Administrator

Administrator

 • በፊፋ ስር ዝውውራቸውን ህጋዊ የሚያደርግ ዲፓርትመንት ተቋቁሞ መንቀሳቀስ ከጀመረ 6 ወራትተቆጥረዋል፡፡
    • በፕሪሚዬር ሊጉ ብዛታቸው ከ10 የተለያዩ አገራት 32 ተጨዋቾች ናቸው፡፡

                   
          በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የተጨዋቾች የደሞዝ መረጃ በከፊል
  ስም  ክለብ  ወርሃዊ ደሞዝ

ታደለ መንገሻ አርባ ምንጭ ከነማ 125,000.0
እንዳለ ከበደ አርባ ምንጭ ከነማ 104,166.0
ጌታነህ ከበደ ደደቢት 100,000.0
ሳሙኤል ሳኑሚ ኢትዮ.ቡና 100,000.0
አስራት መገርሳ ደደቢት 83,333.0
ተሾመ ታደለ አርባ ምንጭ ከነማ 79,166.7
አማኑኤል ጎበና አርባ ምንጭ ከነማ 79,166.0
ወንድወሰን ሚልኪያስ አርባ ምንጭ ከነማ 72,916.7
ሳምሶን ጥላሁን ደደቢት 68,205.0
አንተነህ መሳ አርባ ምንጭ ከነማ 66,666.0
አመለ ሚልኪያ አርባ ምንጭ ከነማ 66,666.0
ምንተ ስኖት አበራ አርባ ምንጭ ከነማ 66,666.0
ተመስገን ካስትሮ አርባ ምንጭ ከነማ 66,666.0
ተካልኝ ደጀኔ አርባ ምንጭ ከነማ 66,666.0
ወንድሜነህ ዘሪሁን አርባ ምንጭ ከነማ 66,666.0
ገብረ ሚካኤል ያእቆብ አርባ ምንጭ ከነማ 62,500.0
በረከት ቦጋለ አርባ ምንጭ ከነማ 62,500.0
ወርቅይታደስ አበበ አርባ ምንጭ ከነማ 62,500.0
አንድነት አዳነ አርባ ምንጭ ከነማ 62,500.0
ዳዊት ፈቃዱ ደደቢት 61,795.0
ስዩም ተስፋዬ ደደቢት 61,795.0
ዘሪሁን ታደለ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
ፍሬው ጌትነት ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
አሉላ ግርማ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
አንዳርጋቸው የላቅ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
አበባው ቡጣቆ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
መሃሪ መና ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
አይዛክ ኢሴንዴ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
አሰቻለው ታመነ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
ሳላሃዲን ባርጌቾ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
በሃይሉ አሰፋ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
ተስፋዬ አለባቸው ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
ምንተስኖት አዳነ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
ምን ያህል ተሾመ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
አዳነ ግርማ ቅዱስ ጊዮርጊስ 58,333.3
አብዱልከሪም መሃመድ ኢትዮ.ቡና 58,333.0
አይናለም ሃይሉ ደደቢት 55,385.0
አክሊሉ አየነው ደደቢት 52,780.0
ብርሃኑ ቦጋለ ደደቢት 52,178.0
ጃክሰን ፊጣ አርባ ምንጭ ከነማ 50,000.0
ሰለሞን ሃብቴ ደደቢት 42,564.0
ዘካሪያስ ቱጂ ቅዱስ ጊዮርጊስ 41,666.7
ደጉ ደበበ ቅዱስ ጊዮርጊስ 41,666.7
ናትናኤል ዘለቀ ቅዱስ ጊዮርጊስ 41,666.7
ራምኬል ሎክ ቅዱስ ጊዮርጊስ 41,666.7
ሮበርት ኦዱንግካራ ቅዱስ ጊዮርጊስ 40,000.0
ያሳር ሙገረዋ ቅዱስ ጊዮርጊስ 40,000.0
አብዱልከሪም ዞኮ ቅዱስ ጊዮርጊስ 40,000.0
ሶፎኒያስ ሰይፈ ደደቢት 38,462.0
ታገስ አበበ አርባ ምንጭ ከነማ 33,333.2
ጸጋዬ አበራ አርባ ምንጭ ከነማ 33,300.0


       የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን የፕሪሚዬር ሊግ  ክለቦች የውጭ ተጨዋቾችን ቅጥር አስመልክቶ የሚሰራ ክፍል አቋቁሞ መስራት ከጀመረ ስድስት ወራት ተቆጥረዋል፡፡ ይህ የፌደሬሽኑ ዲፓርትመንት የአይቲሲ፤ የቲኤምኤስ እና የፊፋ ቲኤምኤስ ተግባራትን የሚያከናውን ሲሆን ሃላፊው አቶ ሚካኤል እምሩ ይባላል፡፡ አቶ ሚካኤል እምሩ ለስፖርት አድማስ እንደተናገረው ዲፓርትመንቱ በፊፋ ማኔጅመንት ሲስተም ስር የሚንቀሳቀስ ነው፡፡ የውጭ ተጨዋቾች ዝውውርን ተከታትሎ ይመዘግባል፡፡ ከሌሎች አገራት ፌደሬሽኖች  ግንኙነት መፍጠር መረጃዎችን ያሳውቃል፤ ይመረምራል፤ የውጭ ተጨዋቾች ቅጥሮችን በፊፋ የማኔጅመንት ሲስተም ደንቦችና መመርያዎች መሰረትም ያረጋግጣል በመጨረሻም የሊጉ ክለቦች የሚፈፅሟቸውን ዝውውሮች የውጭ ተጨዋቾች ፓስፖርት በመስጠት ያፀድቃቸዋል፡፡
በየሊጉ ክለቦች የውጭ ተጨዋቾችን ለመቅጠር መፈለጋቸውን  በግልፅና ዝርዝር መረጃዎች ማሳወቅ ይኖርባቸዋል፡፡ የፌደሬሽኑ ዲፓርትመንት ደግሞ የውጭ ተጨዋቾቹ ከሚመጡባቸው አገራት ፌደሬሽኖች ጋር ግንኙነት በመፍጠር ህጋዊ ምዝገባ መከናወኑን ይጠይቃል። ከዚያም የሚገኘውን ምላሽ በዝውውሩ የሚያስፈልጉ የተጨዋቹ የቀድሞ ክለብ እና አዲስ ሊዛወርበት የፈለገው ክለብ የኮንትራት ውሎችና ሌሎች መረጃዎች ተገቢነትን ሙሉ ለሙሉ በመመርመር በድጋሚ ከሌላኛው አገር ፌደሬሽን በሚያደርገው ግንኙነት የሚያረጋጥ ይሆናል፡፡ በመጨረሻም በፊፋ የማኔጅመንት ሲስተም መረብ ተጨዋቹን ያስመዘግባል፡፡
በአጠቃላይ  የውጭ አገር ተጨዋቾች ለአንድ ክለብ ተገቢ ሆነው መጫወት የሚችሉት የፊፋ የዝውውር ስርዓት በሚጠብቅ አካሄድ ሆኗል፡፡
ተጨዋቹ የሚጫወትበትን ክለብ በደብዳቤ ጠይቆ   ስምምነት   ሲያገኝ፤ የሚጫወትበት ክለብ ለሀገሩ ፌዴሬሽን ስምምነቱን ሲያሳውቅ፤ ተጫዋቹ የሚጫወትበት አገር ፌዴሬሽን ዓለም አቀፍ የዝውውር መልቀቂያ ወረቀት እንዲልክለት የኢት/እግር ኳስ ፌዴሬሽንን ሲጠይቅና በዚህ ጥያቄ መሰረትም ፌዴሬሽኑ ተጨዋቹ የሚገኝበትን ሀገር ፌዴሬሽን በጽሁፍ ሲጠይቅ፤ ተጫዋቹ የሚጫወትበት አገር ፌዴሬሽን ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ዓለም አቀፍ የዝውውር መልቀቂያ ወረቀት /ITC/ በቀጥታ ሲልክ፤ ከሚጫወትበት ኢትዮጵያዊው ክለብ ጋር በዘመን የተደረገ የውል ስምምነት ለፌዴሬሽኑ ሲቀርብ ከሚመለከታቸው የመንግስት መ/ቤቶች የመኖሪያና የሥራ ፈቃድ ክለቡ አሟልቶ ሲያቀርብ የዝውውሩ ሂደት ህጋዊና በፊፋ ማኔጅመንት ሲስተም የተተገበረ ይሆናል ማለት ነው፡፡
 የፌደሬሽኑ  የአይቲሲ፤ የቲኤምኤስ እና የፊፋ ቲኤምኤስ  ሃላፊ አቶ ሚካኤል እምሩ ለስፖርት አድማስ እንደተናገሩት ዲፓርትመንታቸው መንቀሳቀስ በጀመረባቸው ባለፉት 6 ወራት 45 የውጭ ተጨዋቾች በኢትዮጵያ የፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች የዝውውር እንቅስቃሴ ተሳትፈዋል ሲሆን በተጨማሪም ዲፓርትመንቱ 4 የውጭ ተጨዋቾች ከኢትዮጵያ የለቀቁበትን ዝውውር ህጋዊነት መረጋገጡንና  በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች ህጋዊ የውጭ ተጨዋች ፓስፖርታቸውን ያገኙ የውጭ ተጨዋቾች ብዛት 32 እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡ እነዚህ ተጨዋቾች ከ10 የተለያዩ አገራት ማለትም፤ ከጋና፤ ናይጄርያ፤ አይቬሪኮስት፤ ብሩንዲ፤ ሴራሊዮን፤ ናይጄርያ፤ ኬንያ፤ ኡጋዳ፤ ቶጎና ቤኒን የመጡ ናቸው፡፡
ባለፈው የውድድር ዘመን በኢትዮጵያ እግር ኳስ የክለቦች ውድድር ከአፍሪካ 6 አገራት የተውጣጡ ከ26 በላይ የውጭ ተጨዋቾች በ7 ክለቦች ህጋዊ እውቅና  አግኝተው በመቀጠር ተጫውተዋል፡፡ ያኔ የእግር ኳስ ፌደሬሽን ለሚዲያው አሰራጭቶት በነበረው ዝርዝር መሰረት በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ሲጫወቱ የነበሩት 26 የውጭ ተጨዋቾች 8 ከካሜሮን፤ 7 ከናይጄርያ፤ 6 ከጋና፤ 3 ከኡጋንዳ እንዲሁም የተቀሩት ከኬንያ እና ከደቡብ አፍሪካ የመጡ ነበሩ፡፡ ከ26ቱ ተጨዋቾች ጊዮርጊስ 7፤ መብራት ኃይል እና ሀረር ቢራ እያንዳንዳቸው 5፤ ደደቢት 4፤ ኢትዮጵያ ቡና እና ድሬዳዋ ከነማ እያንዳንዳቸው 2 እንዲሁም ኒያላ ለ1 ተጨዋች ቅጥር ፈፅመው በፌደሬሽኑ የእውቅና ማረጋገጫ በማግኘት የውድድር ዘመኑን አሳልፈዋል፡፡
“ሜዳዎች ለስላሳና ምቹ ሳር ቢነጠፍባቸው…”
ባሪ ሊድዮም ከናይጄርያ
በሙሉ ስሙ ባሪ ሌድዮም ተብሎ ይታወቃል። የ24 ዓመቱ ናይጄሪያዊ የአጥቂ መስመር ተጫዋች ነው፡፡ የኢትዮጵያን እግር ኳስ ከተቀላቀለ ዘንድሮ 5ኛ ዓመቱን የያዘ ሲሆን፤ ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣቱ በፊት በናይጄርያ ትውልድ ከተማው ፖርት ሃርኮት በሚገኝ ክለብ በመጫወት አሳልፏል፡፡ ከዚያም በኋላ ወደ ህንድ በማቅናት በሙምባይ ኤፍ.ሲ ክለብ ለ1 ዓመት ተጫውቶ ነው ወደ ኢትዮጵያ የመጣው፡፡  የመጀመሪያ ክለቡ የሆነው በብሄራዊ ሊግ የሚወዳደረው ወልቂጤ ከነማ ሲሆን  ለ1 ዓመት ከ6 ወራት ተጫውቷል፡፡ ሁለተኛ ክለቡ በ2006 ዓመት በብሄራዊ ሊግ የነበረው የጂማ አባቡና ክለብ ሲሆን 1 ዓመት በዚያው አሳልፏል።  በሁለቱ ክለቦች በብሔራዊ ሊግ የ2 ዓመት ከ6 ወር ቆይታው የነበረውን አጠቃላይ ልምድ ባሪ ሌድዮም ለስፖርት አድማስ ሲናገር፣ የብሔራዊ ሊግ ተሳትፎ ወደ ፕሪሚዬር ሊግ ለመግባት ለሚፈልጉ ተጨዋቾች ከፍተኛ ልምድ የሚያስገኝ መሆኑን ገልፆ፤ ተወዳዳሪ ክለቦች በቂ የሚዲያ ሽፋን አለማግኘታቸውና በተሟሉ የስፖርት መሰረተ ልማቶች የሚንቀሳቀሱ ባለመሆናቸው የተጎዱ ናቸው ብሏል፡፡
ናይጄሪያዊው ባሪ በብሄራዊ ሊግ የነበረውን ቆይታ ካጠናቀቀ በኋላ ባለፈው የውድድር ዘመን በፕሪሚዬር ሊግ ተሳታፊ የሆነውን ሲዳማ ከነማን ተቀላቅሏል፡፡ በሲዳማ ከነማ ክለብ ባሳለፈው የመጀመሪያ የውድድር ዘመን ከሊጉ ጋር ለመላመድ መቻሉን ጠቅሶ፣ ዘንድሮ ከክለቡ ጋር በሊጉ ጠንካራ ብቃት ለማሳየት ተስፋ ማድረጉን ገልጿል፡፡  በሊጉ ክለቦች ናይጄሪያዊ ዜግነት ያላቸው ተጫዋቾች ብዛት እየቀነሰ መምጣቱን የገለፀው ባሪ፣ ከእሱ ሌላ ሁለት ተጫዋቾች በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እንዲሁም ሌላ ተጨዋች በቡና እንደሚገኙ አውቃለሁ ይላል፡፡ ባሪ ሊድዮም ለስፖርት አድማስ እንደገለፀው አሁን በሚጫወትበት የሲዳማ ቡና ክለብ ሁለት ኬንያውያን አንድ የሃይቲ ተጫዋቾች ይገኛሉ፡፡ ደጋፊዎች በክለቡ ለሚገኙ የውጭ ተጫዋቾች ልዩ ማበረታቻ እና ድጋፍ እንደሚያደርጉ ገልጾ፤ በየጊዜው ውጤታማ እንድንሆን መፈለጋቸው ጥሩ ሞራል እንደሚፈጥር ተናግሯል፡፡
ባሪ ሉድዮም በኢትዮጵያ እግር ኳስ ባሳለፈው ልምድ ዙሪያ ለስፖርት አድማስ አስተያየቱን ሲሰጥ በአፍሪካ ደረጃ ሁሉም ነገር ተሟልቶ እንዲገኝ መጠበቅ አያስፈልግም ብሎ በተለይ የሊግ ውድድሩ በፉክክር ደረጃው መሻሻል እየታየበት መሆኑን ገልጿል፡፡  በተለይ ግን የሊጉ ተወዳዳሪ ክለቦች ለጨዋታ የሚጠቀሙባቸው ሜዳዎች ለስላሳና፣ ምቹ ሳር ቢነጠፍባቸው በማለትም ምክሩን ለግሷል፡፡
‹‹የማልያ ቁጥር መቀያየር የለበትም››
ሱሌማን አሊ ከጋና
የ31 ዓመቱ ሱሌማን አሊ በዜግነቱ ጋናዊ ነው፡፡ ዘንድሮ በሊጉ ተወዳዳሪ በሆነው መብራት ኃይል  ክለብ በግብ ጠባቂነት በመጫወት ላይ ይገኛል፡፡ ሱሌማን ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣቱ በፊት በታዋቂ የሞዛምቢክ ክለብ ለ5 ዓመታት ተጫውቷል፡፡ ወደ ኢትዮጵያ ሲመጣ የመጀመርያ ክለቡ ደደቢት የነበረ ሲሆን ለ6 ወራት ከተጫወተ በኋላ ኢትዮጵያን ለቅቆ በመውጣት በማልዲስ ለሚገኝ ክለብ ለ6 ወራት በመጫወት በኤሽያን ካፕ የመሳተፍ እድል ነበረው፡፡ በድጋሚ ወደ ኢትዮጵያ ሲመለስ የተቀላቀለው መብራት ኃይልን ሲሆን የፈረመው ኮንትራት  ለ2 ዓመት ነው፡፡ በውድድር ዘመኑ መጀመርያ  ክለቡ የሲቲ ካፕ ዋንጫውን ማሸነፉ አስደሳች እንደሆነ የገለፀው ሱሌማን፤ በሊጉ ጠንካራ ተፎካካሪ ለመሆን የሚያነሳሳ ሲሆን  መነሻ እንደሚሆንና ከ1-5 ባለው ደረጃ ለመጨረስ ተስፋ ማድረጋቸውን ለስፖርት አድማስ አስተያየት ሰጥቷል፡፡
በኢትዮጵያ እግር ኳስ ገና የሁለት አመት ልምድ ያለው ግብ ጠባቂው ቀስ በቀስ እድገት እያሳየ የሚሄድበትን አቅጣጫዎች መታዘቡን ተናግሯል፡፡ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አንዳንድ የክለብ ተጨዋቾች የማልያ ቁጥራቸውን በየጊዜው መቀያየራቸው ልክ እንዳልሆነ ያመለከተው ሱሌማን፤ ማንኛውም ተጨዋች ውድድር ዘመኑ ሲጀመር የለበሰውን የማልያ ቁጥር ዓመቱን ሙሉ ሳይቀይር እንዲጫወት የሚያስገድድ መመርያ መኖር አለበት ብሏል፡፡ በተጨማሪም የሊጉን የፉክክር ደረጃ ለማሳደግ ጨዋታዎችን በዝርዝር በመዘገብ ሚዲያዎች ሽፋን መስጠት ይኖርባቸዋል ብሎ ይህ አሰራር ለውጭ ተጫዋቾቹ የመተዋወቅ ዕድል የሚፈጥር መሆኑን አስረድቷል፡፡
“የኢትዮጵያ ሊግ ተሻሽሏል …”  
አዳሙ አህመድ ከጋና
ጋናዊ አዳሙ አህመድ   የመሀል ተከላካይ መስመር ላይ የሚጫወት ሲሆን ላለፉት 7 ዓመታት በኢትዮጵያ የክለብ እግር ኳስ ከፍተኛ ልምድ አካብቷል፡፡ ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣቱ በፊት በጋና ፕሪሚየር ሊግ  ለ3 የተለያዩ ክለቦች የተጫወተ ሲሆን በቱርክ ክለብ ለ1 ዓመት፣ በአልቤንያ ክለብ ለ6 ወራት፣ በእስራኤል ክለብ ለ6 ወራት የተጫወተበት ልምድ ነበረው፡፡ ወደ ኢትዮጵያ ከመጣ በኋላ ደደቢትን በመቀላቀል ለ6 ዓመታት የተጫወተ ሲሆን የፕሪሚየር ሊግ የሻምፒዮናነት ክብር ከማጣጣሙም በላይ፤ በሁለት የውድድር ዘመናት በአፍሪካ ኮንፌደሬሽን ካፕ እና በአንድ የውድድር ዘመን በአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ በቅቷል፡፡
በደደቢት ክለብ የነበረውን ቆይታ ከጨረሰ በኋላ ወልዲያ ከነማን ተቀላቀለ፡፡ ባለፈው የውድድር ዘመን በሱፐር ሊግ ስኬታማ የውድድር ዘመን ያሳለፈ ሲሆን   ዘንድሮ በፕሪሚየር ሊግ ደረጃ እየተጫወተ ነው፡፡ ባለፉት 5 እና 6 ዓመታት የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ በየውድድር ዘመኑ መሻሻል እየታየበት ነው በማለት ለስፖርት አድማስ አስተያየቱን የሰጠው አዳሙ፤ በተለይ ክለቦች የፋይናንስ አቅማቸውን በማጠናከርና የስፖርት መሰረተ ልማታቸውን በማሳደግ ላይ መሆናቸው የሚበረታታ እንደሆነም ጠቅሷል፡፡
‹‹ የተጨዋቾች ማጓጓዣ አውቶብሶች ደረጃን ማሻሻል ያስፈልጋል፡፡››
 ጋብሬል አህመድ ከጋና
የ26 ዓመቱ ጋናዊ ጋብሬል አህመድ የአማካይ መስመር ተጨዋች ሲሆን በደደቢት ክለብ ለ3 ዓመታት በመጫወት አሳልፏል፡፡ ከደደቢት ክለብ ጋር 1 ጊዜ የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃ ሲሆን፤ በሁለት የውድድር ዘመናት ክለቡ በሁለተኛ ደረጃ ሊጉን ሲያጠናቅቅ አስተዋፅኦም ነበረው፡፡ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ካለው ልምድ ባሻገር በስዊድን ክለብ ለ2 ዓመታት እንዲሁም በዴንማርክ ክለብ ለ5 ወራት ለመጫወት ችሏል፡፡
ለመጀመርያ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ ሲመጣ የሚያስታውሰው አገር ትመስለው የነበረችው የአፍሪካ ህብረት መቀመጫ አዲስ አበባ ከተማ መሆኗን መገንዘቡ አስገርሞት እንደነበር የሚያታውሰው ጋብሬል፤ ከእንግሊዘኛ ተናጋሪ አገር በመምጣቱ በቋንቋ በኩል ከቡድን አጋሮቹ ጋር በቀላሉ ለመግባባት ቸግሮትም ነበር። ሌላው የውጭ ተጨዋች ፈተና የኢትዮጵያን ባህላዊ ምግቦች ከመላመድ አንፃር ነውም ብሏል፡፡
ጋብሬል አሁን በተያዘው የውድድር ዘመን የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተጨዋች ነው፡፡ ክለቡ በጣም ጥሩ አደረጃጀት እና ብቁ የአስተዳደር ሃላፊዎች ያሉበት፤ በልምምድ ሜዳ ደረጃ ያለውን መሰረተልማት ያሟላ በመሆኑ ደስተኛ ነው፡፡ የተጨዋቾች ማጓጓዣ አውቶብሶችን ደረጃ ማሻሻል እንደሚያፈልግ ግን ጠቁሟል፡፡ ክለቦች ለሌሎች የመሰረተልማቶች የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ ያህል ለተጨዋቾች ምቹ የሆኑ የትራስፖርት አገልግሎቶችን በማከናወን መስራት እንዳለባቸው ሲመክርም፤ የተጨዋቾች ማጓጓዣ አውቶብሶች በቅዱስ ጊዮርጊስ እና በደደቢት ክለቦች እንደሚታየው ደረጃቸውን የጠበቁ የስፖርት ባሶች መሆን እንዳለባቸው፤ የክለቦችን ብራንድ የሚያስተዋውቁ ስለሆኑ በዚያ አቅጣጫ ትኩረት ማድረግ ያስፈልጋል ብሏል፡፡
የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ በየዓመቱ ለውጥና መሻሻል እየታየበት ቢሆንም በሌሎች የምስራቅ አፍሪካ አገራት በኬንያ፤ በታንዛኒያ እና በሱዳን የሚታዩ እንቅስቃሴዎችን ለመስተካከል ጥረት መደረግ አለበት ብሎ ምክሩን የሚለግሰው ጋብሬል አህመድ፤ የኬንያ ሊግ በዲኤስቲቪ መተላለፉ የታንዛኒያ እና የሱዳን ሊጎች በስፖንሰርሺፕ መንቀሳቀሳቸው ጠቃሚ መሆኑን መገንዘብ ይገባል ሲል ተናግሯል፡፡ በሌላ በኩል  መገናኛ ብዙሓናት ለውጭ አገር የሊግ ውድድሮች የሚሰጡት ሽፋን ለአገር ውስጥም ማድረግ እንዳለባቸው የጠቆመው ጋብሬል፤ በየትኛውም አገር ቅድሚያ የሚሰጥበትን አሰራር በኢትዮጵያም መተግበር ይገባል ብሏል፡፡ በኢትዮጵያ የፕሪሚዬር ሊግ ደረጃ መሻሻል በአፍሪካ ደረጃ ለሚኖረው ተፎካካሪነት አስተዋፅኦ እንዳለው መታወቅ አለበት የሚለው ጋሬል አህመድ፤ የኢትዮጵያ ክለቦች በአፍሪካ ደረጃ በሚካሄዱ ውድድሮች እስከምድብ ድልድል ለመድረስ ከበቁ ከፍተኛ ስኬት ላይ መደረሱን ያረጋግጣል ብሏል፡፡
‹‹የውጭ ተጨዋቾች የሚገጥሟቸውን ፈተናዎች ተቋቁመው ማለፍ አለባቸው››
ሳሙኤል ሳኑዊ ከናይጄርያ
ናይጄርያዊው ሳሙኤል ሳኑዊ በኢትዮጵያ የክለብ እግር ኳስ የ6 ዓመታት ልምድ ያለው ሲሆን፤ በትልልቅ ክለቦች በመጫወት ከፍተኛ ልምድ ያካበተ ነው፡፡
በቤኒን ክለብ ልምድ የነበረው የ24 ዓመቱ የአጥቂ መስመር ተሰላፊ በኢትዮጵያ የመጀመርያ ክለቡ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ሲሆን ለ2 የውድድር ዘመና በዚያ ክለብ ካሳለፈ በኋላ በቀጣይ ለ1 የውድድር ዘመን በቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ በመጫወት የሲቲ ካፕ እና የፕሪሚዬር ሊግ ሁለት ዋንጫዎችን መጎናፀፍ ችሏል፡፡ ከጊዮርጊስ በኋላ ያለፉትን ሁለት የውድድድር ዘመና በደደቢት ሲጫወት ያሳለፈ ሲሆን አሁን የሚገኝበት ክለብ ኢትዮጵያ ቡና ሆኗል፡፡
በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ኮከብ ግብ አግቢነት ከፍተኛ ዝና ያለው ሳሙኤል ሳኑዊ ሊጉ በየዓመቱ በተለያያየ የፉክክር ደረጃ የሚቀያየር መሆኑን ገልፆ ከውጭ የሚመጡ ተጨዋቾች እግር ኳስ ሙያችን ነው ብለው ከተነሱ የሚገጥሟቸውን ፈተናዎች ተቋቁመው ማለፍ እና ውጤታማ ለመሆን በትጋት መስራት አለባቸው ሲል ምክሩን ለስፖርት አድማስ ሰጥቷል፡፡ በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ እያገኘ ያለው ልምድ በቀጣይ የፕሮፌሽናል የእግር ኳስ ህይወቱን የማሳደግ ህልሙን እንደሚያጠናክርለት እምነት አለኝ የሚለው ሳሙኤል ሳኑዊ፤ እቅዱ ወደ አውሮፓ ክለብ ማቅናት እንደሆነና በተለይ አርሰናልን መቀላቀል ፍላጎቱ እንደሆነ  ተናግሯል።

