Administrator

Administrator

ባልተለመደ መልኩ በምስጢር ተይዞ የቆየው የአንጋፋው ደራሲና ሃያሲ አለማየሁ ገላጋይ 17ኛ መፅሐፍ ዛሬ  ከቀኑ በ10 ሰዓት ይመረቃል።
የመፅሀፉ ርዕስም ሆነ ርዕሰ ጉዳይ በዛሬው ዕለት በዋልያ መፃህፍት ሲመረቅ ይፋ እንደሚሆን ነው የታወቀው።
በ17ኛው አዲስ መፅሐፉ ዙሪያ አዲስ አድማስ ጥያቄ ያቀረበለት ደራሲው፤ ሁሉም ነገር ርዕሱን ጨምሮ ለህዝብ ይፋ የሚደረገው በዛሬው ዕለት መሆኑን ተናግሯል።
አዲስ አድማስ በደራሲ አለማየሁ ገላጋይ የፈጠራ ስራዎች  ዙሪያ ከተለያዩ የሥነ-ጽሁፍ ሰዎች ያሰባሰባቸውን አስተያየቶች በገጽ 12 ይመልከቱ።

 (በጓድዬ ብሽዬ ኤረማ) የቤተ-ጉራጌ ምሳሌያዊ አነጋገር


         አንድ በጣም ባለፀጋ የሆኑ የተከበሩ ባላባት በአንድ መንደር ይኖራሉ፡፡ ጌታዬ ጌታዬ የማይላቸው የለም፡፡ እኝህ የተከበሩ ባላባት አንድ ብርቄ የሚባል ነባር አሽከር ነበራቸው፡፡ ብርቄ አሽከርነት ያምርበታል፡፡ ሲልኩት ወዴት፣ ሲጠሩት አቤት ለማለት ይችልበታል፡፡ ዘወትር ግብር ገብቶ፣ ድግሱ ተበልቶ ጌትዬውን ብርቄ እጅ ሲያስታጥብ፤
“ሰማህ ወይ ብርቄ” ይሉታል፡፡
“አቤት ጌታዬ” ይላል ብርቄ፡፡
“አሁን እኔ ብሞት ምን ታደርግ ይመስልሀል?”
“ጌታዬ፤ እርሶ ከዚህቺ አለም ተለይተው እኔ ከዚህ ቤት አልቀመጥም”
“ታዲያ ምን ትሆናለህ?”
“እመንናለሁ፡፡ አለም በቃኝ እላለሁ፡፡ ጀርባዬን ለአለም ፊቴን ለገዳም እሰጣለሁ”
“ተው፤ አታረገውም ብርቄ?”
“በጭራሽ፡፡ እርሶ ሞተው እኔ እዚህች ቤት አንዲት ቀን እህል ውሃ አልቀምስም!”
“መልካም፡፡ ለዚህ ታማኝነትህ አንድ ኩታ ተሸልመሃል!” ብርቄ እጅ ነስቶ ኩታወን አገኘ፡፡
ሌላም ቀን፤ “ብርቄ እኔ ብሞት ምን ታደርጋለህ?” ይሉታል፡፡
“ምን ያጠያይቃል ጌታዬ? መመነን ነዋ! ከእርሶ ወዲያ አለም ለምኔ” ይላል፡፡
”ብርሌ ጠጅ ስጡት ይባላል!”
ሌላ ቀን፡፡ “ብርቄ እኔ ብሞት ምን ታደርጋለህ”
“እለቱን፤ እኔን ጨርቄን ሳልል፣ ወደ ገዳም ነዋ ጌታዬ!”
“እውነት ታደርገዋለህ፤ ብርቄ?”
“አይጠራጠሩ ጌታዬ! ምን ቀረኝ ብዬ እዚህ ቤት እቀመጣለሁ?”
“እኔ ምልህ ብርቄ?”
“አቤት ጌታዬ?”
“እንደው ለነገሩ፤ ከኔ ቀድመህ መሞት ታስቦህ ያውቃል? አንዳንዴ ለምን እኔ ቀድሜዎት ልሙት እንኳ አትለኝም?”
ብርቄም ትንሽ አሰብ አድርጎ፤
“አይ ጌታዬ ሳላስበው ቀርቼ መስሎት? አስቤዋለሁ፡፡ ግን ከተናገርኩ የጌታዬን የተሻማሁ እንዳይመስልብኝ ብዬ ነው፡፡”
ሌላ ቀን፡፡ ብርቄን ጠርተው ደግመው በጨዋታ መሃል፤
“ከእኔ ቀድመህ የምትሞት አይመስልህም?”
“ኸረ በጭራሽ ጌታዬ?”
“ለምን?”
“እኔ ከሞትኩ ማን እንደኔ ያለቅስሎታል! ኸረ በጭራሽ እግዜር እንደዚህ ያለ ነገር አያድርስብን!! እርሶ ከሞቱ ግን እዚህች ቤት አንዲት ጀንበር አላድርም- ወደ ገዳም ነው!”
“ይህን ያህል ትወደኛለሃ?”
“እንዴት ይጠራጠራሉ?”
