Administrator

Administrator

 *ከሊባኖስ እስከ ዌስተርን ባንክ እና ዋሺንግተን የተቀጣጠለው ተቃውሞ
       *ለጋዛ የሆስፒታል ፍንዳታ እስራኤል ተጠያቂ አይደለችም - ዋይት ሃውስ
       *አሜሪካ በመላው ዓለም ለሚገኙ ዜጎቿ የጉዞ ማስጠንቀቂያ ሰጥታለች
       *3500 ፍልስጤማውያን፤ ከ1400 በላይ እስራኤላውያን ተገድለዋል

          የእስራኤል ሃማስ ጦርነት በተጀመረ በ12ኛው ቀን ላይ፣ መላውን ዓለም ያስቆጣና ያሳዘነ የሮኬት ጥቃት በጋዛ ተፈፀመ፡፡ ባለፈው ማክሰኞ ጥቅምት 6 ቀን 2016 ዓ.ም፣ በጋዛ የሚገኘው የአል-አህሊ ሆስፒታል ላይ በደረሰ ፍንዳታ 500 የሚደርሱ ፍልስጤማውያን መገደላቸውን ታጣቂው ቡድን  ሃማስ ያስታወቀ ሲሆን፤ ትክክለኛውን ቁጥር በተመለከተ ከገለልተኛ ወገን ማረጋገጥ አልተቻለም ተብሏል፡፡ የጥቃቱ ሰለባዎች በሆስፒታሉ ተጠልለው የነበሩና ህክምና የሚጠባበቁ ፍልስጤማውያን ነበሩ ተብሏል፡፡
 ሃማስ ለጥቃቱ እስራኤልን ተጠያቂ ያደረገ ሲሆን፤ እስራኤል በበኩሏ ፍንዳታውን ያደረሰው የፍልስጤሙ ኢስላሚክ ጂሃድ ነው ስትል ወንጅላለች፡፡ ለዚህም የተለያዩ ማስረጃዎችን አቅርባለች፤ የተጠለፈ የሃማስ ታጣቂዎች ንግግር ኦዲዮን ጨምሮ፡፡  
የጋዛው ፍንዳታ በተሰማ በጥቂት ሰዓታት ውስጥ ከሊባኖስ እስከ ዌስት ባንክ እንዲሁም  ዋሺንግተን ዲሲ ድረስ ከፍተኛ የህዝብ ቁጣና ተቃውሞ ተቀጣጥሏል፡፡ የዓለም አገራትና መንግስታትም ጥቃቱን ክፉኛ አውግዘዋል፡፡ የዓለም ጤና ድርጅት፣ አውሮፓ ህብረት፣ አፍሪካ ህብረት፣ ቱርክ፣ ኢራን፣ ኳታር፣ ፈረንሳይ፣ዮርዳኖስ፣ ግብጽና ሌሎች በርካታ አገራት አሰቃቂውን የጋዛ ፍንዳታ በማውገዝ፣ የጥቃቱ ፈጻሚ ናት ያሏትን፣  እስራኤልም አጥብቀው ኮንነዋል፡፡
በቤሩት መዲና ሊባኖስ፣በጋዛ በደረሰው ፍንዳታ የተቆጡ በሺዎች የሚቆጠሩ ተቃዋሚዎች፤  በአሜሪካና ፈረንሳይ ኤምባሲዎች አቅራቢያ ተሰባስበው እስራኤልን ያወገዙ ሲሆን ለፍልስጤምም አጋርነታቸውን ገልጸዋል፡፡ የጸጥታ ሃይሎች፣ ረብሻና ግጭት ለመፍጠር በሞከሩ ተቃዋሚዎች ላይ አስለቃሽ ጭስ ተኩሰዋል፡፡
በዮርዳኖስ አማን ደግሞ ከ1ሺ በላይ የሚሆኑ ሰዎች በእስራኤል ኤምባሲ ደጃፍ ላይ በመሰባሰብ ለፍልስጤምና ሃማስ ድጋፋቸውን የገለጹ ሲሆን፤ እስራኤልን ክፉኛ አውግዘዋል - “ሞት ለእስራኤል!” በማለት፡፡ የእስራኤልንና የአሜሪካንን ሰንደቅ አላማ ሲያቃጥሉም ተስተውለዋል። ተቃዋሚዎች በእስራኤል ኤምባሲ ላይ ጥቃት ለመፈጸም ቢሞክሩም፣ የፀጥታ ሃይሎች አስለቃሽ ጭስ በመተኮስ ተቃውሞውን ለመበተን ችለዋል፡፡
በቱርክ ኢስታንቡል በሺዎች  ተቃዋሚዎች በእስራኤል ቆንስላ አካባቢ ተሰባስበው በጋዛ  ለደረሰው ፍንዳታ እስራኤልን ያወገዙ ሲሆን፤ ለፍልስጤም ድጋፋቸውን አሰምተዋል፡፡ ተቃዋሚዎቹ ወደ ቆንስላው ህንፃ ድንጋይ፣ ዱላና ተቀጣጣይ ነገሮችን ሲወረውሩም ታይተዋል፡፡ በተመሳሳይ በፈረንሳይ ኤምባሲ አቅራቢያ የተሰባሰቡ ተቃዋሚዎች፤ እስራኤል በጋዛ ላይ ፈጽማዋለች ያሉትን ጥቃት በህብረት አውግዘዋል፡፡ አንድ ተቃዋሚ ለጋዜጠኛ በሰጠው አስተያየት፤ የቱርኩ ፕሬዚዳንት፣ እስራኤልን ከማውገዝ ባለፈ ከድርጊቷ እንድትታቀብ የሚያደርጋት ተጨባጭ እርምጃ እየወሰዱ አይደለም ሲል ወቅሷቸዋል፡፡
 ባለፈው ረቡዕ በዋሺንግተን ዲሲ፣ አፍቃሬ - ፍልስጤም የሆኑ በርካታ የአሜሪካ- አይሁድ ተቃዋሚዎች፣ ካፒቶል  ህንጻ ውስጥ ተሰባስበው በመግባት፣ አስራኤል በጋዛ የምትፈጽመውን የአየር ድብደባ እንድታቆም ጠይቀዋል - በጭብጨባና በመዝሙር ታጅበው፡፡ “አሁኑኑ የተኩስ አቁም፤ ነፃነት ለፍልስጤማውያን፤ የዘር ማጥፋት ወንጀል ይቁም” የሚሉ መፈክሮችንም  አሰምተዋል፡፡ በመጨረሻ ግን ፖሊስ ለመበተን አሻፈረኝ ብለዋል ያላቸውን 300 የሚደርሱ ተቃዋሚዎች፣ በቁጥጥር ሥር  ማዋሉ ታውቋል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ሦስቱ ደግሞ የፖሊስ መኮንንኖች ላይ ጥቃት በመፈጸም መከሰሳቸውን የካፒቶል ፖሊስ አስታውቋል፡፡
 በተቃውሞ ትዕይንቱ ከተሳተፉት አንዱ የሆነው  ማቲው ሆህ፤ ከኖርዝ ካሮሊና ድረስ የመጣው በተቃውሞው ላይ ለመናገራል፡፡ በኢራቅና አፍጋኒስታን ጦርነቶች ውስጥ  መሳተፉን የገለጸው ማቲው፤ አሁን ግን ይጸጽተኛል ብሏል፡፡
