የኮበለሉ ጋዜጠኞች ወደ አገራቸው እንዲመለሱ ጥሪ አቅርበናል
ሥልጠናው ከምርጫ ጋር የሚያገናኘው ምንም ነገር የለም
የአቅም ግንባታ እንጂ የርዕዮተ ዓለም ማስረጫ አይደለም

ከነሐሴ አጋማሽ ጀምሮ ለዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እየተሰጠ ባለው ስልጠናና በአምስት የግል መጽሄቶችና በአንድ ጋዜጣ ላይ የተመሰረተውን ክስ ተከትሎ ከአገር በወጡት በርካታ ጋዜጠኞች ዙሪያ የአዲስ አድማስ  ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፤ የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ፅ/ቤት ሚኒስትር ዲኤታ አቶ እውነቱ ብላታን  ሰሞኑን በፅ/ቤታቸው አነጋግሯቸዋል፡፡

ለከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ተማሪዎች የተዘጋጀው ስልጠና ዓላማ ምንድን ነው?
የስልጠናው ዋና ዓላማ፣ አንደኛ በዩኒቨርሲቲዎች አካባቢ ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሂደት በተቀላጠፈ መልኩ ማስቀጠል ነው፡፡ ሁለተኛ ሃገሪቱ በምትከተለው የልማት ስትራቴጂ ዙሪያ እስካሁን የደረስንበት፣ እንዲሁም ከፊታችን የሚጠብቁን ተግዳሮቶችና ስራዎች ምን እንደሆኑ የጠራ ግንዛቤ ማስያዝ ነው፡፡ ሀገሪቱ ባለፉት 23 ዓመታት የተጓዘችባቸውን መንገዶች በተለይ ወጣቱ ትውልድ በደንብ እንዲያውቀውና የበኩሉን ሃገራዊ የዜግነት ግዴታውን እንዲወጣ ጭምር ከየት ተነሳን ወዴት እየሄድን ነው የሚለውን ለማስጨበጥ ነው፡፡ ሌላው ሃገሪቱ እየተከተለች ባለችው ልማታዊና ዲሞክራሲያዊ ስርአት ግንባታ ላይ ያሉ ክፍተቶች ምንድን ናቸው? እንዴትስ ይቀረፋሉ? የመልካም አስተዳደር ትግላችን ምን ያህል ተጉዟል? ምንስ ይቀረዋል? በዚህ የመልካም አስተዳደር ጉዞ ውስጥ ከወጣቱና ከከተማው ህዝብ ምን ይጠበቃል? በአጠቃላይ ሃገሪቱ ለተያያዘቻቸው የሰላም፣ የልማትና የዲሞክራሲ ስርአት ግንባታ ወጣቱ ሚናውን መጫወት በሚችል መልኩ ግንዛቤ ለመስጠት ተፈልጎ ነው ስልጠናው እየተሰጠ ያለው፡፡ ይሄ ስልጠና ዘንድሮ የተጀመረ አይደለም፤ በየጊዜው በየትምህርት ተቋማቱ ሲሰጥ የቆየ ነው፡፡ የዚያው ቀጣይ ፕሮግራም ነው፡፡
ሥልጠናው በዩኒቨርሲቲዎች ብቻ የሚያበቃ ሳይሆን ለመንግስት ሰራተኞችም የሚሰጥ ነው፡፡ በህዝባዊ አደረጃጀቶች ውይይቶች እየተካሄዱ፣መንግስት በ5 ዓመቱ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ አፈፃፀም ላይ የደረሰባቸው የእድገት ደረጃዎች የነበሩት ውጤታማ ተሞክሮዎች ምን ነበሩ? ከዚህ ምን ተምረን ለቀጣዩ እቅድ እንዴት እንሰራለን? የሚለውንና በአጠቃላይ ትልልቅ በሆኑ አገራዊ አጀንዳዎችና በህዳሴው ጉዞ ላይ  የሰፊውን ህዝብ  ተሣትፎ ለማጠናከር ታስቦ እየተካሄደ ያለ ስልጠና ነው፡፡ አሁን በዩኒቨርስቲዎች ለነባር ተማሪዎች ሁለተኛ ዙር ስልጠና እየተሰጠ ነው ያለው፡፡ ዩኒቨርሲቲ ማለት ይህቺን አገር የሚረከበው ወጣቱ ሃይል የሚገኝበት ነው፡፡ ይሄ በእውቀት የተካነው ወጣቱ ሃይል፣ ነገ ወደ ስራ ሲሰማራ የበኩሉን አስተዋጽኦ ማበርከት ይችል ዘንድ በአገሪቱ ነባራዊ ሁኔታ ላይ ግንዛቤ ለማስጨበጥ ተፈልጐ ነው ስልጠናው  የሚካሄደው፡፡ በዩኒቨርሲቲ ያለው የተማረ ሃይል ስለብዝሃነት፣ ስለመቻቻል፣ ስለመከባበር የጠራ ግንዛቤ እንዲኖረው ጭምር ነው ስልጠናው እየተሰጠ ያለው፡፡
ስልጠናው በተማሪዎቹ ፍቃደኝነት ሳይሆን በግዴታ ነው የሚካሄደው የሚሉ ቅሬታዎች ይሰማሉ፡፡  እውነት በግዴታ ነው ?
ስልጠናው ግዴታ አይደለም፡፡ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ወዶና ፈቅዶ የሚሳተፍበትና ግንዛቤ የሚያገኝበት ነው፡፡ ተማሪው በአጠቃላይ አገራዊ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች ላይ የሚወያይበት ስለሆነ በግዴታ ላይ የተመሠረተ ነው የሚያስብለው ነገር የለም፡፡ ስልጠናው በፍፁም በግዴታ ላይ የተመሰረተ አይደለም፡፡
ተማሪዎች በስልጠናው ተሳትፈው ሠርተፊኬት ካልተሰጣቸው ለትምህርት መመዝገብ እንደማይችሉ ተነግሯቸዋል ይባላል፡፡ ይሄ ውሸት ነው ማለት ነው?
የአንድ ወይም የሁለት ሣምንት የተለመዱ ስልጠናዎች ይሠጣሉ፡፡ ማንኛውም ስልጠና ሲካሄድ ለማንኛውም ሠልጣኝ ሠርተፊኬት ይሰጣል፡፡ ስልጠናው ምን ያህል ገብቶታል ወይም የተሳትፎ ብቃቱ ምን ያህል ነው የሚለውን ለመመዘን አይደለም፡፡ እንኳንስ ለ15 ቀን በተከታታይ ሰፊ ስልጠና ተሰጥቶ ይቅርና ለሁለትና ሦስት ቀናት ስልጠናም ሠርተፊኬት ይሰጣል፡፡ ተማሪዎችም በትላልቅ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ነው የተወያዩት፤ በሀገሪቱ ውስጥ ስላለው መቻቻል፣ ህገ መንግስቱንና ህገ መንግስታዊ ስርአትን ተከትሎ መስራት ምን አንድምታ እንዳለው የሚዳስስ ሥልጠና ነው የወሰዱት፡፡ ትላልቅ አገራዊ አጀንዳ ላይ ለሠለጠነ አካል ሠርተፊኬት መስጠት አግባብ ነው፡፡ ሠርተፊኬቱ መሳተፉን ማረጋገጫ ነው፡፡ ከዚያ ውጭ የሚሰጠው ጥቅም የለም፡፡ ሠርተፊኬት መሰጠቱን እንደ ግዴታ ማሳያ ማድረግ ስህተት ነው፡፡ ማንም ተገዶ እንዲሰለጥን አይደረግም፡፡
የስልጠናው ውጤታማነትስ ምን ያህል ነው?
እኔም አሰልጣኝ ሆኜ ተሳትፌያለሁ፡፡ እንደውም አሁን ከመቱ መመለሴ ነው (ቃለምለልሱ የተደረገው ሃሙስ ከሰአት ነው) መጀመሪያ ላይ የተለያዩ ብዥታዎችን በማሠራጨት ስልጠናውን ለማደናቀፍ ጥረት ተደርጓል፡፡ በዚህ የተነሣ ተማሪውም ዘንድ በግንዛቤ ማጣት ከውጭ በሚነዙ አሉባልታዎች የመነዳት ችግሮች ነበሩ፡፡ እነዚህ ችግሮች የመጀመሪያዎቹ ቀናት አካባቢ ድረስ ብቻ ነው የዘለቁት፡፡ የስልጠናውን ጠቃሚነትና አስፈላጊነት ከተረዳና ጥቅሙ ለራሱ፣ ለማህበረሰቡና ትምህርት ቤት ለላኩት ወላጆቹ መሆኑን ከተገነዘበ በኋላ ግን ስልጠናውን በፍላጎትና በተነቃቃ ስሜት ነው የተሳተፈው፡፡
 ከአንዳንድ ወገኖች ስልጠናውን የማደናቀፍ ተልዕኮ ተቀብለው ወደ ስልጠናው የገቡት እንኳ መጨረሻ ላይ ራሳቸውን አጋልጠው “ይሄ የኔ ሃሳብ አይደለም፣ ይሄን ስልጠና ማዘግየታችሁ እኛን ለብዥታ እንድንጋለጥ አድርጐናል” ብለዋል፡፡ በስልጠናው ላይ መልካም መልካም ነገሮች  ብቻ አይደለም የቀረቡት፤የአገሪቱ ተግዳሮቶችና ማነቆዋች በሙሉ ተነስተዋል፡፡ በአፈፃፀም ሂደት የነበሩ ጉድለቶች፣ የስርአቱም ሆነ የዚህች አገር አደጋዎችና የአደጋ ስጋቶች ምን ምን እንደሆኑ ጎልተው ወጥተው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡ ሁሉም ነገር ሳይደበቅ ግልጽ በሆነ አካሄድ ነው ስልጠናው የተሰጠው፡፡ እንደውም ወደ መጨረሻ ላይ ተማሪዎቹ በፍቅር እየወደዱት መጥተዋል፡፡
 እናም ውጤታማና በድል የተጠናቀቀ ስልጠና ነበር ማለት ይቻላል፡፡ አሠልጣኝም አስተባባሪም ስለነበርኩ በዚህ ረገድ ያየሁትን በሚገባ መመስከር እችላለሁ፡፡ ሌሎች አካባቢ ስለተደረጉት ስልጠናዎች አንደኛው ዙር ከተፈፀመ በኋላ ግምገማ ተካሂዷል፡፡ አፈፃፀማችን እንዴት ነበር? በቀጣይ የነበሩትን ጉድለቶች እንዴት እናስተካክል? የሚል አጠቃላይ ግምገማ ስለተካሄደ ውጤታማና ከጠበቅነው በላይ ነበር ማለት እችላለሁ፡፡ ከተማሪዎቹም ዘንድ ሥልጠናው በአመት አንድ ጊዜ ቢካሄድ-- የሚል ሃሳብ ሲቀርብ ስለነበር እጅግ ውጤታማ የሆነ ስልጠና ነው፡፡
ኢህአዴግ የመንግስት ሃብትና ገንዘብን ለራሱ ርእዮተ ዓለም ማስፈፀሚያ እያዋለ ነው የሚል ትችት ይሰነዘራል፡፡ በዚህስ ላይ ምን ይላሉ?
በመጀመሪያ መንግስት ይሄን ስልጠና የማከናወን ሙሉ መብትና ነፃነት አለው፡፡ አሁን ፓርቲውን በዚህ ለመክሰስ ተፈልጐ ከሆነ፣ ፓርቲው በምርጫ አሸንፎ ስልጣን ላይ እስከሆነ ድረስ በመንግስት የሚሠራው አሸናፊው ፓርቲ የቀረፃቸው ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች ናቸው፡፡ እነዚህ የፓርቲው ፖሊሲዎች ከምርጫ በኋላ ወደ ስልጣን ሲመጣ፣ አገራዊ ፖሊሲ ሆነዋል፡፡ አገራዊ ፖሊሲና ስትራቴጂውን ደግሞ መንግስት በመላ አገሪቱ የማስፈፀም ግዴታ አለበት፡፡ በዚህ አስታኮ ገዥውን ፓርቲ ለመክሰስ የሚደረገው ጥረት ውሃ አይቋጥርም፤ምክንያቱም የአገሪቱን ፖሊሲና ስትራቴጂ የሚያስፈጽመው ፓርቲው ነው፡፡
 አሁን የተሰጠውና እየተሰጠ ያለው ስልጠና በመንግስት እንጂ በፓርቲው አይደለም፡፡ ስለዚህ የሀገሪቱን የአቅም ግንባታ፣ መሠረተ ልማት፣ የአዕምሮ ግንባታንም ጭምር የመስራት ሙሉ ነፃነትና መብት ያለው መንግስት ነው፡፡ ይሄ አንዱ የአቅም ግንባታችን አካል ነው፡፡ የአቅም ግንባታው የሚሰጠው ደሞዝ ተከፋይ ለሆነውና በመንግስት ስልጣን ላይ ላለው ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ ለአርሶ አደራችን፣ ለተማሪዎችና ለተለያዩ ህብረተሰብ ክፍሎች ነው፡፡ ይህ የአቅም ግንባታ እንጂ የርዕዮተ ዓለም ማስረጫ አይደለም፡፡ በአጠቃላይ ስለአገሪቱ እጣ ፈንታ የማወቅና የመወሰን ጉዳይ ነው፡፡ ይህን የማድረግ ደግሞ በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ታሪካዊ ሃላፊነት ነው፡፡ ህገ-መንግስታዊ ግዴታውም ነው፡፡ መንግስታዊ ሃላፊነትንና ግዴታን የመወጣት ጉዳይ ነው፡፡
ስልጠናው መጀመሪያ የታቀደ ሳይሆን ድንገት የመጣ አጣዳፊ ፕሮግራም ነው፤ እንደውም የግንቦቱን ምርጫ ታሳቢ ያደረገ ነው፤ የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ እርስዎ ምን ይላሉ?
ይሄ የተለመደ ነው፡፡ ታስታውሱ እንደሆነ የህዳሴው ግድብ ራሱ ለምርጫ ተብሎ እንጂ የታሰበበት አይደለም ሲባል ነበር፡፡ ነገር ግን የሚሠራውን የሚያስበው በስራው ላይ ያለው አካል ነው፡፡ ከዚያ ውጭ ያለው አካል ከመሬት ተነስቶ የታሰበበት አይደለም፤ መታሰቡንም አላውቅም ብሎ ሊበይን አይችልም፡፡ እነዚህ ወገኖች በመንግስት ውስጥ እስካልሆኑ ድረስ የታሰበውን ነገር ሁሉ አስቀድመው የሚያውቁበት እድል ሊኖር አይችልም፤ነቢያቶች እስካልሆኑ ድረስ፡፡
 ስለዚህ ስልጠናው በመንግስት እቅድ ውስጥ የነበረ እንጂ በዱብ እዳ የተሠራ አይደለም፡፡ ከምርጫ ጋርም የሚያቆራኘው ምንም ጉዳይ የለም፡፡ “ኢህአዴግን ብቻ ምረጡ” የሚል አረፍተ ነገር በአንዲት ቦታ ተብሎ ከሆነ፣ ይሄን በማስረጃ አስደግፎ ማቅረብ ይቻላል፤ ነገር ግን እንዲህ የተባለበት ቦታ የለም፡፡ ከምርጫ ጋር ፈጽሞ ሊያያዝ አይገባም፡፡ ይሄ ጉዳይ ከአንድ ዙር ምርጫ በላይ የዘለለ ነው፡፡ ስለ አገር ህልውና፣ በቀጣይ አገሪቱን ስለሚረከብ ዜጋ ጉዳይ ነው፡፡
 ስለ አገሪቷ እጣ ፈንታ ቀጣዩ ትውልድ እንዲገነዘብ የማድረግ ጉዳይ ነው፡፡ ትውልድን የመቅረጽ ጉዳይ ነው፡፡
 እነዚህ ነገሮች የተለመዱ ናቸው፡፡ ከዚህ በፊት የስነ ዜጋ ትምህርት ሲጀመር ኢህአዴጋዊ ለማድረግ ነው ሲባል ነበር፤ስለዚህ አዲስ ነገር አይደለም፡፡ ይልቁንም “ይሄ ነገር ለአገር በጐ ከማሰብ የተደረገ ነው” ቢባል ኖሮ ነበር በጣም የሚገርመው፡፡ የአሁኑ ግን የተለመደና መሠረተ ቢስ እንደሆነ ላረጋግጥ እወዳለሁ፡፡
ከስልጠናው ምን ተገኘ? ወደፊትስ ምን  ታቅዷል  
በዩኒቨርስቲዎቹ ያሉ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታት የሚያስችል ግብአት አግኝተናል፡፡ በቀጣይም ለአዲስ ገቢ ተማሪዎች፣ ለመምህራንና ለአስተዳደር አካላት የአስር ቀናት ስልጠና ይሠጣል፡፡
በቅርቡ ከአገር የተሰደዱ ጋዜጠኞች ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ ጥሪ እንዳቀረቡ ሰምቼአለሁ---
አዎ አቅርበናል፡፡
በምን መልኩ ነው ጥሪው የቀረበው?
በጋዜጠኞች ስልጠና ላይ የመክፈቻ ንግግር ሳደርግ አንዱ ያነሳሁት ጉዳይ ነበር፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በፍትህ ሚኒስቴር ከተከሰሱ 5 መጽሔቶችና 1 ጋዜጣ ጋር በተገናኘ የተሰደዱ ጋዜጠኞች አሉ የሚል ነገር በየቦታው ይወራል፡፡ እነዚህ ጋዜጠኞች በክሱ ተደናብረው ከሃገር ኮብልለው ከሆነ፤ እነሱን ሊያስጠይቅ የሚችል ነገር ስለሌለ መኮብለላቸው አግባብ አይደለም፡፡ ብዥታው አግባብነት ስለሌለው በአስቸኳይ ወደ ሀገራቸው ተመልሰው ስራቸውን እንዲቀጥሉ ነው ጥሪ ያስተላለፍነው፡፡
አሁንም ደግሜ የምለው፤ ጋዜጠኞቹ ከአገር የወጡት በጋዜጣውና መጽሔቶቹ ክስ ምክንያት ከሆነ፣አግባብ ስላልሆነ  ወደ ሀገራቸው ተመልሰው ስራቸውን እንዲቀጥሉ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