በኢትዮጵያ ሱዳናውያን ቁጥር 322 ሺህ 452 ደርሷል
    ወደ ኢትዮጵያ የሚሰደዱት ደቡብ ሱዳናውያን ቁጥር እየጨመረ ነው ያለው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽን፤ በየቀኑ በኣማካይ 547 ያህል ደቡብ ሱዳናውያን ድንበር አቋርጠው ጋምቤላ ውስጥ ወደሚገኘው ፓጋክ የስደተኞች ማዕከል እንደሚገቡ አስታወቀ፡፡
በኮሚሽኑ የኢትዮጵያ ቃል አቀባይ አቶ ክሱት ገብረ እግዚያብሄርን ጠቅሶ ‹‹አናዶሉ ኤጀንሲ›› ትናንት እንደዘገበው፣ ካለፈው መስከረም ወር መጀመሪያ አንስቶ 40 ሺህ የሚደርሱ ደቡብ ሱዳናውያን ስደተኞች ወደ ኢትዮጵያ የገቡ ሲሆን፣ ከእነዚህም መካከል 86 በመቶ ያህሉ ሴቶችና ህጻናት ናቸው፡፡ ከስደተኞቹ ጋር በተያያዘ ከፍተኛ ፈተና የሆነው የምግብ እጥረት እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፤ ወደ ኢትዮጵያ ከገቡት ደቡብ ሱዳናውያን ህጻናት መካከል 4 ሺህ 929 ያህሉ የምግብ እጥረት ተጠቂ መሆናቸውንም አክሎ ገልጧል፡፡
ኮሚሽኑ ከሳምንት በፊት ያወጣው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ እስካለፈው ህዳር አንድ ቀን ድረስ በጋምቤላና በአሶሳ የሚገኙ ደቡብ ሱዳናውያን ስደተኞችና ጥገኝነት ጠያቂዎች ቁጥር 322 ሺህ 452 ደርሷል፡፡

3.1 ኪሎ ግራም ክብደት ያለው ወርቅ በህገ-ወጥ መንገድ በድብቅ ወደ ህንድ ለማስገባት የሞከረች ኢትዮጵያዊት፣ ከትናንት በስቲያ በአውሮፕላን ጣቢያ የጉምሩክ ፍተሻ ሰራተኞች ተይዛ መታሰሯን “ዚኒውስ” የተባለው የአገሪቱ ድረገጽ ዘገበ፡፡
ስሟ ያልተገለጸው ይህቺው ኢትዮጵያዊት፣ ከአዲስ አበባ በመነሳት ወደ ህንድ ያደረገቺውን ረጅም የአውሮፕላን ጉዞ አጠናቅቃ፣ ኒው ደልሂ በሚገኘው ኢንድራ ጋንዲ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ ስትደርስ፣ የጉምሩክ ሰራተኞች በሻንጣዋ ላይ ባደረጉት ፍተሻ፣ በህገወጥ መንገድ ልታስገባቸው የነበሩ በድምሩ 3.1 ኪሎ ግራም የሚመዝኑ አምስት ቁራጭ ወርቆችና የወርቅ ጌጣጌጥ መያዛቸውን ዘገባው ጠቁሟል፡፡
የኒው ዴልሂ የጉምሩክ መስሪያ ቤት ጉዳዩን በተመለከተ ትናንት ያወጣውን መግለጫ በመጥቀስ፣ ግለሰቧ በድብቅ ልታስገባቸው የነበሩት ወርቆች በፖሊስ እንደተያዙና እሷም ወደ እስር ቤት እንደገባችም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡
ትናንት በዋለው የብሄራዊ ባንክ የውጭ ምንዛሬና የወርቅ ዋጋ ተመን መሰረት፣ ኢትዮጵያዊቷ በህገ ወጥ መንገድ ወደ ህንድ ልታስገባው የሞከረቺው ወርቅ 3 ሚሊዮን ብር ያህል እንደሚያወጣ ይገመታል፡፡

  ከዳያስፖራ የተላከና በሃዋላ የመጣ፣ 990 ሚ. ዶላር ተቀብያለሁ ብሏል
      የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሃምሌ እስከ መስከረም፣ 7.7 ቢሊዮን ብር አጠቃላይ ገቢ ማግኘቱንና 4 ቢሊዮን ብር ማትረፉን ለአዲስ አድማስ ገለፀ። የባንክ ሂሳብ የከፈቱ ደንበኞቹ ወደ 14 ሚሊዮን እንደሚጠጉ ባንኩ ጠቅሶ፣ በሩብ ዓመት ውስጥ ተቀማጭ ሂሳብን በ7.7 ቢሊዮን ብር በማሳደግና ወደ 296.1 ቢሊዮን ብር ማድረሱን አስታውቋል፡፡
በወጪ ንግድ ከሚያካሂዳቸው ስራዎች 210 ሚ. ዶላር እንዳስገባ በሩብ ዓመት ሪፖርቱ ጠቅሶ፤ ከዳያስፖራ በሃዋላ የመጣ 990 ሚ. ዶላር እንደሰበሰበ ገልጿል - ባንኩ፡፡ በብድርና በቦንድ ሽያጭ 17.7 ቢሊዮን ብር ለተበዳሪዎች በማቅረብ፣ 12 ቢሊዮን ብር ብድር ተመላሽ አድርጌያለሁ ብሏል። 14 አዳዲስ ቅርንጫፎችን በመክፈት፤ ጠቅላላ የቅርንጫፍ ብዛቱን 1 ሺህ 151 ማድረሱን ሲገልፅ፤ 880ሺ ደንበኞች በሞባይል የባንክ አገልግሎት እየተጠቀሙ ናቸው ብሏል፡፡  

• ፓርቲው ለተቃዋሚዎች ሁሉ ጥሪ አድርጓል፤ ውጥኑ ይሳካለት ይሆን?
• አንድ ጠንካራ ተቃዋሚ ለመፍጠር ህልውናውን ለማፍረስ ዝግጁ ነው
• ዓላማው የህዝቡን ትግል መምራት፣ህዝቡን የስልጣን ባለቤት ለማድረግ ነው
• ሁሉም ተቃዋሚ ፓርቲ በአንድ ጠረጴዛ ዙሪያ ተቀምጦ መነጋገር አለበት

ኢዴፓ ከወትሮው ለየት ያለ አቅምና ቁርጠኝነትን የሚፈታተን፣ ድፍረትም የሚጠይቅ አጀንዳ ወጥኖ ተግባራዊ ለማድረግ ተነሳሽነቱን ወስዶ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ባለፈው ሳምንት ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ አስታውቆ ነበር፡፡ አጀንዳው አገር ውስጥ ከሚንቀሳቀሱ ህጋዊ ፓርቲዎች ህብረት ወይም ቅንጅት በመፍጠር አንድ ጠንካራ ተቃዋሚ ፓርቲ ለመመስረት ያለመ ነው፡፡ ለዚህም የተቃዋሚዎችን፣ የምሁራንና፣ የህዝቡን ሰፊ ድጋፍና እገዛ ጠይቋል፡፡
ኢዴፓ ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር ተቀራርቦ ለመስራትና ለመጠናከር የራሱን ህልውና ለማፍረስ ጭምር ዝግጁ መሆኑን ጠቁሟል፡፡ አጀንዳውን ለመተግበር በተቋቋመው ኮሚቴ ውስጥ የተመረጡት የፓርቲው መስራች አባል አቶ ልደቱ አያሌው፣ ጠንካራ ፓርቲ የመፍጠር ዓላማው የህዝቡን ትግል ለመምራት ነው ይላሉ፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፤ ኢዴፓ ይዞት በመጣው አዲስ አጀንዳ ዙሪያ ከአቶ ልደቱ ጋር ሰፊ ቃለ ምልልስ አድርጓል፡፡

