Administrator

Administrator

ባለፈው ሐምሌ 18 ቀን 2007 ዓ.ም በወጣው  የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ዕትም ላይ ዮሐንስ የተባሉ ፀሐፊ፣ በአሜሪካ መንግስት ድጋፍ የሚደረግለት ፓወር አፍሪካ ኢንሼቲቭ አካል በሆነው በኩርቤቲ የሚገነባው የጂኦተርማል ኃይል ማመንጫን አስመልክተው የፕሮጀክቱን አክሳሪነት፤ “የኦባማ ስጦታ ለኢትዮጵያ፡ የ 40 ቢሊዮን ብር ኪሳራ!!” በሚል ርዕስ ባሰፈሩት አስተያየት ለመግለጽ ሞክረዋል። በርግጥ አቶ ዮሐንስ ለኢትዮጵያና ለአፍሪካ ኪሳራ ብለው የመደቡት ገንዘብ በየትኛው ስሌት እንዳስቀመጡት የሚያሳይ አሳማኝ መረጃ ባያቀርቡም፣ ስለ ፕሮጀክቱ ያላቸውን ስጋት በደፈናው ያስቀመጡበትን ሁኔታ ለመገንዘብ አዳጋች አይደለም፡፡ ነገር ግን ፀሐፊው መለስ ብለው የፓወር አፍሪካ ኢንሼቲቭ አላማን ለመረዳት ቢሞክሩ መልካም ነበረ በማለት የግል አስተያየቴን ለመሰንዘር እወዳለሁ።

     በፕሬዚደንት ኦባማ ሃሣብ አመንጪነት የተቋቋመው ፓወር አፍሪካ የተሰኘው ኢንሼቲቭ፤ አፍሪካ ለእድገቷ የሚያስፈልጋትን የኃይል ፍላጎት ለማሟላት እያደረገች ያለችውን ጥረት ለመደገፍ ያለመ ፕሮጀክት እንደሆነ መረጃዎች ያመላክታሉ። ኢንሼቲቩ ኢትዮጵያን ጨምሮ በስድስት የአፍሪካ አገራት፣ 20 ሚሊዮን ነዋሪዎችን የኤሌክትሪክ ኃይል ተጠቃሚ ለማድረግ የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በመንደፍ በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል።
 ኢትዮጵያ የጀመረችውን የእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ከግብ ለማድረስ በሁሉም ዘርፍ የሚደረገው ልማት ወሳኝነት አለው። በተለይ የኃይል ልማቱ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ትኩረት የሚያሻው በመሆኑ የሃገሪቱን የኃይል ፍላጎት በበቂ ሁኔታ ለመመለስ የ25 ዓመት የአረንጓዴ ልማት ስትራቴጂ በመንደፍ፣ የኃይል አቅርቦቱን አሁን ካለው 4000 ሜጋ ዋት ወደ 37000 ሜጋ ዋት ለማሳደግ፣ የግል አልሚዎችንም በማሳተፍ ጭምር ዓላማውን ከግብ ለማድረስ ዘርፈ ብዙ ስራዎች በመከናወን ላይ ይገኛሉ። ከነዚህም ፕሮጀክቶች በዋነኝነት የትውልድ አሻራ ያረፈበት ታላቁ የህዳሴ ግድብ ግንባታ ተጠቃሽ ሲሆን ዮሐንስ ባሰፈሩት ሃሳብ፣ “የፓወር አፍሪካ የገንዘብ ርዳታ ለምን ለህዳሴው ግድብ አይሆንም” ሲሉ ገልጸዋል፤ ነገር ግን  የህዳሴ ግድብን በተመለከተ እኛው በኛው ለኛው የምንሰራው ግድባችን መሆኑን ፀሐፊው አልሰሙ ይሆን? የውጪ እርዳታ ለማግኘት ጥረት ተደርጎ ባለመሳካቱ አልነበረም እንዴ እኛው ራሳችን ለመስራት ቃል የገባነው፡፡
እስካሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታ በሃገራችን 94% ያህሉ የኤሌክትሪክ ኃይል የሚመነጨው ከሃይድሮ ፓወር መሆኑ ግልፅ ነው። ይህ ማለት ግን ያለን የኃይል አማራጭ በግድብ ግንባታ ላይ የተመሰረተ ብቻ ነው ማለት አለመሆኑን ፀሐፊው ሊረዱት ይገባል ባይ ነኝ። ለኢኮኖሚው ቀጣይ እድገት አስተማማኝና ዘላቂ የኃይል አቅርቦትን ለማሟላት ከተለያዩ የኃይል ምንጮች የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫዎችን መገንባት ግድ የሚለን ወቅት ላይ ደርሰናል። ለዚህም ሲባል ከንፋስ ኃይል 800 ሜጋ ዋት ኃይል ለማመንጨት በዕቅድ የተያዘ ሲሆን አሽንጎዳ 120 ሜጋ ዋት፣ አዳማ I የነፋስ ኃይል ማመንጫ 51 ሜጋ ዋት ኃይል ያመነጫል።  