Administrator

Administrator

በዳንኤል ተገኝ ተደርሶ በአለምፀሐይ በቀለ ዳይሬክት የተደረገውና በዳኒሮጐ ማስታወቂያና ፊልም ፕሮዳክሽን የቀረበው “የሴም ወርቅ” የተሰኘ ፊልም ባለፈው ሰኞ ምሽት በቀይ ምንጣፍ ሥነስርዓት ተመረቀ፡፡
የ1፡45 ደቂቃ ርዝማኔ ያለውን ፊልም ሰርቶ ለማጠናቀቅ 2 ዓመት ያህል የፈጀ ሲሆን 1.5 ሚ. ብር እንደወጣበት አዘጋጆቹ ጠቁመዋል፡፡ በዚህ ልብ አንጠልጣይ የቤተሰብ የፍቅር ፊልም ላይ አርቲስት ፍቃዱ ተ/ማርያም፣ አምለሰት ሙጬ፣ ዳንኤል ተገኝ፣ ሙሉ ሰለሞን፣ ዝናህብዙ ፀጋዬ እና ሌሎች አንጋፋና ወጣት ተዋንያን ተሳትፈውበታል ተብሏል፡፡
በምረቃ ስነ ስርአቱ ላይ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትሩ አቶ አሚን አብዱል ቃድርን ጨምሮ አርቲስት አበበ ተስፋዬ (ፋዘር) እና ሌሎችም ታዋቂ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች የተገኙ ሲሆን ሚኒስትሩ ፊልሙን ከተመለከቱ በኋላ በሰጡት አስተያየት፤“በጣም ደረጃውን የጠበቀ የአገራችንን ገፅታ የሚያሳይ ፊልም ነው” ሲሉ ማድነቃቸውን አዘጋጆቹ ለአዲስ አድማስ ጠቁመዋል፡፡
የፊልሙ 70 ከመቶ ቀረጻ የተካሄደው በባህር ዳር እና ጎንደር ከተሞች ላይ ሲሆን ቀሪው አዲስ አበባ መቀረጹን ለማወቅ ተችሏል፡፡ በፊልሙ ላይ ከዕውቅ ተዋናዮች ባሻገር የዳሽን ቢራ ሰራተኞችን ጨምሮ ከ100 በላይ የሚሆኑ ሰዎች መሳተፋቸውን የጠቆመው የፊልሙ ደራሲና ፕሮዱዩሰር አርቲስት ዳንኤል ተገኝ፤ዳሽን ቢራ ለፊልሙ ከ1.3 ሚሊዮን ብር በላይ ስፖንሰር ማድረጉን ገልጿል፡፡
ዳሽን ቢራ ፊልሙ ለተመልካች እንዲበቃ ላደረገው ድጋፍ፣ታዋቂ አርቲስቶችና የውጭ ሃገር ዜጎች የተሳተፉበት ማስታወቂያ ሰርተው ለፋብሪካው በስጦታ ማበርከታቸውን አርቲስቱ ተናግሯል፡፡ ባለፈው ሰኞ በፊልሙ ምረቃ ላይ የታደሙ አንዳንድ ተመልካቾች፤ፊልሙ የዳሽን ማስታወቂያ ይመስላል የሚል ትችት የሰነዘሩ ሲሆን በብስጭት ፊልሙ ከመጠናቀቁ በፊት ጥለው የወጡ እንደነበሩም ለማወቅ ተችሏል፡፡ አርቲስት ዳንኤል፤ ስፖንሰር አድራጊውን የዳሽን ቢራ ፋብሪካን በፊልሙ ውስጥ ቀጥተኛ ባልሆነ መንገድ ለማስተዋወቅ መሞከሩን አልካደም፡፡ ነገር ግን መላ ፊልሙ የዳሽን ቢራ ማስታወቂያን ይመስላል የሚያሰኝ አይደለም ብሏል፡፡   
 #የሴም ወርቅ” በአዲስ አበባ በሚገኙ ሲኒማ ቤቶች በሙሉ በመታየት ላይ መሆኑን የጠቆሙት አዘጋጆቹ፤በባህር ዳር እና በጎንደር ባለፈው ረቡዕ እና ሐሙስ መመረቁን አክለው ገልጸዋል፡፡  

የደራሲ ኻሊድ ሆሴኒ “A Thousand Splendid Sun” የተሰኘው ልቦለድ በአያልቅበት አደም “ዶስቲ” በሚል ርዕስ ወደ አማርኛ የተተረጐመ ሲሆን በቅርቡ ለንባብ እንደሚበቃ ተርጓሚው ለአዲስ አድማስ ጠቁሟል፡፡
ኻሊድ ሆሴኒ ይበልጥ የሚታወቀው “The Kite Runner” በተሰኘ የበኩር ሥራው ሲሆን አሁን ወደ አማርኛ የተተረጎመው ሁለተኛው ሥራው ነው ተብሏል፡፡ በ361 ገፆች የተቀነበበው “ዶስቲ”፤በ80 ብር ለገበያ እንደሚቀርብ ለማወቅ ተችሏል፡፡