በመምህር ሃይማኖት ታደሰ አራጋው የተፃፈው “ያንዳንድ አጥንት እጣ” የተሰኘ የግጥም መድበል በገበያ ላይ ዋለ፡፡ በመፅሃፉ ውስጥ ተካተቱት ግጥሞች ማህበራዊና ፖለቲካዊ እንዲሁም ፍልስፍናዊ ጉዳዮችን ያነሳሉ ተብሏል፡፡ 43 ግጥሞችን የያዘው መድበሉ፤ 48 ገፆች ያሉት ሲሆን በ20 ብር እየተሸጠ እንደሆነ ታውቋል፡፡
ደራሲው ከዚህ ቀደም “እንበለ ጥበብ” እና “የማርገዝ ነፃነት” የተሰኙ የግጥም መፅሃፍት ያሳተመ ሲሆን ከሌሎች ገጣሚያን ጋር በመሆንም “የማለዳ ነፍሶች” የተሰኘ የግጥም መድበል ለአንባቢያን አድርሷል፡፡

“ድህረ አብዮት ሰልፍ ሜዳ ለሁለት ተከፍሎ፣ ቀበሌ ሃያ ዘጠኝና ቀበሌ ሰላሳ ተብሎ ተዋቀረ፡፡ ሰልፍ ሜዳ

የሚለው ስም የመጣውም ከአብዮቱ በኋላ ነው፡፡ ነዋሪዎቹ ለሁሉ ነገር ይሰለፉ ነበር፡፡ ለዳቦ፣ ለጋዝ/ኪሮሲን፣

ለስኳር፣ ለዘይት፣ ለዱቤ ዱቄት፣ ለቦኖ ውሃ፣ የዕድር ሊቀመንበር ለመምረጥ… ሰልፍ….ሰልፍ….ሰልፍ ለሁሉም፡፡ …

የአሜሪካ ኢምፔሪያሊዝም ተስፋፊነትን ለማውገዝ፤ ለላቲን አሜሪካ ወዛደሮች ትግል አጋርነትን ለማሳየት፤… ነጋ

ጠባ፤ ዘመን መጣ፤ ዘመን … ሔደ… ሰልፍ! ሰልፍ! ሰልፍ! ሰልፍ! ነው! የሌላ ሠፈር ሰዎች፤ ሰልፍ እኛ ሰፈር ብቻ

ያለ ይመስል፤ “ሰልፍ ሜዳ” ሲሉ ጠሩት መንደራችንን፡፡ … እኛም የሰልፍ ሜዳ ልጆች ሆንን፡፡



ንዋይ ንዋይ የሚሸቱ የጥበብ ስራዎችን ዱካ ለማነፍነፍ ብዙ መድከም አይጠበቅብንም፡፡ በልባሳቸው መዥጎርጎር

አሊያም በሚመርጧቸው ርዕሶች በቀላሉ እንለያቸዋለን፡፡ ስገምት ነጋዴ ጸሐፍት ከመጽሐፍት ገበያ ትኩሳት ጋር

አብሮ ከፍ ዝቅ የሚል ርዕስና ርዕሰ-ጉዳይ ሲቃርሙ የሚውሉ ይመስለኛል፡፡ ስገምት ንግዱንም ትርፉንም

በሚገባ ያውቁበታል፡፡ ስገምት ቴሌቪዥን ማታ ማታ “ስግብግብ ነጋዴዎች…” ብሎ ዜና ባነበበ ቁጥር የሚበረግጉ

ይመስለኛል፡፡ ሁልጊዜም የሚከፋኝ ግን አንባቢ እነዚህን ንዋይ አፍቃሪ ጸሐፍት ፊት አለመንሳቱ ነው፡፡
ጥበበኛስ? ጥበበኛ ከነጋዴ ፀሐፍት ጋር ሆድና ጀርባ ነው፡፡ በገበያው ግርግር ውስጥ ተላላነት ያጠቃዋል፡፡

ትርፍና ንግድ በሚሉት ጉዳዮች ባይተዋርነቱ ያይላል፡፡ ተመስጦ ውስጥ ሆኖ በጥቂቶች ልብ ይበራል፡፡ ጥበበኛ

ቅድሚያ የሚሰጠው ለህሊናው ነፃነት ነው፡፡ ቅድምያ የሚሰጠው ለራሱ ስሜት ነው - ለመንፈሱ፡፡
ጥበበኛ ጥበብን ሲከውን እንደመተንፈስ ይቀለዋል፡፡ ዘና ማለቱ ለተደራሲያኑም ይተርፋል፡፡ በዚህ መሰሉ

መዝናናት የተበጃጀ የምናብ አብራክ ክፋይን አይቶ እንዳላየ ማለፍ ከባድ ነው፡፡ እኔም ከሰሞኑ ከአራሙቻው

መሐል ጎንበስ ቀና የሚል እሸት ጥበብ፣ ከዓይኔ ሲገባ ዝምታን ወግድ ብዬ አንድ ሁለት ለማለት ፈለግሁ፡፡

ለትችትም ለሙገሳም የሚበቃ ንፁህ የጥበብ ሥራ ማግኘት አሁን አሁን እንደመታደል የሚቆጠር ሆኗል፡፡ ሰልፍ

ሜዳ ከእነዚህ ውስጥ የሚካተት የጥበብ ሥራ ነው፡፡ በዚህ ፅሁፌ ይሄን ልቦለድ ነው ለአንባቢያን ለማስቃኘት

የወደድኩት፡፡
የሰልፍ ሜዳ ሽፋን፤ ጽልመት የወረሰው፣ የኾነ የሚጨፈግግ  ቀንን የሚያስታውስ ነው፡፡ ጫፉ የማይታይ ጉም

የለበሰ ሰማይ ስር፣ ከሰው የተራቆተ ጎዳና፣ በደብዛዛ ብርሃን አንዲት ወልጋዳ ሰማያዊ ታክሲ እንደነገሩ

ትታያለች፡፡ ደራሲው ግርማ ተስፋው፤ ተደራሲያኑ ገና የመጽሐፉን ልባስ ማየት ሲጀምሩ በፈተና ሊቀበላቸው

የፈለገ ይመስላል፡፡ እንዴት? ቢሉ በመጽሐፉ ሽፋን ላይ የድብርት ቆሌ አርብቦበታልና ነው፡፡
የመጽሐፍ ሽፋን የጎጆ በር ማለት ናት፡፡ ደራሲው ከመጽሐፉ ገጾች ሳቅና ጨዋታን እንዳንጠብቅ ጎጆዋን ከል

አልብሷታል፡፡ በ240 ገጾች የተቀነበበው ይህ ረዥም ልብወለድ፤ መቼቱ በደርግ መውደቂያ ዋዜማ ላይ ነው፡፡

መላ ታሪኩ ተጀምሮ የሚጠናቀቀው አዲሳባ ከምትገኝና ደራሲው በምናብ ከፈጠራት “ሰልፍ ሜዳ” ከተባለች

መንደር (ሰፈር) ነው፡፡ ይህ ምናባዊ ሰፈር “ሰልፍ ሜዳ” ለምን ተባለ ለምንል ተደራሲያን በገጽ 70 ላይ እንዲህ

ተብራርቶልናል፡-
“ድህረ አብዮት ሰልፍ ሜዳ ለሁለት ተከፍሎ፣ ቀበሌ ሃያ ዘጠኝና ቀበሌ ሰላሳ ተብሎ ተዋቀረ፡፡ ሰልፍ ሜዳ

የሚለው ስም የመጣውም ከአብዮቱ በኋላ ነው፡፡ ነዋሪዎቹ ለሁሉ ነገር ይሰለፉ ነበር፡፡ ለዳቦ፣ ለጋዝ/ኪሮሲን፣

ለስኳር፣ ለዘይት፣ ለዱቤ ዱቄት፣ ለቦኖ ውሃ፣ የዕድር ሊቀመንበር ለመምረጥ… ሰልፍ….ሰልፍ….ሰልፍ ለሁሉም፡፡ …

የአሜሪካ ኢምፔሪያሊዝም ተስፋፊነትን ለማውገዝ፤ ለላቲን አሜሪካ ወዛደሮች ትግል አጋርነትን ለማሳየት፤… ነጋ

ጠባ፤ ዘመን መጣ፤ ዘመን … ሔደ… ሰልፍ! ሰልፍ! ሰልፍ! ሰልፍ! ነው! የሌላ ሠፈር ሰዎች፤ ሰልፍ እኛ ሰፈር ብቻ

ያለ ይመስል፤ “ሰልፍ ሜዳ” ሲሉ ጠሩት መንደራችንን፡፡ … እኛም የሰልፍ ሜዳ ልጆች ሆንን፡፡
በዚህ ማብራሪያ ደራሲው የሰልፋም ሰፈርነቱን (ሰሙን ማለት ነው) ያትት እንጂ ወርቁን ሊነግረን አልዳዳውም፡፡