ከባድ ጉርሻ ያጎርሱትና “ጠጅ ስጡት!” ብለው ያዙለታል፡፡
ጌትየው እንዳሉት እሳቸው ቀድመውት ሞቱ፡፡  ከሚስታቸው አንድ ትንሽ ወንድ ልጅ ብቻ ነው ያላቸው፡፡ ሚስታቸው 6 ወር ሃዘኑንም መንፈቃቸው ከወጡ በኋላ ሌላ ባል አገቡ፡፡ ብርቄም ያዲሱ ጌታ አሽከር ሆኑ፡፡ “እርሶ ከሞቱ እመንናለሁ!” ማለቱን ቀጠለ፡፡
አንድ ቀን አዲሱ ጌታው ግብር አግብቶ፣ ሰው በድንኳን ግጥም ብሎ እየተበላ፣ እየተጠጣ ብርቄ እንደልማዱ ተፍ ተፍ እያለ እያስተናገደ ሳለ፤ አንድ አዝማሪ ተነስቶ መሰንቆውን እየገዘገዘ ጨዋታ ጀመረ፡፡
ድምፁን አዝልጎ “ትላንትና ማታ ጌታዬን አግኝቼ” አለና ጀመረ፡፡ ህዝቡ በከፊል፤ አዝማሪውም የሞቱትን ጌታ በማንሳቱ “ምን ሊል ይሆን?” በሚል አይነት ፀጥ አለ፡፡ አዝማሪው፤ ደገመና
“ትላንትና ማታ ጌታዬን አግኝቼ” አለ፡፡
አሁን ሰው ሙሉ በሙሉ ጸጥ እርጭ  አለ፡፡ ምን ሊል ነው በሚል መንፈስ፡፡ አዝማሪውም
“ትላንትና ማታ ጌታዬን አግኝቼ
… ሚስቴስ ደና ናት ወይ? (ወደ ሚስትየው እያየ)
… ልጄስ አደገ ወይ? (ወደ ልጅየው እያየ)
… ብርቄስ መ…መ…ነ ወይ!?” (ወደ ብርቄ ቀና ብሎ) ብለው ቢጠይቁኝ፣
ሚስቶት ደና ናቸው፤ ልጆትም አድጓል፡፡
(ቆም አድርጎ ወደ ብርቄ እያየና እያንዳንዱን ቃል እየረገጠ)
…ብ…ር…ቄ….ም አ…ል…መ…ነ…ነ…ም!! ብዬ ብነግራቸው፤
አይጉድ! አይጉድ! አይጉድ! ያሉበት፤ እረገፈ ጣታቸው!!”
ሲል ገጠም፡፡ ሰው ሁሉ ወደ ብርቄ ተመለከተ፡፡ ብርቄን የሰው አይን ከአገር አስወጣው፡፡
*   *   *
ለእምነታቸው የሚኖሩ፣ ማተማቸውን የማይበጥሱ፣ የተናገሩትን የማያፈርሱ፣ በምላሳቸው የማይኖሩ ብቻ ናቸው በህዝብ የሚታመኑት፡፡ ጌታቸውንና አለቃቸውን ለማስደሰት ወይም ለመሸንገል ሲሉ ብቻ “አቤት!” “ወዴት!” የሚሉ የየሥርአቱ አሸርጋጅ ይሆናሉ እንጂ፣ በየተደገሰበት ሁሉ ከበሮ መቺ ይሆናሉ እንጂ ለህሊናቸውና ለእምነታቸው አያድሩም፡፡ “ህዝቡን ልናገለግል” ፣ “አገርን ልናድን” “ምድር ሰማዩ ልናለማ”፣ “የህዝቡን የአኗኗር ዘይቤ ልንለውጥ”፣ “ከተማ ልናሰፋ፣ የገጠሩን ህዝብ ልናሰለጥን፣” ወዘተ የሚል አይነት ቃል መግባትና “ይህ ካልሆነ ወንበሬን እለቃለሁ”፣ “ይህ ካልሆነ የጓዶች አጥንት እሾህ ሆኖ ይውጋኝ!”፣ “ይህ ካልሆነ ማናቸውንም ፍዳ ልቀበል!” ማለት የተለመደ ሆኗል፡፡ እንደ ብርቄ “እርሶ ከሞቱ በቃ፤ እመንናለሁ” ማለት፡፡ ከዚያም ምንም ለውጥ ሳይመጣ ሲቀር ለአዲሱ ጌታ ማደር፡፡ አይንን በጨው ታጥቦ “ዛሬም እንደ ትላንት በአላማ ፅናት ራእይን እውን ለማድረግ “እስከ መጨረሻ ድረስ የደም ጠብታ፣ እስከ መጨረሻ አንድ ሰው፤ እታገላለሁ” ሲሉ ቃለመሃላ ማዥጎድጎድ፡፡ ጌታዬ ከሞቱ እዚህች አገር አንዲትም ቀን አልውልም አላድርም ማለት!... ቃል መግባት … እቅድ ማቀድ… ፖሊሲ መንደፍ… በየወንዙ መማል… መማማል መመሪያ ማውጣት… አዋጅ ማወጅ… በየፌርማታው አበጀህ መባባል… መግለጫ ማውጣት… መፅሐፍ መግለጥ… ፕሮጀክት መቅረፅ… መርቆ መክፈት… መጨባበጥ “ከመቸውም በበለጠ በአዲስ መንፈስ ተነስተናል” ማለት… ትላንትን በላጲስ ማጥፋት… ነገን በእርሳስ መሳል… ተግባርና “አፈፃፀም” ግን የለም፡፡ ቃል ይፈርሳል፡፡ ቃል ይበላል፡፡ የሚወገዝ ይወገዛል፡፡ መካድ፡፡ መካካድ ይቀጥላል፡፡ የሚረገም ይረገማል፡፡ በድሮ ጊዜ ብሎ ጥሩምባ ነፊው “ካድሬያችን ኑና አራግሙን ብሏል!” እንደተባለው ነው፡፡ በትብብር፣ በደቦ፣ በብዙሃን ድምፅ መራገም እንጂ ከልብ የሚሆን ምንም ነገር የለም እንደማለት ነው፡፡ “ሲቸግር የእንጀራ እናቱን እምዬ ይልዋል” ነውና የትላንቶቹን ለመርገም የትላንት ወዲያውን መጥቀስና ማወደስ ይቀጥላል፡፡
አዲስ መፈክር ይቀመራል፡፡ በህብረት ያንን መፈክር ማስገር ይቀጥላል፡፡ በልብ መክዳት በአካል አለሁ ማለት ይዘወተራል፡፡ እስከ ሌላ መከዳዳት፣ እስከ ሌላ ቃል ማፍረስ “ልጅ እገሌ” ፣ “ጉድ እገሌ”፣ “ክቡር እምክቡራን” መባባል፡፡ ሆኖም “በጭለማ ማፍጠጥ ደንቆሮን መቆጣት ነው” እንደሚባለው ልብ ውስጥ እውነተኛ ፍቅር፣ እውነተኛ አገር መውደድ፣ እውነተኛ ለህዝብ የመቆም ስሜት፣ ሳይኖር አላማና እቅድን በስራ ላይ ማዋል ከቶም ዘበት ነገር ነው፡፡ መሪና መሪ፣ አለቃና አለቃ፣ ፓርቲና ፓርቲ፣ ባለስልጣንና ባለስልጣን፣ ዜጋና ዜጋ በመካከላቸው ልባዊ መተማነን ከሌለው ስራ አይሰራም፤ እቅድ አይፈፀምም፡፡ ፕሮግራም አይተገበርም፡፡ ቃል ህይወት አይሆንም፡፡ ይስሙላ፣ ለበጣ፣ የአደባባይ ማስመሰል፣ የሸንጎ ዲስኮ፣ የስብሰባ ንግግር ብቻ ሆኖ ይቀራል፡፡
የሀገራችን አንዱ አንኳር ችግር ከእቅድ ነዳፊው እስከ ፈፃሚው ድረስ ልባዊ መተማመን አለመኖር ነው፡፡ “ይህን ያለው ይህን ሊል ፈልጎ ነው” በሚል የግራ ትርጉም የታጠረው አስተሳሰብ ይበዛል፤ ቡድንና ቡድን አይተማመንም፡፡ መስመሩን ሳይሆን በመስመሮች መሃል ማንበብ (Between the lines እንዲሉ) ነው ፈሊጡ፡፡ በውስጡ የተቀበረው ፍላጎት (Hidden motive) ካለ ምንዛሬ ይበዛል፤ ቅጥያና ዘርፍ እያበዙ “ትርጉም የኔ”፣ “ስርዝ ያንተ”፣ “ቅንፍ የነሱ” ማለት ቋንቋ ይሆናል፡፡ አፋዊ የሆነ ያሸበረቀ ቃል ሲበዛ ተግባር ባዶውን ይቀራል፡፡ ዞሮ ዞሮ ወሳኙ ግን ልባችን ውስጥ ምን አለ የሚለው ነው፡፡ ልባችን ትግል እያሰበ አፋችን ድል ቢያወራ ዋጋ የለውም፡፡ ልባችን አትጠጉኝ እያለ አፋችን ስለ አፍሪካ ህብረት እና ጉባኤ ቢያወራ ነገር ሁሉ የይስሙላ ይሆናል፡፡ ልባችን ሹመት እያሰበ አፋችን የኢኮኖሚ ልማት ቢያወራ ነገ የሚጋለጥ ከንቱ ዲስኩር ይሆናል፡፡ ሁሉም የሚያስተጋባውና የሚተገብረው ጥንት የተሰራበትን ንጥረ-ነገር ነው፤ የውስጡን፡፡ የጠዋቱን፡፡
እውነተኛ ፍሬ ከእውነተኛ ተግባር፣ ከእውነተኛ እምነት ነው የሚገኘው፡፡ ያ ሳይኖር ፍሬ መጠበቅ ከንቱ ነው፡፡ ነጭ ባህር ዛፍ ላይ ቀይ ባህር ዛፍ አይበቅልም ማለትም ይኸው ነው፡፡


