Administrator

Administrator

• ባለፈው ዓመት በትራፊክ አደጋ የ448 ሰዎች ህይወት አልፏል
• 22 ተሳፋሪዎች፣ 19 አሽከርካሪዎች፣ የተቀሩት እግረኞች ናቸው

  ለአሽከርካሪዎች የወጣው ደንብ፤ ማንኛውም ሹፌርም ሆነ ከጐን የተቀመጠ ተሳፋሪ፤ የአደጋ መከላከያ ቀበቶ (Seat belt) ሳያስር በጉዞ ላይ ከተገኘ 120 ብር እንደሚቀጣ የሚጠቁም ሲሆን ለሁለቱም ወገን ተጠያቂው አሽከርካሪው ነው ይላል፡፡ እስካሁን ግን ህጉ ከአሽከርካሪዎች በቀር ተሳፋሪ ላይ ሳይተገበር ቆይቷል፡፡ ተሳፋሪዎች እንኳንስ ቀበቶ ሊያስሩ ቀርቶ አብዛኞቹ መኪኖች የአደጋ መከላከያ ቀበቶ ከእነአካቴው የላቸውም፡፡ ተሳፋሪው ቀበቶ የማሰር ልማድ ቢያዳብር ኖሮ፣ በተለያዩ ጊዜያት በሚደርሱ በርካታ አሰቃቂ አደጋዎች ላይ የሟቾችን ቁጥር መቀነስ ይቻል ነበር ይላል - ፖሊስ፡፡
ተወዳጇ አርቲስት ሰብለ ተፈራም በዘመን መለወጫ ዕለት፣ መስከረም 1 ቀን 2008 ዓ.ም በደረሰባት ድንገተኛ የመኪና አደጋ ወቅት ቀበቶ አስራ ቢሆን ኖሮ የተሻለ የመትረፍ ዕድል ሊኖራት ይችል ነበር ተብሏል፡፡
የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን እንደገለፀው፤ ትራፊኮች የአሽከርካሪን ብቻ ሳይሆን ከጐን የሚቀመጡ ተሳፋሪዎችንም ቀበቶ እንዲያስሩ ቁጥጥር አለማድረጋቸው  ስህተት ነው፡፡
የኮሚሽኑ የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ ኢንስፔክተር አሰፋ መዝገቡ ስለጉዳዩ ተጠይቀው ሲመልሱ፤ “በወቅቱ ቀበቶ የማሰርን ጉዳይ በአሽከርካሪው ላይ ብቻ ያጠበቅነው አብዛኞቹ መኪኖች ከእርጅና ጋር በተያያዘ ቀበቶ ስላልነበራቸው ነው” ብለዋል፡፡
ዘንድሮ ግን ህጉ በጥብቅ ተግባራዊ መደረግ እንደሚጀምር የጠቁሙት ኢንስፔክተሩ፤ አሽከርካሪዎች በህጉ መሰረት የተሳፋሪውንም ቀበቶ አሁኑኑ እንዲያስተካክሉ አሳስበዋል፡፡
“ህይወትን ከአደጋ መከላከል ለራስ ነውና በተለይ በግል ተሽከርካሪ የሚጠቀሙ ግለሰቦች ቀበቶ ማሰርን ካሁኑ መላመድ ይኖርባቸዋል” በማለት ኢንስፔክተሩ ምክራቸውን ለግሰዋል፡፡
ባለፈው ዓመት (2007 ዓ.ም) በአዲስ አበባ በትራፊክ አደጋ ምክንያት 448 ሰዎች ህይወታቸው ያለፈ ሲሆን ከነዚህ ውስጥ 22ቱ ተሳፋሪዎች፣ 19ቱ አሽከርካሪዎች፣ የቀሩት እግረኞች እንደነበሩ የትራፊክ ፖሊስ መረጃ ያመለክታል፡፡


