Administrator

Administrator

Saturday, 05 September 2015 09:54

የኪነት ጥግ

ዝነኛ ስትሆን ድክመትህ ሁሉ የሚጋነን ይመስለኛል፡፡
ማሪሊን ሞንሮ
ዝነኛ መሆን ሳይሆን ስኬታማ መሆን ነበር የምፈልገው፡፡
ጆርጅ ሃሪሰን
ዝነኞች ዕድሜ ልካቸውን ታዋቂ ለመሆን ሲለፉ ኖረው በኋላ ላይ እንዳይታወቁ ፊታቸውን በጥቁር መነፅር የሚሸፍኑ ሰዎች ናቸው፡፡
ፍሬድ አለን
የዝነኛ አማካይ የህይወት ዘመን በከሰል ማዕድን ማውጪያ ውስጥ ከሚሰራ ሰው በ20 ዓመት ያንሳል፡፡
ሞቢ
ምን መስራት እንደምፈልግ ብትጠይቁኝ - ዝነኛ መሆን አልፈልግም፤ እኔ የምሻው ትርጉም ያለው ለውጥ መፍጠር ነው፡፡
ሌዲ ጋጋ
የእኔ የስኬት መለኪያ ገንዘብ ወይም ዝነኝነት አይደለም፡፡ የስኬት መለኪያዬ ደስተኛነት ነው፡፡
ሉፔ ፊያስኮ
ዝነኛ ስትሆን ዓለም አንተንና መልካም ስምህን የራሱ ንብረት ያደርገዋል፡፡
ሜጋን ፎክስ
በመጀመሪያ የእግዜአብሔር ልጅ ነኝ፡፡ ዝነኛ ከመሆኔ በፊት የተጠመቅኩ ክርስትያን ነኝ፡፡
Mr.t
ወደፊት ሁሉም ሰው ለ15 ደቂቃ ዝነኛ ይሆናል
አንዲ ዋርሆል
ዝነኛ የመሆን አስከፊው ነገር የግል ህይወትህ መጣሱ ነው፡፡
ጀስቲን ቲምበርሌክ
ብዙ ባጨበጨቡ ቁጥር ደሞዝህ ያድጋል
አና ኸልድ

Saturday, 05 September 2015 08:53

የፀሐፍት ጥግ

(ስለ ግጥም)
- ግጥም በደስታ ተጀምሮ በጥበብ
ይቋጫል፡፡
ሮበርት ፍሮስት
- ማንኛውም ጤነኛ ሰው ያለ ምግብ
ለሁለት ቀ ናት ሊ ቆይ ይ ችላል፡፡ ያ ለ
ግጥም ግን አይሞከርም፡፡
ቻርለስ ባውድሌይር
- ለእኔም ለራሴ የማይገቡኝ ጥቂት
ግጥሞችን ፅፌአለሁ፡፡
ካርል ሳንድበርግ
- ሙዚቃን መተርጎም እንደማይቻል
ሁሉ፣ ግጥምንም መተርጎም
አይቻልም፡፡
ቮልቴር
- ለእኔ ግጥም ዓላማ ሆኖ አያውቅም፤
ፍቅር እንጂ፡፡
ኤድጋር አላን ፖ
- ዓይን የገጣሚ የማስታወሻ ደብተር
ነው፡፡
ጄምስ ረስል ሎዌል
- ግጥም የተጣራ ህይወት ነው፡፡
ግዌንዶሊን ብሩክስ
- ግጥም ከብርሃኑ መጨረሻ ያለው ዋሻ
ነው፡፡
ጄ. ፓትሪክ ሌዊስ
- ግጥም ል ክ እንደ ጨ ረቃ ም ንም ነ ገር
አያስተዋውቅም፡፡
ዊሊያም ብሊሴት
- ግጥም ሁሉ ቦታ አለ፤ የሚፈልገው
አርትኦት ብቻ ነው፡፡
ጄምስ ታት
- ግጥም ፈጠራ ነው፤ ገጣሚነት ዓለምን
ዳግም መፍጠር ነው፡፡
አሌክሳንድሬ ቪኔት
- ጸሎትህ ግጥም፤ ግጥምም ፀሎትህ
ሊሆኑ ይችላሉ፡፡
ቴሪ ጉይሌሜትስ
- ግጥም ግግር እሳት ነው፡፡
ጄ. ፓትሪክ ሌዊስ
- ግጥም ቢያንስ ውበት፤ ቢበዛ ራዕይ
ነው፡፡
ሮበርት ፊትዝጌራልድ
- በግጥም ትቀሰቅሳለህ፤ በስድ ፅሁፍ
ታስተዳድራለህ፡፡
ማርዮ ኩርኖ
- ግጥም ሙያ አይደለም፤ እጣ ፈንታ
ነው፡፡
ሚክሃዬል ዱዳን
- ገጣሚያን ዕውቅና ያልተሰጣቸው
ዓለም ህግ አውጪዎች ናቸው፡፡
ፔርሲ ባይሺ ሼሊይ

የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር፤ ከ900 በላይ የቤተ ክርስቲያኒቱን ልኡካን እያወያየ ነው
“እንደ ሌላው መድረክ አታስቡት፤ ለዓላማና ለለውጥ የሚደረግ ጉባኤ ነው” /ሚኒስትሩ/

      በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ ንብረቶች አላግባብ ሀብት ያፈሩና ለግል ጥቅማቸው ሲሉ ቤተ ክርስቲያኒቱን ለምዝበራ ያጋለጡ የአድባራት ሓላፊዎች ጉዳይ በሕግ እንዲታይ የቀረበውን ውሳኔ ቋሚ ሲኖዶስ አጸደቀ፡፡
በሙሰኛ የአድባራት ሓላፊዎች ላይ ለተላለፈው ውሳኔ መሠረት የኾነውንና በ58 አድባራት የገቢ ማስገኛ ተቋማት ዙሪያ በሚታዩ የአፈጻጸም ችግሮች ላይ የተዘጋጀውን ጥናታዊ ሪፖርት ያዳመጠው ቋሚ ሲኖዶሱ፣ የመፍትሔ ሐሳቦቹንም በሙሉ ድምፅ ተቀብሎ ለጠቅላይ ጽ/ቤቱ ተጨማሪ መመሪያዎችን ሰጥቷል፡፡
ለቤተ ክርስቲያኒቱ መገልገያነት ከመንግሥት የተሰጡ መሬቶች፣ የተገነቡ ሕንጻዎች፣ ሱቆች፣ መካነ መቃብርና ሌሎች የገቢ ማስገኛ ተቋማት ሕጋዊ፣ ፍትሐዊና ቤተ ክርስቲያኒቱን ተጠቃሚ በማያደርጉ ውሎች ለሦስተኛ ወገን እየተከራዩ ለግለሰቦች በመሸጥ ላይ እንደኾኑ ጥናታዊ ሪፖርቱ ይዘረዝራል፡፡የአድባራት ሓላፊዎች ጥፋት በሕግ አግባብ እየታየ ክሥ ለመመሥረትም፤ ጥናቱ በሸፈናቸው አድባራትና ገዳማት የተደረጉ ሕገ ወጥ ውሎች የተፈጸሙበትን ትክክለኛ ጊዜ፣ የወቅቱን የአካባቢ የመሬት ዋጋ፣ በውል አሰጣጡ የተሳተፉ ሓላፊዎችና የመሳሰሉት ዝርዝር መረጃዎች በጠቅላይ ጽ/ቤቱ ተጣርተው መታወቅ እንደሚገባቸው ቋሚ ሲኖዶሱ ለጠቅላይ ጽ/ቤቱ ተጨማሪ መመሪያ ሰጥቷል፡፡
በተያያዘ ዜና፣ የሀገረ ስብከቱን የአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ማኅበረ ካህናት፣ ሰባክያነ ወንጌል፣ የሰንበት ት/ቤቶች ሊቃነ መናብርት እና የአንድነት አመራሮች በተናጠል ሲያነጋግር የቆየው የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር፣ ከትላንት ጀምሮ ኹሉንም አካላት ያቀፈ የማጠቃለያ ውይይት በማካሔድ ላይ ነው፡፡
937 ያኽል የቤተ ክርስቲያኒቷ ልኡካን በሚሳተፉበት በዚኹ የኹለት ቀናት ውይይት፣ በሃይማኖት ተቋማት የውስጥ አሠራር ችግሮች ላይ ያተኰረ ጽሑፍ በሚኒስትሩ ዶ/ር ሺፈራው ተክለ ማርያም የቀረበ ሲኾን በቡድንና በጋራ ውይይት ይካሔድበታል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቀደምትና ጥንታዊት መኾኗን ያወሱት ሚኒስትሩ÷ በአካባቢና በጥቅመኝነት ላይ የተመሠረተ የሰው ኃይል አሿሿምና አመዳደብ፣ ግልጽነት በጎደለው የፋይናንስ ዝውውርና አጠቃቀም በውስጥ የሚነሣው አለመግባባት እየሰፋ መምጣቱ ጥያቄ እያስነሣ መሆኑን አብራርተዋል፡፡
እኔ ብቻ ልጠቀም በሚል ከሕግና ሥርዐቱ ውጭ የመንቀሳቀስ ስሜት በራሱ የሚፈጥረው አደጋ እንዳለ ያሳሰቡት ዶ/ር ሺፈራው፣ መድረኩም እንደሌላው መርሐ ግብር የሚታይ ሳይኾን ለዓላማና ለለውጥ የሚካሔድ የምክክር ጉባኤ ነው በማለት ውይይቱን ተከትሎ በተከታይ ሊወሰድ የሚችል ርምጃ እንደሚኖር ጠቁመዋል፡፡

ከፍተኛው የሆቴሎች ዋጋ ጭማሪ የታየው በሻርም አል ሼክ ነው

   ኤስ ቲ አር ግሎባል የተባለው አለማቀፍ የጥናት ተቋም በተለያዩ የአፍሪካ አገራት ከተሞች የሆቴሎች ዋጋ ዙሪያ ባደረገው ጥናት፤ አዲስ አበባ በሆቴሎች ዋጋ ውድነት ቀዳሚውን ደረጃ መያዟን ትናንት ባወጣው ሪፖርት መግለጹ ተዘገበ፡፡
ተቋሙ ይፋ ባደረገው የጥናት ውጤት፤ ባለፉት ስድስት ወራት በአዲስ አበባ ሆቴሎች ለአንድ መኝታ ክፍል ለአንድ ቀን አዳር በአማካይ 231.78 ዶላር ሲከፈል መቆየቱን ጠቁሞ፤ ይህም የከተማዋ ሆቴሎች ዋጋ ከሌሎች የአፍሪካ ሆቴሎች የበለጠና እጅግ ውዱ መሆኑን እንደሚያሳይ ጋና ቢዝነስ ኒውስ ድረገጽ ዘግቧል፡፡
የናይጀሪያዋ ሌጎስ 215.75 ዶላር፣ የኬንያዋ ናይሮቢ 144.76 ዶላር፣ የደቡብ አፍሪካዋ ኬፕታውን 122.30 ዶላር ለአንድ አዳር በማስከፈል እስከ አራተኛ ያለውን ደረጃ መያዛቸውንም ዘገባው ጠቁሟል፡፡የአገሪቱ ኢኮኖሚ ላለፉት አስር ያህል አመታት በአማካይ ከ10 በመቶ በላይ ዕድገት ማስመዝገቡ፣ የተለያዩ አለማቀፍ ጉባኤዎችን ማስተናገዷ፣ የአፍሪካ ህብረት መቀመጫ መሆኗ እና በእድገት ላይ የሚገኘው የኢትዮጵያ አየር መንገድ የመዳረሻዎቹንና የተሳፋሪዎቹን ቁጥር ማሳደጉ፣ በአገሪቱ የዘመናዊ ሆቴሎች ፍላጎት እንዲጨምር አድርጓል ያለው ጥናቱ፣ ይሄም ሆኖ ግን አዲስ አበባ አሁንም ድረስ ከፍተኛ የጥራት ደረጃ ያላቸው ሆቴሎች እጥረት አለባት ብሏል፡፡ባለፉት 12 ወራት በአፍሪካ የተለያዩ ከተሞች የታዩ የሆቴሎች ዋጋ ጭማሪዎችን የዳሰሰው ጥናቱ፣ በተጠቀሰው ጊዜ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ የታየው በግብጹ የመዝናኛ ስፍራ ሻርም አል ሼክ መሆኑን ጠቁሞ፣ የዋጋ ጭማሪውም 42.5 በመቶ እንደሆነ ገልጿል፡፡በተጠቀሰው ጊዜ በሆቴሎች ዋጋ ላይ አዲስ አበባ የ14.9 በመቶ፣ ጆሃንስበርግ የ11 በመቶ፣ ኬፕታውን የ10.8 በመቶ ጭማሪ ማድረጋቸውንና በአንጻሩ ግን የካዛብላንካ ሆቴሎች ዋጋ በ4 በመቶ ቅናሽ ማሳየቱን አስታውቋል፡፡