   ኢዴፓ በአሁኑ ወቅት አንድ ጠንካራ ፓርቲ ለመፍጠር የተነሳበት ዋና ምክንያት ምንድን ነው?
እንግዲህ እንደሚታወቀው ላለፉት በርካታ አመታት ተቃዋሚው ፓርቲ በሚፈለገው መጠን ጠንካራ አይደለም፡፡ የኛን ፓርቲ ጨምሮ ሁሉም ከኢህአዴግ ግዝፈት ጋር ሲነፃፀር፣ ከህዝቡ የለውጥ ሂደት ጋር ሲነፃፀር በጣም ደካማ ሁኔታ ውስጥ ነው ያለነው፡፡ ይሄን ድክመት በአግባቡ ገምግመን፣ ራሳችንን የማናስተካክል ከሆነ፣ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ የተቃዋሚው ጎራ ሚና ትርጉም የለሽ እየሆነ ነው የሚሄደው፡፡ የህዝቡን ትግልም አስተባብሮ መምራት አይችልም፡፡ በዚህም ኢህአዴግ ለቀጣይ 20 እና 25 ዓመታት የሚገዛበትን ሌላ እድል ነው የምንሰጠው፤ ስለዚህ ራሳችንን እናጠናክር ስንል ነው የነበረው፡፡ ነገር ግን ይሄን ጉዳይ በቅንነት የሚቀበል አልነበረም፡፡ እንደውም የተቃዋሚውን ድክመት ስናወራ፣ ብዙ ሰው ለኢህአዴግ የማሰብ አድርጎ ይመለከተው ነበር፡፡ ለምን ተቃዋሚውን ትተቻላችሁ፣ መተቸት ያለበት ገዥው ፓርቲ ነው የሚል አስተያየት ይሰነዘራል፡፡ በኛ እምነት ግን ተቃዋሚውም ካልተገመገመ፣ ካልተተቸ ሊጠናከር አይችልም፤ ደካማ ሆኖ ነው የሚቀረው --- እያልን ይህ አሁን የተፈጠረው ሁኔታ ሊመጣ እንደሚችል ቀድመን ነው መናገር የጀመርነው፡፡
ባለፉት ሁለት ዓመታት ኢትዮጵያ ውስጥ የተፈጠረውን ችግር ካየን፣ ተቃዋሚ ፓርቲ ረብ የለሽ ነው የሆነው፤ ትርጉም የለሽ ነው የሆነው፡፡ ህዝቡ ለውጥ ይፈልጋል፤ በየአካባቢው ትግል ያደርጋል፤ ነገር ግን በተደራጀ ኃይል እየተመራ አይደለም። በአካባቢ የጎበዝ አለቃ፣ በፌስቡክ ወይም ደግሞ ውጭ ባሉ የፖለቲካ ኃይሎች ነው የሚመራው፡፡ ህዝቡ ውስጥ አብረው ያሉ ኃላፊነት የሚሰማቸው ድርጅቶች ትግሉን እየመሩት አይደለም፡፡ አይደለም መምራት የወረቀት መግለጫ ከማውጣት ውጪ በህዝቡ ትግል ላይ ምንም ሚና የላቸውም፡፡ ይሄ በዚህ ከቀጠለ ወዴት ነው የምንሄደው? በአንድ በኩል ህዝቡ ለውጥ ይፈልጋል፤ በሌላ በኩል ያንን ፍላጎት በስርአት መርቶ፣ ህዝቡ ወደሚፈልገው የፖለቲካ ለውጥ የሚያደርስ ፓርቲ የለም፡፡ ኢህአዴግ እንኳ በህዝብ ትግል ቢወድቅ ስልጣን ለመረከብ ዝግጁ የሆነ የለም፡፡ ይሄ ከፍተኛ ክፍተት ነው፡፡ አንደኛ፤ ህብረተሰቡ በትግሉ ውስጥ እየገባ ህይወቱን እየሰዋ ነው፡፡ ከፍተኛ የሆነ ጉዳት እየደረሰበት ነው። እንዲህ አይነት ጉዳይ እንዳይደርስበት የተደራጀ ኃይል ያስፈልጋል፡፡ ባልተደራጀ ሁኔታ ህዝቡ የሚያደርገው ትግል ለጥቃት ነው የሚያጋልጠው፡፡ ውጤታማ አይሆንም፡፡ ኢህአዴግ ቢወድቅ እንኳን በስክነት ተወያይቶ አቅጣጫ የሚያስይዝ የተደራጀ ኃይል የለም፡፡ ይሄ አደጋ ነው፡፡
በአንድ በኩል ገዥው ፓርቲ ስልጣኑን ለማጋራትም ሆነ ስልጣኑን ዲሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ ለመልቀቅ ፍቃደኛ ባልሆነበት ሁኔታ፣ በሌላ በኩል ህዝቡ ከፍተኛ ስሜት ውስጥ  ገብቶ ባልተደራጀ መልኩ እንቅስቃሴ በሚያደርግበት ወቅት የዚህች ሀገር አጠቃላይ ህልውና አደጋ ውስጥ ነው ያለው፡፡ ስለዚህ የተቃዋሚዎች የወቅቱ ዋነኛ አጀንዳ መሆን ያለበት፣ ራሳቸውን ጠንካራ ፓርቲ አድርገው አውጥተው፣ በህዝብ ትግል ላይ ተጨባጭ የሆነ ሚና እንዲኖራቸው ማድረግ ነው፡፡ እኛ ይሄን በፊትም ስንለው የነበረው ነው፤ አሁን ደግሞ ወቅቱ የበለጠ አጀንዳ አድርገን እንድንይዘው አስገድዶናል፡፡ ይሄን ጉዳይ ግን ብቻችንን የምንይዘው አይሆንም፤ ሁሉም ተቃዋሚ መምጣት አለበት፡፡ ህብረተሰቡ ደግሞ ዝም ብሎ ማየት የለበትም፤ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ውስጥ እየገባ ካላጠናከራቸው የትም ሊደርሱ አይችሉም። ስለዚህ ይሄ አጀንዳ ያስፈለገው ምሁራኑ፣ ባለሀብቱ፣ ወጣቱ፣ ህብረተሰቡ በአጠቃላይ በፓርቲዎች ዙሪያ ተሰባስቦ እንዲታገል ነው፡፡ ፓርቲዎች ደግሞ ከእርስ በእርስ መናቆርና ግጭት ወጥተን፣ ህብረተሰቡን አስተባብሮ የሚመራ አንድ ጠንካራ ፓርቲ ለመፍጠር መታገል አለብን፡፡ ይሄ ጠንካራ ፓርቲ በመዋሃድ፣ ህብረት በመፍጠር ሊሆን ይችላል የሚመሰረተው፡፡ ይሄን ለማድረግ አንድ ተነሳሽ ፓርቲ ያስፈልጋል፤ የኛም ጥረት ይሄው ነው፡፡ በኛ በኩል ጠቅላላ ጉባኤያችንን በ6 ወር ውስጥ እናደርጋለን፡፡ ፓርቲያችንን ወትሮ ከነበረው የበለጠ እናጠነክረዋለን፤ ከዚያም መዋሃድ የሚፈልጉ ፓርቲዎች ካሉ፣ በኛ በኩል ስያሜያችንን አፍርሰን ለመዋሃድ ዝግጁ ነን፡፡ ግን ይሄን አስተሳሰብ ሁሉም ፓርቲ ይዞ መንቀሳቀስ አለበት፡፡
ከዚህ በፊት ቅንጅት፣ ህብረት፣ ግንባር የሚሉ አደረጃጀቶች ለተቃዋሚው ጎራ እንዳልበጁት   በመግለጽ ከፍተኛ ትችት ሰንዝረው ነበር። አሁን አቋምዎትን ለወጡ? ወይስ ሁለቱን የሚያስታርቁበት መንገድ አለ ?
አሁንም ቢሆን እያልን ያለነው አስፈላጊው ሆኖ ከተገኘ፣ ለፓርቲዎች መጠናከር የሚጠቅም ከሆነ ህልውናችንን አሳልፈን ለመስጠት ዝግጁ ነን፡፡ ይሄንን በተግባርም ስናደርግ ቆይተናል፡፡ ኢዴፓ የአራት ፓርቲዎች ውህድ ነው፡፡ በውህደት ስሙንም የቀየረባቸው ጊዜዎች ነበሩ፡፡ ይሄን ሁሉ ያደረግነው አብሮ ለመስራት ካለን ፍላጎት ነው። ግን አንዳንድ ጊዜ የተቃዋሚ ጎራ እንዲጠናከር በቅንነት ስንሰራ፣ አጋጣሚውን ለተለየ የቡድን ስሜት ለመጠቀም የሚፈልጉ ኃይሎች አሉ፡፡ ብዙውን ጊዜ በፓርቲ ደረጃ ተንቀሳቅሰው፣ ህዝቡ ውስጥ ገብተው ተጨባጭ ስራ መስራት ሲያቅታቸው፣ ተቃዋሚው ፓርቲ ካልተባበረ የትም መድረስ አይችልም በሚል ምንም ጥቅም በሌለው ስብስብ ውስጥ ሁሉንም እያስገቡ፣ ተቃዋሚ የሚያዳክሙበት ሁኔታ ነበር፡፡ አሁንም በኛ እምነት እስካሁን ድረስ የነበረው የተቃዋሚ ትግል መጠናከር ያልቻለው፣ እንዲህ አይነት አስተሳሰብ ያላቸው ተቃዋሚዎች ስላሉ ነው፤ ህብረት መፍጠርን ለመጠናከር ሳይሆን የግል የፖለቲካ አላማን ለማሳካት የሚጠቀሙበት ወገኖች አሉ፡፡ ይሄ ጉዳይ ለወደፊትም እንቅፋት ሆኖ ሊቀጥል ይችላል፡፡
ህብረት የምንፈጥረው፣ የምንዋሃደውና ህልውናችንን አሳልፈን እንሰጣለን የምንለው ለማይረባ ነገር አይደለም፡፡ ለቡድን ጥቅም ወይም  ራሳቸውን ወደ ስልጣን ለማውጣት ለሚፈልጉ ግለሰቦች ጥቅም አይደለም፡፡ በዚህ መልክ ለሚመጣ ጥያቄ ፍላጎቱ የለንም፡፡ ያለፈውን ስህተትና ጥፋት ለመድገም ሳይሆን የመጠናከር አስፈላጊነትን ከልብ በማመን ለሚመጣ ግን ዝግጁ ነን፡፡ ስለዚህ ይሄ ተለይቶ መታየት አለበት፡፡
ጥሪ የተላለፈው ለማን ነው? በሀገር ውስጥ ላሉት ነው? በውጭ የሚንቀሳቀሱትንስ  ይጨምራል?
በዋናነት የሚያካትተው በህጋዊ መንገድ በሰላማዊ አግባብ፣ በሀገር ውስጥ ተቀምጠው ትግል የሚያካሂዱ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ነው፡፡ እነዚህ ፓርቲዎች ጠንካራ ናቸው፣ ደካማ ናቸው የሚል ፍረጃ ውስጥ አንገባም፡፡ በኛ እምነት፣ እኛንም ጨምሮ ሁላችንም ደካሞች ነን፡፡ ያም  ነው ወደዚህ አይነቱ አጀንዳ እንድንሄድ የገፋፋን፡፡ ሀገር ውስጥ ያለ ማንኛውም ተቃዋሚ ፓርቲ በዚህ ሂደት ተሳታፊ መሆን አለበት፡፡ ለሁሉም ነው ጥሪያችን። በአንድ ጠረጴዛ ዙሪያ ተቀምጦ ሁሉም ተቃዋሚ ፓርቲ መነጋገር አለበት፡፡ በዚህ ሂደት የሚገለል አካል አይኖርም፡፡ አንዱ ትልቅ ችግር የነበረው፣ “እኔ ከእነ እገሌ ጋር አልሰበሰብም” የሚለው ነው፡፡ ይሄ ተገቢ ያልሆነ ፍረጃ ነው እንቅፋት እየሆነ ያለው፡፡ ውጭ ሀገር ያሉ የፖለቲካ ኃይሎችን በተመለከተ፣ አሁን ባለው ሁኔታ፣ በህገ ወጥ መንገድ በጠመንጃ መንግስትን ለመለወጥ ጥረት ከሚያደርጉ ጋር ልንተባበር አንችልም። ተባብረንም እዚህ ሀገር ውስጥ ህልውና ሊኖረን አይችልም፡፡ በአጠቃላይ የሀገሪቱን ችግር ከመፍታት አንፃር ግን ውጭ ያሉም ኃይሎች ሀገር ውስጥ ገብተው በህጋዊ መንገድ የሚንቀሳቀሱበት ሁኔታ መመቻቸት አለብን ብለን እናምናለን። በራሳቸው ፍላጎት ብቻ አይደለም ወደ ውጭ የሄዱት፤ ሀገር ውስጥ ባለው ሊያሰራ በማይችል ሁኔታ ተገፍተውም ነው፡፡ ተገፍተው ስለሄዱ የጠመንጃ ትግል ማድረግ አለባቸው ማለት አይደለም፡፡ አንደኛ እዚሁ ሀገር ውስጥ ተቀምጠው መታገል አለባቸው ብለን እናምናለን። ይህ ሁኔታ ቢመቻችላቸው መልካም ነው የሚል እምነት አለን። ግን እኛ አሁን የምንተባበረው ሀገር ውስጥ ካሉት ጋር ብቻ ነው፡፡ በውጭ ካሉት ጋር እንስራ ብንልም፣ አሁን ባለው ሁኔታ አደጋ ውስጥ ነው የምንገባው። ሀገር ውስጥ ከገቡና ህጋዊ ከሆኑ፣ ከነሱም ጋር የማንሰራበት ምክንያት የለም፡፡