Saturday, 19 September 2015 09:02

የታሪክ ባህሪያትና ዓላማ

(በፕ/ር መስፍን “አዳፍኔ” መነሻነት

   በአማርኛ ቋንቋ ከሚጽፉ እጅግ ጥቂት ኢትዮጵያዊያን ምሁራን መካከል አንጋፋው ምሁር ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም አንዱ ናቸው፡፡ ፕሮፌሰሩ በሚጽፏቸው በሳል ጽሁፎችና በሚያነሷቸው አዳዲስ ጉዳዮች የምሁርነትን ልክ አሳይተውናል ብል ያጋነንኩ አይመስለኝም፡፡ በተለይ ባለፉት አስር ዓመታት በየሁለት አመቱ ልዩነት ማለት ይቻላል በተከታታይ ግማሽ ደርዘን የሚሆኑ መጽሀፍትን አስነብበውናል፡፡ ባለፈው ዓመትም (በ2007) ‹አዳፍኔ፡ፍርሃትና መክሸፍ› በሚል ርዕስ አዲስ መጽሀፍ አሳትመዋል፡፡
‹አዳፍኔ› ፕሮፌሰሩ በ2005 ዓ.ም ያሳተሙት ‹መክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክ› መጽሀፋቸው ተከታይ ክፍል ነው ማለት ይቻላል፡፡ ለዚህም ሁለት አስረጂዎችን ማቅረብ ይቻላል፡፡ አንደኛው ከጭብጥ አኳያ ብዙ ተመሳስሎሽ አላቸው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ ‹አዳፍኔ› ከያዛቸው አስር ምዕራፎች ውስጥ ሶስቱ (ይህም የመጽሀፉን ዘጠና ስድስት ገጾች ወይም 40 በመቶ ያህል ይሸፍናል ማለት ነው) በ‹መክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክ› ላይ በተለያዩ ጸሀፍት ለተሰነዘሩ ትችቶች ምላሽ የሰጡበት (በመጽሀፉ እንደተገለጸው የ‹ ትችቶች ትችት›) ነው፡፡
በዚህ መጣጥፍ አዘጋጅ አተያይ፤የመጽሀፉ ዋነኛ መገለጫዎች (መልኮች) ሁለት ናቸው፤እነዚህ ሁለት መገለጫዎችም የመጽሀፉ ውበቶች ናቸው፡፡ የመጀመሪያው መጽሀፉ በይዘቱ ሰፋ ያለ መሆኑ ነው፤ከዚሁ ጋር የተያያዘው ሁለተኛው፣ መጽሀፉ በቅርጹና አቀራረቡ የራሱ የሆነ አዲስ ቀለም ይዞ መምጣቱ ነው፡፡ አዳፍኔ ፍርሃትና መክሸፍ እጅግ በርካታ ጉዳዮችን ይዳስሳል፤ታሪክ፣ባህል፣ስልጣንና አገዛዝ (ፖለቲካ)፣ኢኮኖሚክስ፣ስነመንግስትና አስተዳደር (አገር፣ህዝብና መንግስት)፣ሀይማኖት፣ትምህርትና ዕውቀት እንዲሁም ዕውነት፣ ስነ-ልቦና፣ፍልስፍና እና በሌሎች የጥናት ዘርፎች ዙሪያ የሚሽከረከሩ ጽንሰ ሀሳቦችን ያነሳል፡፡ ሌላው የመጽሀፉ መልክ ለጥናትና ምርምር፣ለጥልቅ ውይይትና ክርክር የሚጋብዙ ሀሳቦችን ማንሳቱና በዚሁ በተቃኘ አቀራረብ መዘጋጀቱ ነው፡፡
ወጣቱ ደራሲና የታሪክ ተመራማሪ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት፤ በመክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክ መጽሀፍ ዙሪያ ያለውን አተያይ ከሁለት አመታት በፊት ገደማ በአንድ መጣጥፉ አስነብቦናል፡፡ ዲያቆን ዳንኤል በመጣጥፉ ካነሳቸው በርካታ ቁም ነገሮች አንዱ የክሽፈት ታሪክ እንጂ የታሪክ ክሽፈት የሚባል ሊኖር አይችልም የሚለው አንዱ ነው፡፡ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም፤ በአዳፍኔ ፍርሃትና መክሸፍ መጽሀፋቸው ‹የትችቶች ትችት› በሚለው ምዕራፍ ውስጥ ለዚህ መልስ ሰጥተዋል፤ ነገር ግን መልሱ አጥጋቢ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡  መልስ የተሰጠበት አግባብ የተደራጀና ግልጽ አይደለም፡፡ እንዲያም ሆኖ የአዳፍኔ ዋነኛ ጭብጥ በክሽፈት ታሪክና በታሪክ ክሽፈት ዙሪያ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ነገር ግን ሀሳቦቹ እዚህም እዚያም ተበታትነው የቀረቡ በመሆኑ በጉዳዩ ላይ አንባቢ የጠራ ግንዛቤ እንዳይኖረው ያደርጋል የሚል ስጋት አለኝ፡፡
በዚህ መጣጥፍ አቅራቢ እምነት፤ የክሽፈት ታሪክ እና የታሪክ ክሽፈት የሚሉት ሁለት ሀሳቦች ብዙ ጉዳዮችን ያዘሉ በመሆናቸው በጥልቀት መታየት አለባቸው፡፡ በመሆኑም  አዳፍኔ ፍርሃትና መክሸፍ ስለ ክሽፈት ታሪክና ስለ ታሪክ ክሽፈት ያነሳቸውን ሀሳቦች በማሰባሰብ ለማቅረብ ተሞክሯል፡፡ መጽሀፉ ከአደረጃጀት አንጻር በዚህ ሁኔታ ቢቀርብ መልዕክቱን በይበልጥ ለመረዳት ያስችላል፤በመጽሀፉ በተነሱት ጉዳዮች ላይ በአንባቢያን የሚቀርቡ የውይይትም ሆነ የክርክር ሀሳቦች ቅርጽ እንዲይዙ ለማድረግም ያግዛል፡፡
የታሪክ ምንነት፣ባህሪያትና ዓላማ
የታሪክ ፍልስፍና ዘይቤ አባት በመባል የሚታወቀው አውግስ ሚኖስ፤ የታሪክ ምንነትና ዓላማን ሲገልጽ እንዲህ ይላል፡-
ታሪክ መንግስት መቆሙንና መፍረሱን፣ ህዝቦች ማደጋቸውንና መውደቃቸውን ያትታል፡፡ ይህም የሚሆንበት ምክንያት አምላክ ባቀደው መሰረት የሰውን ዘር ወደ እውነተኛው ብርሃን ለመምራትና ለማዳን ሲል ነው፡፡
የፕሮፌሰር መስፍን የታሪክ ምንነትና ዓላማ አረዳድም ከአውግስ ሚኖስ ጋር በይዘቱ አንድ ነው፣ቋንቋው ቢለወጥም፡፡ እንደፕሮፌሰሩ አገላለጽ ታሪክ ማለት፡-
“…..ለአንድም ሰኮንድ የማያቋርጥ የኑሮና የአኗኗር ጅረት ነው፡፡ ……..ታሪክ የአንድ ህዝብ የስራ መዝገብ ነው፡፡” (ገጽ 98-99)
የታሪክ ዓላማ ደግሞ ህዝቡ ያለፈውን ዘመን ከፍታና ዝቅታ አስታውሶ፣ የአሁኑ ትውልድ ካለፈው ትውልድ በጎ ጎኖች ትምህርት ወስዶ፣ ከችግሮቹ ተምሮ፣ በኑሮው መሻሻል እንዲያሳይ ማድረግ ነው (ገጽ 28፣29 )፡፡  
በአጠቃላይ፡- ታሪክ ማለት የትናንት ዕውነትን (በጎም ሆነ በጎ ያልሆኑ) መመርመር ነው፡፡የታሪክ ዓላማ የሰው ልጅ የትናንት በጎ ተግባራቱን አዳብሮ፣ከስህተቱ ደግሞ ተምሮ የዛሬና የነገ ህይወቱን እንዲያቀና ማድረግ ነው፡፡ በዚህም አውግስ ሚኖስ የታሪክን አስፈላጊነትና ዓላማ ከመለኮታዊ ሀይል ዓላማ ጋር ያዛምደዋል፡፡ በዚህም የታሪክ ዓላማ የፈጣሪ አላማ ነው፡፡
ስለታሪክ ባህሪያት
በግሌ የታሪክ ባህሪ ከአምላክ ባህሪ ጋር ይመሳሰልብኛል፡፡ ታሪክ አምላካዊ ባህሪዎችን ሁሉ ይወርሳል፡፡ ታሪክን ከአምላካዊ ባህሪ ጋር ለማንጸር ያደረግሁት ጥረት ያልተመቻቸው የአምላክን ባህሪ የማያውቁ ናቸው ባይ ነኝ፡፡ ለመሆኑ የአምላክ ባህሪያት ምንድናቸው? የታሪክ ባህሪያትስ ?
