Administrator

Administrator

ከዕለታት አንድ ቀን፤ አንድ ሰው ብዙ ከብቶች ወዳሉበት አንድ በረት ገብቶ አንድ ላም ሰርቆ ሲወጣ፤ አንድ መንገደኛ ሰው ያየዋል፡፡ ያም ሌባ ጣቱን አፉ ላይ አድርጐ “ዝም በል አትንገርብኝ ባክህ!” ይለዋል፡፡
ያም መንገደኛ ለማንም እንደማይናገርበት ራሱን በአዎንታ ነቀነቀለት፡፡
ሌላ ጊዜ ሌባውና መንገደኛው አንድ ሆቴል ቤት ተገናኙ፡፡ መንገደኛው ምግቡን በልቶ ሌባውን ክፈልልኝ አለው፡፡
“ለምንድነው የምከፍለው?” አለው ሌባው፡፡
መንገደኛው፤
“ዋ! የላሟን ነገር ለመንደሩ አለቃ እነግርልሃለሁ!” አለው፡፡
ሌባው ተሽቆጥቁጦ ከፈለ፡፡
ሌላ ቀን አንድ የገበያ አዳራሽ ውስጥ ይገናኛሉ፡፡ መንገደኛው የሚችለውን ዕቃ ወስዶ ሲያበቃ ለባለሱቁ፤
“ያ ሰውዬ ይከፍላል” ብሎ ወደ ሌባው ጠቆመ፡፡
ሌባው አሁንም፤
“ለምንድነው የምከፍለው?” አለ፡፡
መንገደኛውም፤
“ዋ! የላሟን ነገር!” አለው፡፡
ሌባው የግዱን ከፈለ፡፡
በሌላ ቦታ መንገደኛው ሌባውን አገኘውና፤
“ገንዘብ ቸግሮኛልና ስጠኝ?” አለው፡፡
ሌባው፤ “ለምንድን ነው የምሰጥህ?” አለ፡፡
“ዋ! የላሟን ነገር!” ሲል ገና፤ ገንዘብ አውጥቶ ሰጠው፡፡
ሆኖም አሁን ቆም ብሎ ማሰብ ጀመረ፡፡
“ለምን ሄጄ ለመንደሩ አለቃ ላም መስረቄን ነግሬ፣ ይቀጣኝም እንደሆን አልቀጣም?” ብሎ አሰበ፡፡ ወሰነ፡፡
ቀጥ ብሎ ወደ መንደሩ አለቃ ሄደና፤
“ጌታዬ፤ ቸግሮኝ ከመንደሩ በረት አንድ ላም ሰርቄያለሁ፡፡ በህጉ መሠረት የምትቀጣኝን ቅጣኝ” ሲል ጠየቀው፡፡ (“የምታፋፍምብኝን አፋፍምብኝና ልሂድ!” እንዳለው ሰው በቀይ ሽብር ዘመን)
አለቅየውም፤ አውጥቶ አውርዶ፤ “ዋናው ይቅርታ መጠየቅህ ነው” ብሎ በምህረት ሸኘው፡፡
ሌባው በደስታ እየፈነጠዘ ሄደ፡፡
ሌላ ቀን መንገደኛው እንደልማዱ “ገንዘብ አምጣ” አለው፤ ሌባውን፡፡ “አልሰጥም” አለ ሌባው።
“ዋ! የላሟን ነገር!” ሲለው፤
“የፈለከው ቦታ ድረስ!” ብሎት ሄደ፡፡
መንገደኛው ተናዶ፤ ወደ መንደሩ አለቃ እየበረረ ሄደና፤ “እገሌ ላም ሰርቋል” ሲል ተናገረ፡፡
አለቃውም “እሱስ ይቅርታ ጠይቋል፡፡ አንተ ነህ ሌባ!”
“ለምን?” አለ መንገደኛው፡፡
“እስካሁን በልብህ ላሟን ይዘህ የምትዞር አንተ ነህ!” አለው፡፡
*   *   *
በአካል የሠረቀው ሌባ ሲባንን ይኖራል፡፡ በልቡ ስርቆቱን የያዘው የባሰ ሌባ፣ ከሌባ እየተሻረከ ሳይነቃበት ይኖራል፡፡ ይህ የሚሆንበት አገር ለከፍተኛ ጥፋት የተጋለጠ ነው፡፡ ቀና የሚመስለው መንገድ ሁሉ ዕውን ቀና ነወይ? ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡ የምንገለገልባቸውን ቃላት እንመርምር።
እንደ “ነፃነት”፣ “አማራጭ” እና “ዕድሎች” ያሉ ቃላት ከሚሰጡት ዕሙናዊ ጥቅም የበለጠ ቀስቃሽ ኃይል አላቸው፡፡ በተግባር ግን ገበያ ቦታ፣ በምርጫ ጊዜ እና በሥራ ቦታ አማራጭ ያለን የሚመስሉን “ሀ” እና “ለ”፤ ሌሎቹን ሆህያት ተትተው የተሰጡን ናቸው፤” ይላል ሮበርት ግሪን፡፡