የሰዓሊና ገጣሚ ገብረክርስቶስ ደስታ “መንገድ ስጡኝ ሰፊ” የተሰኘ የግጥም መድበል ላይ በነገው ዕለት ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ በብሄራዊ ቤተ መፃህፍትና ቤተ መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ ውይይት እንደሚካሄድበት ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ አስታወቀ፡፡
ለውይይቱ መነሻ ሃሳብ የሚያቀርቡት ገጣሚና ጋዜጠኛ ባንችአየሁ ዓለሙ ሲሆኑ የጥበብ ወዳጆች በውይይቱ ላይ እንደሚታደሙ ሚዩዚክ ሜይዴይ ጥሪውን አስተላልፏል፡፡
በሌላ በኩል የደራሲ ገዛኸኝ ላቀው “የደቦቃ ጥንስስ” የተሰኘ መፅሀፍ በነገው ዕለት ከጠዋቱ 3 ሰዓት የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች በሚገኙበት በዚያው በብሄራዊ ቤተ መፃህፍትና ቤተ መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ እንደሚመረቅ የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር ገልጿል፡፡  

“ወጣትነት የኪነ ጥበብ፣የማነቃቂያና የፈጠራ ማሳያ ዝግጅት; በሚል መሪ ቃል በዛሬው ዕለት ከቀኑ 10፡30 ጀምሮ በአክሱም ሆቴል የሥነ ፅሁፍ ዝግጅት ይቀርባል።  
በፕሮግራሙ ላይ ግጥሞችና ወጎች እንዲሁም በወጣቶች የተዘጋጁ ወጣቱን የሚያነቃቁ ስራዎች እንደሚቀርቡ ታውቋል፡፡ ፕሮግራሙ የተዘጋጀው ለመጀመሪያ ጊዜ ሲሆን በዋናነትም ወጣቱን ለማስተማርና ለማዝናናት ያለመ ነው ተብሏል፡፡  

Saturday, 08 August 2015 09:20

የፀሐፍት ጥግ

(ስለጨለምተኝነት)
- ወጣት ጨለምተኛን እንደማየት አሳዛኝ
ነገር የለም፡፡
ማርክ ትዌይን
- ለጨለምተኛ ሃውልት ቆሞለት አይቼ
አላውቅም፡፡
ፖል ሃርቬይ
- ጨለምተኛ ማለት እውነትን ያለጊዜው
የሚናገር ሰው ነው፡፡
ሲራኖ ዲ በርግራክ
- ሙሉ በሙሉ ጨለምተኛ ነኝ ብዬ
አላስብም፡፡ ስለዚህ በሁሉም ፊልሞቼ
ውስጥ ተስፋን የምታዩ ይመስለኛል፡፡
ስፓይክ ሊ
- እኔ ራሴን እንደ ተስፈኛም ሆነ
እንደጨለምተኛ አልቆጥርም፡፡
ኒክ ቦስትሮም
- ጨርሶ ጨለምተኛ አይደለሁም፤ ነገር ግን
ተስፈኛም አልባልም፡፡
ናቴ ሎውማን
- ጨለምተኛ አንድም ጦርነት አሸንፎ
አያውቅም፡፡
አይዞንሃወር
- ዓለምን ስመለከት ጨለምተኛ ነኝ፤ ሰዎችን
ስመለከት ግን ተስፈኛ ነኝ፡፡
ካርል ሮጀርስ
- ጨለምተኝነት ወደ ደካማነት፣ ተስፈኝነት
ወደ ጥንካሬ ይመራል፡፡
ዊሊያም ጄምስ
- ተስፈኞችም ጨለምተኞችም
ለህብረተሰባችን የሚያበረክቱት አስተዋፅኦ
አለ፡፡ ተስፈኛ አውሮፕላንን ሲፈጥር፣
ጨለምተኛ ፓራሹትን ይፈጥራል፡፡
ጂ.ቢ.ስተርን
- ተስፈኛ አዲሱ ዓመት መጥባቱን ለማየት
እስከ እኩለ ሌሊት ሲጠብቅ፣ ጨለምተኛ
አሮጌው ዓመት መሰናበቱን ለማረጋገጥ
እስከ እኩለ ሌሊት ይጠብቃል፡፡
ቢል ቫውግን
- ጨለምተኝነቴ የጨለምተኞችን ሀቀኝነት
እስከመጠራጠር ድረስ ይዘልቃል፡፡
ኢድሞንድ ሮስታንድ
- ጨለምተኛ ማለት፤ ዕድል ስታንኳኳ
በኳኳታው ድምፅ የሚያማርር ሰው ነው፡፡
ኦስካር ዋይልድ
- የጨለምተኛነት መሰረቱ ፍርሃት ብቻ
ነው።
ኦስካር ዋይልድ
- ምንጊዜም ቢሆን ከጨለምተኛ ሰው
ላይ ገንዘብ ተበደሩ፤ ይከፍሉኛል ብሎ
አይጠብቅም፡፡
ያልታወቀ ደራሲ

