Administrator

Administrator

የአንጋፋው ደራሲ የአበራ ለማ አዲስ ስራ የሆነው “ቅንጣት የኔዎቹ ኖቭሌቶች” አዲስ መጽሐፍ ዛሬ ከቀኑ 8፡00 -10፡30 ሰዓት በኢትዮጵያ ቤተ መፃሕፍትና ቤተ መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ ይመረቃል፡፡ በአግዮስ ህትመትና ጠቅላላ ንግድ ኩባንያ የታተመው መጽሐፉ በምረቃው እለት በታዋቂው ሃያሲ አብደላ ዕዝራ ዳሰሳዊ ግምገማ እንደሚቀርብበትም ለማወቅ ተችሏል፡፡

ባቡሩ ነገ ማለዳ ስራውን ይጀምራል
   በነገው ዕለት ስራ ለሚጀምረው የአዲስ አበባ የቀላል ባቡር ፕሮጀክት የሃይል አቅርቦት የማሟላት ሃላፊነቱን የወሰደው “ቻይና ኤሌክትሪክ ፓዎር ኢኩፒመንት ኤንድ ቴክኖሎጂ” የተባለው ኩባንያ የሃይል አቅርቦቱን ያልተቆራረጠና አስተማማኝ አደርጋለሁ ሲል ቃል መግባቱን ዥንዋ ዘገበ፡፡
የኩባንያው ምክትል ጄኔራል ማናጀር ቼን ዊ፤ ኩባንያው በአዲስ አበባ ከተማ በሚገኙ አምስት ቦታዎች የገነባቸውን የቀላል ባቡሩ የኤሌክትሪክ ሃይል ማስተላለፊያ ንኡስ ጣቢያዎች ባስጎበኙበት ወቅት እንዳሉት፣ ምንም እንኳን ኩባንያው የጊዜ መጣበብና በአገር ውስጥ ገበያ የቁሳቁስ አቅርቦት እጥረት ቢያጋጥመውም ንኡስ ጣቢያዎቹን በወቅቱ ገንብቶ የጨረሰ ሲሆን፣ የባቡር ኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦቱን አስተማማኝ ለማድረግ በቻለው አቅም ሁሉ መዘጋጀቱን ገልጸዋል፡፡ቻይና ኤሌክትሪክ ፓዎር ኢኩፒመንት ኤንድ ቴክኖሎጂ ኩባንያ በአዲስ አበባ ያስገነባቸው የቀላል ባቡር የኤሌክትሪክ ሃይል ማስተላለፊያ ንኡስ ጣቢያዎች አምስት ሲሆኑ በቃሊቲ፣ አያት፣ ሚኒልክ፣ መስቀል አደባባይ፣ እግዚያብሄርአብ ቤተ ክርስቲያንና በጦር ሃይሎች አካባቢ እንደሚገኙ ለማወቅ ተችሏል፡፡ በሌላ በኩል ተሳፋሪዎች በጉዞ ወቅት እስከ 10 ኪሎ የሚመዝን እቃ ብቻ ይዘው ለመጓዝ እንደሚፈቀድላቸው የተገለፀ ሲሆን አንዳንድ በባቡሩ ላይ እንዳይጫኑ የሚከለከሉ እቃዎች እንደሚኖሩ ታውቋል፡፡
የባቡር ትራንስፖርቱ ክፍያ እስከ 4 ኪሎ ሜትር ሁለት ብር፣ እስከ 8.8 ኪሎ ሜትር 4 ብር እንዲሁም ከመነሻ እስከ መጨረሻ ፌርማታ 6 ብር ነው ተብሏል፡፡ ትኬት ሳይዙ መጓዝ ከፍተኛ ቅጣት እንዳለውም ተጠቁሟል፡፡

  መመሪያ ያልተሰጠበት የደብሩ የሚሊዮን ብሮች የበጀት ጥያቄ እንዲዘገይ አዟል
 •  የሀገረ ስብከቱን ሥራ አስኪያጅና ምክትላቸውን እያወዛገበ ነው


