Administrator

Administrator

 የአሜሪካ ሴቶች ከ95 አመታት በፊት የተጎናጸፉት መብት ነው
                   70 ሴቶች በዕጩ ተወዳዳሪነት እንደሚቀርቡ ይጠበቃል
    የሳኡዲ አረቢያ ሴቶች በመጪው ታህሳስ ወር በሚካሄደው የከተማ አስተዳደር ምርጫ በዕጩ ተወዳዳሪነትና በድምጽ ሰጪነት በመሳተፍ በአገሪቱ በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የምርጫ ተሳትፎ እድል ተጠቃሚ እንደሆኑ  ሲኤንኤን ዘገበ፡፡በምርጫ ተወዳዳሪነትም ሆነ በመራጭነት የመሳተፍ መብት ተነፍጓቸው የኖሩት የሳኡዲ አረቢያ ሴቶች፤በታሪካቸው ለመጀመሪያ ጊዜ ካለፈው ቅዳሜ ጀምሮ በመራጭነት እየተመዘገቡ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፣ ከነገ ጀምሮም በዕጩ ተወዳዳሪነት ይመዘገባሉ ብሏል፡፡የቀድሞው የአገሪቱ መሪ ንጉስ አብደላ የአገሪቱ ሴቶች እ.ኤ.አ ከ2015 ጀምሮ በምርጫ ተወዳዳሪነትና በድምጽ ሰጪነት መሳተፍ እንደሚጀምሩ ከአራት አመታት በፊት ማስታወቃቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ይሄም ሆኖ ግን ሴቶች ይሳተፉበታል በተባለው ቀጣይ የከተማ አስተዳደር ምርጫ የሚያሸንፉ ሴቶች የተገደበ ስልጣን እንደሚኖራቸው ገልጧል፡፡
በመጪው ምርጫ ሴቶች እንዲሳተፉ መፈቀዱ የአገሪቱን ሴቶች የፖለቲካ ተሳትፎ ተጠቃሚ በማድረግ ረገድ ተስፋ ሰጪ እርምጃ ነው መባሉን ዘገባው ገልጾ፣የሳኡዲ አረቢያ ሴቶች አሁንም ድረስ ከፍተኛ በደልና ተጽዕኖ እንደሚደርስባቸው ጠቁሟል፡፡
የሳኡዲ አረቢያ መንግስት ሴቶችን የምርጫ ተሳታፊ ለማድረግ መወሰኑ በሴቶች መብት ጥሰት ከፍተኛ ውግዘት ስታደርስበት ከኖረችው አሜሪካ ጋር የተሻለ ግንኙነት እንዲፈጥር በር ሊከፍትለት ይችላል ያለው ዘገባው፣ የአሜሪካ ሴቶች በምርጫ የመሳተፍ መብታቸው የተረጋገጠላቸው ከ95 አመታት በፊት እንደነበር አስታውሷል፡፡በመጪው ምርጫ 70 ያህል የሳኡዲ አረቢያ ሴቶች በዕጩ ተወዳዳሪነት ይሳተፋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅና ሌሎች 80 ሴቶችም በምርጫ ዘመቻ ሃላፊነት ለመስራት መመዝገባቸውን የዘገበው ዴይሊ ሜይል በበኩሉ፣ ይሄም ሆኖ ግን የአገሪቱ ሴቶች አሁንም ድረስ መኪና መንዳት፣ የባንክ ሂሳብ መክፈት፣ ከባላቸው ውጪ ፓስፖርት ማግኘትና ወደፈለጉት አካባቢ መዘዋወር እንደማይፈቀድላቸውና ዘርፈ ብዙ የጾታ ጫና እንደሚደርስባቸው ጠቁሟል፡፡
በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጾታዊ እኩልነት መለኪያ መስፈርት መሰረት፤ ሳኡዲ አረቢያ ከአለማችን 140 አገራት 136ኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ዘገባው አክሎ አስታውቋል፡፡

   የጦር ሃይሉ መቀመጫ በአገራቱ መካከል አለመግባባት ፈጥሯል
    የአረብ ሊግ አባል አገራት የመከላከያ ሚኒስትሮች የጋራ የጦር ሃይል ለማቋቋም የሚያስችላቸውን ስምምነት ከትናንት በስቲያ ለመፈረም ይዘውት የነበረውን ዕቅድ ላልተወሰነ ጊዜ ማራዘማቸውን ኤቢሲ ኒውስ ዘገበ፡፡አባል አገራቱ ግጭት በሚከሰትባቸው አካባቢዎች የሰላም ማስከበር ስራ የሚሰራ የጋራ የጦር ሃይል ለማቋቋም የሚያስችላቸውን ስምምነት ባለፈው ሃሙስ ሊፈርሙ ቀጠሮ ይዘው የነበረ ቢሆንም፣ ሊጉ በዋዜማው ባወጣው መግለጫ እቅዱ ላልተወሰነ ጊዜ መራዘሙን አስታውቋል፡፡አንዳንድ የፖለቲካ ተንታኞች ግን፣ እንደ ሊቢያ ባሉ አገራት መንግስትን ለሚቃወሙ ሃይሎች ድጋፍ የሚሰጡ የአረብ አገራት ባሉበት ሁኔታ፣ የሚያቋቁሙት የጋራ የጦር ሃይል ጣልቃ ይግባ አይግባ የሚለው ጉዳይ በአገራቱ መካከል አለመግባባት ሊፈጥር ይችላል ማለታቸውንም ዘገባው ጠቁሟል፡፡ የጦር ሃይሉ መቀመጫ የሊጉ ዋና ጽህፈት ቤት በሚገኝባት ካይሮ ይሁን የሚለው ሃሳብ በአገራቱ መካከል አለመግባባት ፈጥሮ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ ስምምነቱ የተራዘመው ሳኡዲ አረቢያ፣ ባህሬን፣ ኩዌት፣ ኳታር፣ የተባበሩት አረብ ኢሜሬትስና ኢራቅ ባቀረቡት ጥያቄ መሰረት መሆኑንም ገልጧል፡፡አገራቱ የጦር ሃይሉን ለማቋቋም ፈቃደኛ መሆናቸውን ባለፈው መጋቢት ወር በይፋ ማስታወቃቸውንና በግንቦትም ስምምነቱን ማርቀቃቸውን ዘገባው አስታውሶ፣የተራዘመው ስምምነት የሚፈረምበትን ቀን አገራቱ ወስነው እንደሚያስታውቁ ጠቁሟል፡፡

  - ለ4 ተከታታይ አመታት በደካማነት የሚስተካከለው አልተገኘም
                - ላለፉት 20 አመታት አዲስ አውሮፕላን ገዝቶ አያውቅም
                - አብዛኞቹ አውሮፕላኖቹ በ1960ዎቹ የተመረቱ ናቸው
                - ተሳፋሪዎች እቃቸውን በእቅፋቸው ይዘው ይጓዛሉ
    ላለፉት ሶስት አመታት በዓለማችን ከሚገኙ አየር መንገዶች ደካማው ሆኖ የተመረጠው የሰሜን ኮርያው የአየር መንገድ ኩባንያ ኤር ኮርዮ ዘንድሮም የደካማነት ክብረወሰኑን ማስጠበቁን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
ተቀማጭነቱ በእንግሊዝ የሆነውና የዓለማችንን አየር መንገዶች በተለያዩ መስፈርቶች በመገምገም በየአመቱ ይፋ የሚያደርገው ስካይትራክስ የተባለ አለማቀፍ የአቪየሽን አማካሪ ኩባንያ፣ዘንድሮም ደረጃ ከሰጣቸው 600 የተለያዩ አገራት አየር መንገዶች መካከል የሰሜን ኮርያውን ኤር ኮርዮ በመጨረሻ ደረጃ ላይ አስቀምጦታል፡፡
በስድስት አገራት ወደሚገኙ 14 መዳረሻዎች በረራ የሚያደርገው ኤር ኮርዮ፣ ከዚህ በፊትም አብዛኞቹ አውሮፕላኖቹ በ1960ዎቹ የተመረቱና ያረጁ ናቸው በሚል መቀጣቱን ያስታወሰው ዘገባው፣ አየር መንገዱ ላለፉት 20 አመታት አዲስ አውሮፕላን ገዝቶ እንደማያውቅ ገልጧል፡፡
አብራሪዎቹ ዲጂታል ድጋፍ ሳያገኙ ለአደጋ በሚያጋልጥ ሁኔታ እንደሚያበሩ፣ ተሳፋሪዎች እቃቸውን በእቅፋቸው ይዘው እንደሚጓዙ፣ ለመዝናኛ ተብለው የሚከፈቱ ሙዚቃዎችና ቪዲዮዎችም የአገሪቱን መሪ የሚያንቆለጳጵሱ ብቻ እንደሆኑ ኩባንያው ገምግሟል፡፡
ስካይትራክስ አየር መንገዶችን በአውሮፕላኖች ብቃት፣ በደንበኞች አገልግሎት ጥራትና በሌሎች የአቪየሽን መስክ ጥራት መመዘኛ መስፈርቶች እየለካ በየአመቱ ደረጃ እንደሚሰጥ ይታወቃል፡፡

