Administrator

Administrator

 የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በሶርያ ለአመታት የዘለቀውን የእርስ በእርስ ግጭት በመሸሽ ወደተለያዩ አገራት የተሰደዱ የአገሪቱ ዜጎች ቁጥር ከ4 ሚሊዮን በላይ መድረሱንና ይህም ከአገሪቱ ህዝብ አንድ ስድስተኛ ያህሉን እንደሚሸፍን ማስታወቁን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
በሶርያ በ2011 የተቀሰቀሰው ግጭት እየተባባሰ መቀጠሉ የአገሪቱን ዜጎች ከፍተኛ ቀውስ ውስጥ እንደከተታቸው የጠቆመው ዘገባው፣ ባለፉት አራት አመታት በግጭቱ ለህልፈተ ህይወት የተዳረጉ ዜጎች ቁጥር ከ230 ሺህ በላይ መድረሱንና አገራቸውን ጥለው ከተሰደዱት ከ4 ሚሊዮን በላይ ዜጎች በተጨማሪ፣ ከ7 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑትም በአገራቸው ውስጥ መፈናቀላቸውን ገልጧል፡፡
በሶርያ የሚታየውን አስከፊ ሁኔታ፣ “የዚህ ትውልድ አስከፊው የሰብአዊ ቀውስ” ሲሉ የገለጹት የተመድ የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን ሃላፊ አንቶኒዮ ጉቴሬስ፣ የእርስ በእርስ ግጭቱ እያደረሰ ያለው ጥፋት እየከፋ መምጣቱንና ስደቱ በዚሁ ከቀጠለ፣ የስደተኞቹ ቁጥር በመጪዎቹ ስድስት ወራት 4.27 ሚሊዮን ሊደርስ ይችላል ብለዋል፡፡
የተመድ መረጃ እንደሚለው፤ በርካታ ሶርያውያን በተሰደዱባት ቱርክ፣ የስደተኞቹ ቁጥር 1.8 ሚሊዮን የደረሰ ሲሆን፣ በድንበር አካባቢ ያለው ግጭት እየተባባሰ መምጣቱን ተከትሎ የስደተኞቹ ቁጥር እንደሚያሻቅብ ይጠበቃል፡፡ በሊባኖስ 1.2 ሚሊዮን፣ በዮርዳኖስም 629ሺህ ያህል ሶርያውያን ስደተኞች እንደሚገኙ ተመድ አስታውቋል፡፡ በተለያዩ የአውሮፓ አገራት ጥገኝነት የጠየቁ ሶርያውያን ስደተኞች ቁጥር 270 ሺህ ያህል መድረሱንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

 7ሺህ 800 ሰራተኞቹን ለመቀነስ ወስኗል

    ታዋቂው ማይክሮሶፍት ኩባንያ በኖኪያ የስማርት ሞባይል ቀፎ ንግዱ ላይ 7 ነጥብ ስድስት ቢሊዮን ዶላር ኪሳራ ማጋጠሙን ተከትሎ፣ 7ሺህ 800 ሰራተኞችን ከስራ ገበታቸው እንደሚቀንስ ባለፈው ረቡዕ ማስታወቁን ዘ ጋርዲያን ዘገበ፡፡
ከሁለት አመታት በፊት ኖኪያን በ7.3 ቢሊዮን ዶላር የገዛውና የሞባይል ቀፎዎችን እያመረተ ለገበያ ማቅረብ የጀመረው ማይክሮሶፍት፣ ቢዝነሱ አላዋጣው ማለቱን በማየት ባለፈው አመት ብቻ 12 ሺህ 500 ሰራተኞቹን እንደቀነሰ ያስታወሰው ዘገባው፣
ማይክሮሶፍት ከለመደው የኮምፒውተር ዘርፍ ወጣ ብሎ የተሰማራበት የሞባይል ቀፎ ንግድ ኪሳራ ላይ ጥሎታል ያሉት የኩባንያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ሳትያ ናዴላ፣ ቢዝነሱ ለምን አክሳሪ እንደሆነና በቀጣይ መወሰድ የሚገባቸውን እርምጃዎች በተመለከተ ግምገማ እያደረግን ነው ብለዋል፡፡
ኩባንያው በቅርቡ የስማርት ፎን ንግዱን አዋጭ በሆነ ሁኔታ ማስቀጠል የሚችልበትን አዲስ አቅጣጫ እንደሚዘረጋና 18ሺህ ሰራተኞቹን መቀነስን ጨምሮ ሰፊ የመዋቅር ለውጥ እያደረገ እንደሚገኝም ተናግረዋል፡፡
ማይክሮሶፍት የፊንላንዱን ኖክያ የገዛው፣ ከዚህ በፊት ያመርታቸው የነበሩትን የዊንዶውስ ሞባይሎች ከአፕል አይፎኖችና ከጎግል አንድሮይድ ሲስተሞች ጋር በገበያ ላይ ተወዳዳሪ ለማድረግ በማሰብ እንደሆነም ዘገባው ጨምሮ አስታውሷል፡፡

የዘመድ ችግር የሚፈታው በዘመድ ነው፡፡
የስዋሃሊ አባባል
በጋራ ጀልባ ወንዙን ተሻገሩ፡፡
የቻይናውያን አባባል
እዩኝ እዩኝ ማለት ለትችት ያጋልጣል፡፡
የጃፓናውያን አባባል
ማስታወቂያ የንግድ እናት ነች፡፡
የጃፓናውያን አባባል
ልብ ትክክል ሲሆን ስራም ትክክል ይሆናል፡፡
የጃፓናውያን አባባል
ብዙ የምታስካካ ዶሮ ብዙ እንቁላል አትጥልም፡፡
የኮሪያውያን አባባል
የዛፍ ፍሬ ከዛፉ ርቆ አይወድቅም፡፡
የኮሪያውያን አባባል
በእጅህ መዳፍ መላውን ሰማይ ልሸፍን አትበል፡፡
የኮሪያውያን አባባል
ብዙ እጆች የሥራ ጫናን ያቀላሉ፡፡
የሰሜን አሜሪካውያን አባባል
አንድ ግንዲላ ብቻውን ምድጃ እንኳን ለማሞቅ በቂ አይደለም፡፡
የእስያውያን አባባል
መቶ ሰዎችን ለማስፈራራት አንዱን ግደል፡፡
የቻይናውያን አባባል
ውሃ ጀልባን ማንሳፈፍ ብቻ ሳይሆን ማስመጥም ይችላል፡፡
የቻይናውያን አባባል
ባዶ ጆንያ ቀጥ ብሎ መቆም አይችልም፡፡
የስዋሂሊ አባባል
አንድ ምሰሶ ቤት አያቆምም፡፡
የስዋሂሊ አባባል
ብዙ ካፒቴኖች ያሏት መርከብ መስጠሟ አይቀርም፡፡
የስዋሂሊ አባባል
ሁለት እርምጃ መንገድ አይሆንም፡፡
የናይጄሪያውያን አባባል
ወላጆችህ ጥርስህን እስከምትነቅል ከተንከባከቡህ፣ አንተም ጥርሳቸውን እስኪ ነቅሉ ትንከባከባቸዋለህ፡፡
የናይጄሪያውያን አባባል