ባለፈው ማክሰኞ በጋዛ ሆስፒታል ላይ ለደረሰው ፍንዳታ፣ ሃማስ እስራኤልን ተጠያቂ ለማድረግ ያለ ወትሮው ተጣድፏል የሚሉ የፖለቲካ ተንታኞች፤ የሟቾችን ቁጥርም በዚያ ፍጥነት ይፋ ማድረጉ ጥርጣሬ እንደፈጠረባቸው ይገልጻሉ፡፡ ከሁሉም ደግሞ ዓለማቀፍ ሚዲያዎች ከሃማስ የተሰጠውን መግለጫ ተቀብለው እንደ ተዓማኒና ገለልተኛ መረጃ በእርግጠኝነት ማሰራጨታቸው ብዙዎችን አስገርሟል፡፡ “እስራኤል በጋዛ ሆስፒታል ላይ ባደረሰቸው ፍንዳታ 500 የሚደርሱ ፍልስጤማውያን ተገደሉ” የሚለው መረጃ በጥድፊያ መሰራጨቱ፣ በመካከለኛው ምስራቅ ከፍተኛ ቁጣና ተቃውሞ ቀስቅሷል የሚሉ አስተያየት ሰጪዎች፤ የሃማስም ዓላማ በትክክል ይኸው ነበር ይላሉ፤ አጋጣሚውን በመጠቀም የአረቡ ዓለም በእስራኤል ላይ በጋራ እንዲነሳ ማድረግ፡፡
ሃማስ የጋዛው ሆስፒታል ፍንዳታ የደረሰው እስራኤል በተኮሰችው የሮኬት ጥቃት ነው ሲል ቢከስም፤ እስራኤል ግን ክሱን በማጣጣል፣ ፍንዳታውን ያደረሰው የፍልስጤሙ ኢስላሚክ ጂሃድ መሆኑን በማስረጃ አስደግፋ አቅርባለች፡፡ የእስራኤል ጦር ሰራዊት ቃል አቀባይ ሰሞኑን በሰጡት መግለጫ፣ ሮኬቱ ከእስራኤል የተተኮሰ ሳይሆን ከጋዛ የተተኮሰ ነው ብለዋል። የድምፅ፤ የምስልና የኢንተለጀንስ ማስረጃዎችንም ይፋ አድርገዋል፡፡
የጋዛ ሆስፒታል ፍንዳታን ተከትሎ፣ በተለይ በመካከለኛው ምሥራቅ የተቀሰቀሰው ከፍተኛ ቁጣና ተቃውሞ፣ የምዕራብ አገራት ለዜጎቻቸው የጉዞ ጥንቃቄ አለርት እንዲያወጡ አስገድዷቸዋል፡፡ በተለይ ደግሞ ወደ ሊባኖስ ከመጓዝ እንዲታቀቡ እያሳሰቡ ነው፡፡ የአሜሪካ ስቴት ዲፓርትመንት ሰሞኑን ባወጣው የማስጠንቀቂያ አለርት፤ በሊባኖስ የሚገኙ አሜሪካውያን አስቸጋሪ ነገር ተፈጥሮ በረራ ከመታገዱ በፊት በፍጥነት አገሪቱን ለቀው እንዲወጡ አሳስቧል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ ባለፈው ረቡዕ ለ7 ሰዓት ያህል በእስራኤል ጉብኝት ያደረጉት የአሜሪካው ፕሮዚዳንት ጆ ባይደን፣ ከእስራኤሉ ጠ/ሚኒስትር ቤንጃሚን ኔትንያሁና ከሌሎች ከፍተኛ የአገሪቱ ባለሥልጣናት ጋር ተወያይተዋል፡፡ ሃማስ በእስራኤል ህጻናት እናቶችና አረጋውያን ላይ በጅምላ የፈጸመውን  አስከፊ ጥቃት አጥብቀው ያወገዙት ባይደን፤ “ሽብርተኛነት አያሰንፍም፤ አሸናፊው  ነጻነት ነው” ብለዋል፡፡
ጆ ባይደን ከውይይቱ በኋላ በሰጡት መግለጫ፤ የጋዛው ፍንዳታ የተፈፀመው ሃማስ እንደሚለው በእስራኤል ሳይሆን፣ በሌላ ታጣቂ ቡድን መሆኑን ተገንዝቤአለሁ ብለዋል፡፡ “ማክሰኞ በጋዛ ሆስፒታል ላይ በደረሰው ፍንዳታ የብዙዎች ህይወት በመጥፋቱ ተቆጥቻለሁ፤ አዝኛለሁም። ያሉት ማስረጃዎች ግን የሚያመለክቱት፣ ፍንዳታው የደረሰው በጋዛ በሚገኝ የሽብርተኛ ቡድን በተተኮሰ ሮኬት መሆኑን ነው፡” በማለት እስራኤልን ከተጠያቂነት ነፃ አድርገዋታል፡፡
ፕሬዚዳንቱ፤ ከእስራኤሉ ጉብኝታቸው በኋላ በዮርዳኖስ አማን ከተማ፤ ከግብጽ፣ ፍልስጤምና ዮርዳኖስ መሪዎች ጋር ተገናኝተው፣ በጋዛ ጉዳይ ለመምከር ቀጠሮ ይዘው እንደነበር ይታወቃል፡፡ የጋዛውን አስከፊ ፍንዳታ ተከትሎ ግን የአረብ መሪዎቹ ከባይደን ጋር የሚያደርጉትን ስብሰባ መሰረዛቸውን  አስታወቁ፡፡ ይህም የሃማስ ሃሰተኛ መግለጫና የሚዲያዎች ሙያዊ ሥነምግባር የጎደለው  ዘገባ ውጤት ነው ይላሉ - የፖለቲካ  ተንታኞች፡፡
በሌላ በኩል፤ 20 የሰብአዊ እርዳታ የጫኑ ተሽከርካሪዎች ወደ ጋዛ እንዲገቡ ግብፅ መስማማቷን የአሜሪካው ፕሬዚዳንት  ባለፈው ረቡዕ  አስታውቀዋል፡፡ ከእስራኤል ወደ ዋሺንግተን ሲመለሱ በፕሬዚዳንቱ አውሮፕላን “ኤር ፎርስ ዋን” ውስጥ ሆነው ለሪፖርተሮች  ማብራሪያ የሰጡት ጆ ባይደን፣ ከግብፁ ፕሬዚዳንት አብደል ፋታህ አል-ሲስ ጋር፣ ፍልስጤማውያን ሰብአዊ እርዳታ በሚያገኙበት ሁኔታ ላይ በስልክ መወያየታቸውን የገለጹ ሲሆን፤ የግብፁ ፕሬዚዳንት የተወሰኑ ሰብአዊ እርዳታዎች በራፋህ በኩል ወደ ጋዛ እንዲገባ በመፍቀዳቸው፣ “ከፍተኛ ምስጋና ይገባቸዋል” ሲሉ አድናቆታቸውን ገልጸዋል፡፡ እርዳታውን የተባበሩት መንግስታት ሠራተኞች ጋዛ ላይ ተቀብለው ለፍልስጤማውያኑ ያከፋፍሉታል ተብሏል።
ከሁለት ሳምንት በፊት ልክ በዛሬው ዕለት፣ ኦክቶበር 17 ቀን 2023 ዓ.ም ታጣቂው የሃማስ ቡድን በእስራኤል ላይ ድንገተኛ ጥቃት መፈጸሙን ተከትሎ፣ ከሁለቱም ወገን ከፍተኛ ዕልቂትና ውድመት እየደረሰ ሲሆን፤ እስካሁን 3ሺ 500 ገደማ ፍልስጤማውያን መገደላቸውንና ከ1ሺ 400 በላይ እስራኤላውያን መሞታቸው ተዘግቧል። ከሁለቱም ወገን ወደ 15ሺ ሰዎች ገደማ ቀላልና ከባድ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል ተብሏል፡፡
***