    የአራዳው መናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ደብር፣ እያሠራው የሚገኘው የሁለገብ ሕንፃ ግንባታ፣ ተደርጎለታል ባለው የዲዛይን ማሻሻያ ሳቢያ በልዩነት የሚያስፈልገው ከመቶ ሚሊዮን ብር በላይ ወጪና ከባለሀብቶች ጋር በመተባበር ለማስገንባት ያቀዳቸው የሌሎች ሁለት ሕንፃዎች ግንባታና በጀት እንዲጸድቁለት ያቀረባቸው ጥያቄዎች፣ ለፓትርያርኩ ቀርበው መመሪያ ያልተሰጠባቸው በመሆናቸው “በአሉበት ሁኔታ እንዲቆዩ” የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት አዘዘ፡፡
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አስተዳደር ጉባኤ፣ በደብሩ ግንባታዎችና የበጀት ይጸደቅልኝ ጥያቄዎቹ ላይ ባለፈው ዓመት ሰኔ ወር መጨረሻ ያሳለፋቸው ውሳኔዎች ለአፈጻጸም ወደ መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤቱ ሳይላኩለት የቆዩበት ምክንያት እንዲብራራለትም ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ከትላንት በስቲያ ለሀገረ ስብከቱ በጻፈው ደብዳቤ ጠይቋል፡፡
የደብሩ ሰበካ ጉባኤ፣ የልማት ዕቅዶቹ በሀገረ ስብከቱ በኩል እንዲጸድቁለት ባለፈው ዓመት ሚያዝያ 16 ቀን 2007 ዓ.ም. መጠየቁን ጠቅላይ ጽ/ቤቱ ባስታወሰበት ደብዳቤው፤ ዲዛይኑ ለተሻሻለው ሁለገብ ሕንፃ ማሠሪያ እንዲሁም በስተምሥራቅ የሚገኙት ሱቆች ፈርሰው በምትካቸው ባለሁለት ፎቅ ሕንፃ መሥራት ይቻል ዘንድ የብር 6 ሚሊዮን በጀት በደብሩ እንደተመደበ፣ በጥያቄው ላይ ለመወሰን ሰኔ 25 ቀን 2007 ዓ.ም. ከተሰበሰበው የሀገረ ስብከቱ አስተዳደር ቃለ ጉባኤ መረዳቱን ጠቅሷል፡፡
በዕለቱ፣ በምክትል ሥራ አስኪያጁ መጋቤ ብሉይ አእመረ አሸብር በተመራው የአስተዳደር ጉባኤው ስብሰባ፣ በደብሩ የቀረበው የበጀት ይጸድቅልኝ ጥያቄ፣ “ከባድና ከሀገረ ስብከቱ አቅም በላይ” ሊሆን እንደቻለ ተጠቁሟል፡፡ ወጪው ከ61 ሚሊዮን ወደ 152 ሚሊዮን ያደገው የዲዛይን ክለሳ ጥናት፤ በገለልተኛ ባለሞያዎች ተገምግሞ፣ ውጤቱ ለጠቅላይ ቤተ ክህነቱ እንዲላክና በዚያው በኩል እንዲጸድቅ፤ የሁለት ተጨማሪ ሕንፃዎች ግንባታ ውሎችም ለአስተዳደር ጉባኤው ቀርበው እንዲታዩና የውሳኔው ቃለ ጉባኤም በምክትል ሥራ አስኪያጁ ሸኚ ደብዳቤ ለመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት እንዲላክ ከስምምነት ተደርሶበት እንደነበር ጠቅላይ ጽ/ቤቱ አውስቷል፡፡
ይኹንና ውሳኔዎቹም ኾኑ የውሳኔዎቹ ቃለ ጉባኤ ለመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤቱ እንዳልተላከ ጠቅሶ፣ ለሦስት ወራት ሳይላክ የዘገየበት ምክንያት ከተጨባጭ ማስረጃ ጋር እንዲብራራለት የሀገረ ስብከቱን ጽ/ቤት አዟል፤ የመናገሻ ገነተ ጽጌ ደብርን ጨምሮ የ48 አድባራትን የመሬትና የገቢ ማስገኛ ተቋማት አጠቃቀምና የኪራይ አፈጻጸም ያጣራው አጥኚ ኮሚቴም፣ ጉዳዩን ተከታትሎ እንዲያስፈጽም በደብዳቤው ግልባጭ መታዘዙን ጠቅላይ ጽ/ቤቱ አስታውቋል፡፡
በቤተ ክርስቲያኒቱ የቃለ ዐዋዲ ድንጋጌ አንቀጽ 12 ንኡስ አንቀጽ 8፣ ቋሚ ንብረትንና ከፍተኛ ወጪን የሚጠይቁ ጉዳዮች በሥራ ላይ ሊውሉ የሚችሉት ከሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ፈቃድ ሲያገኙ ብቻ ነው፡፡ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፣ ከረዳት ሊቀ ጳጳሱ አልፎ የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ልዩ ሀገረ ስብከት እንደመኾኑ፣ በአጥቢያ ሰበካ ጉባኤያቱ ለሀገረ ስብከቱ የሚቀርቡ ጥያቄዎች በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤቱ አማካይነት ለፓትርያርኩ እየቀረቡ አመራር ሲሰጥባቸው፣ ጠቅላይ ጽ/ቤቱ በመመሪያው መሠረት ማስፈጸም ይኖርበታል፡፡
በዚሁ አግባብ፣ በሀገረ ስብከቱ ምክትል ሥራ አስኪያጅ ሰብሳቢነት የተላለፈው ውሳኔ፣ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤቱ አማካይነት ለፓትርያርኩ ቀርቦ መመሪያ እስከሚሰጥበት ድረስ የደብሩ የግንባታና የበጀት ይፅደቁልኝ ጥያቄዎች በአሉበት ሁኔታ እንዲቆዩ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሀገረ ስብከቱን አዟል፡፡
ጠቅላይ ጽ/ቤቱ ይህን ይበል እንጂ፤ ደብሩ በጥያቄው መሠረት ግንባታውን እንዲቀጥል የሚገልጽ ነው የተባለ ደብዳቤ፤ በሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ባለፈው ዓመት መጨረሻ ለደብሩ አስተዳደር አስቀድሞ መጻፉን የሀገረ ስብከቱ ምንጮች ተናግረዋል፡፡ ዋና ሥራ አስኪያጁ የደብሩም ዋና ጸሐፊ እንደኾኑ የጠቀሱት ምንጮቹ፣ በአንድ በኩል ጥያቄ አቅራቢ በሌላ በኩል ውሳኔ ሰጪና አፅዳቂ በመኾን የፈጸሙት ተግባር የተጠያቂነት መርሆዎችንና የአስተዳደር ጉባኤውን ውሳኔ ከመፃረሩም በላይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከምክትል ሥራ አስኪያጁ ጋር እየተካረሩ ለመጡት አለመግባባቶችም አንድ መንሥኤ መኾኑን አስረድተዋል፡፡
የመናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ደብር፣ በሕንፃዎች፣ በሱቆችና በባዶ መሬት አጠቃቀምና የኪራይ አፈጻጸም፣ የአሠራር ችግር እንዳለባቸው ከተዘረዘሩት 15 ገዳማትና አድባራት አንዱ እንደኾነ፣ በፓትርያርኩ ትእዛዝ የተሠየመው ኮሚቴ ባካሔደውና በጠቅላይ ጽ/ቤቱ አማካይነት ለቋሚ ሲኖዶስ በቀረበው ጥናታዊ ሪፖርት ተጠቅሷል፡፡
እንደ ሪፖርቱ፣ የደብሩ ሁለገብ ሕንፃ፣ የዲዛይን ማሻሻያ በሚል ወጪው ከ61 ወደ 171 ሚሊዮን ብር ያደገ ሲኾን አዲስ ተቆጣጣሪ መሐንዲስም በደብሩ ዋና ጸሐፊ ጠቋሚነት ያለጨረታ ተቀጥሯል፡፡ ሀገረ ስብከቱና ሊቀ ጳጳሱ ለአዲሱ የዲዛይን ጥናትና ከብር 110 ሚሊዮን በላይ ላሳየው የዋጋ ጭማሪ ዕውቅናና ፈቃድ ባልሰጡበት ሁኔታ ግንባታው መቀጠሉም አግባብነት እንደሌለው በሪፖርቱ ተገልጧል፡፡
ቋሚ ሲኖዶስ፣ ጥናታዊ ሪፖርቱን ሙሉ በሙሉ በመቀበል ውሳኔዎችን ማሳለፉን ጠቅላይ ጽ/ቤቱ በደብዳቤው ገልጾ÷ የመናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ደብርን ጨምሮ በተዘረዘሩት 15 ገዳማትና አድባራት ተፈጸመ በተባለው ኢ-ፍትሐዊ አሠራር፣ በተናጠልም ኾነ በጣምራ ተጠያቂ የሚኾኑ የአመራር አካላት ከተሰበሰቡት ማስረጃዎች ጋር በንጽጽር እንዲቀርቡለት፤ የሕንፃዎቹ፣ የሱቆቹና የባዶ መሬቶቹ የኪራይ አፈጻጸምና የመካናተ መቃብሩ አጠቃቀም የሚመሩበት መተዳደርያ ደንብ፣ የጨረታ ደንብ፣ የአከራይና ተከራይ የውል ሰነድ በማእከላዊነት በባለሞያዎች ተዘጋጅቶ እንዲቀርብ፤ ጥናቱ ባልሸፈናቸው ሌሎች ገዳማትና አድባራት ላይም እንዲቀጥል መታዘዙንም አስታውቋል፡፡