      ለ31ኛው የአፍሪካ ዋንጫና ለ4ኛው የቻን ውድድር ለማለፍ በሚደረጉ ማጣርያዎች አመርቂ ውጤት ያስመዘገበው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን 2ኛ ምእራፍ ዝግጅቱን ከሁለት ሳምንት በኋላ እንደሚቀጥል ታውቋል። በሁለቱ አህጉራዊ ውድድሮች ዋልያዎቹ  ሦስት ጨዋታዎች በማድረግ በሁለቱ አሸንፈው በአንዱ አቻ ወጥተዋል፡፡ በ2017 የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ በምድብ 10 ከአልጄርያ፤ ሌሶቶ እና ሲሸልስ ጋር የሚገኙት ዋልያዎች በምድብ ማጣርያ የመጀመርያ ጨዋታቸው ሌሶቶን በሜዳቸው 2ለ1 በማሸነፍ   በ3 ነጥብ በግብ ክፍያ በአልጄርያ  ተበልጠው መሪነቱን ተጋርተዋል፡፡ በቻን ቅድመ ማጣርያ ደግሞ ባለፈው ሰሞን ናይሮቢ ላይ ከኬንያ አቻቸው ጋር 0ለ0 ከተለያዩ በኋላ በ2ለ1 የደርሶ መልስ ውጤት ጥለው በማለፍ ለመጨረሻው ማጣርያ አልፈዋል፡፡ በአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣርያ ቀጣይ ተጋጣሚያቸው ከሜዳ ውጭ ሲሸልስ ስትሆን በቻን የመጨረሻ ማጣርያ ደግሞ በደርሶ መልስ ከብሩንዲ ጋር ይገናኛሉ፡፡
ዋልያዎቹ ከሁለት ሳምንት ዕረፍት በኋላ ወደ ዝግጅታቸው ሁለተኛ ምእራፍ እንደሚገቡና  ለቀጣዩ ግጥሚያዎቻቸው መስራት እንደሚጀምሩ እና  በነሐሴ ወር ሁለት የወዳጅነት ጨዋታ በማድረግ አቋማቸውን እንደሚፈትሹ ይጠበቃል፡፡ ከኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በሜዳው ላይ እና ከሜዳው ውጭ የወዳጅነት ጨዋታዎች ለማድረግ የሚፈልጉ አገራት መበርከታቸውን ከፈዴሬሽኑ የሚወጡ መረጃዎች ይገልፃሉ፡፡
በ2017 የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣርያ ከኢትዮጵያ ጋር ከተደለደሉት ቡድኖች በቻን ማጣርያቸው ሲሸልስ ስትወድቅ፤ ሌሶቶ ግን አልፋለች፡፡ ሲሸልስ በሞዛምቢክ 9ለ1 በሆነ የደርሶ መልስ ውጤት ተሸንፋ ስትወድቅ ፤ ሌሶቶ ደግሞ ቦትስዋናን ጥሎ በማለፍ ለመጨረሻ ዙር ማጣርያ በቅታለች፡፡ በመጨረሻ ዙር የቻን ማጣርያ የኢትዮጵያ ተጋጣሚ የሆነችው ብሩንዲ በቻን ውድድር ለመጀመርያ ጊዜ በ2014 ተሳትፋ የነበረ ሲሆን ሱዳንን በመለያ ምቶች 4ለ3 ጥላ በበማፍ ነበር፡፡ በ2009 እኤአ በደርሶ መልስ ማጣርያ ብሩንዲን ያሸነፈችው ሩዋንዳ ስትሆን በ2011 እኤ ደግሞ ኡጋንዳ ነበረች፡፡ ሲሸልስ በ2017 አፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣርያ 2ኛ ጨዋታ ላይ ከኢትዮጵያ ጋር በሜዳዋ ከመገናኘቷ  በፊት ጠንካራ ዝግጅት ለማድረግ ወስናለች፡፡ አሰልጣኙ ማቲዮት ሰሞኑን በሰጡት መግለጫ ቡድናቸው ዛሬ እና ነገ ወደ አልጄርያ በማቅናት  የሁለት ሳምንት ዝግጅት በካፕ ተቀምጦ ያደርጋል፡፡ ከዚህ ዝግጅት በኋላም በኢንድያን ኦሽን ጌምስ በመካፈል ከማዳጋስካር ፤ ከማልዴቪስና  ከማዮቴ ደሴት ብሄራዊ  ቡድኖች ጋር በምድብ ማጣርያ ይጫወታል፡፡

