Administrator

Administrator

  ማላዊን ለአራት አመታት ያስተዳደሩት የቀድሞ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ጆይስ ባንዳ፣ በመቶ ሚሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር ተመዝብሮበታል በተባለ የሙስና ወንጀል ተጠርጥረው በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ የእስር ትዕዛዝ የወጣባቸው ሲሆን በአሜሪካ የሚገኙት ባንዳ ግን “ወንጀሉን አልፈጸምኩም፣ ወደ አገሬ ተመልሼ ንጽህናዬን አረጋግጣለሁ” ብለዋል፡፡
በእሳቸው የስልጣን ዘመን ተሰራ ከተባለው ሙስና ጋር በተያያዘ ፕሬዚዳንቷን ጨምሮ 70 የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት፣ ነጋዴዎችና የመንግስት ሰራተኞች መከሰሳቸውን የዘገበው አልጀዚራ፤ በ2014 በምርጫ መሸነፋቸውን ተከትሎ ወደ አሜሪካ በማቅናት፣ በአንድ የልማት ተቋም ውስጥ በመስራት ላይ የሚገኙት ጆይስ ባንዳ ግን፤ በስልጣን ዘመኔ እንዲህ ያለ አስጸያፊ ተግባር አልፈጸምኩም ሲሉ ውንጀላውን ማጣጣላቸውን አመልክቷል፡፡
በአሁነ ወቅት ለስራ ጉዳይ ባመሩበት ደቡብ አፍሪካ የሚገኙት ጆይስ ባንዳ፤ የአገሪቱ ፖሊስ የእስር ማዘዣ እንዳወጣባቸው መስማታቸውን ተከትሎ፣ ለሮይተርስ በስልክ በሰጡት መግለጫ፣ በስልጣን ዘመናቸው ሙስናን በትጋት የታገሉና የመጀመሪያውን የጸረ ሙስና ኮሚሽን ያቋቋሙ፣ የመጀመሪያዋ የአገሪቱ መሪ እሳቸው መሆናቸውን በመጥቀስ፣ ወደ አገሬ ተመልሼ የሚመጣውን ሁሉ ለመጋፈጥ ዝግጁ ነኝ፤ ምንም የሚያስጠይቀኝ ነገር ስላልሰራሁ የሚያስፈራኝ ነገር የለም ብለዋል፡፡
የቀድሞዋ የማላዊ ፕሬዚዳንት ጆይስ ባንዳ፣ በደቡብ አፍሪካ እያከናወኑት የሚገኙትን የበጎ ምግባር ተልዕኮ እንዳጠናቀቁ፣ ወደ አገራቸው በመመለስ፣ የፍርድ ቤት ምርመራ ሂደቱን እንደሚከታተሉ ይጠበቃል ተብሏል፡፡

 አዲሱ አሰራር የህጋዊ ስደተኞችን ቁጥር በግማሽ ይቀንሳል ተብሏል

      ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ፣ ባለፈው ረቡዕ በይፋ ድጋፋቸውን የሰጡት አዲሱ የአገሪቱ የህጋዊ ስደተኞች አቀባበል ስርዓት ረቂቅ አዋጅ፣ የሴኔት ድጋፍ አግኝቶ የሚጸድቅ ከሆነ፣ አሜሪካ የዲቪ ሎተሪ ዕድለኞችን ከመላ አለም መሰብሰቧን ትታ፣ በተለያዩ መስፈርቶች የላቀ ውጤትና ችሎታ እንዳላቸው የተረጋገጡ፣ የተመረጡ ስደተኞችን ብቻ በመቀበል የመኖሪያ ፈቃድ መስጠት እንደምትጀምር ተዘግቧል፡፡
ኤንቢሲኒውስ ከትናንት በስቲያ እንደዘገበው፣ ዕድልን ሳይሆን ችሎታን መሰረት ያደረገ የስደተኞች አቀባበልን ተግባራዊ ለማደረግ ታስቦ የተዘጋጀው ረቂቅ አዋጅ፤ በየአመቱ በህጋዊነት ወደ አሜሪካ የሚገቡ የተለያዩ የአለማችን አገራት ስደተኞችን ቁጥር በመጪዎቹ አስር አመታት ጊዜ ውስጥ በግማሽ ሊቀንስ ይችላል ተብሏል፡፡
አዲሱ አዋጅ በሴኔት ጽድቆ እንደ ህግ በስራ ላይ የሚውል ከሆነ፣ ስደተኞችን የምትቀበለውና የመኖሪያ ፍቃድ የምትሰጠው በዕጣ እና በኮታ ወይም በዘመድ አዝማድ መጠራራት ሳይሆን የተለያዩ መስፈርቶች ተጠቅማ እየገመገመች ነው ያለው ዘገባው፤ከእነዚህ መስፈርቶች መካከልም የስደተኞቹ የእንግሊዝኛ ቋንቋ ችሎታ፣ የትምህርት ደረጃና ዕድሜ እንደሚገኙበት አመልክቷል፡፡
ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን በቅጡ መደገፍ የሚያስችላቸውን አካላዊ ብቃት መያዝና፣ በኢኮኖሚው ውስጥ የራሱን አስተዋጽኦ የሚያበረክት ክህሎት ባለቤት መሆንም፣ በህጋዊነት ወደ አሜሪካ የሚገቡ የተለያዩ አገራት ስደተኞች፣ ከሚገመገሙባቸውና የመኖሪያ ፈቃድ ከሚያገኙባቸው ሌሎች መስፈርቶች መካከል ይጠቀሳሉ።
ሲኤንኤን በበኩሉ፤ ስደተኞችን ለመቀበልና የመኖሪያ ፈቃድ ለመስጠት መስፈርት የሚደረጉ መመዘኛዎችን በተመለከተ ከትናንት በስቲያ ባወጣው ዝርዝር ዘገባ፣ ዕድሜው ከ26 እስከ 30 የሆነ፣ የሌሎች አገራት የመጀመሪያ ወይም የዶክትሬት ዲግሪ ያለው እና የእንግሊዝኛ ችሎታው እጅግ ከፍተኛ የሆነ ስደተኛ፣ ወደ አሜሪካ የመግባትና የመኖሪያ ፈቃድ የማግኘት እድሉ እጅግ ከፍተኛ እንደሚሆን ጠቁሟል፡፡
የኦሎምፒክ ሜዳይ ባለቤቶች ወይም የኖቤል ሽልማት ተሸላሚዎች የሆኑ የሌሎች አገራት ስደተኞችም፣ ከሌሎች በተለየ ወደ አሜሪካ የመግባትና የመኖሪያ ፈቃድ የማግኘት እድላቸው ከፍ ያለ እንደሚሆንም ዘገባው ገልጧል፡፡
በየአመቱ የመኖሪያ ፈቃድ የሚሰጣቸውን ስደተኞች ቁጥር 50 ሺህ ለማድረስ ያለመውና ባለፈው የካቲት ወር ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ ተሰምቶ ሲያወዛግብ የነበረው ረቂቅ አዋጁ፤ፕሬዚዳንት ትራምፕ ባለፈው ረቡዕ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ በእጅጉ እንደሚደግፉትና ለተግባራዊነቱ እንደሚሰሩ በይፋ ማስታወቃቸውን ተከትሎ፣ እንደገና የውዝግብና የውይይት አጀንዳ መሆን መጀመሩንም ዘገባው ጠቁሟል፡፡
ናሽናል ኢሚግሬሽን ፎረም የተባለው የአገሪቱ ቡድን በበኩሉ፤ በመጪዎቹ 3 አመታት ጊዜ ውስጥ የ7.5 ሚሊዮን ሰራተኞች ዕጥረት እንደሚገጥማት በተነገረላት አሜሪካ፤ከፍተኛ የሰራተኛ የሰው ሃይል ምንጭ የሆነውን የህጋዊ ስደተኞች ፍሰት የሚገታውን ይህን አዋጅ ማጽደቅ፣የአገሪቱን ኢኮኖሚ ክፉኛ የሚጎዳ አደገኛ እርምጃ ነው ማለቱን ኒውዮርክ ታይምስ ዘግቧል። ረቂቅ አዋጁ ከፖለቲካና ኢኮኖሚ ተንታኞች ከፍተኛ ትችት እየተሰነዘረበት ነው ያለው ዘገባው፤ ረቂቅ አዋጁ እንደታሰበው በምክር ቤት ጸድቆ ስራ ላይ የመዋል ዕድሉ እጅግ ጠባብ ነው እየተባለ እንደሚገኝም አመልክቷል፡፡

   ከፈረንሳይኛና ከሌሎች ቋንቋዎች ወደ አማርኛ የተመለሱ ከ20 በላይ አጫጭር ልቦለድ ታሪኮችን ያካተተው “የልብ ሽበትና ሌሎችም” የተሰኘ መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ በተርጓሚና ደራሲ ሀይላይ ገብረ እግዚአብሔር የተተረጎመው ይሄው መፅሐፍ ያካተታቸው ታሪኮች ከዚህ ቀደም በአዲስ አድማስ ጋዜጣና በተለያዩ መፅሄቶች ላይ የወጡና አዳዲስ ታሪኮችም ተጨምረውበት ለንባብ የበቃ መሆኑን ተርጓሚው ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡ በ2015 ገፆች የተመጠነው መፅሐፉ፤ በ68 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