 እጅግ የሚፋቀሩ ባልና ሚስት በአንድ የገጠር መንደር ይኖራሉ። ባል ገበሬ ነው። ቀኑን ሙሉ ሲታትር ውሎ፣ ያረሰውን አርሶ ቤቱ ሲደርስ፣ ሚስት ለእግሩ ውሃ አሙቃ እግሩን አጥባ ራቱን አብልታ፣ አሳስቃ-አጫውታ ታስተኛዋለች። እሱም፣ የፍቅሯን ብዛት ለመግለፅ፣
“እንዲያው አንቺዬ አንቺ ባትኖሪ ምን ይውጠኝ ኖሯል?” ይላል።
“እንዴት? ለምኑ?” ትላለች፤ ጥያቄውን በጥያቄ መልሳ።
“ዘንድሮ እንደሰማዩ ባዶነትና እንደመሬቱ አልታረስ ማለት’ኮ የምንልሰው የምንቀምሰው አይገኝም ነበር። አንቺ ግን ያለውን አብቃቅተሽ፣ ስቀሽ አሳስቀሽ ጠግበን እንድናድር ታደርጊያለሽ”
“ያ የእኔ ሳይሆን የአምላክ ፀጋ ነው። ሁለተኛ ደግሞ የአንተ ድካም ፍሬ ነው። ይልቅ ተመስገን በልና ተኛ! ጎረቤታችንን አያ እገሌን አታየውም? ይጭነው አጋሰስ፣ ይለጉመው ፈረስ፣ ይልከው አሽከር ሞልቶ ተርፎት ሲያበቃ፣ ጧት ማታ አምላክን ሲያማርር እንዲህ ደህይቶ ቁጭ ብሎ ቀረ”
“እሱስ እጅግ ያበዛዋል”
“ዛሬ ጠዋት በተስኪያን ቄሱን ሲጨቀጭቃቸው ነበር። እሳቸው ግን የልብ- አውቃ አደሉ አንጀቴን አራሱኝ።”
“ምን ብለው?”
“ምን ይሆንልሃል፤አጅሬ እንደተለመደው ከስብከት በኋላ ይጠብቃቸዋል። እኔም ቤት መጥተው ጠበል እንዲረጩ ልነግራቸው እዚያው ቆሜያለሁ። ጨርሰው ሲመጡ እንዲህ ይላቸዋል። - “አባ ሰሞኑን ክፉ ክፉ ህልም እያየሁ ተቸግሬአለሁና እስቲ ይፍቱልኝ?”
“ምን ችግር ገጠመህ፣ ምን ህልም አየህ አያ?” አሉት ቄሱ።
“ይሄውሎት አባ፤ በህልሜ በየማታው አንድ በሬ ይመጣብኛል። ቀንዱ በጣም የሾለና አስፈሪ ነው። እየመጣ ሊወጋኝ ሲያባርረኝ አያለሁ። አሁን አሁንማ ጭራሽ ሩጫውና ፍጥነቱ አያድርስብዎት! ይኸው ሣምንቴ ስሮጥ ስባረር! ከእንቅልፌ  እየባነንኩ ስጨነቅ አድራለሁ!! እንደው ምን ባደርግ ይሻለኛል አባ?
“አንተ መኝታህ ምን ላይ ነው?”
“ኧረ የረባም መኝታ የለኝ አባ። እንዲያው የሣር ፍራሽ ላይ ነው የምተኛው።”
“ታዲያ ዋና ቀለቡ ላይ እየተኛህ ዱሮስ ላያባርርህ ኖሯል እንዴ?”
***
በሰው ቀለብ ላይ መተኛት በሰው ህይወት ሂደት ላይ ጋሬጣ መሆን ነው። በሰው እንጀራ መግባትም የዚያኑ ያህል የሌላውን ህይወት መቀማት ነው። ሠራተኛ የሚጠበቅበትን ያህል ሥራ ሰርቶ፣ የሚገባውን መብትና ጥቅም ማስከበር ይፈልጋል። ይህ መብትና ጥቅም ከሚሰራው ስራ ጋር ሁነኛ ትስስር ያለው እንደመሆኑ፣ አንዱ ሲጎድል ሌላኛው መነካቱ፣ ያንዱ ፍሰት ሲቋረጥ የሌላኛው ቧንቧ እንደሚዘጋ አያጠያይቅም።
በሀገራችን ሥራና ሠራተኛ በትክክልና በውል ተገናኝተዋል ለማለት አይቻልም። ሥራና ሠራተኛ የሚገናኙበት ቦታ ደግሞ የሥራ-ብቃት ያለው ሠራተኛ ሞልቶ ተትረፍርፏል ለማለትም ከቶ አያስደፍርም። በዚያ ላይ ሁለቱም በወግ ሰምረው የተገናኙበት ቦታ ደግሞ ጥሩ የሥራ ከባቤ- አየር (Atmosphere) አይኖርም። የግሰብ አለቆች ማንነት፣ የፖለቲካው ንፋስ፣ የሥራ ባህል ድክመት፣ የቢሮ ሥርዓት ማጣት ወዘተ… ብርቱ እንቅፋት ሆነውበት ይገኛል። በዚህ ምክንያት ብዙ ስፍራ ፍየል ወዲህ ቅዝምዝም ወዲያ ሲሆን ይታያል። የታሰበው ግብ አይመታም። እድገት የለም። የሠራተኛ መማረርና ብሶት የዕለት- የሠርክ እሮሮ ይሆናል። ሁሉም በወጉና በሥርዓቱ በቅርበት መመርመር አለባቸው።
ዋናው ባለጉዳይ እያለ አጃቢው የሚያስቸግርበት ሁኔታ ሞልቷል። የሚመለከተው ሹም እያለ ምንዝሩ አለሁ አለሁ የሚልበት ሁኔታ ጎልቶ ይታያል። ትክክለኛው ሰው በትክክለኛው ቦታ የሚለው መርህ፣ አንዱ መሰናከያው ይሄ ነው። “የምትወልደው ገበያ ሄዳ የምታዋልደው ቤት አልጋ ላይ ትተኛለች” የሚባለውም ይሄ ነው። አጃቢና አጫፋሪ በበዛ ቁጥር ዋንኛው ሰው ኃላፊነቱን በአግባቡ የሚወጣበትን እድል ያጣብቡበታል። አንድም ደግሞ ከጳጳሱ በላይ ካቶሊክ የሆኑ ሰዎች ጣልቃ እየገቡ ሥራውን ያበላሹበታል ማለት ነው። እንዲህ ያለው ጉዳይ በተለይ በፖለቲካው መስክ ሲታይ ደግሞ የበለጠ ጎጂ ይሆናል። በሀገራችን በታዩት ለውጦች ውስጥ ሁሉ፣ ዋናው የፖለቲካ ሃላፊ ወይም መሪ በእርጋታ በሚወያይበት ቦታ፣ ካድሬው ከልክ ያለፈ ልፈፋና መፈክር ሲያበዛ፣ ዋናው ባለሥልጣን በመግባባትና በመቻቻል ይፈታል የሚለውን ጉዳይ ካድሬው ጦር ሲሰብቅለት ይገኛል።
ይህም  በወጉ ካልተያዘ ለማናቸውም ሥራ እንቅፋት መሆኑ አሌ አይባልም።
ባልተጋበዙበት ድግስ የሚመጡ፣ የማይመለከታቸው ጉዳይ ላይ ንግግር የሚያደርጉ፣ ባልሰለጠኑበት ሙያ ከባለሙያው በላይ ዘራፍ የሚሉ አያሌ ናቸው። እነዚህም ሥራን በማበላሸት ረገድ ጉልህ ድርሻ አላቸው። እንደዚህ ያሉት “ወይ ትንሽ የምትበላ አይደለህ”፣ ወይም ከበላን በኋላ አልመጣህ” የሚባሉት ዓይነት ሲሆኑ፤ በራሳቸውና በተመደቡበት ስራ ላይ ሳይሆን በቅልውጥ ሥራ የተካኑ ናቸው። ለዚያውም ድግስ ያበላሻሉ። ገበታ ያዘበራርቃሉ። ሥራና ሠራተኛን ያለያያሉ።
በማናቸውም የሥራ መስክ ላይ፣ በቢሮ አካባቢም ሆነ በፖለቲካው የሥልጣን መዋቅር ዙሪያ እጅግ አስቸጋሪና ጎጂ የሆነው ባህል፣ ጥፋትን በሌሎች ላይ የመላከክ (Blame-Shifting) ተግባር ነው።  ይህ አሉታዊ ተግባር ከልሂቅ እስከ ደቂቅ፣ ከትላልቅ የፖለቲካ መሪዎች እስከ አማካዩ ሟች ፍጡር (Average mortal) ድረስ ሥር-የሰደደ አባዜ ነው።
ቀበሌው በወረዳ፣ ወረዳው በቀጠና፣ ቀጠው በመስተዳድሩ ያላክካል። ሚኒስትሩ በምክትሉ፣ ምክትሉ በሥራ አስኪያጂ፣ ሥራ-አስኪያጁ በመምሪያው እያለ እስከ ዜጋው እርከን ድረስ ይወርዳል። ሁሉም “እሱ ነው!” እንጂ “እኔ ነኝ” ለማለት ዝግጁ አይደለም። አንዱ አንደኛውን “ባጋለጠ” ቁጥር የራሱን ንፅህናና ትክክለኝነት ያረጋገጠ እየመሰለው በግብዝነት መደገጉ የተለመደ ክስተት ሆኗል። የሌሎችን ጉድለት በማጉላት የራስን ትልቅነት ማሳየት የሚቻል የሚመስላቸው አያሌ ናቸው። ይህ ደግሞ የአሉታዊነት ባህሪን እያደበረ አገርን እያኮሰሰ ወደ ውድቀት፣ ህዝብ እያጎሳቆለ ወደ ድቀት የሚያመራ፣ ከቶም በቀላሉ የማንሽረው ባህል ነው።
 ዛሬ እኛ በሌላው ላይ ክፉ ስናደርግ ባህሉን ማጠንከራችን ነውና፣ ነገ በእኛ ላይ ላለመድረሱ ምንም ዋስትና እንደማይኖር ልብ ማለት ያስፈልጋል። ለጊዜው እንደ ህልውና የምንቆጥራቸው ትናንሽ ድሎች፣ ከቶም ለጠዋት ድምቀትና መታያነት ያገለግሉ እንደሆነ እንጂ ማምሻው ላይ በዋናው ሰዓት ከተጠያቂነት አያድኑም። “ቀርክህ ጠዋት ለብሶ ማታ ይራቆታል” እንደሚባለው መሆኑ ነው። መንግሥታዊው ፓርቲ በተቃዋሚ፣ ተቃዋሚው በመንግሥታዊ ፓርቲ ላይ ድክመቱን አያሻገረና እያጋባ ይኖራል። የራስን ሥራ የሌላው ሥራ አድርጎ ከወቀሳ ማምለጥ እንደ ዋና ኑሮ ተይዟል። የራስን ጥፋትና ወንጀል የሌላው አድርጎ፣ ሌላውን ማስገምገም ከቀን ቀን እየከፋ የመጣ የአገር በሽታ ሆኗል- እንደቆላ ቁስል አልድን ያለ እክል ነው! በወደቀው መንግሥት በተሸነፈው ፓርቲ፣ በተባረረው ሠራተኛና በተጣሉት ወገን ላይ ጥፋትን እያላከኩ መኖር  እጅግ ክፉ እርግማን ነው። ወላይታ ሲተርት “ወተት የጠጣ ውሻ ሰርዶ በበላ አህያ አፍ ይጠርጋል” የሚለውም ይሄንኑ ነው።