    አዲሱ የተጨዋቾች ደረጃና የዝውውር መመሪያ ባለድርሻ አካላትን ሳያስማማ ተግባራዊ መሆን ጀምሯል፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን አፅድቄዋለሁ የሚለውን ይህ መመርያ ከሐምሌ 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ ሕጋዊ ሰነድ ሆኖ እንደሚቀጥል ገልፆ እየሰራበት ነው።  ከመመርያው ተግባራዊነት በፊት ተጨማሪ ውይይት እንደሚያስፈልግ የተጨዋቾች ተወካዮች  በደብዳቤ ቢጠይቁም ምላሽ አልተሰጣቸውም፡፡ ለፕሪሚዬር ሊግ  ክለቦችም የመመርያው አፈፃፀም በቀጣዩ የውድድር ዘመን በሚኖራቸው ዝግጅት  ላይ እንቅፋት እየሆነባቸውም ይገኛል፡፡
መመርያው ተግባራዊ ከመሆኑ 1  ሳምንት ቀደም ብሎ በክለቦች መካከል የተፈጠሩ ውዝግቦች ነበሩ፡፡ ይህን ተከትሎ የፌዴሬሽኑ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት በመመርያው ቀጣይ ዕጣ ፈንታ ላይ ለመነጋገር ስብሰባ ቢቀመጡም ሳይስማሙ እንደተለያዩ ተነግሯል፡፡
መመርያው ተጨዋቾችንና ቀጣሪዎቻችንን በዋናነት ይመለከታል በማለት የተጨዋቾች ማህበር ተወካዮች ያቀረቡት  ግልፅ ደብዳቤ ትኩረት ስለተነፈገው  ቅር ተሰኝተዋል፡፡  ተጨዋቾቹ በመመርያው የሚመክሩበት ጊዜ እንዲሰጣቸው ፣ በአገሪቱ የአሠሪና ሠራተኛ ውል መሠረት በሁለት ባለጉዳዮች መካከል በሚደረገው ስምምነት ሦስተኛ ወገን እንደማያስፈልግ፣ የክፍያውን መጠንና የአከፋፈሉ ሒደትን በተመለከተም በሁለቱ ባለጉዳዮች ስምምነት የሚወሰን እንጂ በሦስተኛ ወገን ወይም ፌዴሬሽን ሊሆን እንደማይገባ በመጠቃቀስ መስተካከል ስላለባቸው አንቀፆች እንነጋገር ብለው ነበር።   በተለይ ሰኔ 30 ከሆነ በኋላ በሁሉም የፕሪሚዬር ሊግ ተወዳዳሪ ክለቦች    ብዙ ተጨዋቾች ኮንትራታቸው ስለተጠናቀቀ ክፍት በሆነው የዝውውር ገበያ ውላቸውን ለማደስም ሆነ ክለብ ለመቀየር  በፊርማ ክፍያ በተፈጠሩ አለመግባባቶች እየተስተጓጎለ ይገኛል፡
በተለይ በመመርያው እያንዳንዱ ክለብ በስብስቡ ሊኖረው የሚገባን የውጭ ተጫዋቾችን በተመለከተ ቁጥሩ ከአምስት ወደ ሦስት ዝቅ እንዲል መባሉ እና የፊርማ ክፍያ የሚለው አሰራር ተቀይሮ ተጨዋቾች በደሞዝ አገልግሎት እንዲሰጡ በመመርያው መደንገጉ በቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብና በተጨዋቾች ማህበር ተቀባይነት አልነበራቸውም፡፡ የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ የውጭ ተጨዋቾችን ለመገደብ ደንብ ያስፈለገው ለአገር ውስጥ እግር ኳስ ተጫዋቾች የተሻለ ትኩረት መስጠት ያስችላል ብሏል፡፡  የቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ ሃላፊዎች በበኩላቸው የውጪ አገር ተጫዋቾች ወደ ኢትዮጵያ መምጣት ያሉትን ጠቀሜታዎች በመዘርዘር ለማስረዳት ሙከራ አድርገዋል፡፡ የውጭ አገር ተጨዋቾች በክለብ ስብስብ መካተታቸው የአገር ውስጥ ተጨዋቾችን በተፎካካሪነት ጎልተው እንዲወጡ እንደሚያደርግና የፕሮፌሽናልነት ዕድል እንዲፈጠርላቸው ያደርጋል የሚሉ ማስረጃዎችንም ገልፀዋል፡፡ ባለፈው የውድድር ዘመን በኢትዮጵያ ለመጫወት ከአፍሪካ 6 አገራት የተውጣጡ ከ26 በላይ ተጨዋቾች በ7 ክለቦች በመቀጠር ህጋዊ እውቅና በማግኘት ለመጫወት ችለው ነበር፡፡ የውድድር ዘመኑ ከመጀመሩ በፊት የእግር ኳስ ፌደሬሽን ይፋ አድርጎት በነበረው ዝርዝር መሰረት በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ሲጫወቱ የነበሩት 26 የሌላ አገር ተጨዋቾች 8 ከካሜሮን፤ 7 ከናይጄርያ፤ 6 ከጋና፤ 3 ከኡጋንዳ እንዲሁም ከኬንያ እና ከደቡብ አፍሪካ የመጡ ናቸው፡፡ ከ26ቱ የሌላ አገር ተጨዋቾች ጊዮርጊስ 7፤ ኤልፓ እና ሀረር ቢራ እያንዳንዳቸው 5፤ ደደቢት 4፤ ኢትዮጵያ ቡና እና ድሬዳዋ ከነማ እያንዳንዳቸው 2 እንዲሁም ኒያላ ለ1 ተጨዋች ቅጥር ፈፅመው በፌደሬሽኑ የእውቅና ማረጋገጫ የውድድር ዘመኑን አሳልፈዋል፡፡
በኢትዮጵያ እግር ኳስ የተጨዋቾች ዝውውር ገበያ እየተሟሟቀ የመጣው በተለይ ካለፉት አራት ዓመታት ወዲህ ነው፡፡ በተለይ የፊርማ ክፍያ ከተባለው አሰራር ጋር ተጨዋቾች ከፍተኛ ጥቅም እያገኙ ነበር፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ የዝውውር ገበያ ካለፈው 4 ዓመት ወዲህ በ50ሺ ብር የፊርማ ክፍያ ተጀምሮ፤ ወደ 100ሺ ብር ከዚያም ወደ 200ሺ ብር፤ 300ሺብር በአማካይ ወደ 500 ሺ ብር ደርሷል፡፡
የተጨዋቾች ደረጃና የዝውውር መመርያ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ ባቀረበው ጥያቄ በተለይም የመመርያው ዋና ተዋንያን ተብለው በሚጠቀሱት ተጨዋቾች ባቀረቡት ግልፅ ደብዳቤ ሳይፀድቅ ለውይይት በድጋሚ ይቀርባል የሚለው ተስፋ ባለመሳካቱ  ሁኔታዎች የተድበሰበሱ መስሏል፡፡   የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ይፋ ባደረገው መግለጫ ከሐምሌ 1 ቀን 2007 ዓ.ም የመመሪያው ተግባራዊነት እንደሚጀመር አረጋግጦ፤ መመሪያው እንደተሻሻለ ወይም ተግባራዊ እንደማይሆን ከአንዳንድ ወገኖች እየተሠነዘረ የሚገኘው አስተያየት መሠረተ ቢስ ብሎታል፡፡ በመመርያው  የአፈጻጸም ሂደት የሚያጋጥሙ ችግሮችን መሰረት በማድረግ በየጊዜው በሚደረግ ፍተሻ የማሻሻያ እርምጃዎች እንደሚወሰድ የፌዴሬሽኑ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አቋም መሆኑን ያመለከተው የፌደሬሽኑ መግለጫ፤  በቀጣይነትም መመሪያውን በተመለከተ ከተለያዩ አካላት የሚቀርቡትን ገንቢ አስተያየቶች ፌዴሬሽኑ እየተቀበለና እያጤነ በማሻሻል አስፈላጊውን መግለጫ የሚሰጥ መሆኑ እንዲታወቅ መመሪያውን በተመለከተ የተለወጠ ወይም የተሻሻለ ሁኔታ ባለመኖሩ ተግባራዊነቱ የሚቀጥል መሆኑን አሳስቧል፡፡
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን  በአገሪቱ የሚፈፀመው የእግር ኳስ ተጨዋቾች ደረጃና ዝውውር በሕግና በሥርዓት እንዲመራ ባለው ፍላጎት መፅናቱን አረጋግጧል፡፡ መመርያው በፊፋ ዝቅተኛውን የተጨዋቾች ደረጃና ዝውውር መስፈርት ያሟላ እንዲሆን፣ በተጨማሪም አሠራሩ በሕጋዊ ወኪል እንዲመራና ሒደቱም ተጨዋቾችን፣ ክለቦችንና መንግሥትን ተጠቃሚ በማድረግ ለአገሪቱ የእግር ኳስ ዕድገት መፋጠን የራሱን አወንታዊ ሚና እንዲጫወት ይፈለጋልም ተብሏል፡፡
በኢትዮጵያ ከተጨዋቾች ዝውውር ጋር ተያይዞ እየተሠራበት የነበረው አሠራር ለአገሪቱ እግር ኳስም ሆነ ለክለቦች፣ ተጨዋቾችና መንግሥት ምንም ዓይነት ጥቅም እንዳላስገኘ የሚገልፀው ፌደሬሽኑ፤ የዝውውር ሂደቱ የክለቦችን የፋይናንስ አቅም ማዳከሙን፤ ለተጨዋቾችም እንደተከፈለ የሚነገረው ገንዘብ ሙሉ በሙሉ እንደማይደርሳቸው፤ ህገወጥ የዝውውር ደላሎች እንደበዙበት፤  በፕሮፌሽናል ስም የሚመጡት ብዙዎቹ ተጨዋቾች የችሎታቸው ጉዳይ ጥያቄ እንደሚያስነሳ፤ ተጨዋቾች ከደመወዝ ይልቅ ትኩረት ሰጥተው የሚከራከሩት ለፊርማ ተብሎ ስለሚሰጣቸው ገንዘብ መሆኑ፣ ገንዘቡን ከወሰዱ በኋላ ለክለባቸው ተገቢውን አገልግሎት እንደማይሰጡ፣  ክለቦች ታዳጊዎችን አሳድገው ማግኘት የሚገባቸውን ጥቅም በማሳጣቱ፣ አዲሱ ደንብ ተግባራዊ መሆኑ ይህን እነዚህን ችግሮች ለማስተካከል መፍትሄ እንደሚያመጣ በዝርዝር አብራርቷል፡፡