    በሚዩንግ ሰንግ አጠቃላይ ሆስፒታል (ኮሪያ ሆስፒታል) የመድኀኒትና የህክምና መሳሪያዎች ክምችትና አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ሰሞኑን ድንገተኛ ፍተሻ የተካሄደ ሲሆን ከፍተሻው ጋር በተገናኘ ሆስፒታሉ ማብራሪያ እንዲሰጥ መጠየቁን ምንጮቻችን ገለፁ፡፡
ከምንጮቻችን ባገኘነው መረጃ መሠረት፤ የፌደራል የምግብ፣ የመድኃኒት የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን ባለፈው አርብ ድንገተኛ ፍተሻ በማድረግ በሆስፒታሉ ውስጥ የሚገኘውን የመድኃኒት ማከማቻ ክፍል ፣ የማደንዘዣ መድኃኒቶች ማስቀመጫ ክፍሎች፣ የህክምና መሳሪያዎችና ስቴራላይዝ ማድረጊያ ሥፍራዎችን አሽጎ ነበር፡፡ ባለፈው ሰኞ የባለሥልጣኑ ባለሙያዎች እሽጉን በመክፈት ምርመራቸውን ያከናወኑ ሲሆን በወቅቱ ስለተገኙ ነገሮች ፣ ስለ አሠራር ሒደቱ፣ እንዲሁምየ ሰራተኞችን የሙያ ብቃትና ፍቃድ የተመለከቱ መረጃዎች ሆስፒታሉ እንዲያቀርብ ደብዳቤ ተፅፎለታል፡፡በሆስፒታሉ በተደረገው ድንገተኛ ፍተሻ የተገኙት መድኃኒቶችና የህክምና መሳሪያዎች፤ በባለስልጣኑ እውቅናና ፈቃድ የሌላቸውና በባለስልጣኑ በኩል ተመርምረው ወደ አገር ውስጥ እንዲገቡ ፍቃድ ያልተሰጣቸው ናቸው ተብሏል፡፡
እነዚሁ መድኃኒቶችና ልዩ ልዩ የህክምና መገልገያ ቁሳቁሶችም በባለስልጣኑ የምርመራ ሰራተኞች የተወሰዱ ሲሆን፤ ሆስፒታሉ ስለእነዚህ ነገሮች በቂ ማብራሪያ እንዲሰጥ ተጠይቋል፡፡ ስለጉዳዩ ዝርዝር መረጃ ለማግኘት የፌደራል የምግብ የመድኃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን የሥራ ኃላፊዎችን ብንጠይቅም ጉዳዩ ገና በምርመራ ሂደት ላይ በመሆኑ መረጃ ለመስጠት እንደማይቻል ገልፀው የምርመራ ሂደቱን በተመለከተ ሪፖርት እየተዘጋጀ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡
አዲስ አድማስ ጋዜጣ ከዚህ ቀደምም በሆስፒታሉ አገልግሎት አሰጣጥ፣ በሰራተኞች አያያዝና በመድኃኒቶች አቅርቦት ዙሪያ የሚሰሙ ቅሬታና ችግሮችን የተመለከተ ዘገባ ማቅረቡ ይታወሳል፡፡

1. [የባራክ ኦባማ ጉብኝት፤ የትሪሊዮን ዶላሮች ጉባኤ፤ የ100% ምርጫ፤ ዘግናኞቹ ግድያዎች]
2. [የኤክስፖርት ድንዛዜ፣ “እድሜ ለዳያስፖራ”፣ የነዳጅ ዋጋ እና የሚኒስቴሩ አስገራሚ መግለጫ]