    ከ200 በላይ የሀገር ውስጥና የውጭ ኩባንያዎች የሚሳተፉበት 12ኛው አለማቀፍ የኮንስትራክሽን ኤግዚቢሽን በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል ከትላንት በስቲያ ጀምሮ እየተካሄደ ነው፡፡ በኤግዚቢሽኑ ላይ ከ120 በላይ የሃገር ውስጥ ኩባንያዎች ተሣታፊዎች ሲሆኑ ቀሪዎቹ ከ17 የተለያዩ የአለም ሀገራት የተውጣጡ በኮንስትራክሽን ዘርፍ የተሠማሩ ኩባንያዎች ናቸው፡፡ ከውጪ ከተገኙት መካከል የጣሊያን፣ የቱርክ፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬትስና የቻይና ኩባንያዎች ተጠቃሽ ሆነዋል፡፡ ለ12ኛ ጊዜ የሚካሄደው ኤግዚቢሽኑ በኮንስትራክሽን ዘርፍ የተሠማሩ አምራቾችን፣ አሠሪዎችን፣ የሪልእስቴት ኩባንያዎችን፣ የግንባታ ማሽነሪ አስመጪዎችን፣ የፋይናንስ ተቋማትንና በዘርፉ ተዋናይ የሆኑ አካላትን በአንድ ቦታ የሚያገናኝ ይሆናል ተብሏል፡፡ ኤግዚቢሽኑ የፊታችን ሠኞ ይጠናቀቃል፡፡

     ከተለያዩ የአለም ክፍሎች የተውጣጡ በአቬሽን ዘርፍ ላይ የተሰማሩ ድርጅቶችን የሚያሳትፍ “አይማ አፍሪካ” የተሰኘ ዓለም አቀፍ ጉባኤ በአዲስ አበባ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን አዳራሽ፣ ከፊታችን ማክሰኞ ጀምሮ ለ3 ቀናት ይካሄዳል፡፡ ጉባኤው በተለይም በአገሪቷ ያለውን የኤርፖርት የመሰረተ ልማት እድገት ለማስተዋወቅ ትልቅ አስተዋፅኦ እንደሚኖረው የኢትዮጵያ ኤርፖርቶች ድርጅት ጠቁሟል፡፡ የድርጅቱ የኮሙኒኬሽን ጽ/ቤት ሃላፊ አቶ ወንድም ተክሉ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፤ ድርጅቱ ከሌሎች የኤርፖርት አገልግሎት ሰጪና መሰረተ ልማት አቅራቢ ድርጅቶች ጋር የንግድና የወዳጅነት ትስስር ለመፍጠር ጉባኤው መልካም አጋጣሚ ይሆንለታል፡፡ በጉባኤው ላይም ድርጅታቸው፣ “የአሁኑ እና የወደፊቱ የኤርፖርት መሰረተ ልማት” በሚል ርዕሰ ገለፃ እንደሚያቀርብ ኃላፊው አክለው ገልፀዋል፡፡
የአይማ (AIMA – Airport infrastructure maintenance repair & over hall (Mro) aviation) ጉባኤ በአለም ለ20ኛ ጊዜ፣ በአፍሪካ ደግሞ ለ3ኛ ጊዜ የሚካሄድ ሲሆን ከተለያዩ አገራት የተውጣጡ ከ200 በላይ ተሳታፊዎች ይገኙበታል ተብሏል፡፡  