‹‹በመዝባሪ ላይ አልደራደርም፤ እስከ መጨረሻው ከፊት ለፊት ነኝ››

    በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የአድባራቱን ሰፋፊ መሬቶችና የገቢ ማስገኛ ተቋማት እየመዘበሩ ራሳቸውን ያበለጸጉ የአስተዳደር ሓላፊዎች በሕግ እንዲጠየቁ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ መመሪያ ሰጡ፡፡
የአስተዳደር ሓላፊዎቹ የአድባራቱን ሰፋፊ መሬቶችና የንግድ ተቋማት ያለጨረታ ከገበያ ዋጋ በታች ከ15 ዓመት እስከ ዕድሜ ልክ በመዋዋል የቤተ ክርስቲያኒቱን ጥቅሞች አሳልፈው በመስጠት ራሳቸውን አበልጽገዋል- ተብሏል፡፡
ፓትርያርኩ መመሪያውን የሰጡት፣ ላለፉት ስምንት ወራት በሀገረ ስብከቱ አድባራትና አንዳንድ ገዳማት የመሬት፣ የሕንፃና የልዩ ልዩ ገቢ ማስገኛ ተቋማት ኪራይ ተመንን ሲያጣራ የቆየው ኮሚቴ ያዘጋጀው ጥናታዊ ሪፖርት ከጠቅላይ ጽ/ቤቱ የውሳኔ ሐሳብ ጋር ከትላንት በስቲያ ከቀረበላቸው በኋላ ነው፡፡
በፓትርያርኩ መመሪያ የተቋቋመው ኮሚቴው፣ በ51 አድባራት መሬት፣ ሕንፃና ሕንፃ ነክ ጉዳዮች ላይ ባካሔደው ጥናት የተጠቆሙት የመፍትሔ ሐሳቦችና በዋና ሥራ አስኪያጁ በብፁዕ አቡነ ማቴዎስ ሰብሳቢነት የሚመራው የአስተዳደር ጉባኤ የተስማማባቸው የመፍትሔ ሐሳቦች በሙሉ ተፈጻሚ እንዲኾኑ አቡነ ማትያስ ትእዛዝ ሰጥተዋል፡፡
በጥናቱ ሒደት የኮሚቴውን አባላት በጥቅም ለመደለል ከመሞከር ጀምሮ በማስፈራራትና ስም በማጥፋት የማጣራት ሥራውን ለማስተጓጐል ሲጥሩ የነበሩ ሐላፊዎች፣ በመፍትሔው አተገባበር ላይም ዕንቅፋት ሊፈጥሩ ይችላሉ ለሚለው ስጋት ፓትርያርኩ በሰጡት ምላሽ፤ ‹‹ወደ ኋላ ወደ ጎን የለም፤ ወደፊት ነው፤ በቤተ ክርስቲያን ሀብት ምዝበራ ከማንም ጋር አልደራደርም፤ ከጎኔ ኹኑ፤ እስከ መጨረሻው ከፊት ለፊት ነኝ›› ሲሉ በቁርጠኝነት ተናግረዋል፡፡
በጥናታዊ ሪፖርቱ እንደቀረበው፤ የገቢ ማስገኛ የንግድ ተቋማቱ፣ ከአዲስ አበባ የመሬት ገበያ አንጻር ሊታሰብ ከማይችልበት ዝቅተኛው በካሬ ሜትር 0.37 ሳንቲም፣ ከፍተኛው ብር 70 ያለጨረታ ከ15 ዓመት እስከ ዕድሜ ልክ የኪራይ ውል ተፈጽሞባቸዋል፡፡ ይህም ጥቂት ሙሰኛ የደብር ሓላፊዎችና ግለሰብ ነጋዴዎች ሚልየነር እንዲኾኑበት ዕድል በመስጠት ቤተ ክርስቲያኒቱን የበይ ተመልካች እንዳደረጋት ተገልጧል፡፡
የአድባራት አለቆች፣ ጸሐፊዎች፣ ሒሳብ ሹሞችና የሰበካ ጉባኤ አባላት በተገኙበት በተካሔደው ማጣራት ለጥናት ቡድኑ መረጃ በመስጠታቸውና ጥያቄ በማንሣታቸው ከመመሪያ ውጭ ከሓላፊነታቸው የታገዱት፣ የአራዳ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ደብር ዋና ተቆጣጣሪ መጋቤ ጥበብ ወርቁ  አየለና የደብረ ጽጌ ቅዱስ ዑራኤል ቤተ ክርስቲያን ዋና ሒሳብ ሹም ወ/ሮ መና የማነ ብርሃን ሥዩም ወደ ቀድሞ የሓላፊነታቸውና ቦታቸው እንዲመለሱ በአስተዳደር ጉባኤው ተወስኗል፡፡
የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የሕግ አገልግሎት መምሪያ፤ ሙሰኛ ሓላፊዎችን ለሕግ ከማቅረብ በተጨማሪ  የገቢ ማስገኛ ተቋማቱ ለሦስተኛ ወገን እየተላለፉ የተሰጡበትን ውሎች በመሰረዝ የቤተ ክርስቲያኒቱን ጥቅም የሚያስከብርና የሚያስቀድም ወጥ አሠራር እንዲዘረጋ ተወስኗል፤ ተቋማቱም በየአጥቢያው በተናጠል የሚተዳደሩበት አካሔድ ቀርቶ በማዕከል የሚመሩበት ሥርዐት እንደሚበጅ የተጠቆመ ሲኾን፤  ይህንንም የሚያስፈጽም ጽ/ቤትና ፓትርያርኩ የሚሰበስቡት ቦርድ እንደሚቋቋም ታውቋል፡፡
የፓትርያርኩ ልዩ ሀገረ ስብከት በኾነው አዲስ አበባ፣ ጥናቱ ባልሸፈናቸው ሌሎች አድባራትና ገዳማትም እንዲቀጥል አቡነ ማትያስ ያዘዙ ሲኾን በመጪው ዓመት ጥቅምት በሚካሔደው 34ኛው ዓመታዊ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤም በአገር አቀፍ ደረጃ እንዲተገበር በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ እንዲወሰንበት እንደሚያደርጉም አስታውቀዋል፡፡

