Administrator

Administrator

Monday, 24 August 2015 09:49

የኪነት ጥግ

(ስለ ሙዚቃ)

- ማዜም የሚሹ ሁልጊዜ ዜማ አያጡም፡፡
የስዊዲሽ አባባል
- ለማዜም ምክንያት አያስፈልግህም፡፡
ማርቲ ሩቢን
- ነፍስህ ውስጥ ሙዚቃ ሲኖር፣ ሙዚቃህ ውስጥ
ነፍስ ይኖራል፡፡
ክሪስ ጃሚ
- ሙዚቃ ለነፍስ ጥንካሬ ያጎናፅፋል፡፡
ላይላህ ጊፍቲ አኪታ
- ማዜም እየቻልክ ለምን ታስባለህ?
ማርቲ ሩቢን
- እኔ ስፅፍ ነፍሴ ያዜማል፡፡
ሜሊሳ ማርሽ
- በትምህርት ቤት ከህፃናት ጋር ማዜሜ እጅግ
አስደሳች የህይወት ተመክሮዬ ነው፡፡
ፒቲ ሲገር
- ታላቅ ወንድሜ አሁንም ድረስ ከእኔ የተሻለ
ዘፋኝ እንደሆነ ያስባል፡፡
ሮድ ስቲዋርት
- ራሴን እንደ ሃገረሰብ ዘፋኝ አስቤ አላውቅም፡፡
ቦብ ዳይላን
- ሙዚቃ ሃይማኖቴ ነው፡፡
ጂሚ ሄንድሪክስ
- የዓለም እጅግ ዝነኛና ታዋቂ ቋንቋ ሙዚቃ ነው፡

PSY
- ሁሉም ሙዚቃ ውብ ነው፡፡
ቢሊ ስትራይሆርን
- በአሁኑ ጊዜ ፀጥታን የትም አታገኙም፡፡ ይሄን
ነገር አስተውላችኋል?
ብርያን ፌሪ
- የሆነ ጊዜ ላይ ልብህ ውስጥ ዜማ አይኖርም፡፡
እንዲያም ሆኖ ግን አቀንቅን፡፡
ኢሞሪ አውስቲን
- ልብህ ውስጥ ዛፍ አኑር፤ ምናልባት ዘማሪ ወፍ
ትመጣ ይሆናል፡፡
የቻይናውያን አባባል