   አብርሃም ግዛው ኢንተርቴይመንትና ፕሬስ ስራዎች ድርጅት ከኢትዮጵያ ብሮድ ካስቲንግ ኮርፖሬሽን ጋር በመተባበር ልዩ የመስቀል በዓል ፕሮግራም ያካሂዳል፡፡ በኢቴቪ 3 ከቀኑ 11፡30 እስከ ምሽት 1፡30 ሰዓት ድረስ በሚተላለፈው በዚሁ ፕሮግራም ላይ የእርድ፣ የደመራ ማብራት፣ እና የአገር ሽማግሌዎች የምርቃት ስነስርዓት የሚካሄድ ሲሆን ባህላዊና ዘመናዊ ሙዚቃዎች፣ የኮሜዲ ዝግጅትና የመስቀል በዓል አከባበር ታሪካዊ ዳራ እንደሚቀርቡም ጋዜጠኛና ፕሮሞተር አብርሃም ግዛው ተናግሯል፡፡
በእለቱ ታዋቂ ሰዎች የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች፣ የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎችና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ይታደማሉ ተብሏል፡፡ አብርሃም ግዛው ኢንተርቴይመንትና ፕሬስ ስራዎች ድርጅት “የጥበብ ብልጭታ” የተሰኘና በብስራት ኤፍኤም የሚተላለፍ የኪነ ጥበብ ፕሮግራም አዘጋጅ መሆኑ የሚታወስ ሲሆን የመስቀል በዓልን ዘንድሮ ለሁለተኛ ጊዜ ማዘጋጀቱም ታውቋል፡፡

• ባለፈው ዓመት በትራፊክ አደጋ የ448 ሰዎች ህይወት አልፏል
• 22 ተሳፋሪዎች፣ 19 አሽከርካሪዎች፣ የተቀሩት እግረኞች ናቸው

  ለአሽከርካሪዎች የወጣው ደንብ፤ ማንኛውም ሹፌርም ሆነ ከጐን የተቀመጠ ተሳፋሪ፤ የአደጋ መከላከያ ቀበቶ (Seat belt) ሳያስር በጉዞ ላይ ከተገኘ 120 ብር እንደሚቀጣ የሚጠቁም ሲሆን ለሁለቱም ወገን ተጠያቂው አሽከርካሪው ነው ይላል፡፡ እስካሁን ግን ህጉ ከአሽከርካሪዎች በቀር ተሳፋሪ ላይ ሳይተገበር ቆይቷል፡፡ ተሳፋሪዎች እንኳንስ ቀበቶ ሊያስሩ ቀርቶ አብዛኞቹ መኪኖች የአደጋ መከላከያ ቀበቶ ከእነአካቴው የላቸውም፡፡ ተሳፋሪው ቀበቶ የማሰር ልማድ ቢያዳብር ኖሮ፣ በተለያዩ ጊዜያት በሚደርሱ በርካታ አሰቃቂ አደጋዎች ላይ የሟቾችን ቁጥር መቀነስ ይቻል ነበር ይላል - ፖሊስ፡፡
ተወዳጇ አርቲስት ሰብለ ተፈራም በዘመን መለወጫ ዕለት፣ መስከረም 1 ቀን 2008 ዓ.ም በደረሰባት ድንገተኛ የመኪና አደጋ ወቅት ቀበቶ አስራ ቢሆን ኖሮ የተሻለ የመትረፍ ዕድል ሊኖራት ይችል ነበር ተብሏል፡፡
የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን እንደገለፀው፤ ትራፊኮች የአሽከርካሪን ብቻ ሳይሆን ከጐን የሚቀመጡ ተሳፋሪዎችንም ቀበቶ እንዲያስሩ ቁጥጥር አለማድረጋቸው  ስህተት ነው፡፡
የኮሚሽኑ የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ ኢንስፔክተር አሰፋ መዝገቡ ስለጉዳዩ ተጠይቀው ሲመልሱ፤ “በወቅቱ ቀበቶ የማሰርን ጉዳይ በአሽከርካሪው ላይ ብቻ ያጠበቅነው አብዛኞቹ መኪኖች ከእርጅና ጋር በተያያዘ ቀበቶ ስላልነበራቸው ነው” ብለዋል፡፡
ዘንድሮ ግን ህጉ በጥብቅ ተግባራዊ መደረግ እንደሚጀምር የጠቁሙት ኢንስፔክተሩ፤ አሽከርካሪዎች በህጉ መሰረት የተሳፋሪውንም ቀበቶ አሁኑኑ እንዲያስተካክሉ አሳስበዋል፡፡
“ህይወትን ከአደጋ መከላከል ለራስ ነውና በተለይ በግል ተሽከርካሪ የሚጠቀሙ ግለሰቦች ቀበቶ ማሰርን ካሁኑ መላመድ ይኖርባቸዋል” በማለት ኢንስፔክተሩ ምክራቸውን ለግሰዋል፡፡
ባለፈው ዓመት (2007 ዓ.ም) በአዲስ አበባ በትራፊክ አደጋ ምክንያት 448 ሰዎች ህይወታቸው ያለፈ ሲሆን ከነዚህ ውስጥ 22ቱ ተሳፋሪዎች፣ 19ቱ አሽከርካሪዎች፣ የቀሩት እግረኞች እንደነበሩ የትራፊክ ፖሊስ መረጃ ያመለክታል፡፡


