውዬ፣ ከሀያ ገፅ በላይ ፅፌ እንቅልፍ የሚገላግለኝ ጊዜ ስለነበር ነው፡፡ በእጄ ብዙ ልብ ወለድ ቢኖሩኝም- በአልፍሬድ ሂችኮክ ብራድ ስር የሚታተሙ ‹ሚስትሪ ማጋዚን› ላይ የወጡ ብዙ የፍርሀት  ታሪኮችን ወደ አማርኛ ማዞር ያዝኩኝ፡፡
ለ“አዲስ አድማስ” ልብ ወለድ ከመስጠቴ በፊት በጋዜጣው ላይ የወጡትን አጭር ልብ ወለዶች  ደርድሬ በማንበብ ራሴን አዘጋጀሁ፡፡ የፀሐፊዎቹን ስም አልይዝም፡፡ ትኩረቴ የልብ ወለዱ አቅም ላይ ብቻ ነበር፡፡ ለአቅመ “አዲስ አድማስ” እስክደርስ… ተመሳሳይ ይዘት ያለው ‹‹ኔሽን›› የሚባል ጋዜጣ ትኩረቴ ውስጥ ገባ፡፡ “ኔሽን” ላይ ‹‹ሉቂያኖስ››  በሚል ስም የሚፅፈውን ልጅ የእይታ አዲስነት ማድነቅ ጀመርኩኝ፡፡ ልጅ በእውቀቱ ስዩም ስለመሆኑ በጊዜው ምንም መረጃ  አልነበረኝም፡፡
የተረጎምኩትን ልብ ወለድ በአዲስ ሉክ በጥንቃቄ ገልብጬ፣ ወደ ጋዜጣው የዝግጅት ክፍል ሄድኩኝ፡፡… “ማርቲን ኤደን” በሚል ርዕስ፣ ጃክ ለንደን ጻፈው ያልኩት ወጥ ልብወለድ ላይ ደራሲ ለመሆን አሳሩን የሚበላው ገፀ ባህርይ፤ ፅሁፉን ለጋዜጣ ሲያስገባና “rejection slip” ሲሰጠው ነው መፅሐፉ የሚተርከው፡፡ እኔም የማርቲን ኤደን እጣ ፈንታ ይገጥመኛል ብዬ ደምድሜ ነበር ፅሁፌን ያስገባሁት። መቶ ጊዜ ለመመላለስ ዝግጁ ነበርኩኝ፡፡
ግን የሰጠሁት የትርጉም አጭር ልብ ወለድ በተመሳሳይ ሳምንት ጋዜጣው ላይ ወጣ፡፡ ማመን አልቻልኩም፡፡ በውስጤ የነበረውን ኩራት የማጋራው ሰው  ናፈቀኝ፡፡ በአንድ ጊዜ ሁሉንም ሰው ማግኘት ፈለኩኝ፡፡ ገንዘብ ግን አልነበረኝም። ጋዜጣዬን ይዤ ተቀመጥኩኝ፡፡ እገልጠዋለሁ። አነበዋለሁ፡፡ ስሜ ከፅሁፉ በላይ አለ፡፡ ለልብ ወለዱ የካርቱን ስዕል ተስሎለታል፡፡ ትንግርት ሆነብኝ፡፡ በቀጣዩ ሳምንት የአጭር ልብ ወለድ እሩምታ በጋዜጣው ዝግጅት ክፍል ለቀቅሁኝ፡፡ ግን ያስገባሁት አልወጣም፡፡ ተስፋ አልቆረጥኩም፡፡ የማርቲን ኤደን ዕጣ ፈንታ በእኔ የመጀመሪያ ስኬት ተሽሯል፡፡
ምናልባት ወጥ ልብ ወለድ ይሆናል የሚፈልጉት በሚል መፃፍ ጀመርኩኝ፡፡ ግን መፃፍ ስጀምር… የልብ ወለዶቹ አቅጣጫ አዲስነት፣ በጋዜጣ ከማውጣት ስኬት በላይ ይማርከኝ ጀመር፡፡… የጥበብ ጓደኞቼም ሙከራዎቼን ክበው/ከምረው በራስ መተማመን አሳበጡኝ፡፡ በአንድ ሳምንት ውስጥ ሁለት አጭር ልብ ወለድና አንድ መጣጥፍ መፃፍ አለብኝ ብዬ ወሰንኩኝ፡፡ አንዳንዴ ግን ከውሳኔዬ በላይ የምጽፍበትም ጊዜ ነበር፡፡….