 የቴሌግራም ቻናልችንን  በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
https://t.me/AdissAdmas

 

የሶማሊያ ፌደራል መንግሥት፣ በፑንትላንድ ዋና ከተማ ጋሮዌ የሚገኘው የኢትዮጵያ ቆንስላ እንዲዘጋ ያስተላለፈውን ትዕዛዝ እንደማትቀበል ፑንትላንድ አስታወቀች።
የሶማሊያ  መንግሥት የኢትዮጵያ መንግሥት በውስጥ ጉዳዬ ጣልቃ እየገባ ነው በሚል በሞቃዲሾ የኢትዮጵያ አምባሳደር አገሪቱን ለቀው እንዲወጡና በከፊል ራስ ገዟ ፑንትላንድና ነጻነቷን ባወጀችው ሶማሊላንድ ያሉት የኢትዮጵያ ቆንስላ ጽህፈት ቤቶች እንዲዘጉ ማዘዙን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡  
ከጎረቤት አገር ኢትዮጵያ፣ ነጻ አገር ነኝ ከምትለው ሶማሊላንድና በከፊል ራስ ገዝ ከሆነችው ፑንትላንድ ጋር ፖለቲካዊ እሰጣ ገባው ውስጥ የገባው የሶማሊያ ፌደራል መንግሥት፣ ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ሦስቱን መንግሥታት የተመለከተ ጠንካራ ዲፕሎማሲያዊ እርምጃ መውሰዱን አስታውቋል። የፑንትላንድ አስተዳዳር ትላንት ዓርብ መጋቢት 27 ቀን 2016 ዓ.ም. ባወጠው መግለጫ ቆንስላው እንዲዘጋ የተላለፈው ትዕዛዝ፣ የሶማሊያን ሕገ-መንግሥት የሚጥስ ነው በማለት ተግባራዊ እንደማይደረግ አስታውቋል።
የፕሬዚዳንት  ሐሰን ሼክ ሙሐመድ አስተዳደር የኢትዮጵያው አምባሳደር ሙክታር ከድር ዋሬ፣ በ72 ሰዓታት ከአገር እንዲወጡ ትዕዛዝ ከማስተላለፉ በተጨማሪ፣ አዲስ አበባ በሐርጌሳና ጋሮዌ ያላት ቆንስላዎች በአንድ ሳምንት ውስጥ እንዲዘጉ ትዕዛዝ ሰጥቷል።
ይሁን እንጂ የሶማሊላንድና ፑንትላንድ በሚኒስትር ደረጃ ያሉ መሪዎች የፌደራል መንግሥቱ ውሳኔን እንደማይቀበሉ ተናግረው ነበር። ከዚህ በተጨማሪም የሶማሊያ መንግሥት በአዲስ አበባ የሚገኙትን አምባሳደሩን “ለአጠቃላይ ምክክር” ከኢትዮጵያ ለቀው እንዲወጡ ማዘዙን የሶማሊያ የውጭ ጉዳይና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ሚኒስቴር ይፋ አድርጓል።
የሶማሊያ መንግሥት በመግለጫው፤ ኢትዮጵያ “በሶማሊያ ሉዓላዊነትና የውስጥ ጉዳይ” ጣልቃ ገብታለች ሲል ከሷል። ኢትዮጵያ ታኅሣሥ 2016 ዓ.ም. ነጻ አገርነቷን ካወጀችው ሶማሊላንድ ጋር የባሕር ጠረፍ ማግኘት የሚያስችላትን የመግባቢያ ስምምነት መፈረሟ ሞቃዲሾን ያስቆጣ ሲሆን፣ በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን ግንኑነትም አጠልሽቶት ቆይቷል።
ባለፈው ሳምንት ማብቂያ ላይ ደግሞ የሶማሊያ መንግሥት ያደረገውን የሕገ-መንግሥት ማሻሻያ በመቃወም ከፊል ራስ ገዝ የሆነችው ፑንትላንድ ለፌደራል መንግሥቱ እውቅና መስጠት አቁሚያለሁ ብላለች።
ይህ የፑንትላንድ ውሳኔ በሶማሊያ ፖለቲካ ውጥረት ፈጥሮ ባለበት ወቅት የፑንትላንድ የገንዘብ ሚኒስትር ባለፈወው  ረቡዕ መጋቢት 25 ቀን 2016 ዓ.ም. ለጉብኝት አዲስ አበባ ገብተው ከኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ጋር መወያየታቸው ሶማሊያን አስቆጥቷል፡፡
የሶማሊያ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት አሁን የኢትዮጵያን ዲፕሎማት ለማባረርና የቆንስላ ጽህፈት ቤቶቿ እንዲዘጉ ከውሳኔ ላይ የደረሰው የገንዘብ ሚኒስትሩን ጉብኝት ተከትሎ ሊሆን እንደሚችል ተገምቷል።
የፑንትላንድ አስተዳደር መንግሥት ትላንት ዓርብ  ባወጣው መግለጫ፤ የሶማሊያን ውሳኔ እንደሚቃወም ገልጾ፤ ፑንትላንድ የውጭ ፍላጎቷን ለማስጠበቅ ከማዕከላዊው የሶማሊያ መንግሥት እውቅና ውጪ በቀጥታ በራሷ አማካይነት ግንኙነቶችን እንደምታደርግም ጨምራ ገልጻለች።