ባለፉት አስር አመታት የተለያዩ ራስን የማበልጸግና የአመራር ስልጠናዎችን ለመካከለኛና ከፍተኛ አመራሮች በመስጠት የሚታወቀው SAK የስልጠና ማዕከል፤በዘንድሮ ክረምት 80 ለሚሆኑ ህጻናትና ወጣቶች እራስን የማበልጸግ (Personal Development)  ሥልጠና መስጠቱን አስታወቀ፡፡  
ስልጠናው በዋናነት ህጻናትና ወጣቶች ከትምህርት እውቀታቸው በተጨማሪ በባህሪያቸው ታንጸው በራሳቸው የሚተማመኑ፣አላማ መር ህይወት የሚመሩና ሃላፊነትን የሚቀበሉ የነገ አገር ተረካቢዎች እንዲሆኑ ለማስቻል ያለመ ነው ተብሏል፡፡
በሶስት ዙር በተሰጡት ስልጠናዎች ተሳታፊ የነበሩ ተማሪዎች እንዲሁም ወላጆች እርካታቸውን የገለጹ ሲሆን ስልጠናው በ10ኛው ቀን ሲጠናቀቅ የ“አልችልም አስተሳሰብ” የቀብር ስነስርዓት (“I can not do it; funeral) ይካሄዳል፡፡ የቀብር ስነስርአቱ ከመካሄዱ በፊት የሬሳ ሳጥን ይዘጋጅና ሁሉም ተማሪዎች ወደ ኋላ የሚያስቀሯቸው አስተሳሰቦች፣ ለምሳሌ - አልችልም፣ ይሉኝታ፣ ያበሻ ቀጠሮ፣ አይመለከተኝም፣ በጎ ነገሮችን ያለማድነቅ አባዜ፣ እኔ ብቻ ልጠቀም (win-Loss) ወይም ሁለታችንም አንጠቀም (Loss-Loss) ወዘተ---ተጽፈው በሳጥኑ ውስጥ ይገቡና ይቆለፍባቸዋል፡፡ በቀብሩ ስነስርዓት ወቅትም ተማሪዎች የደስታ ቀናቸው ስለሆነ፣ ሁሉም ነጭ ልብስ ለብሰው ወደ መቃብሩ ይሄዳሉ። በጉዞውም ላይ ቻው ቻው አልችልም፣ ባይ ባይ አልችልም የሚል መዝሙር ይዘምራሉ፡፡
የቀብሩን ጉድጓድ ተማሪዎች የሚያዘጋጁ ሲሆን የቀብሩም ቦታ ላይ የአልችልም አስተሳሰብ የቀብር ሥነስርዓት በንባብ ይሰማል፡፡ ከዚያም ሳጥኑ በጉድጓድ ውስጥ ገብቶ ይቀበራል፡፡ በቀብሩ ስነስርኣት ላይም ተማሪዎች እነዚህን የቀበሯቸውን ኋላ ቀር አስተሳሰቦች በድጋሚ እንዳያስቧቸው ቃል ይገባሉ፡፡ በቀብሩ ላይ የተነበበው ንባብ፣ በሰልጣኞች መኝታ ቤት ውስጥ እንዲለጠፍና ሁልጊዜ ተማሪዎቹ እንዲያዩት ይደረጋል፡፡
ሳይረፍድ በልጆቻችን አስተሳሰብ ላይ ለውጥ በማምጣት የወደፊት የህይወት መሰረታቸውን አብረን እንጣል የሚል ጥሪ ማስተላለፉን ያስታወሰው ማዕከሉ፤ጉዞውን በዘንድሮ ክረምት በስልጠና  መጀመሩን አመልክቷል፡፡ ስልጠናው መደበኛ ትምህርት በሚጀመርበት አዲሱ አመትም የሚቀጥል ሲሆን ቅዳሜና እሁድ እንዲሁም በየቀኑ የየእለቱ ትምህርት ከተጠናቀቀ በኋላ እንደሚሰጥ ማዕከሉ ጠቁሟል፡፡
የ SAK የስልጠና ማዕከል ራስን የማበልጸግ ስልጠናው እንደ ማንኛውም ትምህርት በአገራችን የትምህርት ስርአት ውስጥ ተካቶ ለሁሉም ኢትዮጵያዊ ተማሪ ከልጅነት ጀምሮ እንዲሰጥ ያለመ  ሲሆን ይህም ውጤቱ በእውቀትና በባህሪ የተገነባ ትውልድ ማፍራት ነው ይላል፡፡
የአልችልም አስተሳሰብ የቀብር ሥነስርዓት
እኛ ዛሬ እዚህ የተሰበሰብነው እራስን የማበልጸግ ሥልጠና የወሰድን ተማሪዎች፣ በዋናነት አልችልም የሚለውን አስተሳሰብና ሌሎችም እራስን ወደ ኃላ የሚያስቀሩ አስተሳሰቦችን ለምሳሌ፡-
እድለኛ አይደለሁም ብሎ ማሰብን
ለይሉኝታ መገዛትን
የአበሻ ቀጠሮ የሚባለውን ሰዓት የማርፈድ አስተሳሰብ
ሌላ ሰውን ለመምሰል የመፈለግ አባዜ
አይመለከተኝም የሚለውን አስተሳሰብ
አሉታዊ ጎኞች(Negative thinking) ላይ የማተኮር አስተሳሰብ
ድርድር ላይ መሸነፍ፣ መሸነፍ (Lose - Lose) የሚለውን ወይም የዜሮ ድምር አስተሳሰብ
ዛሬ ነሐሴ ----------/2007 ዓ.ም ከቀኑ 5 ሰዓት ላይ ቀብሬያቸዋለሁና ከዚህ በኋላ አነዚህ አስተሳሰቦች ከእኔ ጋር ቦታ የላቸውም፡፡ እነዚህ አሮጌ አስተሳሰቦች የአገራችን እድገት ጠንቅ በመሆናቸው በህይወት ዘመናችን ሁሉ ታግለን ከአገራችን ልናጠፋቸው ቆርጠን ተነስተናል፡፡ ዛሬ በቀበርናቸው አሮጌ አስተሳሰቦች ፋንታ የሚከተሉትን 10 አዲስ አስተሳሰቦች ለመተግበር ወሰነናል፡፡
እራሴን በቀጣይነት በእውቀት ለማሳደግ
እራሴን ተቀብዬ በማንነቴ ለመኩራት
በራሴ ለመተማመን
እችላለሁ በማለት በህይወቴ ለስንፍና ቦታ ላለመስጠት
በጎ አመለካከትን (Positive thinking) የህይወቴ መርህ ለማድረግ
የማድነቅ ባህልን የህይወት መመርያዬ ለማድረግ
ሃላፊነት መቀበልን ከህይወቴ ጋር ለማላመድ
የጋራ ተጠቃሚነትን ሁልጊዜ በህይወቴ ለመተግበር
ጊዜዬን በአግባቡ በመጠቀም ያበሻ ቀጠሮ የሚለውን አስተሳሰብ ለመሻር
ኑሮዩን በራይና በአላማ ለመምራት
ይህንንም የአልችልም አስተሳብ የቀብር ስነስርዓት ጽሁፍ፣ በመኝታ ቤቴ ግድግዳ ላይ ለጥፌ ሁልጊዜ ለማንበብ፤
ቃል እገባለሁ!
ቃል እገባለሁ!
ቃል እገባለሁ!