Saturday, 11 July 2015 11:56

የፀሐፍት ጥግ

የራሳችንን ጭብጦችና ታሪኮች ለመግለፅ
የምዕራባውያንን ዘይቤ ተጠቅመን ፅፈናል።
የሥነ ፅሁፍ ቅርሳችን ግን “አንድ ሺ አንድ
ሌሊቶች”ን እንደሚያካትት እንዳትዘነጉ፡፡
ናጂብ ማህፉዝ
· ጭብጦች በሥራዬ ላይ በተደጋጋሚ እያሰለሱ
ይመጣሉ፡፡
ኢቭ አርኖልድ
· ለእኔ ህይወት እና ሞት በጣም ወሳኝ ጭብጦች
ናቸው፡፡ ሞት በሌለበት ህይወት የለም፡፡ ለዚያ
ነው ለእኔ በጣም ወሳኝ የሆኑት፡፡
ቲቴ ኩቦ
· ለእኔ ጭብጥ፤ ፍቅርና የፍቅር እጦት ነው።
ሁላችንም ፍቅርን እንፈልገዋለን፡፡ ግን እንዴት
እንደሚገኝ አናውቅም፡፡ እያንዳንዱ ድርጊታችን
እሱን ለመጨበጥ የሚደረግ ሙከራ ነው፡፡
ርያን ጐስሊንግ
· እውነት አንድ ብቻ ብትሆን ኖሮ፣ በተመሳሳይ
ጭብጥ መቶ ሸራዎች ላይ አትስልም ነበር፡፡
ፓብሎ ፒካሶ
· የእንግሊዝ ገጠራማ ክፍል እድገትና ውድመት
እውነተኛና አሳዛኝ ጭብጥ ነው፡፡
ኢ.ኤም.ፎርስተር
· አገራት ገንዘብ በመፈለጋቸው የተነሳ ባህላቸውን
አጥተዋል፡፡ በየአገሩ ገንዘብ የወቅቱ ጭብጥ
የሆነበት ጊዜ ነበር፡፡ በዚህም ሳቢያ ባህል
መስዋዕት ተደረገ፡፡
ዩኮ ኦኖ
· አንድ ጭብጥ ውሰድና አድምተህ ስራው …
ጉዳዩ ታዲያ አንድም ከልብህ የምትወደው
አሊያም ከልብህ የምትጠላው መሆን አለበት፡፡
ዶሮቲያ ላንጅ
· ፍቅር፤ በሥራዬ ላይ እየተመላለሰ የሚመጣ
ጭብጥ ነው፡፡
ትሬሲ ቻፕማን
· ቁጭ ብዬ በሴራ እና ጭብጥ መካከል ያለውን
ልዩነት አስቤ አላውቅም፡፡ ለእኔ ያ ጨርሶ
አስፈላጊ ሆኖ አያውቅም፡፡
ሌን ዌይን
· ፀሐፊያን ቁጭ ብለው ስለ አንድ ዓላማ ወይም
ጭብጥ አሊያም ስለሆነ ነገር ለመፃፍ ማሰብ
ያለባቸው አይመስለኝም፡፡ ስለራሳቸው
የህይወት ተሞክሮ ከፃፉ፣ አንድ የሆነ እውነት
ብቅ ይላል፡፡
ዶሪስ ሌሲንግ
· ያለጥርጥር የምማረክበት ጭብጥ ሞት ነው።
አላን ቦል
· ጭብጥህ ውሎ አድሮ ያገኝሃል፡፡ አንተ እሱን
ፍለጋ መውጣት አይኖርብህም፡፡
ሪቻርድ ሩሶ
· ፊልም ሰ ሪዎች፤ “ ስለዚህ ጉ ዳይ ወ ይም በ ዚህ
ጭብጥ ላይ ፊልም መስራት እፈልጋለሁ” ይላሉ፡
፡ እኔ ግን ፈፅሞ እንደዚያ ብዬ አልጀምርም፡፡
አንድሪያ አርኖልድ