Monday, 31 August 2015 09:13

የዘላለም ጥግ

 የስኬትንቁልፍ አላውቀውም፤ የውድቀት ቁልፍ ግን ሁሉን ሰው ለማስደሰት መሞከር ነው፡፡
       ቢል ኮዝቢ
ህይወት ተፅዕኖ የመፍጠር ጉዳይ እንጂ ገቢ የመፍጠር ጉዳይ አይደለም፡፡
      ኬቪን ክሩስ
ሁሉም ሰው ዓለምን ስለመለወጥ ያስባል፤ማንም ግን ራሱን ለመለወጥ አያስብም፡፡
      ሊዮ ቶልስቶይ
ሁላችንም እናልማለን፡፡ ደግነቱ ደግሞ ህልሞች እውን ይሆናሉ፡፡
       ኬቲ ሆልመስ
ህይወት ከባድ ነው፤ደደብ ስትሆን ግን የበለጠ ከባድ ይሆናል፡፡
       ጆን ዋይኔ
ህይወት በጣም አጓጊ ነው-----አንዳንድ ትላልቅ ህመሞችህ የማታ ማታ ትላልቅ  ጥንካሬዎችህ ይሆናሉ፡    ፡
       ድሪው ባሪሞር
አዎንታዊ ህይወትና አሉታዊ አዕምሮ     ሊኖርህ አይችልም፡፡
      ጆይስ ሜየር
የህይወታችን ዓላማ መደሰት ነው፡፡
     ዳላይ ላማ
ህይወትን መኖር እንጂ መመዝገብ አልፈልግም፡፡
      ጃኪ ኬኔዲ
ቀኑን አንተ ትመራዋለህ ወይም ቀኑ አንተን ይመራሃል፡፡
      ጂም ሮህን
ትግል ከሌለ ዕድገት የለም፡፡
      ፍሬድሪክ ዳግላስ
ለውጥ ዕድል ይዞ ይመጣል፡፡
      ኒዶ ኪውቤይን
ህይወትህ የስዕል ሸራ ነው፤በቀለም ሙላው፡፡
      ያልታወቀ ፀሐፊ

የመጽሐፍ ቅኝት - በአብነት ስሜ)