በመሰረቱ የአምላካዊነት መሰረት ሀቅ ነው፤የታሪክ መሰረቱም እንዲሁ ሀቅ (እውነት) ነው፡፡ ፈጣሪ የሰው ልጆችን ጨምሮ በአጠቃላይ በፍጡራን ላይ ፍጹም ስልጣን አለው፤ታሪክም ይህ ስልጣን አለው፡፡ የፈጣሪ ዓላማ የሰው ልጆች ሁሉ በቀና መንገድ እንዲያልፉ ማስተማር ነው፤የታሪክ ዓላማም እንደዚሁ ነው፡፡ ወደር የለሽ ትዕግስትና ሆደ-ሰፊነት አምላካዊ ባህሪ ነው፤ዓላማውም ሰዎች በራሳቸው ከጥፋት መንገድ እንዲታቀቡ፣ካለፈው ስህተታቸው እንዲታረሙ ጊዜ መስጠት ነው፡፡ የታሪክ መንገድም ይህ ነው፡፡ በመሰረቱ ዕውነትን (ታሪክን) መበረዝ ወይም ማጥፋት የሚቻል ሊመስለን ይችላል፡፡ መሪዎችም ይህን ለማድረግ የቻሉ ሊመስለን ይችላል፡፡ ግን በጥልቀት ከመረመርነው አልቻሉም፡፡ የፈጣሪን ትዕግስት ዓላማ ያልተረዱም በስህተት ላይ ስህተት እየፈጸሙ፣ በመጨረሻም ከነጭራሹ የፈጣሪን ስልጣን ሲመኙ፣ሲብስም ህልውናውንም ሲክዱ፣መቀበሪያቸውን ጉድጓድ እየማሱ እንደሆነ ሳይታወቃቸው፣የትዕግስቱ መብዛትም በቆፈሩት ጉድጓድ እንዲቀበሩ ያደርጋቸዋል፡፡ የታሪክም መንገድ ይህ ነው፡፡ ታሪክ ከስህተት ለመማር እድል ይሰጠናል፡፡ ይህን ማድረግ ያልቻሉ ግን በቆፈሩት ጉድጓድ ይቀበራሉ፡፡ በታሪክ ማህደር እንደተዘከረው፤ በታሪክ ላይ የዘመቱ ሁሉ መጨረሻቸው መጥፋት ነበር፡፡ በእርግጥም በዘመናት ሂደት ያለፉ፣ታሪክ ላይ ያመጹ አገዛዞችና ነገስታት አነሳስና አወዳደቅን ለመረመረ ይህ ይገለጥለታል፡፡ ታዲያ የፈጣሪ የቅጣት በትር ፍጹም ፍትሃዊ እንደሆነው ሁሉ የታሪክ ቅጣትም ጊዜ ወይም ቦታ የማይቀይረው፣ ለማንም የማይወግን ፍጹም ፍትሃዊ ነው፡፡ ትናንትም ይሁን ዛሬ በታሪክ ላይ ያመጹ ሁሉ በጥፋታቸው ልክ ተቀጥተዋል፤ነገም እንዲሁ እንደሆነ ይቀጥላል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን በአንድ ዓመት በዓል ወቅት፣ አንድ አባት ልጁን ይዞ ወደ አንድ ሆቴል ቤት ጎራ ይላል፡፡ ለልጁ ለስላሳ ለሱ ነጭ አረቄ አዞ መጠጣት ይጀምራል፡፡ ያን አረቄ በላይ በላዩ ሲጨማምርበት ወደ ሞቅታው ተጠጋ፡፡
አረቄውን ልትቀዱለት የምትመላለሰው ቆንጆ ሴት እየተሞናደለችና ሽንጧን እያተራመሰች ስትመላለስበት ዐይኑ ከሱዋ አልላቀቅ አለ፡፡
“አንቺም ጠጪ፣ ለኔም አምጪ” ማለት ጀመረ፡፡ ቆንጆይቱም መጎንጨት ጀመረች፡፡ ሞቅ አላቸው ሁለቱም፡፡ ተጠቃቀሱና ተራ በተራ ወደ ጓዳ ገቡ፡፡
ይህ ሁሉ ሲሆን ልጅየው ለስላሳውን ትንሽ በትንሽ እየጠጣ ሲያስተውል ቆይቷል፡፡ አባቱ ሳይመለስ ብዙ የቆየ ስለመሰለው፣ ወደሄደበት አቅጣጫ ሄደ፡፡ አንድ ክፍል ውስጥ ተኝተዋል ለካ! ደንግጦ ቶሎ ወደ ቦታው ተመልሶ ተቀመጠ፡፡
አባትዬው ተመለሰ፡፡ አንድ ደግሞ ሂሳብ ከፈለና ወጡ፡፡
ቤት ደርሰው የሚበላ ቀርቦ በልተው እንደጨረሱ ጨዋታ መጣ፡፡
እናት - “እሺ ዙረታችሁ እንዴት ነበር?” አለች ወደ ልጁ እያየች፡፡
ልጁም - “መጀመሪያ ወደ ሆቴል ሄድን”
እናት - “እሺ?”
ልጅ - “አባዬ አረቄ አዘዘ፡፡ ለእኔ ለስላሳ ሰጠኝ”
እናት - “ከዛስ?”
ልጅ - “ከዛማ አባዬ ደጋገመ”
አባት - “በቃህ እንግዲህ! ወሬ አታብዛ”
እናት - “ተወው እንጂ ይንገረኝ”
ልጅ - “ከዛ የምታስተናግደንን ሴትዮ ጋበዛት”
እናት - ጉጉቷ ጨመረ፡፡ “እሺ ከዛስ?”
ልጅ - “ከዛ ሴትዮዋ ወደ ጓዳ ሄደች”
አባት - “አንተ ልጅ! ሁለተኛ ሽርሽር አልወስድህም!”
እናት - “ተወው ይጨርስልኝ!”
ልጅ - “ከዛ አባዬም ወደ ውስጥ ገባ”
እናት  - በችኮላ፤ “እሺ? ከዛስ?”
ልጅ - “አባዬ ሲቆይብኝ የት ሄደ ብዬ ወደዛ ሄድኩ”
እናት - “ከዛስ?”
ልጅ - “ከዛ አይቼ ተመለስኩ”