    አዲስ አመራር እንደሚመረጥ ይጠበቃል

      ሰማያዊ ፓርቲ የመጀመሪያውን ጠቅላላ ጉባኤ ነሐሴ 16 እና 17 የሚያካሂድ ሲሆን በዚህ ጉባኤ አዲስ መራር ይመረጣል ተብሎም ይጠበቃል፡፡ በፓርቲው ህገ ደንብ መሰረት ጠቅላላ ጉባኤ የሚደረገው በየ3 ዓመቱ መሆኑን የጠቀሱት የፓርቲው ብሄራዊ ም/ቤት ሰብሳቢ አቶ ሰይድ ኢብራሂም፤ ጉባኤው በሐምሌ መካሄድ የነበረበት ቢሆንም በአንዳንድ ምክንያቶች ምክር ቤቱ ለ3 ወር የማራዘም ስልጣኑን ተጠቅሞ እስከ ነሐሴ ማራዘሙን ገልፀዋል፡፡ በጉባኤው ላይ የሚሳተፉ አባላት ቁጥርና የጉባኤውን አካሄድ ለመወሰን ብሄራዊ ምክር ቤቱ በነገው እለት ስብሰባ እንደሚያደርግም ሰብሳቢው ተናግረዋል፡፡ ጠቅላላ ጉባኤውን እንዲያሳልጥ የተቋቋመው ኮሚቴምበእለቱ ሪፖርቱን ያቀርባል ብለዋል፡፡ በፓርቲው ህገ ደንብ መሰረት አንድ ፕሬዚዳንት ለሁለት የስልጣን ዘመን ብቻ መመረጥ እንደሚችል የጠቆሙት አቶ ሰይድ፤ በአሁኑ ወቅት ፓርቲውን የሚመሩት ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ለሁለተኛ ጊዜ ይወዳደሩ አይወዳደሩ እስካሁን እንዳላሳወቁ ተናግረዋል፡፡