ካለፈው የቀጠለ
ተራኪው እና ደራሲው
የልቦለዱ ተራኪ እኔ ሞኝ ነኝ፤ እኔ ፈሪ ነኝ ይላል። ነገር ግን፣ ሞኝነቱ ውስጡ አስተዋይነትን፣ ፍርሀቱ ውስጥ ደግሞ ድፍረትን ማየት ይቻላል። ተራኪው ከክርስቶስ ይልቅ ለደቀመዝሙሩ ለጴጥሮስ ይቀርባል። ጴጥሮስ እንደ ህፃን የዋህ፣ ጉጉ፣ ችኩል፣ ፈጣንና ፍርሀት አልባ ነው። ብዙ ይጠይቃል። ይጋፈጣል። ለክርስቶስ በጣም ቅርቡ ነበር። ውሀ ላይ እንደ ክርስቶስ መራመድ ከጀመረ በኋላ መሀል ላይ ራሱን ይጠረጥራል። እናም ይፈራል። መስጠም ሲጀምር ወደ ክርስቶስ ይጮሀል።  ከመስጠምም ይድናል። ጌታውን ሊይዙ ከመጡት ውስጥ ያንዱን ጆሮ በሰይፍ ቀንጥሷል። በዚህም ግን ተገስፆአል። ክርስቶስ በተያዘ ጊዜ ከደቀመዛሙርቱ ውስጥ ለረዥም ጊዜ በድፍረት የተከተለው ጴጥሮስ ነው። በተጠየቀ ጊዜ ግን ስለፈራ፣ “ይህንን ሰው አላውቀውም” ብሎ ሦስቴ ካደ። ድፍረቱ ሳይታይለት በክህደቱ ብዙ ተወቀሰ፤ ተገሠፀ፤ ተሣቀቀ።  ሌሎች ኢየሱስን ጥለውት የሔዱ ደቀመዛሙርት ግን እንደ እርሱ አልተወገዙም። ሐዋርያው ጴጥሮስ የዋህ ቢመስልም ብልህ ነበር፤ ጀግና ቢመስልም ፈሪ ነበር።
የወሪሳ ልቦለድ ተራኪም ለኢየሱስ ሳይሆን ለጴጥሮስ ነው የሚቀርበው።  በተራኪው ውስጥ የምናየው ደራሲውም የተላበሰው ሰብእና ኢየሱሳዊ ሳይሆን ጴጥሮሳዊ ነው።  የዋህና ፍርሀት አልባ ሕፃን ባይሆን ኖሮ እንዲህ ዓይነቱን ህልም አይጽፍልንም ነበር። ይህንን ዘግናኝ ነውራችንን የህፃን የዋህነት የሌለው ደራሲ ካልሆነ ማንም አይነግረንም።
ክርስቺያን አንደርሰን የተባለው ኖርዌጂያዊ እንደዚህ እንደ ዓለማየሁ ገላጋይ ጴጥሮሳዊ ህፃንነትና የዋህነትን የተላበሰ ደራሲ ነበር። “የንጉሱ ልብስ” በተሰኘ ልቦለዱ እንደራሱ ያለ አንድ ህፃን ፈጥሮልን አልፏል። ታሪኩን አብረን እናስታውስ። ንጉሡ ማጌጥ ይወድዳል። ለየት ያሉ አልባሳትን ያደንቃል። ይህን የተረዱ ሁለት አታላዮች ከንጉሡ ዘንድ ይቀርቡና ልዩ የሆነ ትንግርታዊ መጎናፀፊያ ለንጉሡ ለማዘጋጀት እንደአቀዱ ይናገራሉ። ልብሱን ለየት የሚያደርገው በክፉና በተንኮለኛ ሰው ዓይን አለመታየቱ ነው።  አንዱ  የንጉሡ ሚኒስትር ልብሱ ከሚደወርበት ሔዶ እንዲያይ ተላከ። ባዶ የሽመና ዕቃ ብቻ አየ። ልብስ የሚባል የለም። “አይ ክፉና ተንኮለኛ ከምባልስ” በሚል መንፈስ ያላየውን እንደ አየ አድርጎ ተናገረ። ሌሎች ሹማምንትም  እንዲሁ አደረጉ። ልብሱ ተጠናቀቀ ተባለና ወደ ንጉሡ ተወሠደ። ንጉሡም በግብዝነት ያላየውን እንደ አየ፣ የሌለውን እንደ አለ አድርጎ “ልብሱን ለበሰና” በሰልፍ ወጥቶ ወደሚጠብቀው ህዝብ በሰረገላ ሆኖ መታየት ጀመረ። ተመልካቹ ሁሉ “ክፉና ተንኮለኛ” ላለመባል  ሲል “ግሩም ድንቅ” እያለ የንጉሡን አዲስ መጎናጸፊያ አደነቀ። ንጉሡ ግን ራቁቱን ነበር። ታዲያ ከሰልፈኛው ህዝብ መካከል አንድ ህፃን ልጅ እንዲህ አለ፤ “እናንተ ንጉሡ ራቁቱን ነው።” ከዚህ ቃል በኋላ የታወረው ህዝብ አየ። ንጉሡም ከቀን እንቅልፉ ነቃ።
ሐዋርያው ጴጥሮስ በአንደርሰን ተረት ውስጥ እንዳለው ህፃን ነው። የአንደርሰን የራሱም ተፈጥሮ በተረት እንደተፈጠረው ህፃን ነው። ህፃኑ ራሱ አንደርሰን ነው። ዓለማየሁ ገላጋይም ጴጥሮሳዊ ነው። ነገረሥራው ሁሉ እንደ ደራሲው አንደርሰን ነው። የወሪሳ ተራኪና የአንደርሰን ተረት ውስጥ ያለው ህፃንም አንድ ናቸው። ገበናችንን ይገልጡታል፤ጉዳችንን ያሣዩናል።
ወሪሳዊ ተውሳክ
ወሪሳ ስርቆትና ዝርፊያ የነገሡበት የጉድ ሠፈር ነው። በዚያ ሰፈር “ቢዝነስ” መስራት ማለት መስረቅ፣ ማጭበርበር፣ መዝረፍና መግደል ነው።  ይኸ በሀገር ደረጃ የተዋቡና የሚያደናግሩ ቃላት እየተጠቀምን “ሙስና እና ኪራይ ሰብሳቢነት” የምንለው ነገር በወሪሳ ሰፈር ውስጥ ራቁቱን የሚመላለስ ጀግና ነው። በወሪሳ ውስጥ ሰርቶ የሚበላው ሞኙ ተራኪ ብቻ ነው። በዚያ ምድር ሰርቶ የሚበላ “ፋራ” ነው። የሚበላው፣ የሚሰረቀው ግን ማን ነው? የሚበላው ወደ ሥራ የሚሠማራው ሞኝ ወይም ፋራ ነው።  ስለዚህ ወሪሳ ፓራሳይት ወይም ተውሳክ ነው። ተውሳክ በሽታ ነው። የራሱን ምግብ አያመርትም። በተክል ወይም በሰው ላይ ሰፍሮ ሰለባውን እስኪሞት ድረስ ይበላዋል። ሌባ፣ ዘራፊ፣ ጉቦኛ፣ ሙሰኛ፣ ወይም ኪራይ ሰብሳቢ የህብረተሰብ ተውሳክ ነው።
በሀገር ደረጃ ሲታይ ኢትዮጵያም ትልቋ ወሪሳ ነች። ሳንሰራ የምንበላ ሌቦችና ለማኞች እየሞላናት ነው። ሰርቶ የሚበላው ሁሉ እንደ ወሪሳው ተራኪ ፋራ ነው። በዚሁ ከቀጠልን የሚቀሩን ፋራዎች ቁጥር እየተመናመነ ይሔድና ምንም ይሆናል። ያኔ እንግዲህ በአሪፍ የሚበላው ፋራ ይጠፋል። ከዚያ ትልቁ አሪፍ ትንሹን አሪፍ መብላት ይጀምራል። የወሪሳ ነዋሪዎች ሁሉም “ብልጥ” ናቸው። ስለዚህ አይሠሩም። ይሠርቃሉ። የኢትዮጵያ ሰዎችም እንደ ወሪሳ ሰፈር ሰዎች ብልጠታቸው እየጨመረ “ፋራነት” የተባለውን ሠርቶ መብላትን እያስወገዱ ነው።
በ1980ዎቹ አጋማሽ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪ እያለሁ የሰማሁት አንድ ነገር ሁሌም ከአእምሮዬ አይጠፋም። ሴትየዋ በስድስት ኪሎ ካምፓስ አቅራቢያ ጠላ ቤት አላቸው አሉ። ልማደኛ ተማሪዎች እዚያ ያመሻሉ። ኮማሪትዋ የልጆቹን የትምህርት መስክ እየደጋገሙ በመጠየቅ ብዙ አውቀዋል። ታዲያ አንድ ቀን፣ “እኔ ምለው” አሉ። “እኔ ምለው፣ አንዳችሁም እንኳ ጉምሩክ የሚባል ትምህርት አትማሩም?”
የትምህርት ባህላችንም ከሞላ ጎደል ይኸው ነው። ድሮም ሆነ አሁን ያው ነው። ከጥቂት “ፋራዎች” በስተቀር የትምህርት ሥርዓቱ ያፈራልን የወሪሳ መዓት ነው። እንደ አማርኛ አስተማሪው ተራኪ ፋራ የሚሆኑ ጥቂት ናቸው። ሌላው “ግራጁዌት” ሁሉ ወሪሳዊ ነው። አሁን ደግሞ ሁሉም “ነቄ” ሆኗል። ሠርቶ የሚበላ ፋራ እንደ ዳይኖሰር ጠፍቶ ሊያበቃ የቀረው አንድ ሐሙስ ነው። ዛሬ ረቡዕ ነው። ነገ ማለዳ ላይ “አሪፍ” ነን ያሉ ሁሉ “ፋራ” እንደሆኑ ይረዱታል። አጉል አሪፍነታችንን በቶሎ ካላቆምን መጨረሻችን አያምርም። ተረቱ የፉክክር ቤት ሳይዘጋ ያድራል ይላል። ፉክክር የብልጥ ነው፤ብልጠት እናበዛለን።
ገዢዎቻችን
በሀገራችን አንድ የሚገርመኝ ነገር አለ። ሁሉም ፖለቲከኛ ነው። ሁሉም ለፍላፊ ነው።  ሁሉም ሥልጣን ይፈልጋል። ሁሉም መግዛት ይፈልጋል። ሰርቶ የሚበላ ገበሬ ብቻ ነው። ሌላው ገበሬ የሚያመርተውን ይበላል። ከዚያም አልፎ የገበሬው የበላይ ይሆናል።
ስንትና ስንት ህዝብ እያለበት አገር የንጉሥ ነች ይባላል። ንጉሥ ዘራፊ ነው። ዘራፍ ማለት ዘራፊ ከሚለው ቃል የወጣ ነው። ዘራፊ ጀግና ነው። የሚሰርቅና የሚዘርፍ ጀግና ነው ይባላል። ንጉሡ ዘራፊ ነው። ሀገር ሙሉ የኔ ነው ብሏል። የንጉሡ አንጋሾች ዘራፊዎች ናቸው። ሳይሠሩ ነው የሚበሉት። የንጉሡ ወታደሮችም ዘራፊዎች ናቸው። ሳይሠሩ ነው የሚበሉት።
መንግስቱ ለማ የአባታቸውን ትውስታዎች “ትዝታ ዘ አለቃ ለማ” በሚል መጽሐፍ አሳትመውታል። በዚህ መጽሐፍ ውስጥ አስደማሚ ትረካዎች አሉ። አለቃ ለማ አባታቸውን ወደ ትምህርት ላከኝ ብለው የሙጥኝ ይላሉ። ይኸ የዛሬ 150 ዓመት ገደማ ነው። ለማ ካልተማሩና ካህን ካልሆኑ አራሽ ገበሬ ሊሆኑ ነው። በወቅቱ፣ ገበሬ በወታደር ይዋረዳል። ንብረቱን ይቀማል። ሚስቱን ይነጠቃል። በዚያ ሳቢያ እርሻውን እየተወ “የጌታ የሚያድር” ይበዛ ነበር። እንግዲህ አገሩ ሁሉ ገበሬ ነው። የሚያመርት እሱ ነው። እሱ ግን ይዘረፋል፤ ይዋረዳል። ከዚህ ውርደት የሚተርፍ ፍጡር ቢኖር ካህን ብቻ ነው።  ስለዚህ አለቃ ለማ፣ አልቅሰውና ጮኸው ወደ ዘመኑ ትምህርት ተላኩ።