በጋዜጣችሁ የሰኔ 13 ቀን 2007 ዓ.ም ዕትም ላይ አልፋ የትምህርትና ስልጠና አ.ማህበርን በተመለከተ ባቀረባችሁት ዜና፤ “ቅሬታው” በአንድ ግለሰብ የቀረበ መሆኑ እየታወቀ “የአልፋ ባለ አክስዮኖችና አመራሮች እየተወዛገቡ ነው” የሚል ርዕስ መስጠታችሁ አሳሳች፣ ለጋዜጣው አንባቢያን ስለ አክስዮን ማህበሩ የተዛባ መግለጫ የሚሰጥና የአክስዮን ማህበሩን መልካም ስምና ዝና የሚያጐድፍ አቀራረብ በመሆኑ በብዙኃን ባለአክስዮኖች ዘንድ ጥያቄ አስነስቷል፡፡
በተጨማሪም በዘገባችሁ፣ በማንኛውም የበጀት ዓመት በአክስዮን ማህበሩ ተገኝቶ የማያውቀውን ብር 30.000.000 (ሰላሳ ሚሊዮን ብር) የተጣራ ትርፍ ማስረጃ ባላገናዘበ ሁኔታ ተገኝቶ ነበር ብላችሁ መግለፃችሁ እንዲሁም በ2006 በጀት ዓመት የተገኘው የተጣራ ትርፍ ብር 4.5 ሚሊዮን እንደሆነ ተገልፆ እያለ፣ በመጨረሻው በጀት ዓመት ብር 1.5 ሚሊዮን ብቻ እንደተገኘ አድርጋችሁ ማቅረባችሁና ቅሬታ አቅራቢው የገለፀውን አመራሩ ከሰጠው መልስ ጋር በማነፃፀር አለመዘገባችሁ ቅሬታ እንደፈጠረብን ልንገልፅ እንወዳለን፡፡
(ቢኒያም ሀይሉ የዳይሬክተሮች ቦርድ ፀሐፊ)

ከዕለታት አንድ ቀን በደጋው አገር የሚኖሩ ሁለት ጐረቤታም ገበሬዎች ነበሩ። ሁለቱም በሣር ቤት የሚኖሩና ኑሮ አልለወጥ ያላቸው ግን ታታሪ ሰዎች ነበሩ፡፡
“አንድ ቀን አንደኛው በድንገት የኑሮ ለውጥ አሳየ፡፡ የግቢውን አጥር አጠረ። የቤቱን የሣር ክዳን ወደ ቆርቆሮ ጣራ ለወጠ፡፡ ልጆቹ ደህና ደህና ይመገቡ፣ መልካም ልብስም ይለብሱ ጀመር፡፡
ጐረቤትየው ያየውን ለውጥ ማመን አቅቶት ወደ ወዳጁ ሄደና፤
“አያ እገሌ?” አለው፡፡
“አቤት” አለው፡፡
አብረን አንድ አካባቢ እያረስን እየኖርን በድንገት ምን ተዓምር ተፈጥሮ ነው እንዲህ የበለፀግከው?”
የተለወጠው ገበሬም፤
“ሚሥጥሩ ምን መሰለህ ወዳጄ፤ ታች ቆላ ወርጄ ማጭድ፣ ዶማ፣ አካፋ፣ ማረሻ ወዘተ ብዙ ብረታ ብረት ገዝቼ አመጣሁና ለደገኛው ገበሬ ቸበቸብኩት። ትርፉ ትርፍ እንዳይመስልህ! አንድ ሁለት ሶስቴ ተመላልሼ ይሄንን ሥራ ስሠራ ገንዘብ እንደ ጉድ እጄ ገባ!” አለው፡፡
ያም ገበሬ አመስግኖት ወደ ቤቱ ሄደ፡፡ በነጋታው፤ በሬዎቹን ሸጠና ብሩን ይዞ ወደ ቆላ ገበያ ወረደ፡፡ ቆላ ያለ የብረታ ብረት ዘር አንድም ሳይቀረው ገዛና ተሸክሞ ወደ ደጋ ሊመለስ መንገድ ጀመረ፡፡ መንገዱ ወደ ቆላ ሲሄድ ቁልቁለት ነበረ፡፡ አሁን ግን ዳገት ነው፡፡
ግማሽ መንገድ እንኳ ሳይጓዝ በሸክሙ ብዛት ወገቡ ሊቆመጥ ደረሰ፡፡ መቀጠል አልቻለም፡፡ ተዝለፍልፎ፣ ላብ በላብ ሆኖ ወደቀ፡፡
መንገደኛ የሰፈሩ ሰው ወድቆ አየውና፤
“አያ እንቶኔ?”
“አቤት”
“ምነው ምን ገጠመህ?”
“ኧረ ተወኝ ወዳጄ፤ ያ ጐረቤቴ ስለ ብረታ ብረት ንግድ አማክሮኝ፣ እዚህ ወድቄ ቀረሁልህ፡፡”
“እንዴት?”
“ትርፉን ነግሮ መከራውን ሳይነግረኝ!”
*   *   *
በህይወት ውስጥ፣ ደረጃው ይለያይ እንጂ መስዋዕትነትን የማይጠይቅ ምንም ነገር የለም፡፡ ይህንን ልብ ያላለ ፖለቲከኛ ብዙ ዕድሜ አይኖረውም፡፡ በትንሽ በትልቁ ሲበሳጭ፣ ሲነጫነጭ፣ አቤቱታ ሲያበዛ፣ ነገረ ሥራው ሁሉ የዕድል እንጂ የትግል ሳይመስል፣ ማማረር እንጂ መማር ሳይዳዳው፤ በአጭር ይቀጫል፡፡ በዱሮ ጊዜ “ትግላችን እረዥም፣ ጉዟችን መራራ” የሚል መፈክር ነበር፡፡ ጣፋጭና አጭር ትግል የለም ለማለት ነው፡፡ ትግል ጠመዝማዛ እንጂ ቀጥ ያለ መስመር እንደሌለው የሚያፀኸይ ጭምር ነው፡፡ በታሪክ ዕውነተኛ ትግል ያካሄዱ የዓለም ድርጅቶች ወይም የፖለቲካ ፓርቲዎች የሚያስተምሩን ይሄንን ነው፡፡ ሳይታክቱ መታገል፣ ሽንፈትን በፀጋ መቀበል፣ ጉድለትን መመርመር ለቀጣዮቹ ዓመታት፣ ከአሁኑ መዘጋጀት! ዕቅድን እጥጉ ድረስ ማቀድና የትላንቱን እንቅፋት እስከመጨረሻው ማጽዳት ተገቢ ነው፡፡ ባላንጣን አለመናቅና እስከፍፃሜው መገላገል ተገቢው የጉዞው ፋይዳ ነው፡፡ ይሄንን ሳንገነዘብ ትግሉ ውስጥ ከገባን ፀፀት ማትረፋችን አይቀሬ ነው፡፡ ሮበርት ብራውን የተባለ ፀሐፊ እንዲህ ይለናል፡-
“ከሙሴ ጀምሮ የኖሩ ታላላቅ መሪዎች የፈሩትን ጠላት ሙሉ በሙሉ መደምሰስ እንዳለባቸው ያውቃሉ፡፡ (ይህንን የተማሩት በከባድ መንገድ ይሆናል አንዳንዴ) ከተዳፈነ እሳት ውስጥ አንዲት ፍም ካለች ምንም ደብዛዛ ብትሆን ቀስ በቀስ እሳት ማስነሳቷ አይቀሬ ነው፡፡ ግማሽ መንገድ ሄዶ ማቆም ከጠቅላላ ማጥፋት የበለጠ ኪሣራ ላይ ሊጥለን ይችላል፡፡ ጠላት አገግሞ ሊበቀል ይችላል። ስለዚህ በአካልም፣ በመንፈስም ማድቀቅ ያስፈልጋል”
ግማሽ መንገድ ተጉዞ መቆምን የመሰለ አደጋ የለም፡፡ “የነብርን ጅራት አይይዙም፤ ከያዙም አይለቁም” የሚለውን የአበሻ ተረት በጽኑ ማስተዋል ብልህነት ነው፡፡
ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን፤
“…የተወጋ በቅቶት ቢኛ፣ የወጋ መች እንቅልፍ አለው፤
የጅምሩን ሳይጨርሰው፡፡” የሚለን ይሄንኑ ነው፡፡
ገና በጠዋት መንገድ ስንጀምር ትርፉን ሲነግሩን መከራውንም አብረን ማስታወስ፣ ትግልን ስናስብ መስዋዕትነትን አብረን ማሰላሰል፤ እጅግ ወሳኝ መሆኑን ከልባችን እናጢን፡፡ አለበለዚያ “መሳም አምሮሽ፣ ጢም ጠልተሽ” እንዲሉ ይሆናል!!