Saturday, 19 September 2015 09:02

የታሪክ ባህሪያትና ዓላማ

(በፕ/ር መስፍን “አዳፍኔ” መነሻነት

   በአማርኛ ቋንቋ ከሚጽፉ እጅግ ጥቂት ኢትዮጵያዊያን ምሁራን መካከል አንጋፋው ምሁር ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም አንዱ ናቸው፡፡ ፕሮፌሰሩ በሚጽፏቸው በሳል ጽሁፎችና በሚያነሷቸው አዳዲስ ጉዳዮች የምሁርነትን ልክ አሳይተውናል ብል ያጋነንኩ አይመስለኝም፡፡ በተለይ ባለፉት አስር ዓመታት በየሁለት አመቱ ልዩነት ማለት ይቻላል በተከታታይ ግማሽ ደርዘን የሚሆኑ መጽሀፍትን አስነብበውናል፡፡ ባለፈው ዓመትም (በ2007) ‹አዳፍኔ፡ፍርሃትና መክሸፍ› በሚል ርዕስ አዲስ መጽሀፍ አሳትመዋል፡፡
‹አዳፍኔ› ፕሮፌሰሩ በ2005 ዓ.ም ያሳተሙት ‹መክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክ› መጽሀፋቸው ተከታይ ክፍል ነው ማለት ይቻላል፡፡ ለዚህም ሁለት አስረጂዎችን ማቅረብ ይቻላል፡፡ አንደኛው ከጭብጥ አኳያ ብዙ ተመሳስሎሽ አላቸው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ ‹አዳፍኔ› ከያዛቸው አስር ምዕራፎች ውስጥ ሶስቱ (ይህም የመጽሀፉን ዘጠና ስድስት ገጾች ወይም 40 በመቶ ያህል ይሸፍናል ማለት ነው) በ‹መክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክ› ላይ በተለያዩ ጸሀፍት ለተሰነዘሩ ትችቶች ምላሽ የሰጡበት (በመጽሀፉ እንደተገለጸው የ‹ ትችቶች ትችት›) ነው፡፡
በዚህ መጣጥፍ አዘጋጅ አተያይ፤የመጽሀፉ ዋነኛ መገለጫዎች (መልኮች) ሁለት ናቸው፤እነዚህ ሁለት መገለጫዎችም የመጽሀፉ ውበቶች ናቸው፡፡ የመጀመሪያው መጽሀፉ በይዘቱ ሰፋ ያለ መሆኑ ነው፤ከዚሁ ጋር የተያያዘው ሁለተኛው፣ መጽሀፉ በቅርጹና አቀራረቡ የራሱ የሆነ አዲስ ቀለም ይዞ መምጣቱ ነው፡፡ አዳፍኔ ፍርሃትና መክሸፍ እጅግ በርካታ ጉዳዮችን ይዳስሳል፤ታሪክ፣ባህል፣ስልጣንና አገዛዝ (ፖለቲካ)፣ኢኮኖሚክስ፣ስነመንግስትና አስተዳደር (አገር፣ህዝብና መንግስት)፣ሀይማኖት፣ትምህርትና ዕውቀት እንዲሁም ዕውነት፣ ስነ-ልቦና፣ፍልስፍና እና በሌሎች የጥናት ዘርፎች ዙሪያ የሚሽከረከሩ ጽንሰ ሀሳቦችን ያነሳል፡፡ ሌላው የመጽሀፉ መልክ ለጥናትና ምርምር፣ለጥልቅ ውይይትና ክርክር የሚጋብዙ ሀሳቦችን ማንሳቱና በዚሁ በተቃኘ አቀራረብ መዘጋጀቱ ነው፡፡
ወጣቱ ደራሲና የታሪክ ተመራማሪ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት፤ በመክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክ መጽሀፍ ዙሪያ ያለውን አተያይ ከሁለት አመታት በፊት ገደማ በአንድ መጣጥፉ አስነብቦናል፡፡ ዲያቆን ዳንኤል በመጣጥፉ ካነሳቸው በርካታ ቁም ነገሮች አንዱ የክሽፈት ታሪክ እንጂ የታሪክ ክሽፈት የሚባል ሊኖር አይችልም የሚለው አንዱ ነው፡፡ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም፤ በአዳፍኔ ፍርሃትና መክሸፍ መጽሀፋቸው ‹የትችቶች ትችት› በሚለው ምዕራፍ ውስጥ ለዚህ መልስ ሰጥተዋል፤ ነገር ግን መልሱ አጥጋቢ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡  መልስ የተሰጠበት አግባብ የተደራጀና ግልጽ አይደለም፡፡ እንዲያም ሆኖ የአዳፍኔ ዋነኛ ጭብጥ በክሽፈት ታሪክና በታሪክ ክሽፈት ዙሪያ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ነገር ግን ሀሳቦቹ እዚህም እዚያም ተበታትነው የቀረቡ በመሆኑ በጉዳዩ ላይ አንባቢ የጠራ ግንዛቤ እንዳይኖረው ያደርጋል የሚል ስጋት አለኝ፡፡