ባሮክ ኤቨንት ኦርጋናይዘር አ.ማ፣ ከሚያዚያ 10 እስከ ሚያዚያ 28 ቀን 2016 ዓ.ም የሚቆይ  የፋሲካ  ባዛርና ኤክስፖ በሚሊኒየም አዳራሽ እንደሚያካሂድ አስታወቀ፡፡

ለ20 ቀናት ገደማ ክፍት የሚሆነው ባዛርና ኤክስፖ፤ ሸማቹ በተመጣጣኝና ቅናሽ ዋጋ ከራሱ ከአምራቹና አስመጪው የሚገበያይበት ነው የተባለ ሲሆን፤ አምራቹም ከሸማቹ ከፍተኛ ገበያ የሚያገኝበት እንደሚሆን ተነግሯል፡፡

ከ2ሺ በላይ አስመጪና ሻጮች እንደሚሳተፉበት በተነገረለት በዚህ ባዛርና ኤክስፖ፤ በቀን እስከ 10ሺ የሚደርሱ ሸማቾች ይጎበኙታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በዚህ ባዛርና ኤክስፖ ከዓውዳመት ሸቀጦች በተጨማሪ፣ በየቀኑ ታዋቂ ሙዚቀኞች፣ ተወዳጅ ሥራዎቻቸውን እንደሚያቀርቡ ታውቋል፡፡

የፋሲካ ባዛርና ኤክስፖ የፊታችን ሚያዚያ 12 ቀን 2016 ዓ.ም ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ ባለሃብቶች፣ የሚዲያ ባለሙያዎችና ታዋቂ ግለሰቦች በተገኙበት በይፋ ይከፈታል ተብሏል፡፡

የደራሲ እያዩ ደባስ ሦስተኛ መጽሐፍ “ፓርታ” ለንባብ የበቃ ሲሆን፤ ደራሲው በመግቢያው ላይ እንዳሰፈረው፤ “ፓርታ ላልተጻፈው የሐሳብ ዕዳ ክፍያ ይሆን ዘንድ ነው። እነርሱን የመሆን የሐሳብ ዕዳ ውስጥ ለገባ አንድ አሳቢ፣ ሰውን ነጻ የማውጣት የቀናነት ትግል ነው።

መጽሐፉ የትችት፣ የመወቃቀስ፣ የሐሜትና የጥላቻ ግብ የለውም። ከሐሳብነት የተረፈ የመቆሚያ ሥፍራም የለው፤ ብሏል ደራሲው።

የዚህ መጽሐፍ ዋና ገጸ-ባሕርይ “ሐሳብ” መሆኑ የተጠቆመ ሲሆን፤ደራሲው የእድሜ ዘመን ንባብ ያላቸውን ታዋቂ ግለሰቦችን ገጸ ባህሪ አድርጎ በማምጣት፣ለሃሳብ የበረታ ድርሰት ከትቧል፡፡
 
“ፓርታ” በ273 ገጾችና 68 ምዕራፎች የተቀነበበ መጽሐፍ ሲሆን አሳታሚና አከፋፋዩ ጃዕፈር መጻሕፍት መደብር ነው ተብሏል፡፡ መጽሐፉ  በ400 ብር ለአንባቢያን ቀርቧል።

•  የመጀመሪያውን ዙር የመኪና ርክክብ አድርገዋል

አሚጎስ የገንዘብ ቁጠባና ብድር ህብረት ስራ ማህበርና ኢትዮፒካር፣. የኤሌክትሪክ መኪኖችን በብድር ለማቅረብ የሚያስችል ስምምነት ዛሬ ጠዋት መጋቢት 27 ቀን 2016 ዓ.ም  የፈፀሙ ሲሆን፤ የብድር መስፈርቱን ላሟሉ ሰባት የ“ምሰሶ የታክሲ ማህበር” አባላት የመኪና ርክክብ አድርገዋል።

ስምምነቱን የፈፀሙት የአሚጎስ ም/ሥራ አስኪያጅ አቶ ዘላለም ይልማና የኢትዮፒካር ባለቤት አቶ ሳሙኤል አዲስዓለም  ናቸው።

በስምምነቱ መሰረት፣ የ"ሆን ዞ" አውቶ ፋክተሪ የኢትዮጵያና ምስራቅ አፍሪካ ብቸኛ ወኪል የሆነው ኢትዮፒካር፣ የአሚጎስ አባላት የሚፈልጓቸውን የኤሌክትሪክ መኪኖች ምቹና ቀልጣፋ በሆነ መልኩ በብድር እንደሚያቀርብ ታውቋል፡፡

 ኢትዮጵያ እንደ ሃገር የውጭ ምንዛሬ እጥረትን ብሎም የአየር ንብረትን ለመጠበቅ ይረዳ ዘንድ የኤሌክትሪክ መኪናን እንደ አማራጭ የመጠቀም ፖሊሲን እየተገበረች ሲሆን፤ በሃገራችን የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ፍላጎትም እያደገ መምጣቱ ተነግሯል፡፡