Monday, 24 August 2015 09:47

የፀሐፍት ጥግ

ስለታሪክ)
- ሰው የህይወት ታሪኩን ለሌላ ሰው የተናገረ ዕለት
ነው ታሪክ የተወለደው፡፡
አልፍሬድ ዲ ቪጅኒ
- ጀግና ፈፅሞ የታሪኩ ኮከብ አይደለም፡፡
ማሪሊም ማንሶን
- ዩኒቨርስ የተሰራው ከአቶሞች ሳይሆን ከታሪኮች
ነው፡፡
ሙርየል ፋክይሰር
- ያልተነገረ ታሪክን በውስጥህ እንደመሸከም ያለ
ስቃይ የለም፡፡
ማያ አንጄሉ
- ሁሉም የየራሱ የህይወት ታሪክ ጀግና ነው፡፡
ጆን ባርዝ
- የሰው ልጅ በቆዳ የተለበጠ ታሪክ ነው፡፡
ፍሬድ አሌን
- ልብ ወለድ ፎቶግራፍ አይደለም፤ የዘይት ቅብ
ሥዕል ነው፡፡
ሮበርትሰን ዲቪስ
- ሁሉም ግሩም ታሪኮች አስር በመቶ እውነት
ናቸው፡፡
ኮሎኔል ዴኒስ ፋኒንግ
- ህብረተሰብን የሚገዙት ታሪክ ተራኪዎች
ናቸው፡፡
ፕሌቶ
- እያንዳንዱ የምፈጥረው ታሪክ እኔን ይፈጥረኛል፡፡
የምፅፈው ራሴን ለመፍጠር ነው፡፡
ኦክታቭ ያ ኢ. በትለር
- እውነቱን ለማወቅ የሁለቱንም ወገኖች ታሪክ
ማግኘት አለብህ፡፡
ዋልተር ክሮንኪት
- እያንዳንዷ ሴት የራሷ ታሪክ ባለቤት መሆን
አለባት፡፡ ያለበለዚያ ሁላችንም የዝምታው አካል
ነን፡፡
ዛይናብ ሳልቢ
- አገራትና ቦታዎች ታሪክ፣ ተረክና ባህል አላቸው።
ሞሼ ሳፍዲ
- ይሄን ታሪክ በፊት ሰምታችሁት ከሆነ
አታስቁሙኝ፡፡ ምክንያቱም ደግሜ ልሰማው
እሻለሁ፡፡
ግሮውቾ ማርክስ