እናት - “ምን አየህ?”
ልጅ - አመነታ!
እናት ሁኔታው ገብቷት - “አይዞህ ንገረኝ”
ልጅ፤ እናቱንም አባቱንም አየና፤
“ያየሁትማ አንቺና ዘበኛችን እንደምትተኙት ዓይነት ነው!” አለ፡፡  
*           *          *
የሌላውን ዐይን ጉድፍ ለማሳየት ከመጣጣር የራስን ጉድፍ አስቀድሞ ማየት፣ አስቀድሞ ማውጣት ታላቅ ብልህነት ነው፡፡ ሁሉም ለስህተት በሚጋለጥበት ሁኔታ ውስጥ እያሉ አንዱ ባንዱ ላይ ጣቱን ቢቀስር ውጤቱ ሲቀሳሰሩ መዋል ነው፡፡ በንጉሡ ዘመን የወጣ አንድ ካርቱን ስዕል ባሳየው ምስል፣ ባለስልጣናት ወይም ሚኒስትሮች በትልቅ የኮንፈረንስ ጠረጴዛ ዙሪያ ተቀምጠዋል፡፡ እያንዳንዳቸው፣ አንዱ ባንዱ ላይ በሌባ ጣቱ ይጠቁማል፡፡ ማንም በማንም ላይ ጣቱን ሳይቀስር የሚታይ የለም፡፡ ሁሉም ጥፋተኛ ነው እንደማለት ነው፡፡ ግምገማዎች ምን ያህል ሀቀኛ ናቸው? ስህተትን ለማረም የሚያስችል ምን ያህል ቅን ልቦና አለ? የተገመገሙት ሁሉ እርምጃ ይወሰድባቸዋልን? ያንንስ ማን ይቆጣጠራል? ግምገማ ከእከክልኝ ልከክልህ ነፃ ነውን? ከየአንዳንዱ ግምገማ ምን ያህል ተምረናል? የሚገመገምና የማይገመገም፣ ይነኬና አይነኬ ሰው የለምን? ግምገማ ራሱ መገምገም የለበትምን? ባለፈው ዘመን የኮሚቴ መብዛት ትልቅ ችግር ሆኖ ተሰበሰቡና አሉ፤ ይህንኑ የሚያጠና ኮሚቴ አቋቁመው ተለያዩ! ሀገራችን አባዜዋ ብዙ ነው፡፡ አንድ ተገምጋሚ፤ ስለሀገራችን የስድስት መስመር የህዝብ መዝሙር ፃፍ ተብሎ አሥር ገፅ ያህል የዓላማ ፅሁፍ ተሰጠው፡፡ ቢለው ቢለው ያን ሁሉ ዓላማ በስድስት መስመር ማጠናቀቅ እንደማይመች ታወቀውና፤
“እንኳን ስድስት መስመር፣ መቶም አይበቃሽ እንደው በደፈናው፣ ዕንቆቅልሽ ነሽ    !”ብሎ ደመደመ ይባላል፡፡
በግምገማ ንፍቀ - ክበብ ዋና ጉዳይ የሚሆነው አዎንታዊነት (Positivism) ነው፡፡ በአዎንታዊነት ውስጥ ተስፋ አለ፡፡ በአሉታዊነት ውስጥ ጨለምተኝነት ነው ያለው፡፡ ሰውን ማነፅ አገርን ማልማት ነው፡፡ ሙያን ማክበር ሙያተኛን ማበልፀግ ነው! ይህም አዎንታዊነት ነው፡፡ መንገድ መሥራት ባለሙያ ይፈልጋል፡፡ ሀዲድ መዘርጋት ባለሙያ ይፈልጋል፡፡ ባቡር ማስኬድ ባለሙያ ይፈልጋል፡፡ በባቡር መሄድ ደግሞ ስልጣኔ ይፈልጋል፡፡ የባቡሩን መነሻና መድረሻ ደግሞ መረጃ ጆሮ ነው የሚፈልገው፡፡ አዎንታዊነት ውስጥ ሟርትን እንዳንከት መጠንቀቅ ያንድ የሰለጠነ ህዝብ ብልህነት ነው፡፡ ብዙ የሰራን እያስመሰልን ውስጡ ውስብስብ መክተት አሉታዊነት ነው! አገር ገንዘብ ይኖራት ዘንድ ሁለት ሶስት ያለው ቢላ መጠቀምም አሉታዊነት ነው፡፡ አገር አቀናለሁ ብሎ ደፋ - ቀና የሚለው ዜጋ፣ በንፁህ ስሜት፣ በቀና ልቦና ሲወድቅ ሲነሳ፤ ሌላው ወገን በአጭር - አቋራጭ (Short-cut)፣ አየር ባየር ከባለሥልጣን በመመሳጠር፣ በቀጭን ቢሮክራሲያዊ ትዕዛዝ ወዘተ… ሀብቱን ሲያከማችና ፎቁን ሰማይ ሲያስነካ ማየት ዘግናኝ ነው! ጉዳይ አስፈፃሚ የሆነ ባለዘመድ (መንገድ አዋቂ) ከባለ ጉዳዩ በላይ የሚያገኝበት አገር ውስጥ ለአስተዋይ ሰው ከኮሜዲው ትራጀዲው ማየሉ አይገርምም፡፡ በየቀኑ ነገር የባሰበት ዜጋ፤ “ደረቁ ከበደኝ እያልኩ፣ እርጥብ ትጨምርበታለች” የሚለው ለዚህ ነው! ከዚህ ያውጣን!!

