Administrator

Administrator

Sunday, 25 December 2016 00:00

አስገራሚ እውነታዎች!!!

· በቀን ለ24 ሰዓት እየቆጠራችሁ፣1 ትሪሊዮን ላይ ለመድረስ፣
 • 31ሺ 688 ዓመት ይፈጅባችኋል፡፡
· የኤሌክትሪክ ወንበር የተፈለሰፈው በአንድ የጥርስ ሀኪም ነው፡፡
· የዶሮ ረዥሙ የተመዘገበ የአየር ላይ በረራ 13 ሰከንድ ነው፡፡
· የጥንት ግብፃውያን ከድንጋይ በተሰራ ትራስ ላይ ይተኙ ነበር፡፡
· እስከ 1976 ዓ.ም (እኤአ) በአሜሪካ ፍራንክሊን በሚል የሚጠራ ግዛት ነበር፡፡
• ዛሬ ያ ግዛት ቴኒዝ በመባል ይታወቃል፡፡
· በዓመት ከ10 ሺ በላይ አዕዋፋት ከመስተዋት መስኮቶች ጋር በመጋጨት ይሞታሉ፡፡
· በምድር ላይ ከአንድ ሚሊዮን በላይ የእንስሳት ዝርያዎች አሉ፡፡
· ከአራት አሜሪካውያን አንዱ በቴሌቪዥን መስኮት ታይቷል፡፡
· አምፑል ፈልሳፊው ቶማስ ኤዲሰን ጨለማን ይፈራ ነበር፡፡
· ሰውነታችን በሰከንድ 15 ሚሊዮን ቀይ የደም ሴሎችን እየፈጠረ ይገድላል፡፡
· ማር አይበላሽም፡፡ 3ሺ ዓመት ያስቆጠረ ማር ለምግብነት ይውላል፡፡

    ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ንሥርና አንዲት ቀበሮ እጅግ የሚዋደዱ ጓደኞች ይሆናሉ፡፡ አንዳችን ላንዳችን የምናስብ፣ በቅርብ የምንተጋገዝ ወዳጆች መሆን አለብን ተባብለው በአንድ ዛፍ ዙሪያ መኖር ይጀምራሉ፡፡ እርስ በርሳቸው በቅርብ በተያዩ ቁጥር የበለጠ ጓደኛሞች እንሆናለን ብለው አሰቡ፡፡
ንሥር፤
‹‹አደራ ቀበሮ፤ እኔ በሌለሁ ጊዜ ልጆቼን ላንቺ ነው ጥዬልሽ የምሄደው፡፡ አንቺም ራቅ ያለ ቦታ የመሄድ አጋጣሚ ቢመጣብሽ ላንቺ ልጆች እኔ አለሁልሽ›› አለች፡፡
ቀበሮም፤
‹‹አይዞሽ፤ እኔም አንቺ ምንም ነገር አጋጥሞሽ ልጆችሽን መጠበቅ ቢያስፈልግ ምንጊዜም ከጎንሽ ነኝ፡፡›› አለቻት፡፡
ስምምነታቸው እንደተጠበቀ ሆኖ፤ ንሥር በረዥሙ ዛፍ ጫፍ ላይ ጎጆዋን ሠራች፡፡ በአንፃሩ ቀበሮ ከዛፉ ግርጌ ችፍግ ባለው ቁጥቋጦ ማህል ሠፈረች፡፡ እዚያም ግልገሎችን ፈለፈለች፡፡ ብዙ ጊዜ ከንሥር ጋር በጎረቤትነት አብረው ኖሩ፡፡
አንድ ቀን፤ ቀበሮ ለግልገሎቿ ምግብ ፍለጋ ራቅ ወዳለ ቦታ ሄደች፡፡
ይህን ያስተዋለችው ንሥር፤ ወደ ዛፉ ግርጌ በርራ ወርዳ፡- እሷም ለጫጩቶቿና ለራሷ ምግብ ያሻታልና፤ የቀበሮን ግልገሎች አንጠልጥላ ወደ ዛፉ ጫፍ ወጣች፡፡
ቀበሮ ተመልሳ የሆነውን ሁሉ አየች! ሆኖም ዛፉ ጫፍ ላይ መውጣት እንደማትችል ስትገነዘብና በምንም መንገድ መበቀል እንደማይሆንላት ስታስብ ከልቧ አዝና ተቀመጠች፡፡ በየጊዜው ቀና ብላ መራገሟን ግን ቀጠለች፡፡
ንሥርም፤
‹‹እመት ቀበሮ፤ ምን ሆነሽ ነው የእርግማን መዓት የምታወርጂው?›› ስትል ጠየቀቻት። እንዳልገባት ሆና ለነገሩ እንግዳ ለመምሰል ነው፡፡
ቀበሮም፤
‹‹አይዞሽ ምንም ካላረግሽ እርግማኔ ሊያስፈራሽ አይገባም፡፡ እኔ እማምነው ግን አንድ ነገር ብቻ ነው፡፡››
ንሥር፤
‹‹ምን?›› ብላ በችኮላ ጠየቀች፡፡
‹‹አለመታመንን የሚያጠብቅ ወንጀለኛ፤ ከሰው ልጅ ቅጣት ሊያመልጥ ይችላል፡፡ የአምላክን ቅጣት ግን ፈፅሞ ለማምለጥ አይችለም!›› አለቻት፡፡
እመት ቀበሮ ገና ይሄን ብላ ከመጨረሷ፤ የሆኑ ሰዎች አንዲት ፍየል ወደ ዛፉ አቅራቢያ እየነዱ መጡ፡፡ ፍየሏን በማረድ ለመስዋዕትነት ሊያቀርቡ ነው ዓላማቸው፡፡ አረዷትና ሥጋዋን መጥበስ ጀመሩ፡፡ ንሥር ዛፍ ላይ ሆና የሚሆነውን ስታይ ቆይታ፣ ቁልቁል በርራ አንዱን ሙዳ ከነእሳቱ መንትፋ ወደ ጫጩቶቿ በርራ ገባች፡፡ ይሄኔ አንድ ያልታሰበ ነገር ተከሰተ፡፡ ከባድ አውሎ ንፋስ ተነሳ፡፡ ከሳር የተሰራው የንስሯና የቤተሰቧ ጎጆ በእሳት ተያያዘ፡፡ የንስሯ ትናንሽ ጫጩቶች ግማሽ በግማሽ በእሳት ተጠብሰው፣ ከዛፉ ላይ ወድቀው ቀበሮዋ ፊት አረፉ፡፡ እመት ቀበሮም፤ ንስሯ ዐይኗ እያየ፤ ተጠብሰው የመጡላትን ጫጩቶች ቅርጥፍ አድርጋ በላቻቸው!!
*         *       *
በመተማመን ላይ የተመሰረተን የቆየ ወዳጅነት ማፍረስ ዋጋ ያስከፍላል፡፡ ከሰው ባይገኝ ከመለኮት በቀሉ ተግባራዊ ይሆናል፡፡ የሰው በልቶ አያድሩም ተኝቶ የሚለው ተረት የዋዛ አይደለም። ለምናደርገው ነገር ሁሉ ምክንያታዊ መሆን ብቻ ሳይሆን ቀና ልቦና ልንጨምርበት ይገባል፡፡ ምክንያቱም የምንፈጥረው ሰበብ ምንም ዓይት አመክኖአዊ ስሌት ይኑረውና ያሳምን፤ ውስጡ ተንኮል ሊኖርበት ይችላልና ነው፡፡ ተንኮል ያለበት ነገር ቢያንስ ውሎ አድሮ ህሊናን ይወጋል፡፡ ቃልን አለማክበር የሀገራችን አባዜ ሆኖ ቆይቷል፡፡ አብዛኞቹ ጥያቄዎቻችን እምንመልሰው ለጊዜው ከውጥረት ለመገላገል ከሆነ፣ ስር የሰደደው ችግር ሳይነቀል ይቀራል። መፍትሄአችን ዋናው መንገድ ሲበላሽ መተንፈሻ ተብሎ እንደሚሰራው መጋቢ መንገድ ብቻ ሊሆን አይገባውም። ምነው ቢሉ፤ መተንፈሻ ብለን የሰራነው መንገድ ዋና ሆኖ ሊቀር ይችላልና! ከዚያ ወዲያ አውራ ጎዳናውን እንረሳዋለን፡፡
የዚህ አይነቱ አሰራር በየቦታው ሲከሰትና ሲጠራቀም አገር - ሙሉ የመንገድ ችግር ያጥለቀልቀናል፡፡ ስለዚህ የዋናና የማስተንፈሻ መፍትሄዎቻችንን ባህሪ መመርመር ትልቅ ቁም ነገር መሆኑን እንገንዘብ፡፡
ችግሮቻችንን ለማስወገድ ጥረትና ትግል የማስፈለጉን ያህል፣ ውስጣዊ ዲሞክራሲን ያለ አንዳች ሽንገላና ይስሙላ መገንባት አማራጭ የለውም፡፡ አለበለዚያ ዋጋ ያስከፍለናል፡፡ በማናቸውም ጠንካራ የትግል እንቅስቃሴ ባለበት ቦታ ሁሉ ሁለት መሰረታዊ አካሄዶች ተጠቃሽ ናቸው። እነዚህም ውስጠ ፓርቲ ትግልና በፓርቲዎች መካከል የሚደረጉ ትግሎች ናቸው፡፡ እነዚህን በድርጅቶችም አናፅሮ ማየት አይከብድም፡፡ (ፈረንጆቹ፣ በተለይም የጥንት አበው ፖለቲከኞች፤ Inter - party and Intra - party struggle የሚሉት መሆኑ ነው፡፡)
ስም ተግባር አይሆንም፡፡ ራስን ማየትን የመሰለ ነገር የለም፡፡ it is all nomenclature, but it is practice that matters - ከስሙ ምን አለህ፤ ዋናው ተግባር ነው እንደማለት ነው፡፡ “ግምገማ”፣ “ውይይት”፣ “ተሀድሶ”፣ “ጥልቅ - ተሃድሶ” … ወዘተ ስሞችና የስም ማሻሻያዎች ብቻ እንዳይሆኑ ተግባራቸውን እንፈትሽ! ከአንደበት ወጥተን ድርጊትን እናድምቅ፡፡ የሀገራችን ፍቱን ጉዳይ የሀብትና የስልጣን ፍትሃዊ ድልድል ነው! መፍትሄዎችን ለነገ አንበል (Procrastination):: የእኔ ጥፋት አይደለም፤ የውጪ ኃይሎች ነው አንበል (No externalization) በሌሎች አናሳብ (No blame - shifting) በአዲሱ የወጣቱ ትውልድ እንመን (The new is invincible) የመንግስት ባለስልጣናት ንግድ  ውስጥ እንዳይገቡ እንታገል (fight bureaucratic capitalism)፡፡ የሁሉም መጠቅለያ ግን ህዝብን የሚያሳትፍ ዲሞክራሲን ዕውን ማድረግ ነው!! አሮጌውን ሥርዓት መታገል ግድ ነው፡፡ አዲሱ እንዲፈልቅ መሳል ተገቢ ነው፡፡ (Fight conservatism Accept the invincibility of the new) ዋናው አገር የሚያድን ይሄ ነው፡፡ ‹‹ሁለት ባላ ትከል፣ አንዱ ቢሰበር ባንዱ ተንጠልጠል›› ዛሬ አያዋጣም፡፡ ያ ከሆነ፤ ‹‹አሮጊት ሚስቱ ጥቁር ፀጉን ስትነቅል፣ ወጣት ሚስቱ ነጭ ፀጉሩን ስትነቅል፤ መላጣ ሆነና አረፈው!›› የሚለው ተረት ዕውን ይሆናል፡፡ በወጉ እንጓዝ! አገር በወጉ እንድትለወጥ መላ እንምንታ!