 የገጣሚ ሰለሞን ሞገስ (ፋሲል) አራተኛ ስራ የሆነው “የተገለጡ አይኖች” የግጥም መፅሐፍ ሰሞኑን ገበያ ላይ ዋለ፡፡ ከ75 በላይ በማህበራዊ፣ ፖለቲካዊና ስነ ልቦናዊ ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥኑ ግጥሞችን ያካተተው የግጥም መፅሐፉ፤ እጥር ምጥን ብሎ በ90 ገፆች የተቀነበበ ሲሆን በ40 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡መፅሀፉ በ3ኛው “ንባብ ለህይወት” የመፃህፍት አውደርዕይ ላይ ለምረቃ ከበቁ 28 መፃህፍት መካከል አንዱ ነበር፡፡ ገጣሚ ሰለሞን ሞገስ ከዚህ ቀደም “እውነትን ሰቀሏት”፣ “ከፀሀይ በታች” እና “ፅሞናና ጩኸት” የተሰኙ የግጥም መድበሎች ለንባብ ማብቃቱ ይታወሳል፡፡

   ‹‹የሰላም መዝሙር ለኢትዮጵያና ለኤርትራ ህዝቦች” የተሰኘ የሙዚቃ ኮንሰርትና የፓናል ውይይት ሊካሄድ ነው፡፡ የሙዚቃ ኮንሰርቱንና የፓናል ውይይቱን የሚያዘጋጀው “ሰለብሪቲ ኤቨንትስ” ባለፈው ሳምንት በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፣ የሁለቱን አገራት ህዝቦች የቀደመ ግንኙነት ወደተሻለ ደረጃ ለማድረስ ያግዛል ያለውን የሙዚቃ ድግስና የፓናል ውይይት የሚያካሂደው በቀጣዩ ዓመት ህዳር ወር ላይ ሲሆን በሙዚቃ ኮንሰርቱ ታዋቂና ዝነኛ የሁለቱ አገራት ድምፃውያን ይሳተፋሉ ተብሏል፡፡
በፓናል ውይይቱ ላይ የታሪክ ምሁራን፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ የማህበረሰብ ሰራተኞች የመንግስትና የተቃዋሚ ፓርቲ ተወካዮች በአጠቃላይ 800 ሰዎች የሚሳተፉ ሲሆን በሁለቱ አገር ህዝቦች የወደፊት ግንኙነት ላይ ይመካከራሉ ተብሏል፡፡ የኮንሰርቱና የፓናል ውይይቱ አላማ የሁለቱ አገራት ህዝቦች ድንበርና ጥበቃ ሳይገድባቸው በችግር ጊዜ አብሮ የመቆምና የመደጋገፍ ባህልን እንዲያዳብሩ፣ እንዲሁም የቀደመ ግንኙነታቸው እንዲጠናከር ያለመ መሆኑን የሰለብሪቲ ኤቨንትስ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ሀብቶም ገ/ስላሴ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል፡፡
የፓናል ውይይቱ በመጪው ህዳር 17 የሚካሄድ ሲሆን ኮንሰርቱ ህዳር 30 በሚሊኒየም አዳራሽ እንደሚካሄድ አቶ አብርሃም ተናግረዋል፡፡ በሙዚቃ ኮንሰርቱ ላይ በኢትዮጵያ በአራቱ መጠለያዎች የሚገኙ የኤርትራ ስደተኞችም ይታደማሉ ተብሏል፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃና መምሪያ ማህበረ ቅዱሳን ስር የሚገኘው የአቡነ ጎርጎሪዎስ ስልጠና ማዕከል፣በበገና እና በመዝሙራት ዙሪያ በጥናታዊ ፅሁፎች ላይ የተመሰረተ የፓናል ውይይት፣ ዛሬ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ በአምስት ኪሎ የማህበረ ቅዱሳን ህንፃ 3ኛ ፎቅ ላይ በሚገኘው አዳራሽ ያካሂዳል፡፡ ጥናታዊ ፅሁፎቹ፤ በመጥፋት ላይ ባሉት የበገናና የመዝሙራት ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥኑ ሲሆን ከጥናታዊ ፅሁፎቹ በኋላ ሰፊ የፓናል ውይይት ይካሄዳል ተብሏል፡፡ በውይይቱ ላይ ሊቃውንት አባቶች፣ ባለድርሻ አካላትና የቀድሞ የአቡነ ጎርጎሪዎስ የዜማ መሳሪያዎችና የልሳነ ግዕዝ ተመራቂዎች ይሳተፋሉም ተብሏል፡፡