ለመፍጠር ያሰባችሁት አንድ ጠንካራ ተቃዋሚ ፓርቲ፣ ዋነኛ አላማው ምንድን ነው?
ዋናው ኢትዮጵያ ውስጥ አንድ ጠንካራ ፓርቲ ተፈጥሮ፣ የህዝቡን ትግል መምራት አለበት። በሌላ በኩል የኢትዮጵያ የፖለቲካ ምህዳር ህዝቡን የስልጣን ባለቤት በሚያደርግ መልኩ መስተካከል አለበት፡፡ እንዲስተካከል ግን ትግል ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ገዥው ፓርቲ ባለፉት 25 ዓመታት እንዳየነው፣በሰላማዊ መንገድ ስልጣን ለህዝብ ማስረከብ የሚፈልግ መንግስት አይደለም። ይሄ መንግስት ይሄን ጥያቄ መቀበል የሚችለው፣ በጥያቄ ብቻ ሳይሆን በትግል ነው፡፡ ስለዚህ ታግለን ህብረተሰቡንም አታግለን፣ ህዝቡ የስልጣን ባለቤት የሚሆንበት ሁኔታ እንዲፈጠር ማድረግ አለብን፤ዞሮ ዞሮ አላማው የስልጣን ጥያቄ ነው። ግን ህዝቡን ነው የስልጣን ባለቤት የምናደርገው። ዋናው ህዝቡን የስልጣን ባለቤት ማድረግ ነው፤ ይሄን ለማድረግ ግን የተደራጀ እንቅስቃሴ ያስፈልጋል፡፡ ያልተደራጀ ኃይል ውጤት ቢቀዳጅም ችግር ይዞ ነው የሚመጣው፡፡
የምትፈጥሩት ፓርቲ እቅዱ አሁን ያለውን እንቅስቃሴ ለመምራት መዘጋጀት ነው?
 ትክክል! ህብረተሰቡ ለውጥ እንደሚፈልግ ባለፉት ሁለት ዓመታት ህይወቱን መስዋዕት በማድረግ ጭምር አሳይቷል፡፡ ያ የለውጥ ፍላጎትና የሚመጣው ለውጥ ግን ወደ እርስ በእርስ ግጭት የሚከተን መሆን የለበትም፡፡ አንድን መንግስት ከስልጣን ሲወርድ፣ ሀገሪቱ መንግስት የለሽ መሆን የለባትም፡፡ ዲሞክራሲያዊ መንግስት የሚተካበት ሁኔታ ነው የሚያስፈልገው፡፡ ያለ መሪ ድርጅት ትግል፣ የሚፈለገው ለውጥ አይመጣም፡፡ በኃይለ ሥላሴ ዘመን የተማሪው ትግል የተደራጀ ኃይል የሚመራው ባለመሆኑ፣ ስልጣን የወደቀው በወታደሩ እጅ ነው፡፡ አሁንም ተመሳሳይ ታሪካዊ ስህተት እንዳንሰራ ነው፡፡
በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ስር ሆኖ ይሄን እንቅስቃሴ ማድረግ አያዳግትም?
በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በግልፅ እንደተነገረው ፍቃድ ያስፈልጋል፡፡ ለአደባባይ ስብሰባ ፍቃድ ያስፈልጋል፤ ለመደበኛ የስራ ስብሰባ ፍቃድ አያስፈልገውም ነበር የተባለው፡፡ አሁን ግን በተግባር እንዳየነው፣ ጋዜጣዊ መግለጫ ለመስጠትም ፍቃድ ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ መሰረታዊ የህዝብ መብቶችም እገዳ እየተጣለባቸው ነው ማለት ነው፡፡ ይሄ ትክክል አይደለም፡፡ መታገል አለብን፡፡ ካልታገልን ይሄ አዋጅ ቋሚ አዋጅም ሊሆን ይችላል፡፡ ለችግሩ ፖለቲካዊ መፍትሄ ከመስጠት ይልቅ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ነገሮችን ማፈን ነው የተፈለገው፡፡ ስለዚህ ፊት ለፊታችን አደጋ አለ ማለት ነው፡፡ የተቃዋሚ ፓርቲዎች መጠናከርና መታገል አስፈላጊነት እዚህ ላይ ነው፡፡ የሀገር ህልውና መጠበቅ አለበት። ተቃዋሚ ፓርቲዎች ለሀገር፣ ለህዝብ የምናስብ ከሆነ፣ ከዚህ ጊዜ በላይ ጠንካራ ሆነን ለመስራት የሚጠበቅብን ጊዜ አይኖርም፡፡
ይሄን ፓርቲ የመፍጠር አጀንዳ እስከ መቼ ይሳካል ብላችሁ ነው ያቀዳችሁት?
እዚህ ላይ የጊዜ ገደብ ማስቀመጥ አያስፈልግም። እኛ በህገ ደንባችን በ6 ወር ውስጥ ጠቅላላ ጉባኤ ማድረግ አለብን፡፡ ግን የተቃዋሚዎችን ጉዳይ ወደ ላቀ ደረጃ ማድረስ የኛ ጉዳይ ብቻ አይደለም። መግለጫችን በሚዲያዎች ከወጣ በኋላ በህብረተሰቡ ዘንድ በጎ ተነሳሽነት እያየን ነው። ወቅታዊ ነው፤ ግፉበት የሚል ግፊት እያየን ነው፡፡ በሚቀጥለው ሳምንት የተከለከለውን ፍቃድ አግኝተን፣ በጉዳዩ ላይ ሰፊ ማብራሪያ ለመስጠት እየተዘጋጀን ነው። ፍቃዱን እንደምናገኝ ተነግሮናል፡፡ ጠንካራ ፓርቲ ኢትዮጵያ ውስጥ የመኖሩ ጉዳይ ለህዝብም ለተቃዋሚዎችም ለመንግስትም ይጠቅማል። ሲያጠፋ የሚጠየቅ ድርጅት ትግሉን ቢመራው መንግስትም ይጠቀማል። አለበለዚያ ግን በድንጋይ ውርወራ የሚደረግ ትግል መንግስትንም ያልሆነ ነገር ውስጥ ይከተዋል፡፡ ያ ደግሞ ለሀገርም የማይጠቅም ነው፡፡
እስከ አሁን ተቃዋሚዎችን በጉዳዩ ላይ አነጋግራችኋል?
መጀመሪያ ሃሳቡን በጋዜጣዊ መግለጫ እናሰራጨው፤ ቀጥሎ የህብረተሰቡን ሁኔታ እያየን ለህዝቡ እንቀጥላለን ብለን ነበር፡፡ ስለዚህ በቀጣይ ሳምንት ጉዳዩን ለሁሉም መገናኛ ብዙኃን ካብራራን በኋላ በሙሉ እንቅስቃሴ የምንገባበት ይሆናል፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ እንቅፋት ሊሆንብን ይችላል እንጂ ህዝባዊ ስብሰባዎችን ሁሉ እያዘጋጀን፣ በዚህ ጉዳይ ላይ ከህዝብ ጋር ለመወያየት ዝግጁ ነን፡፡ መንግስት ይሄን ለማስተናገድ ምን ያህል ፍቃደኛ ነው የሚለውን በሂደት የምናየው ነው የሚሆነው፡፡
ከ97 ምርጫ በኋላ አንዳንዶች ኢዴፓን በለዘብተኝነት፣ ሌሎች ደግሞ በ“ኢህአዴግ ጥገኛነት” ይፈርጁታል፡፡ እንዲህ ያለው አመለካከት የተአማኒነትና የተቀባይነት ችግር አይፈጥርባችሁም?  አጀንዳችሁን ለመተግበር ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ይሁንታ ማግኘት ያስፈልጋችኋልና -----
ችግር ሊፈጥር ይችላል፡፡ ይሄ ነገር ግን ተገቢ እንዳልሆነ ያለፉት ሂደቶች በደንብ የሚያሳዩ ይመስለኛል፡፡ ህብረተሰቡ እኛ ባለን መረጃ፣ የኛን ጉዳይ በደንብ ተረድቷል፡፡ 97 ምርጫ ላይ ኢዴፓ ያለውን ቅንጅት ተቀብሎ፣ ፓርላማ ቢገባና በሙሉ ኃይሉ አዲስ አበባን ተረክቦ ቢሆን ኖሮ የኢትዮጵያ ወቅታዊ ፖለቲካ አሁን ካለበት ብዙ ርቀት የተለየ ነበር የሚሆነው፡፡
ኢዴፓ ከመጀመሪያ አንስቶ ትክክለኛ አቅጣጫ ይዞ፣ ትክክለኛ ነገር ሲያመላክት እንደነበር፣ በተለያዩ ምክንቶች ግን ለአሉባልታዎች ሰለባ እንደሆነ ሰው በደንብ ገብቶታል፡፡ “አሁን ገብቶናል ተረድተናል” ይሉናል፤ ሰዎች፡፡ እርግጥ ነው አንዳንድ ተቃዋሚዎች የተባለው ዓይነት  አስተሳሰብ እንዳላቸው ይታወቃል፡፡ ግን በኛ ላይ ከፍተኛ የአሉባልታ ዘመቻ ያካሄዱ ሰዎች ዛሬ  በመድረኩ የሉም፤ ወይ ቤታቸው ተቀምጠዋል ወይ ተሰደዋል፤ ትግሉን በፅናት እየመራን ያለነው እኛው ነን፡፡ ህብረተሰቡ እስከተረዳ ድረስ ተቃዋሚዎቹም ወደዚህ አስተሳሰብ ይመጣሉ ብለን ተስፋ እናደርጋለን። ሌሎች በዚያው መቀጠል የሚፈልጉ ይኖራሉ፡፡ እነሱን እንግዲህ ምንም ማድረግ አይቻልም፡፡
የምትፈጥሩት ፓርቲ በቀጣዩ የአዲስ አበባ መስተዳድር እና የማሟያ ምርጫ ላይ ሊሳተፍ ይችላል? ምንድን ነው እቅዳችሁ?
የአስፈላጊነቱን ጉዳይ ሁሉም ፓርቲዎች ተገንዝበውት፣ ፓርቲዎቹ ብቻ ሳይሆኑ ህብረተሰቡም ተገንዝቦት፣ በፓርቲዎቹ ዙሪያ ተሰባስቦ ገንዘብ፣ ጊዜ፣ ጉልበት እያዋጣ ተሳትፎ ካደረገ፣ አንድ ዓመት ቀላል አይደለም፡፡ በአዲስ አበባ ምርጫ ከፍተኛ የሆነ ለውጥ እናመጣለን፡፡ በሰላማዊ መንገድ ለውጥ ማምጣት ይቻላል፡፡ እሱን ተጠቅመን ከሶስት ዓመት በኋላ ተቃዋሚው ኃይል ትርጉም ያለው እንዲሆን ማድረግ ይቻላል፡፡ መንግስት እንኳ መሆን ቢያቅተን በቂ የሆነ የፓርላማ መቀመጫ አሸንፈን፣ ሲቻል በ97 እንዳደረግነው አዲስ አበባን አሸንፈን፣ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ላይ የራሳችን ሚና እንዲኖረን ማድረግ እንችላለን፡፡ ይሄ እድል ከፊታችን ነው ያለው፡፡ ይሄን እድል ለመጠቀም ደግሞ አሁን ጥሩ አጋጣሚ ነው። መንግስት አሁን ሀገር በበቂ አቅም ማስተዳደር ባለመቻሉ፣ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አውጇል። ህብረተሰቡ ደግሞ ለለውጥ ተዘጋጅቷል። ይሄን እድል የመጠቀም ያለመጠቀም ጉዳይ የኛ ፋንታ ነው፡፡ ይሄ እድል ካልተጠቀምንበት አደጋ ነው፡፡ ይሄን የተፈጠረውን አደጋ፣ ወደ እድል የመቀየር ጉዳይ በኛ እጅ ነው ያለው፡፡ ስለዚህ የሚመጡትን ሁለት ምርጫዎች፣ ትርጉም ባለው መልኩ የኢትዮጵያን የፖለቲካ ሁኔታ ለመለወጥ ልንጠቀምባቸው እንችላለን፡፡