“በጣም የተደበላለቀ ስሜት ነው የተሠማኝ፤ ለረጅም ጊዜ አብረናቸው የቆየናቸው ወዳጆቻችን ሳይወጡ ምንም አይነት ዝግጅት ሳይኖረንና አስቀድሞ ሳይነገረን ድንገት ውጡ ስንባል ማመን ያቅታል፣ ያስደነግጣል፤ ስሜቱ ደስታም አለበት፡፡ የቀሪዎቹም ወዳጆቻችን ጉዳይ ያሳስበኛል፤ ድብልቅልቅ ያለ ስሜት ነው የተሠማኝ፡፡ እኛ የተፈታነው የውጭውን አየር መተንፈስ ችለናል፣ ቤተሰቦቻችንን ማግኘት ችለናል፣ ጓደኞቻችንን አግኝተናል፡፡ በዚህ ሁሉ መሃል የቀሩት ጓደኞቻችን ስላሉ ደስታችን ሙሉ አይደለም፡፡ እንግዲህ የቀሩት ጓደኞቻችን ይፈታሉ የሚል ተስፋ ነው የሰነቅነው፡፡
በታሰርንበት ወቅት በሃገር ውስጥና በመላው አለም የሚገኙ ኢትዮጵያውያንም ሆኑ የኛን ጉዳይ ሠምተው ከጐናችን ሆነው ሲያበረታቱን ነበሩ የሌላ ሀገር ዜጐች ሁሉ ከልብ የመነጨ አክብሮታችንና ምስጋናችንንና እናቀርባለን፡፡ ለቀሩት ጓደኞቻችንም ሆነ በእስር ላይ ላሉት የሙያ አጋሮቻችን ድጋፋቸውን እንዲያሳዩ ልመናዬን አቀርባለሁ”