Sunday, 25 December 2016 00:00

ስታድዬሞቻችን ያዋጣሉ?!

 • የመሀመድ ሁሴን አሊ አላሙዲ ስታድዬም ጥር 6 በወልዲያ ከተማ ይመረቃል፡፡
                  • በኢትዮጵያና በኢትዮጵያውያን ስታድዬሞች ይገነባሉ፡፡ ሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ

       በሳምንቱ አጋማሽ ላይ በሸራተን አዲስ የሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ቺፍ ኤክዚዮከቲቭ አፊሰር ዶክተር አረጋ ይርዳው ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተው ነበር፡፡ መግለጫው በክቡር ዶክተር ሼህ መሀመድ ሁሴን አሊ አላሙዲ የገንዘብ ወጭ ግንባታው ተጠናቅቆ፣ በጥር 6 በወልዲያ ከተማ የሚመረቀውን አዲስ ስታድዬም ይመለከታል፡፡ መሀመድ ሁሴን አሊ አላሙዲ ስታድየም እና የስፖርት ማዕከል ተብሎ ተሰይሟል፡፡ ዶ/ር አረጋ ይርዳው እንደገለፁት ስታድየሙ ስያሜውን ያገኘው በከተማው ህዝብ ውሳኔ ነው፡፡  ስታድዬሙ በጥር 6 /2009 ዓ.ም በይፋ ከመመረቁ በፊት በአጠቃላይ 567 ሚሊየን ብር ወጭ ሆኖበታል፡፡ በወጭው ከፍተኛነት በኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ የሚጠቀስ ይሆናል። ‹‹ስታድዬሙ የኢትዮጵያ ህዝብ ሃብት  ነው›› ያሉት ዶ/ር አረጋ፤ ‹‹ለዞኑ፣ እና ለከተማው መስተዳድር በኃላፊነት የሚሰጥ፣ የህዝብ ንብረት  ይሆናል›› ብለዋል፡፡  ወልዲያ ከአዲስ አበባ 520 ኪ.ሜ ርቀት ላይ ትገኛለች፡፡  በተራራ የተከበበች ውብና የደጎች ከተማ ይሏታል፡፡  የወልዲያ ህዝብ ለስፖርት ያለው ፍቅር የእህል ውሃ ያህል ነው፡፡ ስታድዬሙ ሊሠራ የቻለው በከተማው ህዝብ በተቆሰቀሰ ፍላጎት ነበር። በመጀመርያ በተደረገው እንቅስቃሴ የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት ተድርጎ እስከ 30 ሚሊዮን ብር  ተሰባስቧል፡፡ ይህ ገንዘብ በቂ አልነበረም፡፡ እናም በሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ አማካኝነት በሸራተን አዲስ ሌላ የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ተዘጋጀ፡፡  ‹‹የወልዲያ ልጆች ስታድዬሙን እኔ እገነባለሁ። ለዶ/ር አረጋ ደግሞ ኃላፊነቱን ሰጥቸዋለሁ፡፡›› በማለት ሼህ መሀመድ 100 በመቶ ወጭውን በመሸፈን እንደሚያሰሩ ቃል ገቡ፡፡ ከዚያም የሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ፕሮጀክቱን የመነሻ ዲዛይኑን በመቀየር በዕጥፍ ዋጋ በፊፋ መስፈርቶች የተቀረፀ ዲዛይን  በድጋሚ አሠራ፡፡
ኦርጋኒኩ፤ መሃመድ ሁሴን አሊ አላሙዲ ስታድዬም
የመሀመድ ሁሴን አሊ አላሙዲ ስታድየም በወልዲያ ከተማ መቻሬ ሜዳ በተባለው ቦታ 177 ሺ ካ.ሜ  ላይ ተቀምጧል፡፡ ከባህር ወለል በላይ 2000 ሜት ከፍታ ላይ የተገነባው ስታድዬሙ በዘመኑ ቴክኖሎጂ የታነፀ ሲሆን ከበጋ እስከ ክረምት ውድድሮችን ማስተናገድ ይችላል። 25115 ወንበሮች ላይ ተመልካቾች የሚይዝ ሲሆን ሙሉ ለሙሉ የተሰሩት በአገር ውስጥ ነው፡፡  በኢትዮጵያ ዙሪያ ገጠም የሆነ ጥላ ፎቅ የተሰራለት የመጀመርያው ስታድዬምም ሆኗል፡፡ በሚያስፈልግ መጠን ብርሃን ሙቀት የሚሰጥና የሚቀንስ  ነው፡፡  በዙርያው ከ156 በላይ ፓውዛ መብራቶች ተገጥመውበታል፡፡ የፊፋን መስፈርት ሙሉ ለሙሉ ያሟላ ነው፡፡ የመሮጫ ትራክም ያለው ሲሆን በዘመናዊ ደረጃ የተዘጋጀው ይህ የአትሌቲክስ ትራክ በመሙ እስከ 8 አትሌቶችን በአንድ የልምምድ መርሃ ግብር ሊያስተናግድ የሚችል ነው፡፡ ዘመናዊ ሜዳ በአንድ ጊዜ አራት ቡድኖች ያስተናግዳል፡፡ ጨዋታዎች በተከታታይ ሊደረጉበት ይችላሉ፡፡ አራት የመልበሻ ክፍሎች እና ሁለት የማሟሟቂያ ሜዳዎች ተሰርተውለታል፡፡ በተጨማሪ ልዩነት የሜዳው ሣር ነው፡፡ ከው ዘርያ ጋር የተዳቀለ የሳር ተከላ ተደርጎለታል። ከሣሩ ስር ባንቧዎች ተቀብረዋል፡፡ ውሃ የሚቋጥር ሜዳ አይሆንም፡፡ በስታዲየሙ ውስጠኛ ክፍል ሁለት ግዙፍ ስክሪኖች ተገጥመዋል፡፡ ሁለት የልዩ እንግዶች (ቪአይፒ) ቦታዎች ተዘጋጅተውለታል፡፡ አንደኛው በመስታውት የተከለለና ለደህንነት አስተማማኝ ሲሆን ሌላኛው ደግሞ መስታውት የሌለው የቪአይፒ መቀመጫዎች ስፍራ ነው፡፡8 ሳውንድ ፕሩፍ ስቱድዮች ያሉት  ሚዲያ ትሪቢዮን አለው። በውስጡ ከ300 በላይ መኪኖች ያቆማል፡፡ የመብረቅ መከላከያ ተገጥሞለታል፡፡  10 በሮች አሉት፡፡ 7 አምቡላንስ ያስገባሉ የአካባቢውን ባህል፣ አኗኗር ታሪክ ለመግለፅ እንዲያመች በሮቹ ስም ተሰጥቶቸዋል፡፡ ለምሳሌ ዳና፣ ላሊበላ…  እንደማዕከልም የመቀጠል ተጨማሪ ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ ሌሎች መሰረተ ልማቶች ስላሟላ ነው።  በውጭኛው ስታድየም ክፍል የዋና ገንዳ፣ የቅርጫት ኳስ፣ መረብ ኳስ፣ እጅ ኳስ እና የሜዳ ቴኒስ ሜዳዎች እንዲሁም ለ34 ሰዎች የሚሆን የእንግዳ ማረፍያ አካቷል፡፡ በዙርያው ከመቶ በላይ የንግድ ሱቆች የተዘጋጀለትም ነው፡፡ ስታድየም የሄሊኮፕተር ማረፍያ፣ በቂ የመኪና ማቆምያ እና ውብ አረንጓዴ ቦታዎች አሟልቷል፡፡ በ2009 ዓም ፕሪሚዬር ሊግን የተቀላቀለው ወልድያ ስፖርት ክለብ በዚሁ ዘመናዊ ስታድየም የሚጫወት ሲሆን ከባህርዳር ስታድዬም ቀጥሎ በክልሉ ሁለተኛው ስታድዬም ሆኖ ይመዘገባል፡፡የወልዲያ ስፖርት ክለብ በሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ይደገፋል፡፡ ስታድዬሙ ከማለቁ በፊት በመልካ ቆሬ ስታድዬም ይጫወት ነበር፡፡ ወደ ፕሪሜርሊጉ ማለፉን ተከትሎም በሚድሮክ ዘርፈ ብዙ ድጋፍ እየተሰጠ ነው፡፡  የመሀመድ ሁሴን አሊ አላሙዲ ስታድዬም በጥር 6 ተመርቆ ስራውን ከጀመረ በኋላ ክለቡ ሜዳው አድርጎ ይጫወትበታል፡፡ ሚድሮክ ቴክኖሎጂ የክለቡን ሎጎ አሰርቷል፡፡ የስፖርት ትጥቅ፣ የመጓጓዣ አውቶብስ  ድጋፎች ከማረጉም በላይ በአዲስ አበባ የተጨዋቾች ካምፕ አዘጋጅቶ አደራጅቶታል፡፡