    በአሁኑ ወቅት እጅግ አሳሳቢ እየሆነ ለመጣው የኩላሊት ህመም መፍትሄ ይሆናል በሚል በዘውዲቱ ሆስፒታል ግቢ ውስጥ በመገንባት ላይ ለሚገኘው የህክምናና የዕጥበት ማዕከል የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ወጣቶች ፎረም ተካሄደ፡፡ ትናንት በግሎባል ሆቴል በተካሄደው በዚህ ፕሮግራም ላይ ለማዕከሉ ግንባታ የሚረዳ ገቢ ለማሰባሰብ በማህበረሰቡ ላይ በጎ ተፅዕኖ የሚፈጥሩ የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች፣ ታዋቂ ሰዎች፣ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎችና የመንግስት ባለስልጣናት ተገኝተዋል፡፡

 የአርቲስት ሰብለ ተፈራ( እማማ ጨቤ) የቀብር ስነስርዓት በመንበረ ፀባኦት ቅድስት ስላሴ ቤተክርስቲያን የውጭጉዳይ ሚኒስቴር ዶር ቴዎድሮስ አድሃኖም ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት ታዋቂ ግለሰቦች  አድናቂዎቿ በተገኙበት የቀብር ስነስርዓቷ ተፈፀመ፡፡
ለወዳጅ ዘመዶቿ እንዲሁም አድናቂውቾ መፅናናትን እንመኛለን፡፡