ከአንድ ጋዜጣ ያገኘነው ተረት የሚከተለውን ይመስላል፡- ተረቱ በተለያየ አገር የሚነገር ቢሆንም በዚህ መልኩ የተነገረው እኛ ጋ ነው፡፡ እንደሚያመች አድርገን አቅርበነዋል፡፡
 እነሆ፡-
ከዕለታት አንድ ቀን ጅብና ቀበሮ ቤት ፍለጋ ይሄዳሉ፡፡ ጅብ ትልቅ ቤት ሲያገኝ፣ ቀበሮዋ ብዙ ቀዳዳዎች ያሉት ትንሽ ቤት አገኘች፡፡ ቀበሮዋም፤
“አንበሳ ቢመጣብህ በየት በኩል ታመልጣለህ? እኔ በቀዳዳዎቹ ለማምለጥ እችላለሁ” ትለዋለች ለጅቡ፡፡
ጅብ ብዙም አርቆ ሳያስተውል፣
“እባክሽ እንቀያየር?” ይላታል፡፡
እሺ፤ብላው ተቀያየሩ፡፡
ሌላ ቀን ጅቡና ቀበሮዋ ምግብ እንፈልግ ተባባሉ፡፡
ጅብ፤
 “ወፍራም በሬ አግኝቻለሁ፤ አንቺስ?” አላት፡፡
ቀበሮ ያገኘችው ተባይ የሞላው አህያ ነው፡፡
“እኔ ያገኘሁት አህያ ነው፡፡ ግን ተመልከት ጮማ ነች! እንቀያር” አለችው፡፡
ተቀያየሩ፡፡
የማረጃ ቢላዋ ፍለጋ ተሰማሩ፡፡
ጅብ ቢላ አገኘ፡፡ ቀበሮ ዶሮ ላባ አገኘች፡፡
“ዶሮ ላባ በጣም ጠቃሚ መሳሪያ ነው፡፡ ቢጠፋብኝ በቀላሉ እተካዋለሁ፡፡ ያንተ ቢላ ግን ቢሰበር መተኪያ የለህም፤እንቀያየር” አለችው፡፡
ጅብ ተስማማ፡፡ ተቀያየሩ፡፡
በሬውን ለማረድ ጅቡ አልቻለም፡፡ ቀበሮ ግን ቢላውን በላባ ሸፍና በሬውን አረደችና አብረው በሉ፡፡ ቆይተው በመንገድ ላይ ማርና ቅቤ የተሸከመ ግመል አዩ፡፡ ቀበሮ፣ ግመሉን ለሚነዱት ሐማሎች፤
“ደክሞኛል፤ እባካችሁ ግመሉ ላይ ጫኑኝ” አለች፡፡ ጫኗት፡፡
ማሩንና ቅቤውን ግጥም አድርጋ በላች፡፡
 “አውርዱኝ ቤቴ ደርሻለሁ” አለች፤ጥግብ ስትል፡፡ አወረዷትና ወደ ገበያ ሄዱ፡፡ እዚያ ሲደርሱ “ጉድ!” አሉ። የተሰሩት ገባቸው፡፡ በቁጭትና በንዴት የአካባቢውን ቀበሮዎች ሁሉ ሰበሰቡና፤ “ዝለሉ!” አሉ፡፡ ያቺ ቀበሮ ቅቤና ማሩ ስለሚከብዳት እንደ ልቧ ስለማትዘል በቀላሉ ሊለይዋት ነው! እውነትም እመት ቀበሮ መዝለል አቅቷት ተያዘች። ታሰረች፡፡ “በኋላ እንገርፋታለን” ብለው ወደ ገበያው ሄዱ፡፡
 ያ ጅብ መጣና አገኛት፤  
“ለምንድነው የታሰርሺው?” ሲል ጠየቃት፡፡
“ቅቤና ማር ብይ ሲሉኝ እምቢ ብዬ!” አለችው፡፡
ጅቡም፤ ብልጥ የሆነ መስሎት፤
“በይ ቦታ እንለዋወጥ!” አላት፡፡ ፈታትና ቦታ ተለዋወጡ፡፡
ነጋዴዎቹ ሲመለሱ፣ በቀበሮዋ ቦታ ጅቡን አገኙ፡፡
“ምን ልትሰራ መጣህ?” አሉት፡፡
“ቀበሮ ቅቤና ማር ታገኛለህ ብላኝ ነው!” አላቸው፡፡
ቀበሮ ዛፍ ላይ ሆና፣
“ዐይኑን አትግረፉት! ጆሮውን አትንኩት! ሌላ ቦታ ላይ ግን ግረፉት” ትላለች፡፡
ሰዎቹ እንዳይሞት እንዳይድን አድርገው ገረፉት፡፡ ቆዳው ተልጦ ሥጋው ይታይ ጀመር፡፡ ከዚያ ጥለውት ሄዱ፡፡
ጅቡ ወደ ቤቱ ሄደ፡፡ ቤት ሲደርስ ልጆቹ ሲያዩት፤
“አባታችን ስጋ ይዞልን መጣ” ብለው ራሱን ተቀራመቱት!
*       *     *
ከላይኛው ተረት የቤትን ችግር ማስተዋል አያዳግተንም፡፡ ነገ ጠላት ቢያጋጥም ለማምለጥ ማስተዋል እንዳለብን ልብ እንላለን፡፡ ቦታ በመቀያየር ዙሪያ ብዙ ጅልነት እንደሚኖር እናጤናለን፡፡ ምግባችንን መለዋወጥም የራሱ ጣጣ እንዳለው እንገነዘባለን፡፡ ማረጃችን ቢላ ወይስ ዶሮ - ላባ? የሚለውንም እናሰምርበታለን፡፡ ቢላ በላባ ሸፍነው ማረድ ግን ማኬቬሊያዊ አካሄድ ነው! የማርና ቅቤ ተሸካሚ ግመል፣ ግመሉንም የሚነዱ ነጋዴዎች ብዙ ናቸው፡፡ ግመሉ ላይ የሚጫኑ ብልጣ - ብልጦች ግን አያሌ ናቸው፡፡ ያም ሳይበቃቸው እንደ ጅቡ ሁሉ ለብዙዎች መታሰር ምክንያት የሚሆኑ አያሌ ናቸው! በልተው፣ መብላታቸው ተነቅቶባቸውም በአፋቸው ሌሎችን አስቀፍድደው፤ ዛፍ ጫፍ ላይ ሆነው የሚያላግጡ በርካቶች ናቸው! ለማን አቤት ይባላል?! ጅልነት በራስ ወገን እስከ መበላት ያደርሳል! “አብዮት ልጇን ትበላለች!” ይሉ ነበር የዱሮ ገዢዎቻችን፡፡
ሎሬት ፀጋዬ እንዳለው፤
“አንዲት የዱር አውሬ፣ በአንዳንድ የመከራዋ ሰሞን
ልጇን ትበላለች አሉ፣ ምጥ የጠናባት እንደሆን!
ዕውነቱ ሁሌም አይቀሬ ነው፡፡ ዩኒቨርሳል እንደሆነው ሁሉ “የቤት - ጣጣም” አለበት፡፡ ዲበ - ኩሉ ይሰውረን እንጂ በሹም - ሽር የምንገላገለውስ አይደለም! “ጉልቻ ቢቀያየር ወጥ አያጣፍጥም” የሚለው ተረት ዱሮ ይሰራ ነበር፡፡  
አሁን ግን፤
‹‹የጣፈጠ ወጥ በጉልቻ መቀያየር የሚበላሽበት ዘመን መጣ›› በሚለው መተካት ሳያሻው አይቀርም፡፡ ሁሉን ነገር በሙከራ ብቻ አንዘልቀውም፡፡ ከወገናዊነት ነፃ እንሁን፡፡ ከልባችን ወደፊት እንጓዝ!!
አገሪቱ ከቤተ ሙከራነት መውጣት አለባት፡፡ በመካከለኛው የቢሮክራሲ ማዕድ የሚነሳውን ቢሮክራሲያዊ ሙስና አባዜ መላቀቅ ያሻል! ግምገማ ዕውነተኛ መሆኑ መፈተሽ አለበት፡፡ ባጠፉ አመራሮች ላይ እርምጃ እንወስዳለን ሲባል፣ ሁለት ነገሮች ግንዛቤ ውስጥ መግባት አለባቸው፡፡ አንደኛው ገምጋሚዎቹ ምን ያህል ንፁሀን ናቸው? ሁለተኛ የሚወሰደው እርምጃ ምን ያህል ሥር ነቀል ነው? ለእነዚህ ጥያቄዎች አዎንታዊ ምላሽ ማግኘት ወሳኝ መሆኑን አንዘንጋ! ከዚህ ሁሉ በኋላ ደግሞ በቦታቸው የሚተካውስ ማነው? አስተማማኝ ነውን? ብሎ መጠየቅም ያባት ነው! ዞሮ ዞሮ ከሥርዓቱ መመሪያ ውጪ አዲስ ነገር የለም! ጆርጅ ፍሪድማን፤ ‹‹ቀጣዮቹ መቶ ዓመታት›› (The next 100 years ) በሚለው መጽሐፉ፤
‹‹ኦባማ የቡሽን የውጪ ጉዳይ ፖሊሲ አራማጅ ነው፡፡ ቡሽ በኢራቅ ላይ ያወጣው መመሪያ እንዳለ አለ። ከአውሮፓውያን በተለይም ከጀርመን ያለው ግንኙነት ያው ነው፡፡ ከኢራንና ከኩባ ጋር ለመግባባት የሞከረው ውጤቱ ፍሬ ቢስ ነበር፡፡ ከሩሲያ ጋር ያለውም ዝምድና የቡሽ እንደነበረው ነው፡፡ ከጆርጂያ፣ ከዩክሬን.. ከፖላንድም ያለውን ዝምድና ማዝለቅ ነው፡፡ ኦባማ ለፕሬዚዳንትነት በመወዳደርና ፕሬዚዳንት በመሆን መካከል ያለውን ልዩነት ጥርት አድርጎ ያውቃል፡፡ እንደ ተመራጭ ብዙ ነገር ትናገራለህ፡፡ እንደ መሪ ግን ከነባራዊው ዕውነታ ጋር ትጋፈጣለህ። እንደ ቼዝ ተጫዋች የምትሄድበት አቅጣጫ ይጠፋሃል፡፡ መሪነት የዋዛ ነገር አይደለም፡፡”
ዶናልድ ትራምፕም ከመመሪያው ውጪ እንዳይደለ ከላይ ካነሳነው ሁኔታ መገንዘብ አያዳግተንም፡፡ የሀገራችንን አመራሮችም ሆነ የመካከለኛ ቢሮክራሲ ሹማምንት በዚህ ረገድ መገምገም አዳጋች አይደለም፡፡
እንደ ፀሀፊው አሪፍ አገላለፅ፤
‹‹United States is a bizarre mixture of overconfidence and insecurity›› (አሜሪካ ከመጠን ያለፈ ልበሙሉነትና ደህነነቷን የማጣት ሥጋት ቅልቅል የሆነች አገር ናት እንደ ማለት ነው) ይላታል፡፡ እኛስ ብንሆን? ብሎ መጠየቅ አስማታዊነትን አይጠይቅም፡፡ የትኛውም መሪ፣ መካከለኛ መሪ፤ ወይም ታህታይ መሪ፤ በፓይለቶች ቋንቋ፡-
‹‹Soft-Landing›› በሰላም መሬት መድረስ ካጋጠመው ዕድለኛ ወይም የበቃ ሰው ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ አያጋጥምም፡፡ እጅግ ወደ ፅርሃ-አርያም ለወጣ ምድር ሩቅ ናት፡፡ ስለዚህ አዕምሮውን ማዘጋጀት አለበት - ለመውረድ። አለበለዚያ ዐረቦች፤
‹‹ንጉሥ ሆኖ ሳይከሳ የሚሰናበት የለም!” የሚሉትን ተረትና ምሣሌ ልብ እንድንል እንገደዳለን!