ወርቁን ገጽ በገፋን ቁጥር፣ እንደ በቆሎ እየፈለፈልን እንድናገኘው ነው የፈለገው፡፡
ሰልፍ ሜዳ ዙሪያ ጥምጥም ነው፡፡ ወሰን ድንበር ፍጻሜው አይታየንም፡፡ ወትሮ እንደለመድናቸው የልብወለድ

ታሪኮች፣ የስሜት ከፍታን በእያንዳንዱ ኩርባ ላይ ለመቃረም ከዳዳን አይሳካልንም፡፡ እፍ ክንፍ ያለ የፍቅር

ታሪክ፣ ሴራ ጉንጎና፣ ልብ ሰቀላና የመሳሰሉት የሥነ-ፅሁፍ ጌጦች በዚህ መጽሀፍ ውስጥ ብርቅ ናቸው፡፡ ለልብ

ሰቀላ ሲሉ መጽሐፍ ለሚያነቡ ተደራሲያን፣ ይህ መጽሐፍ ደመኛቸው ቢኾን አይገርምም፡፡ በሰልፍ ሜዳ ኩርባ

የሚባል ነገር የለም፡፡ የታሪክ መቋጫ ፍለጋ ከተንደረደርን፣አድማስ ጋር ሰዶ ማሳደድ እንገባለን፡፡
የመፅሐፉ አንኳር ጭብጦች
መጽሐፉ ስለብቸኝነት፣ ስለባዶነት፣ ስለከንቱነት----መብሰክሰክ ይበዛዋል፡፡ ገጸ-ባህርያቱ እዚህ ግቡ የማይባሉ

ተራ ሰዎች ናቸው፡፡ እንደ ወይዘሮ ከድጃ አይነት ቡና ማፍያ የሚለምኑ፤ እንደ እሙ ከሴተኛ አዳሪ ተወልደው

ቆሎ የሚያዞሩ… ወዘተ፡፡ እንዲያውም አንዳንዶቹ ሲኖሩ ትዝ የማይሉን፣ ነገር ግን ሲሞቱ ይበልጥ

የምናስታውሳቸው ናቸው፡፡ ለምሳሌ ንጉሴ የተባለው ገጸ ባህሪ ወፍጮ አስፈጪ ነው፡፡ የሰልፍ ሜዳ ሰው፣ ንጉሴ

በህይወት መኖሩ ትዝ ያለው ለአካባቢው ዳቦ በምታድል መኪና የተገጨ ዕለት ነው፡፡ “… ንጉሴ ሰው ሳይሆን

የሰው ጥላ ይመስለኝ ነበር፤ በኑሮው ሳይኾን በሞቱ ሰው መስሎ ተሰማኝ” (ገጽ 8)፡፡
በገመናችን የሚዘባበቱት አያቱ!
“ስማ የእግዜር ቀልድ ይሉኝ ነበር አያቴ” በሚል ንግግሩ ነው የልቦለዱን ዋና ገፀ ባህሪ የምንተዋወቀው፡፡ ታሪኩ

ይባላል፡፡ በአንደኛ መደብ ሙሉ ታሪኩን የሚተርክልን ይኼ ገጸ ባህሪ ነው፡፡ የታሪኩ አያት ብርቱ ሰብእና

አላቸው፡፡ ብሽቀታቸውን መሸሸግ አይሆንላቸውም፡፡ በአገኙት አጋጣሚ ፈጣሪን በነገር ጎሸም ማድረግ

ይቀናቸዋል፡፡ ማህበረሰቡንም እንደዚያው፡፡ ጉሸማው ለሌላ አይደለም፡፡ የንቃ ዓይነት ደውል ነው፡፡
አዛውንቱ በገመናችን ይዘባበታሉ፡፡ በአመለካከታችን፣ በስንፈታችን፣ በጉብዝናችን፣ በእምነታችን፣ በክህደታችንና

በታሪካችን ላይ ክፉኛ ይሳለቃሉ፡፡ እኝህ አዛውንት የደራሲውን የብሽቀት ጥሪት ጠቅልለው የተሸከሙ

ይመስላሉ፡፡ በፈጣሪም በህብረተሰቡም ተሳላቂው አያት፤ ጣሊያንን ያንቀጠቀጡ ጎበዝ አርበኛ ነበሩ፡፡ ኋላ ላይ  

ወራሪው ኃይል ከሀገር ሲባረር፣ ወደ ጭቃ ረጋጭነት ሥራ ተሸጋገሩ፡፡ እርሳቸው በዱር በገደሉ ሲዋደቁ ግን

ባንዳዎች የፋሺስት ጫማ ይወልውሉ ነበር፡፡ ከድል በኋላ ጫማ ወልዋዮቹ ባንዳዎች ሹመት ሲሰጣቸው፣

እርሳቸው ግን ጭቃ ረጋጭ ሆነው ቁጭ አሉ፡፡
“ሀገሬ ኢትዮጵያ ሞኝ ነሽ ተላላ፤
የሞተልሽ ቀርቶ የገደለሽ በላ፡፡” የሚለውን ስንኝ ያስታውሰናል - የእሳቸው ታሪክ፡፡
የታሪኩ አያት ታሪክ ብቻ መርምረው አያበቁም፡፡ ስነልቦናችንን ይሰልላሉ፡፡  
የታሪኩ አያት ቄስ ቢኾኑም በአንድ አጋጣሚ ከታሪክ ጋር ሆነው በ “መታፈሪያ ጠጅ ቤት” ታድመዋል፡፡ የሰልፍ

ሜዳ “ጉልቤ” ተስፋሁን፤ አንድ ቦርጫም ጠጪን አንበርክኮ፣ እላዩ ላይ ጠጅ እያፈሰሰ ይንከተከታል፤

ይሳለቅበታል፤ ያዋርደዋል፡፡ ሰዎች በጉልቤው ተስፋሁን፣ እርር ድብን ቢሉም ማንም ለመናገር አይደፍርም፡፡

በሁኔታው የተናደዱ የሚመሰሉት ሽማግሌው የታሪኩ አያት፤ ከተቀመጡበት ብድግ ብለው ጉልቤው ተስፋሁንን

በቁጣ ገደሉት ሲባል፣ በተቃራኒው የተንበረከከውን ሰውዬ ከተስፋሁን ጋር ተደርበው መደብደብ ያዙ፡፡ ይበልጥ

የምንደመመው ግን ይህን ያደረጉበትን ምክንያት ሲገልጹ ነው፡፡ በገጽ 67 እና 68 ላይ እንዲህ ይላሉ፡-
“… መንበርከክ እንደ ተስቦ ከሰው ሰው እንደሚጋባ አታውቅም? አናት አናቱን ማለትማ ተንበርካኪውን ነው!

ኧ---- ያኔ ነው ሰው የሚኾነው፡፡”
“ተንበርካኪ መቼ ምክንያት ያጣል፤ብትጠይቀው እኖር ብዬ፤ ልጅ አሳድግ ብዬ ይልኻል፡፡ የሰው ዝቃጭ፡፡ የኖረ

መስሎታል፡፡ ሞት አይቀር! ተረጋጭም የረጋጭን ያህል ጥፋተኛ ነው፡፡… ይበለው”
ጭቆናን አሜን ብሎ የሚኖር ሰብእና፣ የሀጢያት ዳፋው ከጨቋኙ በላይ ይገዝፍብናል፡፡ ተንበርካኪነትና ጎብጦ

የሚያዘግም ስነልቦናን ደራሲው እንዲህ ባለ ተራ የጠጅ ቤት ግጭት ሊያስዳስሰን ሲሞክር እንወደዋለን፤ እናም

አበጀህ እንለዋለን፡፡
አብደላ ሻይ ቤት እንደ ብሶት አደባባይ
ሳምቡሳ የሚጠበስበት ሻይ ቤት፣ በሰልፍ ሜዳ ላይ ታሪክን ለማንጎድ መደላደያውን ያመቻቸ ታንኳ ሆኖ

እናገኘዋለን፡፡ አብደላ ሻይ ቤት፣ የመጣው ሁሉ ብሶቱን የሚጥልበት ጉሮኖ ነው፡፡ ደራሲው ይህንን ስፍራ

በዋነኛነት ለመጠቀም የፈለገው ምን አልባትም ለአብዛኛው ህብረተሰብ ቅርብ የሆነ ስሜትን እፈጥርበታለሁ

በሚል ምናባዊ ጥንስስ ተገፋፍቶ ሊሆን ይችላል፡፡ በአብደላ ሻይ ቤት ታሪክ ይወጣል ይወርዳል፡፡ ፍልስፍናን

በላይ በላይ እንመገባለን፡፡ ተፈላሳፊዎቹ ደሞ ማንም በማይገምተው መልኩ የመጀመሪያ ደረጃ መምህራን

ናቸው፡፡ አብዮት ተስፋ በሚባል ትምህርት ቤት ያስተምራሉ፡፡ አንባቢው እንዴት ይህን የመሰለ ጥልቅ

ፍልስፍናን ከመጀመሪያ ደረጃ መምህራን እናገኛለን? ብሎ ቢሞግት አይፈረድበትም፡፡ የጊዜ ስሌት ግን ሙግቱን

ውሃ እንዳይቋጥር ያደርገዋል፡፡ ተፈላሳፊዎቹ መምህራን ከአብዮቱ ግርግር ዘመን በፊት ነው የበቀሉት፡፡

መምህራኑ የደራሲው ምናባዊ ፈጠራ ቢኾኑም በዘመኑ የነበሩትን ታሪካዊ ኩነቶች እያነሱ የሚጥሉበት የአስተሳሰብ

ጥልቀት፣ የገሃዱ ዓለም አካል አድርገን እንድንቆጥራቸው ያስገድደናል፡፡ በዚህም ምክንያት የሰልፍ ሜዳ

መምህራንን ከአሁን ዘመን መምህራን ጋር ለማነፃፀር ልኬት ውስጥ የምንገባባቸው አጋጣሚዎች ይበራከቱብናል፡፡
የሁለት መንትዮች ወግ
መንትዮቹ ቸርነትና አሸናፊ ይባላሉ፡፡ የታሪኩ የልብ ጓደኛ የለዓለም ወንድሞች ናቸው፡፡ ደራሲው የሁለቱን

መንትያዎች ስነልቦና የታሪካችን ማሳያ አድርጎ ቀርጾታል፡፡ እዚህ ጋ የደራሲውን ታሪክ አዋቂነት ልብ ይሏል፡፡

ቸርነት በአብዮቱ ዘመን አካባቢ የበቀሉ ልሂቃንን ይወክላል፡፡ ከታሪክ እንደምንረዳው፣ በአብዮቱ መባቻ ላይ

በፊት አውራሪነት የተሰለፉት ልሂቃን ስነልቦና ወጥ ነበር፡፡ ሁሉም፣ ጽንፈኝነትን ያነገቡ፣ ሁሉም እውቀትን

ሳይፈትሹ እንደወረደ የሚያጠልቁ ደብተራዎች ነበሩ፡፡ የቸርነትን ግልብ ስነልቦና በዘመኑ በነበሩት ዘውግ-ዘለል

የፖለቲካ ድርጅቶች ላይ እናገኘዋለን፡፡ ቸርነትን ስንመለከት የማርክሲዝም ሌኒንዝምን ጥቅስ በቃል በማነብነብ

ብቻ ለአዋቂነታቸው ሚዛን የሚሰፍሩ ምሁራንን እናስታውሳለን፡፡ ቸርነት በማርክሲዝም ሌኒንዝም ከተጠመቀ

በኋላ፣የቤተሰቡን እምነት በአንዲት ጀምበር ለመናድ የሚጣደፍበት ሁኔታ ሀገራችንን ከድጡ ወደ ማጡ

የሰደዷትን የአብዮቱን ዘመን የፖለቲካ ልሂቃን ያስታውሰናል፡፡ ለቸርነት ጽንፈኝነት ማሳያ መንትያ ወንድሙ

አሸናፊ በተቃራኒው ተስሏል፡፡ አሸናፊ ሚዛናዊ ነው፡፡ አማካይ ስፍራን መያዝ ይወዳል፡፡ የአርስቶትልን “Golden

Mean”  እዚህ ጋ እናስታውሳለን፡፡ “ዘ ጎልደን ሚን” አርስቶትል ሚዛናዊነትንና ክፍት ስነልቦናን የገለጸበት

መጠሪያ ነው፡፡ በእርግጥም አሸናፊ ይህ ስያሜ ይገባዋል፡፡
ጉዱ ካሳዊው - ለዓለም
ለዓለም መኩሪያ የደራሲው የምናብ ከፍታ ውላጅ ነው፡፡ በ“ፍቅር እስከ መቃብር” ከግርግሩ መሐል