አንድ መሠረታዊ የገዢዎች መርህ አለ፡-
“የመጨረሻው ምርጥ የማጭበርበሪያ ዘዴ፤ ለባላንጣህ አማራጭ የሰጠኸው ማስመሰል ነው። ያኔ ያንተ ሰለባዎች ጉዳዩን የተቆጣጠሩ እየመሰላቸው አሻንጉሊትህ ይሆናሉ፡፡ ከሁለት እኩይ ነገሮች አንዱን እንዲመርጡ አድርጋቸው፡፡ (Choosing between two evils) ሆኖም ሁለቱም አንተን የሚጠቅሙ እንዲሆኑ ማድረግ ነው ዋናው ጥበብ፡፡” (ሮበርት ግሪን)
አማራጮችን አስፍቶ ያለማየት ድህነት፣ አንዱ የድህነታችን ምንጭ ነው፡፡ ይሄ አንድም ከዕውቀትና አቅም ማነስ፣ አንድም አርቆ የማስተዋል ባህል ከማጣት፣ አንድም ደግሞ በአፍንጫ ሥር ዕይታ ከመወጠር ሊከሰት ይችላል፡፡ ከታጠርንበት አጥር ባሻገር ማየት መልካም ነገር ነው። “ይቺን ያቀድኳትን በስኬት ከተወጣሁ” አመቱን እሰየው ብዬ ጨረስኩ፤” ማለት ሌላ እንዳናይ ሊገድበን የሚችል አካሄድ መሆኑን ልብ እንበል፡፡ በአጭር ርዕይ ታቅበን ጊዜ ያመልጣል፡፡ በጀማ ጉዞ ከጀማው ጋር ከማዝገም በላቀ ንቃተ ህሊና መፈትለክ የሚያሻበት ጊዜ ነው፡፡
አንድ ህፃን ልጅ፤ “ወደፊት ምን ለመሆን ታስባለህ?” ተባለ አሉ ዘንድሮ፡፡
ልጁም፤ “ዲያስፖራ!” አለ፡፡ (ስለዲያስፖራ ስንናገር ትውልድን እናስብ!)
ዳያስፖራ ማለት፤ አንድ ተሰብስቦ፣ በአንድ ቦታ ተቀምጦ የነበረ ህዝብ ወይም ቋንቋ አሊያም ባህል፤ ሲበተን ወይም ወደሌላ ሲሰራጭ የሚሰጠው መጠሪያ ነው፡፡ አይሁዳውያን ከእሥራኤል ውጪ የተበተኑበትንም ሁኔታ የሚያመላክት ነውም ይላሉ፡፡ እንግዲህ ለኢትዮጵያውያንም እንደዚያው ነው፡፡
ኢትዮጵያ የውጪውን ዓለም ኢትዮጵያውያን መሰብሰቧ ደግ ነገር ነው፡፡ አያያዟ ምን ያህል ከኢኮኖሚዋ፣ ከፖለቲካዋ፣ ከዲፕሎማሲዋና ከባህሏ ጋር መስተጋብር ይኖረዋል? ዳያስፖራውያኑስ ምን ያህል ከልባቸው መጥተዋል? ተስፋቸው፣ ምኞታቸው፣ የሀገር ፍቅር ስሜታቸው ምን ያህል የጠለቀ፣ ምን ያህልስ ከጥቅም ባሻገር አገርና ህዝብን ያግዛል? የሚለው የነገ ጥያቄ ነው፡፡ እግረ መንገዳችንን፤ ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን፤ “ሰው ሆኖ ካሹት (ከፈተጉት) ጥቅም የማይሰጥ የለም” ያለውን ልብ ማለት ይጠቅማል፡፡
እንግዲህ መንገዱ ረጅም ነው፡፡ ከካሬ ሜትር እስከ ልብ ሜትር የሚያለካካ ነው! ማናቸውም ነገር አልጋ በአልጋ አለመሆኑን መገንዘብ ደግ ነው፡፡ ህጋዊውን፣ ቢሮክራሲያዊውንና ሰዋዊውን መንገድ በቀቢፀ - ተስፋ ለማያይ ሰው፣ ሁነኛና ቀና ብርሃን ሊያስተውልበት የሚችል ሁኔታ አለ። በተወሰነ ደረጃ ግን ሂደቱን ሊያሰናክሉ፣ ሊያቀጭጩና ሊያሟሽሹ የሚችሉ እንከኖች ይኖራሉ? ብሎ አለመጠበቅ ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ “ብላ ያለው ተጋግሮ ይጠብቀዋል፤ ተሸከም ያለው ታሥሮ ይጠብቀዋል” የሚለው ተረት መሠረታዊ፣ አገራዊ ፋይዳ የሚኖረው እዚህ ላይ ነው!  