በጋዜጣዊ መግለጫ ላይ የመሐመድ ሁሴን አሊ አላሙዲ ስታድዬም ኦርጋኒክ ነው በማለት ዶ/ር አረጋ ደጋግመው ይናገሩ ነበር፡፡ ስታድዬሙ በስፖርት መሠረት ልማት ተምሳሌት የሚሆንበት ብዙ ውጤቶች ማስመዝገቡን ሲያብራሩ እንጅ ኦርጋኒክ ያሉት ያለምክንያት አልነበረም። በኢትዮጵያ አቅም የተገነባ ስለሆነ ነው፡፡ ከ95 በመቶ በላይ በስታድዬሙ ግንባታ ላይ የሠሩት መሃንዲሶች እና ሌሎች ባለሙያዎች፣ 90 በመቶ  የግንባታ ቴክኖሎጂዎችና ሌሎች ቁሳቁሶች በአገር ውስጥ በመመረታቸው ነበር፡፡ ለኢትዮጵያውያን በኢትዮጵያ የተሰራ በመሆኑ ስታድዬሙ ኦርጋኒክ ነው የሚሉት ዶክተር አረጋ ይርዳው  የሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ አባል ከሆኑ 25 ኩባንያዎች፤ በተለይም 10 ያህሉ በአጋርነት ተሰልፈው ፕሮጀክቱን በ4 ዓመታት ውስጥ በማከናወን ስታድዬሙ  ሙሉ ለሙሉ ተገንብቶ ሊያበቃ መቻሉን ገልፀዋል፡፡ ሼህ አላሙዲ ገንዘብ መድበዋል። ሁዳ ሪል ስቴት ዋናው የኮንስትራክሽኑ ስራ ተቋራጭ ነበር።  ኩባንያዎቹ በየዘርፉ የኮንትራት ስራ እየተሰጣቸው ገንብተውታል፡፡ የስራ ልማዳቸውን አሳድገውታል፡፡፡ የሙያተኞች ብቃት ተሻሽሏል፡፡ በአገር በቀል መሀንዲሶች ለስታድዬም እና ሌሎች የስፖርት መሰረተ ልማት ግንባታዎች ኢትዮጵያዊ አቅም ተፈጥሯል፡፡ ከወልዲያው ስታድዬም ግንባታ በኋላ ሚድሮክ ሌላ ግንባታ ኮንትራት ለማግኘት ፈልጎ አልተሳካለትም፡፡ ወደፊት ዕድሎች እንደሚፈጥሩ እምነት ግን አለ በስታዲዬም ግንባታ የዕውቀት ሽግግር ለማድረግ ፍላጎት አለን ብለዋል፡፡ ቺፍ ኤክሲኪዩቲቭ ኦፊሰሩ በኢትዮጵያና በኢትዮጵያውያን 50 እና 60 ሺ ተመልካች የሚይዙ ስታዬሞች መገንባት ይቻላል፤ ያስፈልጋልም ብለዋል፡፡
በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ከአዲስ አድማስ ለሚድሮክ ቴክኖሎጁ ግሩፕ ኤክስኪዩቲቭ  ኦፊሰር ዶ/ር አረጋ ይርዳው  የቀረቡ 3 ጥያቄዎች የሚከተሉት ነበሩ፡፡  ስታዲየሞች በብዛት ያስፈልጋሉ ወይ፣ ከሆነስ በየትኞቹ ከተሞችና ክልሎች የሚለው የመጀመርያ ነበር..፡፡  ዶ/ር አረጋ ምላሽ ሲሰጡ “መቼ ነካውና፡፡ አገሪቷ ውስጥ ምን ስታድዬም አለና፡፡ 100 ሚሊዮን ህዝብ ያለባት - 70 በመቶ ወጣት ለሆነበት አገር። ስታድዬም ብዙ ነው የሚያስፈልገን፣ ለጊዜው ተጫዋች ላይኖሩ ይችላሉ፡፡ በየምሽቱ እንደምናየው የማንቸስተር፣ የአርሰናል ስታድዬም አይሟላ ይሆናል፡፡ የአቅም ጉዳይ፣ የስፖርቱ እድገት፣ የተመልካችነት ባህል መጨመር እነዚህን ሁሉ የሚጀምር ነው፡፡ እስከመቼ ድረስ ነው፡፡ በቴሌቪዥን ብቻ የሌላውን አገር ጨዋታ እያየን የምንዘልቀው።  ስታድዬሞች የት ይገንቡ፤ በሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጥናት ተደርጎበታል፡፡  በእያንዳንዱ ክልልና ከተማ ልክ ዩኒቨርሲቲዎች እንዳሉ ስታዲዬሞች መኖር አለባቸው።››
የወልዲያ ከተማ አየር ሁኔታን በተመለከተ እና መቼ ዓለም አቀፍ ጨዋታ ሊያስተናግድ ይችላል የሚሉት ሌሎቹ ከአዲስ አድማስ የቀረቡ  ጥያቄዎች ናቸው፡፡ ዶ/ር አረጋ በመጀመርያ ምላሻቸው ስለአየር ሁኔታው ‹‹የኢትዮጵያ አየር ለማንም ስፖርተኛ መጠናት የሚያስፈልገው አይደለም።  ከወደ በረሃ ለሚመጡ ቡድኖች  አስፈላጊ ነው፡፡ ከአዲስ አበባ ከፍ ያለች ከተማ ነች ወልዲያ … ተጋጣሚ ቡድኖችን እያስተናግደን ቶሎ ቶሎ ብናሸንፍ ጥሩ ነው፡፡›› ብለው ለመጨረሻው ጥያቄ “ስታድዬሙ የተረከበው አካል ይህን በቶሎ ቢያደርግ ማየት ደስ ይለኛል፡፡›› ሲሉ ተናግረዋል፡፡
የስታዲየሙን ፋይዳ አስመልክቶ ዶ/ር አረጋ ሲናገሩ ወልዲያ ለላሊበላ ቅርብ በመሆኗ፣ ባቡር በከተማው ስለሚያልፍ፤ ለመቀሌ፣ ለጎንደር፣ ለጎጃም፣ ለደብረ ማርቆስ አዋሳኝ ከተማ በመሆኗ የቱሪዝም መስህብነቷን እንደሚጨምር በመጥቀስ ነው፡፡ በከተማው ስፖርትን ለማነቃቃት ከፍተኛ አቅም በስታድየሙ መኖር ይገኛል በማለትም አብራርተዋል፡፡
‹‹ስታድዬሙን ወልዲያ ከተማን ያስተዋወቃል በማለት በጋዜጣዊ መግለፃ ላይ የተናገሩት ዶክተር አረጋ ይርዳው፤ በካሊፎርኒያ ቤቨርሂልስ እንደሚገኘው ‹‹ሆሊውድ›› የተሰኘ ላንድ ማርክ ምልክት ቢሰራም የመሃመድ ሁሴን አሊ አላሙዲ ስታድዬም የከተማው ምልክት ይሆናል ብለዋል፡፡ ስታድዬሙ አገር አቀፍና አህጉራዊ ውድድሮች በማስተናገድ  ፈርቀዳጅ እንደሚሆን የሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ እንደሚያምንበት ከፍተኛ የገቢ አቅም ሊፈጥር የሚችል መሆኑንም አመልክተዋል፡፡ ስታዲየሙን የሚያስተዳድረው የከተማው አስተዳደር ነው፡፡ ስታዲየሙን በማከራየት፤ ከዩኒቨርስቲ ጋር በቅንጅት ለመስራት፣ ብዙ ፋይዳዎቹ ይኖሩታል፡፡ ሚድሮክ የስታዲየሙን የቅርብ ክትትል ያደርጋል ዕድሳቶችን በየጊዜው ያከናውናል፡፡
የስታድዬም መሰረተ ልማቶችና የውድድር መስተንግዶዎች
በኢትዮጵያ ስፖርት አንዱ ትልቁ ውጤት የስታድዬም መሰረተ ልማቶች መስፋፋት መሆኑን ባለፉት 3 ዓመታት በየክልሎቹ እና በየከተሞቹ ከሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ማስተዋል ይቻላል፡፡ በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት በተለያዩ የክልል ከተሞች ሙሉ በሙሉ ስራ የሚጀምሩ ከ12 በላይ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያላቸው ስታድዬሞች አገሪቱ ይኖሯታል። እስከ 60ሺ የሚያስተናግደው የባህርዳር ስታድዬም ግንባታውን በቀዳሚነት አጠናቅቆ አገልግሎት በመስጠት ፈርቀዳጅ ነው፡፡ የባህርዳር ስታድዬም የመላው ኢትዮጵያ ጨዋታዎች፤ ከዚያም የአፍሪካ ክለቦች ውድድሮችን እንዲሁም የብሄራዊ ቡድኑን ጨዋታዎች በማስተናገድ ስኬታማ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ አምና 38ኛው የሴካፋ ሲኒዬርስ ቻሌንጅ ካፕ ያስተናገደው በከፍተኛ የጥራት ደረጃ የተገነባው የሐዋሳ ስታዬም  እስከ 45ሺ ተመልካች የሚይዝ ነው፡፡ የሐዋሳ ስታድየም የሴካፋን የምድብ ጨዋታዎች በማስተናገድ በካ እውቅና እግኝቶ ከባህርዳር ስታዬም በመቀጠል ሁለተኛው ውጤታማ መሰረተልማት ሆኗል። ዋልያዎቹ 2ለ0 ሶማሊያን ያሸነፉበትን የመጀመርያውን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ኢንተርናሽናል ጨዋታ ለማስተናገድ የበቃ ሲሆን ከዚያም ለ2017 የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ ከሲሸልስ ጋር የተደረገ ግጥሚያንም ያስተናገደ ነው። ካለፈው ዓመት ጀምሮ የሐዋሳ እና የባህርዳር ስታድዬሞች አገልግሎት መስጠትና በካፍ እውቅና ማግኘት በመጀመርያ የፈጠሩት መነቃቃት በሌሎች ከተሞችም በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታትም የሚቀጥል ይሆናል፡፡ በካፍ እና በፊፋ ዓለም አቀፍ እውቅና ያገኙ ስታዬሞች ደግሞ ብዛታቸው 5 ደርሷል፡፡ የአዲስ አበባው ይድነቃቸው ተሰማ ስታድዬም፤ አበበ ቢቂላ ስታድዬም ቀዳሚዎቹ ሲሆኑ ከዚያም ባለፈው ዓመት የባህርዳር ፤ የሃዋሳ ከነማ እና የድሬዳዋ ስታድዬሞች እውቅና በማግኘት አህጉራዊ ጨዋታዎችን አስተናግደዋል፡፡ በወልዲያ ከተማ የተገነባው ሼህ መሃመድ ሁሴን አሊ  አላሙዲ ስታድዬም ለዓለም አቀፍ እውቅና በመድረስ 6ኛው ስታድዬም ነው፡፡