Friday, 11 September 2015 10:18

የፀሐፍት ጥግ

  (ስለ ሳንሱር)
ማንኛውንም ዓይነት ሳንሱር አበክሬ እቃወማለሁ፡፡
ዶን ጆንሰን
ባኮሪያ ምንም መንግሥታዊ ሳንሱር የለም፡፡
ቦንግ ጁን-ሆ
ሳንሱር ልክ እንደ ችሮታ ከቤት መጀመር አለበት፡፡ ነገር ግን ከችሮታ በተለየ መልኩ እዚያው ማዎም ይኖርበታል፡፡
ክላሬ ቡዝ ሉሴ
ለዕድገት የመጀመሪያው አስፈላጊ ሁኔታ የሳንሱር መወገድ ነው፡፡
ጆርጅ በርናርድ ሾው
በብዙ የዓለም ክፍሎች ስላለው ሳንሱር እጨነቃለሁ፡፡
ጂማ ዋልስ
ዓለም ዘላለማዊ የሚላቸው መፃህፍት የራሳቸውን ውርደት የሚያጋልጡ ናቸው፡፡
ኦስካር ዋይልድ
ሰውን ዝም ስላሰኘኸው ለወጥከው ማለት አይደለም፡፡
ጆን ሞርሌይ
መፃህፍት ታግደው አይቀሩም ሃሳች ዘብጥያ አይወርዱም፡፡
አልፍሬድ ዊትኔይ ግሪስዎልድ
ምንጊዜም መፃህፍት ሲቃጠሉ ሰዎችም በመጨረሻ መቃጠላቸው አይቀርም፡፡
ሁንሪክ ሄይን
ብዙ ጊዜ ሳንሱር አድራጊው ከመድረሱ በፊት ራሳችንን ሳንሱር እናደርጋለን፡፡
ስፓይክ ሊ-
ማንንም ለማስደሰት ብዬ ራሴን ፈፅሞ ሳንሱር አላደርግም፡፡
ናታሊያ ኪልስ
የሰዎችን ህልም ሳንሱር ማድረግ አትችልም፡፡
ሮቢን ሂችኮክ
ዘፋኙን እንጂ ዘፈኑን መከርቸም አትችልም፡፡
ሃሪ ቤላፎንቴ