የአለማችን ተጠቃሽ የኤሌክትሪክ መኪኖች አምራች የሆነው የ"ሆን ዞን" አውቶ ፋክተሪ የኢትዮጵያና ምስራቅ አፍሪካ ብቸኛ ወኪል ኢትዮፒካር ብራንድ፣ የኤሌክትሪክ መኪኖችን ወደ ኢትዮጵያ በማስገባት ለተጠቃሚዎች እያቀረበ ይገኛል፡፡

የዜጎችን ኑሮ ባማከለ መልኩ በባንክ ብድር አማራጭ የሚቀርቡት እነዚህ የኤሌክትሪክ መኪኖች፣ የፋብሪካ ዋስትና እንዳላቸው የተገለጸ ሲሆን፤ድርጅቱ መኪኖቹን መቶ በመቶ በብድር ብቻ ለተጠቃሚዎች ለማቅረብም እየሰራ እንደሚገኝም ለማወቅ ተችሏል፡፡

• ለመጀመሪያ ጊዜ በኦንላይን የተመዘገበ ሰርተፊኬት ተሰጥቷል
የአዲስ አበባ ሌጀንድ ኢንተርናሽናል ፕሮ ቴኳንዶ አሶሴሽን፤ የ2016 ዓ.ም የመጀመሪያዎቹን የ3ኛ ደረጃ የዳኝነት ሥልጠናና ዓለማቀፍ የፕሮ ቴኳንዶ የመጀመሪያ ራስን መከላከል ስልጠና ተሳታፊዎች ትላንት መጋቢት 26 ቀን 2016 ዓ.ም በወወክማ አዳራሽ አስመረቀ፡፡
ሥልጠናው ከአዲስ አበባና ከክልሎች ለተውጣጡ 28 ተሳታፊዎች ለ15 ቀናት ሲሰጥ የቆየ ሲሆን፤ ተመራቂዎቹ ለመጀመሪያ ጊዜ በኦንላይን የተመዘገበ ሰርተፊኬት ማግኘታቸው ታውቋል፡፡
 
ከሰልጣኞቹ መካከል 19 ያህሉ ሥልጠናውን በተሟላ መልኩ አልፈዋል የተባለ ሲሆን ሁለቱ አለማለፋቸው ነው የተነገረው፡፡
በምረቃ ሥነስርዓቱ ላይ እንደተነገረው፤ ሳኦል ኹነቶች ለአራት ሰልጣኞች የስፖርት ማዘውተሪያ አዳራሽ ያመቻቸ ሲሆን፤ በቅርቡ ፒያሳ አካባቢ በኮሪደር ልማት ሳቢያ የስፖርት ማዘውተሪያ ለፈረሰበት አንድ ወጣት በቀጣይ ቦታ ለማመቻችት ቃል ተገብቶለታል።
የአዲስ አበባ ሌጀንድ ኢንተርናሽናል ፕሮ ቴኳንዶ አሶሴሽን ፕሬዚዳንት ማስተር ሃይለየሱስ ፍስሃ በመርሐግብሩ ላይ እንደገለጹት፤ የተሰጠው 3ኛ ደረጃ የዳኝነት ሥልጠና፣ ሌጀንድ ኢንተርናሽናል በኢትዮጵያ የሠጠው የመጀመሪያ ኮርስ ነው፡፡
የሌጀንድ ኢንተርናሽናል ፕሮ ቴኳንዶ አሶሴሽን የአፍሪካ ፕሬዚዳንት የኢትዮጵያ የበላይ ጠባቂ ግራንድ ማስተር (ፒ ኤች ዲ በማርሻል አርት ሳይንስ) ሄኖክ ግርማ፣ለተመራቂዎቹ ሰልጣኞች ሽልማት ሰጥተዋል፡፡
 
ይህ በዚህ እንዳለ፣ የአዲስ አበባ ወርልድ ቴኳንዶ ፌዴሬሽን ከሳኦል ኩነቶች ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የአዲስ አበባ ወርልድ ቴኳንዶ 2016/2024 ኦፕን ቶርናመንት፣ ከግንቦት 3 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ የሚካሄድ ሲሆን፤ ውድድሩን አስመልክቶ ነገ ቅዳሜ በአራት ኪሎ ስፖ/ትም/ሥልጠና ማዕከል በሚገኘው ትልቁ ጅምናዚየም ጋዜጣዊ መግለጫ እንደሚሰጥ ታውቋል፡፡

ይህ ‹‹ሆኖ መገኘት፤ እኔም ኃይሌ ነኝ›› የተሰኘ መጽሐፍ በኢትዮጵያ የድርጅቶች አገልግሎት ልህቀትን ለማሳደግ በማሰብ የተደረገ የእውቀት ሽግግር ጥረት ነው፡፡ ይህ መጽሐፍ ወደ ልህቀት የሚደረግን ጉዞ የሚያግዝ ብቻ አይደለም፤ ይልቁንም መንገድንም የሚያመላክት እንጅ፡፡