በግንባታ ላይ የሚገኙት 30ሺ ተመልካች የሚያስተናግደው ስታድዬም  የመቀሌ ስታድዬም ፤ ከ90 በመቶ በላይ ግንባታው የተጠናቀቀ እና 60ሺ የሚይዘው የነቀምቴ  ስታድዬም በመጨረሻ ምእራፍ ላይ በምደረሳቸው የሚጠቀሱ ይሆናል፡፡ የአዳማና ጋምቤላ ከተሞች ዘግይተው ቢጀምሩም 80ሺ እና 30ሺ ተመልካቾች የሚይዙ ስታድዬሞቻቸውን እንደ ቅደም ተከተላቸው እያስገነቡ ናቸው፡፡ የአዳማ ስታድዬም እስከ 1.7 ቢሊዮን ብር በሆነ ወጭ ተገንብቶ ሲጠናቀቅ በሚይዘው ተመልካች ብዛት ግዙፉ ሊሆን የሚበቃ ሲሆን እስከ 80ሺ በማስተናገድ ነው። እንዲሁም የጋምቤላው ስታድዬም እስከ 380 ሚሊዮን ብር ይወጣበታል፡፡ በሚገነቡ ስታድዬሞች የዘገየው የአዲስ አበባ ከተማ ነው፡፡  እስከ 60ሺ ተመልካች እንደሚይዝ የሚጠበቀው አደይ አበባ የሚል ስም የወጣለት ብሄራዊ ስታድዬም ዋናው የከተማ እቅድ ነው፡፡ ይህ ስታድዬም ከጎኑ የኦሎምፒክ መንደር የሚገነባለት መዋኛ፤ የመረብ ኳስ፤ የቅርጫት ኳስ ሜዳዎች እና ሌሎች የስፖርት መሰረተልማቶች ያሉት  60ሺ ተመልካች የማስተናገድ አቅም የሚኖረው  ይሆናል፡፡ የስታድዬሙ ዲዛይን በ40 ሚሊዮን  በኤምኤች የተሰራ ሲሆን በቻይና ስቴት ኢንጅነሪንግ  ኮርፖሬሽን በሁለት ደረጃዎች የሚገነባ የግንባታ ወጭው በመጀመርያው ምዕራፍ እስከ 2.4 ቢሊዮን ብር የተተመነ ነው፡፡ በተጨማሪም በአዲስ አበባ ከተማ በአምስት ዞኖች እያንዳንዳቸው   ለግንባታቸው 300 ሚሊዮን ብር ወጪ  አምስት ስታድዬሞች እንደሚታነፁ የተገለፀው ከሶስት ዓመት በፊት ነበር፡፡ በመተሳሳይ ወቅት በ1.3 ቢሊዮን ብር በጀት 60ሺ ተመልካች የሚያስተናግደው የአቃቂ ቃሊቲ ስታድዬም ዲዛይኑ በዮሃንስ አባይ ኮንሰልታንሲ ተሰርቶ በተክለብርሃን አምባዬ ኮንስትራክሽን እንደሚገነባም ተገልጿል፡፡ ሻሸመኔ፤ ድሬዳዋ፤ ሃረር፤ ጅማ ፤ ጎንደር፤ ስታድዬሞች መገንባት ያለባቸው ሌሎች ክልሎችና ከተሞች መሆናቸው ከዚህ ጋር ተያይዞ የሚነሳ ይሆናል፡፡
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ከወር በፊት ይፋ ባደረገው የ2008 በጀት ዓመት የገቢ ዝርዝር ትልቁን ድርሻ የሚወስደው ከስታድዬም ትኬት ሽያጭ የተገኘው ነው፡፡ በውድድር ዘመኑ ከብሄራዊ ቡድኑ ጨዋታዎች፤ ከሴካፋ እና ከፕሪሚዬር ሊግ ውድድሮች በተያያዘ የተገኘው ገቢ ከ13.6 ሚሊዮን ብር በላይ ነው፡፡
የስታድዬሞች መሰረተ ልማት መስፋፋት  
ኢትዮጵያ በአህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ውድድሮች የሚኖራትን ንቁ ተሳትፎ የሚያነቃቃ ይሆናል፡፡ አገሪቱ ለትልልቅ የስፖርት መድረኮች በመስተንግዶው፣ በትራንስፖርት አቅርቦት፤ በፀጥታና ደህንነት ያሏትብ አቅሞች  ከስታድዬሞቹ ግንባታ ጋር የሚፋጠን ነው። በተለይ ኢትዮጵያ በ2020 እኤአ የምታስተናግደው 6ኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ ቻን በስታድዬሞች መሰረተልማት በኩል ያላት ዝግጁነት የተረጋገጠ ነው።  እንደ ቻን አይነት አህጉራዊ የእግር ኳስ ውድድር ለማስተናገድ አምስት ደረጃውን የጠበቁ ስታድዬሞች በቂ ናቸው፡፡ ለአፍሪካ ዋንጫ ደግሞ በአማካይ 40ሺ ተመልካች የሚያስተናግዱ 4 ስታድዬሞች ከተገነቡ  ምናልባትም ኢትዮጵያ  የአፍሪካ ዋንጫን የምታስተናግድበት እድል በሚቀጥሉት 16 ዓመታት ሊሳካ የሚችል ይመስለኛል፡፡
ከ2020 እኤአ የቻን ውድድር መስተንግዶ በኋላ ትኩረቱ የአፍሪካ ዋንጫ እንዴት ይዘጋጃል? መሆን አለበት፡፡ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን ለአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጅነት ብቁ የሚላቸው አገራት በሆቴል እና መስተንግዶ፤ ቢየያንስ አራት አለም አቀፍ ደረጃ የጠበቁ ስታድዬሞች ከእነ ልምምድ ስፍራቸው፤ በቂ የአየር እና የየብስ ትራንስፖርት አገልግሎት፤ አስተማማኝ ደህንነት እና ፀጥታን በዋና መስፈርቶቹ ይመለከታል፡፡
በአህጉራዊ ውድድር መስተንግዶ በሁሉም ከተሞች የሚገኙ ስታድዬሞች  ከአምስት በላይ ከብሄራዊ ኮሚቴው ጋር ተፈራርመው የሚሰሩ የመንግስት ተቋማት ከወዲሁ ማፈላለግ እና በአጋርነት የመስራት ስምምንት ማድረግ ይኖርባቸዋል፡፡ በአጠቃላይ ግንባታቸው ተጠናቅቆ ስራ እየጀመሩ የሚገኙት እና በግንባታ ላይ ያሉት ብዙዎቹ ስታድዬሞች በአፍሪካ ደረጃ ተመጣጣኝ ጥራት ያላቸው መሆናቸው የሚያበረታታ ነው፡፡ የስታድዬሞቹ በየክልሉ መስፋፋት ታላላቅ ውድድሮችን የማዘጋጀት አቅም፤ የየተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት የሚያነቃቃም ይሆናል። የስፖርቱን አስተዳደር ሁለገብ አቅም ያሳድጋል፡፡ አለም አቀፍ ትኩረት ይገኝበታል፡፡ የስፖርት መሰረተ ልማቶች እንዲስፋፉ ምክንያት ይሆናል፡፡ የስፖርት እድገትን ለማቀላጠፍ ያግዛል፡፡ አንድ አገር አህጉራዊ እና ዓለም አቀፋዊ የስፖርት መድረኮችን በማስተናገድ በቂ ተመክሮ እና አቅም እየገነባ ሲሄድ እንደ ዓለም ዋንጫ ኦሎምፒክ መድረኮችን ማዘጋጀት የሚቻልበት ምእራፍ ላይ የሚደረስ ይሆናል፡፡
ዎርልድ ስታድዬም ኢንዴክስ የሚባል የዓለም አቀፍ ሪፖርት አለ፡፡ በዳንሽ ኢንስቲትዩት ነው ስፖርት ስታዲስ የተሰራ ጥናት ነው “play the game” በሚል ርዕስ በለቀቀው ሪፖርቱ በ20 አገራት በሚገኙ 75 ስታዲየሞቹ ላይ ያተኮረ ነበር፡፡ ከአውሮፓ ዋንጫ፣ ከዓለም ዋንጫ እና ከአፍሪካ ዋንጫ መስተንግዶዎች ጋር በተያያዘ  በ20 አገራት ባለፉት 15 ዓመታት የተገነቡት 75 ስታድየሞች በ14.5 ሲሆን ዶላር ነው፡፡ የዓለም ዋንጫን ለማስተናገድ የስታድዬም ግንባታና እድሳት በጀት እስከ 2.8 ቢሊዮን ዶላር ነው፡፡ በ2018 እ.ኤ.አ ራሽያ ለ21ኛው ዓለም ዋንጫ 3.8 ቢሊዮን ዶላር እንዲሁም በ2022 እ.አ.አ ኳታር ለ22ኛው ዓለም ዋንጫ እስከ 3 ቢሊዮን ዶላር በጀት የያዙት ከስታዬሞች ግንባታና ዕድሳት ጋር በተገናኘ ነው፡፡  በሌላ በኩል ደረጃውን የጠበቀ የኦሎምፒክ ሙሉ ስታዲየም እስከ 270 ሚ. ዶላር በጀት ይጠይቃል፡፡ በ2008 ዓ.ም ቤጂንግ 29ኛውን ኦሎምፒክ ያስተናደችው በ428 ሚ. ይዞር በተገነባው የወፍ ጎጆ ስታድዬም ነበር፡፡ ባለፉት 15 ዓመታት አፍሪካ ዋንጫን ያዘጋጁ አገራት በአማካይ ከ4-6 ስታድዬሞች እንዲገነቡ በካፍ የመስተንግዶ መስፈርት ይጠይቃሉ፡፡ ለአውሮፓ ዋንጫ መስተንግዶ 8 ስታድዬሞች ለዓለም ዋንጫ  ደግሞ ከ10-12 ስታዲዬሞች መገንባት መስፈርቱ ይጠይቃል፡፡ የአፍሪካ ዋንጫ ስታድየሞች ከፍተኛ 45ሺ ዝቅተኛ 15 ሺ ተመልካች የሚያስተናግዱ መሆን አለባቸው፡፡ የአውሮፓ ዋንጫ ስታድዬሞች  በአማካይ ከ30-50 ሺ ተመልካች የሚያስተናግዱ ናቸው፡፡  በዓለም ዋንጫ የመክፈቻና የዋንጫ ጨዋታዎች የሚያስተናግዱ ስታድዬሞች ያስፈልጋሉ፡፡ ባለፉት 5 የአፍሪካ ዋንጫዎች  አዘጋጅ አገራት በአማካይ ለመስተንግዷቸው ከ3 እስከ አምስት አዳዲስ   ስታድዬሞች ገንብተዋል፡፡ 