ለዓመታት የአዕምሮ ሆስፒታል የቆየ አንድ ሰው ነበረ፡፡ ተሽሎት ከሆስፒታሉ ይውጣ ከተባለ በኋላ
ዶክተሩ እስቲ ለማንኛውም ቃለ - መጠይቅ ላድርግለት ብሎ ያስጠራውና፤
“እስቲ አንድ ነገር ንገረኝ፡፡ አሁን ከዚህ ሆስፒታል ብትወጣ ኑሮህን እንዴት አድርገህ ለመምራት ታስባለህ?” አለው፡፡ ሰውዬውም፤ “መቼም ተመልሼ ህይወት መጀመሬ በጣም ድንቅ ነገር ነው፡፡
ኑሮዬን ለመምራት የመጀመሪያ እርምጃዬ ዱሮ የሠራኋቸውን ስህተቶች አለመድገም ነው። የኒኩሊየር
ፊዚክስ ባለሙያ ነበርኩ፡፡ የኒኩሊየር መሣሪያ ጥናትና ምርምር ነበር አዕምሮዬ እንዲነካ ያደረገው፡፡
ከዚህ ብወጣ ወደ ንፁሁ ንድፈ - ሀሳብ ላይ ብቻ አተኩራለሁ፡፡ ያ ብዙ የማያስጨንቀኝ ስለሆነ
ሰላም አገኛለሁ”
የአዕምሮ ሐኪሙ፡-
“ድንቅ ነው!” አለ በመደሰት፡፡
“አለበለዚያ ደግሞ” አለና ቀጠለ ሰውዬው፤ “ላስተምርም እችላለሁ። የሳይንቲስት ትውልድ የማፍራት ኃላፊነት ያለብን ይመስለኛል፡፡ በዚያ ረገድ ላግዝ እችላለሁ፡፡” “በጣም ትልቅ ሀሳብ ነው” አለ የአዕምሮ ሀኪሙ፡፡ “ሌላው አማራጬ ደግሞ መፃፍ ነው፡፡ ህዝባችን የሳይንስ መፅሀፍ ዕጥረት አለበት፡፡ ወይም ደግሞ
በዚህ መልካም ተቋም ውስጥ ስላገኘሁት ልምድ ልፅፍም እችላለሁ፡፡” “ያማ በጣም የጠለቀ፣ ግሩም አማራጭ ነው” አለ ሀኪሙ፡፡ “በመጨረሻም” አለ የአዕምሮ ህመምተኛው፤
“በመጨረሻም፤ እነዚህ ሁሉ አማራጮች እምቢ ካሉኝ፣ በቃ የቡና ጀበና መሆኔን እቀጥላለሁ!” አለ፡፡
ሐኪሙ ጭንቅላቱን ይዞ፤
“በል እዚሁ ቁጭ በል!” አለው፡፡
*       *      *
ደህና ሄደን ከመቆልመም ይሰውረን፡፡ የጀመርነውን በአግባቡ ለመጨረስ ጥናቱንም ፅናቱንም ይስጠን! በሙስና ከመመንደግ፣ ቁልቁል ከማደግ ዲበ - ኩሉ ይጠብቀን! ከሸፍጠኛ ዳኛ፣ ከአባይ መስካሪ ያድነን! የመጪውን ዓመት ትምህርታችንን ይግለጥልን! ያለፈውን ዓመት ስህተታችንን እንዳንደግም ልብና ልቡና ይስጠን፡፡ ከውጪ ሸረኛ፣ ከውስጥ ቂመኛ ይጠብቀን፡፡ ሀገራችን “ደንጊያና ቅል ተላግቶ፣ ዜጋና ሹም ተሟግቶ አይሆንም” የማንልባት ሀገር መሆን ይኖርባታል፡፡ ሹም ሲበድል ዝም ብለን የማናይበት፣ ዜጋ መብቱን ሳያውቅ ሲቀር ምክንና ውጤቱን በወግ በወጉ የምናስረዳበት ሁኔታ እንዲኖር መጣር ይኖርብናል፡፡ “እናቱ ወንዝ የወረደችበትም እናቱ የሞተችበትም እኩል የሚያለቅሱበት” ሀገር መሆን የለባትም፡፡ ከቶውንም ሃይማኖታዊ አስተምህሮት ከፖለቲካዊ ጥቅም ፍለጋ ተለይተው የሚታዩበት ሀገር ታስፈልገናለች፡፡ ከሁሉም በላይ ዛሬ ሐሳዊ - ዲሞክራሲን (Pseudo - democracy) መዋጋት ግዴታ መሆኑን መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡ በአስመሳይነት በአደባባይ መደስኮርና ዕውነተኛው ዲሞክራሲ ለየቅል ናቸው! መንግሥት የአምስት ዓመቱን ዕቅድ አፈፃፀም ድክመትን በወጉ ገምግሞ ዓይነተኛ መፍትሄ መስጠት ይጠበቅበታል፡፡ የእከክልኝ ልከክልህን ዜማ ቅኝቱን በመሰረታዊ መልኩ መለወጥ ይኖርበታል፡፡
በተለይም ደግሞ በሂደቱ ውስጥ ዓይን እንደሚቆረቁር አሸዋ ሲያስቸግር የነበረውን ሙስና በቅጡ
መፈተሽ ይኖርበታል፡፡ ዛሬም የፍትህን፣ የሰብዓዊ መብቶችን፣  የትምህርት ሂደትን ጉዳይ በአፍዓዊ መልኩ ሳይሆን በልባዊ መልኩ መመርመር መሰረታዊ ነገር ነው፡፡ ይህ ካልሆነ “እያቃጠለ ከሚያጠግበኝ፣ እስኪቀዘቅዝ ይራበኝ” የሚለውን መጥቀስ ግድ ይሆናል፡፡ ከዚህም ይሰውረን!