ካህንና ወታደር የገዥዎች እጅ ናቸው። ካህን ህዝቡን በመስበክ መንፈሱን ያኮላሸዋል። ወታደር ደግሞ ህዝቡን በጦር እየወጋ አካሉን ያደቅቀዋል። በመንፈስና  በአካል የተኮላሸ ህዝብ ብቻ ነው ሊገዛ የሚችል። በወቅቱ ይገዝዛ የነበረው ገበሬው ነው። ከባህላዊው ወደ ዘመናዊው ትምህርት ስንሸጋገርም የሰው ዓላማ ተምሮ ለመሥራት አልነበረም። ይህ መንፈስ አሁንም አለ። የተማረ ሁሉ ስሙ ይለያይ እንጂ ያው ካህንና ወታደር ነው የሚሆነው። የገዥ እጅ ነው። ገዥው የውጭም የሀገር ውስጥም ሊሆን ይችላል። ቁጭ ብዬ ልብላ ብሎ የሚማር ሁሉ ጤነኛ አይደለም። ተውሳክ ነው። ትምህርትን እንደ ጽድቅ ነው የምናየው።  ከጭለማ ወደ ብርሃን የምንወጣበት መንገድ ነው እየተባለ ብዙ ተሰብኳል። እውነታው ግን እሱ አይደለም። ትምህርት የሰለጠኑ ባሮች የማፍሪያ መሣሪያ የሆነበት ጊዜ ብዙ ነው። ትምህርት የዕድገት መሠረት ነው እያልን ስንዘምር አንድ መቶ ዓመት ደፍነናል። እውነታው ግን እድገት የትምህርት መሠረት መሆኑ ነው። አድጎ የተማረ እንጂ ተምሮ የበለፀገ ሀገር የለም።
እነዚህ ሁሉ ውዥንብሮች ወሪሳዎችን እያበዙና “ፋራዎችን” እየቀነሱ ነው። ወደ እውነታው ብንመለስ ይሻላል። እንደ ግብዙ ንጉሥ የዘመኑ ሥልጣኔ ያስገኘውን ድንቅ መጎናጸፊያ ለብሰናል ብለን ራሳችንን ባናታልል ይበጀናል። በብዙ ቦታ እርቃናችንን ነን። ብልጠት አብዝተን የወሪሳ አገር እየሆንን ነው።
ሺ-ትርገጥ እና ጭፍን
ሺ-ትርገጥ የአምበርብር ልጅ ነች። አባትና ልጅ በቀመሩት ታላቅ ሤራ ሺ-ትርገጥ የተራኪው ህጋዊ ሚስት ትሆናለች። ባህሪዋ ጥልቅና ድብልቅልቅ ነው። በአካላዊ መጠን አባትዋ ደቃቃ ነው። እሷ ግን በእናትዋ ወጥታ ግዙፍ ወይም መንዲስ ነች። ግዙፍነትዋ ልዩ ነው። ለእኔ ከጉማሬ እናትና ከዳይኖሰር አባት የተወለደች ሆና ትታየኛለች። ተራኪው በአነስተኛ የሥጋ ተራራ ይመስላታል። አንዳንዴም ከደብረ ዳሞ ተራራ ጋር ያመሳስላታል። ተራኪው በገመድ እየተጎተተ ይወጣል። የገመዱ ጎታች የአማቱ፣ የሺ-ትርገጥ አባት አምበርብር ነው። ይህ ገለፃ የተራኪው ነፍስ በማን እጅ እንደሆነች ይነግረናል።
እዚህ ላይ ፃድቁን ያመላልስ ነበር የተባለው ዘንዶም በማን እንደሚመሰል መገመት ይቻላል። ሺ-ትርገጥ ተራኪውን የምታጠምደው በአልጫና በቀይ የበግ ወጥ ነው። ተራኪው በሆዱ ተጠምዷል። ደሞዙ ከወር ወር አይደርስም። ይርበዋል። በተለይ አንድ ቀን አሜሪካ በ77ቱ ረሀብ ለኢትዮጵያ እንደደረሰችላት ዓይነት ነው ሺ-ትርገጥ አገልግል ተሸክማ በረሀብ ዝሎ በ7 ሰዓት ላይ ከቤቱ አልጋ ላይ ለተንጋለለው ተራኪ የምትደርስለት። ሺ-ትርገጥ ተራኪውን ጭፍን ከተባለች ወዳጁ፣ አሜሪካ ደግሞ ኢትዮጵያን ከሶቪየት ኅብረት ወይም ከሶሻሊስቱ ጎራ ትነጥላታለች።
ሺ-ትርገጥ ተራኪውን ከማግባትዋ በፊት አንድ አገር ልጆች ወልዳለች። በቁጥር ግን አራት ናቸው። ቤት ሞልተው ይንጫጫሉ። የቤቱ ግድግዳ “ፖሊስና እርምጃው” በተሰኘ ጋዜጣ ከዳር እስከ ዳር ለብሷል። ልጆቹ በአያታቸው እየተመሩ እነዚህን ጋዜጦች ያነባሉ። ተራኪው ባልወለዳቸው ልጆች ይከበባል። በህልም አፈታት እነዚህ ልጆች ማን ናቸው?
የተራኪው የፀሐይ ኮከብ ሐመል እሳት ወይም ኤሪስ ነው። ኮከቡ ከኢትዮጵያ የምድር ኮከብ ጋር ይገጥማል። እሱ የኢትዮጵያ ጭንብላዊ ተምሳሌት ነው። ባልወለዳቸው ልጆች የአሳዳጊነት እዳ ገብቷል። የርሱ ገቢ ለነዚህ ሁሉ ልጆች ማሳደጊያ አልበቃም ማለት ይጀምራል። ልጆቹ የዐባይ ወንዝ ጥገኛ የሆኑት ሀገሮች ህዝቦች ናቸው። ግዙፍዋ ሺ-ትርገጥ የአሜሪካ ተምሳሌት ነች። ከዚህ በላይ ለብልህ አይነግሩም፤ ለአንበሳ አይመትሩም ነው ተረቱ። አሁን ደቃቃው የተራኪው አማት፣ የሺ-ትርገጥ አባት የየቷ ሀገር ተምሳሌት እንደሆኑ መገመት የማይችል አንባቢ አይኖርም።
ከሺ-ትርገጥ በተጓዳኝ ሌላ ገፀባህሪ አለች። ጭፍን በመባል ትታወቃለች። ለልቦለዱ ተራኪ ብዙ ተረት ትነግረዋለች። በጭፍን አንደበት የአማርኛ ተረትና ምሳሌዎች ኩላሊታቸው ፈርጦ ጨጓራቸው ይዘረገፋል። ፍቅር እስከ መቃብር የተባለው ልቦለድ በጭፍን “ቨርዥን” ሲተረክ ከፍ ያለ የእሳት እቶን ወይም “ካምፋየር” ውስጥ የገባ ጀሪካን ይሆናል። ሀዲስ ዓለማየሁ ሊብራ ናቸው።
ተራኪው ከጭፍን ጋር አፍላጦናዊ ወደ አልሆነ “ሮማንቲክ” ፍቅር ውስጥ ይገባል። ልቡ አብዝቶ ወደርሷ ይሳባል። ከጭፍን ጋር ያለው ፍቅር በሺ-ትርገጥ የጋብቻ ሤራ ይጨናገፋል። ተራኪው ውሎና አዳሩን የአማቹ ሰፈር ከሆነው ከእሪበከንቱ ሲያደርግ ከአክስቱ የወረሰው የወሪሳ ቤት ወና ይሆናል። ኋላ ላይ ቤቱ በጭፍን እየተጎበኘ እንደሆነ እናውቃለን። ጭፍን የምሥራቁ ዓለም ሀገራት ተምሳሌት ነች። ከቻይና፣ ከጃፓን፣ ከህንድ፣ እና ከኮሪያ አንዱን መምረጥ ይቻላል። የቻይና ኮከብ ሊብራ ነው።
በወናው ቤት ውስጥ ተዳብሎ መኖር የሚጀምር ሌላም አስር ዓመት ያልሞላው የእሪበከንቱ ልጅ አለ። ይህ ልጅ ድመት በሸምቀቆ አድርጎ በሰንደቅ መስቀያ ሲሰቅል የኢትዮጵያን የህዝብ መዝሙር ይዘምራል። ይህ ልጅ ማንን ይወክላል? ማለፊያ የሆነ ህልም ፈቺ ያስብበት። የወና ቤቱ፣ የጭፍንና የሰይጣን ግልገል የሆነው ልጅ ህልማዊ ትንታኔ ብዙ ትንቢታዊ ድምፆች አሉበት። የድመት ገዳዩ ልጅ ዓላማ አንበርብርን ለመግደል ነው። ይኸ ነገር በአጠቃላይ የፀረአይሁድን በተለይ ግን የኢራንና የእስራኤልን ባላንጣዊ ጠላትነት ይወክላል። ልጁ በተለይ የሚወክለው ኦሳማ ቢን ላደንን ነው። እርሱ የሺትርገጥን ልጅ ለመግደል ሙከራ አድርጎ ሸሽቷል፤ በመጨረሻም በወሪሳ ሰፈር በተራኪው ቤት ተሸሽጓል።
የስምንት ዓመቱ የመጣባቸው ልጅ የሺ-ትርገጥን የመጨረሻ ልጅ በገመድ ሸምቅቆ ለመግደል ሙከራ አደረገ። ከዚያ በኋላ ከእሪበከንቱ የወንዝ ጉራንጉር ውስጥ ሸፈተ። በመቀጠል ወሪሳ ከሚገኘው ከተራኪው ቤት ውስጥ ተሸሸገ። አንበርብር እያሳደዱት ነው። የአሜሪካን የ “ናይን ኢለቨን” (9/11) ሽብር ያደራጀ ነው የሚባለው ኦሳማ ቢን ላደን በመጨረሻ ተሸሽጐ የተገኘው የአሜሪካ ተባባሪ ከተባለች አገር ጉያ ውስጥ ነው።
ሺ-ትርገጥ ከተራኪው አርግዣለሁ የምትለው ልጅ የመጣባቸውን የመሰለ ሆኖ እንዲወለድ ትመኛለች። ከዚያም ያለፈ ጥረት ታደርጋለች። ሐሳቧ የመጣባቸውን ልጅ ከበራፍ ተቀምጣ እሱ ሲያልፍና ሲያገድም ማየት ነው። እርጉዝ ሴት ደጋግማ ያየችውን ሰው የመሰለ ትወልዳለች ከሚል እምነት ተነስታ ይመስላል። የሷ ታሪክ ከምን እንደደረሰ ሳናውቅ ነው የ“ወሪሳ” ትረካ የሚያበቃው።
አሜሪካ የኦሳማ ቢን ላደን ነገር ሲያንገበግባት ቆየ። በርሱ ዳፋ ኢራቅ ተደበደበች። ወረራው ወደሌላም አገር ተዛመተ። ይህ እንግዲህ በጆርጅ ደብሊዉ ቡሽ ዘመን ነው። አሜሪካ በቀጣይ ያገኘችው መሪ ባራክ ሁሴን ኦባማ ሆነ። ይህ ሰው ቢያንስ በስሙ ከኦሳማ ቢን ላደን ጋር አንዳች መመሳሰል  አለው። አሜሪካ እንደ ሺ-ትርገጥ የልጇን ገዳይ የመሰለ መውለድ ተመኝታ ነበርን የሚያስብል ግርምታ ይጭራል።
ኮከብን በተመለከተ ጥቂት ቃላትን እንጨምር። የሺ-ትርገጥ ኮከብ ካንሰር ወይም ሸርጣን ውሀ ነው። የጭፍን ኮከብ ሊብራ ነው። ከውጭ ስትታይ ወንዳወንድ የምትመስል ነች። በቅርበት ግን ሞንሟና የሆነች ሴት ነች። ደራሲው ዓለማየሁ ገላጋይ፣ የልቦለዱ ተራኪ ገፀባህሪ፣ ክርስቺያን አንደርሰን፣ በአንደርሰን ተረት ውስጥ ያለው ህፃንና ችኩል የሆነው ሐዋርያው ጴጥሮስ ሁሉም ኤሪስ ናቸው።