• በኹለቱ ዓመታዊ ክብረ በዓላት፣ ከ23   ሚ. ብር በላይ የስዕለት ገቢ ተሰብስቧል
• ማሠልጠኛዎች እንዲገነቡና የማኅበራዊ ልማት ተሳትፎው እንዲጠናከር ተጠይቋል

  በቁሉቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ውስጥ፣ እየተፈጸመ ነው በሚል ከምእመናን በተደጋጋሚ የቀረበው የሙስና  አቤቱታ፣ ተጣርቶ አስፈላጊው ርምጃ እንዲወሰድ፣ የምሥራቅ ሐረርጌ ዞን መስተዳደር ጽ/ቤት አሳሰበ፡፡ የመስተዳድሩ ጽ/ቤት ማሳሰቢያውን ያቀረበው፣ ባለፈው ወር መጀመሪያ ለፓትርያርኩ ቢሮ በጻፈው ደብዳቤ ነው፡፡ በዞኑ ሜታ ወረዳ ቁሉቢ ከተማ በሚገኘው የደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ውስጥ፣ “ኃይለኛ ሙስና እየተፈጸመ” መሆኑን በመጥቀስ ጉዳዩ እንዲጣራ የአጥቢያው ምእመናን ለቤተ ክርስቲያኒቱ ጥያቄ ሲያቀርቡ፣ ለመስተዳድሩም በግልባጭ አስታውቀው እንደነበር ጽ/ቤቱ አስታውሷል፡፡
አቤቱታውን ለማጣራት፣ ከገዳሙ አስተዳደርም ይኹን ከምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ እንዳልተደረገ፣ ከምእመናኑ በድጋሚ መረዳቱን የጠቀሰው የዞኑ መስተዳድር፤ “ለሕዝበ ክርስቲያኑ ክብር አለመስጠትን ያመለክታል፤” ሲል ተችቷል፡፡
“ጉዳዩ ወደ ሌላ አቅጣጫ እንዳያመራ”፣ በገዳሙ እየተፈጸመ ነው ስለተባለው ሙስና በቤተ ክርስቲያኒቱ አመራር በተገቢው መንገድ ተጣርቶ አስፈላጊው እርምጃ እንዲወሰድና ለሕዝበ ክርስቲያኑ እንዲገለጽ የፓትርያርኩን ቢሮ ጠይቋል፡፡ ጉዳዩ፣ በመንግሥት ደረጃ የፓትርያርኩ ቢሮ እስኪጠየቅ ድረስ ቸል መባሉ፣ በእጅጉ ቅር እንዳሰኛቸው የገለጹት የአጥቢያው ምእመናን፤ በአካባቢው በገዳሙ የተከናወነ ተጠቃሽ ማኅበራዊ ልማት አለመኖሩን፤ የአገልጋዮች ደመወዝ የገቢውን ያኽል አለመሻሻሉንና
ካህናቱ ከሚያሳዩት ትጋት ውጭ መንፈሳዊ አገልግሎቱን ለማጠናከር በአስተዳደሩ የሚደረገው ጥረት እዚህ ግባ የማይባል መኾኑን አስረድተዋል፡፡በየዓመቱ ታኅሣሥ 19 እና ሐምሌ 19 ቀን ለገዳሙ በስዕለት ከሚገባው ጥሬ ገንዘብና የተለያዩ ዓይነት ንዋያተ ቅድሳት ውጭ ባሉት ወርኃዊ በዓላትም ከፍተኛ ገቢ እንደሚገኝ ምእመናኑ ይናገራሉ፡፡ የኹለቱ ዓመታዊ ክብረ በዓላት ገቢ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤትና በዞኑ መስተዳድር አካላት ጥብቅ ቁጥጥር የሚደረግበትን ያኽል በሌሎቹም ወራት አለመደረጉ ለከፍተኛ ሙስና አጋልጦታል የሚሉት ምዕመናኑ፤ የጸበል ቦታው በብዙ መቶሺዎች እንዲታወቅ፣ ማረፊያዎችንና መጸዳጃዎችን ምቹ ማድረጉ እንኳ ትኩረት አልተሰጠውም፤ ሲሉ ቅሬታቸውን ይገልፃሉ፡፡የገዳሙ አስተዳዳሪ መልአከ ኃይል አባ ወልደ ጊዮርጊስ በበኩላቸው፤ የዞኑን ጥያቄ በተመለከተ ከጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጋር
መወያየታቸውንና የተሰጠውን ምላሽም ትላንት ለመስተዳድሩ ማድረሳቸውን ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል። “ጉዳዩ መታየት ያለበት በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ነው፤” ያሉት አስተዳዳሪው፣ የሙስና አቤቱታ አቅርበዋል የተባሉት ሰዎች ራሳቸው፣ በወንጀል
የሚፈለጉ መኾናቸውን ጠቅሰው፣ ለሕግ እንዲቀርቡ ጠይቀናል፤ ብለዋል፡፡
የገዳሙ ሒሳብ ሹሙ ወ/ሪት ወይንሸት ግርማም፣ አቤቱታ አቅራቢዎቹ ማንነታቸውን አለመግለጻቸውን ጠቅሰው፣ አቤቱታ የቀረቡባቸውን ጥያቄዎች ከሀገረ ስብከቱ ጋር ለመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በአካል አቅርበን በደብዳቤ የተሰጠውን ምላሽ ደግሞ፤ አዲስ አበባ ለሚገኘው ክልላዊ ቢሮና ለዞኑ ጽ/ቤት መስጠታቸውን አስረድተዋል፡፡
“ገዳሙ፣ በገቢረ ተኣምራቱ ያለውን ታዋቂነትና የገቢ መጠኑን ያኽል፣ መንፈሳዊ አገልግሎቱን ለከተማው ምእመናን ተደራሽ በኾነ አኳኋን እንዲያስፋፋ፤ ቀድሞም የነበሩት የካህናት ማሠልጠኛና የአብነት ት/ቤቶች በተደራጀ መልኩ እንዲከፈቱ፤ እንደ ድሬዳዋና ሐረር ባሉት ከተሞች ተጨማሪ ገቢ የሚያስገኙ የራስ አገዝ ግንባታዎችን በማካሔድ ማኅበረሰባዊ አገልግሎቱን የሚያጠናክርበት አቅም እንዲፈጥር” ጠቁመዋል ምዕመናኑ፡፡ ለዚኽም ገዳሙ፣ “ለረጅም ጊዜ ከቆዩት ሓላፊዎች ይልቅ፡- ሙስናን የሚጸየፉ፣ የተማሩና የነቁ አገልጋዮች” እንደሚያስፈልጉት ጠቁመዋል፡፡በዓመት ኹለት ጊዜ ለሚከበረው የቅዱስ ገብርኤል ክብረ በዓል፣ ከሀገር ውስጥና ከውጭ ወደ ገዳሙ ከሚጓዙ ተሳላሚዎች፣ ከ23 ሚሊዮን 587 ሺሕ ብር በላይ በስዕለት መግባቱን የሐምሌ 19 ቀን 2007 እና የታኅሣሥ 19 ቀን 2008 ዓ.ም. የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሪፖርት ያመለክታል፡፡ ይኸው ገቢ በጠቅላይ ጽ/ቤቱ የበጀት ዕቅድ እየወጣለት፥ ለቤተ ክርስቲያኒቱ የነገረ መለኰት ኮሌጆች፣ ለአብነት መምህራን፣ ለሰባክያነ ወንጌልና ለሠራተኞች ደመወዝ የሚከፈል ሲሆን የሙከራ ሥርጭት እያካሔደ ለሚገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቴሌቭዥን ጣቢያ የ9 ሚሊዮን ብር አስተዋፅኦ ማድረጉም በሪፖርቱ ተገልጿል። በስዕለት የሚሰበሰቡትን የተለያዩ ዓይነት ንዋያተ ቅድሳት፣ ዋጋ አጥንቶና ተማኝ ኮሚቴ አቋቁሞ የሚያሰራጭ የማደራጃ መምሪያ፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የተቋቋመ ሲኾን፤ ተጨማሪ ገቢ ማስገኛ ሕንፃ ለማሠራትም ዕቅድ መያዙን በሪፖርቱ አስታውቋል፡፡  

 ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጀት 95ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን ምክንያት በማድረግ በዛሬው ዕለት ለበጎ አድራጎ ድርጅቶች 132 ሺህ ብር የሚገመት የቁሳቁስ እርዳታ ያበረክታል፡፡
ድርጅቱ “ለቀጨኔ ሴት ህፃናት ማሳደጊያ ተቋም” እና “የወደቁትን አንሱ የአረጋውያን መርጃ ማህበር”፣ የአዲስ አበባ አስተዳደር ሴቶችና ህፃናት ጉዳዮች ቢሮ አመራሮችና ሰራተኞች በተገኙበት እርዳታውን ያበረክታል ተብሏል፡፡
ማተሚያ ድርጅቱ፤ ለእያንዳንዳቸው 66ሺህ ብር በመመደብ፡- 20 አልጋዎች፣ 20 ፍራሽ፣ 20 ብርድ ልብስ፣ 20 አንሶላና የትራስ ልብስ እንዲሁም ሌሎች ልዩ ልዩ ቁሳቁሶች እንደሚያበረክት አስታውቋል፡፡

የአዲስ አድማስ ጋዜጣ መስራች
የአቶ አሰፋ ጎሳዬ ገዳ የ12ኛ ዓመት መታሰቢያ ታህሳስ
6 ቀን 2009 ዓ.ም በቅዱስ ካቴድራል አማኑኤል
ቤተክርስቲያን በፀሎት ታስቦ ውሏል፡፡
አሴዋ ሁሌም እናስብሃለን ቤተሰቦችህ


አንድ ደርዘን ዕድሜ

አሴ!
ከቶም አንድ ደርዘን ዕድሜ፣ አለፈና ዘመን ሆነ
አዋቂውን እያከሳ፣ ድንቁርና እያደነደነ
የነበረው እንዳለ አለ
እንደ አፋር ጫማ ፊት ኋላውን፣ አቅጣጫው አልለይ እንዳለ፡፡
ያልተዘመረለት ነህ፣ ብዬህ ነበር ገና ያኔ
አሁንም ወሮናል አሴ፣ የዕውቀትና ብስለት - ጠኔ
ዛሬም ያልተዘመረለት፣ እንደገባ ነው ምናኔ!
“… አዎ አለ አንዳንድ ሰው
ጉቶ የሸፈነው የአገር ግዙፍ ዋርካ
መስፈሪያ የሌለው፣ ልቡ እማይለካ
… ያልተዘመረለት፣ እሱ ኖሯል ለካ!”
ያልኩህ ትዝ ይበልህ አሴ፣ ዛሬም ያው ጮካ ለጮካ
ኑሮ ሆኗላ እንካ በእንካ!
ዘመኔ መቀነቻ አጥቶ፣ ይሸነጋገላል ሰው ሁሉ
የአፉ ከሆዱ ተጣልቶ፣ ጠፍቶበታል ዕትብት ውሉ፡፡
ሰው ሲጠፋን ስለሰው፣ ማሰብ የማይቀር ዕውነት ነው
ያጎደሏትን አገር፣ መሙላት ጭንቁ መቶ አምሳ ነው
ቅጣቱ ራስን ማጉደል ነው!
አላዋቂው ከላይ ሰፍሮ
አዋቂ ታች ተቀርቅሮ
ዱሮ እንዳየኸው ነው ህይወት፣ ያው የግርምቢጡ ኑሮ!
ሰው ራሱን ለማየት ዛሬም ዐይኑ ጠፍቶበታል
እንንገርህ ብንል ደግሞ፣ ቀድ ጆሮውን ይዘጋል
ደምም መቅመስ አልሆነለት፣ ፍጥረቱ ለጣ’ም ጣም የለው
ስድስተኛ ስሜት አለው፣ ብለን ጥንት የጠረጠርነው
ከነአምስቱም ጠፍቶበታል፣ መደናበር ነው የያዘው!
አሴ እንዳልኩህ ጉቶው በዛ፣ ዋርካ እሚሆን ሰው ጠፋና
በግምገማ ብቻ ቀረን፣ ጧት ማታ እያወራን መና!
አሴ! ፈገግ በል እባክህ፣ ምንም አላጣህምና!
የምንፈልገውን ሳናውቅ፣ የምናውቀውን ሳንፈልግ
የሚሄደውን መራገም፣ ለመጣ ሁሉ ማደግደግ
ይህ ሆኗል የህሊና ሕግ!
አዲስ መውለድ ሲያቅተን፣ ያረጥነውን መናፈቅ
እርግማን ነው የቤት ጣጣ፣ ዘልቆ አገርን የማያዘልቅ
አሴ!
ትውልዱም እንዳስቀመጥከው
ዴሞክራሲም ያው እዚያው ነው
ንግዱ በጭንቅ፣ ኑሮው በጭንቅ፣ ባለቤት
የሌለው እልፍኝ
ከቶም ያልተግባብቶም አገር፣ የሆድ ያንጀት
እማያስገኝ
ወይ ከታሪኩ ያልሆነ፣ ወይ ልባም ታሪክ ያልሰራ
እንደው ሸርተት ሸተት ብቻ፣ የአንድ ደርዘን ዕድሜ ጎራ
ነውና አሴ አልቀረብህም፣ እዚያው ፈገግ ብለህ ኩራ!
ያ ፈገግታ ነው የናፈቀን፣ አሴ ሳቅልን አደራ!!
ከቶም ላልተዘመረለት፣ እንዘምርለት ያልነው
ከቶም ላልተነገረለት እንናገርለት ያልነው
ዛሬም ሀቁ እንደዚያው ነው
አስራ ሁለት ዓመት ሆነ፣ ደርዘን ፈገግታህ ይፍካ
ሁሌም እናስብሃለን፣ በቅን ፍቅራችን ተመካ!
ወደፊት እንሂድ እንጂ፣ ወደኋላ ማሰብ አይቀር
አለህ እውስጣችን አሴ፣ ስምህ የትም አይቀበር
ህዝቡ ይወቅ ብለሃል፣ ዕውቀት የፈራ ያቀርቅር
በዚህ ነው አንተ እምትኖር!
“መርሳት ለዘላለም ይኑር፣” የሚሉ እንዳሉ አቃለሁ
እኔ ግን በልብ ዕምነቴ፣ መርሳት ይሙት እላለሁ!!
(ለአሰፋ ጎሳዬ 12ኛ ሙት ዓመት
እና ለማንረሳቸው ሁሉ መታሰቢያ)
ነቢይ መኮንን

 ሕጻናት ከተወለዱ ከስድስት ወር በሁዋላ ተጨማሪ ምግብ እያገኙ እስከ ሁለት አመት እድሜአቸው ድረስ የጡት ወተት መመገብ ሊቋረጥባቸው አይገባም።
 ሕጻናት ሁሉ በትክክል ጡት ወተት ከተመገቡ በየአመቱ በአለም እስከ 800,000 ልጆችን ሕይወት ማዳን ይቻላል።
 በአለም አቀፍ ደረጃ ከሚወለዱት ሕጻናት ከ40% በታች የሆኑት ሙሉ በሙሉ የጡት ወተት አግኝተዋል ማለት ይቻላል።
 WHO-
       