በዚህ መጣጥፍ አቅራቢ እምነት፤ የክሽፈት ታሪክ እና የታሪክ ክሽፈት የሚሉት ሁለት ሀሳቦች ብዙ ጉዳዮችን ያዘሉ በመሆናቸው በጥልቀት መታየት አለባቸው፡፡ በመሆኑም  አዳፍኔ ፍርሃትና መክሸፍ ስለ ክሽፈት ታሪክና ስለ ታሪክ ክሽፈት ያነሳቸውን ሀሳቦች በማሰባሰብ ለማቅረብ ተሞክሯል፡፡ መጽሀፉ ከአደረጃጀት አንጻር በዚህ ሁኔታ ቢቀርብ መልዕክቱን በይበልጥ ለመረዳት ያስችላል፤በመጽሀፉ በተነሱት ጉዳዮች ላይ በአንባቢያን የሚቀርቡ የውይይትም ሆነ የክርክር ሀሳቦች ቅርጽ እንዲይዙ ለማድረግም ያግዛል፡፡
የታሪክ ምንነት፣ባህሪያትና ዓላማ
የታሪክ ፍልስፍና ዘይቤ አባት በመባል የሚታወቀው አውግስ ሚኖስ፤ የታሪክ ምንነትና ዓላማን ሲገልጽ እንዲህ ይላል፡-
ታሪክ መንግስት መቆሙንና መፍረሱን፣ ህዝቦች ማደጋቸውንና መውደቃቸውን ያትታል፡፡ ይህም የሚሆንበት ምክንያት አምላክ ባቀደው መሰረት የሰውን ዘር ወደ እውነተኛው ብርሃን ለመምራትና ለማዳን ሲል ነው፡፡
የፕሮፌሰር መስፍን የታሪክ ምንነትና ዓላማ አረዳድም ከአውግስ ሚኖስ ጋር በይዘቱ አንድ ነው፣ቋንቋው ቢለወጥም፡፡ እንደፕሮፌሰሩ አገላለጽ ታሪክ ማለት፡-
“…..ለአንድም ሰኮንድ የማያቋርጥ የኑሮና የአኗኗር ጅረት ነው፡፡ ……..ታሪክ የአንድ ህዝብ የስራ መዝገብ ነው፡፡” (ገጽ 98-99)
የታሪክ ዓላማ ደግሞ ህዝቡ ያለፈውን ዘመን ከፍታና ዝቅታ አስታውሶ፣ የአሁኑ ትውልድ ካለፈው ትውልድ በጎ ጎኖች ትምህርት ወስዶ፣ ከችግሮቹ ተምሮ፣ በኑሮው መሻሻል እንዲያሳይ ማድረግ ነው (ገጽ 28፣29 )፡፡  
በአጠቃላይ፡- ታሪክ ማለት የትናንት ዕውነትን (በጎም ሆነ በጎ ያልሆኑ) መመርመር ነው፡፡የታሪክ ዓላማ የሰው ልጅ የትናንት በጎ ተግባራቱን አዳብሮ፣ከስህተቱ ደግሞ ተምሮ የዛሬና የነገ ህይወቱን እንዲያቀና ማድረግ ነው፡፡ በዚህም አውግስ ሚኖስ የታሪክን አስፈላጊነትና ዓላማ ከመለኮታዊ ሀይል ዓላማ ጋር ያዛምደዋል፡፡ በዚህም የታሪክ ዓላማ የፈጣሪ አላማ ነው፡፡
ስለታሪክ ባህሪያት
በግሌ የታሪክ ባህሪ ከአምላክ ባህሪ ጋር ይመሳሰልብኛል፡፡ ታሪክ አምላካዊ ባህሪዎችን ሁሉ ይወርሳል፡፡ ታሪክን ከአምላካዊ ባህሪ ጋር ለማንጸር ያደረግሁት ጥረት ያልተመቻቸው የአምላክን ባህሪ የማያውቁ ናቸው ባይ ነኝ፡፡ ለመሆኑ የአምላክ ባህሪያት ምንድናቸው? የታሪክ ባህሪያትስ ?
በመሰረቱ የአምላካዊነት መሰረት ሀቅ ነው፤የታሪክ መሰረቱም እንዲሁ ሀቅ (እውነት) ነው፡፡ ፈጣሪ የሰው ልጆችን ጨምሮ በአጠቃላይ በፍጡራን ላይ ፍጹም ስልጣን አለው፤ታሪክም ይህ ስልጣን አለው፡፡ የፈጣሪ ዓላማ የሰው ልጆች ሁሉ በቀና መንገድ እንዲያልፉ ማስተማር ነው፤የታሪክ ዓላማም እንደዚሁ ነው፡፡ ወደር የለሽ ትዕግስትና ሆደ-ሰፊነት አምላካዊ ባህሪ ነው፤ዓላማውም ሰዎች በራሳቸው ከጥፋት መንገድ እንዲታቀቡ፣ካለፈው ስህተታቸው እንዲታረሙ ጊዜ መስጠት ነው፡፡ የታሪክ መንገድም ይህ ነው፡፡ በመሰረቱ ዕውነትን (ታሪክን) መበረዝ ወይም ማጥፋት የሚቻል ሊመስለን ይችላል፡፡ መሪዎችም ይህን ለማድረግ የቻሉ ሊመስለን ይችላል፡፡ ግን በጥልቀት ከመረመርነው አልቻሉም፡፡ የፈጣሪን