 በታንዛኒያ ከተማ ዳሬሰላም 13  ክለቦችን በማሳተፍ ሲካሄድ የቆየው 48ኛው የምስራቅ አፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንሺፕ (ካጋሜ ካፕ) ትናንት በግማሽ ፍፃሜ ጨዋታዎች ቀጥሏል፡፡
ከግማሽ ፍፃሜ ጨዋታዎቹ በፊት በተደረጉት 26 ጨዋታዎች 74 ጎሎች ተቆጥረዋል፡፡ በአንድ ጨዋታ በአማካይ 2.54 ጎሎች ማለት ነው፡፡
የኡጋንዳው ክለብ ካምፓላ ሲቲ የሱዳኑን አልሃሊ ሸንዲ 3ለ0 በማሸነፍ እንዲሁም ሌላው የኡጋንዳ ክለብ አዛም የታንዛኒያውን ያንግ አፍሪካንስ በመለያ ምት 5ለ3 አሸንፎ ለግማሽ ፍፃሜ ደርሰዋል፡፡ ሁለቱም ክለቦች በምድብ 3 ከአዳማ ከነማ ጋር የተደለደሉ ነበሩ፡፡ በግማሽ ፍፃሜ እርስበራስ ተገናኝተዋል፡፡ ሌሎቹ የግማሽ ፍፃሜ ተፋላሚዎች የሱዳኑ አል ካርቱም እና የኬንያው ጎሮማሃያ ናቸው፡፡ አልካርቱም በሩብ ፍፃሜ የሩዋንዳውን ኤፒአር 4ለ0 ሲረታ ጎሮማሃያ ደግሞ የደቡብ ሱዳኑን አል ማላይካ 2ለ1 በማሸነፍ ለግማሽ ፍፃሜው ደርሰዋል፡፡ ትናንት ሁሉም የግማሽ ፍፃሜ ጨዋታዎች ተደርገዋል፡፡
ኢትዮጵያን በመወከል የተሳተፈው  አዳማ ከነማ በምድብ 3 ባደረጋቸው ሶስት ጨዋታዎች ተሸንፎ በጊዜ የተሰናበተው ምንም ነጥብ ሳያስመዘግብ በሰባት የግብ እዳ ነው፡፡  በምድብ 3 የመጀመርያ ጨዋታውን ከደቡብ ሱዳኑ ክለብ ማላይካ ጋር ባደረገበት ወቅት በ30ኛው ደቂቃ ታከለ አለማየሁ ባስቆጠረው ግብ  አዳማ ከነማ መምራት ቢችልም በመጨረሻ 2ለ1 ነበር የተሸነፈው፡፡  በሁለተኛው ጨዋታ ተገናኝቶ የነበረው ከኡጋንዳው ተወካይ ኬሲሲ ጋር ነበር፡፡  በ79ኛው ደቂቃ ያቆብ ፍስሃ በፈፀመው ፋውል ፍፁም ቅጣት ከተሰጠበት በኋላ የኬሲሲ አምበል  ጎሉን በማስቆጠሩ 1ለ0 ተሸንፏል፡፡ በምድብ 3 የመጨረሻ ጨዋታውን ከታንዛኒያ ክለብ አዛም ጋር አድርጎ 4ለ0 ከተሸነፈ በኋላ ከውድድሩ መሰናበቱ ይታወቃል፡፡ በሴካፋ የክለቦች ሻምፒዮና ካጋሜ ካፕ ታሪክ የኢትዮጵያ ክለቦች ውጤታማነት ቢያንስ ከአምስት የዞኑ አባል አገራት ከኬንያ፤ ኡጋንዳ፤ ታንዛኒያ፤ ሩዋንዳና ብሩንዲ ያነሰ ነው፡፡ በክለቦች ሻምፒዮናው ኢትዮጵያን የወከለ ክለብ ያስመዘገበው ትልቁ ውጤት ቅዱስ ጊዮርጊስ በ2010 እኤአ ላይ ለዋንጫ ጨዋታ የደረሰበት ብቻ ነው፡፡ በምስራቅ አፍሪካ የክለቦች ሻምፒዮና ላይ እጅግ ውጤታማው ክለብ የታንዛኒያው ሲምባ ሲሆን ባገኛቸው ስድስት ዋንጫዎች ነው፡፡ የኬንያው ኤፍሲ ሊዮፓርድስ፤ የታንዛኒያው ያንግ አፍሪካንስ፤ የኬንያዎቹ ጎሮማሃያ እና ታስከር ኤፊሲ እኩል ለ5 