አዳማ II በቅርቡ 153 ሜጋ ዋት ኃይል ማመንጨት የጀመረ መሆኑን ሰምተናል አይተናልም። በአፍሪካ ትልቁ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ጣቢያ በሚያሰኘው ደረጃ ላይ መገኘቱ ኢትዮጵያ በታዳሽ ኢነርጂ ልማትን በማፋጠን ላይ እንደምትገኝ ዋቢ ሆኖ ሊቆጠር ይችላል። ከእነዚህ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ጣቢያዎች ባጠቃላይ በአሁኑ ወቅት 324 ሜጋ ዋት ኃይል ለማመንጨት ያስቻለ አቅምንም ፈጥረዋል።
እንደ ንፋስ ኃይልና ጂኦተርማል ያሉት የኃይል ምንጭ አማራጮች  የሃይድሮ ፓወርን በመደገፍ የዝናብ መጠን አነስተኛ በሚሆንባቸው ወቅቶች  ለክፉ ቀን ደራሾች መሆናቸው የሚያስማማን ይመስለኛል።       
ሁሉንም የታዳሽ ኃይል ምንጮች የማልማቱ ተግባር ከሚፈጥረው ሰፊ አማራጭ በተጨማሪ በተወሰኑ የኃይል ምንጮች ላይ የሚኖረውን ጥገኝነትንም ይቀንሳል። ኢትዮጵያ በስምጥ ሸለቆ አካባቢዎች ከፍተኛ የጂኦተርማል ኃይል የማመንጨት አቅም እንዳላት በየጊዜው የሚደረጉ ጥናቶች እያመላከቱ ነው።
ከዚህ የኃይል ምንጭ ብቻ ከ10‚000 ሜጋ ዋት በላይ ማመንጨት እንደሚቻል ታውቋል፡፡ በእስካሁኑ ሁኔታ ከጂኦተርማል ለመጠቀም የተቻለው ኃይል 7% ብቻ ነው። ይህም በዘርፉ ያለውን አቅም የመጠቀም ውስንነት እንዳለ ቢያሳይም በቅርቡ በአሜሪካ መንግስት ድጋፍ 1000 ሜጋ ዋት ኃይል ማመንጨት የሚያስችል ስምምነት ላይ ተደርሷል።
የጂኦተርማል ኢነርጂ ከአካባቢ ብክለት ነጻ የሆነ አስተማማኝ የታዳሽ ኢነርጂ ምንጭ ሲሆን ከቅሪተ አካል ኢነርጂ ምንጮች ከሚወጣው ወጪ 80% ያህል ቅናሽ እንደሚኖረውም ይነገራል።
 ከዚህ አንጻርም ለትራንስፖርትና ለማመንጫ ጣቢያዎች ጽዳት የሚወጣን ወጪ ከመቀነሱ ባሻገር ለዓለማችን ስጋት ከሆነው የግሪን ጋዝ ልቀትና የአካባቢ ብክለት ነጻ የሆነ ኃይል ለማምረት ያስችላል። በግንባታው የመጀመሪያ ወቅት ወጪው ከፍተኛ ቢሆንም በማመንጨት ሂደቱ በቀጥታ ለጥቅም መዋሉ ተመራጭና ርካሽ አማራጭ ያደርገዋል። እንግዲህ ዮሐንስ በአንድ አቅጣጫ ትኩረት ከሚያደርጉ ይልቅ የተለያዩ መረጃዎችን መመልከት ቢችሉ ፅሁፋቸውን በመረጃ የበለጸገ ለማድረግ በረዳቸው ነበር።
የጂኦተርማል ኢነርጂን ማልማት ለወደፊቱ ተመራጭና ተደራሽነቱም አስተማማኝ እንደሚሆን ተተንብይዋል።አገራት የወደፊቱን የኢነርጂ አማራጫቸውን በታዳሽ ኢነርጂ ላይ እንደሚያደርጉ የወቅቱ የዓለም አየር ንብረት ለውጥ እያስገደዳቸው እንደሆነ በግልፅ እየታየ ነው። በዓለማችን የጂኦተርማል ኢነርጂን በማልማት  በቀዳሚነት 24 አገራት ከዚህ የኃይል ምንጭ ተጠቃሚዎች ሆነዋል፡፡
በዓለም ዓቀፍ ደረጃ 12.8 ጌጋ ዋት አቅም ያለ ሲሆን ከዚህም ውስጥ 28 በመቶውን ማለትም 3‚548 ሜጋ ዋት ኃይል በማመንጨት አሜሪካ በመሪነት ደረጃ ላይ ትገኛለች፡፡ ፊሊፒንስ 1‚904 ሜጋ ዋት፣ ኢንዶኔዥያ 1‚222 ሜጋ ዋት በማመንጨት በሁለተኛና ሦስተኝነት ይከተላሉ፡፡ በቀጣዮቹ ዓመታትም የዘርፉ አቅም ከ14.5-17.6 ጌጋ ዋት እንደሚደርስ ይገመታል።

      አንዳንድ ታሪክ ካልተደጋገመ ሰሚ አያገኝም፡፡ የሚከተለው እንደዚያ ነው፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ጋብሮቮ ወደ ሩቅ መንደር ሄዶ ሲመለስ ብርቱካን ይዞ መጣ፡፡ የመንደሩ ሰዎች “ብርቱካን ስጠን”፣ “ስጠን” እያሉ አስቸገሩት፡፡
ጋብሮቮው እንዲህ አላቸው፡-
“የሰፈሬ ህዝብ ሆይ! የእኔን በጣት የምትቆጠር ብርቱካን ከምትለምኑ ለምን ከዋናው ቦታ ሄዳችሁ እንደ እኔ ፋንታችሁን አትወስዱም?”
የሰፈሩ ሰዎችም፤
“ዋናው ቦታ ወዴት ነው?” አሉት፡፡
ጋብሮቮውም፤
“ማዶ ያለው መንደር ብርቱካን በነፃ እየታደለ‘ኮ ነው!”
“አትጠራጠሩ ይልቅ ቶሎ ብላችሁ ሩጡ፡፡ በገፍ እየተሰጠ ነው!”
ህዝቡ ጋብሮቮው ያለውን በማመን ወደተባለው መንደር መሮጥ ጀመሩ፡፡
መንገድ ላይ ያሉ ሌሎች ሰዎች የሚሮጡትን ሰዎች ይጠይቋቸዋል፡፡
“ወዴት ነው የምትሮጡት?”
“እማዶ ካለው መንደር ብርቱካን እንደጉድ በነፃ ይታደላል”
እነዚህኞቹም የተባለውን አምነው መሮጥ ጀመሩ፡፡ ቀስ በቀስ የመንደሩ ህዝብ በጠቅላላ መሮጥ ቀጠሉ፡፡
ጋብሮቮው ዘወር ብሎ ሲመለከት አገር በሙሉ በአንድ አቅጣጫ ሲሮጥ አየ፡፡
ይሄኔ ጋብሮቮ ሆዬ፤
“እንዴ! ይሄ ነገር እውነት ይሆን እንዴ?” ብሎ ወደ ህዝቡ ሩጫውን ቀጠለ፡፡
***
ራሳችን በፈጠርነው ህልም ራሳችን ከመወናበድ ይሰውረን፡፡ ራሳችን የወለድነውን ልጅ የእኛ አይደለም ከማለትም ያድነን፡፡ የራሳችን ውሸት እውነት መስሎን ዳግመኛ ከመሳሳት አምላክ መልካሙን ያሳየን፡፡
“ዕድለ ቢስ ወፍ ማሽላ ሲያሸት ትታወራለች” ይባላል፡፡ አንዳንድ ታጋይ በሚበላበት ሰዓት ከቦታው ይሰናበታል፡፡ አንዳንድ የተማረ ሰው የሱ ሙያ ሲያብብ እሱ ይጠወልጋል፡፡
“ያውና እዛ ማዶ ብርሃን ያድላል
አሁን እኔ ብሄድ አለቀ ይላሉ” እንዳለው ነው ዐይነ ስውሩ ለማኝ፡፡
የተነገረውን ሁሉ በደፈናው የሚያምኑ የዋሃን፤ አሳዛኝ ናቸው! ህዝብ፤ ማንም ሹመኛ፣ ምሁር፣ ጊዜያዊ አለቃ፣ አውቃለሁ ባይ አፈ-ቀላጤ ወዘተ ተናገረ በሚል ሙሉ እምነቱን ዋና ማተብ አድርጐ እንዳፈተተ መጓዝ የለበትም፡፡ ቀልቡን ገዝቶ፣ ነፍሱን አግዝፎ መንቀሳቀስ ይኖርበታል፡፡ ግዙፉን ነገር፣ ማቴሪያሉን ብቻ ሳይሆን መንፈሱን ማሰብ ቁልፍ ነገር ነው፡፡
ስለ ሹመትና ስለ ሃላፊነትም ስናስብ፤
“በግራም ወጣ ወደ ኮርቻ፣ በቀኝም ወጣ ወደ ኮርቻ”፤ እንደተባለው ተረት ውስጠቱን ማስተዋል ይገባናል፡፡
እንደ ጋብሮቮው፤ እኛው በፈጠርነው የጥንቃቄ ኢኮኖሚ ተገዝተን፣ እኛው መልሰን ተታልለን፣ “ለካ ልክ ነበርን፣ ህዝብ ከእኛ ጋር ነው” ብለን መሞኘት የለብንም፡፡
የእኛን የፖለቲካ ወዳጆች፣ አባሎች፣ አጋሮች፣ እንከንና ስህተት፣ ጥበት እና ትምክህተኝነት፣ በቅጡ አስተውለን፣ እነሱም መክረው፣ ዘክረውና አምነው ነው ወደፊት ተጉዘናል ማለት ያለብን፡፡ “እከክልኝ ልከክልህ” እንደማይሰራ ሁሉ፤ “ወገኔ ነው በዚህ እንኳ ይጠቀም” ማለትም በፍፁም አይሰራም!
አገራችንን ጉድ ያደረጋት የመዓት ዝምድና ገመድ ትብትብ ነው፡፡
የማህበረሰብ ግንዛቤያችንን ከፖለቲካና ኢኮኖሚ ግንዛቤ ይልቅ በባህል ዙሪያ ማሰብ ትልቅ ፍሬ አለው፡፡ ለዚህ በዓለም ላይ ያለውን ባህልና የሃይማኖት ጦርነት ስራዬ ብሎ ማስተዋል አንዳች ዋጋ አለው፡፡ ባህል ምን ያህል ዋጋ ቢኖረው ነው ዓለም በጠቅላላው ባህል ያላቸውን ሀገሮች ጦርነት ውስጥ እየዘፈቀች ለጥፋትም እየዳረገቻቸው ያለው፡፡ (ሶርያ፣ ኢራቅ፣ ግብፅ፣ የመን፣ ወዘተ ልብ ይሏል) ብሎ መጠየቅ የአባት ነው! ሃይማኖትስ ምን ያህል የጠብ ጫሪነት ነዳጅ ቢኖረው ነው ሃይማኖት ያላቸው ሀገሮች ለጦርነት እንዲዳረጉ ማገዶ የሚሆነው? ብሎ ማሰብ ብልህነት ነው፡፡
ዘመን እየተለወጠ ሲመጣ ሰዓሊው አዲስ ምስል፣ ገጣሚው አዲስ ምንባብ፣ ደራሲው አዲስ መጽሀፍ፣ ፖለቲከኛው አዲስ ግንዛቤ፣ መንግስት ደግሞ አዲስ ዕቅድ ሊያመጣ ይጠበቃል፡፡ የትላንቱን ካነበብን፣ የትላንቱን መንገድ ከደረትን፣ ሌላው ቀርቶ የትላንቱን ሳቅ ከሳቅን አዲስ ሳቅ ነጠፍን ማለት ነው፡፡ “ብትናገር ያምናውን፣ ብትፈትል አንድ ልቃቂት” የሚለው ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ነው፡፡