‹‹ሆኖ መገኘት›› ማዕከል የሚያደርገው የአገልግሎት ልህቀት ከፍ እያለ በተግባር እየታየበት ያለውን ኃይሌ ሪሶርቶችና ሆቴሎች ሲሆን የሥረ ነገር ማጠንጠኛውም ራሱ ሆኖ መገኘትን ያሳዬን ኃይሌ ገብረ ሥላሴ ነው፡፡ መጽሐፉ የሥራ ባህል ምን ያህል ወሳኝ መሆኑን አጽኦት የሚሰጥ ከመሆኑም በላይ የስራ ባህል ምንነትን እና ተግባራትን ከመቅረጽ አንጻር ያለውን ሚና ያትታል፡፡

ሆን ተብሎ ቢሆንም እና ባይሆንም ባህል እያንዳንዱ ከባቢ ላይ ተጽዕኖውን ያሳርፋል፤ የግለሰቦች ይሁን የድርጅቶችንም ግብር እና ምግባር ይቀርጻል፡፡ ይህን ሀቅ ስንቅ አድርጎ በመያዝ ኃይሌ ሪሶርቶችና ሆቴሎች  ከቃል በላይ የሆነ በተግባርም የተገለጸ አዲስ ባህልን ለመፍጠር ችሏል፡፡

በዚህ መጽሐፍ የምንነግራችሁ ንድፈ ሐሳብ አይደለም፤ ይልቁንም እየተኖረ ያለ እና በተግባር የተገለጸን እውቀት እንጅ፡፡ ይህም እውቀት የጋራ የሆነ እንጅ ለጥቂቱ ተገልጦ ብዙኃኑ ያላገኙት ትንቢት አይደለም፡፡ ለውጡም ከተግባርዎ፣ ከምግባርዎ፣ ከሥነ ልቦናዎም ዘንዳ የሚታጨድ እሸት ነው፡፡ ስሊዚህም እንዲህ እንላለን ‹‹ማንም ቢሆን ልክ እንደ ኃይሌ ማሰብን መልመድን እና መሥራትን ይችላል›› ስለዚህም ‹‹እኔም ኃይሌ ነኝ›› ፍልስፍና የስኬት ቁልፍ ለእርስዎ እነሆ!

“አንዲት እናት ልጆቿን ብቻዋን ታሳድጋለች፡፡ የአስተዳደግ ዘይቤዋ ከሌሎች ወላጆች ለየት ይላል፡፡ ልጆቿ ከሰፈር ልጆች ጋር ተቀላቅለው ሲጫወቱ አይቼ አላውቅምና ሁሌም ጥያቄ ይፈጥርብኝ ነበር፡፡ ልጆችሽ ከእድሜ እኩዮቻቸው ጋር ሲጫወቱ አይቼ አላውቅም አልኳት፡፡
“በልጅነቴ ብቸኛ ወንድሜን ያጣሁት ሰፈር ውስጥ በተወረወረ ድንጋይ ነው” ወዲያውም ስቅስቅ ብላ አለቀሰች፡፡
“በጣም አዝናለሁ፤ መጠየቅ አልነበረብኝም” አልኳት፡፡
“እነዚህን ብርቅዬ ልጆች እንደ ወንድሜ ማጣት አልፈልግም፡፡ ውጭ እንደ ሌሎች ልጆች ቢጫወቱ ይሞቱብኛል ብዬ እፈራለሁ፡፡” አለችኝ::
ህክምና ያላገኘ የልጅነት ጠባሳ ጊዜ ጠብቆ በትዳር ህይወትም ይገለጣ:ል፡፡”
**
በደራሲ ብርሃኑ በላቸው አሰፋ የተዘጋጀው “ክቡር ልጆች፣ የልጆች ስነ ልቦና ለመገንባት እና የስሜት ስብራት ለመጠገን የሚረዱ ቁልፍ መንገዶች ” የተሰኘው መጽሐፍ፤ የፊታችን እሁድ መጋቢት 29 ቀን 2016 ዓ.ም፣ ሳር ቤት በሚገኘው በኢንተርናሽናል ኢቫንጀሊካል ቤተ ክርስቲያን እንደሚመረቅ ደራሲው ለአዲስ አድማስ ተናግሯል፡፡ (ለመግቢያ የተጠቀምንበት ጽሁፍም ከመጽሐፉ የተቀነጨበ ነው፡፡)
መጽሐፉ፤ በልጆች ስነ ልቦና ላይ ጥናትን መሰረት ያደረገና ሀገራዊ ለዛ ያለው እውነተኛ ታሪኮችን የሚያስቃኝ ሲሆን፤ በተለያየ ተግዳሮት ውስጥ ለሚገኙ ልጆች የመፍትሄ ሃሳብ ይዞ መቅረቡም ተጠቁሟል፡፡ በዋናነትም ልጆች የሚስተዋልባቸውን የስነ ልቦና ጫና እና የስሜት ስብራት የሚተነትን ሲሆን፤ በጥናት ላይ የተደገፈ የመፍትሄ ሃሳብን በተጨባጭ እንደሚያመላክትም ተነግሯል፡፡
“ክቡር ልጆች“ በአማርኛና አፋን ኦሮሞ ተዘጋጅቶ የተቀረበ ሲሆን፤ በዋናነትም ለትዳር ለሚዘጋጁ፣ ለወላጆች፣ ለመምህራን፣ እንዲሁም በልጆች ላይ ለሚሰሩ ባለሙያዎችና ለሌሎችም ታስቦ የተዘጋጀ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡
ደራሲው በሆሊስቲክ ቻይልድ ዴቨሎፕመንት ሁለተኛ ዲግሪ ፣ በሶሽዮሎጂ ሁለተኛ ዲግሪና በስነፅሑፍና ቋንቋ ጥናት የመጀመሪያ ዲግሪ ያለው ሲሆን፤ ከልጆችና ወጣቶች እድገት ጋር በተያያዘ በተለያዩ ሚዲያዎች ላይ በተጋባዥ እንግድነት እየቀረበ ሙያዊ ትንታኔዎችን በመስጠት ይታወቃል፡፡
 