በባይተዋርነት ቆሞ የሚሟገተውን ጉድ ካሳን በሰልፍ ሜዳ ላይ ለዓለም ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ለዓለም ለእንቶ

ፈንቶው ፊት መንሳት ያውቅበታል፡፡ እጅግ የላቀ ቁርጠኝነትንና ጽናትን ከሚጠይቁ ጉዳዮች ጋር ሲጋፈጥ

እናስተውለዋለን፡፡ በገጽ 104፤ ለዓለም ከጓደኛው ታሪኩ ጋር በሚያደርገው ምልልስ የአመለካከቱን አስኳል

እናገኛለን፡-
“መፍራት ካለብህ ብቻውን መሆን የማይወድን ሰው ፍራ፡፡ ሰው በህብረት ሲሆን እምነት የለኝም፡፡ ታሪኩ፤ ሰው

ማህበራዊ እንስሳ ነው የሚሉህን አትስማቸው፡፡ ቆፈናሞች!! አፍንጫችሁን ላሱ በላቸው፡፡ በቡድን አደራጅተው፤

ከፋፍለው ከፋፍለው ለማጋደል፣ ለማሰርና ለመግዛት እንዲመቻቸው ነው፡፡ ሰው ብቸኛ እንስሳ ነው፡፡ ትልቁ

ትራጄዲ ብቸኝነቱን መሸሹና መፍራቱ ነው፡፡”
ይህ ዓይነቱ ከመንጋ የመነጠል አባዜ፣ የጉዱ ካሳ እምነትና አመለካከት፣ ቀኖና ውላጅ ነው፡፡ ለዓለም ግርግሩን

ለመሸሽ በሚያደርገው ጥረት፣ ከህዝበ ሰልፍ ሜዳ ብርቱ ወከባ ሲያጋጥመው እናስተውላለን፡፡
የመጽሐፉ ድክመቶች
ገጸ ባህሪን ከማስተዋወቅ አንጻር
ገፀ-ባህሪን ከተደራሲያኑ ጋር ከማስተዋወቅ አንጻር በመፅሃፉ ውስጥ ጉልህ ክፍተት ይታያል፡፡ በመጀመሪያው

ምዕራፍ መግቢያ አካባቢ፣ በመኪና አደጋ ለህልፈተ ህይወት የበቃው ንጉሴ፤ ድንገት ሞትን እንደ አልአዛር ድል

አድርጎ፣ በገጽ 93 በዳቦ ሰልፍ ላይ እናገኘዋለን፡፡ የንጉሴ ከአንባቢው ጋር ድንገት ፊት ለፊት መላተም፣ የታሪኩን

ፍሰት ያንገራግጨዋል፡፡ ስለንጉሴ ምንነት በቅጡ ለማወቅ ንባቤን ገታ አድርጌ፣ ያለፍኳቸውን ገጾች እንደገና

መመርመር ነበረብኝ፡፡ ይህ ግርታ የኔ ብቻ ሳይሆን የብዙ ተደራሲያን እንደሚሆን እገምታለሁ፡፡
መቼት
ገፀ-ባህሪያቱ በጊዜና በቦታ መለኪያ ሲሰፈሩ በደንብ አልታሹም፡፡ አብደላ ሻይ ቤት በልብወለዱ ውስጥ

በጉልህነት ከሚነሱት ቦታዎች አንዱ ነው፡፡
በገጽ 11 ላይ፤ “አብደላ በቀይ ሽብር ዘመን በተባራሪ ጥይት የተገደለ የሙሰማ ታናሽ ወንድም ነው፤ በተባራሪ

ጥይት ለሞተ፣ ሐውልት የሚያቆምም የሚያጀግንም ስለሌለ፣ ይህን ምግብ ቤት በታናሽ ወንድሙ ስም ጠራው፤

የአብደላ ስምም በመላው ሰልፍ ሜዳና በዙሪያው ባሉ የአዲስ አበባ ሰፈሮች ሁሉ ታወቀ” ሲል ስለስያሜው

ያትታል፡፡
ደራሲው ስያሜው ከጊዜው ጋር ይጣጣም አይጣጣም ግድ የሰጠው አይመስልም፡፡ በቀይ ሽብር የተገደለን

ሰው፣በአዲስ አበባ ነዋሪዎች ፊት ለመዘከር ድኅረ ደርግና ቅድመ ደርግ ለየቅል መሆናቸውን ማንም ሊረዳው

የሚችል ሀቅ ነው፡፡ ሌላው ቢቀር በቀበሌ ሹማምንት ዘንድ ይህ ተግባር ጥርስ የሚያስገባ ድፍረት ነው፡፡ ለዚህም

እራሱን ልብወለዱን ምስክር ማድረግ እንችላለን፡፡ ደራሲው የሰልፍ ሜዳ ህብረተሰብ የቀበሌውን ሊቀመንበር

ጓድ እንዳይላሉ መርሻን ሲመለከት፣ ብርክ እንደሚይዘው በመጀመሪያው ምዕራፍ ገጾች ላይ እየደጋገመ

እየነገረን፣ ሙሰማን እንደ ጸረ አብዮት በሚያስቆጥር ተግባር ላይ ደፋር ማድረጉ ከምን የመጣ ነው ብለን

እንድንጠይቅ ያስገድደናል፡፡ እዚህ ጋ ከግምት መጣፍ ያለብን የቤቱን ጭርንቁስነት ሳይሆን የጊዜውን እውነታ

ነው፡፡ በወቅቱ የነበረው የፖለቲካ ትኩሳት፣ የቤቱ ስያሜን ተዓማኒነት እንደሚያጎድል መታሰብ ነበረበት፡፡
በእንግዳ ቃላት ማደናገር
ሰልፍ ሜዳ የቃላት ደሃ አይደለም፡፡ የቃላት ደሃ አለመሆኑ ግን ያዘናጋው ይመስላል፡፡ ደራሲው እንግዳ ቃላትን

ወይም አገላለጽን ያለ ማብራሪያ ዝም ብሎ ነው የሚያልፉቸው፡፡ ለአብነት ያህል በገጽ 175 ላይ እንዲህ የሚል

ስንኝ ሰፍሯል፡-
ቀነውኒ አደውየ ወእገርየ
ወኈለቍ ኩሉ አዕፀምትየ
ቀነውኑ እንደውየ ወአገርየ
ትንሽ አለፍ ብሎ “አምንስቲቲ ሙክርያ” የሚል ቃል ይገኛል፡፡ ደራሲው የቃላቱን  ትርጉም በቅንፍ ጠቆም

አድርጎ ማለፍ ወይም የህዳግ ማጣቀሻ መጠቀም ይችል ነበር፡፡
በአጠቃላይ ግን ሰልፍ ሜዳ ባልተሄደበት ጎዳና ለመንጎድ የጀገነ፣ ግሩም የቋንቋ ዉበት ያለው፣ እንደወቅቱ

በድፍረት ተነስቶ ስለማያውቁት ጉዳይ መጽሐፍ የመጻፍ ደዌ ዉስጥ ያልተዘፈቀ፣ በስክነትና በእውቀት የተከተበ፣

ኩልል ያለ የጥበብ ስራ ሆኖ አግኝቼዋለሁ፡፡ ደራሲው አንድ ተጨማሪ የጥበብ ስራ ከደገመን ምናልባት አዳም

ረታ ታናሽ የጥበብ ወንድም አገኘ ብለን ለማወጅ እንደፍር ይሆናል፡፡  

Published in ጥበብ

በበለጠ በላቸው ይሁን የተፃፈው “ጅቡቲ የጥገኝነታችን መስፈሪያ” የተሰኘ መጽሐፍ ባሳለፍነው ሳምንት መጨረሻ

ለንባብ በቃ፡፡ በስድስት ምዕራፎች ተከፋፍሎ በ222 ገፆች የተመጠነው መጽሐፉ፤ ከአፄ ኃይለስላሴ መንግስት

ጀምሮ በበርካታ የኢትዮጵያና ጅቡቲ ጉዳዮች ላይ ትንታኔ ያቀርባል፡፡ መጽሐፉ በ65 ብር ለገበያ እንደቀረበ

ለማወቅ ተችሏል፡፡

Monday, 29 September 2014 09:15

ያልተከፈለ ስለት

         ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ በግጥሞቹ አንባቢን መመሰጥና መዉሰድ ችሏል። ፍካት ናፋቂዎች እና እዉነት ማለት የኔ ልጅ በተሰኙ ሁለት የግጥሞች ስብስብ ኮስታራ ጭብጦች በዉብ ቋንቋና ዜማ ተቀርፀዉ ያዉካሉ፤ ያወያያሉ። በዚህ ብዕሩ ለግጥም እጁን የሰጠ አልያም አልቀነበብ ያለ ጉዳይ በአጭር ልቦለድ ለማበልፀግ፥ ለመግራት መወሰኑ ለሚናፍቀን ተደራሲያን ስጋትም ጥርጣሬም ነዉ። አንደ ብርቅ ባለቅኔ ግጥሞቹን ችላ ብሎ በትረካ እየቀዘፈ ሳይመለስ በዚያዉ ይቀር ይሆን ? ወሳኙ ጥያቄ ግን አጭር ልቦለዶቹ የግጥሞቹን ጥልቀትና ጥበባዊ ዉበት ይመጥናሉ ወይ ? አንድ ብርቱ የልቦለድ ደራሲ በ“ያልተከፈለ ስለት” ምናባችንን ሲያንኳኳ አድምጠነዋል ወይስ እንደነገሩ ነዉ ? ዶ. በድሉ በመቀኘትም በመተረክም ሰምሮለታል። እርካታም ተስፋም ነዉ፤ በሁለቱም ዘዉጐች ምናልባትም በአብይ ልቦለድ [novel] ገና የሚያስነብበን የኑሮ ምስጢር ይኖራል።

ጊዜና ሰዉን የታከኩ ክስተቶች ጐምዝዘዉ ጣፍጠዉም የተደራሲን ልቦና እና የዕለት በዕለት ኮሽታዉን ለማፍጠንም ለመገደብም ይበቁ ይሆናል። ስምንት አጭር ልቦለዶች ናቸዉ፤ መቼታቸዉና ጭብጣቸዉ እጅጉን ይለያያሉ፤ በአንድ ጉዳይ ወይም አዉድ መታጠር መድንዘዝ አይመቸዉም፤ ከአንድ የዉሃ ጉድጓድ ብቻ አይቀዳም። ዛሬ፥ ትናንት በደርግ ዘመንና በመሳፍንት አገዛዝ ወቅት ለኑሮ መብሰክሰክ፥ በስልጣን የመቆየት አባዜ፥ ለቤተክርስትያንና ለአድባር የማደር ትንቅንቅ፥ ለመንፈስ የመገጣጠብ ክፋት ... ተጠላልፎበታል። ወሲብና ፍቅር የጣዕም ጉዳይ ብቻ ሳይሆን ለባል ጓደኛ በስምምነት መዉለድ ሥነልቦናዊና ኅላዌ ቀዉሱ ያደናቅፋል። ረዘም የሚለዉ - በስድሳ ገፅ የተፍታታዉ ልቦለድ “ዉድቅትን በዉድቅት” ግለ ታሪክ ቢሆንም በአፃፃፍና ትረካ ጥበቡ ከሌሎቹ አይተናነስም።

በአማርኛ ልቦለድ ታሪክ በግልጥ ደራሲዉ የኖርኩትን ህይወት ነዉ የፃፍኩት ማለቱ ፈር-ቀዳጅ ነዉ። የእዉነተኛ ታሪክና የልቦለድ ድርሰት ወሰን የት ላይ ነዉ ? ... አንዳንዱ የተኖረ ህይወት የልቦለድ ድርሰትን ያህል እዉነትነት ያንሰዋል። አንዳንዱ ልቦለድ ድርሰት ደግሞ ከተኖረ ህይወት የበለጠ እዉነት ሆኖ ይገኛል። ህይወትና ድርሰት ሁነታቸው የተጣቀሰ፥ ድንበራቸዉ የተጣረሰ ነዉ። [ገፅ 121 ] ግለ ታሪክ ይባል እንጂ፥ ዶ.ዮናስ አድማሱና ዶ.ፈቃደ አዘዘ አድማጭና አሳብ ቀስቃሽ ሆነዉ በትረካዉ መካከል እየተናገሩ እና የዉድቅት እንቅልፍ ሳያሸልባቸዉ፣ ለእሳት ዳር የአባቶች ተረት ከልጅነት ስንቅ መጓጓትን እየተዋሱ ቢደምቅም፣ ጥሬ ታሪክ አይደለም። እንደፈሰሰ ሳይከረከም የሚያወጉት አይደለም። ዋናዉን ዶ.በድሉ የኖረዉን ከሞት ወደ እዉቀት የሽሽት ጉዞ ሌጣዉን ሳይሆን በሁለት ምሁራን እንቅስቃሴና መጠበብ ተርብም ታጅቦ፥ በመካከሉ በሽፍታዉ አዛዉንት ታሪክ፥ ወኔና ጭካኔ የተወጠረም ነዉ።