• በቅዱስ ዐማኑኤልና በአቡነ አረጋዊ አድባራት፤ አስተዳደሩና ሰበካ ጉባኤያት ተፋጠዋል
• ፓትርያርኩ የመሩበት ጥናታዊ ሪፖርት ለቋሚ ሲኖዶሱ ይኹንታ አለመቅረቡ አነጋጋሪ ኾኗል


    በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በርካታ አድባራት፣ የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናትን መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት በበላይነት ለመምራትና ለመቆጣጠር ሥልጣንና ተግባር ያላቸው የሰበካ መንፈሳዊ አስተዳደር ጉባኤ አባላት፣ በሙስናና ብልሹ አሠራር በሚታሙ የአስተዳደር ሓላፊዎች መታገዳቸው አደገኛ አዝማሚያ እየያዘ መምጣቱ ተገለጸ፡፡ ሀገረ ስብከቱም ተጣርተው በሚቀርቡለት ሪፖርቶች ላይ አፋጣኝ ውሳኔ አለመስጠቱ “ትክክለኛ መፍትሔ የማግኘት ተስፋችንን አዳክሞታል፤” ይላሉ ምእመናኑ፡፡ባለፉት ሦስት ወራት ለአዲስ አድማስ የደረሱ ጥቆማዎች እንደሚያስረዱት፤ የሰበካ ጉባኤያቱ ምክትል ሊቃነ መናብርት፣ ከሓላፊነት ይታገዳሉ አልያም በአስተዳደር ተግባር የመሳተፍ ድርሻቸው ተዳክሞ ደመወዝና ሥራ ማስኬጃ በመፈረም ብቻ ተወስኗል፡፡ ከአስተዳደሩ ሓላፊዎች የተለየ ሐሳብ የሚያነሡ የማኅበረ ካህናት ተወካዮች፤ ከሥራና ከደመወዝ ይታገዳሉ፤ ከፈቃዳቸው ውጭ ወደ ሌሎች አድባራት ዝውውር ይጠየቅባቸዋል፤ የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራንና የንብረት አመዘጋገብን አጥብቀው የሚቆጣጠሩ የማኅበረ ምእመናን ተወካዮች ከአባልነት ከመታገዳቸውም በላይ “ለማበጣበጥ እየሠሩ ነው፤ አሸባሪዎች ናቸው” በሚል ለመንግሥታዊ አስተዳደርና የፍትሕ አካላት ክሥ ይቀርብባቸዋል ተብሏል፡፡
በደብረ ከዋክብት አቡነ አረጋዊና ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን፣ አስተዳዳሪው፤ የሰበካ ጉባኤውን ውሳኔ እንደማይተገብሩ የጠቆሙ ምዕመናን፤ በምክትል ሊቀ መንበሩ የማይታወቁ የባንክ ሂሳቦችን በደብሩ ስም እንደሚያንቀሳቅሱ፣ አግባብነት የሌለው የሠራተኞች ዕድገትና ዝውውር እንደሚፈፅሙ ተናግረዋል፡፡
አስተዳዳሪው ቀደም ሲል የቤተ ክርስቲያንን መሬት ለግል ጥቅም በማዋላቸው ከሓላፊነት ታግደው እንደነበር ያስታወሱት ምእመናኑ፤ ደብሩ ለሀገረ ስብከቱ መክፈል የሚገባውን የኻያ ፐርሰንት ፈሰስ ሳይከፍሉ በመቅረታቸው ለዕዳ እንደዳረጉት ይናገራሉ፡፡ የሰበካ ጉባኤው አባላት፣ በማኅበረ ካህናቱ ተቀባይነት እንዳይኖራቸው በተወላጅነት እንደሚከፋፍሉና ካህናቱን ከደመወዝና ከሥራ በማገድ ለችግር እንደሚያጋልጧቸው ምዕመናኑ ይገልፃሉ፡፡
የአለመግባባቱ መንሥኤ፣ የሰበካ ጉባኤው አባላት የደብሩን ገቢና ወጪ አጥብቀው በመቆጣጠራቸውና የፋይናንስ ሪፖርት፤ በመጠየቃቸው እንደኾነ የሚገልጸው የክፍለ ከተማው ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ሪፖርት አባላቱ፣ ደመወዝ ፈርሞ ከማውጣት ውጭ በውሳኔ አሰጣጥ ረገድ በቃለ ዐዋዲው በተሰጣቸው ሥልጣንና ተግባር እየተሳተፉ እንዳልኾነ አረጋግጧል፡፡ የአስተዳዳሪውን አልታዘዝ ባይነት የሚገልጸው ሪፖርቱ፤ ለሀገረ ስብከቱ ማስተላለፉን ቢያውቁም ምንም ዐይነት ምላሽ አለመሰጠቱ ግራ እንዳጋባቸው - ምእመናኑ ይናገራሉ፡፡
በተመሳሳይ አኳኋን ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በቅርቡ ባካሔደው የሕንጻ እና የመሬት ኪራይ ተመን ጥናታዊ ሪፖርት ከበድ ባለ ሙስና የተተቸው የደብረ ገሊላ ቅዱስ ዐማኑኤል አስተዳደር፤ ከሙዳየ ምጽዋት ቆጠራና ከንብረት ሽያጭ ጋር በተያያዘ ከምእመናኑ ጋር ፍጥጫ ውስጥ ገብቷል፡፡ በየካቲት 2007 የተመረጠው ሰበካ ጉባኤ፣ የደብሩን የአሠራር ክፍተቶች በመቅረፍ ገቢውን በተሻለ መልኩ ለመቆጣጠርና ለማሳደግ ቢንቀሳቀስም አንድ የካህናት ተወካይ ከሥራና ከደመወዝ፣ ኹለት የምእመናን ተወካዮች ደግሞ ከአባልነት መታገዳቸው ውዝግቡን እንዳካረረው ተጠቅሷል፡፡
የቤተ ክርስቲያኒቱን ሀብትና ንብረት ለመጠበቅ ሲባል ካህናትና ምእመናን የሥራ ሓላፊነታቸውንና የቤተ ክርስቲያን ልጅነት ግዴታቸውን ለመወጣት በሚያደርጉት ጥረት ለሚፈጠርባቸው ዕንቅፋት ሀገረ ስብከቱ ሓላፊነት እንደሚወስድ ቢገልጽም ልኡካኑ ችግሩን ለመፍታት ባለመቻላቸው “ትክክለኛ መፍትሔ የማግኘት ተስፋችንን አዳክሞታል፤ ለሚደርሰው ማንኛውም ጥፋት ተጠያቂዎች አንኾንም” ሲሉ ምእመናኑ አሳስበዋል፡፡
በብሥራተ ገብርኤል፣ በካራ ቆሬ ፋኑኤል፣ በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም፣ በላፍቶ ቅዱስ ሚካኤል፣ በፉሪ ቅዱስ ገብርኤል፣ በደብረ ሲና እግዚአብሔር አብ፣ በሰሚት ቅ/ጊዮርጊስ፣ በሰሚት ኪዳነ ምሕረት፣ በሰሚት ቅ/ሩፋኤል፣ በጨፌ አያት ቅ/ገብርኤል፣ በአያት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፣ በፉሪ ቅ/ዑራኤል እና በሰሚት መድኃኔዓለም ከሰበካ ጉባኤ አባላት የሥራ ጊዜ መጠናቀቅ፣ የካህናትና ምእመናኑን ከአስተዳደሩ ጋር አለመግባባት ውዝግብ እንደፈጠረ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ የሰበካ ጉባኤ አባላት በሥልጣናቸው አለመሥራት፣ የአስተዳደር ሓላፊዎች ብቃት ማነስ፣ ሙስና እና ብልሹ አሠራር እንዲኹም የስብከተ ወንጌል እንቅስቃሴ መዳከም በዐበይት መንሥኤነት ተዘርዝረዋል፡፡
በተያያዘ ዜና፣ ቋሚ ሲኖዶሱ ይኹንታውን እንዲሰጥበት ፓትርያርኩ የመሩበትና ሙሰኛ የአድባራት ሓላፊዎች ምዝበራ በሕግ አግባብ እንዲታይ የሚጠይቀው የጠቅላይ ጽ/ቤቱ ጥናታዊ ሪፖርትና ውሳኔ በአጀንዳነት አለመቅረቡ አነጋጋሪ ሆኗል ተባለ፡፡
የቅዱስ ሲኖዶስ አስፈጻሚ አካል የኾነውና በፓትርያርኩ ሊቀመንበርነት የሚመራው ቋሚ ሲኖዶሱ፣ በዚኽ ሳምንት መደበኛ ስብሰባው ይኹንታውን እንደሚሰጥበት ቢጠበቅም፤ የቅዱስ ሲኖዶሱ ዋና ጸሐፊ የፓትርያርኩ ምሪት እንዳልደረሳቸው በመግለጻቸውና የተመራበት ሰነድም የትኛው አካል ጋር እንዳለ በስብሰባው ወቀት ባለመታወቁ በአጀንዳነት ሳይቀርብ መቅረቱን የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ምንጮች ተናግረዋል፡፡
ዘግይቶ በደረሰን ዜና፣ ጥናታዊ ሪፖርቱና የውሳኔው ቃለ ጉባኤ ትላንት ከቀትር በኋላ ለብፁዕ ዋና ጸሐፊ አሁነ ሉቃስ ዘግይቶ በመድረሱ በቀጣይ ሳምንት ማክሰኞ በአጀንዳነት ቀርቦ ይኹንታ እና የአፈጻጸም አቅጣጫ የሰጥበታል ተብሎ እንደሚጠበቅ ምንጮቹ ጠቁመዋል፡፡