ይህ አመት ለእኔ ድምፄን ያገኘሁበት አመት ነው ብዬ ስለማስበው…. ትቶብኝ የሄደው ብርሀናማ ትዝታ ተራ ቦታ የሚሰጠው አይደለም፡፡ ግን ይኼ አመት እኔ የድርሰት ድምፄን ያገኘሁበት ነበር ብልም… በሀገሪቷ ታሪክ ግን አስገራሚ ቁጥር ያለው ህዝብ ድምፁን ለምርጫ ለመጀመሪያ ጊዜ ሰጥቶ የተነጠቀበት ተብሎ የሚታወስ ታሪካዊ አመት ነው። ዓመቱ 1997 ነበር፡፡  
የፖለቲካ ውዝግቡ ሳይረብሸኝ መሰረታዊ ብዬ የማስባቸውን የልብ ወለድ ንድፎች የፃፍኩበት ወቅት ነበር፡፡ 97 ለመላው ኢትዮጵያ ሌላ ትዝታ ቢኖረውም፤ ለእኔ ግን ‹‹የንፋስ ህልም እና ሌሎች የምናብ ታሪኮች›› የሚለውን ከ97 አምስት አመታት በኋላ ያሳተምኩትን መፅሐፍ ጥንስስ ያቦካሁበት ልዩ አመት ነበር፡፡
ታዲያ አሁን ይኼንን ታሪክ ለምን ልብ ወለድ አስመስዬ ፃፍኩት? ለብልሃቴ ብዬ ነው፡፡ ‹‹የንፋስ ህልም›› በድጋሚ ታትሞ ገበያ ላይ ለመውጣት ዝግጅቱ ጦፏል፡፡ ይሄን መረጃ ለናንተ ለውድ አንባብያን ለመጠቆም የዘየድኩት መላ ነው፡፡ መፅሐፉን ማንበብ ከመፅሐፉ ጀርባ ያለውን ታሪክ አይነግርም፡፡
(በፊልም The making of the film እንደሚሉት መሰለኝ) እኔ ግን ‹‹የንፋስ ህልም›› አፃፃፍን ከፅሁፉ ነጥሎ መደበቅ ንፉግነት ስለመሰለኝ እነሆ ብያለሁኝ። መጽሐፉ እስኪወጣም መዳረሻ ይሆናችኋለሁ፡፡

 መንግስት ተጠርጣሪዎች በመብዛታቸው አዳዲስ ፍርድ ቤቶችን እየገነባ ነው

       በቱርክ ከከሸፈው መፈንቅለ መንግስት ጋር በተያያዘ 32 ሺህ ሰዎችን ያሰረው የአገሪቱ መንግስት፣በቀጣይም ሌሎች ተጨማሪ ሰዎችን እንደሚያስር ማስታወቁን አሶሼትድ ፕሬስ ዘገበ፡፡
የአገሪቱ የፍትህ ሚኒስትር በኪር ቦዝዳግ ከኤንቲቪ የቴሌቪዥን ጣቢያ ጋር ያደረጉትን ቃለ መጠይቅ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ በሃምሌ ወር አጋማሽ ከተሞከረው መፈንቅለ መንግስት ጋር ንክኪ አላቸው በሚል የተጠረጠሩ 70 ሺህ ያህል ሰዎች ጉዳያቸው እየተጣራ እንደሚገኝ የተገለጸ ሲሆን፣ 32 ሺህ ያህሉ እንደታሰሩና በቀጣይም ሌሎች ተጨማሪ ሰዎች እንደሚታሰሩ ተነግሯል፡፡ ከመፈንቅለ መንግስቱ ጋር ንክኪ አላቸው በሚል የተጠረጠሩት ሰዎች ቁጥር ከፍተኛ ከመሆኑ ጋር በተያያዘ ምርመራውን በወቅቱ ለማጠናቀቅ አዳጋች በመሆኑ፣ የቱርክ መንግስት የተጠርጣሪዎችን ጉዳይ የሚመረምሩ አዳዲስ ፍርድ ቤቶችን እየገነባ እንደሚገኝ ሚኒስትሩ ማስታወቃቸውንም ዘገባው ገልጧል፡፡ 270 ሰዎችን ለህልፈተ ህይወት በዳረገውና ባለፈው ሃምሌ ወር አጋማሽ ላይ ተሞክሮ በከሸፈው የቱርክ መፈንቅለ መንግስት፣ ተሳትፎ አላቸው የተባሉ ከ50 ሺህ በላይ ሰዎች ከስራ ገበታቸው መባረራቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