    በፖለቲካው መስክ፣ የባራክ ኦባማ ጉብኝትና የዩኤን የፋይናንስ ጉባኤ በበጎነት የሚጠቀሱ ክስተቶች ናቸው። በእርግጥ፣ የኦባማ የፖለቲካ ቅኝት፣ የአሜሪካ የነፃነትና የብልፅግና አርአያነትን ይወክላል ብዬ አላስብም።
እንደ ኢትዮጵያ የመሳሰሉ አገራት፣ ወደ ተሻለ አቅጣጫ እንዲጓዙ፣ የመገፋፋት ብቃት አላቸው ብዬም አላምንም።
ቢሆንም ግን፣ የኦባማ ጉብኝት፣ ለኢትዮጵያ መልካም ክስተት ነው። ከአሜሪካ የተሻለ የስልጣኔ አርአያ ስለሌለ፣ ከአሜሪካ ጋር መወዳጀት ጥሩ ነው። የኢትዮጵያ ፖለቲካና ኢኮኖሚ በተወሰነ ደረጃ እንዲሻሻል፣ ያም ባይሆን፣ ይብስ እንዳይበላሽ ይረዳ ይሆናል - የአሜሪካ ወዳጅነት። በዚያ ላይ፣ የስራ እድል የሚከፍቱ፣ የቢዝነስ አሰራርን ለማሻሻል የሚያግዙ የውጭ ኢንቨስተሮች፣ ወደ ኢትዮጵያ እንዲመጡም ያደፋፍር ይሆናል።
የዩኤን ጉባኤስ? ለድሃ አገራት የገንዘብ ምንጭ ለማፈላለግ፣ በአዲስ አበባ የተካሄደው የዩኤን የፋይናንስ ጉባኤ፣ እንደ ድሮው ከቢሊዮን ዶላሮች አልፎ፣ ስለ ትሪሊዮን ዶላሮች የተወራበት ጉባኤ ነው። ግን፣ ጉባኤው ለኢትዮጵያ እንደ በጎ አጋጣሚ የሚቆጠረው፣ ዩኤን እንደሚያወራው፣ ዶላር ይጎርፍልናል በሚል አይደለም።
እንደ ካሁን ቀደሙ፣ አብዛኛው የእርዳታ ወሬ፣ በዚያው ወሬ ሆኖ ነው የሚቀረው።  የተወሰነ እርዳታ አይመጣም ማለት አይደለም። ይመጣል። ነገር ግን፣ እርዳታ... ካሁን በፊት እንደታየው፣ ለተወሰነ ጊዜ በሕይወት ለመቆየትና ከአደጋ ለማምለጥ ያግዛል እንጂ፣ ብልፅግናን አያስገኝም።
ቢሆንም፣ ስብሰባው በአዲስ አበባ መካሄዱ መልካም ነው። በሺ የሚቆጠሩ ተሰብሳቢዎች የተገኙበት ትልቅ ጉባኤ መሆኑ፣ አንድ ነገር ነው። ግን፣ ከዚህም ይበልጣል። እንደ ሌላው ጊዜ፣ በአንድ አዳራሽ የተካሄደ ወይም በጥቂት ስብሰባዎች የተጠናቀቀ ጉባኤ አይደለም። ጎን ለጎን፣ ከ200 በላይ ስብሰባዎች ናቸው የተካሄዱት። ትልልቆቹ ሆቴሎች፣ በአንድ ቀን ውስጥ፣ ከአምስት እስከ ሰባት አዳራሾችን፣ ማከራየት ሲችሉ አስቡት። አንዱን አዳራሽ ሁለቴና ሦስቴ ሲያከራዩስ? ጉባኤው፣ ለበርካታ ሆቴሎች፣ የአመቱ ትልቅ ባለውለታ ነው።
የ100% ምርጫ
ሌላኛው የአመቱ ክስተት፣ ፉክክር የራቀውና 100% ኢህአዴግ ያሸነፈበት የፓርላማ ምርጫ ነው። የአገራችን ፖለቲካ፣ ገና ኋላቀር መሆኑን የሚመሰክር ምርጫ ቢሆንም፣ አወንታዊ ነገር እናውጣለት ብለን መሞከር እንችላለን።
አንደኛ ነገር፣ በተወሰነ ደረጃም ቢሆን፣ የፓርቲዎችን ክርክር በቴሌቪዥን አይተናል። ሁለተኛ ነገር፣ ምርጫው ላይ፣ አንዳችም የፉክክር ምልክት አልነበረም ማለት አይደለም። ተቃዋሚ ፓርቲዎች የፓርላማ ወንበር ባያሸንፉም፣ በበርካታ ከተሞች፣ እስከ 30 በመቶ ድረስ ድምፅ ያገኙበት ምርጫ እንደነበረ ማስታወስ ያስፈልጋል። ሦስተኛ ነገር፣ አላስፈላጊ ቀውስ አልተፈጠረም።
ከዚህ ውጭ፣ ያው፣ ወደፊት እንዲሻሻልና፣ ከፉክክር ጋር በሰላም የሚካሄድ ምርጫ እውን እንዲሆን መመኘትና መጣር ነው።

ሃዘንና ቁጭት - በአክራሪነትና በዘረኝነት
2007 ዓ.ም፣ በጣም አሳዛኝ ክስተቶችን ያስተናገድንበት  አመት ነው። አለምን እያናወጠ የሚገኘው የሃይማኖት አክራሪነትና አሸባሪነት፣ ኢትዮጵያዊያንን የሚምር አልሆነም። በእርግጥም፣ ከየትኛውም እምነት ቢሆን፣ ከእስልምናም ሆነ ከክርስትና፣ ከሂንዱም ከሆነ ከቡድሃ እምነት፣ ብዙም ልዩነት የለውም። የሃይማኖት አክራሪነት፣ ማንንም አይምርም። ይሄ እውነት ነው። እንዲያም ሆኖ፣ አሸባሪዎች፤ ሊቢያ ውስጥ፣ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ላይ የፈፀሙት አረመኔያዊ ግድያ፣... አእምሮ ከሌለው ክፉ አውሬ እንኳ የማይጠበቅ ነው።
ያልታጠቁ ሲቪሎችን፣ ለዚያውም ስደተኞችን በጅምላ መጨፍጨፍ ምን ይባላል?... የሃይማኖት አክራሪነት የእብደት መጠን፣ “እዚህ ወይም እዚያ ድረስ ነው” ተብሎ የሚገለፅ አልሆነም።
በዚህ መሃል፣ ገዢው ፓርቲ፣ ያንንም ያንንም “አሸባሪ” ብሎ እየወነጀለ፣ እጅግ አሳሳቢ የሆነውን ጉዳይ፣ ተራ የፖለቲካ መጫወቻ ካርድ ሲያደርገው ማየት ያሳዝናል። እጅግ አላዋቂነት ነው። ይህም ብቻ አይደለም።  
ሁሉም ባይሆኑም፣ በርካታ ተቃዋሚዎችም፣ ‘ገዢውን ፓርቲ ለማሳጣት ይጠቅመናል’ በሚል ቀሽም ስሌት፣ ጨርሶ የሃይማኖት አክራሪነትና የሽብር ስጋት የሌለ እስከማስመሰል ይደርሳሉ።
እባካችሁ፣ ገዢው ፓርቲ እና ተቃዋሚዎች፣ ... ምናለ፣ አንዳንድ ከባባድ ጉዳዮች፣ በጭራሽ የፖለቲካ መጫወቻ ካርድ መሆን እንደሌለባቸው ብትገነዘቡልን።
የዘረኝነት እብደትም፣ እዚህ ላይ መጥቀስ ያስፈልጋል። የዘረኝነት እብደት፣ ገደብ እንደሌለው፣ በደቡብ አፍሪካ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን እና ሌሎች ስደተኞች ላይ በተፈፀመው ዘግናኝ ግድያ አይተናል።
ድሮ ድሮ የምናውቀው፣ በዘር የተቧደኑ ጥቂት ነጮች፣ በጥቁሮች ላይ ጥቃት ሲፈፅሙ፤... ወይም ሮበርት ሙጋቤ እንዳደረጉት፣ በዘር የተቧደኑ ጥቂት ጥቁሮች፣ በነጮች ላይ ሲዘምቱ ነበር። ሮበርት ሙጋቤን የሚያደንቁ ‘አላዋቂዎች’፣ ምንን እያደነቁ እንደሆነ መች አወቁ?
ዘረኝነት፣ “ጥቁርና ነጭ” በሚል መቧደኛ ውስጥ ታጥሮ፣ እዚያው እንደተቀመጠ ሊቀር አይችልም። በአገር፣ በብሄረሰብ፣ በጎሳ፣ በወረዳ... እያለ፣ ከላይ እስከ ታች ሁሉንም ሳያዳርስ፣ የጥፋት ሰደዱ አይቆምም - ሙሉ ለሙሉ ካላስወገዱት በቀር። በተግባር እያየነው አይደል?