ማይና ፕሮሞሽን ኢንተርቴይመንት ከኢትዮጵያ ሆቴል ጋር በመተባበር የሚያዘጋጀው ወርሃዊው “ህብረ ትርዒት”፣ የኪነ ጥበብ ምሽት የፊታችን አርብ ከ11፡30 ጀምሮ በኢትዮጵያ ሆቴል ይካሄዳል፡፡ በዕለቱ አጭር ኮሜዲ ተውኔት፣ ግጥም በጃዝ፣ ወግ፣ ሙዚቃና ስታንዳፕ ኮሜዲ እንደሚቀርቡ ማይና ፕሮሞሽንና ኢንተርቴይመንት ለአዲስ አድማስ አስታውቋል፡፡

   የቴሌቪዥን ተከታታይ ፊልም በውድድሩ ተካትቷል

       በሸገር ኤፍ ኤም 102.1 ሬዲዮ ላይ የሚተላለፈው የ‹‹ለዛ›› ፕሮግራም አድማጮች የሽልማት ስነ - ስርዓት 7ኛ ዙር ሊካሄድ መሆኑ ተገለፀ፡፡ በዘንድሮው ውድድር ላይ የተካፈሉት ከሐምሌ 1 ቀን 2008 ዓ.ም እስከ ሐምሌ 1 ቀን 2009 ዓ.ም ድረስ የወጡ የፊልምና የሙዚቃ ስራዎች ሲሆኑ የሽልማት ሂደቱ ከወትሮው በተለየ ምርጥ የቴሌቪዥን ተከታታይ ፊልም የሚል አዲስ ዘርፍ ማካተቱን የለዛ ፕሮግራም ዋና አዘጋጅና የሽልማቱ ፈጣሪ ጋዜጠኛ ብርሃኑ ድጋፌ ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡ አዲሱ ምድብ የሽልማት ዘርፎቹን ዘጠኝ ያደርሳቸዋል የተባለ ሲሆን ምርጥ አልበም፣ ምርጥ ፊልም፣ ምርጥ ተዋናይ፣ ምርጥ አዲስ ድምፃዊና ድምፃዊት፣ ምርጥ ነጠላ ዜማ፣ ምርጥ የሙዚቃ ቪዲዮና የህይወት ዘመን ተሸላሚ በሚሉ ዘርፎች ውድድሮች ይካሄዳሉ፡፡
የሙዚቃ ቪዲዮ ምድብ ተሳታፊዎች  በአልበምነት በተጠቀሰው ዓመት የቀረቡና የሙዚቃ ቪዲዮ የተሰራላቸው መሆን አለባቸው ያሉት አዘጋጆቹ፤ ይህም የተደረገው የአልበም ስራዎችን ለማበረታታት እንደሆነ ተገልጿል፡፡ የዘንድሮውም የድምፅ አሰጣጥ የመጀመሪያ ዙር በwwwshgerfm.com የሚከናወን ሲሆን፣ በሁለተኛው ዙር ምርጥ አምስቱ ከተለዩ በኋላ ኮድ ተሰጥቷቸው በ8101 በአጭር የፅሁፍ መልዕክት ተጨማሪ የድምፅ ማሰባሰብ ስራ እንደሚካሄድ ተጠቁሟል፡፡ የሙዚቃ ድምፅ አሰጣጡ መቶ በመቶ ለአድማጭ የተሰጠ ሲሆን የውድድሩን ሂደትና የድምፅ ቆጠራውን ለመቆጣጠር ጉዳዩ የሚመለከታቸው ማህበራትና ተቋማትን ለማሳተፍ እንደታቀደ አዘጋጆቹ  ተናግረዋል፡፡ በፊልም ስራው ውድድር 60 በመቶ በዳኞች፣ ቀሪው 40 በመቶ በተመልካች የሚዳኝ ሲሆን በዚህ የምርጫ ሂደት ህብረተሰቡ ንቁ ተሳትፎ እንዲያደርግና ሽልማት የሚገባቸውን የኪነ - ጥበብ ሰዎች ለመሸለም የበኩሉን አስተዋፅኦ እንዲደርግ የሽልማቱ አዘጋጅ ጋዜጠኛ ብርሃኑ ድጋፌ ጥሪ አድርጓል፡፡  

   በህዳር ወር 1957 ዓ.ም ላይ ነበር እስከዛሬም ድረስ መለያቸው የሆነውን “ጤና ይስጥልኝ ልጆች… የዛሬ አበባዎች የነገ ፍሬዎች…” የሚለውን ሰላምታቸውን አስቀድመው፣ በዘመኑ ብርቅዬ በነበረው ባለጥቁርና ነጭ ቀለሙ ቴሌቪዥን ለመጀመሪያ ጊዜ ብቅ ያሉት። እንዲህ እንደ ዛሬው ቴሌቪዥን በየሰው ቤት ሣይገባ የዘመኑ ልጆች የአበባ ተስፋዬን ተረትና ቀልዶች ለመስማት ቴሌቪዥን ላላቸው ጎረቤቶቻቸው የጉልበት ዋጋ ይከፍሉ ነበር፡፡ ግቢ ማፅዳት…አትክልት መኮትኮት…ቆሻሻ መድፋት.. እና የመሳሰሉት ሥራዎች የወቅቱ ልጆች ለአባባ ተስፋዬ ተረትና ጨዋታ የሚከፍሏቸው ዋጋዎች ነበሩ፡፡