የአባ ባሕርይ መዝሙር /3/ በግጥም መልክ በግዕዝ ቋንቋ የፃፉት የሚከተለው ምሣሌ ይገኝበታል፡፡ እንዳመቸ አቅርበነዋል፡፡
በአንድ ዘመን እንዲህ ሆነ፡፡ አንድ ሰው በመንገድ እየሄደ ሳለ፣ በድንገት ከየት መጣ ሳይባል አንድ አውራሪስ ከተፍ አለበት፡፡ ሰውዬው እግሬ አውጪኝ ብሎ ፈፋውን ጉድባውን እየዘለለ፣ ጫካውን እያቋረጠ መጭ አለ፡፡ ፍርሃቱ የትየለሌ ሆነ፡፡ ነብሱን ሳያውቅ ሸሸ፡፡ በመጨረሻ ገደል ገጠመውና ወደ ገደሉ ሲወድቅ አንድ የዛፍ ቅርንጫፍ ፈፋውን ታኮ ተዘርግቶ ኖሮ፤ ያን ሲያይ ሰውዬው አፈፍ አድርጐ ተንጠለጠለበት፡፡ እዚያው ተንጠልጥሎም ሳለ፤ ከጐኑ በኩል አራት እባቦች እየተሳቡ ሲመጡ አየ፡፡ ይብስ ብሎም ከበታቹ አንድ ዘንዶ አየ፡፡ ያ ዘንዶ ሰውዬውን ለመዋጥ አፉን ከፍቶ ወደ እሱ እየተንጠራራ ይጠብቀዋል፡፡
ቀን ያመጣው አይቀሬ ነውና ሁለት ጥቁርና ነጭ አይጦች ደግሞ፤ ሰውዬው የተንጠለጠለበትን የዛፍ ቅርንጫፍ ተጐምዶ እንዲወድቅ እየገዘገዙ የበኩላቸውን እኩይ ተግባር እየፈፀሙ ይገኛሉ፡፡ እኒህንም አየ፡፡
በዚህ ሁሉ መሃል፣ ሰውዬው በፍርሃትና በጭንቀት ተውጦ እያለ፣ ከዚያ ዛፍ ቅርንጫፍ ላይ የሚንጠፈጠፍ የማር ወለላ አየ፡፡ ሰውዬው አፉን ከፈተና ማሩ ወደ አፉ ይፈስለት ዘንድ ጠበቀ፡፡ የማር ወለላው ጥቂት በጥቂት ፈሰሰለት፡፡
ከቶውንም በምን ዘዴና ብልሃት ላመልጣቸው እችላለሁ ያላቸውን ፍርሃቶች፤ ከባዶቹን የእባብ፣ የዘንዶና የአይጥ ፈተናዎች በምን መንገድ አልፋቸዋለሁ? የሚሉትን ጭንቀቶች፤ በወለላው ጣዕም ምክንያት ለጥቂት ጊዜ ሊረሳቸው ቻለ፡፡
                                                   *   *   *
የሰው ልጅ እጅግ አስከፊ በሆነ መከራና ጣጣ አረንቋ ውስጥ ወድቆ እንኳ አንዳች ፋታ የሚያገኝባትን ቅንጣት ቅፅበት ይፈልጋታል፡፡ በእሷም ረክቶ ህይወቱን የሚታደግባትን ተስፋ ይጠነስሳል፡፡ ገደል የከተተውን አውራሪስ መሸሹ እኩይ ዕጣው ነው! ሙሉ በሙሉ ገደል ገብቶ እንዳይንኮታኮት ያ ቅርንጫፍ ተዘርግቶ መጠበቁ ሰናይ ዕጣው ነው፡፡ ከዚህ ዙሪያ ደግሞ እባብና ዘንዶ አሰፍስፈው መንጠራራታቸው፣ ለሰውዬው የታዘዙ እኩይ ዕጣዎች ናቸው፡፡ ይሁን እንጂ ጠብታዋ ወለላ ማርም የሰውዬው ሰናይ ዕጣ ናቸው! መከራዎቻችን የተስፋ ዕልባት አላቸው፡፡ በብዙ ድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ነጥብ ብርሃን የማየት ችሎታ መኖር መታደል ነው!
አያሌ ውጣ - ውረዶችን ባየንባት አገራችን፤
“ኧረ እናንተ ሰዎች ተውኝ እባካችሁ
እንኳን የመሶቡን የጄን ተውኩላችሁ”
…ስንል ኖረናል፡፡ ለማን ነው የምንተወው? ለምንድን ነው የምንተወው? እስከመቼስ የምንተወው? የሚሉትን ጥያቄዎች አላነሳንም፡፡ በዚህ ውስጥ መታሰብ ያለባቸውን ኃላፊነታችንን የመወጣትና መብታችንን የማስከበር ፍሬ - ጉዳዮች ምን ያህል አስበንባቸዋል? በምን ያህል ዕቅድና የረዥም መንገድ ትግበራስ ውጤታማ እንደምንሆን እርግጠኞች ነን? ማለት የአባት ነው፡፡
ተጨባጭ ችግሮቻችንን በተጨባጭ መንገድ መፍታት አለመቻል አንዱ ተጨባጭ ችግራችን ነው፡፡ በሀሳብ አንደጋገፍም፡፡ ሀሳብ ካቀረብን ስለችግር እንጂ ስለመፍትሄ አይደለም፡፡ ስለሆነም በችግራችን ላይ ሌላ ችግር ጨምረን ነው የምንለያየው፡፡
የኮሚቴ መብዛት ችግር አለ ተብሎ፣ ያን የሚፈታ ኮሚቴ እናቋቁም ብለው ተለያዩ እንደተባለው  ነው፡፡ አንዱ መሰረታዊ ዕጣችን ስለጊዜ ያለን አስተሳስብ ነው፡፡ ሊቀ-ጠበብት አክሊለ ብርሃን የደረሱትን ማህሌት ልብ እንበል፡-
“በሰላማ ጊዜ የረጋ ወተት
ተንጦ ተንጦ ቅቤው ወጣለት”
ጊዜ የወሰደ ሰው አንድ ቀን ቅቤው ይወጣለታል ነው ነገሩ፡፡ ጊዜን አርቀን ለማሰብ ግን የአዕምሮም የልቡናም አቅም የለንም፡፡ (ለምሳሌ የሃያ ዓመት ዕቅድ አይገባንም፡፡)
ከቀደምት ዘመናት ጀምሮ በአገራችን ብዙ አጋጣሚዎችን አጥተናል፡፡ በተለይ ቀለም የቀመሰው ክፍል ብዙ ዕድሎችን አጥቷል፡፡ አንድም አንፃር በማብዛት፣ አንድም ከሥርዓቱ ጋር አብሮ የመሥራት ባህል ስለሌለው፡፡
“አገራችን የዕድል ሳይሆን የታጡ - ዕድሎች አገር ናት” ይላል አንድ ፈላስፋ (A land of missed opportunities not of opportunities) የእኛም ምሁራን እንዲሁ ቢሉ እንዴት መልካም ነበር! ዶክተር ጌታቸው ኃይሌ ከፃፉት ውስጥ “ጌታ ዲነግዴ የሳምንት ገበያ ሲደርስ ከከብቶቻቸው አንዱን በሬ ለመሸጥ ገበያ ይወስዳሉ፡፡ ግን አንዳንድ ጊዜ ገበያ እስኪፈታ እዚያው ውለው በሬውን ሳይሸጡት ይቀሩና መልሰው ያመጡታል፡፡ አባቴ፤ “ጌታ ምነው በሬውን መለሱት? ገዢ አጡ እንዴ?” ሲላቸው፤ “የለም ልጄ ገዢስ ሞልቶ ነበር፤ ግን ስጠይቃቸው፤ በቀዬው ለበሬዬ የሚበቃ የመስኖ ሣር ያለው አንድም ሰው አላገኘሁም፡፡ ለእነሱ ሸጬ በሬዬን ረሀብ ላይ እንዳልጥለው ብዬ መልሼ አመጣሁት” ይሉታል… የሚል ይገኝበታል፡፡ ይህንንም በምግብ ራስን መቻል ከሚለው የዛሬ ትግላችን ጋር አዛምዶ ማየት ደግ ነው! በሬው ተሸጦ የሚበላው እንዳያጣ የሚታሰብበትም ዘመን ነበር - ያኔ፡፡
በተደጋጋሚ ከሚነሱት የምሁር አምባ ችግሮች ወሳኙ፤ “ጠባብነትና ትምህክተኝነት የምሁሩ አባዜዎች መሆናቸውን አለመርሳት ነው!” የሚለው ነው፡፡ በሁለቱም ፅንፍ የተቸከልን ብዙ ምሁራን አለን! አምላክ ደጉን ያምጣልን!!
አበሻ “ጅብ ከሄደ ውሻ ጮኸ” ይለናል፡፡ ችግሮቻችን መፍትሄ ሳያገኙ ሰንብተው ካንሠር አከል (Cancerite) ከሆኑ በኋላ ብንጮህላቸው ከንቱ መባዘን ነው፡፡ “ቀድሞ ነበር እንጂ መጥኖ መደቆስ አሁን ምን ያደርጋል ድስት ጥዶ ማልቀስ” የተባለውን ማጤን ነው፡፡
አገር እንደ ፅጌረዳ አበባ ብንመስላት፤ “ፅጌረዳዋ ከደረቀች በኋላ፣ ጎርፍ የሆነ ዝናብ ምን ይበጅ?!” የሚለው ይገባናል፡፡ ቀድመን እንዘጋጅ!!