የአካባቢ ገለጣ፥ በጥንቃቄ መተረኩ እና የቋንቋዉ መሳጭነት በግለ ታሪክ ጥበት አያስቀነብበዉም። የደረሰን ታሪክ በአፃፃፍ ጥበብ ወደ ፈጠራ ድርሰት እንደ ማበልፀግ ነዉ። ሰዉ ከሞት አፋፍ ለመመለስ ሲዳክርና ለትምህርቱ ሲያድር -የወጣት በድሉ ታሪክ- በአንፃሩ ቀላል እንደነበር የምናጤነዉ፥ የአዛዉንቱን ሽፍታ ወደ ሞት የምንደርደር ተደጋጋሚ ሩጫና መብሰክሰክ ሲያስደምመን ነዉ። የተኖረም ይሁን፥ ምናብ የጫረዉ ታሪክ፥ የአጻጻፍ ክህሎቱ ነዉ ወደ ልቦለድ ጥበብ የቀላቀለዉ። “መስዋእት ፍለጋ” ወደ መሳፍንት ዘመን ያፈገፈገ ታሪክ ይምሰል እንጂ፥ ሁሉንም ዘመን የሚወክል ተምሣሌት ነዉ። ተደጋጋሚ የእንቅልፍ ቅዠት እዉነታን ተክቶ፥ ግለሰብ በፍርሃት ተሸብቦ፥ ሰዎች ውስጠታቸዉ ሲላላጥ ራስን እንደ መታዘብ ነዉ። ለስብስቡ ርዕስ የተመረጠዉ “ያልተከፈለ ስለት” ፖለቲካዊ ይዘት እንዴት ጥበባዊ ብስለት ሊወርስ እንደሚችል እና በዶ.በድሉ ክህሎት ደረቅ ጉዳይ ሲለሰልስ፥ ሲገራ እንደመምበታለን። ምርጫዉን ማን አሸነፈ ሳይሆን ሰዉ በፈቃዱ የጠየቅኩህን ከፈፀምክልኝ እምከፍልህ አለኝ ብሎ ለፈጣሪዉ ለታቦት ... ሲሳልና ቃል ሲገባ ድባቡና ገመናዉን ታክኮ መተረኩ ድንቅ ነዉ።

የሰፈር ሰዎች የግንቦት ልደታን ሲያከብሩ፣ እየተበላና እየተጠጣ ሊጨፈር ብቻ ሳይሆን ከታደሙት ጥቂቶቹ “ነፍሳቸዉ በየግል ተብሰልስሎታቸዉ ይናጣል”፤ ይህም ነዉ ልቦለዱን ከፍ ያደረገዉ። ልብስ ሰፊዉና አሮጌ ዕቃ እየጠጋገነ የሚኖረዉ ጓደኛሞች ናቸዉ። “የወዳጅነታቸዉ ጥልቀት ... ሁለቱም የግንፍሌን ነዋሪ ጓዳ ጐድጓዳ ፥ ገመናዉን ማወቃቸዉ ነዉ።” ለህሊና ወይስ ለጥቅም ወይስ ስለት ለመክፈል የምትቅበዘበዝ ነፍስ መሸሸጊያ ትነፈጋለች። ቅኔያዊ ርዕስ የታከለበት አጭር ልቦለድ “የህይወት ቅዳጆች”፣ ደራሲዉን የረጅም ጊዜ የአተራረክ ክህሎት የተካነ ያስመስለዋል። ተራኪዉ ሥራዉን ትቶ ለሁለተኛ ድግሪ እጅ አጥሮት እየተማረ ነዉ። ከተከራየዉ ቤት የሰፈሩን ሰዉ በመላላክ የምታገለግል ወይኗ አለች። “ገና አስር አመት ሳይሞላት እናቷንና አሮጊት አሳዳጊዋን የገፋች፥ በያለችበት የምታድር የመንደሩ ተላላኪ” “እሱ በዝርግ ሰሀን እያረመደ፥ እሷ በእጇ ጨምድዳ በጥርሷ እየቦጨቀች” ምሳቸዉን እንጀራ በሚጥሚጣ ተካፈሉ።

ወይኗ ከሰል እያቀጣጠለችለት ሳለ ስኳር የተገዛበትን ወረቀት ሲገላልጥ “በጥቁር እስክሪብቶ ጥቅጥቅ ተደርጐ ተጽፎበታል” ትረካዉን አንዲት ልጃገረድ ትረከበዋለች። “ንጽህናዬን አላስደፍር ብዬ ስሮጥ፥ የሚያባርረኝ የአያ ንግሩ ልጅ ጉግሳ፥ ሳር ጥልፎት ወደቀ። ሲወድቅ ጉቶ በደረቱ ተሰንቅሮ ኖሮ አፍታም ሳይቆይ ሞተ።” በዚህ ምክንያት ወደ አክስቷ ቤት ብትሸሽም አሁንም በሌላ ወንድ ላለመደፈር ባደረገችዉ ሙከራ አክስቷም የዋህነቷም ለእንግልት ይበቃሉ፤ ሴት መሆን፥ እጦት ታክሎበት ያስጠቃል። ዶ.በድሉ “የህይወት ቅዳጆች” ሲል ሰዉ በተለይም ህፃንና ወጣት ሴት ትልታይ፥ ቁራጭ፥ እራፊ ... አክላ ከኑሮ ለመላተም እጅጉን ሊከብዳት እንደሚችል፥ የንብረት የረባ ዘመድ አለኝታ መነፈግ የአዋቂንም ጉዞ እንዲሚያዳልጥ የተቀኘበት ነዉ።

ሶስት ታሪኮች በአንድ አጭር ልቦለድ የተወሳሰቡበት ነዉ። ይበልጥ ግን አንጀት የምትበላዉ ገና በአስር አመቷ መጠለያ አጥታ፣ ሜዳ ላይ እጣ ፈንታዋን የባዶ ድስት ህይወት ለመዉረስ የምትዳክረዉ ወይኒቱ ናት። ይህን የሚታዘበዉ ሥራዉን ትቶ ለድኅረ ምረቃ ትምህርት መስዋዕት እየከፈለ -እየተራበ- የሚያቃስተዉ ተራኪዉ ነዉ። ከሰፈሩ የእንጀራ ጋጋሪዋን ልጅ፥ ብሎም መቅዘፍያዋን የተቀማች ህፃን ፥ ሌላዉንም እያጤነ አያበቃም። ሳይጠብቀዉ፥ ከሩቅ ይሁን ከቅርብ መንደር ከስኳር ጋር አብሮ የተጠቀለለ የአንዲት ልጃገረድ የድንግልና ታሪክ አስተዉሎቱን ያደፈርስበታል። ቀና ብሎ ነገን በጉጉት ሳይሆን በስጋት የመጠበቅ አባዜ ይመዘምዛል። በዕዉቀቱ ሥዩም በአንድ እምቅ ግጥሙ የተቀኘዉን ያስታዉሰናል። “ያንን ገለባ ልብ ከደጅ የወደቀዉ/ አድራሻህ ወዴት ነዉ ? ብለህ አትጠይቀዉ/ የነገዉ ነፋስ ነዉ መንገዱን የሚያውቀው” ተራኪዉ ብቻ ነዉ እያቃሰተ የነገዉን ህይወት አቅጣጫ ለማግኘት አቅም የሰበሰበዉ። ህፃኗ አትተርፍም፤ ወጣቷም ዉስጧ የመሸገ የሚርበተበት ዉበት ስንቅ ከሚሆናት ወጥመድ ሆናት።

ልቦለዱ እንደ ዘመናዊ አጣጣፍ ታሪኩ ሳያበቃ -open end- ከምናብ ለምናክልበት ስፍራ ያስተርፋል። ከስምንት ትረካዎቹ በተሰለቸ ጉዳይ የተጣደዉና ውይይቱ ደራሲዉ የቀረፀዉ -fabricated- የመሰለዉ በ “ከቀብር መልስ” ነዉ። የዶ. በድሉን ክህሎት አይወክልም። “ሰዉ የተሰበሰበበት ቦታ ይጨንቀኛል፤ ... ይሉኝታ ከአግዳሚዉ ጋር ሰፍቶ ይዞኝ እንጂ መሄድ ከፈለኩ ቆየሁ” ድንኳን ዉስጥ የተጨናነቀዉ እድርተኛ ለልዩ አጭር ልቦለድ ሊበቃ አቅም እያለዉ ዋናዉ ገፀባህርይ ከአንድ ምሽት ቤት ሲገባ፣ ልቦለዱ መዝመም ይጀምራል፤ ይሰለቻል። የመጀመሪያዉ ልቦለድ “አዝማሪዉ፥ ከተሜዉ ...” ትረካዉ በአዝማሪ ስንኞች እየታደሰ፥ በአደባባይ “ሰዉ” መስለዉ ህሊናቸዉ ለነቀዙ ግለሰቦች ትዝብት ነዉ። ግጥምና ትረካ እየተፈራረቁ ጥርጣሬ፥ ቅናት፥ ሙስና ... እንደ ዘገባ ሳይሆን እንድ የኑሮ ቅኔ ይጠራራሉ። ሆኖም በአንደኛ መደብ ስለሚተረክ ገፀባህርዩ ባልተገኘበት የዴንማርኩን ፈረንጅ ገመና እንዴት አወቀ ? ከጐጆዉ ክዳን የሚነሳዉን ጭስ እያስተዋለ በስጋትና በተስፋ መንፈሱ ስለጣመነ ገበሬ አጠገቡ ሳይገኝ እንዴት ተረከ ? አንደኛ መደብ የአንፃር ምርጫ ስለማይፈቅደዉ ወደ ሁልን አዋቂ መሻገር ይቻል ነበር። ይህ ግን ለተአማኒነት ካልሆነ በልቦለዱ ለመመሰጥ አያግድም።

“ያልተከፈለ ስለት” ከታተመ ገና ጥቂት ወራት አልቆጠረም፤ በተደራሲያን እጅ ሲመላለስና ሲነበብ ለዳግም ሂሳዊ ንባብ መቀስቀሱ አይቀርም። ሰባት ልቦለዶች ባይሰለቹም በተለይ ለኔ ለጥልቅና ዝርዝር ሂስ የሚያጓጉኝ ሁለት ናቸዉ። “እናታቸዉ የሞተች እለት” እና “የረከሰ መብአ” አይዘነጉም። ዶ. በድሉ ከነአዳም ረታ፥ ዓለማየሁ ገላጋይ፥ በዕዉቀቱ ሥዩም እና እንዳለጌታ ክልል በመቀላቀል የራሱን የጥበብ ድንበር እያበጀ ይገኛል። አማረ ማሞና ዘርይሁን አስፋዉ ያስተማሩንን የአጭር ልቦለድ አፃፃፍ ብልሀት ቸል ብሎ ዘመናዊ ይትበሃል በመከተሉ ረቀቅ እያለ ነዉ። ይህን ሀሌታ ንባብ፣ ወጣት ገጣሚ በአካል ንጉሤ “ፍላሎት” በሚል ርዕስ ካሳተመዉ ስብስቡ “ብርሃን ከላይ” በመጥቀስ መቋጨት ይቻል ይሆን? ብርሃን እንደ ዝሃ ህላዌን እንደ ማግ አድርቼና አቅልሜ ሸምኜ ሸምኜ ያን የብርሃን ሸማ፥ ደርቤ ብለብሰዉ ጨለማ ወረሰዉ። (ለካንስ) ብርሃን መሆን እንጂ፥ ብርሃንን መደረብ አይጠቅመዉም ለሰዉ።

ዶ. በድሉ ሰዉና ክስተትን ብርሃን በመሆንና ብርሃን በመደረብ ቅንፍ ሳይቀነብብ ከጨላማ ፥ ከግራጫ ግለሰብን እያደባ ትናንት በመቀኘቱ፥ዛሬ በመተረኩ ለኛም በጅቶናል። የሚመጥን የፈጠራ ድርሰት ባነበብኩ ወቅት ዝነኛዉ Milan Kundera ስለ ልቦለድ የተናገረው ትዝ ይለኛል። “All great works (precisely because they are great) contain something unachieved” የልሂቃን ትልቅ የጥበብ ዉጤት የሚመስጠን፥ የሚያነቃቃን በሰመረላቸዉ ፈጠራ ብቻ ሳይሆን፥ ሞክረዉ አልሰበሰብ ባለዉም ምናባቸዉ ጭምር እንጂ እንደማለት።

Published in ጥበብ
ላቭሊ የውበት ስራ ማሰልጠኛ ተቋም በተለያዩ የውበት ሥራ ሙያዎች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች በሚቀጥለው ሳምንት ቅዳሜ ከቀኑ 6፡00 ሰዓት ጀምሮ በግሎባል ሆቴል እንደሚያስመርቅ ስራ አስኪያጁ አቶ ፋሲል ሚካኤል አስታወቁ፡፡ በእለቱ የሚመረቁት ተማሪዎች በሞዴሊንግ፣ በፀጉርና በውበት ስራ፣ በፋሽን ሾው፣ እንዲሁም በሌሎች የፈጠራ ስራዎች የሚሰጠውን ትምህርት ተከታትለው ያጠናቀቁ ሲሆን በየዘርፉ በትምህርት ብቃታቸው ብልጫ ላሳዩ ተማሪዎች ሽልማት እንደሚሰጥም ዋና ስራ አስኪያጁ ተናግረዋል፡፡ ላቭሊ የውበት ማሰልጠኛ ተቋም ላለፉት 16 ዓመታት በዘርፉ ስልጠና ሲሰጥ የቆየ ሲሆን በርካታ ዜጐችን የሙያ ባለቤት እንዳደረገም ተገልጿል፡፡
Monday, 29 September 2014 09:03

ያቺን ቀን ፍለጋ!