ሰኔ 20 ቀን 1915 ዓ.ም በባሌ ክፍለ አገር ከዱ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ የተወለዱት አባባ ተስፋዬ (ተስፋዬ ሳህሉ)፤ የልጅነት ህይወታቸው ያለፈው በከፍተኛ ችግርና እንግልት ነበር፡፡ ወላጆቻቸውን በሞት የተነጠቁት ገና በለጋ ዕድሜያቸው ስለነበር ያደጉት አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ በአንድ መምህር ቤት ነበር። ግፈኛው የጣሊያን ወራሪ እኚህን አሣዳጊያቸውንም በስቅላት ገድሎባቸዋል፡፡ ይህንን መከራና ሐዘን መቋቋም ያቃታቸው አባባ ተስፋዬ፤ በከፍተኛ ሁኔታ ታመሙና ሚኒሊክ ሆስፒታል ገቡ። በሆስፒታሉ የሚሰጣቸውን ሕክምና አጠናቀው ሲጨርሱም መሄጃና መጠጊያ ስለአልነበራቸው በወቅቱ ሆስፒታሉን የሚያስተዳድረው ጣሊያናዊ በሆስፒታሉ ውስጥ በአቅማቸው እንዲያገለግሉ ፈቀደላቸውና ሥራ ጀመሩ። መርፌ ከመቀቀል፣እስከ ቁስል ማሸግና የፈንጣጣ ክትባትን መከተብ እንዲሁም የአበላዘር በሽታዎችን እስከ ማከም  ድረስ ይሰሩ ነበር፡፡
ከጣሊያን ወረራ በኋላ በ1937 ዓ.ም በአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት 11 ብር ወርሃዊ ደመወዝ ተቆርጦላቸው ሥራ ጀመሩ፡፡ ሴት ተዋንያን በሌሉበት ዘመን ፀጉራቸው ላይ ሻሽ በማሰርና ፂማቸውን ሙልጭ አድርገው በመላጨት፣ እንደ ሴት ሆነው ለአራት ዓመታት ተውነዋል፡፡ የመጀመሪያ የመድረክ ቲያትራቸውም “የአርበኛው ሚስት” የሚል ሲሆን በዚህ ቲያትር ላይ የሴት ገፀባህርይን ወክለው ነበር የተወኑት፡፡ ግማሽ ምዕተ ዓመት ለሚጠጋ ጊዜ በሙያቸው አገራቸውንና ወገኖቻቸውን ሲያገለግሉ የኖሩት አባባ ተስፋዬ፤ በመድረክ ላይ ከተጫወቷቸው ቲያትሮች መካከል አፋጀሺኝ፣ የደም ድምፅ፣ ጎንደሬው ገ/ማርያም መቀነቷን ትፍታ፣ አርበኞችና ኢትዮጵያ የተባሉት ይገኙበታል፡፡
በ1944 ዓ.ም በጀነራል መንግስቱ ንዋይ ተመርጠው፣ ወደ ኮሪያ ከዘመተው የኢትዮጵያ ጦር ጋር አብረው ዘመቱ፡፡ በዚህም የሃምሣ አለቃ ማዕረግ ተሰጥቶአቸዋል፡፡ በኮሪያ ቆይታቸውም ከእውቁ ኮሚዲያን ቻርሊ ቻፕሊንና ከፊልም ተዋናይ ማርል ቦሮ ጋር የመገናኘት ዕድል ገጥሞአቸዋል፡፡
አበባ ተስፋዬ፣ የልጆች ፕሮግራምን በቴሌቪዥን ማቅረብ በጀመሩበት ወቅት ደመወዛቸው በፕሮግራም 175 ብር ነበር፡፡ በወቅቱ ሥራውን የሚቆጣጠረው አንድ እንግሊዛዊ ስለነበር  ክፍያቸው ጥሩ ነበር - “እንደ ፈረንጅ ነበር የሚከፈለኝ” ይሉ ነበር - በወቅቱ ስለነበረው ደመወዛቸው ሲናገሩ፡፡ እንግሊዛዊው ሥራውን አስረክቦ ሲሄድ ደመወዛቸው ቁልቁል ወርዶ፣ 70 ብር ሲደረግ ቅሬታ አላቀረቡም፡፡ ለዘጠኝ ዓመታት ሥራቸውን ሲያቀርቡ ከቆዩ በኋላ ደርግ ስልጣን ያዘ፡፡ ያኔ ደግሞ የአባባ ተስፋዬ ደመወዝ ወደ አምሳ ብር፣ ቀጥሎም ወደ 25 ብር እንዲያሽቆለቁል ተደረገ፡፡ ሁኔታው እጅግ የሚያበሳጭ ቢሆንም አባባ ተስፋዬ ስራቸውን ያለምንም ቅሬታ ቀጠሉ፡፡ የአገልግሎት ዘመናቸውና እያበረከቱት ያሉት አስተዋፅኦን ከግምት ውስጥ ያስገባው የወቅቱ የቴሌቪዥን ጣቢያው አስተዳደር፤ ለአባባ ተስፋዬ 750 ብር ወርሃዊ ደመወዝ ይገባዎታል ብሎ ቆረጠላቸው፡፡