መንግሥት ከአንድ ዓመት በፊት በሽብር ጠርጥሬያቸዋለሁ ብሎ ክስ ከመሰረተባቸው ጋዜጠኞችና ጦማሪያን መካከል የአምስቱን ክስ አንስቶ ሰሞኑን ከእስር የለቀቀ ሲሆን ቀሪዎቹ ክሳቸው ይቀጥላል ብሏል፡፡ በሌላ በኩል ሽብርተኛ ድርጅትን በሙያ በመርዳት በሚል 5 ዓመት የተፈረደባት ጋዜጠኛና መምህርት ርዕዮት አለሙ ከ4 ዓመት ከ1 ወር እስር በኋላ ከትናንት በስቲያ በአመክሮ ደብዳቤ ከእስር ተለቃለች፡፡
ረቡዕ አመሻሽ ላይ በድንገት ከእስር የተለቀቁት ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ፣ አስማማው ኃ/ጊዮርጊስ፣ ኤዶም ካሣዬ እንዲሁም ጦማሪያኑ ማህሌት ፋንታሁን እና ዘላለም ክብረት ሲሆኑ ጦማሪያኑ አቤል ዋበላ፣ በፍቃዱ ሃይሉ፣ ናትናኤል ፈለቀ እና አጥናፍ ብርሃኔ ክሳቸው ይቀጥላል ተብሏል፡፡
ከተለቀቁት ጋዜጠኞች አንዱ የሆነው ተስፋለም ወልደየስ፤ መለቀቁ ቢያስደስተውም ቀሪ ወዳጆቹ አሁንም እስራቸው መፅናቱ ብዥታ እንደፈጠረበት ለአዲስ አድማስ ተናግሯል፡፡ “ደስታችን ሙሉ አይደለም፣ የተደባለቀ ስሜት ነው እየተሰማን ያለው” ብሏል ጋዜጠኛ ተስፋለም፡፡
በመንግስት አሸባሪ ተብለው ከተሰየሙ የተለያዩ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት ፈጥረዋል የሚል የሽብር ክስ ቀርቦባቸው የነበሩት ጋዜጠኞቹ፤ አቃቤ ህግ ማስረጃ አቅርቦ በማስረጃውና በክሱ ቀጣይ ሂደት ላይ ፍ/ቤት ብይን ለመስጠት ለሐምሌ 13 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቶ እንደነበር ይታወሳል፡፡
በሌላ በኩል ሽብርተኛ ድርጅቶችን በሙያ መርዳት በሚል ክስ ከ15 ዓመት የእስራት ፍርድ በይግባኝ ወደ 5 ዓመት እስር ዝቅ የተደረገላት ጋዜጠኛና መምህርት ርዕዮት አለሙ፤ የአመክሮ ጊዜዋ ቢጠበቅላት ኖሮ ባለፈው ጥቅምት ወር ትፈታ እንደነበረ ጠቁማ “ጥፋትሽን እመኚ” ተብላ እሺ በማለቷ፤ ሙሉ የእስራት ጊዜዋን ጨርሳ ልትወጣ 11 ወራት ሲቀራት ከትላንት በስቲያ በድንገት ከእስር መለቀቋን ለአዲስ አድማስ ገልፃለች፡፡
በሌላ በኩል ከአዲስ አበባ እና የፊንፊኔ ዙሪያ ኦሮሚያ ከተሞች ማስተር ፕላን ጋር በተገናኘ ተቃውሞ አስነስተዋል የተባሉ 6 የኦሮምያ ክልል የተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ተማሪዎችም ከ1 አመት ከ3 ወር እስር በኋላ ሰሞኑን እንደተለቀቁ ታውቋል፡፡
ከዩኒቨርሲቲዎቹ በፖሊስ ተወስደው ታስረው ከነበሩት ተማሪዎች መካከል አዱኛ ፌሶ፣ ቢሊሱማ ዳመና፣ ሌንጂሣ አለማየሁ፣ አብዲ ከማል፣ የአገር ሰው ወርቁ እና ቶፊክ ራሺድ ከ1 አመት በላይ በወህኒ ቤት ቢቆዩም በብዙዎቹ ላይ ክስ አልተመሰረተም ተብሏል፡፡
የጋዜጠኞቹ ጦማሪያኑ መፈታት ከህግ አንፃር
የጋዜጠኞቹና ጦማሪያኑ የህግ አማካሪና ጠበቃ የሆኑት የህግ ባለሙያው አቶ አመሃ መኮንን፤ በ5ቱ ታሳሪዎች መፈታት ጉዳይ ላይ ለአዲስ አድማስ በሰጡት ማብራሪያ፤ በህጉ ፍትህ ሚኒስቴር በማንኛውም ሰአት የጀመረውን ክስ የማቋረጥ ስልጣን እንዳለው ጠቅሰው፣ በፊት በነበረው አሰራር የወንጀለኛ መቅጫ ህጉን መነሻ በማድረግ፣ ክስ ለማንሳት ፍ/ቤትን ማስፈቀድ ይጠየቅ እንደነበረ ተናግረዋል፡፡ ፍ/ቤቱ ካመነበት ብቻ ክሱን ያነሳ ነበር ያሉት የህግ ባለሙያው፤ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ የወጡት አዳዲስ ህጎች የቀድሞውን ሽረው ለፍትህ ሚኒስቴር ክስ የማንሳት ስልጣን ሰጥተውታል ይላሉ፡፡
አዲሱ አዋጅ፣ የፍትህ ሚኒስትሩ ካመነበት ክሱን ያነሳል ብሎ ክስ የማንሳትን ስልጣን ለሚኒስትሩ ይሰጣል የሚሉት አቶ አመሃ፤ በተቃራኒው ፍ/ቤት “ክሱን ለምን አነሳህ?” የሚል ጥያቄ ፍትህ ሚኒስቴርን እንዲጠይቅ አለመደረጉን ይገልፃሉ፡፡ ሙሉ ለሙሉ ክስ የማንሳት ስልጣን ለፍትህ ሚኒስቴር የመሰጠቱ ጉዳይ በሚገባ መተርጎም ያስፈልገዋል ያሉት አቶ አመሃ፤ ሚኒስቴሩ በፈለገ ሰአት ክስ እያነሳና በፈለገ ጊዜ ደግሞ ክሱን እንደገና እያንቀሳቀሰ ዜጎችን መብት የማሳጣት አቅም ሊሰጠው አይገባም የሚል አተያይ አለኝ ብለዋል፡፡
ፍትህ ሚኒስቴር ይሄን ስልጣን ተጠቅሞ “ከዚህ ቀደም ለጊዜው ክሳችንን አንስተናል” ካለ በኋላ፣ በድጋሚ ክሱን የቀጠለበትን የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ የክስ ሂደት ያስታወሱት የህግ ባለሙያው፤ “በወቅቱ ተጨማሪ ምርመራ ለማድረግና ጠንካራ ክስ ለማደራጀት የሚል ምክንያት አቅርቦ አቃቤ ህግ ክሱን አንስቶ የነበረ ቢሆንም ኋላ ላይ ያንኑ ክስ በድጋሚ ሊያቀርብ ችሏል” ሲሉ ያስረዳሉ፡፡ “አዋጁ አላግባብ እየተተረጎመ በመሆኑ ነው እንጂ ፍትህ ሚኒስቴር ሲያሻው ክስ አቋርጦ ሲፈልግ ክሱን ማንቀሳቀስ አይችልም፤ ክሱን ሲያቋርጡ ምክንያታቸውን እንዲያቀርቡም በፍ/ቤት መጠየቅ አለባቸው” ብለዋል - ጠበቃው፡፡
የጋዜጠኞቹና ብሎገሮቹም ጉዳይ የአቃቤ ህግን ማስረጃ ይከላከሉ ወይስ በነፃ ይሰናበቱ በሚለው የህግ ሂደት ላይ ብይን ለመስጠት ለሐምሌ 13 ቀን 2007 ዓ.ም ተቀጥሮ ሳለ በድንገት 5ቱ ሲለቀቁ፣ የተለቀቁበት ምክንያት በግልፅ አልተብራራም ያሉት ጠበቃው፤ በዚህም የተነሳ ጋዜጠኞቹና ብሎገሮቹ ላይ በፈለጉት ጊዜ ክሱን ሊያንቀሳቅሱ ይችላሉ የሚል ስጋት ይፈጥራል፤ ክሱ የተነሳበት ምክንያት ባልታወቀበት ሁኔታ መተማመኛ ማግኘት አይቻልም ብለዋል፡፡
“መንግስት በፈለገ ሰአት አስሮ ባሻው ጊዜ መልቀቁ እስከመቼ ይቀጥላል” ሲል የሚጠይቀው ጋዜጠኛው፤ የተፈቱት ልጆች በአሁን ሁኔታው ነገ ተመልሰው እስር ቤት የማይገቡበት ምክንያት አይኖርም ብሎ ሙሉ ለሙሉ መተማመን አይቻልም” ብሏል፡፡
የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችም የህግ ባለሚያውን ስጋት ይጋራሉ፡፡ የመላ ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ፕሬዚዳንት አቶ አበባው መሃሪ፤ “የጋዜጠኞቹና ጦማሪያኑ መለቀቅ መልካም ቢሆንም ከእስር የተለቀቁበት መንገድ መንግስት ባሻው ጊዜ መልሶ ስላለማሰሩ ዋስትና አይሆንም” ብለዋል፡፡
የኢዴፓ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ወንደወሰን ተሾመ በበኩላቸው፤ ጋዜጠኞቹና ጦማሪያኑ መፈታታቸው መልካምና አስደሳች መሆኑን ጠቅሰው፣ የቀሩትም ቢሆኑ መፈታት አለባቸው የሚል አቋም አለን ብለዋል፡፡ “የኦባማ ወደ ኢትዮጵያ ለመምጣት ማቀድ በራሱ ተፅዕኖ ሳይፈጥር እንደማይቀር ጥርጣሬ አለን” ያሉት አቶ ወንድወሰን፤ የዳያስፖራው ሰሞነኛ ተፅዕኖም ቀላል ግምት የሚሰጠው አይደለም ይላሉ፡፡
የፖለቲካ ሳይንስ መምህሩና የመድረክ አመራር ዶ/ር መረራ ጉዲና በሰጡት አስተያየት፤ “የጦማሪያኑና የጋዜጠኞቹም ሆነ የሌሎች ፖለቲከኞች እስር በምዕራባውያኑ ሚዲያዎች መነጋገሪያ መሆኑን ተከትሎ እዚህ ያሉት የአሜሪካ አምባሳደር በመንግስት ላይ ተፅዕኖ ሳያሳርፉ አይቀርም የሚል ግምት አለኝ” ብለዋል፡፡
“ጋዜጠኞቹና ጦማሪያኑ በመፈታታቸው ደስ ብሎኛል፤ እንኳን ደስ ያላችሁ የሚል መልዕክቴ ይድረሳቸው” ያሉት ዶ/ር መረራ፤ “መንግስት ምንም እንኳ እነሱን ቢፈታም የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን ጨምሮ ሌሎች በኦሮሚያ ክልል ያሉ ወጣቶችን እያሰረ ነው” ብለዋል፡፡ “ወከባና እንግልቱም ከምርጫው በኋላ ተጠናክሮ ቀጥሏል” የሚሉት ምሁሩ፤ “አንዱን መፍታት አንዱን ማሰር የኢህአዴግ ባህሪ ነው” ይላሉ፡፡ “የጦማሪያኑና ጋዜጠኞቹ ከእስር መለቀቅን እንደ ቋሚ የፖሊሲ ለውጥ ማየት አያሻም” የሚሉት ምሁሩ፤ ለኦባማ እጅ መንሻ የተደረገም ሊሆን ይችላል ብለዋል፡፡
የፍትህ ሚኒስቴር የ5ቱን ጋዜጠኞችና ጦማሪያን ከእስር መለቀቅ አስመልክቶ ለመገናኛ ብዙሃን በላከው መግለጫ፤ በህግ በተሰጠው ክስን የማቋረጥ ስልጣን የጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ፣ አስማማው ሃ/ጊዮርጊስ፣ ኤዶም ካሣዬ እንዲሁም የጦማሪያኑ ማህሌት ፋንታሁን እና ዘላለም ክብረት ክስን ማቋረጡን ጠቅሶ፣ የቀሪዎቹ 4 ተከሳሾች ክስ ይቀጥላል ብሏል፡፡
አለማቀፍ ሚዲያዎችን ጨምሮ የተለያዩ አስተያየት ሰጪዎችና ፖለቲከኞች፤ የጋዜጠኞቹ መፈታት በቅርቡ ኢትዮጵያን ይጐበኛሉ ተብሎ የሚጠበቁት የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ተፅዕኖ ውጤት መሆኑን እየገለፁ ሲሆን መንግስት በበኩሉ፤ የክሱ መቋረጥና የታሣሪዎቹ መፈታት የፕሬዚዳንቱ ተፅዕኖ ውጤት አይደለም ብሏል፡፡
የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ እውነቱ ብላታ፤ የፍትህ ሚኒስቴር በህግ በተሰጠው ስልጣን በፈለገው ጊዜ ክስ ማቋረጥ እንደሚችል ጠቅሰው፤ “ለፍትህ ሚኒስቴር ክስ የማቋረጥ ስልጣን የሰጠው ህግ የወጣው ኦባማ ስለሚመጣ አይደለም፤ አስቀድሞም ያለ ነው” ብለዋል፡፡ አክለውም፤ “መንግስት በየትኛውም መንገድ ቢሆን የሀገር ሉአላዊነትን ጉዳይ ለድርድር አያቀርብም፤ ክሱ የተነሳው በማንም ተጽእኖ አይደለም፤ ፍትህ ሚኒስቴር ባለው ስልጣን ብቻ የተነሳ ነው” ብለዋል - ሚኒስትሩ ለአዲስ አድማስ በሰጡት ማብራሪያ፡፡