 ሕጻናት ከተወለዱ ከስድስት ወር በሁዋላ ተጨማሪ ምግብ እያገኙ እስከ ሁለት አመት እድሜአቸው ድረስ የጡት ወተት መመገብ ሊቋረጥባቸው አይገባም።
ሕጻናት ሁሉ በትክክል ጡት ወተት ከተመገቡ በየአመቱ በአለም እስከ 800,000 ልጆችን ሕይወት ማዳን ይቻላል።
በአለም አቀፍ ደረጃ ከሚወለዱት ሕጻናት ከ40% በታች የሆኑት ሙሉ በሙሉ የጡት ወተት አግኝተዋል ማለት ይቻላል።
 WHO-
    ጡት ማጥባት ከምንም በላይ ለልጆች ጠቃሚ ነው ቢባልም አንዳንድ ጊዜ ግን ልጆች የሚጎዱበት ምክንያት እንደሚያጋጥም ግልጽ ነው። ይኼውም ከጤና አኩዋያ ሲሆን ጥቂቶቹ የሚከተሉት ናቸው።
ኤችአይቪ ከእናት ወደልጅ ከሚተላለፍባቸው መንገዶች አንዱ ጡት የማጥባት ወቅት ነው። ሌላው ሕመም ደግሞ የሳንባ በሽታ ሲሆን በተለይም በወቅቱ ካልታከመ ይህ ለሕጻኑ ጉዳት ለስከትል ይችላል። የካንሰር ሕመም ገጥሞአት ኬሞራፒ የተባለውን ሕክምና የምትከታተል እናት ልጁዋን ጡት በምታጠባበት ወቅት ለልጁዋ ሕመምን ሊያስከትል ይችላል።
ከላይ ከተጠቀሱት ውጪ እንደ ኮኬይን ፣ማሪዋና፣ሲጋራ ማጨስና መጠጥ አዘውትራ የምት ጠጣ እናት ልጁዋን በምታጠባበት ወቅት ለልጁ ጎጂ ሊሆን ይችላል። አንዳንድ መድሀኒቶችን ለምሳሌም ማይግሪን ለተሰኘው ከባድ የራስ ሕመም እና ተመሳሳይ የጤና ችግሮች በሐኪም ትእዛዝ የሚወሰዱ መድሀኒቶችም የጡት ወተቱን ጎጂ ሊያደርጉ ስለሚችሉ ጥንቃቄ ማድረግ ይገባል። ስለዚህ ምንም አይነት የጤና እና የባህርይ ችግር ቢኖር ጡት ለማጥባት መቻል አለመቻልን ከሕክምና ባለሙያ ጋር መምከር ጠቃሚ ይሆናል። አንዳንድ ጊዜ ጎጂ ናቸው ተብለው የሚታሰቡ እንደ ጉንፋን ወይም የብርድ ሕመም የመሳሰሉት ጡት ከማጥባት የሚያግዱ አይደሉም። የጡት ወተት በእራሱ በሽታን የመከላከል አቅም ስላለው ጡት የሚጠባውን ልጅ ከሕመም ሊከላከልለት ይችላል። አንዳንድ የህክምና ጠበብት ሕጻን ከተወለደ ከ4/ወር ጀምሮ አይረንና ቫይታሚን ዲ የተሰኙትን ንጥረነገሮች በሐኪም ትእዛዝ መስጠት ይችላል። ነገር ግን ለሕጻኑም ሆነ ለእናትየው ይህ ድጋፍ ሰጪ ቋበቅቅቁስቂስቃቋ ከመቼ ጀምሮ እና ምን ያህል መወሰድ እንዳለበት ሐኪምን ማነጋገር ያስፈልጋል።
እናቶች ልጆቻቸውን ለምን ጡት ማጥባት አይፈልጉም?
አንዳንድ እናቶች ምክንያቱ ባልታወቀ ሁኔታ ልጆቻቸውን ሲያጠቡ መታየት አይፈልጉም። ምናልባትም የሁዋላቀርነት ምልክት አድርገው ሊወስዱት ይችላሉ።አንዳንድ ጊዜ ደግሞ የልጁ አባት ወይንም በቤት ውስጥ ልጁን የሚንከባከቡ ቤተሰቦች ጡጦ በማዘጋጀት ሊሰጡት ስለሚ ችሉ ልጁ ተጎጂ አይደለም...እንዲያውም ተጠቃሚ ነው ብለው የሚያስቡ ይኖራሉ። ከዚህ በተጨማሪም ልጆች ከጡት ወተት ይልቅ የተዘጋጀ ወተትን በቀስታ ይመገባሉ። የጡት ወተት ግን በተደጋጋሚ ሊወስዱት የሚችሉት ቀለል ያለ ምግብ ስለሆነ ምናልባትም የሚጠግቡት በተዘጋጀው ወተት ስለሆነ በእርጋታ ይመገባሉ የሚል እሳቤ የሚኖራቸው እናቶች ይኖራሉ።ይህ ግን ተክክል ስላልሆነ የወለዱትን ልጅ ጡት በተገቢው መንገድ ማትባት ጠቃሚነት አለው።
ጡት ለማጥባት አስቸጋሪ ሁኔታዎች
የጡት ጫፍ መቁሰል
ልጅ እንደተወለደ በመጀመሪያው ሳምንት የጡት ጫፍ መቁሰል እንደሚኖር አስቀድሞ ማወቅ ብልህነት ነው። ልጁ በትክክል ጡት መያዙን ማረጋገጥ እና ሲጨርስም ጡቱን ከአፉ ከመጎተት ይልቅ አንድ ጣትን ወደልጁ አፍ በመክተት ጡቱን ከአፉ ለማውጣት በቂ ክፍተት መፍጠር ይጠቅማል።ቁስለቱ ቶሎ የማይድን ከሆነ ጡት ባጠቡ ቁጥር ወተቱን ጨርሶ እንዲጠባ እና ጡቱ እንዳያግት ማድረግ ይጠቅማል። ይህ ካልሆነ ግን ጡቱ በወተት ይሞላል ፣ያብጣል ፣ ሰለሆነም ሕመም ይኖረዋል። ልጅ ከጠባ በሁዋላ ድጋሚ እስኪሰጠው ባለው ጊዜ ጡቱ ደረቅ እንዲሆን ማድረግ ይጠቅማል። ልጁ ደጋግሞ በጠባ ቁጥር በጡት ጫፍ ላይ ያለው ቁስለት እየቀነሰ እንዲያውም እየዳነ ይሄዳል። ስለዚህ የጡት ጫፍ ቆሰለ ተብሎ ልጁ ጡት ከመጥባት መታገድ የለበትም።
ደረቅና የተሰነጣጠቀ የጡት ጫፍ
የጡት ጫፍን ለማጽዳት የሚጠቀሙበት ሳሙና ወይንም የሽቶ መአዛ ያላቸው ቅባቶች እና ሎሽኖች በውስጣቸው አልኮል ስላላቸው ማስወገድ ተገቢ ነው። ከጡት ማጥባት በሁዋላ ንጹህ የሆኑ ጠረን የሌላቸው ቅባቶችን መጠቀም ይጠቅማል። ቅባት ከተቀቡ በሁዋላ ጡት መልሶ ለማጥባት የተቀባውን ቅባት በደንብ ማጠብና ማስወገድ ያስፈልጋል። የጡት መያዣዎ ከጥጥ የተሰራ እንዲሆን ይመከራል።
በቂ የጡት ወተት የለኝም ብሎ መጨነቅ
አንድ ልጅ በቀን በበቂ ሁኔታ ጡት ጠብቶአል ወይንም ተመግቦአል የሚባለው በቀን ከ6 እስከ 8 ዲያፐር ሲቀይር ነው። አንድ ልጅ እስከ 6 ወር ድረስ ካለምንም ተጨመቀሪ ምግብ የጡት ወተት መጥባት አለበት። የእናትየው ሰውነት የልጁን ጡት መጥባት ፍላጎት በየተወሰነው ሰአት ስለሚረዳ ማለትም ጡቱ ወተት ስለሚሞላ ቸል ባለማለት በተገቢው ማጥባት ይገባል። ጡት በተሳበ ቁጥር ወተቱም መመረቱ ይቀጥላል። አንዳንድ ሴቶች ጡታ ቸው በተፈጥሮው ትንሽ ስለሆነ ወተት የለኝም ብለው ያስባሉ። ነገር ግን የጡት መጠን መተ ለቅ ወይንም ማነስ ወተትን በማምረት በኩል ምንም ልዩነት የለውም። እናቶች ባቅማቸው ጥሩ መመገብ ፣ተገቢ የሆነ እረፍት ማድረግ እና ጡታቸውን በተገቢው እያጸዱ ማድረቅ ልጃቸውን ለማጥባት ምቹ ሁኔታን ይፈጥርላቸዋል።
ጡትን ማለብና ወተቱን ማስቀመጥ
ጡቱን በእጅ በመጭመቅ ወይንም በማለቢያ በማለብ የጡት ወተት እንዲገኝ ያስችላል። በተ ለይም እናቶች በቶሎ ወደስራ የሚሄዱ ከሆነ የታለበ የጡት ወተት ማግኘት ስላለባቸው በእቃ መመገቡን አስቀድሞ ማለማመድ ያስፈልጋል። የጡት ወተት ከታለበ በሁዋላ እስከሁለት ቀን ድረስ በማቀዝቀዣ ውስጥ በማስቀመጥ መጠቀም ይችላል። የቀዘቀዘውን የጡት ወተት በማይ ክሮዌቭ ማሞቅ ግን ጠቃሚ ንጥረ ነገሮችን ሊያሳጣ ስለሚችል አይመከርም። የታለበውን የጡት ወተት ለልጁ መስጠት ሲያስፈለግ ከማቀዘቀዣ ውስጥ በማውጣት ትንሽ ማቆየት ወይ ንም የሞቀ ውሀ በሳህን ውስጥ አድርጎ ወተቱን የያዘውን እቃ በሳህኑ ውስጥ ማስቀመጥ ያስፈልጋል።
ጡት በወተት መሞላት
ጡት በወተት ሊሞላ ወይንም ሊወጠር ይችላል። ጡቱ በወተት መሞላቱ ትክክለኛና ተፈጥሮ አዊ ነው። ነገር ግን በጡት ላይ ያሉት የደም ስሮች ሊወጣጠሩና ሊጨናነቁ ይችላሉ።በዚህ ጊዜ ጡት ጠጣር ይሆናል። እንዲሁም በመወጣጠሩ ሕመም ይሰማል። በዚህ ጊዜ በበረዶ በቀዝቃ ዛው ወይንም ሙቅ ሻወር በመውሰድ እንዲላላ ማድረግ ይቻላል።
የጡት ወተት የሚፈስበት መስመሮች
መጠጠር ወይም መታመም
በጡት ውጫዊ አካል ላይ የሚታዩ ቀያይ ወይንም ትኩሳት ያላቸው ነጠብጣቦች የጡት ወተት መፍሰሻው መታመሙን ሊያመላክቱ ይችላሉ። ይህንን አካባቢ በጥንቃቄ መዳሰስ ወይንም ሙቀት እንዲሰማ ጨመቅ ጨመቅ በማድረግ እንዲላላ እና እንዲፍታታ በማድረግ የጠጠረ ውን ነገር እንዲወገድ ማድረግ ይቻላል።
የጡት ኢንፌክሽን
የጡት ኢንፌክሽን ወይንም መመረዝ የሚገጥመው የተሰነጣጠቀው ጡት ከልጁ አፍ ከወጣ በሁዋላ በባክሪያ ሲያዝ ነው።ጡት የመመረዝ ባህርይ ሲያሳይ ትኩሳትና መሰል ስሜቶች ከተስተዋሉ ሐኪምን ማማከር ያስፈልጋል።
ጭንቀት
አንዲት እናት ጭንቀት ካለባት የጡት ወተትዋ ፍሰቱን ሊቀንስ ይችላል። ሰውነት በተፈጥሮው ያመረተውን ወተት ጭንቀት ቢያግደውም ልጁ መጥባት ሲፈልግና እናትየው የልጅዋን ጡት መፈለግ ስታይ ግን ከጭንቀት ስለምትላቀቅ ያን ጊዜ ወተት እንደልብ መፍሰስ ይጀምራል። ስለዚህ የምታጠባ እናት በተቻለ መጠን ዘና ማለት እና መደሰት እንጂ መጨነቅ የለባትም።
እድገቱ ያልተሟላ ሕጻን
አንድ ሕጻን ካለቀኑ ከተወለደና አቅም ከሌለው ጡት መሳብ ሊያቅተው ይችላል። በዚህ ጊዜ የጡት ወተቱን በማለብ በጡጦ ለልጁ ማጠጣት ይገባል።
ባጠቃላይም የተወለደ ልጅን የጡት ወተት መመገብ ተፈጥሮአዊና ጤናማ ተግባር ነው። ነገር ግን ከሐኪም ጋር መመካከር የሚያስፈልግበት አጋጣሚ እንደሚኖር መዘንጋት የለበትም።
ጡት ባልተለመደ ሁኔታ የመቅላት የመቁሰል የመጠንከር እና የመሳሰሉትን ምልክት ካሳየ
ከጡት ውስጥ በጫፉ በኩል ፈሳሽ ወይንም ደም የሚወጣ ከሆነ
ሕጻኑ ክብደቱ እየቀነሰ የሚሄድ ከሆነ ሳይውሉ ሳይድሩ ከሐኪም ጋር መመካከር ያስፈልጋል።  
ምንጭ፡- WebMD, LLC