“ጥያቄው አገሪቱ ከአጎራባቾቿ ጋር ያለትን የቆየ ቁርሾ እንደመቀስቀስ ይቆጠራል”
                            
           ጠ/ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ  ሰሞኑን ለጎረቤት ሀገራት  ያቀረቡትን  የወደብ ባለቤትነት ድርድር ጉዳዪ የሚመለከታቸው ሁሉም አገራት ውድቅ አደረጉት ። ኤርትራ  ጅቡቲና  ሱማሊያ  የጠቅላይ ሚኒስትሩን ጥያቄ እንደማይቀበሉ ይፋ አድርገዋል ።   የወደብ ባለቤትነት  ጥያቄው  አገሪቱ  ከአጎራባቾቿ ጋር ያለትን የቆየ ቁርሾ እንደመቀስቀስ ይቆጠራል ተብሏል ።


ሱማሊያ  ከጠ/ሚኒስትር የቀረበውን የወደብ ባለቤትነት ውይይት እንደማትቀበለውና የወደብ ጉዳይ ልክ እንደ ሌሎች የሉኣላዊነት ጉዳዮች የሚታይ ነው ማለቷን ብሉንበርግ ዘግቧል ።የሶማሊያ ፕሬዝዳንት አማካሪ አብዲራህማን አብዲሻኩር  በኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት በኩል በተደጋጋሚ የወደብ ባለቤትነትን አስመልክተው የሚሰጡትን አስተያየት እንዲሁ ችላ  የሚባል አለመሆኑንና   መንግስታቸው ሁኔታውን በትኩረት እንደሚከታተለው መግለፃቸውን ሶማሊ ጋርድያን በድረገጹ አስነብቧል።

የሶማሊያ ብሔራዊ የደህንነት መስሪያ ቤት (NISA) ምክትል ዳይሬክተር የነበሩት ኢስማኤል ኦስማን በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ በቀይባህር ዙሪያ የወደብ ባለቤት ለመሆን እየሄደችበት ያለው መንገድ አለም አቀፍ አካሄድን የጣሰ ነው ሲሉ አስጠንቅቀዋል።ኢስማኤል ኦስማን በሰጡት ትንታኔ፤ የአለም ሀገራት የራሳቸው የሆነ በርካታ የተፈጥሮ ሀብት እንዳላቸው ጠቁመው፤ ሀገራት ይህንን የተፈጥሮ ሀብት ማለትም ነዳጅም ሆነ ወደብ በአለም አቀፍ የትብብርና በሰላማዊ መንገድ በሽያጭና በተለያየ መንገዶች በጋራ እንደሚጠቀሙ አስታውቀዋል።