በኢኮኖሚው መስክ፡
“የነዳጅ ዋጋና አስገራሚው የንግድ ሚኒስቴር ስጋት”
(“የኤክስፖርት ድንዛዜ” ፣ “እድሜ ለዳያስፖራ”፣ “አስፊሪ የብድር ክምር”)
በ2007፣ ለኢትዮጵያ ትልቅ ትርጉም ያለው አለማቀፍ የኢኮኖሚ ዜና፣ የነዳጅ ዋጋ መቀነሱ ነው። ባለፉት ስድስት ወራት፣ የድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ፣ በትንሹ ከፍና ዝቅ ቢልም፣ ከአመት በፊት ከነበረው ዋጋ ጋር ሲነፃፀር ግን፣ በጣም ወርዷል -  በበርሜል ከ110 ዶላር ወደ 50 ምናምን ዶላር። ይህም ብቻ አይደለም።
የነዳጅ ዋጋ፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ፣ እንደገና ሊጨምር ይችላል ተብሎ አይገመትም። አንደኛ ነገር፣ የበርካታ አገራት ኢኮኖሚ፣ ብዙ የመነቃቃት አዝማሚያ አይታይበትም። በርካታዎቹ ደግሞ፣ የለየለት ቀውስ ውስጥ ገብተዋል። ሁለተኛ ነገር፣ የሳዑዲ አረቢያ መንግስትና ሌሎቹ፣ የነዳጅ ምርት ለመቀነስ ፍላጎት እንደሌላቸው በተደጋጋሚ ገልፀዋል። እንዲያውም፣ የነዳጅ ምርት ጨምሯል - በተለይ አሜሪካ ውስጥ በተስፋፋውና ‘ፍራኪንግ’ የተሰኘ አዲስ የቴክኖሎጂ ፈጠራ አማካኝነት።
ሦስተኛ ነገር፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ፣ የቻይና ኢኮኖሚ፣ በበርካታ ችግሮች ሳቢያ መደነቃቀፍ አብዝቷል። የኢኮኖሚ እክል ሲያጋጥም፣ የነዳጅ ፍጆታ እንደሚቀንስ ሲያስረዱ የከረሙት አለማቀፍ የሚዲያ ተቋማት፤ ባለፉት ጥቂት ሳምንታት፣ ከቻይና የኢኮኖሚ እክል ጋር፣ የነዳጅ ዋጋ ይበልጥ እንደወረደ ዘግበዋል። ለሚቀጥሉት በርካታ ወራት፣ ያን ያህልም የዋጋ ጭማሪ አይከሰትም ሲሉም ግምታቸውን ገልፀዋል። ይሄ፣ ለኢትዮጵያ መልካም የኢኮኖሚ ዜና ነው። መንግስት የተጣራ ነዳጅ ለማስመጣት የሚከፍለው ዋጋ በ45% እንደቀነሰ፣ በቅርቡ ብሔራዊ ባንክ ባወጣው ሪፖርት ገልፆ የለ! ግን ምን ማለት ነው? ልዩነቱን መመልከት ትችላላችሁ።
በ2007 ዓ.ም ከጥር እስከ መጋቢት መጨረሻ፣ የተጣራ ነዳጅ ገዝቶ ወደ ኢትዮጵያ ለማስመጣት የዋለው ገንዘብ፣ 317 ሚሊዮን ዶላር ነው።
በ2006 ዓ.ም የነበረው ዋጋ ባይቀንስ ኖሮ ግን፣ 583 ሚሊዮን ዶላር ያስፈልግ ነበር። ልዩነቱ ቀላል አይደለም። በሦስት ወራት ብቻ፣ 266 ሚሊዮን ዶላር ማዳን፣ እጅግ ትልቅ ነገር ነው። የነዳጅ ዋጋ፣ በዚህ ከቀጠለ፣ በዓመት ውስጥ፣ ከአንድ ቢሊዮን ዶላር በላይ ወጪ ዳነ ማለት ነው - ወደ 22 ቢሊዮን ብር ገደማ።
“ጥሩ ነው። ጥሩ ነው። ግን፣ ጥሩነቱ አየር ላይ እንደተንሳፈፈ ቀረሳ” የሚል ስሜት ቢፈጠርባችሁ አይገርምም። ትንሽ ወደ መሬት እናውርደው።  
አምና፤ በመጋቢት 2006 ዓ.ም፣ ቤንዚን ገዝቶ ወደ አገር ለማስገባት፣ በሊትር 14.70 ብር ይፈጅ ነበር።
ከወደብ ለመረከብና ወደ ነዳጅ ማደያዎች ለማድረስ፣ የማጓጓዣ ወጪ አለ። የታክስ ክፍያም ይጨመርበታል። የችርቻሮ የአገልግሎት ክፍያና ሌሎችም ወዘተ...። ነገር ግን፣ የችርቻሮ ዋጋው፣ በገበያ ውድድር ሳይሆን፣ መንግስት በሚያወጣው ተመን ነው የሚወሰነው። እናም በሊትር፣ 20.30 ብር ነበር የሚቸረቸረው - አምና በመጋቢት ወር።
[በ14.70 ተገዝቶ ይመጣል። በ20.30 ይቸረቸራል]
ዘንድሮስ?
ዋጋው ስለወረደ፣ ቤንዚን ወደ አገር ለማስገባት፣ ወጪው ከ8.50 ብር በታች ሆኗል - ለአንድ ሊትር ቤንዚን።
መንግስት የተመነለት የችርቻሮ ዋጋስ? ለአንድ ሊትር፣ 17.90 ብር ነው።
[በ8.50 ተገዝቶ ይመጣል። በ17.90 ይቸረቸራል]። ይሄ በፍፁም ተገቢ ያልሆነ ዋጋ ነው የምትሉ ከሆነ አልተሳሳችሁም።
የአለም ባንክ፣ ባለፈው ሐምሌ ባወጣው ሪፖርት፣ የችርቻሮ ዋጋው፣ ወደ 14.80 ብር መውረድ እንደነበረበት ይጠቁማል። (4TH ETHIOPIA ECONOMIC UPDATE - ገፅ 15)። ግን፣ አልወረደም። በዚህ ምክንያት ብቻ ከቤንዚንና ከነናፍጣ፣ መንግስት የሚያገኘው ትርፍ፣ ከ7.5 ቢሊዮን ብር በላይ ነው። ‘ያልታሰበ ሲሳይ’ ሆኖ ሊታየው ይችላል።
በዚህ መሃል፣ ረቡዕ እለት፣ የንግድ ሚኒስቴር ያወጣውን መግለጫ ሰምታችሁ ይሆናል። በአለም ገበያ፣ የነዳጅ ዋጋ ይበልጥ መውረዱን ይጠቅሳል መግለጫው። የአገር ውስጥ የችርቻሮ ዋጋ ግን አይቀየርም፡፡ እስካሁን የነበረው ተመን፣ በመስከረም ወርም እንዲቀጥል ወስኛለሁ ብሏል ሚኒስቴሩ።
የችርቻሮ ዋጋው፣ ከአለም ገበያ ጋር እንዲቀንስ የማይደረገው ለምንድነው? ሚኒስቴሩ፣ ለዚህ ጥያቄ ምላሽ አዘጋጅቷል።
የእስካሁኑ የዋጋ ተመን እንዲቀጥል የተወሰነው፣ የአገሪቱ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች በተረጋጋ ሁኔታ እንዲቀጥሉ በማሰብ እንደሆነ ሚኒስቴሩ ገልጿል።
እንዴት እንዴት?
የአለም ገበያን ተከትሎ፣ የችርቻሮ ዋጋው ከተቀነሰ፣ “የአገሪቱ ኢኮኖሚና ማህበራዊ እንቅስቃሴ ይናጋል” ማለት ነው? የንግድ ሚኒስቴር ስጋት፣ ግራ የሚያጋባ ነው። “በአለም ታይቶና ተሰምቶ የማይታወቅ አስገራሚ ስጋት” ተብሎ ለድንቃድንቅ መዝገብ ቢመረጥ አይበዛበትም።
“አንተ፣ ዋጋውን አስተካክል እንጂ፣ ቀሪውን ለኛ ተወው። ጨርሶ ስጋት አይግባህ” ብላችሁ ልታሳምኑት ከቻላችሁ ሞክሩ - የሚሰማ ከሆነ።
እንደሚመስለኝ ግን፣ መንግስት ይህንን የገንዘብ ምንጭ በቀላሉ ለመልቀቅ ፈቃደኛ ይሆናል ብዬ አልጠብቅም። መዓት ወጪዎችን ለመሸፈን ገንዘብ ያስፈልገዋል። እየተከመሩ የመጡ እዳዎችን ለመክፈል፣ ገንዘብ ያስፈልገዋል። አስቀድሞ፣ ወጪዎችን ለመቀነስና ብድር ላለማብዛት የማይጠነቀቅ ከሆነ፣ ምን ማድረግ ይቻላል?
ለማንኛውም ግን፣ በአለም ገበያ፣ የነዳጅ ዋጋ መቀነሱ ጥሩ ነው። አንድ ቢሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሪ ከየት ይመጣ ነበር?
ከኤክስፖርት?
የኤክስፖርት ነገርማ፣ አሳዛኝ ሆኗል። ላለፉት አራት አመታት፣ ምንም አይነት እድገት ሳይታይበት፣ እዚያው በነበረበት ቦታ እየረገጠ ነው። የጠቅላይ ሚኒስትር አማካሪ፣ ዶ/ር አርከበ እቁባይ የተናገሩትን መጥቀስ ይበቃል - “በጣም በጣም አሳሳቢ ነው” ብለዋል፡፡  
እንደ መንግስት ‘እቅድ’ ቢሆን ኖሮ፣ ወደ ውጭ ምርታቸውን የሚልኩ ድርጅቶች እየበዙና እያደጉ፣ በአመት የሚያገኙት የሽያጭ ገቢ፣ ዘንድሮ ቢያንስ ቢያንስ ስምንት ቢሊዮን ዶላር ይደርስ ነበር። ግን አልሆነም። ከአራት አመት በፊት የነበረበት ቦታ ላይ ቆሟል - 3 ቢሊዮን ዶላር ላይ።
ሌላኛው፣ የውጭ ምንዛሪ ምንጭ፣ የውጭ እርዳታና ብድር ነው። እርዳታው ባይቋረጥም፣ እንደታሰበው አልጨመረም። እርዳታ ሰጪዎቹ የአውሮፓና የአሜሪካ መንግስታት፣ ተጨማሪ እርዳታ የመስጠት አቅማቸው ተንጠፍጥፏል። እነሱ ራሳቸው፣ በኢኮኖሚ ድንዛዜና በበጀት እጥረት ተወጥረዋል። ብድርስ? ብድርስ አልጠፋም። ግን፣ ምን ዋጋ አለው? ብድር ሲደራረብ ያስፈራል። እንዴት ተደርጎ ከነወለዱ መመለስ እንደሚቻል እንጃ!
ምንም፣ መልካም ወሬ የለም ማለት ግን አይደለም። “እድሜ ለዳያስፖራ” ብንል ይሻላል። ለቤተሰብ የሚልኩት ገንዘብ፣ ከአመት አመት እየጨመረ መጥቷል። በ2007 ዓ.ም የመጀመሪያዎቹ ስድስት ወራት ብቻ፣ ከዳያስፖራ የመጣው ገንዘብ፣ ከ1.7 ቢሊዮን ዶላር በላይ ነው። በአመት፣ ወደ 3.5 ቢሊዮን ዶላር ይጠጋል። ከኤክፖርት ገቢ ይበልጣል ማለት ነው።
በጥቅሉ ሲታይ፣ በ2007 ዓ.ም፣ አገሪቱ በውጭ ምንዛሪ እጥረት፣ ጉድ ከመሆን የተረፈችው፣ በሁለት ምክንያቶች ነው ማለት ይቻላል - ‘ዳያስፖራዎች’ ለቤተሰብ የሚልኩት ገንዘብ በመጨመሩና በአለም ገበያ የነዳጅ ዋጋ በመቀነሱ።