Saturday, 15 August 2015 15:46

የፀሐፍት ጥግ

(ስለ ንባብ)
- የአዳዲስ መፃህፍት ክፉ ነገራቸው አሮጌዎቹን
እንዳናነብ ማድረጋቸው ነው፡፡
ጆን ውድን
- ብዙ ጊዜዬን የማሳልፈው በማንበብ ነው፡፡
ቢል ጌትስ
- ንባብ የአዕምሮ ባትሪዬን ለመሙላት
ያስችለኛል፡፡
ራሁል ድራቪድ
- እንደ ንባብ ርካሽና ዘላቂ ደስታ የሚያጐናፅፍ
መዝናኛ የለም፡፡
ሜሪ ዎርትሌይ ሞንታጉ
- ንባብ ለህፃናት መቅረብ ያለበት እንደ ግዴታ
ሳይሆን፤ እንደ ስጦታ ነው፡፡
ኬት ዲካሚሎ
- ንባብ ደስታ እንጂ ሥራ መሆን የለበትም፡፡
ጆአን ሪቨርስ
- ንባብ የማይታወቁ ወዳጆችን ያመጣልናል፡፡
ሆኖሬ ዲ ባልዛክ
- ያለ መፃህፍት መኖር አልችልም፡፡
ቶማስ ጃፈርሰን
- የመፃህፍት ገፆች ነፍስ የሚዘሩት ሲገለጡ
ብቻ ነው፡፡
ኤል.ጄ.ዴቬት
- ግሩም አንባቢ ዓለምን የመነቅነቅ ኃይል
አለው፡፡
አማን ጃሳል
- ጊዜህን በማሰብ ለማጥፋት የማትፈልግ ከሆነ
ማንበብ ጀምር፡፡
አማን ጃሳል
- ከንባብ ጋር ፍቅር ይዞኛል፡፡
ላይላህ ጊፍቲ አኪታ
- አንድ ሺ መፃህፍትን አንብብ፡፡ ያኔ ቃላት
ከአንደበትህ እንደ ወንዝ ይፈሳሉ፡፡
ሊሳ ሲ
- አንባቢ ከመሞቱ በፊት አንድ ሺ ህይወቶችን
ይኖራል፡፡ ጨርሶ የማያነብ ሰው ግን አንድ
ህይወት ብቻ ይኖራል፡፡
ጆርጅ አር.አር.ማርቲን

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሰራተኛ ነው ተብሏል

   ከአዲስ አበባው ቦሌ አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ተነስቶ ወደ ስዊድን ስቶክሆልም በመብረር ትናንት ማለዳ አርላንዳ አውሮፕላን ማረፊያ በደረሰው የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን የእቃ መጫኛ ክፍል ውስጥ ተደብቆ የተጓዘው ኢትዮጵያዊ ጥገኝነት መጠየቁን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሰራተኛ እንደሆነ የተነገረለትና በሃያዎቹ እድሜ ክልል ውስጥ እንደሚገኝ የተገለጸው ወጣቱ፣ አውሮፕላኑ ማረፉን ተከትሎ ሰራተኞቹ ጭነት ሊያራግፉ በሩን ሲከፍቱ ክፍሉ ውስጥ ተደብቆ እንደተገኘ የጠቆመው ዘገባው፣ ወዲያውኑ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውሎ በተደረገለት የጤና ምርመራ ምንም አይነት የጤና ችግር እንደሌለበት መረጋገጡን ገልጿል፡፡
ለስምንት ሰዓት ያህል በርሮ አርላንዳ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ በደረሰው አውሮፕላን ተደብቆ የተገኘው ወጣቱ፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሰራተኛ መሆኑን የሚያሳይ የደረት ላይ መታወቂያ ማድረጉን ዘገባው ጠቅሶ፣ ወደ ስቶክሆልም ኢሚግሬሽን ቢሮ ተወስዶ ጥገኝነት መጠየቁንም አመልክቷል፡፡
የአርላንዳ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ ምክትል መኮንን የሆኑት ስቴፋን ፋርዲክስ፤ ወጣቱ ምንም አይነት የወንጀል ድርጊት ፈጽሟል ተብሎ እንደማይጠረጠር ገልጸው፣ በስዊድን አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያዎች መሰል ድርጊት ተፈጽሞ እንደማያውቅና የአሁኑ የመጀመሪያው እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