ከዚህ ውጭ ግን በጉልበት ለማግኘት መጣር አለም አቀፍ አካሄድን የጣሰ ነው ሲሉ ተችተዋል።
ጠ/ሚኒስትር በቀይባህር ዙሪያ የወደብ ባለቤት ለመሆን ያቀረቡት ሀሳብና ለማግኛነት ያቀረቡት አካሄድ የተባበሩት መንግስታት ቻርተርንና አለም አቀፍ ህግን የጣሰ ነው ሲሉ ገልጸዋል።
የቀድሞ የሶማሊያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ የነበሩት ባላል ሞሃመድ ኩስማን በበኩላቸው፤ የጠ/ሚኒስትሩ የወደብ ባለቤትነት ሀሳብ፣ ኢትዮጵያ ከአጎራባቾቿ ጋር ያለትን የቆየ ቁርሾ እንደመቀስቀስ ይቆጠራል ሲሉ ተችተዋል።
ባላል ሞሃመድ፤ ሂራን ድረገጽ ላይ ባሰፈሩት ጽሁፍም ጠ/ሚኒስትር አብይ ዛይላ ወደብን አስመልክቶ የሰጡት አስተያየት፣ በብዙ ጥረት ወደ መልካም ግንኙነት የተመለሰውን የሶማሊያና ኢትዮጵያን ግንኙነት የሚያበላሽ ነው ሲሉ አሳስበዋል።


ጉዳዩ ቀጠናውን ወደ ቀውስ የሚወስድ ነው ሲሉም አስጠንቅቀዋል። ጠ/ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ  ሰሞኑን ለጎረቤት ሀገራት  ያቀረቡትን  የወደብ ባለቤትነት ድርድር ጉዳይ የተቃወመችው ሌላኛዋ አገር ጅቡቲ ነች ። የጅቡቲ ፕሬዝዳንት እስማኤል ኡመር ጊሌ ከፍተኛ አማካሪ የሆኑት አሌክሴስ ሞሃመድ፤ ጅቡቲና ኢትዮጵያ ጠንካራ የሆነውን ግንኙነታቸውን አስጠብቀው የሚኖሩ ሀገራት  መሆናቸውን ጠቅሰው፤ “ ነገር ግን ጅቡቲ ሉአላዊ ሀገር ናት፤ የግዛት አንድነታችን ዛሬም ሆነ ወደፊት ጥያቄ ውስጥ የሚገባ አይደለም” በማለት ጥያቄው በሀገራቸው በኩል ተቀባይነት እንደሌለው መግለጻቸውን ብሉምንበርግ ዘግቧል ። ኤርትራ በማስታወቂያ ሚኒስትሯ በኩል በሰጠችው ምላሽ፤ ኤርትራ የኢትዮጵያን የወደብ ባለቤትነት ጥያቄ እንደማትቀበለውና ቦታ እንደማትሰጠው ገልፃለች፡፡ ኤርትራ አክላም፤ በባሕር በር ዙሪያ የተነሳው ትርክት “ከመጠን ያለፈ” እና “ግራ የሚያጋባ ነው” ስትል ጉዳዩን ውድቅ አድርጋዋለች ።

ምግብ በልጆች ሁለንተናዊ እድገት ላይ ያለው ሚና ከፍተኛ መሆኑ ይታወቃል። በተለይ ልጆች ከተወለዱበት እስከ 2 አመት እድሜያቸው ድረስ ያለ አመጋገባቸው ለአእምሮአዊም ሆነ አካላዊ እድገታቸው እጅግ ወሳኝ ነው፤ ስለዚህ በዚህ ወቅት አስፈላጊው ሁሉ ተሟልቶላቸው እንዲያድጉ በልጆች ዙርያ ያሉ ሁሉ ኃላፊነት መውሰድ ይኖርባቸዋል።

በቅድሚያ ልጆችን በምንመግብበት ወቅት ማወቅ ከሚገቡን ነገሮች መካከል ማሳተፍ (responsive feeding) የምንለውን ነው ፤ ይህም ልጆች ምግብን እንዲሁም የአመጋገብ ሂደትን እንዲወዱት ይረዳናል።
ልጆችን ስንመግብ የስነ ልቦና እና ማህበራዊ እድገታቸውን ታሳቢ ያደረጉ መመርያዎችን (principles of psychosocial growth and development) መከተልም እጅግ አስፈላጊ ነው፤ ምክንያቱም በዚህ እድሜአቸው ከአመጋገብ በተጨማሪ ለእነርሱ ብዙ አይነት ክህሎቶችን (life skills) የሚማሩበት ጊዜ ስለሆነ ነው።

ልጆችን ስንመግብ ተሳትፎአቸውን የምንጨምርባቸው መንገዶች ምን ምን ሊሆኑ ይችላሉ?

1ኛ. ልጆች እንደየእድሜአቸው ራሳቸውን ችለው እንዲመገቡ ማበረታታት።
ጨቅላ ህፃናት በትልልቅ ሰዎች መመገብ ሲኖርባቸው ፤ ልጆች እድሜያችው ከፍ ሲልና በእጅ የሚያዝ ምግብ ካስጀመርናቸው በኋላ ግን በራሳቸው እንዲበሉ ማበረታታት እና ማገዝ (assist) ብቻ በቂ ነው፤ ሁል ጊዜ በእኛ እጅ ብቻ እንዲመገቡ መፈለግ የለብንም (ይህም ምግባቸውን እንዲወዱት እና በአመጋገብ ስርዓታቸው ላይ ኃላፊነት እንዲሰማቸው ከማድረግም በላይ በራስ መተማመናቸው እንዲጨምር ያግዛል)

2ኛ. የልጆችን የምግብ ምርጫ ማስፋት።
አንዳንድ ጊዜ ልጆች የምናቀርብላቸውን ምግብ ያለመፈለግ ሊያሳዩ ይችላሉ፤ በዚህ ጊዜ አልወደዱትም ብለን ሙሉ በሙሉ የምንተው / የምንቀይር ከሆነ ጠባብ የምግብ ምርጫ እንዲኖራቸው ወይም picky eaters እንዲሆኑ ስለሚያደርጋቸው በተለያየ ጊዜ በተለያየ አዘገጃጀት ደጋገመን መሞከር ይኖርብናል። ይህም የምግብ ምርጫቸውን እንዲያሰፉ እንዲሁም ከየምግቡ አይነት ማግኘት ያለባቸውን ጥቅም ሁሉ እንዲያገኙ ይረዳቸዋል። እንዲሁም ይህንን በተደጋጋሚ በማድረግ ባህርይ አድርገው እንዳይዙትም ጭምር ያግዛል።
   
3ኛ. በምግብ ሰዓታቸው ተግባቦትን ማዳበር።
ለልጆች የምግብ ጊዜ ከመብላትም ባለፈ ከቤተሰባቸው እና አካባቢያቸው ካሉ ሰዎች ብዙ የሚማሩበት ስለሆነ እያዋራናቸው፣ እያጫወትናቸው እንዲሁም በተለያየ በሚገባቸው መንገድ communicate እያደረግናቸው ልንመግባቸው እና አብረናቸው ልንሆን ያስፈልጋል፣ በዚህ ጊዜ የተለያዩ ማህበራዊ ክህሎቶችን (social skills) እና ፍቅርን ይማራሉ፤ ስለ ምግብም መጥፎ አመለካከት ይዘው እንዳያድጉ ያደርጋቸዋል። ልጆችን በሚመግቡበት ጊዜ ከልጅዎ ጋር ጥሩ የጋራ ፣የመቀራረብ እና የአብሮነት ወይም bonding ጊዜ ያሳልፉ።