Saturday, 12 November 2016 13:49

ከትራምፕ ድል ማግስት...

 - በቅስቀሳቸው ወቅት አደርገዋለሁ ያሉትን ሁሉ ያደርጉት ይሆን?...
         - ከነጩ ቤት ወደ በፊት ፍርድ ቤት ያመራሉ
         - አይሲስ እና አልቃይዳ በትራምፕ ድል ፈንድቀዋል
      በስተመጨረሻም...
አወዛጋቢው ሰውዬ ሰተት ብለው ወደ ነጩ ቤት መግባታቸውን አረጋገጡ፡፡
ዓለም የሰማችውን ለማመን ተቸገረች። ባልተጠበቀ መንገድ የተቋጨው የዘንድሮው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ፣ የአለማችን መነጋገሪያ ትኩስ ትንግርት ሆነ፡፡
የምርጫ ውጤቱ ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ የተለያዩ አለማቀፍ መገናኛ ብዙሃን ካወጧቸው ዘገባዎች የተወሰኑትን ጨለፍ አድርገን እንመልከት።
እንኳን ደስ አለዎት!...
የትራምፕ አሸናፊነት ከተሰማ በኋላ ፣ ፈጥነው የእንኳን ደስ አለዎት መልዕክት ከላኩት የዓለማችን መሪዎች አንዱ፣ “የትራምፕ ደጋፊ ነው” እየተባሉ በዲሞክራቶች ሲብጠለጠሉ የከረሙት የሩስያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ናቸው፡፡ ፑቲን ከክሪምሊን ባስተላለፉት መልዕክት፤ ተኳርፈው የነበሩት ሩስያና አሜሪካ የሚታረቁበት ጊዜ እንደመጣ ተስፋ አለኝ ብለዋል፡፡ ቻይናም በበኩሏ፣ በምርጫ ቅስቀሳቸው በክፉ ሲያነሱ ሲጥሏት የከረሙትን ትራምፕን “ስለተመረጡ ደስ ብሎኛል፤ የሁለትዮሽ ግንኙነታችንን ለማሳደግ ከአዲሱ የአሜሪካ መንግስት ጋር ለመስራት ፍቃደኛ ነኝ” ብላለች፤ በውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯ በኩል፡፡
የእንግሊዟ ቴሬሳ ሜይ፣ የአፍጋኒስታኑ አሽረፍ ጋና፣ የግብጹ አብዱል ፈታህ አል ሲሲ፣ የህንዱ ናሬንድራ ሞዲ፣ የኬንያው ኡሁሩ ኬንያታ፣ የደቡብ አፍሪካው ጃኮብ ዙማ እና የፍልስጤሙ መሃሙድ አባስ ለትራምፕ የእንኳን ደስ አለዎት መልዕክታቸውን ካስተላለፉ በርካታ የዓለም አገራት መሪዎች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡
የአውሮፓ ህብረት ከፍተኛ ባለስልጣናት በበኩላቸው ለትራምፕ በጻፉት ደብዳቤ፣ የእንኳን ደስ አለዎት መልዕክታቸውን ገልጸው፣ “በቻሉት ፍጥነት ሁሉ ዛሬ ነገ ሳይሉ ወደ አውሮፓ ይምጡና አስቸኳይ ስብሰባ እናድርግ” ሲሉ ጠይቀዋል፡፡
ያሉትን ሁሉ ያደርጉታል?...
አወዛጋቢው ዶናልድ ትራምፕ በምርጫው አሸንፈው መንበረ ስልጣኑን መረከባቸው፣ በአሜሪካና በተቀረው አለም ላይ ምን አይነት ለውጥ ያመጣ ይሆን? የሚለው ጥያቄ ብዙዎችን እያነጋገረ ያለ ጉዳይ ነው፡፡ ሰውዬው ስልጣን ብይዝ አደርጋቸዋለሁ በሚል በምርጫ ቅስቀሳቸው ወቅት የተናገሯቸውን አስገራሚና አስደንጋጭ ጉዳዮች፣ በእርግጥ ስልጣን ላይ ሲወጡ ይተገብሯቸው ይሆን? ከተገበሯቸውስ ምን አይነት ለውጥ ይመጣ ይሆን? ብለው በጉጉት የሚጠይቁ በርክተዋል፡፡
ብዙዎች ይህን ጥያቄ ለመመለስ የየራሳቸውን አስተያየት እየሰጡ ሲሆን ቢቢሲም የትራምፕ ፕሬዝደንት መሆን አገሪቱ ከተቀረው አለም ጋር ባላት ግንኙነት ላይ ይፈጥራቸዋል ያላቸውን ቁልፍ ለውጦች ዘርዝሯል፡፡
ትራምፕ በያዙት የንግድ ፖሊሲ የሚገፉበት ከሆነ፣ አሜሪካ ከተቀረው አለም ጋር ባላት የንግድ ግንኙነት ላይ ከፍተኛ ለውጥ መምጣቱ አይቀሬ ነው ይላል ቢቢሲ፡፡ ለስራ አጥነት ምክንያት ሆነዋል ያሏቸውንና አገሪቱ ከሌሎች አገራት ጋር የገባቻቸውን ነባር የነጻ የንግድ ስምምነቶች ሊያፈርሱ፤ ከአለም የንግድ ድርጅት አባልነቷ እንድትወጣ አደርጋለሁ ያሉትን እቅዳቸውንም ተግባራዊ ካደረጉ እጅግ ትልቅ ለውጥ ይፈጠራል ይላል፡፡
አሜሪካ አምና ከ195 የአለማችን አገራት ጋር የተፈራረመቺውን የፓሪሱ የአየር ንብረት ለውጥ ስምምነት እንደሚያፈርሱና ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሙቀት መጠን መጨመር ፕሮግራሞች የምትሰጠውን ገንዘብ እንደሚያቋርጡ መናገራቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ እንዳሉት የሚያደርጉ ከሆነ ሌላ ለውጥ ሊታይ ይችላል ብሏል።
አገሪቱን ከሜክሲኮ የሚያካልል የግንብ አጥር የመገንባት፣ ከኔቶ ጋር ያለመቀጠልና ከሩስያ ጋር የነበረውን የተካረረ ግንኙነት የማለዘብ እቅዶቻቸውም፣ የመተግበር ዕጣቸው እውን ከሆነ ተጽዕኗቸው እጅግ የጎላ ይሆናል ይላል፤ ቢቢሲ። ኒውዮርክ ፖስት ግን፣ ትራምፕ በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ቃል የገቧቸውን ጉዳዮች በእርግጥም ስልጣን ላይ ሲወጡ ተግባራዊ ስለማድረጋቸው ይጠራጠራል፡፡ ዘገባው እንደሚለው፤ ትራምፕ በተለይ ዋና ዋናዎቹን ቃል የገቧቸው ጉዳዮች ተግባራዊ ለማድረግ፣ የኮንግረሱን ድጋፍና ይሁንታ ማግኘት ግድ ይላቸዋል፡፡ እርግጥ ሪፐብሊካኖች በሁለቱም ምክር ቤቶች አብላጫ ድምጽ ያላቸው መሆኑ፣ ጉዳዩን ያን ያህል ፈታኝ ላያደርገው ይችላል።
ይሄም ሆኖ ግን፣ ትራምፕ የተወሰኑ ለውጦችን የማድረግ ስልጣንና አቅም ባያጡም፣ በምርጫ ቅስቀሳቸው ወቅት ቃል የገቡትን የወፈፌ ሃሳብ የሚመስል ዕቅድ ሁሉ፣ መንበረ ስልጣኑን ስለተቆናጠጡና የእሳቸው ሃሳብ ስለሆነ ብቻ ያለ ከልካይ ተግባራዊ ያደርጉታል ብላችሁ አትስጉ ያለው ደግሞ ዋሽንግተን ፖስት ነው፡፡
እዚያም ምርጫን ተከትሎ አመጽ...
አሁን...
የምርጫ ውጤት ይፋ መደረግን ተከትሎ የሚመጣ አመጽና ተቃውሞ የእነ አፍሪካ መገለጫ ብቻ አይደለም! ልዕለ ሃያል አሜሪካም፣ የምርጫ ውጤትን በጸጋ ከመቀበል ወደ አመጽና ተቃውሞ ወርዳለች፡፡ ትራምፕ ማሸነፋቸው ከታወቀ በኋላ በካሊፎርኒያ በመቶዎች የሚቆጠሩ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች አደባባይ ወጥተው ተቃውሟቸውን ማሰማታቸውን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡ በምርጫው ውጤት ያልተደሰቱት ከ500 በላይ የሚሆኑ ተማሪዎች ረቡዕ ማለዳ አደባባይ በመውጣት ጸረ- ትራምፕ መፈክሮችን ማሰማታቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ በበርክሌይ፣ ኤርቪንና ሳንጆሴ አካባቢዎችም ተመሳሳይ አነስ ያሉ ተቃውሞዎች መደረጋቸውን ገልጧል፡፡ የትራምፕን አሸናፊነት አምነው ለመቀበል ያልፈለጉ በሺህዎች የሚቆጠሩ አሜሪካውያን፣ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች አደባባይ ወጥተው ተቃውሟቸውን ማሰማታቸውን ቀጥለዋል፡፡ በርካታ አሜሪካውያን ማንሃታን ውስጥ ወደሚገኘው ግዙፉ የትራምፕ ህንጻ በማምራት ሰውዬው በስደተኞችና በሙስሊሞች ላይ የያዙትን አቋም በመንቀፍ፣ ለመሪነት አይበቁም ሲሉ ተቃውመዋል፡፡ በኦክላንድም 6 ሺህ ያህል የትራምፕ ተቃዋሚዎች አደባባይ ወጥተው የትራምፕን ፎቶግራፍ አቃጥለዋል፣  የመደብሮችን መስኮቶች ሰባብረዋል፡፡ ወደ ትራምፕ ኢንተርናሽናል ሆቴል ሲያመሩ የነበሩ 1 ሺህ 800 ተቃዋሚዎችም በፖሊስ እገዳ ተመልሰዋል፡፡
ትራምፕ ፕሬዝዳንታችን አይደለም የሚል መፈክር ያነገበው ተቃውሞው፤ ወደ ሎሳንጀለስ፣ ፖርትላንድ፣ ዋሽንግተን ዲሲ፣ ፊላዴልፊያ፣ ቦስተን፣ ሲያትል፣ ሳን ፍራንሲስኮና ሌሎች የአሜሪካ አካባቢዎች መዛመቱን ቢቢሲ የዘገበ ሲሆን፣ ዘረኝነትን የሚያወግዙ 200 ያህል እንግሊዛውያንም ለንደን በሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ደጃፍ ባደረጉት ተቃውሞ ትራምፕን አውግዘዋል ብሏል - ዘ ኢንዲፔደንት፡፡
አይሲስና አልቃይዳ በደስታ ፈንጥዘዋል
“ላሸንፍ እንጂ ሙስሊሞች የአገሬን ምድር አይረግጡም!...” የሚለው የትራምፕ ንግግር ብዙዎችን አስደንግጦ ነበር፡፡ ይህ ንግግር ብዙዎችን ቢያስደነግጥና ቢያስከፋም፣ አይሲስን ለመሳሰሉ ጽንፈኛ ቡድኖች የተለየ ትርጉም ነበረው። የሰውዬው ንግግር በሙስሊሞች ላይ ቁጣን የሚቀሰቅስ ከመሆኑ በተጨማሪ፣ ለእነዚህ ቡድኖች አዳዲስ አባላትን መመልመያ ፕሮፓንዳ ሆኖላቸው ነበር። የአይሲስ እና የአልቃይዳ አጋሮች የሆኑ አክራሪ ቡድኖች ባለፈው ረቡዕ የዶናልድ ትራምፕን ማሸነፍ ሲሰሙ፣ እንደ አንድ የሪፐብሊካን ደጋፊ በደስታ ነበር የፈነጠዙት፡፡
ዋሽንግተን ፖስት እንደ ዘገበው፤ ከአይሲስ ጋር ግንኙነት ያለው አል ሚንባር ጂሃዲ የተባለ ሚዲያ፣ “በፈጣሪ ድጋፍ አሜሪካን በገዛ እጃቸው የሚያጠፏት ሰው በፕሬዚዳንትነት ተመረጡ!... የእሳቸው መመረጥ ሙስሊሙ በአሜሪካ ላይ ጥላቻ እንዲኖረው ያደርጋል” ብሏል፡፡ የአይሲስ ጂሃዲስት ታጣቂዎች፣ “አህያው ትራምፕ መመረጡ የአሜሪካ ውድቀት ምልክት ነውና በማሸነፉ ደስተኛ ነን” ሲሉ መናገራቸውንም ዘ ዴይሊ ሚረር ዘግቧል፡፡
ዘ ሰን በበኩሉ፤ አሸባሪው ቡድን አል ቃይዳም የትራምፕ ማሸነፍ ለአሜሪካ ጥፋት በር የሚከፍት በመሆኑ እንዳስደሰተው መግለጹን በመጠቆም፣ ቡድኑ በምርጫው ሰሞን በአሜሪካ የሽብር ጥቃት ለመፈጸም አቅዶ እንደነበር ደርሼበታለሁ ሲል ኤፍቢአይ አስታውቆ እንደነበርም ዘግቧል፡፡
ሄላሪን በሚሼል?
በርካታ አሜሪካውያን ለሄላሪ ክሊንተን ድምጻቸውን በመስጠት በአገሪቱ ታሪክ የመጀመሪያዋን ሴት ፕሬዚዳንት ወደ ስልጣን ለማምጣት ቋምጠው ነበር ይላል፤ ዘ ዴይሊ ቴሌግራፍ፡፡ ያልተጠበቀው የምርጫ ውጤት ግን፣ ለሄላሪ የታጨውን መንበር ለትራምፕ አሳልፎ በመስጠት ህልማቸውን አጨናገፈው፡፡
በዚህ ዱብ እዳ የተናደዱት ሴት መሪ ናፋቂ አሜሪካውያን፣ ዘንድሮ በሄላሪ ያጡትን ስኬት ከአራት አመታት በኋላ በሚሼል ኦባማ ከእጃቸው ለማስገባት አቅደዋል ተብሏል፡፡አንደበተ ርዕቱዋ ቀዳማዊት እመቤት ሚሼል ኦባማ፣ ከአራት አመታት በኋላ በሚካሄደው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ዲሞክራትን ወክለው ቢወዳደሩ ለድል ሊበቁ እንደሚችሉ አስተያየታቸውን የሚሰጡ አሜሪካውያን በርካታ መሆናቸውን ዘገባው ይጠቁማል፡፡
እነዚህ በሄላሪ በለስ ያልቀናቸው ሴት መሪ ናፋቂ አሜሪካውያን፣ ዛሬ ነገ ሳይሉ በትዊተር ድረገጽ ሚሼል2020 የሚል የድጋፍ ዘመቻ መጀመራቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ ዘመቻውን የሚቀላቀሉ ዜጎች ቁጥር በአጭር ጊዜ ውስጥ በከፍተኛ ሁኔታ ማደጉንም አስረድቷል፡፡
የዝነኞች ኩርፊያ
የዘንድሮው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ሂደት፣ ዝነኞች ከወትሮው በተለየ ፖለቲካዊ አቋማቸውን በአደባባይ ያንጸባረቁበት ነበር፡፡ ታላላቅ ድምጻውያን፣ የፊልም ተዋንያን፣ ደራሲያንና የመዝናኛው ኢንዱስትሪ ከዋክብት፣ የሚደግፉትን ዕጩ ተወዳዳሪ ማንነት በይፋ ከመናገር አልፈው፣ አድናቂዎቻቸውም እነሱ ለሚደግፉት ዕጩ ድምጻቸውንእንዲሰጡ በይፋ ቅስቀሳ ሲያደርጉ ቆይተዋል፡፡
ተሸናፊዋ ሄላሪም፣ ወደ ዋይት ሃውስ የሚገቡበትን ጎዳና ይጠርጉልኛል በሚል ቢዮንሴና ጄይዚን ጨምሮ በርካታ ታዋቂ ድምጻውያንን ከጎናቸው አሰልፈው የምረጡኝ ቅስቀሳቸውን ሲያጧጡፉት ከርመው ነበር - አልሆነም እንጂ፡፡
የምርጫ ውጤቱ ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ ምድረ ዝነኛ በድንጋጤ ክው ማለቱን ዘ ቴሌግራፍ ዘግቧል፡፡
“አሜሪካ ሆይ... ተግተሽ ጸልይ!...” ብላለች፤ የሰማችው ነገር ከአቅሟ በላይ የሆነባት ሌዲ ጋጋ፡፡
ከቀናት በፊት ሄላሪን አቅፋ የምርጫ ቅስቀሳ መድረክ ላይ ስትፈካ የታየቺው ድምጻዊት ኬቲ ፔሪ ግን፣ ከጸሎት ይልቅ አብዮት ያዋጣል ባይ ናት። “አብዮት ሊፈነዳ ነው!...” ብላለች፤ ድምጻዊቷ የሄላሪን መሸነፍ ከሰማች በኋላ በትዊተር ገጽ ላይ ባሰፈረቺው ጽሁፍ፡፡“ምንድን ነው እየሆነ ያለው?...” በማለት ግራ መጋባቱን የገለጸው ታዋቂው ራፐር ስኑፕ ዶግ ሲሆን፣ ክሪስ ኢቫንስ በበኩሉ፤ “አሳፋሪ  ነው፤ በጥላቻ የተሞላ ሰው ታላቂቷን አገር ይመራ ዘንድ ፈቅደንለታል!...” በማለት በምርጫው ውጤት መበሳጨቱን ጠቁሟል፡፡
ከትራምፕ ያልተናነሰ የፈነደቀው እንግሊዛዊ
የዘንድሮው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ፣ እጅግ ከፍተኛውን ደስታ ያጎናጸፈው ለአሸናፊው ትራምፕ እንደሆነ አያጠራጥርም፡፡ አንድ እንግሊዛዊ ግን ከትራምፕ ያልተናነሰ በደስታ ፈንድቋል፡፡ ዘ ኢንዲፔንደንት እንደዘገበው፣ ነዋሪነቱ በለንደን የሆነውና ስሙ ያልተጠቀሰው እንግሊዛዊ፣ የምርጫውን ውጤት ከትራምፕ ባልተናነሰ እጅግ በከፍተኛ ጉጉትና ጭንቀት ሲጠባበቅ ነበር፡፡ ሰውዬው የምርጫ ውጤቱን በጉጉትና በጭንቀት የጠበቀው፣ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት በእሱ ህይወት ላይ ያን ያህል ተፅዕኖ የሚፈጥር ስለሆነ አልነበረም፡፡
በምርጫው የሚያሸንፈው ሰው ካሸነፈ በኋላ የሚፈጥረው ነገር ሳይሆን፣ ማሸነፉ በራሱ ነበር እንግሊዛዊውን ያጓጓውም ያስጨነቀውም፡፡ እየጓጓና እየተጨነቀ የምርጫውን ውጤት ሲጠብቅ አመሸ፡፡ በስተመጨረሻም የትራምፕን ድል ሰማና፣ በደስታ ፈነጠዘ፡፡
ትራምፕ ያሸንፋል ብሎ ባስያዘው የቁማር ጨዋታ፣ 200 ሺህ የእንግሊዝ ፓውንድ በላ!
ከነጩ ቤት በፊት፣ ፍርድ ቤት
ሮይተርስ ደግሞ፣ ዘግየት ብሎ አጉል ዘገባ አመጣ...
የታላቂቷ አሜሪካ ቀጣዩ ታላቅ መሪ ዶናልድ ትራምፕ፣ ወደ ነጩ ቤት ከማምራታቸው በፊት ወደ ፍርድ ቤት ማምራታቸው አይቀርም ይላል፤ ሮይተርስ። ዘገባው እንዳለው፣ ዶናልድ ትራምፕ አገልግሎቱን ባቆመው የቀድሞው ትራምፕ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች የተመሰረተባቸውን ክስ ለመከታተል፣ ካሊፎርኒያ ውስጥ ወደሚገኝ የፌዴራል ፍርድ ቤት በሳምንታት ጊዜ ውስጥ ያመራሉ፡፡
ምንም እንኳን የአገሪቱ ህግ ፕሬዚዳንቶች ከስራቸው ጋር በተያያዘ ክስ እንዳይመሰረትባቸው ጥበቃ የሚያደርግላቸው ቢሆንም፣ ከስልጣን በፊት በሰሯቸው ጥፋቶች ሊከሰሱ እንደሚችሉ ይደነግጋል ብሏል ዘገባው፡፡
ትራምፕ ከተለያዩ የንግድ ኩባንያዎቻቸው ጋር በተያያዘ ከዚህ በፊት የተመሰረቱባቸውና ያልተዘጉ ሌሎች የፍርድ ቤት ክሶች እንዳሉባቸው የዘገበው ዩኤስ ቱዴይ በበኩሉ፣ ዶናልድ ትራምፕና የሚያስተዳድሯቸው ኩባንያዎች ባለፉት 30 አመታት ከ4ሺህ በላይ ክሶች እንደተመሰረቱባቸው አስታውሷል፡፡