አንድ አንበሳ እያረጀ መጣ፡፡ ከሰፈር ወጥቶ ወደ ሌላ ጫካ መሄድ አቃተው፡፡ ልጆቹም ሆኑ ሚስቱ ብዙ ትኩረት የሚሰጡት ዓይነት አልሆኑም፡፡ ሲያረጁ አይበጁ እንዲሉ ሆኗል፡፡
ከዕለት ዕለት እየዛለ፣ እንደ ልብ መራመድም እያቃተው ሄደ፡፡
አንድ ቀን ልጆቹን ጠርቶ፤
“ልጆቼ! እኔ እናንተን ለማሳደግ በየጫካው ተንከራትቻለሁ፡፡ አድኜ መግቤያችኋለሁ! አደንም አስተምሬያችኋለሁ! መከበሪያችሁም ሆኛለሁ! ዛሬ ግን ሁላችሁም በእኔ ላይ ፊታችሁን አዞራችሁብኝ!”
“ኧረ ፊታችንን አላዞርንብህም አባባ! አንተ አርጅተህ ቤት ስትውል፤ ተሯሩጠን አድነን፣ ቤታችን ሞቅ እንዳለ እንዲቀጥል እየጣርን ነው፡፡ እንግዲህ አንተም ውጪ ውጪ ማለትህን ትተህ፣ ሰብሰብ ብለህ ተቀመጥ፡፡ መሞቻህ ከደረሰም እኛ ተንከባክበን እንቀብርሃለን!” አሉት ልጆቹ፤ እየተፈራረቁ፡፡
“አይ ልጆቼ! እንኳን ሞት እርጅና አለ አይደለም ወይ?!”
“ለምን እንዲህ አልክ አባባ?” አለ አንደኛው ልጅ፡፡
“እርጅና በቁም መረሳት ነው ልጄ”
“እንዴት አባባ?” አለ ሌላኛው ልጅ፡፡
“ይሄው እናንተ የምታደርጉት ማስረጃ ነው! ጀማው ህብረተ-እንስሳን ተመልከቱ - ዞር ብሎ የሚያየኝ ጠፋ! ንጉሳቸው እንደነበርኩ የሚያስታውስ፣ ውለታዬን ከቁም ነገር የሚቆጥር አንድ እንስሳ ጠፋ! ግን ልጆቼ፤ ሁሌ ልጅ ሆኖ አይኖርም - ሁላችሁም አንድ በአንድ ተራችሁን እያረጃችሁ ትሄዳላችሁ፤ ትረሳላችሁ፣ ትጣላላችሁ!”  አለ፡፡
“አሁን ምን እናድርግልህ አባባ?”
“አሁንማ እርስ በርሳችሁ ሳትከፋፈሉ፣ ሳትሻሙ፣ ሳትጣሉ፤ ተመካከሩ፡፡ እኔንም ሆነ በእኔ ዕድሜ ያሉትን ሁሉ አትናቁ፣ አትኮንኑ! የወደፊቱን ብታስቡ ከብዙ መዘዝ ትወጣላችሁ! አለበለዚያ ያለጊዜ ማርጀትም ይመጣል! ያ ደግሞ ከእርጅና የከፋ እርግማን፣ ከመርገምት ሁሉ የከፋ መርገምት ነው! የጋራ ጫካችንን እንዴት እናቆየው ብላችሁ ጨክናችሁና በቅንነት ካልተነጋገራችሁ ጫካውም ጫካ አይሆን፣ ቤታችሁም ቤት አይሆንም!”
“ታዲያ ምን ታወርሰናለህ?”
“እስካሁን የነገርኳችሁን ምክርና የእኔን የልጅነት ልብ!! ለማንኛውም ያለፈውን አትኮንኑ፣ እርስ በርስ አትካሰሱ! ከሁሉም በላይ ግን ዳኛ አያሳጣችሁ!” ብሎ አሸለበ፡፡
*           *         *
እርስ በርስ አለመተሳሰብ፣ አለመነጋገር፣ ነገር በሆድ መያዝ ክፉ ልማድ ነው፡፡ አባትህን መዘንጋት ደግ አይደለም፡፡ በውርስ መልክ መናቆርን መረከብ መርገምት ነው፡፡ “አያረጅ የለም አይለዋወጥ” የሚለውን ሁሌም ልብ ማለት ነው፡፡ በአንፃሩ አዲሱ መምጣቱ አይቀሬ ነው” (The New is Invincible) የሚለውንም ማጤን ነው! ሁሉ ነገር ተለዋዋጭ ነው፡፡ አሮጌው ያልፋል፤ አዲሱ ይተካል፡፡ ከአሮጌው አዲሱ ልብ ውስጥ የሚቀር ነገር አለ፡፡
የሩሲያን፣ የቻይናንና የኩባን መሪዎች አስመልክቶ ስብሀት ገ/እግዚአብሔር “ሽፍቶችና መሪዎች” በሚለው ጽሑፉ፤ “ባጠቃላይ እንዲያው በጭፍን ያህል ስንናገር፣ በአንድ ልብ፣ በአንድ ወኔ፣ ለአንድ ዓላማ ሲዋጉ የነበሩት ሽፍቶች፣ መሪዎች በሆኑ በማግሥቱ፤ ዓላማቸውም ልባቸውም መለያየት ይጀምራል፡፡ ልዩነቶቻቸው እየበዙ እየከረሩ ሲሄዱ፣ ጠላትነት እየተንፏቀቀ መኻላቸው ይገባል፡፡ በራሺያ ስታሊን ትሮስኪን ያባርረዋል፡፡ ከዚያም ሜክሲኮ ድረስ ልኮ ያስገድለዋል፡፡ ሽፍቶች የነበሩት የትሮትስኪ ወገኖች፣ ሽፍቶች በነበሩት የስታሊን ወገኖች ይጨፈጨፋሉ፡፡ በቻይና ሽፍታ የነበረው ሊዩ-ሻዎ-ቺ ሽፍቶቹ ወደ መሪዎቹ ሲለወጡ የመከላከያ ሚኒስትር ሆኖ ቆየ - ያውም አሪፍ! ማኢና ሊዮ የኋላ ኋላ ተቃቃሩ … አንድ ቀን ሊዮ - ሻዎ - ቺ ከአገር ለመጥፋት በአውሮፕላን ሲበር፣ የሊቀመንበር ማኦ ወገኖች ነቅተውበት ኖሮ ተኩሰው አውሮፕላኑን አጋይተው ይገሉታል፡፡
ወደ ኩባ ስንመጣ ግን ቼ እና ካስትሮ እንደተባበሩ እንደተዋደዱ ተለያዩ፡፡ ትምህርታችንን ከገለጠልን ጋሽ ስብሃት ትልቅ ትምህርት ጥሎልን አልፏል፡፡ ሥልጣን እንዳያለያየንና ዓላማችንን እንዳንረሳ! ያም ሆኖ ለስልጣን ያበቃናቸው ሰዎች፤ ስልጣናቸው ላይ እንዳይተኙ መጠንቀቅ ያባት ነው፡፡ አስረጅ ይሆነን ዘንድ የደጃች ማሩ ወግ እነሆ፡-
“ደጃች ማሩ አሽከሮቻቸውን ሰብስበው አንዱን ፊታውራሪ፣ አንዱን ግራዝማች፣ ወዘተ ብለው ሾሙ አሉ፡፡ ሆኖም ምንም ሥራ የለም፡፡ ስለዚህ አሽከሮች ጋቢ ለብሰው በየጠዋቱ ፀሐይ ይሞቃሉ፡፡
መንገደኛ አይቷቸው፤ “ምን እየሰራችሁ ነው?” ይላቸዋል፡፡
ተሿሚዎቹም፤ “ዝም ብለህ እለፍ! የደጃች ማሩ እሥረኞች ነን!” አሉት፡፡ ከዚህ ይሰውረን!!
ቅርንጫፍ ባበዛን ቁጥር የሚመች ሁኔታ አይኖርም፡፡ ለሰዓቱ ይኮናል? ስንቱን ማርካት ይቻላል?  ተመቸኝ ብሎ የማይፏልሉበት፣ አልተመቸኝም ብሎ እሪዬ - ወዬ የሚሉበት ሁኔታ እንዳይፈጠር ትልቅ ዐይን ያስፈልጋል! በአንፃሩ ዕውነተኛ ተተኪ፣ ዕውነተኛ ወራሽ አለማግኘት መረገም ነው፡፡ “ከሁለት የወለደ አይደሰት፤ ሳይወልድ የሞተ አስተዛዛኝ የለው!” የሚለው ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ሃቅ ነው!!