ግማሽ ምዕተ ዓመት ለሚጠጋ ጊዜ አገራቸውንና ወገኖቻቸውን በትጋት ሲያገለግሉ የኖሩት የትውልድ ድልድዩ አባባ ተስፋዬ፤ የብዙ ሙያዎች ባለቤት ነበሩ። ተዋናይ፣ ደራሲ፣ ድምፃዊ፣ ሐኪም፣ የሆቴል ቤት አስተናጋጅ፣ የምትሃት ትርኢት አቅራቢ፣ ኮሜዲያን፣ መድረክ መሪ፣ ወታደር፣ ገበሬ እና የሞራል መምህር ሆነው የሚወዱትን ህዝብና አገራቸውን አገልግለዋል፡፡ እኚህን የበርካታ ሙያዎች ባለቤትና የሞራል መምህር፣ አገር በአንድ ድምፅ “አባባ” የሚል ማዕረግ ደርቦ፣ አክብሮአቸው ለዓመታት ኖረዋል፡፡ ከ42 ዓመታት በላይ የህፃናት መካሪ፣ አስተማሪና አጫዋች በመሆን ያገለገሉትን እኚህን ባለሙያ፤የማታ ማታ፣የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በሁለት መስመር ደብዳቤ፣የሥራ ውላቸው መቋረጡን ነግሮ ነው ያሰናበታቸው፡፡ ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ አንዲት የ3 ዓመት ህፃን ባወራችው ቀልድ ላይ የብሔረሰቦችን ክብር የሚነካ ነገር ተናግራለች የሚል ነበር፡፡ ለዚህ ጉዳይ ተጠያቂ ሆነው የስንብት ደብዳቤው እስከተሰጣቸው መስከረም 30 ቀን 1998 ዓ.ም ድረስ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ህፃናትን በስነ ምግባር ኮትኩተው አሳድገዋል፡፡
እኚህን ታላቅ የሞራል መምህርና የአገር ባለውለታ የቴሌቪዥን ጣቢያው በዚህ መልኩ ያሰናብታቸው እንጂ ለአገራቸውና ለወገኖቻቸው ያበረከቱትን አስተዋፅኦ የሚዘክርና ክብራቸውን የሚገልፅ ልዩ ልዩ ፕሮግራሞች በተለያዩ ጊዜያት በአክባሪዎቻቸውና በመንፈስ ልጆቻቸው ተዘጋጅቶላቸዋል፡፡ ከዚህም መካከል ህዳር 28 ቀን 2000 ዓ.ም በሸራተን አዲስ ተከናውኖ የነበረው ልዩ የምስጋና ምሽት ተጠቃሽ ነው። በወቅቱም ለክብራቸውና ለውለታቸው መታሰቢያነት የተዘጋጀላቸውን የወርቅ ሜዳልያ ከደጃዝማች ዶ/ር ዘውዴ ገ/ሥላሴ እጅ ተቀብለዋል፡፡
በትወና ችሎታቸው ከቀድሞው ንጉስ አፄ ኃይለ ሥላሴ የወርቅ ሜዳሊያዎችን በሽልማት ያገኙት አባባ ተስፋዬ፤ በተለያዩ ጊዜያት ልዩ ልዩ ሽልማቶችንም ለማግኘት በቅተዋል፡፡ ከእነዚህ ሽልማቶችም መካከል የኢትዮጵያ የስነ ጥበባትና የመገናኛ ብዙኃን የሽልማት ድርጅት፣ በ1991 ዓ.ም ያዘጋጀውና በቴአትር ዘርፍ በተዋናይነት የህይወት ዘመን ተሸላሚ የሆኑበት ዋንኛው ነው፡፡ ዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ እኚህን ታላቅ የአገር ሀብት ከዓመታት በኋላ አስታውሶ፣ በዘንድሮው ዓመት፣ የክብር ዶክትሬት ሰጥቶአቸዋል፡፡

የአባባ ተስፋዬ እውነታዎች
ወላጅ አባታቸው ኤጀርሣ በዳኔ ይባላሉ፡፡ የሚጠሩበት ሣህሉ የአሳዳጊያቸው ስም ነው፡፡
አዲስ አበባ የገቡት በ10 ዓመታቸው ነበር፡፡
የተማሩት ተፈሪ መኮንን፣ አሁን ኮከበ ፅባህ በተባለው ት/ቤት ነው፡፡
በአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት ነው መጀመሪያ የተቀጠሩት፡፡
ደመወዛቸው 11 ብር ነበር፡፡