 ከእስራኤል መስራች አባቶች አንዱ እንደሆኑ የሚነገርላቸውና አገሪቱን በፕሬዚዳንትነትና በጠቅላይ ሚኒስትርነት ያስተዳደሩት የኖቤል የሰላም ተሸላሚው ሺሞን ፔሬዝ ባደረባቸው ህመም በተወለዱ በ93 አመታቸው ባለፈው ረቡዕ ከዚህ አለም በሞት መለየታቸው ተዘግቧል፡፡
ከፍልስጤም ጋር የሰላም ድርድር እንዲደረግ ላበረከቱት አስተዋጽኦ እ.ኤ.አ በ1994 የኖቤል የሰላም ሽልማትን የተቀበሉት ፔሬዝ፣ ከሁለት ሳምንታት በፊት በልብ ህመም ተጠቅተው ቴል አቪቭ አቅራቢያ ወደሚገኝ ሆስፒታል የገቡት ፔሬዝ፣ በህክምና ሲረዱ ቆይተው ባለፈው ረቡዕ ማለዳ ማረፋቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታኒያሁ ባወጡት መግለጫ፣ በፔሬዝ ሞት የተሰማቸውን ጥልቅ ሃዘን ገልጸው፣ ፔሬዝ በእስራኤልና በአካባቢው ሰላም እንዲሰፍን እስከ እለተ ሞታቸው ያለመታከት የሰሩ ባለ ራዕይ መሪ ነበሩ ብለዋል፡፡  
የሽሞን ፔሬዝ ህልፈተ ህይወት ይፋ መደረጉን ተከትሎ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፣ ጆርጅ ደብሊው ቡሽ፣ ቢል ክሊንተን፣ ቭላድሚር ፑቲን፣ ቶኒ ብሌር፣ ፍራንኪዮስ ሆላንዴ እና ጀስቲን ትሬዱን ጨምሮ በርካታ የአለማችን አገራት የቀድሞና የወቅቱ መሪዎች የሃዘን መግለጫ ያወጡ ሲሆን፣ ፔሬዝ ሰላምን በማስፈን ረገድ ያበረከቱትን ጉልህ ሚና አድንቀዋል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ጸሃፊ ባንኪ ሙን በበኩላቸው፣ ሽሞን ፔሬዝ በእስራኤልና በመካከለኛው ምስራቅ አገራት ሰላም ለማስፈን ከፍተኛ ጥረት ያደረጉ መሪ መሆናቸውን በመግለጽ፣ የሁለትዮሽ መፍትሄን በማመንጨት የአገሪቱ ዜጎች ከፍልስጤማውያንና ከአካባቢው አገራት ጋር በሰላም እንዲኖሩ ለማስቻል የለፉ ታላቅ ሰው ነበሩ ሲሉ አሞግሰዋቸዋል፡፡
ሃማስ በአንጻሩ ረቡዕ ዕለት ባወጣው መግለጫ የፔሬዝን ህልፈተ ህይወት በደስታ እንደተቀበለው ገልጾ፣ ሰውዬው ወንጀለኛ መሆናቸውንና ፍልስጤማውያንም በግለሰቡ ሞት ጥልቅ ደስታ እንደሚሰማቸው ማስታወቁን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
እ.ኤ.አ በ1923 የተወለዱት ሽሞን ፔሬዝ፣ በ1959 ለመጀመሪያ ጊዜ ተመርጠው የእስራኤል ፓርላማ አባል መሆናቸውን ያስታወሰው የአጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘገባ፣ ከ1984 እስከ 1986 እንዲሁም ከ1995 እስከ 1996 ለሁለት ጊዜያት የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር፣ ከ2007 እስከ 2014 ደግሞ ፕሬዚዳንት በመሆን ማገልገላቸውንም አክሎ ገልጧል፡፡ የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ፣ የመከላከያና የፋይናንስ ሚኒስትር በመሆን ያገለገሉት የሽሞን ፔሪዝ የቀብር ስነስርዓት የአለማችን ታላላቅ መሪዎች በተገኙበት ትናንት በእየሩሳሌም ተፈጽሟል፡፡