አምበርብር የቶረስ፣ የስኮርፒዮ፣ የካፕሪኮርንና የአኳሪየስ ኮከቦች በጎጂ መልኩ ተሰባጥረው የሚታዩባቸው ገፀባህሪ ናቸው። ከዚህ ውስጥ የጨረቃ ኮከባቸው ካፕሪኮርን ነው። ይኸ ኮከብ የአይሁድ ወላጆች ኮከብ ነው ይባላል፤ በጨረቃና  በወላጅነት ውስጥ።
የግዙፎቹ የሺ-ትርገጥ ኮከብና የአሜሪካ ኮከብ ካንሰር ነው። የአሜሪካ ሙሉ ኮከብ ስብጥሩ በጥሩ ሁኔታ የተቀመረና የታሰበበት ቢሆንም አንድ ወሳኝ ጉድለት አለበት። አሜሪካ ውስጥ ያሉ እስቴቶች ኮከብም ይታወቃል። የትኞቹም ግዛቶች ግን የኤሪስ ኮከብ የላቸውም። በዚህ ሳቢያ አሜሪካ በጦርነቱ ዘርፍ የኤሪስን ጀግንነት አልታደለችም። በየወቅቱ በገጠመቻቸው ጦርነቶች እንደ ኤሪሶቹ እንግሊዞችና  ጀርመኖች የሚያኮራ ጀግንነት አሳይታ አታውቅም። ሀገሪቱ ውስጥ ኤሪስ ግዛቶች ስለሌሉ አሜሪካ የኤሪስ ኮከብ ላላቸው ሰዎች ብዙም አትመችም ይባላል። ይህ ግን ትንሽ የተጋነነ ነው። ለብዙ ኤሪሶች ገነት የሆነችባቸው ጊዜያቶች ብዙ ናቸው። እንዲያም ሆኖ ግን ለኤሪስ ግለሰቦች አስጨናቂ የምትሆንበት ጊዜ አለ። ከውሀ ኮከብዋ ጋር ያለው ሰፊ እንክብካቤዋ እሳቶቹን ኤሪሶች ቀዝቀዝ ያደርጋቸዋል። ችግሩ ከዚህ ብቻ የሚመነጭ ነው።
ካንሰርዋ ሺ-ትርገጥ በራስዋ ጥሩ እናትና ወላጅ ነች። ኤሪሱ ተራኪ ግን ይፈራታል። አፍና የምትገድለው ይመስለዋል። እሳት ውሀን የሚፈራውን ያህል ሲያያት ይርበደበዳል፤ ፍርሀቱ ውስጥ ግን ማሾፍም አለበት። የኤሪሱ ተራኪ ኮከብ የገጠመው ከሊብራዋ ጭፍን ጋር ነው። ኤሪስና ሊብራ ዋልታዊ ኮከቦች ናቸው። በተለይ በተቃራኒ ፆታዎች መካከል ሲሆን ሁለቱ ኮከቦች አብዝተው ይሳሳባሉ። ነገሩ ሁለት ማግኔቶች በተቃራኒ ጎናቸው ሲጠጋጉ እንደሚሳሳቡትና እንደሚሳሳሙት ዓይነት ነው። ሊብራዋ ጭፍን የኤሪሱ ተራኪ ተቆርቋሪ ነች። ከአደጋ ልትከላከለውም ትተጋለች። አልሆንለት ይላል እንጂ እርሱም ከእቅፏ ባይወጣ ይመርጥ ነበር።
የወሪሳ ሰፈር የአኳሪየሳዊት ኢትዮጵያ ተምሳሌት ነች። ሊነጋ ሲል በጣም ይጨላልማል እንደሚባለው ክፉ ዛር ለቋት ሊሔድ ሲቃረብ የእብደቷ መጠን ከፍተኛውን ደረጃ ይደርሳል።  የዚህ ውክልናም ወሪሳ ነች። ወሪሳ ወደ ሞት እንጂ ወደ ህይወት የምትሄድ አትመስልም። ነገር ግን የተስፋ ጭላንጭል አለ። ፀሐይ ትወጣለች። የኢትዮጵያ ኮከብም በቅርቡ ሙሉ በሙሉ ይወጣል። ከዚያ በኋላ ኢትዮጵያ ደጅ እያደረች ኮከብ አትቆጥርም። የእንጀራ እናትዋንም በወላጅ እናትዋ ትተካለች። ወሪሳንም እሪበከንቱንም አትሆንም። ምሥራቅም ምዕራብም አትልም፤ ራስዋን ትችላለች፤ ራስዋን ትሆናለች።
በወሪሳ አስራሁለቱም ኮከቦች መጥፎና ደካማ ጎናቸውን አፍርጠውና ገልጠው የዛር ድቤአቸውን ይደልቁባታል። የወሪሳ መንደር ሰዎች በኤሪሳዊ ድፍረትና ጭካኔ ይተራረዳሉ፤በቶረሳዊ ስግብግብነት ይቀማማሉ፤ በጄሚናዊ መንታ ምላስ ታሪካቸውን ይከታትፋሉ፤ በካንሰራዊ ጥፍር ይነጣጠቃሉ፤ በሊዮአዊ ማን አለብኝነት ያጓራሉ፤ በቪርጎአዊ ንዝንዝ ይጠቃጠቃሉ፤ በሊብራዊ ስንፍና ቀን ከሌት ያንኳርፋሉ፤ በስኮርፒአዊ በቀል በውድቅት ሌሊት ይገዳደላሉ፤ በሳጁታሪየሳዊ ልቅ አንደበት ይዘራጠጣሉ፤ በካፕሪኮርናዊ ቅዝቃዜ ይጠላለፋሉ፤ በአኳሪየሳዊ የቀውስ ዛር ልብሳቸውን ጥለው ያብዳሉ፤ በፓይሰሳዊ ቅዥት ውዥንብር ይፈጥራሉ። ሁሉም አብደዋል። የበረከትን ዝናብ ይናፍቃሉ። ሁሉም ታውረዋል። የበረከትን ጮራ ይሻሉ። ሁሉም እየጓጎሩ ነው። ከቅዠታቸውና ከአስፈሪ ህልማቸው ካልባነኑ አይድኑም።
አንድ ሀገር ልጅ ያላትን ሺ-ትርገጥን ያገባው ተራኪ የእንጀራ ልጆቹ ቀላቢ ይሆናል። ኋላ ላይ ሙሉ ደሞዙን ለሚስቱ ያስረክባል። ለራሱ የአውቶብስ መሳፈሪያ የሚሆነው አንድ ብር እንኳን ይከለከላል። ይኸ የዐባይ ወንዝ ተምሳሌት ነው።
ኢትዮጵያ የራሷንም ድርሻ እንኳን ስትከለከል ቆይታለች። የሺ-ትርገጥ ልጆች ከዐባይ ተፋሰስ አገሮች ውስጥ በተለይ የግብፅ አገር ህዝቦች ተምሳሌቶች ናቸው። አሁን ጥያቄው የአማርኛ አስተማሪ ነኝ የሚለው ተራኪ ሙሉ ደሞዙን እየተቀማ ለራሱ አንድ ብር እንኳን እየተከለከለ እስከመች ይቆያል ነው? ተራኪው በምግብም እየተበደለ ይራባል። አንድ ሁለቴ ጭፍን ሰርቃ ካገኘችው ስትጋብዘው እናያለን። ተራኪው ለነፃነቱ እየቃተተ ነው። ኢትዮጵያ የዐባይን፣ ተራኪው ደግሞ የደሞዙን ነፃነት ይሻሉ። ልቦለዱ በብዙ ዓለማቀፋዊ ትእምርቶች የተሞላ ነው፤ከላይ የዘረዘርኩት ጥቂቱን ብቻ ለቅምሻ ነው።  
ማጠቃለያ
የዓለማየሁ ገላጋይ ወሪሳ ለየት ያለ ድርሰት ነው። የልቦለዱ ፋይዳ ከመዝናኛ ግብአትነት አለፍ ይላል። ልቦለዱ ህልም ነው። ህልሙ ውስጥ ህመም አለበት። ህመሙ የኅብረተሰብ ህመም ነው። ህልሙ መፈታት፣ ህመሙ ደግሞ መዳን አለበት።
“ሀገሬ ኢትዮጵያ ሆይ! እስኪ ህልምሽን ንገሪን” ለምንል ዜጎችዋ፣ ጦቢያ ልክ የዛሬ 50 ዓመት ህልሟን በፍቅር እስከ መቃብር ነግራናለች፤ ዛሬ ደግሞ በወሪሳ። ያኔ በሊብራው ሐዲስ ዓለማየሁ፤ ዛሬ በኤሪሱ ዓለማየሁ ገላጋይ። ህልሟን መናገር የርሷ፣ ህልሟን መፍታት ደግሞ የኛ ድርሻ ነው። ያለፈውን ፈለግና መንገዳችንን ብቻ ሳይሆን የመፃኢውን ዒላማና ዓላማችንን ጭምር በሀገራችን ህልም ውስጥ እናነበዋለን፡፡  
ልቦለድን እንደ ህልም ስንፈታ የምናቀርበው ትርጓሜ ፈርጀ ብዙ ነው መሆን ያለበት። አንዱ ትእምርታዊ ገፀባህሪ ወይም የትረካ አንጓ ከአንድ በላይ ትርጓሜዎች ይኖሩታል። የዚህ ዓይነቱን የሥነኂስ ስልት በቅጡ ለመረዳት ብዙም ርቀን መሔድ አያስፈልገንም። እዚሁ ሀገራችን ለዘመናት የሰፈነ የአንድምታ ትርጓሜ የሚባል ባህልና ጥበብ አለን።
ይህን ሒሳዊ ብእሮግ ከአንድምታ ትርጓሜ ጠቅሼ ልቋጭ። በመጽሐፍ ቅዱስ በዘፀአት መጽሐፍ በምእራፍ ሁለት፣ በቁጥር አምስት ላይ እንዲህ የሚል ዓረፍተ ነገር አለ። “ወወረደት ወለተ ፈርዖን ከመ ትትሐፀብ በውስተ ተከዚ” [የፈርዖን ልጅ ገላዋን ትታጠብ ዘንድ ወደ ዐባይ ወንዝ ወረደች።] የሀገራችን ሊቃውንት ለዚህ ዐረፍተ ነገር ያስቀመጡት የአንድምታ ትርጓሜ ቀጥሎ ያለውን ይመስላል።
ተርሙት የምትባል የፈርዖን ልጅ ልትታጠብ ወደ ፈሳሹ ወረደች፤ ስለ ምን ቢሉ በፈሳሹ ዳር እንደ መዋት ያለ ነበር፤ ኮብሽ የሚባል ደዌ ነበረባትና ለመጠመቅ፤ አንድም ነጋዴ ወዳጅ ነበራትና ያንን ለመቀበል፤ አንድም አዞ ጉማሬ ታመልክ ነበረችና ስለዚህ፤አንድም በጎርጎራ ሳለ ያጤ መለክ ሰገድ ልጆች ውሀ ዋና ይማሩ እንደነበረ ውሀ ዋና ልትማር ነው።
የፈርዖኑ ልጅ የተርሙት ወደ ዐባይ ወንዝ መውረድ አራት አንድምታዊ ትርጓሜዎች ተሰጥተውታል፤ አንድም ለህክምና ጠበል፤ አንድም ለድብቅ ፍቅር፤ አንድም ለጉማሬ አምልኮ፤ አንድም ለውሀ ዋና ትምህርት በሚል። አንድምታዊ ትርጓሜ ጥልቅ ንባብ ነው። እንደ ቁጥር ስሌት ሁለት ሲደመር ሦስት አምስት ነው ብሎ አያቆምም፤ ከዚያ ብዙ ያልፋል።
 ይህን ድንቅ የሆነ የጥልቅ ንባብ ባህላችንን ወደ ልቦለዶቻችንም ልናመጣው ይገባናል ብዬ አስባለሁ። የወሪሳ ትንታኔ ብዙ የሚሔድ ነው፤ ላሁኑ ግን በዚሁ ይብቃኝ።
 [ድኅረ-ማስታወሻ፤ ፍካሬ ኢትዮጵያ በተባለው መጽሐፌ ውስጥ የፍቅር እስከ መቃብር የአንድምታ ትርጓሜ ይገኛል። የፈጠራ ድርሰትን እንደ ህልም የማየትን የሒስ ስልት፣ ሚካኤል ሺፈራው በምስጢረኛው ባለቅኔ መጽሐፉ ተግብሮታል። ስለእርሱ የሒስ ስልት በሌላ ጽሑፍ ለማቅረብ እቅዱ አለኝ።]