ትዕግስት ዓላማ ያልተረዱም በስህተት ላይ ስህተት እየፈጸሙ፣ በመጨረሻም ከነጭራሹ የፈጣሪን ስልጣን ሲመኙ፣ሲብስም ህልውናውንም ሲክዱ፣መቀበሪያቸውን ጉድጓድ እየማሱ እንደሆነ ሳይታወቃቸው፣የትዕግስቱ መብዛትም በቆፈሩት ጉድጓድ እንዲቀበሩ ያደርጋቸዋል፡፡ የታሪክም መንገድ ይህ ነው፡፡ ታሪክ ከስህተት ለመማር እድል ይሰጠናል፡፡ ይህን ማድረግ ያልቻሉ ግን በቆፈሩት ጉድጓድ ይቀበራሉ፡፡ በታሪክ ማህደር እንደተዘከረው፤ በታሪክ ላይ የዘመቱ ሁሉ መጨረሻቸው መጥፋት ነበር፡፡ በእርግጥም በዘመናት ሂደት ያለፉ፣ታሪክ ላይ ያመጹ አገዛዞችና ነገስታት አነሳስና አወዳደቅን ለመረመረ ይህ ይገለጥለታል፡፡ ታዲያ የፈጣሪ የቅጣት በትር ፍጹም ፍትሃዊ እንደሆነው ሁሉ የታሪክ ቅጣትም ጊዜ ወይም ቦታ የማይቀይረው፣ ለማንም የማይወግን ፍጹም ፍትሃዊ ነው፡፡ ትናንትም ይሁን ዛሬ በታሪክ ላይ ያመጹ ሁሉ በጥፋታቸው ልክ ተቀጥተዋል፤ነገም እንዲሁ እንደሆነ ይቀጥላል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን በአንድ ዓመት በዓል ወቅት፣ አንድ አባት ልጁን ይዞ ወደ አንድ ሆቴል ቤት ጎራ ይላል፡፡ ለልጁ ለስላሳ ለሱ ነጭ አረቄ አዞ መጠጣት ይጀምራል፡፡ ያን አረቄ በላይ በላዩ ሲጨማምርበት ወደ ሞቅታው ተጠጋ፡፡
አረቄውን ልትቀዱለት የምትመላለሰው ቆንጆ ሴት እየተሞናደለችና ሽንጧን እያተራመሰች ስትመላለስበት ዐይኑ ከሱዋ አልላቀቅ አለ፡፡
“አንቺም ጠጪ፣ ለኔም አምጪ” ማለት ጀመረ፡፡ ቆንጆይቱም መጎንጨት ጀመረች፡፡ ሞቅ አላቸው ሁለቱም፡፡ ተጠቃቀሱና ተራ በተራ ወደ ጓዳ ገቡ፡፡
ይህ ሁሉ ሲሆን ልጅየው ለስላሳውን ትንሽ በትንሽ እየጠጣ ሲያስተውል ቆይቷል፡፡ አባቱ ሳይመለስ ብዙ የቆየ ስለመሰለው፣ ወደሄደበት አቅጣጫ ሄደ፡፡ አንድ ክፍል ውስጥ ተኝተዋል ለካ! ደንግጦ ቶሎ ወደ ቦታው ተመልሶ ተቀመጠ፡፡
አባትዬው ተመለሰ፡፡ አንድ ደግሞ ሂሳብ ከፈለና ወጡ፡፡
ቤት ደርሰው የሚበላ ቀርቦ በልተው እንደጨረሱ ጨዋታ መጣ፡፡
እናት - “እሺ ዙረታችሁ እንዴት ነበር?” አለች ወደ ልጁ እያየች፡፡
ልጁም - “መጀመሪያ ወደ ሆቴል ሄድን”
እናት - “እሺ?”
ልጅ - “አባዬ አረቄ አዘዘ፡፡ ለእኔ ለስላሳ ሰጠኝ”
እናት - “ከዛስ?”
ልጅ - “ከዛማ አባዬ ደጋገመ”
አባት - “በቃህ እንግዲህ! ወሬ አታብዛ”
እናት - “ተወው እንጂ ይንገረኝ”
ልጅ - “ከዛ የምታስተናግደንን ሴትዮ ጋበዛት”
እናት - ጉጉቷ ጨመረ፡፡ “እሺ ከዛስ?”
ልጅ - “ከዛ ሴትዮዋ ወደ ጓዳ ሄደች”
አባት - “አንተ ልጅ! ሁለተኛ ሽርሽር አልወስድህም!”
እናት - “ተወው ይጨርስልኝ!”
ልጅ - “ከዛ አባዬም ወደ ውስጥ ገባ”
እናት  - በችኮላ፤ “እሺ? ከዛስ?”
ልጅ - “አባዬ ሲቆይብኝ የት ሄደ ብዬ ወደዛ ሄድኩ”
እናት - “ከዛስ?”
ልጅ - “ከዛ አይቼ ተመለስኩ”
እናት - “ምን አየህ?”
ልጅ - አመነታ!
እናት ሁኔታው ገብቷት - “አይዞህ ንገረኝ”
ልጅ፤ እናቱንም አባቱንም አየና፤
“ያየሁትማ አንቺና ዘበኛችን እንደምትተኙት ዓይነት ነው!” አለ፡፡  
*           *          *