ማንኛውንም ከብት ያለ ንግድ ፈቃድ መሸጥ አይቻልም

በአዲስ አበባ የዳልጋ ከብት ግብይት ከትላንት ጀምሮ በደረሰኝ እንዲካሄድ የተወሰነ ሲሆን ማንኛውም የቁም እንስሳት የንግድ ግብይት ያለ ንግድ ፈቃድ ማከናወን እንደማይቻልም የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ አስታውቋል፡፡
የከብት ግብይቱ የሚካሄደው በ5 የገበያ ማእከላት፡- በጉለሌ፣ የካ ካራሎ፣ ንፋስ ስልክ፣ አቃቂና ኮልፌ ቀራኒዮ መሆኑን የገለፀው ቢሮው፤ ከእነዚህ ማእከላት ውጪ ምንም አይነት የቁም እንስሳት ንግድ ማካሄድ እንደማይቻል አስጠንቅቋል፡፡
የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ ገመቺሳ መላኩ ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፤ ለጊዜው የደረሰኝ ግብይት ሥርዓቱ የሚመለከተው የዳልጋ ከብት (በሬና ላም) ብቻ ቢሆንም ወደፊት የበግና ፍየል ንግድም በደረሰኝ እንደሚሆን ታውቋል፡፡
የልኳንዳ ማህበር ከግብር ጋር በተያያዘ ሂሳብ ማወራረድ በመቸገሩ ግብይቱ በደረሰኝ እንዲካሄድ በተደጋጋሚ መጠየቁን ኃላፊው ጠቁመው፣ የደረሰኝ ግብይቱ የማህበሩን ችግር እንደሚፈታ ይጠበቃል ብለዋል፡፡
የደረሰኝ  ግብይቱ ህገወጥ እርድን፣ የቤት ለቤት ማደለብንና መሰል ህገወጥ ተግባራትን ለመቆጣጠር እንደሚያስችልና የህብረተሰቡን ጤናም ለመጠበቅ እንደሚያግዝ የተገለፀ ሲሆን የቁም እንስሳት ንግድ ግብይት ሥርዓቱን ለማዘመንም ዓይነተኛ መፍትሄ ነው ተብሏል፡፡
እስካሁን በ5ቱ የገበያ ማእከላት የሚገኙ ነጋዴዎች የንግድ ፍቃድ እንዲያወጡ የተለያዩ ጥረቶች መደረጋቸውንና አብዛኞቹም የንግድ ፍቃድ እንዳላቸው የጠቆሙት አቶ ገመቺስ፤ ፈቃድ ሳያወጡ ተቀላቅለው እየሰሩ ያሉ ነጋዴዎችም ፍቃድ አውጥተው ወደ ህጋዊ ስርአት እንዲገቡ ይደረጋል ብለዋል፡፡ የደረሰኝ ቁጥጥር ስርዓቱንም የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን እንደሚከታተለው ታውቋል፡፡

ተቋሙ ከኢትዮጵያ ጋር መስራቴን  ሙሉ ለሙሉ አቋርጫለሁ ብሏል

አለማቀፉ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ሂዩማን ራይትስ ዎች ለኢትዮጵያ የመረጃ ጠለፋ ቴክኖሎጂዎችን ሸጧል፤ ለደህንነት ባለሙያዎች ስልጠና በመስጠት የዜጎች መብቶች እንዲጣሱ እገዛ አድርጓል ያለውን “ሃኪንግ ቲም” የተባለ የጣሊያን ተቋም በጉዳዩ ዙሪያ በቂ ምላሽ አልሰጠም፣ የመብቶች ጥሰቶችን ለማስቆምም እርምጃ አልወሰደም ሲል ከሰሰ፡፡
ሃኪንግ ቲም ለተለያዩ አገራት መንግስታት የመረጃ መጥለፊያ ቴክኖሎጂዎችን በመሸጥና ለባለሙያዎች ስልጠና በመስጠት፣ መንግስታት የዜጎችን ሰብአዊ መብቶች እንዲጥሱ እገዛ ያደርጋል ያለው ሂዩማን ራይትስ ዎች፣ በኢትዮጵያ ሲከናወን የቆየውን የመረጃ ጠለፋና የመብቶች ጥሰት በተመለከተ ምላሽ እንዲሰጠው ቢጠይቅም በቂ ምላሽ ሊሰጠው እንዳልቻለ ከትናንት በስቲያ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
ተቋሙ ጉዳዩን በተመለከተ ምርመራ ለማድረግም ሆነ የኢትዮጵያ መንግስት ቴክኖሎጂውን በመጠቀም በዜጎቹ ላይ የሚያደርሰውን የመብቶች ጥሰት ለማስቆም ምንም አይነት ተጨባጭ እርምጃ አልወሰደም ሲል የከሰሰው ሂዩማን ራይትስ ዎች፣ ሃኪንግ ቲም ለኢትዮጵያ የደህንነት ባለሙያዎች የግለሰቦችን ኮምፒውተሮች ሰብረው መግባት የሚችሉበትን ስልጠና መስጠቱን እንደቀጠለና ቀጣይ ስምምነቶችን ለማድረግ እንቅስቃሴ ጀምሮ እንደነበር የሚያረጋግጡ መረጃዎችን በሃምሌ ወር እንዳገኘ አስታውቋል፡፡
ሃኪንግ ቲም ለኢትዮጵያ መንግስት የሸጣቸው የመረጃ መጥለፊያ ቴክኖሎጂዎች ከቫይረስ መከላከያ ፕሮግራሞች አቅም በላይ እንደሆኑና በቀላሉ ወደ ግለሰቦች ኮምፒውተሮች በመግባት መረጃዎችን እንደሚወስዱ የጠቆመው ሂዩማን ራይትስ ዎች፣ ከተቋሙ ኢሜይል አፈትልከው የወጡ መረጃዎችም ተቋሙ በሚያዝያ ወር ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ከ700 ሺህ ዶላር በላይ የሚገመት አዲስ የቴክኖሎጂና የስልጠና ስምምነት ለመፈጸም ሲያደርጉት የነበረው እንቅስቃሴ ሳይሳካ መቅረቱን ያመለክታሉ ብሏል፡፡
ሃኪንግ ቲም ጉዳዩን በተመለከተ ምላሹን እንዲሰጥ ባለፈው ሃምሌ ወር ላይ ከሂውማን ራይትስ ዎች ለቀረበለት ጥያቄ በሰጠው ምላሽም፣ የሚያመርታቸው ሶፍትዌሮች የሚንቀሳቀሱት በእሱ ሳይሆን በገዙት ደንበኞቹ መሆኑን ጠቁሞ፣ ቴክኖሎጂው ለስለላ ተግባር ስለመዋሉ የሚያውቀው ነገር እንደሌለ ገልጾልኛል ያለው ሂዩማን ራይትስ ዎች፣ ከተቋሙ አፈትልከው የወጡ መረጃዎች ግን የኢትዮጵያ መንግስት የስለላ ተግባራት የሰብአዊ መብቶችን የሚጥሱ መሆን አለመሆናቸውን ለማጣራት በርካታ አጋጣሚዎች እንደነበሩት የሚያመለክቱ ናቸው ብሏል፡፡
ተቋሙ በዚሁ ምላሹ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ያለውን ግንኙነት በ2015 የመጀመሪያዎቹ ወራት ሙሉ ለሙሉ አቋርጫለሁ ማለቱንም ሂውማን ራይትስ ዎች ጠቁሟል፡፡

በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን ኖኖ ወረዳ ነዋሪ የሆኑ ከ70 በላይ አማርኛ ተናጋሪ ገበሬዎች፣ ቤት ንብረታቸው ተቃጥሎ ከመኖሪያ ቀዬአቸው መፈናቀላቸውን የሰብአዊ መብቶች ጉባኤ (ሰመጉ) በሪፖርቱ አመለከተ፡፡ የአንድ ሰው ሕይወት መጥፋቱንም አረጋግጫለሁ፤ ብሏል፡፡
ሰመጉ ጉዳዩን ሲመረምር መክረሙን ጠቁሞ፣ “ብሔር ተኮር ማፈናቀልና እንግልት በአስቸኳይ ይቁም” በሚል ርዕስ ይፋ ባደረገው 136ኛ ሪፖርቱ የወረዳው የጸጥታ ሓላፊዎችና ባለሥልጣናት የብሔር ግጭቱን መቀስቀሳቸውን አስታውቋል፡፡
እንደ ሪፖርቱ፣ የወረዳው ባለስልጣናትና የፀጥታ ኃላፊዎች አርሶ አደሮቹን፣ “እናንተ የዚህ የአካባቢው ተወላጅ ሳትሆኑ ሀብት እያፈራችሁ የአካባቢው ተወላጆች ግን ከእናንተ ያነሰ ገቢ ነው ያላቸው፤ … ይህን ገቢ ያገኛችሁት በኛ መሬት ነው፤ የክልሉ ተወላጆች ባለመሆናችሁ ክልሉን ለቃችሁ ውጡ፤” በማለት በተለያዩ ጊዜያት ንብረታቸውን በመንጠቅና ለእስራት በመዳረግ እንግልት ሲፈፅሙባቸው ቆይተዋል፡፡ በተለይ መጋቢት 27 ቀን 2007 ዓ.ም አንድ የአካባቢው ተወላጅ ተገድሎ መገኘቱን ተከትሎ የወረዳው የፀጥታ ኃላፊ “ግድያው የተፈፀመው በአማራ ብሄር ተወላጆች ነው” በማለታቸው ግጭት ተቀስቅሶ፤  ሚያዚያ 9 ቀን 2007 ዓ.ም 85 አርሶ አደሮች ለእስራት መዳረጋቸውን፣ የአማራ ተወላጅ አርሶ አደሮች መኖሪያ ቤቶች እንዲቃጠሉ መደረጉን እንዲሁም የታሠሩትን የነዳጅ በሚል 300 ብር ከእያንዳንዳቸው በመቀበል እንደተለቀቁ ሰመጉ አጣርቻለሁ፤ ብሏል፡፡   በግጭቱ የአንድ ሰው ሕይወት ሲጠፋ 10 ሰዎች ላይ ቀላልና ከባድ የአካል ጉዳት መድረሱን፣ 99 የሳር ክዳን ቤቶችና 25 የቆርቆሮ ቤቶች በእሳት ተቃጥለው መውደማቸውን የዘረዘረው ሰመጉ፤ መኖሪያ ቤታቸው ለተቃጠለበቸውና በተለያዩ ቦታዎች ተበታትነው ለሚገኙ ዜጐች አስቸኳይ ሰብአዊ እርዳታ እንዲያገኙ ጠይቋል፡፡ መንግሥትም ለተፈጸመው የሰብአዊ መብት ጥሰት፣ የተጠናና የማያዳግም የመፍትሔ ርምጃ ከሕዝብ ጋር በመመካከር እንዲወሰድ የሰብአዊ መብቶች ጉባኤ አመልክቷል፡፡ 