ጠ/ሚኒስትሩ ተፎካካሪ ፓርቲዎች ሰብሰብ ብለው እንዲታገሉ ጥሪ አቀረቡ

”60 ፓርቲዎች ሆናችሁ ልንደግፋችሁ ይቸግረናል“

ለሁለት ወር ግድም ከተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች ጋር ውይይት ያደረጉት ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ፤ ባለፈው ሰኞ መጋቢት 23 ቀን 2016 ዓ.ም በመቶዎች ከሚቆጠሩ የተፎካካሪ ፓርቲዎች አመራሮች  ጋር በተለያዩ አገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ተወያይተዋል፡፡

የፓርቲ አመራሮቹ በውይይቱ ላይ ለጠ/ሚኒስትሩ የተለያዩ ጥያቄዎችን ያቀረቡ ሲሆን፤ ከእነዚህም መካከል የሰላምና ጸጥታ ችግር፣ የህግ የበላይነት አለመኖር፣ የፖለቲካ  ምህዳር መጥበብ፣ የሜጋ ፕሮጀክቶች ተጠያቂነትና  የዜጎች መፈናቀል ጉዳዮች ይጠቀሳሉ፡፡

የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ም/ቤት ሃላፊን ጨምሮ አንዳንድ የፓርቲ አመራሮች የቢሮ፣ የአዳራሽና የፋይናንስ ችግር  እንዳለባቸው ጠቅሰው ላነሱት ጥያቄ፣ ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ  ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

እኛ እንደ ፓርቲ ማድረግ የምንችላቸውን ነገሮች እናያለን ያሉት ጠ/ሚኒስትሩ፤ ያንን ለማድረግ ግን ለፓርቲዎቹ ቅድመ ሁኔታ አስቀምጠዋል - አሁን ያሉት 70 የሚደርሱ ፓርቲዎች 4 ወይም 5 ሆነው ሰብሰብ እንዲሉ፡፡

“አሁን ኢትዮጵያ ውስጥ 66 ወይም 68 ገደማ ፓርቲዎች አሉ፡፡ ለ68 ሊቀ መንበር ቦታ የለንም፤ ለ68 ሊቀ መንበር ቢሮ የለንም፤ 2-3-4-5 ሆናችሁ ብትሰባሰቡ --- ከብልጽግና ጋር 5 ወይም 6 ፓርቲ ብንሆን አንቸገርም ነበር፡፡”  ያሉት ዐቢይ፤ ”ለምሳሌ ዛሬ በውይይቱ ላይ ከእያንዳንዱ ፓርቲ አምስት አምስት ሰው ቢወከል፣ 25ቱም ሰዎች መናገር ይችሉ ነበር” በማለት አስረድተዋል፡፡

 “ስንበዛ መበተን ብቻ ሳይሆን በዚያው መጠን አቅማችንም ውስን ይሆናል፤” ሲሉም አክለዋል፡፡



ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ፤ ውይይቱን የቋጩትም  የፖለቲካ ፓርቲዎቹ ሰብሰብ እንዲሉ በመማጸን ነበር፡፡

“እባካችሁ ወደ 4 ወይም 5 ፓርቲ ሰብሰብ በሉ፡፡ ግዴለም ይጠቅማችኋል፡፡ እንደዚያ ከሆናችሁ ፓርላማውም ይከፈታል፤ የምታስቡትም ሥልጣን ይመጣል፡፡ በዋና ዋና ጉዳይ ከተግባባችሁ በጋራ ሆናችሁ ብትታገሉ---አትጠራጠሩ ፓርላማውንም እንከፋፈለዋለን፡፡” ብለዋል፡፡

“እናንተ ግን አሁን 60 ናችሁ፤ ይሄ ለህዝብም ያስቸግራል” ያሉት ጠ/ሚኒስትሩ፤ ”እኔ እንኳን ስማችሁን አላውቀውም፤እንኳን የኢትዮጵያ ህዝብ--” ሲሉም ፓርቲዎቹ ሰብሰብ ብለው እንዲታገሉ መክረዋል፡፡

ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ፣ ከዚህ ቀደምም የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ሰብሰብ ብለው በጋራ እንዲታገሉ ጥሪ አቅርበው እንደነበር አይዘነጋም፡፡

Page 2 of 700