ስንፍና የኃጢያቶች ሁሉ ሥር ነው፡፡
   የግሪካውያን አባባል
እርቃኑን የተወለደ መልበስ ያሳፍረዋል፡፡
   የግሪካውያን አባባል
ወይ በጊዜ አግባ ወይ በጊዜ መንኩስ፡፡
  የግሪካውያን አባባል
በወይን ጠጅ ውስጥ እውነት አለች፡፡
  የሮማውያን አባባል
እናትና ልጅ ሲጣሉ፣ ሞኝ እውነት ይመስለዋል፡፡
  የአፍጋኒስታውያን አባባል
ድመቶች አይጥ የሚይዙት እግዚአብሔርን ለማስደሰት ብለው አይደለም፡፡
  የአፍጋኒስታውያን አባባል
ሞት ሲመጣ ጥሩንባ አይነፋም፡፡
  የኮንጎዎች አባባል
ስለ እሳት ማውራት ድስቱን አያበስለውም፡፡
  የአፍሪካ አሜሪካውያን አባባል
በእናቱ ጀርባ ላይ የተቀመጠ ህፃን የመንገዱን ርዝመት አያውቀውም፡፡
  የአፍሪካውያን አባባል
ቢራቢሮ መብረር ስለቻለች ብቻ ወፍ ነኝ ብላ ታስባለች፡፡
  የአፍሪካውያን አባባል
እስስት ቀለሟን እንጂ ቆዳዋን ፈፅሞ አትቀይርም፡፡
  የአፍሪካውያን አባባል
ቢላ ባለቤቱን አይለይም፡፡
  የአፍሪካውያን አባባል
የክፋትን ዘር በጊዜ ካላጠፋኸው አንተኑ ያጠፋሃል፡፡
  የቻይናውያን አባባል
ባሏ ከሞተ ሴት ጋር ግንኙነት ከመጀመርህ በፊት፣ ባሏን የገደለው ምን እንደሆነ መጠየቅ አለብህ፡፡
  የአፍሪካውያን አባባል