ከ13 ሚሊዮን ዶላር በላይ ወጪ ሆኖበታል ተብሏል
ኮሪያ ሆስፒታል ከ13 ሚሊዮን ዶላር በላይ ወጪ በማድረግ የሰራው የሆስፒታሉ የማስፋፊያ ፕሮጀክት በትላንትናው ዕለት ተመረቀ፡፡ ሆስፒታሉ በኮሪያ ዘመቻ ላይ የተሳተፉ ኢትዮጵያውያን ዘማቾች ላደረጉት አስተዋፅኦ እንደ ምስጋና ሆኖ እንዲሰራና አገልግሎት እንዲሰጥ ታስቦ እ.ኤ.አ በህዳር ወር 2004 ዓ.ም መመስረቱን የገለፁት የሆስፒታሉ ሜዲካል ዳይሬክተር ዶክተር ኪም ቹልሱ፤ዛሬ በአገሪቱ በህክምናው ዘርፍ ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሱ የህክምና ባለሙያዎችና ዘመናዊ መሳሪያዎች የሚገኙበት ታላቅ ሆስፒታል ለመሆን መብቃቱን ገልፀዋል፡፡ እስከአሁን በአገሪቱ ውስጥ የማይሰጡ የተለያዩ የህክምና አይነቶችን ጨምሮ ከ20 በላይ ዲፓርትመንቶችን ያቀፈው አዲሱ የማስፋፊያ ፕሮጀክት፣እጅግ ዘመናዊ የህክምና መሳሪያዎችና ከ60 በላይ VIP አልጋዎችን መያዙን ዳይሬክተሩ ጠቁመዋል፡፡ የማስፋፊያ ፕሮጀክቱ ሆስፒታሉ ሲቋቋም ይዞት ከነበሩ ዕቅዶች ሁለተኛው ሲሆን ተግባራዊ መሆን ከሚገባው ጊዜ በጥቂት አመታት መዘግየቱ ተጠቁሟል፡፡ ቀጣዩ የሆስፒታሉ ዕቅድ (Third phase) መንትያ ህንፃዎችን መገንባትና የሆስፒታሉን አስተዳደርና ስራውን ሙሉ በሙሉ ለኢትዮጵያውያን ማስረከብ እንደሆነም በዚሁ ወቅት ተገልጿል፡፡