  ባለፈው የሪዮ ኦሎምፒክ፣ የኬንያን ልኡካን ቡድን በመምራት ወደ ብራዚል ያቀኑት ስቴፈን አራፕ ሶይ፣ ለቡድኑ አባላት የውድድር ቆይታ ከተመደበው ገንዘብ 256 ሺህ ዶላር ዘርፈዋል በሚል ናይሮቢ በሚገኝ ፍርድ ቤት ክስ እንደተመሰረተባቸው አሶሼትድ ፕሬስ ዘገበ፡፡
የኦሎምፒክ ቡድን መሪው ወደ ብራዚል በተደረገው ጉዞ ለሚመለከታቸው የአገሪቱ የመንግስት አካላት ሳያስታውቁ ይዘውት የወጡት 234 ሺህ ዶላር የገባበት አልታወቀም፤ በተለያዩ አጋጣሚዎችም 22 ሺህ ዶላር የመንግስት ገንዘብ ዘርፈዋል የሚል ክስ እንደቀረበባቸው ዘገባው ጠቁሟል፡፡ ግለሰቡ ባለፈው ረቡዕ ናይሮቢ በሚገኘው ፍርድ ቤት ቀርበው የቀረበባቸውን ክስ ያደመጡ ሲሆን፣ የተጠቀሰውን ገንዘብ አልዘረፍኩም ሲሉ ክደው መከራከራቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ሌሎች ሁለት የኬንያ ኦሎምፒክ ቡድን ባለስልጣናትም ናይኪ ኩባንያ በስፖንሰርነት ለቡድኑ ያበረከተውን ትጥቅ ሰርቀዋል በሚል የቀረበባቸውን ክስ በእለቱ ክደው መከራከራቸውን አመልክቷል፡፡
የኬንያ የኦሎምፒክ ኮሚቴና የአትሌቲክስ ፌዴሬሽን ከፍተኛ ባለስልጣናት በሪዮ ኦሎምፒክ በሙስና እንደተጠረጠሩ ያስታወሰው ዘገባው፣ ባለፈው አመትም የአገሪቱ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት፣ ምክትል ፕሬዚዳንትና ገንዘብ ያዥ 700 ሺህ ዶላር ያህል በመዝረፋቸውና ሌሎች የሙስና ወንጀሎችን በመስራታቸው ከስራ ገበታቸው እንደተሰናበቱና ምርመራ እንደተደረገባቸው ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

   የጀርመኑ ቮልስዋገን እና የጃፓኑ ቶዮታ እየተቀያየሩ ሲመሩት በዘለቁት የዘንድሮው የአለማችን ታላላቅ የመኪና አምራች ኩባንያዎች ውድድር ከሰሞኑ ቶዮታ መሪነቱን መያዙን ፎርብስ መጽሄት ዘገበ፡፡
ቶዮታ በዘንድሮው የፈረንጆች አመት ያለፉት ስምንት ወራት ብቻ 6.69 ሚሊዮን መኪኖችን አምርቶ ለአለም ገበያ በማቅረብ መሪነቱን መያዙን የጠቆመው ዘገባው፣ በተመሳሳይ ጊዜ 6.69 ሚሊዮን መኪኖችን ለገበያ ያቀረበው የጀርመኑ ቮልስዋገን በሁለተኛነት እንደሚከተል ገልጧል፡፡