ጊዜያት ዋንጫዎችን በመውሰድ በከፍተኛ ውጤት ሁለተኛ ደረጃን ተጋርተዋል፡፡ የሩዋንዳው ኤፒአርና የሱዳኑ አልሜሪክ እያንዳንዳቸው ሁለት ዋንጫዎችን ሲቀዳጁ፤ የኡጋንዳው ኬሲሲ፤ የሩዋንዳው አትራኮን፤ የኡጋንዳው ፖሊስ ኤፍሲ፤ የሩዋንዳው ራዮን ስፖርትስ፤ እንዲሁም የብሩንዲው ቪታሎ ኦ ቢያንስ አንድ ጊዜ የዋንጫው ተሸላሚ ሆነዋል፡፡ በአገር ደረጃ ደግሞ የኬንያ ክለቦች 15 ጊዜ ሻምፒዮን በመሆን ሲመሩ፤የታንዛኒያ ክለቦች በ11 የዋንጫ ድሎች ይከተሏቸዋል፡፡ የኡጋንዳ ክለቦች 5 ጊዜ፤ የሩዋንዳ ክለቦች 4 ጊዜ ፤ የሱዳን ክለቦች 3 ጊዜ እንዲሁም አንድ የብሩንዲ ክለብ የዋንጫ ተሸላሚ ሆነዋል፡፡
በዓለም አቀፉ የእግርኳስ ፌደሬሽኖች ታሪክ እና አሃዛዊ መረጃ አሰባሳቢ ማህበር (IFFHS) መሰረት ባለፉት 10 ዓመታት ምርጥ የምስራቅ አፍሪካ ክለቦች የደረጃ ዝርዝር እስከ 10ኛ እንድም ኢትዮጵያዊ ክለብ የለበትም፡፡ በደረጃ ሰንጠረዡ በዝተው የሚገኙት የኡጋንዳ፤ የኬንያ፤ የታንዛኒያና የብሩንዲ ክለቦች ናቸው፡፡ በአይኤፍኤችኤችኤስ መለኪያ መሰረት ባለፉት 10 ዓመታት ባስመዘገበው ውጤት አንደኛ ደረጃ የተሰጠው የታንዛኒያው ክለብ ሲምባ ነው፡፡ በመቀጠል ደረጃውን አከታትለው እስከ 4ኛ ደረጃ የያዙት የኡጋንዳ ክለቦች ኤስሲ ሲቪላ፤ካምፓላ ሲቲ ኬሲሲ እና ኤክስፕረስ ናቸው፡፡ የኬንያው ታስከር፤ የኡጋንዳው ዪአርኤ፤ የታንዛኒያዎቹ ያንግ አፍሪካንስና ሚትብዋ ሹገር፤ የኬንያው ማታሬ ዩናይትድ፤ የብሩንዲው ኡሊንዚ ስታርስ እና ሶኒ ሹገር እስከ 10 ያለውን ደረጃ ወስደዋል፡፡
የምስራቅ አፍሪካ ክለቦች በአንፃሩ በህጉራዊ የክለብ ውድድሮች ሻምፒዮንስ ሊግ እና ኮንፌደሬሽን ካፕ ብዙም ውጤታማ አይደሉም፡፡ የሱዳን ክለቦች አልሁላል፤ ኤልሜሪክ በቅርብ አመታት በሻምፒዮንስ ሊግ ያስመዘገቡት ስኬት ብቻ ለየት አድርጎ አውጥቷቸዋል፡፡የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን በሚያወጣው የየአምስት ዓመቱ የአህጉራዊ ክለቦች የውጤት ደረጃ በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ላይም የሱዳን ክለቦች በ33 ነጥብ 5ኛ ደረጃ ላይ ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ክለቦች በ4 ነጥብ 17ኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ፡፡ በኮንፌደሬሽን ካፕ አሁንም የሱዳን ክለቦች በ31 ነጥብ አምስተኛ ሲሆኑ፤ የኢትዮጵያ በ7 ነጥብ 17ኛ ናቸው፡፡