     ከአንድ ወር በፊት ኢትዮጵያን የጎበኙት የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ በአዲስ አበባ በነበራቸው የሁለት ቀናት ቆይታ ለሆቴል 1.3 ሚ. ዶላር ማውጣታቸውን ዊክሊ ስታንዳርድ ድረገጽ ከትናንት በስቲያ ዘገበ፡፡
ኦባማ እና አብረዋቸው የመጡ የደህንነትና የልኡካን ቡድን አባላት በአዲስ አበባ በሚገኙ አራት ሆቴሎች ማረፋቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ በሁለት ቀናት ቆይታቸው ለሆቴሎቹ በድምሩ 1.3 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር መከፈሉን ገልጿል፡፡የጉብኝቱ አዘጋጆች በመጀመሪያ ከሂልተን ሆቴል ጋር የ412ሺ 390 ዶላር ውል መፈጸማቸውንና በቀጣይም ከኢሊሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል ጋር የ246ሺ 877 ዶላር፣ ከካፒታል ሆቴልና ስፓ ጋር ደግሞ የ178ሺ 433 ዶላር ውል መፈጸማቸውን የጠቀሰው ዘገባው፤ በመጨረሻም ከሸራተን አዲስ ሆቴል ጋር የ488ሺ 141 ዶላር ስምምነት መፈጸማቸውን ጠቁሟል፡፡የልኡካን ቡድኑ አባል የሆነ አንድ የዋይት ሃውስ ፎቶ ግራፍ አንሺን እማኝነት በመጥቀስ ዘገባው እንዳለው፣ ኦባማ በሁለት ቀናት ቆይታቸው ያረፉት በሸራተን አዲስ ሆቴል እንደነበር መረጋገጡንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡

     በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ከሚገኙ የተለያዩ ትምህርት ቤቶች ከፍተኛ ነጥብ አምጥተው ዩኒቨርሲቲ ለገቡ ከ2 ሺ 500 በላይ ሴት ተማሪዎች ትላንት የሽኝት ፕሮግራም ተደረገ፡፡
“ዘር ኢትዮጵያ” በተባለ ድርጅት በአፍሪካ ህብረት አዳራሽ በተካሄደው ፕሮግራም፤ በተለያዩ የሥራ መስኮች ስኬታማ የሆኑ ሴቶች ለተማሪዎቹ ከህይወት ልምድና ተሞክሮአቸው አካፍለዋል፡፡
ሴት ተማሪዎቹ በዩኒቨርሲቲ ቆይታቸው የሚገጥሟቸውን በርካታ ችግሮችና መሰናክሎች በአሸናፊነት ለመወጣት የዓላማ ፅናት ሊኖራቸው እንደሚገባ የተነገራቸው ሲሆን ለዚህም ከወዲሁ ራሳቸውን ማዘጋጀት እንደሚኖርባቸው ምክር ተለግሰዋል፡፡ለወጣት ተማሪዎቹ የህይወት ልምድና ተሞክሮአቸውን ካጋሩ ስኬታማ ሴቶች መካከል የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የኢንፎርሜሽን ሲስተም ምክትል ፕሬዚዳንት ወ/ሮ መሊካ በድሪ፣ በመከላከያ ሚኒስቴር የስነ ምግባር መከታተያ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ብ/ጄ ዘውዱ ኪሮስና  የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢንጂነር አዜብ ወርቁ ይጠቀሳሉ፡ሽኝት የተደረገላቸው ሴት ተማሪዎች በአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ በኩል የተመረጡ መሆናቸው ታውቋል፡፡
የፕሮግራሙ አዘጋጅ “ዘር ኢትዮጵያ”፤ አራት መቶ ሴትና አንድ መቶ ወንድ ተማሪዎችን በየወሩ 200 ብር ድጋፍ እያደረገ ትምህርታቸውን እንዲከታተሉ የሚያበረታታ ሲሆን በቀጣዩ ዓመት ድጋፍ የሚደረግላቸውን ተማሪዎች ቁጥር ወደ  1000 ለማድረስ እቅድ መያዙ ተገልጿል፡፡  

     በመዲናዋ ባሉ ክፍለ ከተሞች በተመረጡ 10 ወረዳዎች ከ40 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ዘመናዊ የሰፈሮቹ የአድራሻና አቅጣጫ መጠቆሚያ ስርአት ሊዘረጋላቸው እንደሆነ እያካሄደ መሆኑን የአዲስ አበባ አስተዳደር የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ አስታወቀ፡፡
የቢሮው የኮሙኒኬሽን የሥራ ሂደት መሪ አቶ ማርቆስ አለማየሁ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፤ ዝርጋታው አቅጣጫ ጠቋሚ ምልክቶችን፣ ብሎክና የቤት ቁጥር ታፔላዎችን ያካትታል፡፡ የአድራሻ ስርዓቱ በዋናነት ለፖስታ አገልግሎት፣ የእሳት አደጋ መኪኖች ፈጥነው እንዲደርሱ እንዲሁም የአምቡላንስ አገልግሎት ለማግኘትና ወንጀልን ለመከላከል ወሳኝ መሳሪያ ይሆናል ተብሏል፡፡
ስርአቱን ለመዘርጋትም ካርታ የማዘጋጀት ስራ ሲከናወን የቆየ ሲሆን ታፔላዎቹ ደረጃቸውን ጠብቀው እንዲመረቱ ከብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን፣ ከህብረት ማኑፋክቸሪንግ ማሽን ኢንዱስትሪ ጋር የ40 ሚሊየን ብር ውል መገባቱን የጠቆሙት አቶ ማርቆስ፤ አሁን የስራው የመጀመሪያ ምዕራፍ ወደ ሆነው ምልክት ተከላ ተሸጋግሮ ስራው እየተገባደደ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡
ከአስሩም ክፍለ ከተሞች አንድ አንድ ወረዳ የተመረጠ ሲሆን ለአብነትም ጉለሌ ወረዳ 10፣ የካ ወረዳ 13፣ ቂርቆስ ወረዳ 2 እና አዲስ ከተማ ወረዳ 9ን ጠቅሰዋል፡፡ የእነዚህ ወረዳዎች ተከላ እንደተጠናቀቀም 30 የሚሆኑ ወረዳዎች ላይ ወደ ተግባር ለመግባት በዝግጅት ላይ ነን ብለዋል - የሥራ ሂደት መሪው፡፡

መንግስት ለአስቸኳይ እርዳታ 33 ሚ. ዶላርቢያሰባስብም፣ ተመድ 230 ሚ. ዶላር ያስፈልጋል ብሏል
• “አብዛኛው ተረጂ የሚገኘው በኦሮምያ ክልል ነው”

   የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በኢትዮጵያ በተከሰተው የዝናብ እጥረት ሳቢያ የምግብ እህል እርዳታ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች ቁጥር ከዚህ በፊት ከተገመተው በላይ በከፍተኛ ሁኔታ ማደጉንና 4.5 ሚሊዮን መድረሱን አስታወቀ፡፡
አንድ ከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣን በበኩላቸው፤ ችግሩን ለመፍታት ክልሎች ራሳቸው ከሚመድቡት በጀት በተጨማሪ መንግሥት 700 ሚ. ብር መድቦ ለተረጂዎች ድጋፍ ለማድረግ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ጠቅሰው ከተረጂዎች መካከል 40 በመቶ ያህሉ በኦሮምያ ክልል እንደሚገኙ ገልፀዋል፡፡የተመድ የሰብዓዊ ጉዳዮች ትብብር ቢሮ ያወጣውን ሪፖርት ጠቅሶ አጃንስ ፍራን ፕሬስ ትናንት እንደዘገበው፣ በአመቱ የዝናብ መጠኑ ከተገመተው በታች መሆኑን ተከትሎ የምግብ እርዳታ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች ቁጥር ከተገመተው 2.9 ሚሊዮን የ55 በመቶ ጭማሪ በማሳየት 4.5 ሚሊዮን ደርሷል፡፡
በኢትዮጵያ የተመድ የሰብዓዊ ጉዳዮች ትብብር ቢሮ ሃላፊ ዴቪድ ዴል ኮንቴ እንዳሉት፤ በዝናብ እጥረቱ ክፉኛ የተጎዱት የአገሪቱ አካባቢዎች ምስራቃዊ አፋርና ደቡባዊ ሶማሌ ክልሎች ሲሆኑ በአንዳንድ የኦሮምያ፣ የትግራይና የአማራ ክልሎች አካባቢዎችም፣ ባልተለመደ ሁኔታ የከብቶች ግጦሽና የውሃ ሃብቶች እጥረት ተከስቷል፡፡በአሜሪካ መንግስት የሚደገፈው “ፋሚን ኧርሊ ዋርኒንግ ሲስተምስ ኔትወርክ” የተባለ የርሃብ ቅድመ ማስጠንቀቂያ የሚሰጥ ተቋምም፤ በኢትዮጵያ በርካታ እንስሳት በመኖ እጥረት ተጠቂ ሊሆኑ እንደሚችሉ ማስጠንቀቁንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡የኢትዮጵያ መንግስት ለአስቸኳይ የምግብ እርዳታ 33 ሚሊዮን ዶላር አሰባስቧል ያለው ዘገባው፤ ይሄም ሆኖ ግን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፣ መንግስት በመጪዎቹ አራት ወራት ጊዜ ውስጥ 230 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልገው ማስታወቁን አመልክቷል፡፡የእርዳታ ሰጪ ድርጅቶች ሃላፊዎች ችግሩ በተከሰተባቸው አካባቢዎች ምግብ የማከፋፈሉ እንቅስቃሴ ፈጣን አለመሆኑ እንዳሳሰባቸው ጠቁሞ፣ ለዚህ ችግር መከሰት አስተዋጽኦ ካበረከቱ ጉዳዮች መካከልም በጅቡቲ ወደብ ያለው መጣበብ አንዱ ነው ብሏል፡፡

- ፖሊስ በህገ ወጥነት የተጠረጠሩ 66 ሺህ ያህል ድረ ገጾችን እየመረመረ ነው
       - ቻይናውያን በአሜሪካ ላይ 700 ያህል የኢንተርኔት ጥቃቶችን ፈጽመዋል


     የቻይና ፖሊስ የአገሪቱን ደህንነት አደጋ ላይ በሚጥሉ አገር አቀፍና አለማቀፍ የኢንተርኔት ወንጀል ተግባራት ላይ ተሰማርተው ተገኝተዋል ያላቸውን 15 ሺህ ያህል ዜጎች በቁጥጥር ስር ማዋሉን ባለፈው ማክሰኞ ማስታወቁን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
የቻይና የደህንነት ሚኒስቴርን መረጃ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ የአገሪቱ ፖሊስ ከኢንተርኔት ጋር የተያያዙ 7 ሺህ 400 የወንጀል ክሶችን ሲመረምር ቢቆይም የተጠቀሱት 15 ሺህ ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር የዋሉት በምን ያህል ጊዜ ውስጥ እንደሆነ አልገለጸም፡፡
የቻይና መንግስት ባለፈው ወር ኢንተርኔትን ማጽዳት የተሰኘ መሰል ወንጀሎችን መከላከል የሚያስችል የስድስት ወራት ብሄራዊ ዘመቻ ተግባራዊ ማድረግ መጀመሩን የጠቆመው ዘገባው፤ ተጠርጣሪዎችን በማሰር የተጀመረው እርምጃ በቀጣይም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የአገሪቱ የደህንነት ሚኒስቴር ማስታወቁን ገልጿል፡፡
ዘመቻው በኢንተርኔት የሚሰሩ ወንጀሎችን ከመከታተልና ተጠርጣሪዎችን ለፍርድ ከማቅረብ በተጨማሪ ተደራጅተው በኢንተርኔት ወንጀል የሚሰሩ ቡድኖችን የማጥፋት ተልዕኮ እንዳለውም ዘገባው ጠቁሟል፡፡
የቻይና ፖሊስ ህገወጥና ጉዳት የሚያስከትሉ መረጃዎችን በሚያስተላልፉ እንዲሁም የወሲብ፣ የጦር መሳሪያዎችና የቁማር ማስታወቂያዎችን በሚያሰራጩ 66 ሺህ ያህል የአገሪቱ ድረገጾች ላይ ምርመራ ሲያደርግ መቆየቱንም አስረድቷል፡፡
ኤንቢሲ ኒውስ በበኩሉ፤ የተደራጁ ቻይናውያን የኢንተርኔት ዘራፊዎች የአሜሪካን ከፍተኛ የደህንነት ባለስልጣናት የኢሜይል ቁልፍ ሰብረው በመግባት የተለያዩ የወንጀል ድርጊቶችን እንደፈጸሙ መረጋገጡን ዘግቧል፡፡
ቻይናውያን የኢንተርኔት አጭበርባሪዎች ባለፉት አምስት አመታት በአሜሪካ ላይ ለ700 ጊዜያት ያህል ጥቃት ፈጽመዋል ያለው ዘገባው፤ ከ600 በላይ የሚሆኑት ስኬታማ ጥቃቶች የተፈጸሙትም በአሜሪካ የመንግስት፣ የግልና የኩባንያ ድረገጾችና የኢሜል አድራሻዎች ላይ መሆኑንም ገልጿል፡፡