    ያለፈውን የትግል ሂደቱን ሲገመግም የሰነበተው የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ፤ አዲስ የትግል ስልት መቀየሱን ጠቁሞ በአጭር ጊዜ ውስጥ ከግንባር ወደ አንድ ውህድ ፓርቲ ለመሸጋገር ማቀዱን አስታወቀ፡፡
የአራት ብሄር ተኮር ፓርቲዎች ግንባር የሆነው መድረክ፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ እያንዳንዱን የፓርቲ አባላት በማሳመን በውህደት አንድ ፓርቲ እንደሚፈጥር የጠቆሙት አቶ ጥላሁን፤ በቀጣዩ ምርጫም አንድ ፓርቲ ሆኖ ለውድድር ይቀርባል ብለዋል፡፡
መድረኩ በሁለት ቀን ጉባኤው፣ አባል ድርጅቶች በውህደት ጉዳይ ላይ ትኩረት ሰጥተው በመወያየት የውህደቱን ሂደት እንዲያፋጥኑ ከስምምነት ላይ የተደረሰ ሲሆን በየ6 ወሩ በሚካሄደው ስብሰባም የውህደቱ አጀንዳ እንደሚገመገም ኃላፊው ገልፀዋል።
ግንባሩ ባለፈው የግንቦት ወር ምርጫ ያጋጠሙ ተግዳሮቶችን መገምገሙን የጠቆሙት አቶ ጥላሁን፤ ገዥው ፓርቲ ምርጫውን ለማሸነፍ ማስፈራራትን፣ ጉልበትንና የገንዘብ አቅምን መጠቀሙን፣ እንዲሁም ምርጫው ህግና ስርዓትን በተከተለ መንገድ አለመከናወኑን ገምግሟል ብለዋል፡፡
ባለፈው ሳምንት ቅዳሜና እሁድ መድረኩ ባካሄደው ጉባኤ፣ እስካሁን ያከናወናቸው ፖለቲካዊ ትግሎች ያስገኙትን ውጤትና በቀጣይ ሊወሠዱ የሚገቡ አዋጭ የትግል ስልቶችን መገምገሙን የጠቆሙት የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው አቶ ጥላሁን እንደሻው፤ ግንባሩ የነበሩበትን ድክመቶች ለይቶ ማስመቀጡንና ከአሁን በኋላ የመንግሥትን ጫና ተጋፍጦ ወደ ህዝቡ በመውረድ፣ የተለያዩ አደረጃጀቶች ፈጥሮ ለመታገል መወሰኑን ተናግረዋል።
ባለፉት ምርጫዎች መድረኩ ጫናዎችን ተቋቁሞ ህዝቡን ለትግል በማደራጀትና በማንቀሳቀስ ረገድ የራሱ ድክመቶች እንደነበሩበት የገመገመ ሲሆን፤ ግንባሩ በምርጫው ሙሉ ኢትዮጵያን መወከል አለመቻሉም ተጠቅሷል፡፡ በአማራ ክልልና በአዲስ አበባ የመድረኩ እንቅስቃሴ በደካማነት ተገምግሟል ያሉት አቶ ጥላሁን፤ በትግራይና በኦሮሚያ በአንፃራዊነት ተሳትፎው እንደጨመረ ገልፀዋል። በጋምቤላ፣ ቤኒሻንጉል፣ አፋርና ሌሎች ክልሎች የመድረክ መዋቅር እንዳልተዘረጋ ሃላፊው ጠቁመው በቀጣይ በነዚህ ክልሎች መዋቅር ለማበጀት ግንባሩ እንደሚተጋ አስታውቀዋል፡፡
በሁለቱ ቀናት ጉባኤው ግንባሩ ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር ሊኖረው ስለሚገባ ግንኙነት መምከሩ የተገለፀ  ሲሆን ከመድረኩ አላማና ፕሮግራም ጋር የሚቀራረቡ ፓርቲዎችን ለመሳብ በሩን ከፍቶ መጠበቅ ብቻ ሳይሆን የተወሰነ ርቀት ሄዶ ለመጋበዝም እንዳቀደ ታውቋል፡፡