በ1947 ዓ.ም አግብተው በትዳር ለ48 አመት ኖረው፣ ባለቤታቸውን በሞት ተነጥቀዋል፡፡
ስልክ ማናገር አይወዱም ነበር፡፡
ቃጫ በጥቁር ቀለም ነክሮ፣ እንደ ዊግ መጠቀም የጀመሩት እሳቸው ናቸው፡፡
በሐረር ራስ ሆቴል፣ ከአስተናጋጅነት እስከ ኃላፊነት ደረጃ ሰርተዋል፡፡
በ1938 ማዘጋጃ ቤት ሲቀጠሩ፣ የሴት ተዋናይ ባለመኖሩ ለአራት ዓመታት እንደሴት በመሆን ተውነዋል፡፡
በአንድ ቲያትር ላይ 3 ገፀ ባህርያትን ወክለው ተውነዋል፡፡
በሚሰሩት የምትሀት ትርኢት ሳቢያ፣ ከሰው ተገልለው ነበር፡፡  
የፃፏቸውን የተረት መፃህፍት ከገበያ እየገዙ፣ በየቦታው እያዞሩ ይሸጡ ነበር፡፡
አፋጀሺኝ የተሰኘው ቲያትር ላይ፣ የንግስቲቱን ገፀባህርይ በመወከል ተውነዋል፡፡


         የታወቀ ተረት ይሁን እንጂ አንድ መፅሐፍ ላይ እንደሚከተለው የቀረበ ታሪክ አለ። በአንድ ወቅት አንበሳ፤ የተፈጥሮ ጥላቻውንና ተቀናቃኝነቱን ይብቃኝ ብሎና በሆነ ምክንያት ትቶ፤ ኑሮና ሕይወትን ቀላልና ውጤታማ ለማድረግ ፈለገ፡፡ ለዚህ ደግሞ ከሌሎች እንስሳት ጋር መተባበር አስፈላጊ መሆኑን አመነበት፡፡ ይሄንኑ ለማድረግ ወደ ጅብ፣ ነብርና ተኩላ ሰፈር ሄደ፡፡
ባልተለመደ ትህትናዊ መንገድ የዱሮ ጉልበተኛነቱንና ማስፈራራቱን ሁሉ ትቶ፤ አዲሱን ዕምነቱን ነገራቸው፡፡ ሦስቱም በጣም ተደሰቱ፡፡ ዕምነቱን መጋራታቸውንና ተግባራዊ እንደሚያደርገው ለማረጋገጥ ወደ ጫካ ሄደው፤
የመጀመሪያውን ትብብር በአንድ ታላቅ አደን እናሳይ፤ ተባባሉ፡፡ ሰለባቸውን በመሻት፣ አንድ ላይ ሲጓዙ አርፍደው፤ በመጨረሻ ቋጥኝ የሚያክል ጎሽ አጋጠማቸው፡፡
እርዳ ተራዳ ብለው፤ ተባብረው ጎሽን ግዳይ ጣሉት፡፡
የንብረት ክፍፍሉ ሰዓት ደረሰ፡፡ አንበሳ፤ እንደተለመደው፣ ከውሉና ከስምምነቱ ውጪ፣ የግዳዩ ዋና አዳይና ደልዳይ እኔ ነኝ አለ፡፡ በባህሪያቸው አራቱም የተለያየ የምግብ አወሳሰድ ባህል ስላላቸው፤ አብረው መብላት አይችሉም፡፡ ነገሩን የተረዳው አንበሳ፤ ድርሻ ድርሻችንን መካፈልና መውሰድ አለብን ሲል ወሰነ፡፡ ሶስቱም በጥርጣሬ እያዩት ተስማሙ፣ ይሁን እሺ አሉት፡፡
አንበሳ ሥጋውን በአራት ከፈለውና፤
ይህ የአራዊት ንጉስ በመሆኔ ይገባኛል፤ አለ
ሁለተኛውን መደብ እያሳየ፤ ይሄ ደግሞ፤ በዚህ አደን ትልቁን ሚና ስለተጫወትኩ ዋጋዬ ነው፣ ለእኔ ይገባል
ሦስተኛውን መደብ አቅርቦ፣ ይሄ በእንስሳነቴ የእኔ የግል ድርሻዬ ነው
አራተኛውንና የመጨረሻውን መደብ እያሳያቸው፤ ‹‹ይሄን የሚነካ ወዮለት!›› አለ፡፡
*   *   *
ማንም ቢሆን፤ የባህሪውን፣ የጠባዩን ፈፅሞ አይተውም፡፡ ጅብ ማንከሱን፣ አዞ ማልቀሱን፣ እባብ መላሱን፣ ግስላ ዘራፌነቱን፣ ሰጎን አሸዋ ውስጥ አንገቱዋን መቅበሯን… አይተዉም፡፡ መቼም ቢሆን መቼም፣ የአንበሳውን ድርሻ በእኩልነት የሚካፈል እንስሳ አይፈጠርም፡፡ አንበሳ አንበሳ ነውና፣ የአራዊት ሁሉ ንጉስ መሆኑን ብቻ ነው የሚያምነው!! እንድንቀበለው የሚፈልገውም ይሄንኑ እውነት ነው፡፡ ስለሆነም ሌላው እሱን ለማገልገል እንደተፈጠረ አድርጎ ማየቱና ማስገበሩ ግድ ይመስለዋል፡፡ ሌሎቹ እንስሳት፤ ‹‹ድር ቢያብር አንበሳ ያስር›› የሚለውን ተረት አያውቁትም ብሎ ያስባል፤ ወይም እውነትም አያውቁትም!