    አቃቤ ህግ ይግባኝ እጠይቃለሁ ብሏል
    ከአንድ አመት በፊት በሽብር ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር ከዋሉት 10 ተከሳሾች መካከል  የቀድሞ የአንድነት የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ሀብታሙ አያሌውን ጨምሮ አራት የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና አንድ ሌላ ግለሰብ በቀረበባቸው ክስ ላይ መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ እንዲሰናበቱ ፍ/ቤቱ ከትናንት በስቲያ በይኗል፡፡ ቀሪዎቹን 5 ተከሳሾች ይከላከሉ ብሏል - ፍ/ቤቱ፡፡ አቃቤ ህግ ይግባኝ እጠይቃለሁ ብሏል፡፡
ፍ/ቤቱ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮቹን፡- ሀብታሙ አያሌው፣ የሸዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታና ዳንኤል ሺበሺ እንዲሁም አብርሃም ሰለሞን የተባለውን ግለሰብ ነው በነፃ ያሰናበተው፡፡ ዘላለም ወ/አገኘሁ፣ ዮናታን ወልዴ፣ ሰለሞን ግርማ፣ ባህሩ ደጉና ተስፋዬ ተፈሪ የተባሉት ተከሳሾች ደግሞ ተከላከሉ ተብለዋል፡፡
አቃቤ ህግ፤ ግለሰቦቹ ከ2000 ጀምሮ ግንቦት 7 ከተባለ የሽብርተኛ ድርጅት ጋር ግንኙነት በመፍጠር፣ በተለያዩ ማህበራዊ ድረገፆች መረጃ በመለዋወጥ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ በአረቡ ዓለም የተከሰተውን አመፅ ለመተግበር የተለያዩ እንቅስቃሴዎች ማድረጋቸውንና ከሽብር ድርጅቱ የሚላክላቸውን ገንዘብ እስከመቀበል መድረሳቸውን በመጥቀስ ነው በአራት የሽብር ወንጀሎች ክስ የመሰረተባቸው፡፡የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ የነበረው አቶ ሀብታሙ አያሌው ላይ አቃቤ ህግ ያቀረባቸው ማስረጃዎች፣ አንድ ሳምሰንግ
ሞባይል ስልክና ከብሄራዊ መረጃና ደህንነት ተገኙ የተባሉ ተከሳሹ በተለያዩ ስብሰባዎች ላይ ያስተላለፋቸው መልዕክቶችና የስልክ ልውውጦች ሲሆኑ የአቃቤ ህግ ምስክሩም በፍተሻ ወቅት ሳምሰንግ ሞባይል በቤቱ እንደተገኘና በስልኩ ውስጥ ምን እንዳለ እንደማያውቅ ለፍ/ቤት አስረድቷል፡፡ ፍ/ቤቱም ማስረጃዎቹንና ምስክሩን መርምሮ በሰጠው ብይን፤ ግለሰቡ ሳምሰንግ ሞባይል ብቻ መያዙ ሽብርተኛ አያስብልም ብሏል፡፡
በማስረጃነት የቀረቡትን ሰነዶችም የመረመረው ፍ/ቤቱ፤ ንግግር አድርጓል በሚል የቀረቡት ማስረጃዎች የሚያስረዱት የአንድነት ድርጅት የመረጃ ኃላፊ መሆኑን ብቻ ነው በማለት ክሱ በሰውና በሰነድ ማስረጃ ያልተደገፈ በመሆኑ በነፃ እንዲሰናበት በይኗል፡፡ ሌላው ተከሳሽ የአንድነት ፓርቲ የድርጅት ጉዳይ ም/ኃላፊ ዳንኤል ሺበሺም ሁለት ሳምሰንግ ሞባይል እንደተገኘበትና በሞባይሉ ውስጥ ምን እንዳለ አለማየታቸውን የአቃቤ ህግ ምስክሮች ማስረዳታቸውን የጠቀሰው ፍ/ቤቱ፤ ከብሔራዊ ደህንነት መረጃ የተገኘው ሰነድም
ክሱን በበቂ የሚያስረዳ አይደለም ሲል ግለሰቡን በነፃ አሰናብቷል፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ አመራር አቶ የሸዋስ አሰፋና የአረና ፓርቲ አመራር አቶ አብርሃ ደስታም በተመሳሳይ ሁኔታ በነፃ የተሰናበቱ ሲሆን፤ ከፖለቲካ ፓርቲ አመራሮቹ በተጨማሪ ሌላው ተከሳሽ አብርሃም ሰለሞንንም ፍ/ቤቱ በነፃ አሰናብቷል፡፡ በነፃ ከተሰናበቱት ተከሳሾች መካከል ሀብታሙ አያሌውና አብርሃም ሰለሞን በሌላ ጉዳይ የማይፈለጉ ከሆነ ከሐሙስ ጀምሮ ከማረሚያ ቤት እንዲለቀቁ ፍ/ቤቱ ያዘዘ ሲሆን የሺዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታና ዳንኤል ሺበሺ ከዚህ ቀደም ፍ/ቤት በመዳፈር  እስከ 1 ዓመት ከ4 ወር በሚደርስ  እስራት የተቀጡ በመሆኑ ቅጣታቸውን ሲጨርሱ እንዲፈቱ በይኗል፡፡ ተከላከሉ በተባሉት 5 ተከሳሾች ላይ ፍ/ቤት ምስክሮቻቸውን ለመስማት ለህዳር 13 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ይዟል፡፡ የፍርድ ቤቱን ብይን አስመልክቶ አስተያየታቸውን የሰጡት የሰማያዊ ፓርቲ ም/ፕሬዚዳንት አቶ ስለሺ ፈይሣ፤ የፓርቲያቸው አመራር
አባል አቶ የሺዋስን ጨምሮ ፖለቲከኞቹ ነፃ መባላቸው ተገቢ መሆኑን ጠቅሰው፣ “አስቀድሞም እነዚህ ሰዎች ሽብርተኞች አልነበሩም፤ በሰላማዊ ትግል የሚያምኑ ሰላማዊ ታጋዮች ናቸው” ብለዋል፡፡
በእነ የሸዋስ ላይ ምንም ማስረጃ አልተገኘም መባሉ የተፈረደባቸው ሌሎቹ እስረኞች ማስረጃ ተገኝቶባቸዋል ማለት እንዳልሆነ አቶ ስለሺ አክለው ተናግረዋል፡፡ በነፃ ከተሰናበቱት የአንድነት አመራሮች ጋር በአንድ ካቢኔ ውስጥ ሲሰሩ የነበሩት የፓርላማ አባሉ የተከበሩ አቶ ግርማ ሰይፉ በሰጡት
አስተያየት፤ በፍ/ቤቱ ውሳኔ ደስተኛ መሆናቸውን ጠቁመው፤ እንዲህ ያሉ የፍ/ቤት ውሳኔዎችን ማበረታታት እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡  መንግሥት በጀመረው መንገድ ሌሎች የህሊና እስረኞችንም መፍታት አለበት ብለዋል - አቶ ግርማ፡፡