20 ኪሎ ሜትር ቁመት ይኖረዋል፣ “የጠፈር አሳንሰር” ይገጠምለታል
   ቶዝ ቴክኖሎጂ የተሰኘው የካናዳ የጠፈር ምርምር ቴክኖሎጂ ኩባንያ በዓለማችን ትልቁ እንደሚሆን የተነገረለትንና 20 ኪሎ ሜትር ቁመት ያለውን ሰማይ ጠቀስ ማማ በመገንባት፣ ረጅሙን የጠፈር አሳንሰር ሊዘረጋ መሆኑን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
የጠፈር ተመራማሪዎችን ያለ መንኮራኩር በቀጥታ ወደ ጠፈር ማጓጓዝ የሚችለው  አሳንሰር፤ ጠፈርተኞችን በመንኮራኩር ወደ ጠፈር ለመውሰድ ከሚያስፈልገው ነዳጅ 30 በመቶ ያህል ያነሰ ነዳጅ እንደሚጠቀምና ወጪ ቆጣቢ እንደሆነ ተገልጿል፡፡
የጠፈር አሳንሰሩ ዲዛይነር የሆኑት ዶ/ር ብሬንዳን ኩይኔ እንዳሉት፣ ጠፈርተኞች በአሳንሰሩ ተሳፍረው ከመሬት በ20 ኪሎሜትሮች ርቆ ከሚገኘው የማማው አናት ላይ ከወጡ በኋላ፣ በቀላሉ በጠፈር አውሮፕላኖች እየተሳፈሩ ወደ ጠፈር ጠልቀው የሚገቡበትና ስራቸውን የሚያከናውኑበት ዕድል ይፈጠርላቸዋል፡፡
አሳንሰሩ የሚገጠምበት ሰማይ ጠቀስ ማማ፣ በአሁኑ ወቅት የአለማችን ረጅሙ ህንጻ በመሆን ክብረ ወሰን ይዞ ከሚገኘውና 830 ሜትር ርዝማኔ ካለው የዱባዩ ቡርጂ ከሊፋ ህንጻ በ20 እጥፍ ያህል ቁመቱ እንደሚረዝም የጠቆመው ዘገባው፤ ማማው  ከዚህ በተጨማሪም ለነፋስ ሃይል ማመንጫነት፣ ለኮሙኑኬሽንና ለቱሪዝም አገልግሎት እንደሚውልም ገልጿል፡፡
ማማው ቁመተ ረጅም ከመሆኑ ጋር በተያያዘ በንፋስ የመገንደስ አደጋ ሊገጥመው አይችልም ወይ ለሚለው የብዙዎች አስተያየት ምላሽ የሰጡት የኩባንያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ካሮሊን ሮበርትስ፤ ስጋት አይግባችሁ፣ መሰል አደጋዎችን መቋቋም እንዲችል አድርገን ነው ንድፉን የሰራነው ብለዋል፡፡
የአሜሪካ የፈጠራ መብቶች ቢሮ፤ የካናዳው ኩባንያ ላቀረበው ልዩ የሆነ የጠፈር ማማና አሳንሰር ፈጠራ እውቅና መስጠቱንና ፕሮጀክቱም ተቀባይነት ማግኘቱን ዘገባው አክሎ ጠቁሟል፡፡ 

  ፌስቡክ  በግማሽ ደቂቃ 5 ሺ 483 ዶላር ገቢ ያገኛል

   በድረ-ገጾች አማካይነት በአለማቀፍ ደረጃ የሚከናወነው “የኤሌክትሮኒክ ንግድ” በየግማሽ ደቂቃው በድምሩ የ1.2 ሚሊዮን ዶላር ገቢ እያስገኘ መሆኑ በጥናት መረጋገጡን ዘ ሂንዱ ታይምስ ረቡዕ ዕለት ዘገበ፡፡
አሶቻም ዲሎይት የተባለው አለማቀፍ የጥናት ተቋም ሰሞኑን ይፋ ያደረገውን የጥናት ውጤት ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ በከፍተኛ ሁኔታ በመስፋፋት ላይ በሚገኘውና ትርፋማነቱ እየጨመረ በመጣው የኤሌክትሮኒክ ንግድ ከፍተኛ ገቢ እያገኙ ካሉት የአለማችን ታላላቅ ኩባንያዎች መካከል ቀዳሚነቱን የያዘው ታዋቂው የማህበራዊ ድረ-ገጽ ፌስቡክ ነው።
ፌስቡክ በኤሌክትሮኒክ ንግድ በየሰላሳ ሰከንዱ 5 ሺህ 483 ዶላር ገቢ ያገኛል ያለው ጥናቱ፤ ፒንተረስት እና ትዊተር የተባሉት የማህበራዊ ድረ ገጾችም በ4 ሺህ 504 እና በ4 ሺህ 308 ዶላር የግማሽ ደቂቃ ገቢ ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃዎችን የያዙ የአለማችን የኤሌክትሮኒክ ንግድ ገቢ ቀዳሚ ኩባንያዎች ናቸው ብሏል፡፡
ማህበራዊ ድረገጾች መስፋፋታቸው በአለማቀፍ ደረጃ በኤሌክትሮኒክ ንግድ ገቢና ትርፍ ረገድ ከፍተኛ እድገት እንዲመዘገብ ቁልፍ ሚና ተጫውቷል ያለው ዘገባው፤ ማህበራዊ ድረ ገጾቹ የኩባንያዎችን ምርቶችና አገልግሎቶች በተመለከተ ፈጣን መረጃዎችን በማሰራጨትና ንግዱን በስፋት በማቀላጠፍ ረገድ አስተዋጽኦ እንዳደረጉ ዘገባው ገልጿል፡፡
ኤሌክትሮኒክ የክፍያ ስርአቶች በስፋት መዘርጋታቸውም ንግድ በአለማቀፍ ደረጃ የተቀላጠፈ እንዲሆንና ገዢና ሻጮችን ለአደጋ ከሚያጋልጠው የካሽ ግብይት ወደ ኤሌክትሮኒክ ክፍያ ፊታቸውን እንዲያዞሩ ያደረገ ሲሆን የኤሌክትሮኒክ ንግድ እንዲስፋፋም የራሱን አስተዋጽኦ አበርክቷል ተብሏል፡፡