Monday, 31 August 2015 09:11

የግጥም ጥግ

አረማሞ
ተደባልቆ በቃይ
ሲናር አረማም
ሲዘራ ካልዘሩ
ምርጥ ዘር አክሞ
ገለባ ነው ትርፉ
ቀን ቆጥሮ ለከርሞ፡፡
ሙግት
ያኮረፈ ሌሊት
…መንጋቱን የረሳ
ውስጤ እያደመጠ
…የነፍሴን ጠባሳ
እርምጃ ውልክፍክፍ
…ጉዞውም የአንካሳ
የጨለማ ሙግት
…የንጋት ወቀሳ፡፡
ጀንበሩ ወልደዮሐንስ
(ከኒዮርክ ቡፋሎ)
* * *
“አንተ” - ማለት!...
“አንተ” ማለት፡-
ብዙ ነህ!
ብዙ - ብዙ! … የብዙ - ብዙ!
“አንተ” ማለት ….
አገር ነህ፣
አገር ከነጉዝጓዙ፡፡…
ያገር ጉዝጓዙ…
አቤትና አቤት … አቤት! ብዛቱ፡…
ጂባው፣ አጐዛው - ጀንዴው - ቁርበቱ፡፡…
ተራራው - ሸለቆው - ዱሩ፣
እንኮይ - መስኩ፣
መብሰክሰኩ…፤
እሾህ አሜኬላው - ቆንጥሩ…
ባንድ ሌማት
እሬት!
ምሬት!
የአጋም ፍሬው --- ጣዝማ ማሩ፣
ደግሞም፡-
አድባር! አውጋር! … ያለ መጣፍ፣
አማኝ - እምነት
በመጣፍም
ያለ መጣፍ፡፡…
መቼም - ሰው “አገር ነውና”
አገርም “ሰብዓ ምርቱ”
ታሪክ - ቋንቋ - ባህል - ቀኖናውና
- ትውፊቱ፣
እሱ ነው! የማንነትህ እትብቱ፡፡…
ከእኒህ - መነቀል…
ማለት፡-
ከሥር - መመንገል!
ካናት - መቃጠል!
ከእግር - መመንቀል!
ማለት ነው፣
አገር እንደ ሰው!!
ሰማህ!?
(ወንድዬ ዓሊ)

   መርዛማ የሃሞት ፈሳሾች በጉበታችን ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንደሚያስከትሉና የጉበት ሴሎችን ቀስ በቀስ ወደ ቲሹዎች በመቀየር ከጥቅም ውጪ ሊያደርጉት እንደሚችሉ ተጠቆመ፡፡
በሔድልበርና ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች የተደረገውና በቅርቡ ይፋ የሆነው አንድ ጥናት እንደሚያመለክተው፤ ሃሞት የጉበት ሴሎች ጋር እንዳይደርስ የሚከላከሉት አካላት ሲጠፉና መርዛማ የሃሞት ፈሳሾች የጉበት ሴሎች ጋር ደርሰው ጉዳት ሲያስከትሉ ጉበት Cirrhosis (ኪሮሲስ) ተብሎ ለሚጠራው የጉበት በሽታ ይጋለጣል፡፡ ይህ በሽታ ደግሞ ጉበታችን ተግባሩን በአግባቡ እንዳያከናውን እንቅፋት በመሆንና ሴሎቹን ወደ ቲሹዎች በመቀየር ጉበትን ሙሉ በሙሉ ከጥቅም ውጪ የሚያደርግ መሆኑን ጥናቱ አመልክቷል፡፡
ለዚህ ችግር መነሻ ምክንያቶች ሊሆኑ ይችላሉ ተብሎ በጥናቱ ላይ ከተገለፁት መካከልም የጉበት ቫይረሶች፣ ከፍተኛ የአልኮል መጠጥ፣ መድሃኒቶችና ልዩ ልዩ ኬሚካሎች እንደሚገኙበት ተጠቁሟል፡፡