    ግሪን ኮፊ አግሮ ኢንዱስትሪ፤ የመንግሥት ይዞታ የነበረውን የቴፒ ቡና ተክል ልማት ድርጅት በ1 ቢ. ብር  ጠቅልሎ መግዛቱን አስታወቀ፡፡
ትናንት ረፋድ ላይ በሂልተን ሆቴል በተደረገው የሽ    ያጭ ውል ስምምነት፣ የፕራይቬታይዜሽንና የመንግሥት ልማት ድርጅቶች ተቆጣጣሪ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ በየነ ገ/መስቀልና የግሪን ኮፊ አግሮ ኢንዱስትሪ ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ አቶ ታደለ አብርሃ ውሉን ተፈራርመዋል፡፡
አቶ ታደለ በተለይ ለአዲስ አድማስ እንደገለጹት፣ ግሪን ኮፊ ከሁለት ዓመት ተኩል በፊት የቴፒ ቡና ተክል ልማት ድርጅትን ድርሻ 51 በመቶ በመያዝ፣ መንግሥት ደግሞ ቀሪውን 49 በመቶ ይዞ በሽርክና ለመሥራት ተስማምተው እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ 12 ሺህ ሄክታር ስፋት ያለውን የእርሻ ልማት፣ በ1 ቢሊዮን ብር እንደገለፁት አቶ ታደለ፤ የፊርማ ሥነ - ሥርዓቱ የተፈፀመው የዋጋውን 35 በመቶ፣ 265 ሚሊዮን ብር ባንክ አስገብተው ሲሆን ቀሪውን 65 በመቶ በ5 ዓመት ውስጥ ከፍለው ለማጠናቀቅ መስማማታቸውንም አስረድተዋል፡፡
12ቱ ሺህ ሄክታር መሬት ባረጁ የቡና ዛፎች የተሸፈነ ስለሆነ፣ ከ8-9 ሄክታሩን የተሻለ ምርት በሚሰጡ አዳዲስ ዝርያዎች መተካቱን ጠቁመው፣ ቀሪውም በየዓመቱ 1000 ያህል ሄክታር በአዲስ ምርታማ ዝርያ ይተካል ብለዋል፡፡ ከእርሻ ልማቱ አጠገብ የጋምቤላ ክልል ይዞታ የሆነውን 3ሺህ ሄክታር መሬት ክልሉን ጠይቀው ስለፈቀደላቸው አዲስ ፕሮጀክት ቀርፀው እንደሚያለሙትም አቶ ታደለ አክለው ገልፀዋል፡፡
ከእርሻው የሚገኘውን የቡና ምርት ኤክስፖርት በማድረግ 20 ሚሊዮን ዶላር እንደሚገኝ የጠቀሱት ባለሀብቱ፤ እርሻው ለማር ምርት አመቺ በመሆኑ በዓለም ተወዳጅ የሆነውን ኮፊ ሀኒ የተባለ የማር ዓይነት በአነስተኛ መሳሪያ እያዘጋጁ ወደ ውጭ ሲልኩ ቆይተዋል፡፡ አሁን በብዛት (50 እና 60 ኮንቴይነር ኮፊ ሀኒ) ወደ ውጭ በመላክ ከ4-5 ሚሊዮን ዶላር ለማግኘት ፋብሪካ እየገነቡ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
የቴፒ ቡና እርሻ ልማት በረከት ይህ ብቻ አይደለም፡፡ የተለያዩ ቅመማ ቅመሞች እያመረቱ ለመላክ አቅደዋል፡፡ ብዙም ባይሆን በኢትዮጵያ ውስጥ ፓልም ኦይል የሚገኘው በቴፒ እርሻ ልማት ብቻ እንደሆነ የጠቀሱት አቶ ታደለ፤ ለሙከራ ከማሌዢያና ኢንዶኔዢያ የተለያየ ዝርያ አምጥተው በ120 ሄክታር መሬት ላይ በመትከል ምርቱ ደርሶ አይተውታል፡፡ በአነስተኛ መሳሪያ እያዘጋጁ በየወሩ አንድ መኪና ዘይት ለተለያዩ ድርጅቶች የሚያቀርቡ ሲሆን፤ ወደ ዘይት ከመለወጡ በፊት ያለውን ድፍድፍ፣ የሳሙና ፋብሪካዎች በጥሩ ዋጋ በሰልፍ እንደሚገዙና በየወሩ አንድ መኪና ድፍድፍ እንደሚሸጡ ተናግረዋል፡፡ የፓልም እርሻውን ወደ 10,000 ሄክታር ለማሳደግ የገንዘብ ድጋፍ የሚያደርግ ኩባንያ ማግኘታቸውን ጠቅሰው፣ የእርሻ መሬት ለማግኘት ከክልሉ ጋር እየተነጋገሩ መሆኑንም አቶ ታደለ ገልፀዋል፡፡
በቴፒ እርሻ ልማት ውስጥ ባሉ 6 እርሻዎች፣ 16ሺ ሰራተኞች ተቀጥረው እንደሚሰሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡

Saturday, 08 August 2015 09:38

የዘላለም ጥግ

(ስለ ስኬት)
ውድቀት አማራጭ አይደለም፡፡ ሁሉም ሰው ስኬትን መቀዳጀት አለበት፡፡
አርኖልድ ሽዋዚንገር
ያለ አንተ ይሁንታ ማንም ሰው የበታችነት ስሜት እንዲሰማህ ማድረግ አይችልም፡፡
ኢሊኖር ሩስቬልት
ስኬት የዕድል ጉዳይ ነው፡፡  ያልተሳካለትን ማንኛውንም ሰው ጠይቁ፡፡
ኢርል ዊልሰን
አሸናፊው ሽንፈትን ይፈራል፡፡ የተቀረው ደግሞ ማሸነፍን ይፈራል፡፡
ቢሊ ዣን ኪንግ
ውድቀት በራሱ ከተማርንበት ስኬት ነው፡፡
ማልኮም ፎርብስ
የስኬት ምስጢሩ ሃቀኝነት ነው፡፡
ዣን ጊራውዶክስ
ተፈጥሮአችን ነው፡- የሰው ልጆች ስንባል ስኬትን እንወዳለን፤ ስኬታማ ሰዎች ግን እንጠላለን፡፡
ካሮት ቶፕ
ስኬትን መቀዳጀቴ ብቻ በቂ አይደለም - ሌሎች መውደቅ አለባቸው፡፡
ዴቪድ ሜሪክ
ስኬት ሁሉንም ነገር አይደለም፤ ነገር ግን ሰውን ቀጥ ብሎ እንዲቆም ያደርገዋል፡፡
ሊሊያን ሄልማን
ስኬት ምንም ምስጢር የለውም፡፡ የዝግጅት፣ ተግቶ የመስራትና ከውድቀት የመማር ውጤት ነው፡፡
ኮሊን ፓውል
ህልሞችህን ገንባ፤ ያለበለዚያ ሌሎች ህልማቸውን እንድትገነባላቸው ይቀጥሩሃል፡፡
ፋራህ ግሬይ
ህይወት ራስህን የመፈለግ ጉዳይ አይደለም፤ ራስህን መፍጠር ነው፡፡
ጆርጅ በርናርድ ሾው
ደስታ ሁልጊዜ ክፍት እንደነበር ባላሰብከው በር ያጮልቃል፡፡
ያልታወቀ ሰው

Saturday, 08 August 2015 09:33

የግጥም ጥግ

 ላንቺ
(በ.ሥ)
እንዳገው ጃንጥላ፤ ሰማይ ተሽከርክሮ
እንደ ጎፋ ፈረስ፤ መሬቱ ደንብሮ
ሁሉ ሲያዳልጠኝ
ሁሉ ሲያዳክመኝ
ቀሚስሽን ይዤ፤ መትረፌ ገረመኝ፡፡

ኤልሻዳይ ምኞት
(በ.ሥ)
እንደ ድሮ ቀሚስ፤ መሬት እየጠረግሁ
ኮቴሽን ምድር ላይ፤ ተግቸ እየፈለግሁ
እንደ ጉም
ሳዘግም
እንደ ሰርዶ ስሳብ
ባካል ብታመልጭኝ፤ ደረስኩብሽ ባሳብ
መች ሊያግደኝ በሩ፤ መች ሊገታኝ መስኮት
በዝግ በርሽ ገባሁ፤ ልክ እንደ መለኮት
ላንዲት መስቲካ ሻጭ ህጻን
(በ.ሥ)
በደብተርሽ ምትክ
ትንሽ ሱቅ ታቅፈሽ
ካልፎሂያጅ እግር ስር፤ እንደ ድንቢጥ ከንፈሽ
ጋሼ ግዙኝ ስትይ፤ ኣንጋጠሽ ወደ ላይ
ለጉድ ተጎልቸ፤ ምታረጊውን ሳይ
ራሴስ ይታመም፤ ምላሴን ምን ነካው
ግራዋ ይመስል፤ መረረኝ ማስቲካው፡፡
ኣፈር ጠጠር ለብሶ፤ በዶዘር ተድጦ
መስኩ ከነጎርፉ
ሰማይ ከነዶፉ
ለጌቶች ተሽጦ
ኣተር ነው እያሉ፤ ኣፈር ዘግኖ መፍጨት
ገነት ነው እያሉ፤ መስክ ላይ መፈንጨት
ጠበል ነው እያሉ፤ ተጎርፉ መራጨት
ይህንን ማን ሰጦሽ
ገና በልጅነት፤ ልጅነት ኣምልጦሽ፡፡
በምቢልታ በዋሽንት፤ በከበሮ ታጥሮ
በክራር ተማግሮ
በቆመ ከተማ
እምባሽ ቅኝት የለው፤ ለሰው ኣይሰማ፡
ጠዋት የፎከረ፤ ቀትር ላይ ሲረታ
ዛሬ ዝሎ ሲወድቅ፤ ትናንት የበረታ
ኑሮን ያህል ሸክም፤ ያላንቀልባ ሲያዝል፡፡
ምን ጸጋ ለብሶ ነው፤ ትከሻሽ የማይዝል፡፡