      ያለፈው የስራ ዘመናችን መጠነኛ ነበር፡፡ የስራ እንቅስቃሴዎቹ ደህና ናቸው፡፡ ያለፉት አመታት ላይ አጥልቶ የነበረው የስራዎች መጓተት በዚህኛውም ላይ አጥልቶ ነበረ፡፡ በዚህ ምክንያት እንቅስቃሴያችን መጠነኛ ነበር፡፡
በቀጣይ አመት ግን ብሩህ ተስፋ እናያለን፡፡ በኢህአዴግ ጉባኤ ላይ እንደተገለፀው፤የመልካም አስተዳደር ችግር ተቀርፎ፣ ለሀገር ውስጥ ባለሀብቶች የማጠናከሪያ ድጋፍ እየተደረገ ይሄዳል የሚል እምነት አለን፡፡ የሪል እስቴት ግዢና ሽያጭ ህግም ይፀድቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ እሱም በሪል እስቴት ላይ አዎንታዊ አስተዋፅኦ ይኖረው ይሆናል፡፡ በአጠቃላይ መጪው ጊዜ ብሩህ ነው ብሎ ማሰብ ይቻላል፡፡ ለኢትዮጵያ ህዝብም ሰላም፣ ጤናና፣ ፍቅር ይብዛለት!

    ያለፈው ዓመት ጥሩ የሚባሉ ስራዎችን የሰራሁበት ዓመት ነው፡፡ ሁለት ልጓሞቼን (ወርቅ በወርቅና፣ ሄሮሺማን) በቪሲዲ፣በዲቪዲ ለተመልካች ያቀረብኩበት ዓመት ነበር፡፡ የህዳሴውን ዋንጫም ይዘን ኢትዮጵያን የዞርኩበት ዓመት ነው፡፡ ዘመናዊ  ሲኒማ ቤትና የስፖርት ላውንጅ ግንባታም የጀመርኩበት ዓመት ነው፡፡ በብዙ መልኩ ለኔ ስኬታማ ዓመት ነበር፡፡
ቦሌ አካባቢ ያስገነባሁት ሲኒማ ቤት፣በአዲሱ ዓመት ሥራ ይጀምራል፡፡ መደበኛ ስራዎቹ እንደተጠበቁ ሆነው ሌላ አዲስ ፊልም የመስራት እቅድም አለኝ፡፡

   አንጋፋዋ ድምፃዊት አስቴር አወቀና ማዲንጎ አፈወርቅ ለአዲስ ዓመት ዋዜማ ዛሬ ምሽት  በጊዮን ሆቴል የሙዚቃ ኮንሰርት ያቀርባሉ፡፡ ከቀኑ 10፡30 ላይ የኮንሰርቱ መግቢያ በሮች እንደሚከፈቱ አዘጋጆቹ ገልፀዋል፡፡
የዝግጅቱ አስተባባሪ አቶ እዩኤል ልዑልሰገድ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፤በኮንሰርቱ ላይ ድንገተኛ (surprise) እንግዳ የሚኖር ሲሆን እንግዳው 2 ወይም 3 ዘፈኖችን ያቀነቅናል፡፡ አስቴር በዋዜማው ኮንሰርት 25 ዘፈኖችን የምታቀርብ ሲሆን ማዲንጎ 8 ወይም 9 ዘፈኖችን እንደሚያቀርብ ተገልጿል፡፡
የ2008 አዲስ ዓመትን ለመቀበል ከሌሊቱ 6 ሰዓት ላይ የርችት ተኩስ ሥነስርዓት ይካሄዳል ተብሏል፡፡ የVIP አቀማመጡ ከመድረኩ ፊት ለፊት መደረጉን የገለፁት አዘጋጆቹ፤ቲኬቶቹ ኤሌክትሮኒክ ስለሆኑ ግፍያ አይኖርም ብለዋል፡፡  

 የዘመን መለወጫ በዓልን ምክንያት በማድረግ የአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት ከፖሊስ ኦርኬስትራ የሙዚቃ ባንድ ጋር በመተባበር በነገው ዕለት ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ ልዩ የዓውዳመት የመዝናኛ ፕሮግራም ማዘጋጀቷን አስታውቋል፡፡ በእለቱ አጫጭር ድራማዎችን ጨምሮ ዘመናዊና ባህላዊ ዘፈኖች ከነውዝዋዜያቸው ይቀርባሉ፡፡ ፕሮግራሙን ከቀኑ 8፡00 ሰዓት እስከ 11፡30 በ30 ብር መግቢያ መታደም እንደሚቻል አዘጋጆች ተናግረዋል፡፡