በወጣቷ የፊልም ባለሙያ ሕይወት አድማሱ የተሰራው “አዲስ ዓይኖች” የተሰኘው አጭር ፊልም በዓለም አቀፎቹ የቬነስና ቶሮንቶ ፊልም ፌስቲቫሎች ላይ እንዲታይ መመረጡ ተገለፀ፡፡
ፊልሙ አንዲት የ13 ዓመት ሴት ልጅ የሚጋጥማትን አካላዊና የስሜት ዕድገት ለውጥ ተከትሎ ከማህበረሰቡ ጋር የምትፈጥረውን ግጭት የሚያሳይ ነው ተብሏል፡፡
የፊልሙ ፀሐፊና ዳይሬክተር ህይወት አድማሱ፤ በመላው ዓለም ካሉ 10 ባለተሰጥኦ ወጣት የፊልም ሰሪዎች አንዷ ሆና በቶሮንቶው የፊልም ፌስቲቫል ለሚካሄድ ልዩ ፕሮግራም በመመረጥ ከአፍሪካ ብቸኛዋ እንደሆነች ገልፃለች፡፡
“አዲስ ዓይኖች” በእንግሊዝና በፈረንሳይ የፊልም ኩባንያዎች ፕሮዱዩስ እንደተደረገ ወጣቷ ተናግራለች፡፡
ህይወት በኤሌክትሪክና ኮምፒዩተር ኢንጂነሪንግ የመጀመሪያ ዲግሪዋን ያገኘች ሲሆን በብሉናይል የፊልምና የቴሌቪዥን አካዳሚ ገብታም የፊልም ጥበብን ተምራለች፡፡ ወጣቷ በተለያዩ ዓለም አቀፍ የፊልም ዎርክሾፕና ስልጠናም ላይ መካፈሏንም ጠቁማለች፡፡

በፈቃዱ ሲሳይ የተፃፈው “ምፅኣተ ዓም-ሓራ… በአዲሶቹ ዓም-ሓሮች” የተሰኘ ፖለቲካዊ ልቦለድ መፅሃፍ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ በ269 ገፆች የተቀነበበው ልቦለዱ፤ ለአገር ውስጥ በ75 ብር፣ ለውጭ አገር በ25 ዶላር ይሸጣል፡፡