                 ሰለሞን ወደግል ድርጅቴ ያለ ቀጠሮ መጣ፡፡ የሥራ ዲሲፒሊን አለኝ ብዬ አምናለሁ፡፡ ቀጠሮ ላይ በጣም ጥብቅ ነኝ፡፡ ያለ ቀጠሮ ባለጉዳይ አላነጋግርም፡፡ ነገር ግን ሰለሞን በጣም የምወደው አብሮ አደግ ጓደኛዬ ነው፡፡ አሁን አሁን የኑሮ ሩጫ እንደልብ ባያገናኘንም እወደዋለሁ፡፡ ከሰሞን ባህርይ የማልወድለት ሲበዛ ጠጪ መሆኑን ነው፡፡ በዚያም ላይ ሾፌር ነው፡፡ ደጋግሜ ብነግረውም አልተለወጠም፡፡ “እንዲህ በእግር በፈረስ የፈለከኝ በደህና ነው?” አልኩት ሰላምታ ተለዋውጠን ከተቀመጠ በኋላ፡፡ “ምን ዓይነት ችግር?” ደንገጥ ብዬ ጠየቅሁት፡፡ “መኪናዬ ተበላሽታብኛለች፤ በዚያ ላይ ደግሞ አባባ ታሟል፤ ና ተብዬ ወደዚያው ልሄድ ነው፡፡ አንድ ሳምንት ሙሉ ምንም ሥራ የለም፤ አባባ ጋር ከሄድኩ ደግሞ ባዶ እጄን እንዴት ብዬ ታውቀዋለህ አይደል?” “እና?” “ምን እና ያስፈልገዋል? ገንዘብ እንድታበድረኝ ፈልጌ ነው” በዝምታ ጥቂት አሰብኩ፡፡ ከዚያም፡- “ሶል አጉል ጊዜ ነው የመጣኸው፤ በአሁኑ ወቅት ልሰጥህ የምችለው ገንዘብ የለኝም” አልኩት “እንዴት ገንዘብ የለኝም ትላለህ?” አፈጠጠብኝ “ገንዘብ የለኝምና ልሰጥህ የምችለው ገንዘብ የለኝም ይለያያል፡፡ ልጆቼን ላንጋኖ ላዝናናቸው ቃል ስለገባሁላቸው አሁን ልሰጥህ አልችልም፡፡” አልኩት ፍርጥም ብዬ፡፡

“እኔ አባቴ ታሟል እያልኩህ አንተ ልጆቼን ላንጋኖ ይዤ እ - ቂ! ቂ - ቂ - ቂ!” ከተቀመጠበት ተነስቶ ቁልቁል ከተመለከተኝ በኋላ የምሬት ሳቁን ትቶልኝ ከቢሮዬ ወጥቶ ሄደ፡፡ ምንም ማድረግ አልችልም፡፡ ለህፃናት ልጆች ቢቻል ቃል አለመግባት፣ ቃል ከገቡ ደግ መፈፀም አለበት ብዬ አምናለሁ፤ ይህን በምንም አልለውጠውም፤ ለልጆቼ ከኔ በላይ የሚቀርባቸው ደግሞ ማንም የለም፡፡ መኪናዬ ጋራዥ ገብታ ያለው እውነት ሊሆን ይችላል፤ መኪናው ሰበበኛ ናት፤ አምስት ቀን ከሰራች አምስት ቀን ትቆማለች፡፡ አባቴ ታሟል ያለውን ግን እጠራጠራለሁ፤ ምናልባት ለዚያችው ለሱሱ ለመጠጡ ፈልጎ ይሆናል…” እንዲህ እንዲህ እያሰብኩ ቆይቼ ወደቤቴ አመራሁ፡፡ ፋታ የሌላቸው ቀናት፣ ፋታ ሳይሰጡ ነጎዱ፡፡ ሰሞኑንማ ለጉድ ነው! በሰንበት እንኳ ፋታ የለም፡፡ ቀጠሮዬ ቦታ በጠዋት ደርሻለሁ፡፡ ይኼ ቀጠሮ ቢሳካልኝ እንዴት ጥሩ ነበር? ሰለሞን ያኔ ከኔ ቢሮ ከወጣ ከአንድ ወር በኋላ ጠጥቶ ሲያሽከረክር የመኪና አደጋ ደርሶበት ሆስፒታል ገብቷል፡፡

አንድ ጊዜ ሄጄ ጠይቄዋለሁ፡፡ ከዚያ በኋላ ግን ዛሬ እሄዳለሁ ነገ እሄዳለሁ ስል ፋታ የት ተገኝቶ! ከትናንት በስቲያ ባለቤቱ ሄዋን ስትደውልልኝ እንዴት እንዳፈርኩ! “እባክህን” አለችኝ ሄዋን “ለልጆቼ የደንብ ልብስና የትምህርት ቤት ማስመዝገቢያ እጅ አጠረኝ፤ አንተን ላስቸግር ነው” ምስኪን አልኩኝ በልቤ፡፡ “የምን ማስቸገር ነው ያውም ለሰለሞን! ያውም ላንቺ ለሄዋን ልጆች… ምንስ ቢሆን .. በቃ አታስቢ!” አልኳት፡፡ አቤት ቅብጠት! ምን ተይዞ ነው አታስቢ! ይኸው ሃሳቡ ለኔው ብቻ ተረፈ፡፡ ያውም በመስከረም አታስቢ? እንደሰሞኑ ዝናብ እኝ እኝ የሚል ማለቂያ የሌለው ወጪ ከፊቴ ተከምሮ ያፈጥብኛል፡፡ መስቀል ደግሞ ይኸው መጣሁ እያለ ነው፡፡ ዓይኖቼ መንገድ መንገዱን እየቃኙ የቆጠርኩትን ባለሀብት መኪና ይቃኛሉ፡፡ ከአጠገቤ ካለው መዝሙር ቤት ወደሚሰማው ስብከት ጆሮዬን አዘንብዬ በማድመጥ ላይ ነኝ፡፡

“በሙሴ በኩል ሕዝቤን ልቀቅ እያለ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር የተለያዩ ምልክቶችን ቢያሳየውም ፈርኦን ይበልጥ ልቡን እያደነደነ ሄደ፡፡ ይባስ ብሎም ለጡብ መስሪያ ያስቀርብላቸው የነበረውን ጭድ ‹ራሳችሁ ፈልጋችሁ አምጡ› አላቸው፤ ልብ በሉ! ጫፍና ጫፉ ላይ ቅርጫት የተንጠለጠለበት አግዳሚ እንጨት ትከሻቸው ላይ አስቀምጠው፣ ሁለት ቅርጫት ሙሉ የጡብ መሥሪያ ጭቃ ተሸክመው፣ በግራና በቀኝ እጃቸው የተሸከሙትን እንጨት ደግፈው ቀኑን ሙሉ ሲመላለሱ መዋል እንዴት አድካሚ እንደሆነ ይታያችኋል? ይህ ሁሉ ሳያንስ ይህ ሁሉ ሳይበቃ፣ በዚህ ላይ ተጨማሪ ጭድ ሲጨመርበት ጭዱን ለመሰብሰብ የሚፈጅባቸው ጊዜ የሚታሰብ አይደለም፡፡

ከአሁን በፊት ሲሰሩት እንደነበረው እንዲሰሩ ነው የተደረገው፡፡ ትከሻቸው ላይ ያለውን እንጨት በሚደግፉበት በእጃቸው ጭድ ሲታቀፉበት፣ ትከሻቸው ላይ ያለው እንጨት በእጅ መደገፍ ስለቀረ፣ ከትከሻቸው ወደኋላ እንዳይወድቅ ወደፊታቸው አጎንብሰው ጎብጠው መሄድ ጀመሩ፤ ከኋላቸው ደግሞ በፈረጠመ ክንዳቸው ጅራፋቸውን በማስጮህ፣ ጀርባ ጀርባቸውን እያሉ የሚያጣድፏቸው የፈርዖን ወታደሮች ይከተሏቸዋል፡፡ ቀና ማለት አይችሉም፤ ሁሉም አጎንብሶ የየራሱን መንገድ ይጠበጥባል፡፡ ሁኔታቸውን በዓይነ ህሊናዬ ስስለው አስገረመኝ፡፡ ደግሞ ለኔ ጭምር የተነገረ መሰለኝ፡፡ ጎብጫለሁ፡፡ አጎንብሻለሁ፡፡ ምን እኔ ብቻ? ሁላችንም ጎብጠናል፡፡ የምንሸከመው ጡብ ዓይነቱ ይለያይ እንጂ የሁላችንም ቅርጫት አንድ ዓይነት ነው፤ የማናወርደው የማንጥለው ኑሮ የሚባል ቅርጫት! ጊዜ ደግሞ እንደ ጅራፍ ደረስኩ እያለ እየጮኸ ይከተለናል፡፡ “ዛሬ ይሄን ካላደረስክ!”፣ “ዛሬ ይሄን ካልከፈልክ!” “ዛሬ ይሄን ካልጨረስክ” ዛሬ… ዛሬ… አሁን!... የጊዜ ጅራፍ ሳያቋርጥ በቀናቶቻችን ላይ እየጮኸ ፋታ ይነሳናል፤ ለማይሞላ ቅርጫት… ቅርጫቱ… ግራና ቀኝ ትከሻችን ላይ የተሸከምነው ቅርጫት … በቃኝ አያውቅም… የቤት ኪራይ… የመብራት … የውሃ… የስልክ … አገር ውስጥ ገቢ… መዋጮ… የቤት አስቤዛ… የልጆች… ሁሉም ዓይነት ወጪ… የዘበኛ… የቤት ሰራተኛ… የላውንደሪ… የጋራዥ… የወፍጮ… ወዘተ... ወዘተ… ወዘተ ቅርጫቱ ሞልቷል፤ ይከብዳል፡፡

ከኔ ቅርጫት ውስጥ “በቃ አታስቢ!” ብዬ የተቀበልኩት ጭድ፤ ራሴ እፈልገው ዘንድ ግድ የሆነብኝ ጭድ! እናም ይኸው ጭድ ልፈልግ ወጥቻለሁ፤ ከወገቤ ቀና ብዬ ወደ ጎን ሌላውን ለማየት አልችልም፤ አለመፈለግ ሳይሆን አለመቻል ነው፡፡ በየዕለቱ አጎንብሼ የራሴን መንገድ ብቻ እጠበጥባለሁ፡፡ የኑሮ ሸክም አጉብጦኛል፤ አጎብንሼ መንገድ መንገዴን ብቻ አያለሁ፡፡ በዚህ ሁሉ መሀከል ግን ቀና ብዬ የምቆምበትን ቀን እናፍቃለሁ፡፡ ከጎኔ የኑሮ ሸክም ያጎበጠውን… ሸክሙን አግዤው ቀና እንዲል፤ ቀና ብሎ እንዲራመድ፡፡ ሁላችንም ቀና እንድንል፡፡ ያቺን ቀን እናፍቃለሁ፡፡ ነገር ግን ያቺ ቀን መቼ ናት? ድንገት የቀጠርኩት ሰው ከመኪናው ወርዶ እኔ ወዳለሁበት ሲያመራ ተመለከትኩ፡፡ ያቺ ቀን ዛሬ ትሆን? ከተቀመጥኩበት ተነሳሁ፡፡

Published in ልብ-ወለድ

ውድ እግዚአብሔር፡-
ት/ቤት ሁሉም የራሱ ምርጥ ጓደኛ አለው፤ እኔ ብቻ ነኝ የራሴ ጓደኛ የሌለኝ፡፡ አንድ ጓደኛ ልትሰጠኝ ትችላለህ?