የሶስተኛነት ደረጃን ይዞ የሚገኘው የአሜሪካው ጄኔራል ሞተርስ ኩባንያ በ2016 የመጀመሪያዎቹ ስምንት ወራት 6.3 ሚሊዮን መኪኖችን አምርቶ ለአለም ገበያ ማቅረቡ ተነግሯል፡፡ ቶዮታ እና ቮልስዋገን እያንዳንዳቸው በየአመቱ 10 ሚሊዮን መኪኖችን አምርተው ለገበያ የሚያቀርቡበት አቅም ላይ እንደደረሱ ማስታወቃቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ በሁለቱ ኩባንያዎች መካከል ያለው ፉክክር መቀጠሉንና በቀሪዎቹ ወራት የመሪነቱን ስፍራ ይዞ የሚቀጥለውንና የአመቱ የዓለማችን ትልቁ የመኪና አምራች የሚሆነውን ኩባንያ ለመገመት አዳጋች እንደሆነ ገልጧል፡፡

 “ህገ-መንግስቱን በማክበር ለተተኪው ስልጣን የምለቅበት ጊዜ ላይ ነኝ”

       ላለፉት 12 አመታት ሲሼልስን የመሩት ፕሬዚዳንት ጄምስ ሚሼል ከወራት በፊት የተደረገው የአገሪቱ ህገ መንግስታዊ ማሻሻያ የስልጣን ዘመናቸው ማብቃቱን የሚያረጋግጥ ከመሆኑ ጋር በተያያዘ፣ በሁለት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ ስልጣን እንደሚለቁና ለተተኪው እንደሚያስረክቡ ማስታወቃቸውን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘገበ፡፡
የ72 አመቱ ፕሬዚዳንት ጄምስ ሚሼል ባለፈው ማክሰኞ በአገሪቱ ብሄራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያ ባደረጉት ንግግር፣ ለ12 አመታት አገሪቱን አስተዳድሬያለሁ፤ አሁን ህገ-መንግስቱን በማክበር ስልጣኔን ለተተኪው መሪ የማስረክብበት ጊዜ ነው፤ አዲሱ መሪ ሲሼልስን ወደቀጣዩ የልማት ምዕራፍ ያሸጋግራታል ብዬ አምናለሁ ሲሉ መግለጻቸውን ዘገባው አስታውቋል፡፡ ከዚህ በፊት መምህር ሆነው ያገለገሉት ፕሬዚዳንቱ፤በሚያዝያ ወር 2004 በምክትል ፕሬዚዳንትነት ወደ ስልጣን መምጣታቸውንና ከ2014 እስካሁን በፕሬዚዳንትነት እየሰሩ እንደሚገኙ የጠቆመው ዘገባው፣ ባለፈው ታህሳስ ወር ላይ በተደረገው ምርጫ አሸንፈው ለሶስተኛ የስልጣን ዘመን አገሪቱን መምራት መቀጠላቸውን ገልጧል፡፡
ባለፈው ሚያዝያ ወር ላይ የአገሪቱ ብሄራዊ ምክር ቤት የፕሬዚዳንትና የምክትል ፕሬዚዳንትን የስልጣን ዘመን ሁለት ዙር ብቻ እንዲሆን መወሰኑ፣ ባለፈው አመት ሁለተኛ የስልጣን ዘመናቸውን የጨረሱትን ፕሬዚዳንቱን ስልጣናቸውን እንዲለቁ መነሻ እንደሆናቸውም ዘገባው አስታውቋል፡፡ ፕሬዚዳንቱን በመተካት አገሪቱን የመምራት ስልጣኑን የሚረከቡት፣ በአሁኑ ወቅት የሲሼልስ ምክትል ፕሬዚዳንት የሆኑት የ54 አመቱ ዳኒ ፋኦሬ እንደሚሆኑም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

     በአሜሪካ 80 ከመቶ የጫማ ፍላጎት የሚያሟላው የጫማ አከፋፋዮችና ቸርቻሪዎች ማኅበር (ኤፍ ዲ አር ኤ) በኢትዮጵያ የሥራ ጉብኝት ያደረገ ሲሆን ከትናንት በስቲያ በኢሲኤ አዳራሽ በቆዳ ዘርፍ ከሚመለከታቸው ኃላፊዎች ጋር ውይይት አካሂዷል፡፡