      የግብጽ የአቅርቦትና የንግድ ሚኒስትር ካሊድ ሃናፊ፤ የኢትዮጵያን የስጋ ምርት አሁን ከሚሸጥበት ባነሰ ቅናሽ ዋጋ ለመግዛትና ለዜጎች ለማቅረብ የሚቻልበትን ሁኔታ ለማመቻቸት  እንቅስቃሴ መጀመራቸውን ባለፈው ረቡዕ ማስታወቃቸውን ዘ ካይሮ ፖስት ዘገበ፡፡ግብጽ የኢትዮጵያን የስጋ ምርት በቅናሽ ዋጋ በመግዛት በቶጎና በሌሎች የምዕራብ አገራት ለሚገኙ ግብጻውያን ማቅረብ የሚቻልበትን ሁኔታ ለመፍጠር በኢትዮጵያ የግብጽ አምባሳደር ከሆኑት አቡ በከር አል ሃናፊ እና በቶጎ የግብጽ አምባሳደር ከሆኑት ሞሃመድ ከሪም ሸሪፍ ጋር መወያየታቸውን ሚኒስትሩ ገልጸዋል፡፡ግብጽ ከኢትዮጵያ ስጋ ለመግዛት ያሰበችበትን አዲሱን የቅናሽ ዋጋ በተመለከተ ሚኒስትሩ ያሉት ነገር ባይኖርም፣ በአገሪቱ ወቅታዊ ገበያ አንድ ኪሎ ስጋ ከ9.58 እስከ 11.1 ዶላር እየተሸጠ እንደሚገኝ ዘገባው ጠቁሟል፡፡ባለፈው መጋቢት ወር ላይ የግብጹ ፕሬዚዳንት አብዱል ፈታህ አል ሲሲ እና ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ በሁለቱ አገራት ግንኙነት ዙሪያ መምከራቸውንና በወቅቱም የግብጽ ባለሃብቶች በአገራቱ መካከል ያለውን የኢኮኖሚና የንግድ ግንኙነት ለማሳደግ እየሰሩ እንደሚገኙ ለአገራቱ መሪዎች መግለጻቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ባለሃብቶቹ የኢንዱስትሪ ዞን እንዲቋቋም ወይም የትራንስፖርት ወጪን የሚቀንሱና የኢትዮጵያን ኢንዱስትሪ ለማሳደግ የሚያስችሉ ሌሎች እርምጃዎች እንዲወሰዱ መጠየቃቸውንም
አክሎ ገልጧል፡፡