ግን ቶሎ ብለህ እሺ?!
ዴቭ - የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ሃና ከክፍላችን በጣም ቆንጆ ናት፡፡ ሳሚ ደግሞ በሩጫ የሚበልጠው የለም፡፡ ቲና ጥርሷ ያምራል፡፡ ለእኔ ግን

ምንም የተለየ ነገር አልሰጠኸኝም፡፡ ረስተኸው ነው?
ጁዲ - የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
እህቴ ባል እንድታገባ እባክህ ቆንጆ አድርጋት፡፡
ቤቲ - የ7 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
የፕላስቲክ አበቦች ስታይ አትናደድም? እኔ አንተን ብሆን በጣም ነበር የምናደደው፡፡
ጆሲ - የ8 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ታላቅ ወንድሜ እኔን እንደሚቆጣኝ፣ እኔም የምቆጣው ወንድም እፈልጋለሁ፡፡ ትንሽዬ ወንድም ትሰጠኛለህ?
ቶኒ - የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ሶፊ የሚያምር ጫማ አላት፡፡ እኔም የእሷ ዓይነት ጫማ እፈልጋለሁ፤ ግን ልሰርቃት አልፈለግሁም፡፡ አንተ

ልትሰጠኝ ትችላለህ?
ውድ እግዚአብሔር፡-
አንዳንዴ ጥርሴን የውሸት ስቦርሽ ታውቅብኛለህ አይደል? ግን ለማሚ እንዳትነግርብኝ እሺ!?
ካሌብ - የ5 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ከዓለም ላይ መጥፎ ነገሮችን ካላስወገድክ በሚቀጥለው ጊዜ የምትመረጥ አይመስለኝም፡፡ እኔ እኮ ላንተ ብዬ

ነው፡፡ ወይስ መመረጥ አትፈልግም?
ኤርሚ - የ7 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ከፃፍካቸው ታሪኮች ሁሉ የወደድኩት የኖህን ታሪክ ነው፡፡ እኔም በውሃ ላይ መጓዝ ደስ ይለኛል፡፡
ሳቤላ - የ8 ዓመት ህፃን




Published in ጥበብ
Monday, 29 September 2014 08:40

የፍቅር ጥግ

ዝነኞች ስለጋብቻ የዛሬዋ ምሽት እጅግ ልዩ ናት፡፡ በፓሪስ የኤፍል ማማ ጫፍ ላይ ቃል ኪዳናችንን ዳግም ማደሳችን ምን ያህል እፁብ ድንቅ እንደሆነ ልገልፀው አልችልም፡፡ ማሪያ ኬሪ (አሜሪካዊት ዘፋኝ) ምንም ዓይነት ሁኔታ ቢገጥመን ተደጋግፈን ማለፋችን ጠቅሞናል፡፡ ጃዳን የመሰለች ሴት በማግኘቴ ዕድለኛ ነኝ፡፡ እጅግ ግሩም ሴት፣ ሚስትና እናት ናት፡፡ ዊል ስሚዝ (አሜሪካዊ የፊልም ተዋናይ) ህፃናቱ እንድንጋባ ጫና አሳድረውብናል፡፡ የእኛ መጋባት ለእነሱ ምን ማለት እንደሆነ አልተገነዘብንም ነበር፡፡ ስንጋባ ግን ለእኛም ያለውን ትርጉም ተረድተነዋል፡፡ ብራድ ፒት (አሜሪካዊ የፊልም ተዋናይ) አሁንም ልክ መጀመሪያ ላይ ስንተዋወቅ እንደነበረው እንፋቀራለን፤ ዕፁብ ድንቅ የሆኑ ልጆች አሉን … በጣም ደስተኞች ነን፡፡ የስራና የቤተሰብ ኃላፊነታችንን በማመጣጠን ህይወታችንን እንመራለን፡፡ ምንጊዜም ቅድምያ የምንሰጠው ለልጆቻችን ነው፡፡ ዴቪድ ቤክሃም (እንግሊዛዊ የእግር ኳስ ተጫዋች) ከ20 ዓመት በፊት ልታገባኝ የተስማማችው እቺ ሴት ባትኖር፣ ዛሬ የሆንኩትን አይነት ሰው አልሆንም ነበር፡፡ ይሄን ነገር በአደባባይ ልበለው፡- ሚሼል፤ እንዲህ አፍቅሬሽ አላውቅም፡፡ መላው የአሜሪካ ህዝብ በቀዳማዊት እመቤትነትሽ በፍቅር ሲወድቅልሽ እንደማየት የሚያኮራኝ ነገር የለም፡፡ ባራክ ኦባማ (የአሜሪካ ፕሬዚዳንት) ጋብቻ የሰመረ እንዲሆን ሁለት ነገሮች ያስፈልጋሉ፡፡ አንደኛው ለስኬታማነቱ መትጋት ነው፡፡ ሌላው ከእናንተ በላይ የሆነ ሰው ማግባት ነው፡፡ እኔ በሁለቱም ረገድ ተሳክቶልኛል፡፡ ቤን አፍሌክ (አሜሪካዊ የፊልም ተዋናይ) በእኔና በእሷ ግንኙነት ውስጥ ሁለት መመሪያዎች አሉን፡፡ የመጀመሪያው መመሪያ፤ ማናቸውንም ነገሮች እያገኘች እንደሆነ እንድታስብ ማድረግ ነው፡፡ ሁለተኛው መመሪያ ደግሞ፤ ማናቸውንም ነገሮች በራሷ መንገድ እንድታከናውን መፍቀድ ነው፡፡ ይሄ አሁን ድረስ እየሰራልን ነው፡፡ ጀስቲን ቲምበርሌክ (እንግሊዛዊ ዘፋኝ)

Published in የግጥም ጥግ

               ስሙን ያገኘው የዓባይ ወንዝ መፍለቂያ ከሆነውና ሰከላ ወረዳ (ጐጃም) ከሚገኘው ቦታ ነው፡፡ በ1970ዎቹ መጀመሪያ ላይ እንደ ንጋት ኮከብ ደምቀው ከነበሩት የክፍለ ሀገር ኪነት ቡድኖች አንዱ የጐጃሙ ግሼ ዓባይ ይገኝበታል፤ የወሎው ላሊበላ፣ የትግራይ፣ የአርሲ እና የወለጋ ክፍላተ ሀገር የኪነት ቡድኖችም በወቅቱ ስመጥር ነበሩ፡፡ የጽሑፌ ዓላማ በጐጃሙ ግሼ ዓባይ ላይ ያተኮረ ስለሆነ ሌሎችን አቆያቸዋለሁ፡፡ በ1971 ዓ.ም መጨረሻ አካባቢ የባህርዳር ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ የኪነት ቡድን የሙዚቃ ሥራውን እየተዟዟረ ሲያሳይ ቆይቶ፣ በወቅቱ የጐጃም ክፍለሀገር ዋና ከተማ ወደነበረው ደብረማርቆስ ያመራል፡፡ በወቅቱ በክፍለሀገሩ ውስጥ ይገኙ ከነበሩት እጅግ በጣም ጥቂት ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤቶች አንዱ ከነበረው ድብዛ ት/ቤት አዳራሽ ተገኝቶ ትርኢቱን ማቅረብ ይጀምራል፡፡ በወቅቱ ኪነት ከፍተኛ ተወዳጅነት ነበረውና የትምህርት ቤቱ አዳራሽ በተመልካች ጢም ከማለቱም በላይ የክ/ሀገሩዋ አስተዳዳሪ የነበሩት ሻለቃ ካሳዬ አራጋውና ሌሎች የክፍለሀገሩ ባለሥልጣናትም ታዳሚዎች ነበሩ፡፡

የኪነት ድግሱ እየሞቀ ሲሄድ ድንገት አንድ ችግር ተፈጠረ፡፡ እሱም የኪነት ቡድኑ አስተዋዋቂ ቡድኑን “የጐጃም ክፍለሀገር የኪነት ቡድን” ብሎ በማስተዋወቁ ትልቅ ግርግር ተነሳ፤ አንዳንድ ተመልካቾች እንዲያውም ከአዳራሹ ውጭ በመውጣት ጣራውን በድንጋይ መደብደብ ጀመሩ፡፡ ሁኔታው ሲረጋጋ የችግሩ ምክንያት “አስተዋዋቂው የጐጃም ክፍለሀገር ኪነት ብሎ የሚያስተዋውቀው ማን ወክሎት ነው?” የሚል ቅሬታ ሆኖ ተገኘ፡፡ እግረመንገዱንም የህዝቡ የኪነት ቡድን ይቋቋምልን ጥያቄ ግልጽ ሆነ፡፡ ይህንን ጥያቄ የክፍለሀገሩ ዋና አስተዳዳሪ በዋዛ አላለፉትም ነበርና ሳይውል ሳያድር ኮሚቴ ተቋቋመ፤ በወቅቱ ከነበሩት ሰባት አውራጃዎች ማለትም ደብረ ማርቆስ፣ ሞጣ፣ ብቸና፣ ባህርዳር፣ መተከል፣ ቆላ ደጋዳሞት እና አገው ምድር አውራጃዎች ውስጥ ከሚገኙ 35 ወረዳዎች ፍላጐቱና ችሎታው ያላቸው ወጣቶች እንዲመለመሉ ትዕዛዝ ሰጡ፡፡ ከብሔራዊ ቲያትር የመጡ ባለሙያዎች ምልመላውን እንዲያካሂዱ፣ የ35 ወረዳዎች ዋና አስተዳዳሪዎችም ለዚሁ ዓላማ ብቁ ናቸው ያሏቸውን ወጣቶች ደብረማርቆስ ከተማ ድረስ እንዲልኩ ቀጠሮ ያዙ፡፡

ከየወረዳው የመጡት ወጣቶች ደብረማርቆስ ቤተመንግስት አዳራሽ ዘፈኖቻቸውን እያቀረቡ ከመሃላቸው የተሻሉት ከብሔራዊ ቲያትር በመጡት ባለሙያዎች ተመለመሉና ህዳር 25 ቀን 1972 ዓ.ም እዚያው ደብረማርቆስ ከተማ ከሚገኘውና “ድኩማን ድርጅት” በመባል ይታወቅ ከነበረው ተቋም በማሰባሰብ ሥልጠና ተጀመረ፡፡ በወቅቱ የተመለመሉት ወጣቶች ሰባ አንድ ሲሆኑ፤ ከአማራ፣ አገው፣ ጉሙዝ፣ ሽናሻ፣ ወይጦና ቅማንት የተውጣጡ ነበሩ፡፡ ወጣቶች ብቻ ሳይሆኑ የሚተዳደሩበት ገንዘብም ከየወረዳው ህዝብ የተሰበሰበ ነበር፡፡ ለስምንት ወራት ሲሰጥ በቆየው ስልጠና የአባላት ቁጥር ወደ ሰላሳ ስድስት ዝቅ አለ፡፡ የዚህ ምክንያቱ በዲሲፕሊንና በችሎታ ማነስ ስለሚባረሩ ነው፡፡ ከስምንት ወራት የዳንኪራ (ውዝዋዜ)፣ የአቀንቃኝነት (ድምጻዊነት)፣ የተውኔትና የሙዚቃ (በተለያዩ የሙዚቃ መሣሪያዎች አጨዋወት) ስልጠና በኋላ ሐምሌ 5 ቀን 1972 ዓ.ም የወቅቱ የባህል ሚኒስትር ሻለቃ ግርማ ይልማና ሌሎች ከፍተኛ ባለስልጣናት በተገኙበት ተመረቀ፡፡

ከሁለት ቀናት በኋላም መኖሪያውን ወደ ባህርዳር ለማድረግ ጓዙን ጠቅልሎ ተጓዘ፡፡ ብዙም ሳይቆይ በ5ኛው የአብዮት በዓል ላይ ለመገኘት ወደ አዲስ አበባ መጣ፤ የወቅቱን የሱዳን መሪ ጃፋር ኤል - ኑሜሪንና የሃንጋሪያው ፕሬዚዳንት ፓል ሎሼንሲ የክብር አቀባበል ላይ በመገኘት ትርዒቱን አቀረበ፤ ከዚያም የክፍለሀገሩን ልዩ ልዩ ዘፈኖች በብሔራዊ ቲአትርና በተለያዩ አዳራሾች በማቅረብ፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ ስመ ገናና ሆነ፡፡ በወቅቱ ይታተሙ በነበሩት “አዲስ ዘመን” ፣ “የካቲት” እና “የዛሬይቱ ኢትዮጵያ” ላይ ተደጋጋሚ ሙገሳዎችን ከማግኘቱም በላይ የኢትዮጵያ ራዲዮና ቴሌቪዥን ጋዜጠኞችም ከብዙ ሙገሳ ጋር የቡድኑን ዘፈኖች በተደጋጋሚ በማቅረብ ጣቢያዎቻቸውን ተወዳጅ ለማድረግ ጣሩ፡፡ ከዚያ በኋላ ቡድኑ በአርሲ፣ በወለጋ፣ በሲዳማ፣ በሐረር፣ በባሌ፣ በሸዋ፣ በትግራይ፣ በኤርትራ፣ በወሎ፣ በጐጃምና በጐንደር ክፍላተሀገር በመዘዋወር ድንቅ ብቃቱን ማሳየቱን ተያያዘው፡፡ በምሥራቅ ግንባር በነበሩት በሺላቦ፣ በለምበል፣ አህመድ ጐሬ፣ ኢላላ፣ ጐዴ እና በመሳሰሉት፤ በሰሜንም በተለይ በኤርትራ ግንባር፤ ምፅዋ፣ አልጌና (መርሳተኽላይ፣ መርሳቡልቡል፣ ሰምበር፣ እንቁላል…) ወዘተ በመዘዋወር ሥራውን ለሠራዊቱና ህዝቡ በማቅረብ ተወዳጅነቱን ጣራ እንዲነካ አድርጓል፡፡ በትግራይ ግንባር ለነበረው ሠራዊትም ተመሳሳይ ተግባር በማከናወን በሠራዊቱ ልብ ውስጥ የማይረሳ ትዝታ መፍጠር የቻለ ቡድን ሆነ፡፡ በተለይም በምርጥ አቅራሪነቷ (ሽለላዋ) ዝነኛ የነበረችው ዘቢደር አምሳሉ፤ “ነግረኸው፣ መክረኸው ምክርህን ካልሰማ፣ አደንቁረው በዕርሳስ ጆሮው እስቲገማ፡፡ የሱማሌ እረኛ እንዴት ተዋረደ፣ ታንኩን አስረክቦ ጣሳ ይዞ ሄደ፡፡ የሶማሌ ጊደር የላትም ወይ አውራ? አንበሳው ላይ ወጥታ ቀረች ተሰባብራ፡፡ ነግረኸው ካልሰማ ከርፋፋ ወንበዴ፣ አጭዶ መከመር ነው እንዳፈራ ስንዴ…” እያለች ስታንጐራጉር የሠራዊቱን ወኔ እንደ ቋያ እሳት ታቀጣጥለው ነበር፡፡ አለማየሁ ቦረቦር “አገር መስታውቴ” እና “ያችውና መጣች”፣ አለባቸው ተፈራ “ሃሜት መወጣጫው”፣ ወይኒቱ አንዱር “አንበሳውያን፣ አስናቆ ኢላላ፣…”፣ አቡኔ አበጀሁ “ሉላ”፣ ማናማሁ ሲራጅ “ቀናበል ከአንገትህ፣ አያ እንግዳ…” እናንዬ አደራ “የመኩ የመኩ፣ ጐፈሬው ዘመመ…” ሲራጅ ኢድሪስ “አያ በለው…”፣ አዳነች ጣሰው “ሞት ፈርቶ ትግል የለም”፣ ይሁኔ በላይ “የአገሬ ልጅ…”፣ ሰማኸኝ በለው “አንቱየዋ!”፣ ታደሰ ላቀው “ነይልኝ ማርቆስ…”፣ አያሌው ፀጋዬ “ደኔ ደኔ…” ወዘተ በተባሉ ዘፈኖቻቸው ተመልካችን ከመቀመጫው ብድግ ቁጭ የማድረግ ልዩ አቅም ነበራቸው፡፡ በሙዚቃ መሣሪያ ተጨዋችነትም ሁለገቡ ሙዚቀኛ አሳየ ዘገየ፣ ሰጠኝ አጠናሁ፣ ሙሉጌታ፣ ይኩኖአምላክ አዱኛ፣ አቡሃ ይባዬ፣ መሐባው ግዛቸው፣ ምትኩ ገላው፣ ሰላምሰው ግዛቸው፣ አንዱዓለም፣ ገበየሁ ማሞ፣ ሐብቱ ንጋቱ (አንሙቴ) ወዘተ የማይረሱ ምርጥ ባለሙያዎች ናቸው፡፡