ኤፍዲአርኤ የጫማ ምርቶችን የሚገዛው ከምስራቀው ኤዥያ አገሮች ከካምቦዲያ፣ በርማ፣ ላኦስ፣ … ሲሆን ወደ ኢትዮጵያ የመጣው የሜድ ኢን ኢትዮጵያ ኩባንያ ባለቤት ወ/ሮ ቤተልሄም ጥላሁንና ኢንተርፕራዝ ፓርትነርስ ባደረጉት ያላሰለሰ ጥረት መሆኑን የኢንተርፕራይዝ ፓርትነርስ የኮሙኒኬሽን አማካሪ አቶ ዳዊት ከተማ ገልጸዋል፡፡
175 አባላት ያሉት ማኅበሩ ባለፈው ማክሰኞ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ጣቢያ ሲደርስ በውጭ ጉዳይ ሚ/ር አቀባበል የተደረገለት ሲሆን፣ 11 የታወቁ ብራንድ ያላቸው አከፋፋዮችና ቸርቻሪዎች ከፍተኛ የስራ አመራሮች ከቡድኑ ጋር መምጣታቸው ታውቋል፡፡ ቡድኑ ወደ ኢትዮጵያ የመጣው በአገሪቱ ያለውን የጫማ ሁኔታና ከኢትዮጵያ ጫማ ቢገዛ ምን ጥቅም እንደሚያገኝ ለማጥናት ሲሆን ባለፈው ረቡዕ የቆዳ አምራቾችን፣ የቆዳ ማልፊያ ፋብሪካዎችን፣ የጫማ ፋብሪካዎችን፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድን የጭነት ተርሚናል መጎብኘቱ ታውቋል፡፡
በጉብኝታቸው ወቅት ባዩት ነገር፣ በተደረገላቸው አቀባበልና መስተንግዶ መደሰታቸውን የገለጹት የኤፍ ዲ አር ኤ የመንግስትና የተቆጣሪ ጉዳዮች ዳይሬክተር ሚ/ር ቶማስ ክሮኬት ባለፈው ዓመት አሜሪካ 2.4 ቢሊዮን ጥንድ ጫማዎች ከውጭ መግዛቷን ተናግረዋል፡፡
አሜሪካኖቹ የጫማ ነጋዴዎች ኢትዮጵያን የወደዱበትን ምክንያት አቶ ዳዊት ሲገልጹ ወደ አሜሪካ ጫማ ሲገባ ትልቁ ወጪ ቀረጥ ነው፡፡ ኢትዮጵያ የአጉዋ አባል ስለሆነች ምንም ቀረጥ ሳትከፍል ታስገባለች፡፡ በከፊልና በሙሉ የሰለጠነ የሰው ኃይል ስላል ተወዳዳሪ የሆነ የጉልበት ዋጋ በኢትዮጵያ ስላለና በኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ዋጋ እጅግ በጣም ርካሽ በመሆኑ ነው ብለዋል፡፡ ኢንተርፕራዙ ከአንድ ወር በፊት በሀዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክ ያለውን የሰለጠነ የሰው ኃይል እጥረት ለመቅረፍ 60 ሺህ ሰዎች ለማሰልጠን መፈራረሙን ጠቅሰው ወደ ጫማ ኢንዱስትሪ የሚገቡ የአሜሪካ ኩባንያዎች ካሉ፣ ሊገጥማቸው የሚችለውን የሰው ኃይል እጥረት ለመቅረፍ ኢንተርፕራይዙ ዝግጁ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡
የኢትዮጵያ ቆዳ ኢንዱትሪ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሻሻለ ጥሬ ቆዳ መላክ አቁሞ እሴት እየጨመረ ያለቀለት ጫማ፣ ጓንት፣ ቀበቶ፣ የቆዳ አልባሳት፣ … ወደ ውጭ እየላከ መሆኑን የጠቀሱት አቶ ዳዊት፣ በኤፍ ዲ አር ኤ በኩል ወደ አሜሪካ ገበያ መግባት በጣም ትልቅ ዕድል ነው፡፡ ስለዚህ ሁኔታዎችን የበለጠ ማመቻቸትና ጠንክረን መስራት ይጠበቅብናል ብለዋል፡፡