4ኛ. ልጆችን በማንኛውም ምክንያት በአመጋገብ ሁኔታቸውና በምግብ ምርጫቸው ከሌሎች ልጆች ጋር አለማወዳደር።
በማንኛውም ምክንያት በልጆች ላይ ይህን ማድረግ በፍጹም አያስፈልግም፤ ይህ ይበልጥ ምግብን እየጠሉ እንዲሄዱ እና ነፃነት እንዳይሰማቸው ከማድረጉም በላይ በራስ መተማመናቸውን የሚያወርድ ተግባር ስለሆነ ፈጽሞ ልናደርገው አይገባም።

5ኛ. ልጆችን በግድ እኛ በምንፈልገው መንገድ እና ሁኔታ እንዲመገቡ አለማድረግ።   
ልጆችን ስንመግብ ማስገደድ ተገቢ አይደለም ፤ ምክንያቱም የቀረበውን ምግብም ሆነ የምግብ መብላት ስርዓቱን እንዲጠሉት ሊያደርግ ስለሚችል ነው። ልጆች እያጎረስናቸው እንዲመገቡ ማድረግ ያለብን በእጅ ተይዘው የሚበሉ ምግቦች እስኪጀምሩ ድረስ ብቻ ነው (ይህም ማለት እድሜያቸው 9 ወር እስኪሞላ ነው)፤ ከዚያ በኋላ ግን ለራሳቸው በሰሃን ሰጥተን በሚፈልጉት መንገድ እንዲመገቡ መፍቀድ ይኖርብናል።

በዚህ ጊዜ በሚገባ መረዳት ያለብን ነገር ቢኖር ፤ እኛ ባሰብነው መንገድ ላይበሉ ይችላሉ ማለትም፦
• ረዘም ያለ ጊዜ ሊወስዱ ይችላሉ
• ራሳቸውን እና አካባቢያቸውን ሊያቆሽሹ ይችላሉ
• ምግባቸውን ሊደፉ ይችላሉ ወይም በተለያየ ምክንያት እኛ በቂ ብለን በምናስበው መንገድ ላይመገቡልን ይችላሉ።

ነገር ግን ታግሰን እንዲለምዱ ማድረግ ይኖርብናል፣ እንዲሁም እርዳታችንን ሲፈልጉ ብቻ ልናግዛቸው ይገባል። ይህም በተመሳሳይ የኃላፊነት እና ተቆጣጣሪነት (control) ስሜት እንዲኖራቸው ስለሚያደርግ የምግብ ጊዜአቸውን እንዲወዱት እና እንዳይጨነቁ ይረዳል ፤ በጊዜ ራሳቸውን እየቻሉ  ስለሚሄዱም ለእኛም በአመጋገባቸው ዙርያ ጭንቀትን በሂደት ይቀንስልናል።
ከዚህም ጋር በተያያዘ ደግሞ ምግብ ሲበቃቸው ያላቸውን ስሜት ልንረዳቸው ይገባል።

6ኛ. ልጆች በልተው ሳይጨርሱ ከስር ከስር ማጽዳት (እጃቸውን ፣ ፊታቸውን እና አካባቢያቸውን መጠራረግ) የለብንም ፤ ይህም ምግብን በትክክለኛው መንገድ እንዳይረዱት ያደርጋቸዋል።

7ኛ. ለልጆች ብቻቸውን ምግብ ከመስጠት ይልቅ በተቻለ ጊዜ ሁሉ ቤተሰብ ምግብ በሚበላበት ሰዓት አብረው እንዲበሉ ማድረግ የምግብ ፍላጎታቸው እንዲጨምር፤ ትኩረታቸው ምግቡ ላይ ብቻ እንዲሆንና ለብዙ ምግቦች ተጋላጭ እንዲሆኑ (exposure እንዲኖራቸው) ይረዳል።

ተጋላጭነት (Exposure) ስንል ግዴታ ስለሚበሉት ብቻ ሳይሆን አካባቢያቸው ላይ የቀረቡ ምግቦችን ማየትን፣ ማሽተትን፣ መንካትን፣ መቅመስን ወይም መሞከርን ሁሉ እንደሚያካትት ልንገነዘብ ይገባል።

በተጨማሪም ልጆች ምግብ ሲበሉ እንደ ቴሌቪዥን ፣ ስልክ እና የመሳሰሉ ትኩረታቸውን የሚስቡ ነገሮችን ማስወገድ ያስፈልጋል። ይህም ትኩረታቸውን በመውሰድ ምግቡን እንዳያጣጥሙት ከማድረጉም በላይ ከመጠን በታች ወይም በላይ እንዲበሉ ሊያደርግ ይችላል። በቀጣይም ካለእነዚህ ነገሮች ለመብላት ስለሚያስቸግሩ ለተንከባካቢዎቻቸው አስቸጋሪ ይሆናል።

ሌላው በሚገባ ማወቅ ያለብን ህፃናት በዚህ ወቅት ያላቸው አመጋገብ በእድገታቸው እና በቀጣይ እድሜያቸው እንዲሁም ጤናቸው ላይ ያለውን አስተዋጽዖ ነው።  የምግቦችን ትክክለኛ የስነ ምግብ ይዘት አለማወቅና ስለ አንዳንድ ምግቦች ያለን መጥፎ አመለካከት ልጆች ከሚመገቡት ምግብ በቂ ንጥረ ነገር እንዳያገኙና በአግባቡ እንዳያድጉ ያደርጋቸዋል።

ኢማን ዘኪ
የስነ ምግብ ህክምና ባለሙያ

Friday, 20 October 2023 14:53

ለአእምሮ ጤና እንሮጣለን

ሁልጊዜ በየዓመቱ እ.ኤ.አ ጥቅምት 10 ቀን የሚከበረው የአእምሮ ጤና ቀን ዓለማቀፋዊ ኢኒሸቲቭ ያለው ሆኖ በተለያዩ መሪ ቃሎችና ዝግጅቶች ይከበራል፡፡ የ2016 የዓለም የአእምሮ ጤና ቀን የአእምሮ ጤና ዓለማቀፋዊ ሰብዓዊ መብት ነው በሚል መሪ ቃል እየተከበረ ይገኛል ፡፡

ይህንን ቀን የአማኑኤል አእምሮ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ከጤና ሚ/ር፤ ከማረሚያ ቤቶች ኮሚሽን እና ከሌሎችም አጋርና ተባባሪ አካላት ጋር በመሆን በ4/2/2015 ዓ.ም  ካሳንችስ በሚገኘው ሰላም መንገድ ላይ የተለያዩ የመንግስት መ/ቤትና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅት ሰራተኞች ያሳተፈ የ5 ኪ.ሜ የጎዳና ላይ የማስ ሩጫ ፌስቲቫል አካሂዷል፡፡

የፌስቲቫሉ ዋና ዓላማ ማንኛውም የማህበረሰብ አካል የአእምሮ ጤና ጉዳይ የእኔም ጉዳይ ነው ይመለከተኛል ብሎ በመውሰድ የአእምሮ ጤና አጠባበቅ መሰረታዊ ሰብዓዊ መብት መሆኑን በመረዳት በአእምሮ ህሙማን ላይ የሚደርሰውን አድሎና መገለል መከላከል እንደሚገባ ለማስገንዘብ ያለመ ነው፡፡ በመሆኑም የአእምሮ ህሙማን ማንኛውም ሰው ልጅ ያለውና ሊከበርለት የሚገቡት ሰብዓዊ መብቶች እንዲሁ ሊከበሩላቸው እንደሚገባም በፌስቲቫሉ ተንፀባርቋል፡፡

ለአእምሮ ጤና መጠበቅና መጎልበት  እንዲሁም ለአእምሮ ህሙማን ሰብዓዊ መብት መከበርና መረጋገጥ ሁልጊዜም ግንባር ቀደም በመሆን ልንሮጥ ይገባል!!!