የሌላውን ዐይን ጉድፍ ለማሳየት ከመጣጣር የራስን ጉድፍ አስቀድሞ ማየት፣ አስቀድሞ ማውጣት ታላቅ ብልህነት ነው፡፡ ሁሉም ለስህተት በሚጋለጥበት ሁኔታ ውስጥ እያሉ አንዱ ባንዱ ላይ ጣቱን ቢቀስር ውጤቱ ሲቀሳሰሩ መዋል ነው፡፡ በንጉሡ ዘመን የወጣ አንድ ካርቱን ስዕል ባሳየው ምስል፣ ባለስልጣናት ወይም ሚኒስትሮች በትልቅ የኮንፈረንስ ጠረጴዛ ዙሪያ ተቀምጠዋል፡፡ እያንዳንዳቸው፣ አንዱ ባንዱ ላይ በሌባ ጣቱ ይጠቁማል፡፡ ማንም በማንም ላይ ጣቱን ሳይቀስር የሚታይ የለም፡፡ ሁሉም ጥፋተኛ ነው እንደማለት ነው፡፡ ግምገማዎች ምን ያህል ሀቀኛ ናቸው? ስህተትን ለማረም የሚያስችል ምን ያህል ቅን ልቦና አለ? የተገመገሙት ሁሉ እርምጃ ይወሰድባቸዋልን? ያንንስ ማን ይቆጣጠራል? ግምገማ ከእከክልኝ ልከክልህ ነፃ ነውን? ከየአንዳንዱ ግምገማ ምን ያህል ተምረናል? የሚገመገምና የማይገመገም፣ ይነኬና አይነኬ ሰው የለምን? ግምገማ ራሱ መገምገም የለበትምን? ባለፈው ዘመን የኮሚቴ መብዛት ትልቅ ችግር ሆኖ ተሰበሰቡና አሉ፤ ይህንኑ የሚያጠና ኮሚቴ አቋቁመው ተለያዩ! ሀገራችን አባዜዋ ብዙ ነው፡፡ አንድ ተገምጋሚ፤ ስለሀገራችን የስድስት መስመር የህዝብ መዝሙር ፃፍ ተብሎ አሥር ገፅ ያህል የዓላማ ፅሁፍ ተሰጠው፡፡ ቢለው ቢለው ያን ሁሉ ዓላማ በስድስት መስመር ማጠናቀቅ እንደማይመች ታወቀውና፤
“እንኳን ስድስት መስመር፣ መቶም አይበቃሽ እንደው በደፈናው፣ ዕንቆቅልሽ ነሽ    !”ብሎ ደመደመ ይባላል፡፡
በግምገማ ንፍቀ - ክበብ ዋና ጉዳይ የሚሆነው አዎንታዊነት (Positivism) ነው፡፡ በአዎንታዊነት ውስጥ ተስፋ አለ፡፡ በአሉታዊነት ውስጥ ጨለምተኝነት ነው ያለው፡፡ ሰውን ማነፅ አገርን ማልማት ነው፡፡ ሙያን ማክበር ሙያተኛን ማበልፀግ ነው! ይህም አዎንታዊነት ነው፡፡ መንገድ መሥራት ባለሙያ ይፈልጋል፡፡ ሀዲድ መዘርጋት ባለሙያ ይፈልጋል፡፡ ባቡር ማስኬድ ባለሙያ ይፈልጋል፡፡ በባቡር መሄድ ደግሞ ስልጣኔ ይፈልጋል፡፡ የባቡሩን መነሻና መድረሻ ደግሞ መረጃ ጆሮ ነው የሚፈልገው፡፡ አዎንታዊነት ውስጥ ሟርትን እንዳንከት መጠንቀቅ ያንድ የሰለጠነ ህዝብ ብልህነት ነው፡፡ ብዙ የሰራን እያስመሰልን ውስጡ ውስብስብ መክተት አሉታዊነት ነው! አገር ገንዘብ ይኖራት ዘንድ ሁለት ሶስት ያለው ቢላ መጠቀምም አሉታዊነት ነው፡፡ አገር አቀናለሁ ብሎ ደፋ - ቀና የሚለው ዜጋ፣ በንፁህ ስሜት፣ በቀና ልቦና ሲወድቅ ሲነሳ፤ ሌላው ወገን በአጭር - አቋራጭ (Short-cut)፣ አየር ባየር ከባለሥልጣን በመመሳጠር፣ በቀጭን ቢሮክራሲያዊ ትዕዛዝ ወዘተ… ሀብቱን ሲያከማችና ፎቁን ሰማይ ሲያስነካ ማየት ዘግናኝ ነው! ጉዳይ አስፈፃሚ የሆነ ባለዘመድ (መንገድ አዋቂ) ከባለ ጉዳዩ በላይ የሚያገኝበት አገር ውስጥ ለአስተዋይ ሰው ከኮሜዲው ትራጀዲው ማየሉ አይገርምም፡፡ በየቀኑ ነገር የባሰበት ዜጋ፤ “ደረቁ ከበደኝ እያልኩ፣ እርጥብ ትጨምርበታለች” የሚለው ለዚህ ነው! ከዚህ ያውጣን!!

    በአሁኑ ወቅት እጅግ አሳሳቢ እየሆነ ለመጣው የኩላሊት ህመም መፍትሄ ይሆናል በሚል በዘውዲቱ ሆስፒታል ግቢ ውስጥ በመገንባት ላይ ለሚገኘው የህክምናና የዕጥበት ማዕከል የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ወጣቶች ፎረም ተካሄደ፡፡ ትናንት በግሎባል ሆቴል በተካሄደው በዚህ ፕሮግራም ላይ ለማዕከሉ ግንባታ የሚረዳ ገቢ ለማሰባሰብ በማህበረሰቡ ላይ በጎ ተፅዕኖ የሚፈጥሩ የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች፣ ታዋቂ ሰዎች፣ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎችና የመንግስት ባለስልጣናት ተገኝተዋል፡፡