በዳንኪራ በኩል፣ የዝባየሽ ታረቀኝ፣ ባኬ አንተነህ፣ እሱባለው ጫኔ፣ እንኰይ ትኩ፣ ሞላ ፈጠነ፣ ሽፈራው ወርቅነህ፣ የሹሜ ነጋሽ፣ ታደሰ ወንዴ፣ ዓለመወርቅ አስፋው፣ አልጋነሽ ለገሠ፣ ብዙአየሁ ጐበዜና ሌሎችም እንደ ባህር ቄጠማ ሲውዘፈዘፉ የተመልካችን ቀልብ የመሳብ መግነጢሳዊ ኃይል ነበራቸው፡፡ ጌታቸው ተሥፋዬ፣ አበረ አዳሙ፣ እቴናት ደባሱ፣ ፍቅሬ ገ/ኪዳንና ታሪክ ታምሩ በተውኔት በኩል የቡድኑ ፈርጦች ነበሩ፡፡ ከተጫወቷቸውና ለቡድኑ ዝናን ካተረፉለት ተውኔቶች ውስጥ “ማነህ? ነገ፣ የወጣቷ ህይወት፣ እናት ሃገር፣ ድርብ ምጥ፣ ድርብ ታጋይ፣ የስልኩ ምስጢር፣” በቀዳሚነት የሚጠቀሱ ሲሆን ሌሎች ተውኔቶችንም በማቅረብ ህዝብን አስተምረዋል፤ አዝናንተዋል፤ አሳውቀዋል፡፡ በነገራችን ላይ ቲያትር የሚጫወቱት በውዝዋዜ፣ በድምጽና በሌላም ሥራ ንቁ ተሳትፎ የሚያደርጉ ሁለገብ ወጣቶች ነበሩ፡፡ የግሽ ዓባይ ኪነት ቡድን ይህንን ሁሉ ሲያከናውን ያለምንም ችግር አልነበረም፡፡

የቡድኑ ትልቁ ሀብት የእርስበርስ ፍቅር ነበር፤ እንጂማ በችግር አለንጋ የሚገረፍበት ጊዜ በጣም ብዙ ከመሆኑ የተነሳ ብዙ ጊዜ የመበተን አደጋ ያጋጥመው እንደነበር በህይወት ያሉ አባላት በምሬት ያስታውሳሉ፡፡ ቡድኑ የሚተዳደረው ከህዝብ በተዋጣ ገንዘብ ነበር፤ የዚህ ምክንያቱ ቋሚ በጀት ያለተያዘለት ከመሆኑም በላይ የሚተዳደረውም በኮሚቴ ነበር፡፡ ኮሚቴው ጠንከር ብሎ መንቀሳቀስ ሲጀምር የቡድኑ ህይወት መጠነኛ እፎይታ ያገኛል፤ ካልሆነ ግን አባላት ደሞዝ የሚያገኙት ከ3 እና 4 ወራት ለቅሶ በኋላ ነበር፡፡ ግን ይህ ሁሉ ችግር እያለ የአባላቱ የእርስበርስ መተሳሰብና ጥልቅ የሙያ ፍቅር ትልቁ ስንቃቸው ነበር፡፡ ከህዳር 1972 እስከ 1973 ዓ.ም በኮሚቴ ሲመራ ቆየና ችግሩ እየባሰ ሲመጣ፣ ከ1974 ዓ.ም ጀምሮ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር ቡድኑን የማስተዳደር ኃላፊነት ተረከበ፡፡ ሆኖም እሱም በተገቢ መንገድ መምራት ስላልቻለ፣ በ1975 ዓ.ም ወር ተረኛነቱ ለባህልና ስፖርት ጉዳይ ቅርንጫፍ መ/ቤት ተዛወረ፡፡ ቡድኑን ከፍተኛ ፈተና የገጠመውም በዚሁ ጊዜ እንደነበር አባላት በምሬት ያወሳሉ፡፡ የዚህ ምክንያቱ መደበኛ በጀት ያልነበረው በመሆኑና ከህዝብ የተሰበሰበው ገንዘብ በማለቁ ነበር፡፡ “እንኳንስ ዘንቦብሽ…” አይነት የነበረው የኪነት ቡድኑ አስተዳደር ውጥንቅጡ እየበዛ፣ ቢሮክራሲያዊ ድሩ እየተወሳሰበ ሲሄድ አባላትም ተሥፋ መቁረጥ ጀመሩ፡፡ በዚህ የተነሳ ሥራቸውን እየጣሉ ወደ አዲስ አበባ መኮብለል ያዙ፡፡ ያነጋገርኋቸው አባላት እንደሚያስታውሱት፤ 1977 ዓ.ም የቡድኑ የፈተና ወቅት ነበር፤ ደሞዝ በማጣት ተራቡ፤ ተጐሳቆሉ፣ አንዳንዶችም በዕዳ ምክንያት በየፍትሕ ተቋማቱ መጐተት ጀመሩ፡፡

ወቅቱ ደግሞ ዘግናኙ የ1977 ድርቅ በወሎና ትግራይ ህዝብን እንደ ቅጠል የሚያረግፍበት ነበር፡፡ በዚህ የተነሳ የባለሥልጣናት ትኩረት አነስተኛ መሆኑ አያጠያይቅም፡፡ የኮብላዮች ቁጥር ሲበዛ፣ የቡድኑ ፈጠራ በከፍተኛ ሁኔታ ሲቀዛቀዝ፣ የኋላ ኋላ አንድ መላ መፈጠር ነበረበትና የወቅቱ ባለሥልጣናት በ1978 ዓ.ም የገቢ ማሰባሰቢያ ፌስቲቫል አዘጋጁ፡፡ በውጤቱም ግማሽ ሚሊዮን ብር መገኘቱን በወቅቱ ለበላይ አካላት የቀረበ ሪፖርት ያስረዳል፡፡ ሰማኸኝ በለውና ይሁኔ በላይ ቡድኑን የተቀላቀሉትም ከዚህ በኋላ ነበር፡፡ የገንዘቡ ችግር በዚህ መልኩ ቢቃለልም የአስተዳደሩ ጉዳይ ግን ዘላቂ መፍትሄ አልተገኘለትም፡፡ በዚህ ጊዜም ከባህል ሚኒስቴር ቅርንጫፍ መ/ቤት “ቦርድ” ወደሚባል ሌላ ኮሚቴ ተዛወረ፡፡ ኮሚቴ ደግሞ ያው ኮሚቴ በመሆኑ ለጊዜው መጠነኛ መሻሻል ያደረገ ቢሆንም ለቡድኑ ችግር ዘላቂ መፍትሄ ሊያመጣ አልቻለም፡፡ እንደ ያዝባየሽ ታረቀኝ እና እንኮይ ትኩ ያሉ ድንቅ ችሎታ በነበራቸው አባላቱ በ “ህዝብ ለህዝብ ኢትዮጵያ” ኪነት ቡድን እና በ13ኛው ዓለም አቀፍ የወጣቶች ፌስቲቫል ላይ ፒዮንግያንግ (ሰሜን ኮርያ) ላይ በመገኘት የክፍለ ሀገሩን ህዝብ ባህል ያስተዋወቀው ግሽአባይ፣ እንደ ሰማኸኝ በለው (ሰሜ ባላገር) እና ይሁኔ በላይ፣ ተዘራ ተችሎ፣ አንሙቴ፣ ወዘተ ያሉ ድንቅ ባለሙያዎችን ለአገራችን ያበረከተው ግሽአባይ፣ በጎጃም ክፍለ ሃገር ህዝብ ገንዘብና በልጆቹ የተቋቋመው ግሽአባይ ዛሬ ነበር ሆኗል፡ ለቡድኑ ህልውና ማክተም ምክንያት የሆነው የሥርዓት ለውጡ ነው፡፡

ደርግ በህአዴግ ሥልጣኑን ሲቀማ፣ ቡድኑን በኮሚቴ አባልነት ይመሩ የነበሩት የመንግስት ባለስልጣናት አንዳንዶቹ ለስደት ሌሎችም ለእስር ቤት ሲዳረጉ፣ ቡድኑ ሜዳ ላይ ቀረ፡፡ ሆኖም የወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት ታምራት ላይኔ ቡድኑን የባህርዳር ማዘጋጃ ቤት ተረክቦ እንዲያስተዳድረው ደብዳቤ ጽፈው ነበር፡፡ ግን የቡድኑ አባላት መንታ መንገድ ላይ ቆሙ፤ አንዳንዶች “በተሰጠን ዕድል እንጠቀምና ማዘጋጃ ቤቱ ያስተዳድረን፤ ሙያችንንም እንቀጥል” ሲሉ፣ ሌሎች ደግሞ “የከተማዋን ንፅህና በአግባቡ መጠበቅ የተሳነው ማዘጋጃ ቤት ሊያስተዳድረን አይችልም” በሚል አቋም ፀኑ፡፡ መጨረሻ ላይ ከመንግስት ተሰጥታው ሲገለገልባት የነበረችውና 27 ሰዎችን የመጫን አቅም የነበራት ፊያት መኪና፣ ማቀዝቀዣዎች፣ አልባሳት፣ የሙዚቃ መሳሪያዎችና ሌሎችም የቡድኑ ንብረቶች በመናኛ ዋጋ እየተሸጡ፣ ለእያንዳንዱ አባል እዚህ ግባ የማይባል ብር ደረሰው፡፡መኪናን የሚያህል ንብረት ተሸጦ ለእያንዳንዱ አባል የደረሰው አንድ ሺህ ብር አይሞላም ነበር፡፡ ከንብረት ሽያጭ የደረሳቸውን እጅግ መናኛ ገንዘብ ከተከፋፈሉ በኋላ አባላት ተበታተኑ፤ በኢትዮጵያ የኪነት አየር ላይ እጅግ ደምቆ የነበረው የግሽአባይ ቡድን ውበትም ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ በንኖ ጠፋ፡፡

በቡድኑ ውስጥ የላቀ ሚና ይጫወቱ ከነበሩት መሃል፡- አለማየሁ ቦረቦር፣ ዘቢደር አምሳሉ፣ አለባቸው ተፈራ፣ ታደሰ ወንዴ፣ አያሌው ጸጋዬ፣ ሲራጅ እንድሪስ፣ አለመወርቅ አስፋው፣ ማናማሁ ሲራጅ፣ አንሙቴ (ሐብቱ ንጋቱ)፣ እንኮይ ትኩ፣ የህዝባየሽ ታረቀኝ፣ ወርቁ፣ ብዙአየሁ ጎበዜ የተባሉት በህይወት የሉም (ነፍሳቸውን ይማር)፡፡ ሌሎች ግን በውጭና በአገር ውስጥ በተለያዩ የሥራ መደቦች ተሰማርተው ኑሮአቸውን እየገፉ ናቸው፡፡ ማስታወሻ፡ በጊዜ ብዛትና መረጃ በማጣት ስማቸውን ያልጠቀስኋቸው አባላት ካሉ ይቅርታ እጠይቃለሁ፡፡

Published in ጥበብ
Page 1 of 14