Samuel Tolossa
የአማኑኤል ሆስፒታል ተመላላሽ ህክምና ዳሬክተር

ትምህርት ጥሩ ነው። ኮሌጅ መግባትም አሪፍ ነው። ግን ኮሌጅ ስለገባህ ብቻ እራስህን ትለውጣለህ፣ ሀገርን ትቀይራለህ ማለትም አይደለም። በሀገራችንም ፊደል ከመቁጠር ውጭ  ብዙ ትምህርት የሌላቸው፣ ሆኖም በተፈጥሮ ባላቸው ችሎታ ስኬታማ የሆኑ ሰዎች ብዙ ናቸው፡፡
ወደ ውጭም ስንሄድ .....
ታዋቂው የኦቶሞቢል አምራች የፎርድ ኩባንያ  መሥራች የሆነው ሔነሪ ፎርድ፣ አይደለም ኮሌጅ መግባት  መደበኛ ትምህርቱን እንኳን በወጉ ማጠናቀቅ ያልቻለ ሰው ነበር። ልክ 15 አመት ሲሆነው ትምህርቱን አቆመ። ሆኖም ህልም ነበረው። ያ ህልሙን ያለ አንዳች የመደበኛ ትምህርትና የኮሌጅ ዲግሪ ማሳካት ቻለ፡፡
........
አዶልፍ ዳስለርም  እንደዛው ነው። ዝነኛው የስፖርት ትጥቅ አምራች የአዲዳስ ባለቤት ከሁለተኛ ደረጃ  የዘለቀ ትምህርት አልነበረውም። ሆኖም የኮሌጅን በር አለመርገጡ፣ በአለም ዝነኛ የሆነውን አዲዳስን ከመመስረት አላገደውም። ስለዚህ ተማሪዎች ኮሌጅ ቢገቡ፣ ቢማሩ ጥሩ ነበር፤ ሆኖም በወደቀው የትምህርት ፖሊሲና  በተለያዩ ምክንያቶች ይህን አላሳኩምና፣ እንደ እርባና ቢስ  መቁጠር ትክክል አይደለም። ማን ያውቃል፣ ወደፊት ሀገራችንን የሚለውጡት ዛሬ የኮሌጅ መግቢያ ውጤት ማምጣት ያልቻሉ ተማሪዎች ይሆናሉና፣  ለአእምሯቸው እንጠንቀቅ።
(ዋሲይሁን ተስፋዬ)

Monday, 16 October 2023 00:00

ጦርነት ቅስም ሰባሪ ነው!

ይችን አለም ድንቁርናና ስልጣኔ ተባብረው እንድትጠፋ የፈረዱባት ይመስላል። ጋዛም ይሁን እስራኤል፣ አፍጋንም ይሁን ሶሪያ፣ ሱዳንም ይሁን ዩክሬን፣ አማራም ይሁን አፋር፣ ትግራይም ይሁን ወለጋ ደረጃውና አይነቱ ይለያይ እንጂ የንፁሃን ሰቆቃና ስቃይ ህመሙ አንድ ነው። የሰው ልጆች አንድ ናቸው - ሟች ስጋ ህያው ነፍስ። ልዩነታችን አነጋገር፣ አኗኗርና አበላል ካልሆነ በቀር። ከብረት የተሰራ፣ የመላዕክ ክንፍ ያንጠለጠለ የሰው ልጅ የለም። ደስታችን እንጂ መከራችን የጋርዮሽ ነው። የመከራችን ምንጭ ደግሞ፣ የሰው ልጆች ራስ ወዳድነት፣ ሁሉን የኔ ባይነት ነው። በዘርም ታሰበ በጎሳ፣ ለመረጡት ዘር-ለመሩት ሀገር ዳፋ አውርሰው ያለፉ በታሪክ ብዙ ናቸው።
ጋዛ ወደ ምድር ሲኦልነት ተቀይራለች። ይሄዱበት መንገድ፣ ይኖሩበት ሰፈር ግራ ገብቷቸዋል። እናት ልጆቿን የምታደርስባት አጥታ በእምባ ወደ ሰማይ ትቃትታለች። ማንም ሆነ ማን ጥፋተኛ፣ የጋዛና የእስራኤል እናቶች እኩል እያለቀሱ ነው።
እኛ ድንቁርናችንና ደሃ መሆናችን በጀን እንጂ ይሄኔ በሚሳኤልና በሮኬት እርስ በርስ ተላልቀን ነበር። ተራሮች እስኪስቁብን ድረስ ሰው ባልተረፈን ነበር። ያም ሆኖ እንደ ጋርዮሽ ዘመን በገጀራና በቁመህ ጠብቀኝ ከመጨፋጨፍ አልዳንም።
ጦርነት ምን ያህል ቅስም ሰባሪ እንደሆነ አፋር፣ ምስራቅ አማራና ትግራይ ያየሁት ነገር ከአእምሮዬ ተስሎ አልጠፋ ብሎኛል። በመጨባበጥ የተቋጨው የሰሜን ጦርነት ሚሊዮኖችን ሲኦል በመሰለ የምድር ሰቆቃ ጥሎ እንዳለፈ እኔ ለታሪክም ለተረክም ምስክር ነኝ። እኛ የሰራነውን ዘጋቢ ፊልም፣ እኛ ራሳችን እንኳን አይተን መጨረስ አልቻልንም። የሰው ልጆች ክፋት እንዲህ ይከፋል ብዬ አስቤ አላውቅም ነበር። ዛሬም ሌላ ሰቆቃ…ሌላ እምባ….
ባለፈ ሳምንት ለ20 አመታት በጦርነት የደቀቀችው የአፍጋኒስታን የጤና ሚኒስትር ከነበረ ሰው ጋር አጠር ያለ ውይይት አደረግን። ዋና አላማው ጤናና ሰላም ላይ የሚሰራ አለም አቀፍ ተቋም መመስረት ላይ ቢሆንም፣ ስለ አፍጋን የነገረኝ ነገር ልብ ይሰብራል። ጦርነት የሰውን ልጆች ከመኖር ወደ አለመኖር የሚቀይር ሰቆቃ ነው። በአፍጋን 90 በመቶ የሚሆን ህዝብ አሁን እርዳታ ጠባቂ ሆኗል።
ጦርነት ዝም ብሎ አይጀመርም። ወይ በጠገቡት፣ አሊያም በተገፉት ይጫራል። ከዚያ ይቀጥላል….ንፁሃን ሲያልቁ፣ ወይ በድርድር አሊያም በስልጣን መንበር ይጠናቀቃል። ሲያልቅ ግን 20 እና 50 አመት ወደ ኋላ መልሶን ነው።
ፈጣሪ የንፁሃንን ሰቆቃ ሰምቶ የክፉዎችን ልብ እንዲያራራ ፀሎቴ ነው፡፡
ሰላም ለሰው ልጆች ሁሉ!
(ዘላለም ጥላሁን)