ቴትራሳይክሊን፣ የደም ብዛትና የካንሰር ህመም መድሃኒቶች የጉበት ስብ በሽታን ሊያስከትሉ ይችላሉ

  ጉበት መርዛማ ንጥረ ነገሮች በደም አማካኝነት ወደተለያዩ የሰውነታችን ክፍሎች ውስጥ ዘልቀው ገብተው ጤናችን አደጋ ላይ እንዳይወድቅ ብርቱ ተጋድሎ የሚያደርግ የሰውነታችን ክፍል ነው፡፡ በምንመገባቸው ምግቦችና መጠጦች እንዲሁም ለተለያዩ በሽታዎች ማከሚያነት በምንወስዳቸው መድሃኒቶች ውስጥ የሚገኙና ለሰውነታችን አላስፈላጊ የሆኑ ንጥረ ነገሮች ሁሉ በጉበት አማካኝነት እየተመረጡ እንዲወገዱ ይደረጋል፡፡ ቀይ የደም ሴሎቻችን የአገልግሎት ዘመናቸውን ሲያጠናቅቁ የሚወገዱትም በዚሁ በጉበታችን አማካኝነት ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ጉበታችን ፋቲ አሲድ፣ ፕሮቲን፣ ጉሉኮስንና በሽታን ለመከላከል የሚያስችሉ ንጥረ ነገሮችን እያመረተ ለሰውነታችን ክፍሎች እንደዳረሱ ያደርጋል፡፡ የዚህ የሰውነታችን ዘርፈ ብዙ አገልግሎት ሰጪ የሆነው የሰውነታችን ክፍል በህመም መጠቃት በሰውነታችን ሥርዓተ ዑደት ላይ ከፍተኛ ተፅእኖን ያሳድራል፡፡
ጉበትን በእጅጉ በመጉዳት ከሚታወቁ ነገሮች መካከል አልኮል ዋንኛው ነው፡፡ በአልኮል ሳቢያ የሚከሰተው የጉበት ስብ በሽታ በርካቶችን ለሞት እየዳረገ እንደሚገኝ የህክምና ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡ በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የውስጥ ደዌ ሃኪም የሆኑት ዶ/ር አብርሀም ባየልኝ እንደሚናገሩት አልኮል አመጣሽ በሆነው የጉበት ስብ በሽታ የተጠቁ ሰዎች አምስት አመት በህይወት የመቆየታቸው እድል 50በመቶ % ብቻ ነው፡፡ በሽታው የጉበትን የመሥራት አቅም በፍጥነት የሚያዳክምና ከአገልግሎት ውጪ የሚያደርግ በመሆኑ በበሽታው የተያዙ ሰዎች ለህልፈት የመዳረጋቸው እድል ከፍተኛ ነው፡፡ በሽታው ምንም አይነት ምልክቶችን ሳያሳይ ሊቆይ እንደሚችል የሚገልፁት ሃኪሙ፤ ከ75% በላይ የሚሆኑት የጉበት ስብ ህሙማን በበሽታው የመያዛቸውን ምልክት የሚያሳዩት ጉበታቸው የመጨረሻ ደጃ ላይ ሲደርስና ውሃ መያዝ ሲያቅተው ነው ይላሉ፡፡ የበሽታው ስርጭት በአገራችን እየጨመረ መምጣቱን የጠቆሙት ዶ/ር አብርሃም፤ በተለይ እድሜያቸው ከአርባ ዓመት በላይ የሆኑና አልኮል አዘውታሪ ሰዎች በበሽታው የመያዝ እድላቸው ከፍተኛ እንደሆነና ከመጠን ያለፈ ውፍረት ያለባቸው ህፃናትም ለበሽታው ሊጋለጡ እንደሚችሉ ተናግረዋል፡፡
የጉበት ጤና በማቃወስ ከሚታወቁት ነገሮች መካከል አንዱና ዋንኛው በሆነው ስብ የተጠቃ ጉበት ለጉበት ስብ በሽታ የሚጋለጥ ሲሆን ይህም በሁለት ምክንያቶች የሚከሰትና ጉበትን ወደ ቃጫነት በመለወጥ ከጥቅም ውጪ የሚያደርግ በሽታ ነው፡፡ የጉበት ስብ በሽታ ከሚከሰትባቸው ሁለት ምክንያቶች መካከል አንደኛው የአልኮል መጠጥ ሲሆን ሌላው ከአልኮል ውጪ በሆኑ ሌሎች ምክንያቶች ማለትም ለተለያዩ በሽታዎች ማከሚያነት የምንወስዳቸው መድሃኒቶች እንዲሁም የስኳር በሽታ፣ ውፍረት፣ ጉሉኮስ የማከማቸት ችግርና ኮፐርና ዚንክ የተባሉ ማእድናትን በሰውነት ውስጥ ማከማቸት… ለጉበት ስብ በሽታ መነሻ ምክንያት ሆነው ይጠቀሳሉ፡፡ የአልኮል መጠጦች በጉበት ስብ በሽታ ለመጠቃት 40በመቶ ድርሻ እንዳላቸው ሃኪሙ ገልፀዋል፡፡
የአልኮል መጠጦች ለጉበት ስብ በሽታ መነሻ የሚሆኑባቸውን መንገዶች ሃኪሙ ሲያብራሩ “የአልኮል መጠጦችን በምንጠጣበት ጊዜ በአልኮሉ ውስጥ የሚገኙና ለሰውነታችን ጠቃሚ የሆኑ ነገሮች ጥቅም ላይ ከዋሉ በኋላ ቅሪቱ ንጥረ ነገር በጉበታችን ውስጥ ያልፋል፡፡ በዚህ ጊዜም የጉበታችን ሴሎች ጉዳት ይደርስባቸዋል፡፡ ይህ ደግሞ ጉበታችን በአግባቡ ሥራውን እንዳያከናውን ያደርገዋል፡፡ ጉበታችን ስራውን በአግባቡ ማከናወን ሲሳነው ወደ ሰውነታችን የገቡትና በጉበታችን አማካኝነት መጣራት የሚገባቸው ንጥረ ነገሮች በሰውነታችን ውስጥ ዝም ብለው ይከማቻሉ፡፡ በዚህ ጊዜም ጉበታችን ከመጠን በላይ በሆኑ ስቦች እንዲጨናነቅ ያደርጋል፡፡ ይህ ሁኔታ ደግሞ የጉበታችንን ሴሎች ወደ ቃጫነት በመቀየር ጉበታችን ፋትን ማመንጨትና መጠቀም እንዳይችል እንዲሁም ውሃ መያዝም እንዲያቅተው ያደርገዋል፡፡ ጉበት ሲታመም ፈሳሽ የመቋጠር አቅሙን ያጣል፡፡ ይህም ፈሳሽ በሆዳችን ውስጥ እንዲጠራቀም በማድረግ ሆዳችንን ያሳብጠዋል፡፡ መጣራት ሲኖርባቸው ሳይጣሩ ቀርተው በሰውነታችን ውስጥ የተጠራቀሙት መርዛማ ንጥረ ነገሮችም በደም አማካኝነት ወደ ጭንቅላታችን ውስጥ ገብተው ሩሃችን ያስቱናል፡፡ በተጨማሪም ፕሮቲን ጉሉኮስ፣ ፋትና በሽታን የሚከላከሉ ንጥረ ነገሮች በሰውነታችን ውስጥ መመረታቸው፣ መከማቸታቸውና በጥቅም ላይ መዋላቸው ያቆማል ብለዋል፡፡
ከአልኮል ውጭ የጉበት ስብ በሽታን ከሚያስከትሉ ነገሮች መካከል የሚጠቀሰው ለተለያዩ ህመሞች የምንወስዳቸው የተለያዩ ይዘቶች ያሏቸው መድሃኒቶች ናቸው፡፡ በተለይ ቴትራሳይክሊን፣ የደም ብዛት መድሃኒቶች፣ ለካንሰር ህሙማን የሚታዘዙ መድሃኒቶችና ሆርሞኖች በዋናነት እንደሚጠቀሱም ዶክተር አብርሃም ገልፀዋል፡፡ አብዛኛውን ጊዜ ከአቅም በላይ ካልሆነ በስተቀር መድሃኒቶች ተደራርበው እንዳይወሰዱ ለማድረግ የሚመከረው በመድሃኒቶች ሳቢያ የሚከሰቱ የጐንዮሽ ጉዳቶችን ለመቀነስ በማሰብ እንደሆነም ጠቁመዋል፡፡
የጉበት ስብ በሽታ ምንም አይነት ምልክቶችን ሳያሳይ የመጨረሻ ደረጃ ላይ ሊደርስ እንደሚችል የሚናገሩት ዶክተሩ፤ በአብዛኛው የችግሩ መኖር የሚታወቀው ጉበቱ ከጥቅም ውጪ ከሆነና ለመዳን እጅግ አስቸጋሪ ከሚሆንበት ደረጃ ላይ ከደረሰ በኋላ እንደሆነም አስረድተዋል፡፡
አንዳንድ የጉበት ስብ በሽታ ህሙማን የእግር ማበጥ፣ የአይን ቢጫ መሆን፣ በቀኝ ጐን በኩል የህመም ስሜቶች መኖር ሊያጋጥማቸው እንደሚችልም ገልፀዋል፡፡ በሽታው ስር ያልሰደደ ከሆነና ጉበቱ ሙሉ በመሉ ከጥቅም ውጪ ከመሆኑ በፊት ከተደረሰበት በተለያዩ ቫይታሚኖችና መድሃኒቶች በሽታውን አክሞ ማዳን እንደሚቻል ጠቁመው ከጥቅም ውጪ ለሆነ ጉበት የሚሰጥ ህክምና በአገራችን ደረጃ አለመኖሩን ተናግረዋል፡፡
አልኮልን አዘውትሮ አለመጠጣት፣ መድሃኒቶችን አብዝቶ አለመጠቀም፣ በአመጋገብ ላይ ጥንቃቄ ማድረግና የአካል ብቃት እንቅስቃሴዎችን ማድረግ የጉበት ስብ በሽታን ለመከላከል እንደሚረዱ ዶክተር አብርሃም ገልፀዋል፡፡

     ከተቋቋመ ስድስት ዓመታትን ያስቆጠረውና ልዩ ልዩ የህክምና ምርመራ አገልግሎት በመስጠት የሚታወቀው ውዳሴ ዲያግኖስቲክስ ማዕከል፤ 500 ለሚሆኑና የመክፈል አቅም ለሌላቸው ህሙማን ነፃ የሲቲስካንና የኤምአርአይ ምርመራ አገልግሎት ሊሰጥ ነው፡፡ማዕከሉ “ጳጉሜን ለጤና” በሚል መርህ በየአመቱ ነፃ የምርመራ አገልግሎት የሚሰጥ ሲሆን ዘንድሮም ከመንግሥት የህክምና ተቋማት ለሚመጡና አገልግሎቱን በክፍያ ለማግኘት አቅም ለሌላቸው ህሙማን ነፃ የሲቲስካንና የMRI ምርመራ እንደሚያደርግ የማዕከሉ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ዳዊት ኃይሉ ከትናንት በስቲያ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተናግረዋል፡፡ ከመንግሥት የጤና ተቋማት የሲቲስካንና የኤምአርአይ ምርመራዎች እንደሚያስፈልጋቸው በሃኪም የተፃፈላቸው ህሙማን ከነሐሴ 22 ጀምሮ በስልክ ቁጥሮች 0111574343 ወይም በሞባይል ቁጥር 0940040404 ደውለው በመመዝገብ፣ ወረፋ መያዝና የነፃ ምርመራው ተጠቃሚ መሆን እንደሚችሉ ዳይሬክተሩ ገልፀዋል፡፡
ማዕከሉ ከተቋቋመ ጊዜ ጀምሮ በየአመቱ በጳጉሜ ተመሳሳይ የነፃ ምርመራ አገልግሎቶችን እየሰጠ ሲሆን ባለፈው ዓመት ለ500 ሰዎች ነፃ የሲቲስካንና ኤምአር አይ ምርመራ አገልግሎት ለመስጠት አቅዶ፣ ለ820 ሰዎች ነፃ አገልግሎቱን እንደሰጠ ዳይሬክተሩ ተናግረዋል፡፡ የሲቲስካንና የኤምአርአይ ምርመራ አገልግሎት ለማግኘት ከአንድ ሺህ ብር እስከ ሶስት ሺህ ብር ክፍያን እንደሚጠይቅ ይታወቃል፡፡