     በዘንድሮው ክረምት ሦስት ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በአዲስ አበባ ከተማ 14 ሰዎች በውሃ አደጋ ህይወታቸውን ያጡ ሲሆን ባለፈው ዓመት ክረምት ከደረሰው አደጋ በእጥፍ ጨምሯል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ እሳትና ድንገተኛ አደጋዎች መቆጣጠር ባለስልጣን የኮሙኒኬሽን ባለሙያ አቶ ኪዳነ አብርሃ ለአዲስ አድማስ
እንደገለፁት፤ ክረምቱ ከገባበት ሰኔ 1 ጀምሮ እስከ ትናንት በስቲያ 15 የውሃ አደጋዎች ደርሰው የ14 ሰዎችን ህይወት ቀጥፈዋል፡፡ አብዛኞቹ በኩሬና በወንዞች ውስጥ ለመዋኘት ሲሞክሩ ሰጥመው መሞታቸውን አቶ ኪዳነ ገልፀዋል፡፡ አደጋዎቹ በብዛት ያጋጠሙት በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ሃና ማሪያም አካባቢ በሚገኙ ሁለት ኩሬዎች ውስጥ ሲሆን በእነዚህ ኩሬዎች 6 ሰዎች ህይወታቸውን አጥተዋል ተብሏል፡፡ በጀሞ የኮንዶሚኒየም ሳይት ለቤቶች ግንባታ ለሚውል ጠጠር ማምረቻ በተቆፈረ ጉድጓድ ውስጥ በተጠራቀመ የኩሬ ውሃ ደግሞ 3 ሴት ህፃናት ገብተው መሞታቸውን የባለስልጣኑ መረጃ ያመለክታል፡፡ ባለፈው ዓመት የክረምት ወቅት 21 የውሃ አደጋዎች አጋጥመው የ8 ሰዎች ህይወት ሲጠፋ፣ ዘንድሮ 15 አደጋዎች አጋጥመው የ14 ሰዎችን ህይወት ቀጥፏል፡፡  ዓምና ክረምት ላይ መንገድ ዳር በተቆፈረ ጉድጓድ ውስጥ ገብቶ የሞተ ሰው እንደሌለ የጠቆመው የባለስልጣኑ ሪፖርት፤ ዘንድሮ በዓለም ባንክና በቱሉ ዲምቱ አካባቢ የ60 እና የ65 ዓመት አዛውንቶችን ጨምሮ 3 ሰዎች ጉድጓድ ውስጥ ሞተው መገኘታቸውን ገልጿል፡፡ ክረምት ት/ቤት የሚዘጋበት ወቅት በመሆኑ ህፃናትና ታዳጊዎች ዋና ለመለማመድ በሚል ወንዝና ኩሬ ውስጥ እየሰመጡ የሚሞቱ ሲሆን ወንዝ ይዞ የሚመጣን ቁሳቁስ ለመለቃቀም ሲሞክሩም በውሃ የመወሰድ አደጋዎች እንደሚያጋጥሙ አቶ ኪዳነ ተናግረዋል፡፡ ህብረተሰቡ በተለይ ወላጆች፣ ልጆቻቸው ወደነዚህ ቦታዎች እንዳይጠጉ በማድረግ አደጋውን መከላከል ያሻል ያሉት አቶ ኪዳነ፤ ጎርፍ አቅጣጫውን ስቶ ወደ መኖሪያ ቤቶች እንዳይገባም ቱቦዎችን  ከደረቅ ቆሻሻ መጠበቅ አስፈላጊ ነው ብለዋል፡፡ ማናቸውም የመንግስት አካላትም ሆኑ ሌሎች ወገኖች ለተለያዩ ዓላማዎች የቆፈሩትን ጉድጓድ መልሰው እንዲደፍኑ ያሳሰቡት
የባለስልጣኑ የኮሙኒኬሽን ባለሙያ፤ ሁሉም ሃላፊነቱን በመወጣት አደጋውን መቀነስ እንዳለበት ተናግረዋል፡፡  





     በመጪው ጥቅምት የ70ኛ አመት የምስረታ በዓሉን የሚያከብረው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፤ ኢትዮጵያና የቀድሞው የአገሪቱ መሪ ቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ በድርጅቱ መስራች አባልነት ያበረከቱትን አስተዋጽኦ የሚዘክርና የበዓሉ አካል የሆነ ልዩ ፕሮግራም ማካሄዱን ታዲያስ መጽሄት ዘገበ፡፡
ኒውዮርክ ሲቲ ውስጥ በሚገኘው የተመድ ዋና ጽህፈት ቤት ከትናንት በስቲያ በተከናወነው በዚህ ልዩ ፕሮግራም ላይ አለማቀፍ እውቅና ያላቸው የታሪክ ተመራማሪዎች፣ ጸሃፊያንና በተመድ የቀድሞው የኢትዮጵያ ልኡክ ዶክተር ግርማ አበበ፤ ቀዳማዊ ሃይለ ስላሴ በተመድ የነበራቸውን ሚና በተመለከተ ንግግር አድርገዋል፡፡ቀዳማዊ ሃይለ ስላሴ በሊግ ኦፍ ኔሽንስ ያበረከቱትን አስተዋጽኦ የሚያሳይ ዘጋቢ ፊልምና ንጉሱ እ.ኤ.አ በ1963 በተባበሩት መንግስታት ድርጅት፣ በዋይት ሃውስና በሌሎች መድረኮች ላይ ያደረጓቸውን ንግግሮች የሚያሳዩ የቪዲዮ ምስሎች ለታዳሚው ቀርበዋል፡፡በተመድ የቀድሞው የኢትዮጵያ ልኡክና የተመድ ጽህፈት ቤት የፖለቲካ ጉዳዮች ክፍል ምክትል ዳይሬክተር የነበሩት ዶ/ር ግርማ አበበ ባደረጉት ንግግር፤ ቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ስብሰባዎች ላይ ያደረጓቸውን በሰላም፣ በጸጥታና በሰብዓዊ
መብቶች ዙሪያ የሚያጠነጥኑ ንግግሮችን ዳስሰዋል፡፡

“በካህናትና ሠራተኞች ስም የሚደረግ የተቃውሞ እንቅስቃሴ ተቀባይነት የለውም”