የተጠቃሚዎቹ ቁጥር 1.79 ቢ. ደርሷል
     ታዋቂው የማህበራዊ ድረገጽ ፌስቡክ ባለፈው መስከረም በተጠናቀቀው የዘንድሮው ሶስተኛ ሩብ አመት 2.4 ቢሊዮን ዶላር ማትረፉንና 7.01 ቢሊዮን ዶላር አጠቃላይ ገቢ ማግኘቱን ባለፈው ሳምንት አስታወቀ፡፡
ፌስቡክ የሩብ አመት ትርፉ ካለፈው አመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ166 በመቶ እድገት በማሳየት 2.4 ቢሊዮን ዶላር መድረሱን እንዳስታወቀ የዘገበው ስካይ ኒውስ፤ትርፋማ እንዲሆን ከፍተኛውን አስተዋጽኦ ያበረከተው ከሞባይል አገልግሎት ማስታወቂያ ያገኘው ገቢ መሆኑንም ጠቁሟል፡፡የፌስቡክ ተጠቃሚዎች ቁጥር 1.79 ቢሊዮን መድረሱን ያስታወቀው ኩባንያው፤ በሞባይል ብቻ ፌስቡክ የሚጠቀሙ ደምበኞቹ ቁጥርም 1.66 ሚሊዮን መድረሱን አመልክቷል፡፡
ኩባንያው በቀጣዩ አመት ኢንቨስትመንቱን በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚያስፋፋ ማስታወቁንዘገባው ጠቅሶ፣ ከእነዚህ ኢንቨስትመንቶች መካከልም በድሮኖች አማካይነት ለገጠር አካባቢዎች የኢንተርኔት አገልግሎት ማዳረስ አንዱ እንደሆነ መጠቆሙን አስረድቷል፡፡

በዩክሬን የሚገኝ አንድ የኤሌክትሮኒክስ ኩባንያ መጠሪያ ስማቸውን አይፎን 7 ብለው ላስቀየሩ የመጀመሪያዎቹ አምስት ደምበኞቹ አዲሱን ስማርት ፎን፣አይፎን 7 እንደሚሸልም ባወጣው ማስታወቂያ መሰረት፣ የመጀመሪያው ወጣት ስሙን በይፋ ማስቀየሩን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
የ20 አመቱ ዩክሬናዊ ወላጆቹ ያወጡለትን ኦሌክሳንደር ቱሪን የተባለ ስም በአይፎን 7 መቀየሩን ባለፈው አርብ ማስታወቁን ተከትሎ፣ ኩባንያው ቃል የገባለትንና 850 ዶላር የሚያወጣውን አዲሱን የአፕል ምርት አይፎን 7 ስማርት ፎን ሸልሞታል ተብሏል፡፡ወጣቱ በሚመለከተው የአገሪቱ የህግ አካል ስሙን ለማስቀየር ወጪ ያደረገው 2 ዶላር ብቻ በመሆኑ ከተሸለመው አይፎን ዋጋ አንጻር አትራፊ ነው ብሏል ዘገባው፡፡
ዩክሬናዊው ለሽልማት ብሎ ያጸደቀውን አይፎን 7 የሚለውን አዲሱን ስሙን፣ ወደፊት ወደነበረበት በመቀየር በቀድሞ ስሙ ሊጠራ እንደሚችል መናገሩን የጠቆመው ዘገባው፤ ወጣቱ ስሙን መቀየሩ ቤተሰቦቹንና ጓደኞቹን አስደንግጧል ብሏል፡፡

  20ኛ ዓመቱን ለማክበር በዝግጅት ላይ የሚገኘው ወጋገን ባንክ፣ባለፈው ዓመት ባደረገው እንቅስቃሴ ከታክስ በፊት 478.5 ሚሊዮን ብር ማትረፉን አስታወቀ፡፡
ባንኩ ከትናንት በስቲያ ባካሄደው 23ኛ መደበኛና 12 ድንገተኛ ዓመታዊ የባለአክሲዮኖች ጉባዔ የባንኩ ፕሬዚዳንት አቶ አርአያ ገ/እግዚአብሔር ባቀረቡት ሪፖርት፣ አምና (2015/16) ባደረገው እንቅስቃሴ ታክስ፣ መጠባበቂያና ሌሎች ውጪዎች ከተቀነሰ በኋላ 375.6 ሚሊዮን ብር የተጣራ ትርፍ ማግኘታቸውን ገልጸዋል፡፡
ለመንግሥት 102.9 ሚሊዮን ብር ግብር መክፈላቸውን፣ የተገኘው ትርፍ ከቀደመው ዓመት ጋር ሲነፃፀር የ6.6 በመቶ ብልጫ ማሳየቱንና ከእቅዱ 92 በመቶ ማሳካቱም ተጠቁሟል፡፡  
ካቻምና 1.5 ቢሊዮን ብር የነበረው የባንኩ የተከፈለ ካፒታል፣ አምና 1.8 ቢሊዮን ብር መድረሱንና ጠቅላላ ካፒታሉም ወደ 2.8 ቢሊዮን ብር ማደጉን ለማወቅ ተችሏል፡፡ የባንኩ ጠቅላላ ሀብት ካቻምና ከነበረው 13.7 ቢሊዮን ብር አምና ወደ 16.2 ቢሊዮን ብር ደርሷል፡፡ የተሰበሰበ ተቀማጭ ገንዘብ 11.8 ሚሊዮን ብር ሲሆን የመደበኛ ብድር መጠንም የግምጃ ቤት ሰነድ ግዢን ሳይጨምር 7.6 ቢሊዮን ብር እንደሆነ ተነግሯል፡፡
ባንኩ እ.ኤ.አ በ2025 በአፍሪካ ከሚገኙ 10 ስመጥርና ተፎካካሪ ባንኮች አንዱ የመሆን ራዕዩን ለማሳካት እየተጋ መሆኑን የጠቆሙት ፕሬዚዳንቱ፤ የደንበኞች አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል፣ የሰው ኃይል ብቃትን ለማጎልበት፣ የአገልግሎቱን ተደራሽነት ለማስፋትና የኢንፎሜሽን ቴክኖሉጂ አቅሙን ለማሳደግ እየሠራ ነው ብለዋል፡፡  
የባለአክሲዮኖች ቁጥር 2,456 የደረሰ ሲሆን ባንኩ በአሁኑ ሰዓት 3,385 ሠራተኞችን በሥሩ ያስተዳድራል፡፡ ወጋገን፤ ስታዲየም አካባቢ በማስገንባት ላይ ያለው ባለ 23 ፎቅ፣ ዘመናዊ የዋና መ/ቤት ሕንፃ፣75 በመቶ መጠናቀቁ ተጠቁሟል፡፡