ሙስና፤ የሹሞች፣ ከተለመደው አገርን የማገልገል ተግባር ወደ ግል ጥቅም ማፈንገጥ ነው፡፡ ሙስና ያለ ጥርጥር በሁሉም ህብረተሰብ ውስጥ ይኖራል፡፡ ሆኖም ከማህበረሰብ ማህበረሰብ መጠኑ ይለያያል፡፡ ከአንዱ ዘመን አንዱ ዘመን ውስጥ ሊጎላም ይችላል። በስሜታዊ መልኩ የሚታዩ ጭብጦች እንደሚጠቁሙት፤ የሙስና መጠን ከፈጣን ማህበራዊ ኢኮኖሚያዊ ዝመና ጋር ይተሳሰራል፡፡ በአሜሪካ በ18ኛው እና በ20ኛው ክፍለ ዘመን በነበረው ፖለቲካዊ ህይወት ውስጥ የታየው ሙስና፤ ከ19ኛ ምእተ-ዓመትዋ አሜሪካ ሙስና ይልቅ ዝቅ ያለ ነበር የሚል ግምት አለ፡፡ በብሪታኒያም እንደዚሁ፣ በ17ኛው እና በ19ኛው ምእተ-ዓመት መባቻ ላይ የታየው ሙስና፣ በ18ኛው ምእተ ዓመት ከነበረው ያነሰ ነው የሚመስለው፡፡ በአሜሪካም ሆነ በብሪታኒያ የታየው ሙስና፤ ከኢንዱስትሪው አብዮት፣ አዳዲስ የሀብትና የሥልጣን ምንጮች፣ እንዲሁም መንግስት ላይ አዳዲስ ጥያቄን ይዘው ብቅ ካሉት መደቦች መፈጠር ጋር አብሮ መከሰቱ የአጋጣሚ ነገር ነውን? አይደለም፡፡ ከቡቃያ ሀብታሞች መፈልፈል ጋር አብሮ የፈላ ነው፡፡ የእኛ ግን እንቆቅልሽ ነው! ወጡ ሳይወጠወጥ ወስከባዩ ፍጥጥ!
እናቴን ያገባ ሁሉም አባቴ ነው በሚል አስተሳሰብ፣ በተቀነበበ ህብረተሰብ ውስጥ መንግስትን ከልብ ማመን ይኖራል ማለት አዳጋች ነው፡፡ በመሰረቱ በኢትዮጵያ የሚከሰተው ለውጥ እስከ ዛሬም ሆነ አሁን፣ ከሥረ መሰረቱ ውል የያዘና ህዝብን በትክክል ያሳተፈ ባለመሆኑ፣ እኔ ምን ተዳዬ ይበዛዋል፡፡ ገዢ ሁሉ አንድ አይነት ነው። ፖለቲካ ሁሉ ወይ አባብሎ ማዘያ፣ ወይ አስፈራርቶ መግዣ፤ ዘዴ እንጂ ማንም የማንንም እንጀራ አብስሎ የሚሰጥበት ሂደት አይደለም፤ የማለት እምነት የተጠናወተው ነው፡፡ በዚህ ማህል አገር፤ ህዝብ፣ ሉአላዊነት፤ ዲፕሎማሲ ወዘተ. ከልብ የሰፈሩና ከልብ የምንታገልላቸው አጀንዳዎች መሆናቸው ይቀርና፣ ሁሉም “እኔን አዳምጡ” የሚባልባቸው ስብከቶች ይሆናሉ፡፡ ከዚህ ያውጣን!!
ተቃዋሚም ሆነ አጋር ድርጅቶች፤ከአንዱ ገንዘብ እኩል አገኛለሁ ብሎ ገበታው ላይ ዐይኑን ማፍጠጡ፣ ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ የፖለቲካውን መድረክ ፍትሀዊ በሆነ መንገድ ያልተጋራ፣ ከኢኮኖሚው አዝመራ ቁና ይደርሰኛል፤ የአገር ሀብት የእኔም ድርሻ አለበት ቢል፤ ‹‹ሞኝ ጎረቤት፤ከልጅህ እኩል አርገኝ አለ” የተባለውን ዓይነት የደካሞች መጃጃል፣ ወደ ፖለቲካው ጎራ ልክተት የማለትን ያህል የሽንፈት መለዮ ማጥለቅ ነው፡፡ አንበሳው ሙሉውን ሳይደክም ወስዶታል፡፡ እውነተኛው ተረት፤ ‹‹በስመ ማሪያም ብለን ያመጣነውን እንጀራ፣ ያልደከሙ እየበሉት ነው›› የሚለው ነው፡፡