የኢራን መከላከያ ሚ/ር፤ አለም በትራምፕ አገዛዝ ወደ ጦርነት ልትገባ ትችላለች አሉ
     ተመራጩ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባለፈው ሰኔ የምርጫ ቅስቀሳ በሚያደርጉበት ፕሮግራም ላይ፣ የአንድን ፖሊስ ጠመንጃ በመንጠቅ ትራምፕን ለመግደል ሞክሯል የተባለው እንግሊዛዊ ወጣት የአንድ አመት እስራት እንደተፈረደበት ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ማይክል ሳንፎርድ የተባለው የ20 አመት ወጣት፣ ለመርማሪዎች በሰጠው ቃል፤ የሪፐብሊካኑን ዕጩ ዶናልድ ትራምፕን ተኩሶ ለመግደል በማሰብ፣ ከካሊፎርኒያ በመነሳት በወቅቱ ቅስቀሳ ያደርጉበት ወደነበረው ላስቬጋስ ማምራቱን አምኗል፡፡ ወጣቱ በምርጫ ቅስቀሳው ላይ በጥበቃ ስራ ተሰማርቶ የነበረን ፖሊስ ጠመንጃ በመንጠቅ ትራምፕን ተኩሶ ለመግደል የያዘው ዕቅድ ባይሳካለትም፣ የጦር መሳሪያ በመያዝና ስራን በማስተጓጎል ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘቱ፣ በላስቬጋስ የፌዴራል ፍርድ ቤት የ1 አመት እስር እንደተጣለበት ዘገባው ጠቁሟል፡፡ ተከሳሹ ሳንፎርድ የአእምሮ ችግር እንዳለበት በመጥቀስ ጠበቆቹ ለፍርድ ቤቱ ያስገቡት የቅጣት ማቅለያ በምርመራ ተጨባጭ ሆኖ መገኘቱ በመረጋገጡ ቅጣቱን እንዳቀለለለትም ታውቋል፡፡
በሌላ ዜና ደግሞ፣ የኢራን የመከላከያ ሚኒስትር ሁሴን ዴጋን፣ የትራምፕ ስልጣን መያዝ አለማችንን ወደ ጦርነት ሊያስገባት ፣ እስራኤልንም ለጥፋት ሊዳርጋት ይችላል ሲሉ ማስጠንቀቃቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡ “ትራምፕ በንግድ ስራ ላይ ተሰማርቶ የኖረ ሰው ነው፤ አማካሪዎቹና ረዳቶቹ በተለይም በባህረ ሰላጤው አገራት ላይ ቀውስ ወደሚፈጥር እንዲሁም እስራኤልን ወደሚያጠፋና አካባቢውን አተራምሶ፣ አዲስ የአለም ጦርነት ወደሚቀሰቅስ አደገኛ አቅጣጫ ሊመሩት ይችላሉ” ብለዋል- ሚኒስትሩ፡፡

ባለፉት 2 አመታት በሶርያና በኢራቅ 50 ሺህ ያህል የአሸባሪው ቡድን አይሲስ ታጣቂዎች መገደላቸውን አንድ የአሜሪካ ከፍተኛ ወታደራዊ ባለስልጣን ማስታወቃቸውን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
ባለስልጣኑ የተገደሉትን የአይሲስ ታጣቂዎች በተመለከተ “የተገመተው ቁጥር ይህን ያህል መድረሱ አሜሪካና ጥምር ሃይሉ በአሸባሪው ቡድን ላይ የከፈቱት ዘመቻ ምን ያህል ስኬታማ እንደሆነ ያሳያል” ማለታቸውንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡
 ከሁለት አመታት በፊት በኢራቅና በሶርያ የሚገኙ የአይሲስ ታጣቂዎች ቁጥር ከ20 እስከ 30 ሺህ እንደሚገመት የአሜሪካ የመረጃ ተቋም መግለጹን ያስታወሰው ዘገባው፤ ወታደራዊ ሃላፊው ተገድለዋል ያሏቸው ታጣቂዎች ቁጥር ከዚህ የሚበልጥ መሆኑን አስረድቷል፡፡ በሌላ በኩል አንድ የኩርድ ከፍተኛ የጦር መሪ፣ የታጣቂዎቹ ቁጥር ወደ 200 ሺህ እንደሚጠጋ  መናገራቸውን ዘገባው አስታውቋል፡፡

በመላው ዓለም 259 ጋዜጠኞች በእስር ላይ ይገኛሉ
     በተለያዩ የአለማችን አገራት በእስር ላይ የሚገኙ ጋዜጠኞች ቁጥር በተገባደደው የፈረንጆች አመት 2016 ላይ  259 መድረሱን ያስታወቀው ሲፒጄ የተባለው አለማቀፍ የፕሬስ ተሟጋች ቡድን፣ የጋዜጠኞችን እስር በማጥናት ይፋ ማድረግ ከጀመረበት ከ1990 ወዲህ ከፍተኛው በእስር ላይ የሚገኙ ጋዜጠኞች ቁጥር መሆኑንም ገልጧል፡፡
ቁጥሩ ከፍተኛው ደረጃ ላይ ለመድረሱ ምክንያት የሆነው፣ የቱርክ መንግስት ባለፈው ሃምሌ ወር የተቃጣበትን የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ተከትሎ በጋዜጠኞች ላይ የወሰደው ከፍተኛ የእስር እርምጃ መሆኑን የጠቆመው ቡድኑ፤ በተገባደደው የፈረንጆች አመት ከአለም አገራት በርካታ ጋዜጠኞችን በማሰር ቱርክ ቀዳሚነቱን መያዟን ጠቅሶ፣ የአገሪቱ መንግስት በአመቱ ከ81 በላይ ጋዜጠኞችን ወህኒ መወርወሩን አስታውቋል፡፡
በአመቱ ከቱርክ ቀጥሎ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ጋዜጠኞች የታሰሩባት ሁለተኛዋ የአለማችን አገር ቻይና መሆኗን የጠቆመው የቡድኑ አመታዊ ሪፖርት፤ በአገሪቱ የታሰሩ ጋዜጠኞች ቁጥር 38 መድረሱን አመልክቶ፣ ሶስተኛ ደረጃን በያዘቺው ግብጽ ደግሞ 25 ጋዜጠኞች መታሰራቸውን ጠቅሷል፡፡ በመላው አለም በእስር ላይ የሚገኙ ጋዜጠኞች ቁጥር ከአንድ አመት በፊት ከነበረው 199 ዘንድሮ ወደ 259 ከፍ ማለቱን ሪፖርቱ ገልጾ፣ በእስር ላይ ከሚገኙት ጋዜጠኞች መካከል ሶስት አራተኛ ያህሉ ጸረ-መንግስት ተግባር ፈጽመዋል የሚል ክስ የቀረበባቸው መሆናቸውንና ከታሰሩት 259 ጋዜጠኞች መካከል 20 ዎቹ ሴቶች እንደሆኑ ጠቁሟል፡፡
በኤርትራ 17፣ በኢትዮጵያ 16 ጋዜጠኞች በእስር ላይ እንደሚገኙም ቡድኑ በሪፖርቱ አስታውቋል፡፡