Friday, 20 October 2023 11:45

ሰሞንኛ

ከትናንት ወዲያ አንድ ጓደኛዬ ለልጁ ልደት ጠራኝ፤ ቤቱ ስደርስ፥ ከማላውቃቸው እንግዶች ጋራ ደነበኝ፤   ሁለት አረጋዊ  ባልና ሚስት  ከወጣት ልጃቸው ጋር ጎን ለጎን ተቀምጠዋል፤ ልጅቷ  እንደ አበባ ማስቀመጫ ብርጭቆ ጥድት ያለች ናት፡፡  ከልጅቱ አጠገብ አንድ ጎልማሳ ተጎልቷል፤ ሰውየው መልከ መልካም ነው፤ ጢሙን ደግሞ ከጎን በቅርጽ አሳድጎታል፤ የድሮ የባቢሎን ንጉስ ይመስላል፡፡ ልጅቱን ክፉኛ እንደ ከጀላት ያስታውቃል፤ ትኩረቷን ለማግኘት ሲጥመለመል አየዋለሁ፡፡  የልጅቱ አባትና እናት አንድ አንድ ጥያቄ ጠየቁኝ፤ በዋዛ መለስኩ፡፡ እናትየው በረጅም ሳቅ ተባበሩኝ፡፡  አባትየው፤ “ተው በሳቅ እንዳትገለን” ሲሉኝ፤ በነፍስ ግድያ እንዳልጠየቅ ብዬ ጨዋታዬን ገታሁ፡፡   ጎልማሳው ግን በሳቁ ውስጥ አልተሳተፈም፤ በብዙ ቁጣ፥ በብዙ መከፋት፥ ሲያፈጥብኝ ከቆየ በሁዋላ፥
“እንዲህ አጭር አትመስለኝም ነበር” የሚል ቃል ሰነዘረ፡፡
“አጭር ነኝ ብዬ አላስብም” በማለት ተፈጥሮዬን  አስተባበልኩ፡፡
“ምንድነኝ ብለህ ነው እምታስበው?”  አለ ጎልማሳው፡፡
“በቁመት  ቀዳማዊ ሀይለስላሴ ጋራ እኩያ ነን፤ እና  ብዙ ጊዜ ራሴን “ንጉስ -አከል” ወይም king-sized ብዬ ነው እምጠራው”
አባትየው በመልሴ በጣም ተደነቁና አምስት ሺህ ብር  ሸለሙኝ::
 ልጅቷ ፈገግ አለችልኝ፡፡
 “አግብተሀል?” አሉኝ እናቲቱ፡፡
“አላገባሁም” አልኩኝ ቀልጠፍ ብዬ፡፡
 “መንግስት ካልመደበላቸው በቀር አጭሮች ከየት አምጥተው ያገባሉ?” አለ ጎልማሳው፡፡“ልክ ነው ሴቶች አስቀድመው  የሚያዩት ረጅም ወንድ ነው” ብዬ ጀመርሁ፤ ጎልማሳው በድል አድራጊነት  ፈገግ ብሎ ወደ ልጅቱ ተመለከተ፡፡
“በዚህ ምክንያት፥ አጭር ወንዶች የሴቶችን ቀልብ ለመግዛት መላ መፍጠር ይገደዳሉ፤ ወይ አሪፍ ፈልሳፊ፤  አሪፍ ሙዚቀኛ ፥ወይ አሪፍ አትሌት፤ ወይ አሪፍ ሀሳብ አፍላቂ!፤ ወይ አሪፍ ባለሀብት ለመሆን ይታገላሉ፤ አጭር ወንዶች የሴቲቱን ቀልብ ለመሳብ የፈጠሯቸው ጸጋዎች አንዳንዶቹ የስልጣኔ ማድመቂያ ለመሆን በቅተዋል፤ ረጅም  ሸበላ ወንድ  በተፈጥሮው ስለሚረካ ሴቲቱ መጥታ እስክትወድቅለት  ይጠብቃል፤ አጭር ወንድ ግን የጅንጀና ጥበብን ፈልስፏል፤  ዞሮ ዞሮ ረጃጅሞች የሚበሉት እራት ከአጭሮች የተረፈውን ነው” በማለት ዲስኩሬን ዘጋሁት፡፡   
ሰውየው  በጣም ተናደደ::
ሳይደበድበኝ ጨዋታውን ወደ  ሰሞኑ ፖለቲካ አዞርኩት፡፡  አረጋዊውና ሚስቲቱ እስራኤልን ሲደግፉ፣ ልጅቱ ደግሞ የፍልስጤም ተቆርቋሪ መሆናቸውን ተገነዘብኩ፤ የኔን ሀሳብ ጠየቁኝ፡፡ “ኢትዮጵያዊ  ጎራ ለይቶ እሚነታረክበት ምክንያት አይገባኝም፤ አበሻ ቢችል አስታራቂ ባይችል ተመልካች መሆን ነው ያለበት፤ እኛ እኮ የእብራውያንንና የአረቦችን ባህል እኩል በሚባል ደረጃ የወረስን ህዝብ ነን” አልኩ፡፡
“የሰለሞንና የማክዳን ታሪክ አላነበብህም መሰል” አሉኝ አባትየው፤ በሽልማት የሰጡኝን አምስት ሺህ ብር  መልሰው እየወሰዱ፡፡
“የሰለሞንና የማክዳ ታሪክ ከእስራኤል ጋራ ያለንን ዝምድና የሚተርክ መጽሐፍ ነው፤ ግን ከአረብኛ  የተተረጎመ መጽሐፍ መሆኑንም  አንርሳ” ካልኩ በሁዋላ ወደ ወደ ጎልማሳው ዞሬ፤
“በዚህ ጉዳይ አንተ ምን ታስባለህ?” አልኩት፡፡
“እኔ ፖለቲካ ላይ የለሁበትም፤ እልል ያልሁ  ዘመናዊ ጫማ ነጋዴ ነኝ፤”
  ከጥቂት ዝምታ በሁዋላ ይቺን አስከተለ፤
“ረጅም ተረከዝ ያለው ጫማ ስትፈልግ ወደ ሱቄ ጎራ ማለት ትችላለህ”
(በእውቀቱ ስዩም)

ካቻ የተሰኘ የዲጂታል ፋይናንሲንግ ሰርቪስ የግል ክፍያ ሰነድ አውጪ በመሆን አገልግሎቱን በይፋ አስጀምሯል። በኢትዮጵያ የመጀመሪያው ነው የተባለው አገልግሎቱ ከብሔራዊ ባንክ የአገልግሎት ፈቃድ ያገኘ እና የሞባይል የገንዘብ ዝውውርና ሌሎች የፋይናንስ አገልግሎቶችን በተለያየ ደረጃና አማራጮች ያካተተ መሆኑ ታውቋል።

ይህን ተከትሎ በካቻና በተለያዩ ባንኮች፣ የማይክሮ ፋይናንስ ተቋማት እና ሌሎች ስትራቴጂካዊ አጋሮች ጋር በጋራ አብሮ ለመስራት የፊርማ ሥነ ስርዓት ተካሂዷል።

በተጨማሪም ካቻ ከአለም አቀፍ ሓዋላ አስተላላፊዎች ጋር የፈጠረውን አጋርነት ያሳየው ደህንነቱ የተጠበቀ የውጪ ሓዋላን በማሳለጥ፤ ላኪዎችም ሆኑ ተቀባዮች ለተጨማሪ የፋይናንስ አገልግሎቶች ዕድል የሚያገኙበት አሰራር መዘርጋቱን ገልጿል።

የካቻ ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ተሾመ በየነ የካቻ ዓላማ ለደንበኞች በላቀ ቴክኖሎጂ የታገዘ ደህንነቱ የተጠበቀና የፋይናንስ አካታችነት ያለው የዲጂታል ባንኪንግ አገልግሎት ማቅረብ ነው ብለዋል

Page 10 of 676