 ለ2008 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ለማለፍ የሚካሄደውን የብሄራዊ ሊግ ማጠቃለያ ውድድር የድሬዳዋ ከተማ እንደምታስተናግድ ተገለፀ፡፡ የብሄራዊ ሊግ ማጠቃለያ ውድድሩ ነሃሴ 17 ይጠናቀቃል የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን መግለጫ እንዳመለከተው በዋናነት በአብይ ኮሚቴ እንዲሁም ለውድድሩ በተመደቡ  24 ታዛቢዎችና አርቢትሮች እና ልዩ ልዩ አገልግሎት ሰጪዎችና  አስፈጻሚዎች በጽህፈት ቤት መመደባቸውን አስታውቋል፡፡
ውድድሩ በ2007 ዓ.ም ስራ ላይ በዋለው የብሄራዊ ሊግ ውድድር ደንብ መሰረት  እንደሚካሄድ እና ከደንቡ የወጣ የውድድር ማስፈጸሚያ ሰነድ ለእዚሁ ውድድር ሲባል ተዘጋጅቷል፡፡  የፌደሬሽኑ መግለጫ 24ቱ ተወዳዳሪ ክለቦች የምድብ እጣ ድልድላቸውን ሃምሌ 24 ቀን ካወቁ በኋላ፤ የድሬዳዋ ከተማ አስተዳዳር ቡድን የመክፈቻ የነጥብ ጨዋታውን በእጣ ከሚደለደልለት ቡድን ጋር ሀምሌ 25 በማካሄድ እንደሚጀመር አመልክቷል፡፡
በብሄራዊ ሊግ ለመወዳደር ውል የገባ ተጨዋች የውል ጊዜው የሚያበቃው የውድድሩ መርሃ ግብር ሲጠናቀቅ እንደሆነም ፌዴሬሽኑ አስገንዝቧል፡፡
የስፖርታዊ ጨዋነት ተሸላሚው ቡድን የሚለየው በቢጫና ቀይ ካርድ፣ በፖዘቲቭ ጨዋታ፣ ለተጋጣሚ ክብር በመስጠት ፣ለዳኞች ክብር በመስጠት እንዲሁም በቡድን አባላትና ደጋፊዎች ስፖርታዊ ጨዋነት መመዘኛዎች መሰረት እንደሚሆን፣ በአጠቃላይ ውድድሩ ሻምፒዮን የሚሆነው ቡድን የዋንጫ እንዲሁም የ35 ወርቅ ሜዳሊያዎች ሽልማት እንደሚሆኑ ሁለተኛና ሶስተኛ የሚወጡ ቡድኖች ደግሞ እያንዳንዳቸው የ35 ብርና የነሃስ ሜዳሊያዎች ተሸላሚ ይሆናሉ የፌደሬሽኑ መግለጫ ገልጿል፡፡ ከየምድቡ አንደኛ በመውጣት ያለፉት 8 ቡድኖች ውድድሩ ሲጀመር ዋንጫ እንደሚሸለሙ፤ በዞን ተከፋፍሎ በተካሄደው ውድድር ከፍተኛ ግብ ያስቆጠረው ተጨዋች ተሸላሚ እንሚሆንና ከፍተኛ ግብ ያስቆጠሩት ተጨዋቾች ሁለት አና ከዚያ በላይ ከሆኑ ሽልማቱን እኩል እንደሚካፈሉ እንዲሁም በ24ቱ ቡድኖች ወድድር ከፍተኛ ግብ ለሚያስቆጥረው ተጨዋችም ሽልማት እንደሚበረከት በዝርዝር አሳውቋል፡፡በ24ቱ ቡድኖች ውድድር ኮከብ ግብ አግቢ፣ ተጨዋችና አሰልጣኝ በብሄራዊ ቴክኒክ ኮሚቴ አማካኝነት ተመርጦ እንደሚሸለም በተጨማሪ ያረጋገጠው ፌደሬሽኑ፤ የጥሎ ማለፍ ውድድሮች በ90 ደቂቃ ውስጥ ካልጠተናቀቁ አሸናፊዎቹ በመለያ ምቶች እንደሚለዩ እና በ24ቱ ቡድኖች ውድድር 1ኛ አና 2ኛ የሚወጡት ቡደኖች ወደ ፕሪሚየር ሊግ እንደሚያልፉም ገልጿል፡፡ በ24ቱ ቡድኖች ውድድር በአራት ምድቦች በአጠቃላይ የሚካሄዱት ጨዋታዎች ብዛት 68 ይሆናል፣የምድብ ጨዋታዎች በዛት 60 ሲሆን በሩብ ፍጻሜ 4 በግማሽ ፍጻሜ 2 እንዲሁም የደረጃ እና የዋንጫ ጨዋታዎች ይከናወናሉ ብሏል፡፡