    በቤተ ክርስቲያኒቱ ሀብት፣ ዘረፋ እና ምዝበራ ጥፋታቸው የተረጋገጠባቸው የአድባራት እና የሀገረ ስብከት ሙሰኛ ሓላፊዎች ለሕግ ተጠያቂነት ተላልፈው እንደሚሰጡ፣ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ተናገሩ፡፡የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ምንጮች እንደጠቆሙት፣ ፓትርያርኩ ይህን የማረጋገጫ ቃል የተናገሩት፣ ስለ አድባራቱ የመሬት፣ የሕንጻ እና የልዩ ልዩ ገቢ ማስገኛ ተቋማት ኪራይ ተመን በተካሔደው ጥናታዊ ሪፖርት ላይ የሀገረ ስብከቱን ዋና ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ማእምራን የማነ ዘመንፈስ ቅዱስ፤ ባለፈው ማክሰኞ ጠዋት በጽ/ቤታቸው ባነጋገሩበት ወቅት ነው፡፡ጥናታዊ ሪፖርቱ፣ ‹‹አድሏዊ እና ግለሰቦችን ለማጥቃት የተደረገ ነው›› በሚል በአንዳንድ አድባራት ተቃውሞ ማስነሣቱን ዋና ሥራ አስኪያጁ ለፓትርያርኩ ጠቅሰዋል፡፡ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ አስተዳደር ጉባኤ፣ የጥናታዊ ሪፖርቱን የመፍትሔ ሐሳቦች በሙሉ ድምፅ በመቀበል፣ የአድባራቱ ሓላፊዎች ጥፋት በሕግ አግባብ እንዲታይና ክሥ እንዲመሠረትባቸው ያሳለፈው ውሳኔም ሌላ አማራጭ
እንዲፈለግለት ፓትርያርኩን ጠይቀዋል ተብሏል፡፡ ጥናቱ፣ ራሳቸው በሰጡት ትእዛዝ እና የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ አስተዳደር ጉባኤ ባቋቋመው ኮሚቴ በይፋ መካሄዱን ያስታወሱት ፓትርያርኩ፣ ሪፖርቱን ለመቃወም በሚል ካህናትንና ልዩ ልዩ ሠራተኞችን በማደራጀት በጎን የሚቀርብላቸውን አቤቱታ እንደማይቀበሉት ለዋና ሥራ አስኪያጁ ገልጸዋል፡፡‹‹ለማንም ሰው ከለላ መኾን አልፈልግም፤ ሽፋንም አልሰጥም፤ ለአንተም ጨምሮ፤›› በማለት አቋማቸውን ያረጋገጡት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ ‹‹በዚኽ አጸያፊ የዘረፋና የምዝበራ ሥራ ውስጥ እጁ የተገኘበትን ሰው ኹሉ ቤተ ክርስቲያኒቱ አሳልፋ ትሰጣለች፤ ይኼ የመጨረሻ አቋሜ ነው፤›› ሲሉ የሕግ ተጠያቂነቱ አይቀሬ መኾኑን አስታውቀዋል፡፡በፓትርያርኩ ጠንካራ አቋም መደናገጥ ታይቶባቸዋል የተባሉት ዋና ሥራ አስኪያጁ፣ በሀገረ ስብከቱ ተከማችተው ለቆዩትና በየአድባራቱ እየተባባሱ ለመጡት የሙስና እና የመልካም አስተዳደር ዕጦት ችግሮች የአሠራር ማሻሻያዎችን በመተግበር ላይ እንደሚገኝ በማስረዳት፣ ጥናታዊ ሪፖርቱን እንደሚቀበሉትና እንደሚደግፉት ለፓትርያርኩ እንደገለፀላቸው ታውቋል፡፡
ላለፉት ስድስት ወራት በ58 አድባራት ላይ ሲካሔድ የቆየው ጥናት፣ ከሓላፊዎቹ ጋር የጥቅም ትስስር ለፈጠሩ ግለሰቦች በሚያደሉ ውሎች የቤተ ክርስቲያኒቱ መሬት፣ ሕንጻዎች፣ ሱቆች እና ልዩ ልዩ የገቢ ማስገኛ ተቋማት ላይ የተጧጧፈ ዘረፋና ምዝበራ መፈፀሙን አረጋግጧል፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ ሀብትና ንብረቷን ከብክነት ለመታደግ ያወጣችውን የቃለ ዐዋዲ ደንብ ማስከበር የሚገባው የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትም፤ ከድንጋጌው ውጭ ለተሠሩ ሥራዎች ዕውቅና በመስጠት የሕግ ጥሰቱ አካል እንጂ የሕግ አስፈጻሚ መኾን
አለመቻሉ የችግሩ ባለቤት እንደሚያደርገው በሪፖርቱ ተጠቁሟል፡፡

ከ400 በላይ የአገር ውስጥና የውጭ ሀገራት ተሣታፊዎች የሚካፈሉበትና ከ500ሺ በላይ ሰዎች ይጐበኙታል ተብሎ የሚጠበቀው “አበሻ አዲስ አመት ኤክስፖ 2008” ዛሬ ይከፈታል፡፡
የቀድሞው ፕሬዚዳንት ግርማ ወልደጊዮርጊስና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አቶ ቴዎድሮስ አድሃኖምን ጨምሮ ሌሎች ታላላቅ የመንግስት ባለስልጣናት በእንግድነት ይገኙበታል በተባለው በዚህ የአዲስ አመት ኤክስፖ ላይ ከ100 በላይ የአገሪቱ ታላላቅ ድምፃውያንና ኮሜዲያን ሥራዎቻቸውን ለጐብኚዎች ያቀርባሉ ተብሏል፡፡
ለሃያ አንድ ቀናት በሚቆየው በዚህ ኤክስፖ፤ የአለማችንን ትልቁ የሻማ ዛፍ የማብራት ሥነስርዓት እንደሚካሄድም ታውቋል፡፡