ባለፈው ሐምሌ 18 ቀን 2007 ዓ.ም በወጣው  የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ዕትም ላይ ዮሐንስ የተባሉ ፀሐፊ፣ በአሜሪካ መንግስት ድጋፍ የሚደረግለት ፓወር አፍሪካ ኢንሼቲቭ አካል በሆነው በኩርቤቲ የሚገነባው የጂኦተርማል ኃይል ማመንጫን አስመልክተው የፕሮጀክቱን አክሳሪነት፤ “የኦባማ ስጦታ ለኢትዮጵያ፡ የ 40 ቢሊዮን ብር ኪሳራ!!” በሚል ርዕስ ባሰፈሩት አስተያየት ለመግለጽ ሞክረዋል። በርግጥ አቶ ዮሐንስ ለኢትዮጵያና ለአፍሪካ ኪሳራ ብለው የመደቡት ገንዘብ በየትኛው ስሌት እንዳስቀመጡት የሚያሳይ አሳማኝ መረጃ ባያቀርቡም፣ ስለ ፕሮጀክቱ ያላቸውን ስጋት በደፈናው ያስቀመጡበትን ሁኔታ ለመገንዘብ አዳጋች አይደለም፡፡ ነገር ግን ፀሐፊው መለስ ብለው የፓወር አፍሪካ ኢንሼቲቭ አላማን ለመረዳት ቢሞክሩ መልካም ነበረ በማለት የግል አስተያየቴን ለመሰንዘር እወዳለሁ።

     በፕሬዚደንት ኦባማ ሃሣብ አመንጪነት የተቋቋመው ፓወር አፍሪካ የተሰኘው ኢንሼቲቭ፤ አፍሪካ ለእድገቷ የሚያስፈልጋትን የኃይል ፍላጎት ለማሟላት እያደረገች ያለችውን ጥረት ለመደገፍ ያለመ ፕሮጀክት እንደሆነ መረጃዎች ያመላክታሉ። ኢንሼቲቩ ኢትዮጵያን ጨምሮ በስድስት የአፍሪካ አገራት፣ 20 ሚሊዮን ነዋሪዎችን የኤሌክትሪክ ኃይል ተጠቃሚ ለማድረግ የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በመንደፍ በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል።
 ኢትዮጵያ የጀመረችውን የእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ከግብ ለማድረስ በሁሉም ዘርፍ የሚደረገው ልማት ወሳኝነት አለው። በተለይ የኃይል ልማቱ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ትኩረት የሚያሻው በመሆኑ የሃገሪቱን የኃይል ፍላጎት በበቂ ሁኔታ ለመመለስ የ25 ዓመት የአረንጓዴ ልማት ስትራቴጂ በመንደፍ፣ የኃይል አቅርቦቱን አሁን ካለው 4000 ሜጋ ዋት ወደ 37000 ሜጋ ዋት ለማሳደግ፣ የግል አልሚዎችንም በማሳተፍ ጭምር ዓላማውን ከግብ ለማድረስ ዘርፈ ብዙ ስራዎች በመከናወን ላይ ይገኛሉ። ከነዚህም ፕሮጀክቶች በዋነኝነት የትውልድ አሻራ ያረፈበት ታላቁ የህዳሴ ግድብ ግንባታ ተጠቃሽ ሲሆን ዮሐንስ ባሰፈሩት ሃሳብ፣ “የፓወር አፍሪካ የገንዘብ ርዳታ ለምን ለህዳሴው ግድብ አይሆንም” ሲሉ ገልጸዋል፤ ነገር ግን  የህዳሴ ግድብን በተመለከተ እኛው በኛው ለኛው የምንሰራው ግድባችን መሆኑን ፀሐፊው አልሰሙ ይሆን? የውጪ እርዳታ ለማግኘት ጥረት ተደርጎ ባለመሳካቱ አልነበረም እንዴ እኛው ራሳችን ለመስራት ቃል የገባነው፡፡
እስካሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታ በሃገራችን 94% ያህሉ የኤሌክትሪክ ኃይል የሚመነጨው ከሃይድሮ ፓወር መሆኑ ግልፅ ነው። ይህ ማለት ግን ያለን የኃይል አማራጭ በግድብ ግንባታ ላይ የተመሰረተ ብቻ ነው ማለት አለመሆኑን ፀሐፊው ሊረዱት ይገባል ባይ ነኝ። ለኢኮኖሚው ቀጣይ እድገት አስተማማኝና ዘላቂ የኃይል አቅርቦትን ለማሟላት ከተለያዩ የኃይል ምንጮች የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫዎችን መገንባት ግድ የሚለን ወቅት ላይ ደርሰናል። ለዚህም ሲባል ከንፋስ ኃይል 800 ሜጋ ዋት ኃይል ለማመንጨት በዕቅድ የተያዘ ሲሆን አሽንጎዳ 120 ሜጋ ዋት፣ አዳማ I የነፋስ ኃይል ማመንጫ 51 ሜጋ ዋት ኃይል ያመነጫል።  አዳማ II በቅርቡ 153 ሜጋ ዋት ኃይል ማመንጨት የጀመረ መሆኑን ሰምተናል አይተናልም። በአፍሪካ ትልቁ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ጣቢያ በሚያሰኘው ደረጃ ላይ መገኘቱ ኢትዮጵያ በታዳሽ ኢነርጂ ልማትን በማፋጠን ላይ እንደምትገኝ ዋቢ ሆኖ ሊቆጠር ይችላል። ከእነዚህ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ጣቢያዎች ባጠቃላይ በአሁኑ ወቅት 324 ሜጋ ዋት ኃይል ለማመንጨት ያስቻለ አቅምንም ፈጥረዋል።
እንደ ንፋስ ኃይልና ጂኦተርማል ያሉት የኃይል ምንጭ አማራጮች  የሃይድሮ ፓወርን በመደገፍ የዝናብ መጠን አነስተኛ በሚሆንባቸው ወቅቶች  ለክፉ ቀን ደራሾች መሆናቸው የሚያስማማን ይመስለኛል።       
ሁሉንም የታዳሽ ኃይል ምንጮች የማልማቱ ተግባር ከሚፈጥረው ሰፊ አማራጭ በተጨማሪ በተወሰኑ የኃይል ምንጮች ላይ የሚኖረውን ጥገኝነትንም ይቀንሳል። ኢትዮጵያ በስምጥ ሸለቆ አካባቢዎች ከፍተኛ የጂኦተርማል ኃይል የማመንጨት አቅም እንዳላት በየጊዜው የሚደረጉ ጥናቶች እያመላከቱ ነው።
ከዚህ የኃይል ምንጭ ብቻ ከ10‚000 ሜጋ ዋት በላይ ማመንጨት እንደሚቻል ታውቋል፡፡ በእስካሁኑ ሁኔታ ከጂኦተርማል ለመጠቀም የተቻለው ኃይል 7% ብቻ ነው። ይህም በዘርፉ ያለውን አቅም የመጠቀም ውስንነት እንዳለ ቢያሳይም በቅርቡ በአሜሪካ መንግስት ድጋፍ 1000 ሜጋ ዋት ኃይል ማመንጨት የሚያስችል ስምምነት ላይ ተደርሷል።
የጂኦተርማል ኢነርጂ ከአካባቢ ብክለት ነጻ የሆነ አስተማማኝ የታዳሽ ኢነርጂ ምንጭ ሲሆን ከቅሪተ አካል ኢነርጂ ምንጮች ከሚወጣው ወጪ 80% ያህል ቅናሽ እንደሚኖረውም ይነገራል።
 ከዚህ አንጻርም ለትራንስፖርትና ለማመንጫ ጣቢያዎች ጽዳት የሚወጣን ወጪ ከመቀነሱ ባሻገር ለዓለማችን ስጋት ከሆነው የግሪን ጋዝ ልቀትና የአካባቢ ብክለት ነጻ የሆነ ኃይል ለማምረት ያስችላል። በግንባታው የመጀመሪያ ወቅት ወጪው ከፍተኛ ቢሆንም በማመንጨት ሂደቱ በቀጥታ ለጥቅም መዋሉ ተመራጭና ርካሽ አማራጭ ያደርገዋል። እንግዲህ ዮሐንስ በአንድ አቅጣጫ ትኩረት ከሚያደርጉ ይልቅ የተለያዩ መረጃዎችን መመልከት ቢችሉ ፅሁፋቸውን በመረጃ የበለጸገ ለማድረግ በረዳቸው ነበር።
የጂኦተርማል ኢነርጂን ማልማት ለወደፊቱ ተመራጭና ተደራሽነቱም አስተማማኝ እንደሚሆን ተተንብይዋል።አገራት የወደፊቱን የኢነርጂ አማራጫቸውን በታዳሽ ኢነርጂ ላይ እንደሚያደርጉ የወቅቱ የዓለም አየር ንብረት ለውጥ እያስገደዳቸው እንደሆነ በግልፅ እየታየ ነው። በዓለማችን የጂኦተርማል ኢነርጂን በማልማት  በቀዳሚነት 24 አገራት ከዚህ የኃይል ምንጭ ተጠቃሚዎች ሆነዋል፡፡
በዓለም ዓቀፍ ደረጃ 12.8 ጌጋ ዋት አቅም ያለ ሲሆን ከዚህም ውስጥ 28 በመቶውን ማለትም 3‚548 ሜጋ ዋት ኃይል በማመንጨት አሜሪካ በመሪነት ደረጃ ላይ ትገኛለች፡፡ ፊሊፒንስ 1‚904 ሜጋ ዋት፣ ኢንዶኔዥያ 1‚222 ሜጋ ዋት በማመንጨት በሁለተኛና ሦስተኝነት ይከተላሉ፡፡ በቀጣዮቹ ዓመታትም የዘርፉ አቅም ከ14.5-17.6 ጌጋ ዋት እንደሚደርስ ይገመታል።